መዝገበ ቅዱሳን
20.7K subscribers
1.92K photos
9 videos
6 files
24 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
#ጥቅምት_5

ጥቅምት አምስት ቀን የታላቁ አባት #አቡነ_ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ (ገብረ ሕይወት) የዕረፍታቸው መታሰቢያ፣ የቊስጥንጥንያው #ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ጳውሎስ እረፍት፣ የሐዋርያው #ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_እልፍዮስ መታሰቢያው፣ የከበረ ጳጳስ #ቅዱስ_ኪራኮስ ከእናቱ #ከቅድስት_ሐና ጋራ በሰማዕትነት ያረፈበት ቀን ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ (ገብረ ሕይወት)

ጻድቁ የተወለዱት ግብፅ (ንሒሳ አካባቢ) ሲሆን አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ ይባላሉ። አባታችን ገብረ ሕይወት የጻድቃን አለቃ የቅዱሳን የበላይ ተጋድሎአቸውና ድንቅ ተአምራቸው እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ ቅዱስ ሰው ናቸው። የጻድቁን ክብር መናገር የሚችል ምን አነደበት ይኖራል? እንደ ምንስ ባለ ብራና ይጻፋል? ዜናቸውንስ ለመስማት የታደለ እንደ ምን ዓይነት ሰው ይሆን?

አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለ562 ዓመታት በዚህች ዓለም ሲኖሩ እህል ያልቀመሱ /ምግባቸው ምስጋና ነውና/ ልብስ ያልለበሱ /ጠጉር አካላቸውን ይሸፍን ነበርና/ ሐዋርያዊ ሆነው ከግብፅ እስከ ኢትዮዽያ ብዙ ነፍሳትን ያዳኑ አባት፤ ሃገራችንን አስምረው አስራት እንድትሆናቸውም ተቀብለው ምድረ ከብድ አካባቢ አርፈዋል።

ጻድቁ ገብረ መንፈስ ቅዱስም ገብረ ሕይወትም ይባላሉ። በ562 ዓመታት ሕይወታቸው እንደ ሐዋርያት ከምድረ ግብፅ እስከ ኢትዮዽያ ወንጌልን ሰብከዋል። በዚህም በሚሊየን (አእላፍ) ለሚቆጠሩ ነፍሳት የድኅነት ምክንያት ሆነዋል።

ጻድቁ እንደ ሰማዕታትም ከከሃዲ ሰዎች ብዙ መከራን ተቀብለዋል። እንደ ባሕታውያን ለብዙ መቶ ዓመታት ሰው ሳያዩ ቆይተዋል። ለየት የሚለው ግን የጽድቅ ሕይወታቸው ነው፤ ከእልፍ አዕላፍ አጋንንት ጋር ተዋግተው ድል ማድረግ ችለዋልና።

የንሒሳው ኮከብ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለኢትዮጵያ ልዩ ፍቀር አላቸው። ስለ ሃገሪቱና ሕዝቧ ፍቅር ሲሉ ለ100 ዓመታት በደብረ ዝቋላ መከራን ተቀብለዋል። ምሕረትን ሲለምኑ ሥጋቸው አልቆ በአጥንታቸው ቁመው ነበርና ሃገራችን አሥራት ሆና ተሰጠቻቸው።

ስለዚህም ነው በሃገሪቱ ውስጥ ከ2,000 በላይ የጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳማትና አድባራት ዛሬም ድረስ ያሉት። በ8ኛው ክ.ዘ አካባቢ የተወለዱት አባታችን ያረፉት በ14ኛው መቶ ክ.ዘ አካባቢ ነው። ፍጥረታትን ሁሉ አዘው መጋቢት 5 ቀን ሲያርፉ ግሩማን መላእክት ገንዘው አካላቸውን ሠውረዋል።

ሥላሴን የተሸከመ አካላቸው በጐልጐታ ተቀብሯል የሚሉም አሉ። "ሰላም ለመቃብሪከ ዘኢተከሥተ ለባዕድ: ከመ መቃብሩ ለሙሴ ወልደ ዮካብድ: ዜና መቃብሪከሰ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸማድ: ቦ ዘይቤ በኢየሩሳሌም አጸድ: ወቦ ዘይቤ ኀለወ በከብድ።" እንዲል።

ጻድቁ አባታችን አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ እረፍቱ መጋቢት 5 ቀን ነው ይህ ደግሞ በታላቁ ዓብይ ጾም ወቅት ነው ፍትሃ ነገስት አንቀጽ 15 ላይ በዓብይ ጾም በዓል ማክበር ይከለክላል የሀዘን ወቅት ነውና ከበሮ አይመታም እልልታና ጭብጨባ የለም ፍጹም ሀዘን እንጂ የመጋቢት 27 ስቅለት ጥቅምት 27 ቀን እንደሚከበረው ሁሉ ወደ ጥቅምት 5 ቀን ተዛውሮ እንዲከበር ተደረገ፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ጳውሎስ

ጥቅምት አምስት በዚች ቀን የቊስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጳውሎስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከእርሱ አስቀድሞ በቁስጥንጥንያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ለነበረው ለአባ እለእስክንድሮስ ደቀ መዝሙሩ ነው። አባ እለእስክንድሮስም በሞተ ጊዜ በርሱ ፈንታ ይህ አባት አባ ጳውሎስ ተሾመ።

በጵጵስናውም ወንበር በተቀመጠ ጊዜ የአርዮስን ወገኖች ከቊስጥንጥንያ አገር ከአውራጃውም ሁሉ አውግዞ አሳደዳቸው። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ከሞተ በኋላ ልጁ ሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ በቊስጥንጥንያ አገር ላይ ነገሠ ወንድሙ ቊንስጣም በሮሜ ሀገር ነገሠ። ይህ ቈስጠንጢኖስም አርዮስን ይወደዋል በረከሰች ሃይማኖቱም ያምናል ቅዱስ አባ ጳውሎስም አርዮሳውያንን አውግዞ እንዳሳደዳቸው ሰምቶ እጅግ አዘነ።

አባ ጳውሎስንም ከእንግዲህ የአርዮስን ወገኖች ተዋቸው አታውግዛቸው አለው እርሱ ግን ንጉሡን አልሰማውም ስለዚህም አባ ጳውሎስን ከቊስጥንጥንያ አገር አሳደደው።

እንዲህም ሆነ ከእርሱ አስቀድሞ ከእስክንድርያ ሀገር አባ አትናቴዎስን አሳድዶት ነበርና በሮሜ አገር በሊቀ ጳጳሳት በቅዱስ አባ ዮልዮስ ዘንድ ሁለቱም ተሰበሰቡ። እርሱም በመልካም አቀባበል በፍቅር ተቀበላቸው ወደ ንጉሡም ወደ ሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ እንዲህ ብሎ መልእክትን ጻፈላቸው "እነርሱ እውነተኞች የተማሩ አዋቂዎች ሃይማኖታቸውም የቀና ናቸው ልትቀበላቸው ልታከብራቸውም ይገባል።"

ሊቃነ ጳጳሳቱም አባ ጳውሎስና አባ አትናቴዎስ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በደረሱ ጊዜ የመልእክቱን ደብዳቤ ሰጡት አነበባትም ከሮሜው ሊቀ ጳጳሳት ቃል የተነሳ ፈራ። ተቀብሎም በየቦታቸው በሹመታቸው ወንበር አኖራቸውና ጥቂት ቀኖች በእነርሱ ላይ ታገሰ።

ከዚህም በኋላ ሁለተኛ አሳደዳቸው እነርሱም ወደ ሮሜ ወደ ሊቀ ጳጳሳት ዮልዮስ ተመልሰው ንጉሡ በእነርሱ ላይ ያደረገውን ሁሉ ነገሩት ሊቀ ጳጳሳት ዮልዮስም ወደ ወንድሙ ወደ ንጉሥ ቊንስጣ ይዟቸው ገብቶ ወንድሙ ቈስጠንጢኖስ በእነርሱ ላይ ያደረገውን ነገረው።

ይህም ንጉሥ ቊንስጣ ይቀበላቸው ዘነድ ወደ ወንድሙ መልእክትን ጻፈ እንዲህም ብሎ አዘዘው። እሊህን አባቶች ካልተቀበልካቸው ከእንግዲህ በመካከላችን ፍቅር አንድነት አይሆንም ሊቀ ጳጳሳቱም እንዲሁ ሁለተኛ ደብዳቤ ጻፈ።

ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም የወንድሙን የንጉሥ ቊንስጣንና የሊቀ ጳጳሳቱን መልእክት ተቀበሎ ወደ ሹመታቸው ወንበር መለሳቸው።

ንጉሥ ቊንስጣም በአመጸኞች እጅ ከተገደለ በኋላ ያን ጊዜ ቈስጠንጢኖስ አባ ጳውሎስን ወደ አርማንያ አገር አጋዘውና በዚያ ጥቂት ቀን አሠረው። ከዚህም በኋላ ከአርዮስ ወገን አንዱን በእሥር ቤት በሥውር አባ ጳውሎስን ይገድለው ዘንድ አዘዘው አንዱ አርዮሳዊም በሌሊት ገብቶ አንቆ ገደለው መላ ዕድሜውም አርባ ዓመት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_እልፍዮስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ መታሰቢያው ነው። ቅዱሱ አባቱ እልፍዮስ ወይም ቀለዮጳ ይባላል፡፡ ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ ሲሆን በቅዱስ ወንጌል ላይ በአብዛኛው የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብ እየተባለ ተጠርቷል፡፡ ማቴ 10፥3፣ ማር 3፦17፣ ሉቃ 6፥15፣ ሐዋ 1፥13፡፡

በሌላም በኩል ከታላቁ ያዕቆብ ከዘብድዮስ ልጅ ለመለየት ሲባል ታናሹ ያዕቆብ እየተባለ ተጠርቷል፡፡ ማር 5፥40፡፡ የእመቤታችን እኅት (ዘመድ) የቀለዮጳ ሚስት ማርያም ልጅ በመሆኑ ‹‹የጌታ ወንድም›› ተብሏል፡፡ ማቴ 13፡55፣ ማር 6፡3፣ ገላ 1፡19፡፡ ሦስት ወንድሞች ያሉት ሲሆን እነርሱም ይሁዳ፣ ስምዖንና ዮሳ ናቸው፡፡

ሐዋርያው ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ ብዙ ሀገራት ላይ ዞሮ ወንጌልን ካስተማረና ብዙዎችን ካጠመቀ በኋላ ተመልሶ ወደ ኢየሩሳሌም ገብቶ በምኩራባቸው አስተማረ፡፡ ክፉዎች አይሁድም ‹‹ደሙ በእኛ ላይ ይሁን›› ብለው ከመካከላቸው አውጥተው ወስደው ለሮማው ንጉሥ ለቄሳር እንደራሴ ለሆነው ለንጉሥ ቀላውዴዎስ አቅርበውት "ይህ ሰው ስለ ቄሳር ሳይሆን ስለ ሌላ ንጉሥ ይሰብካል" ብለው ወነጀሉት፡፡ ንጉሡም ይህን ሲሰማ በድንጋይ ወግረው እንዲገድሉት አዘዘና ፈጥነው ወስደው ወግረው ገደሉት፡፡ ዕረፍቱ የካቲት 10 ነው፤ በዚህችም ቀን መታሰቢያው እንደሆነ የጥቅምት አምስት ስንክሳር ይናገራል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ካራኮስ
በዚችም ቀን የከበረ ጳጳስ ኪራኮስ ከእናቱ ከሐና ጋራ ሰማዕት በመሆን በከሀዲው ንጉሥ በኤልያኖስ እጅ ተገደለ። ከሀዲው ንጉሥም ይህን ቅዱስ ወደ አደባባይ በአቀረበው ጊዜ ሰዎች አማልክትን እንዳያመልኩ እየጻፈች የምትከለክል ይቺ እጅህ ትቆረጥ ዘንድ ይገባታል አለው። ኪራኮስም ልብ የሌለህ ውሻ መልካም አደረግህ አለው።

ኤልያኖስም ሰምቶ እርሳስ አፍልተው በአፉ ውስጥ እንዲያፈሱት ደግሞ በጋለ የብረት ዐልጋ ፍም በተጐዘጐዘበት ላይ እንዲአስተኙት ጨውም እንዲነሰንሱበት በመጐተትና በማገላበጥም ሆዱንና ጀርባውን በብረት በትሮች ዐጥንቶቹ እስቲሰበሩ እንዲደበድቡት አዘዘ።

ቅዱስ ኪራኮስም ይህን ሁሉ ታግሦ በዕብራይስጥ ቋንቋ እንዲህ ብሎ ጸለየ ያሮክስ ለያማውታ ያለክ አሲያር ለሜዶር ኤሎሄ ናውና ያዮል ያቤል ቊራም ቤተል አዶናይ ኤሎሄ ሙታ።

ከዚህም በኋላ ፈትተው በእሥር ቤት እንዲያኖሩት እናቱንም ሐናን እንዲአመጧት በጠጉርዋም ሰቅለው ሦስት ሰዓት ያህል ሥጋዋን እንዲሠነጣጥቋት በእሳትም እንዲአቃጥሏት አዘዘ በእሳት ውስጥም እየጸለየች ነፍሷን አሳለፈች።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ኪራኮስን አምጥተው እባቦችና እፍኝቶች ከአሉበት ታላቅ ጉድጓድ ውስጥ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ ሲጨምሩትም ምንም የጐዳው ነገር የለም። ከወታደሮችም አንዱ ስሙ አድሞን የሚባል የክርስቶስን ማዳን አይቶ አደነቀ። ክብር ይግባውና በጌታችንም አመነ ንጉሡንና ጣዖታቱንም ረገመ ያን ጊዜም ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ ንጉሥ ኤልያኖስ አዘዘ እርሱም የኪራኮስ አምላክ ነፍሴን ተቀበላት እያለ አንገቱን አስተካክሎ ለሰይፍ ሰጠ ምስክርነቱንም ፈጸመ።

ቅዱስ ኪራኮስንም ከዘይት ጋር ዝፍት ከፈላበት ምጣድ ውስጥ እንዲጨምሩት ሁለተኛም ደረቱን በጦር እንዲወጉት አዘዘ። እንዲህም ምስክርነቱን በዕለተ ሰንበት ፈጸመ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት
#ጥቅምት_6

ጥቅምት ስድስት በዚህች ቀን እመ ሳሙኤል ነቢይ #ቅድስት_ነቢይት_ሐና ያረፈችበት፣ ቅዱስ አባት #አባ_ጰንጠሌዎን ያረፈበት፣ #ዕንባቆም_ነቢይ መታሰቢያው፣ የሀገረ አቴና ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ዲዮናስዮስ በሰማዕትነት ያረፈበት እና የሴት ልጅ #ቅዱስ_ሄኖስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ነቢይት_ሐና

ጥቅምት ስድስት በዚህች ቀን የታላቁ ነቢይና ካህን የሳሙኤል እናት ቅድስት ነቢይት ሐና አረፈች።

ይችም ቅድስት ከሌዊ ነገድ ናት የታኅርም ልጅ ሕልቃና አገባት ፍናና የምትባልም ሌላ ሚስት አለችው እርሷም ወላድ በመሆኗ ሐና ልጅ ስለሌላት መካንም ስለሆነች ሁልጊዜ ትገዳደራት ነበር።

ሐና ግን ፈጽማ በማዘን አትበላም አትጠጣም ባሏ ሕልቃናም ያረጋጋታል ማረጋጋቱንም አልተቀበለችውም በሊቀ ካህናቱ በኤሊ ዘመንም ወደቤተ እግዚአብሔር ወጣች እያለቀሰችና እያዘነች በእግዚአብሔር ፊት ጸለየች እንዲህም ብላ ስለትን ተሳለች አቤቱ ልጅ የሰጠኸኝ እንደሆነ በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለአንተ የሚያገለግል አደርገዋለሁ።

ካህኑ ኤሊም አያትና እርሷ የወይን ጠጅ ጠጥታ እንደ ሰከረች አሰበ እርሷ በዝምታ በልቧ ትጸልይ ነበርና በቊጣና በግሣጼ የወይን ጠጅ ጠጥተሽ ወደዚህ ወደ እግዚአብሔር ቤት ለምን መጣሽ አሁን ሒጂ ስካርሺን በእንቅልፍ አስወግጂ አላት።

እርሷም እንዲህ አለችው የወይን ጠጅ ከቶ አልጠጣሁም ልጅ ያጣሁ በመሆኔ በልቤ አዝናለሁ እንጂ ካህን ኤሊም አጽናናት እንዲሁም ብሎ ባረካት የእስራኤል ፈጣሪ የለመንሽውን ይስጥሽ በሰላም ሒጂ በቃሉም አምና ወደ ቤቷ ገባች።

ከዚህም በኋላ ፀንሳ ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ሳሙኤል ብላ ጠራችው። ጡትንም በአስጣለችው ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ቤት ይዛው ወጣች ወደ ካህን ኤሊም አቀረበችውና እንዲህ ብላ አስረዳችው ከአሁን በፊት ልጅን ይሰጠኝ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ስጸልይና ስለምን ያየኸኝ ሴት ነኝ ልመናዬንም ሰምቶ ይህን ልጅ ሰጠኝ አሁንም በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለእግዚአብሔር አገልጋይ ይሆን ዘንድ አመጣሁት።

ከዚህም በኋላ ሐና እግዚአብሔርን አመሰገነችው። ልቤ በእግዚአብሔር አምኖ ጸና የሚለውን ጸሎትና ትንቢት እስከ መጨረሻው ተናገረች። ይቺም በዳዊት መዝሙር መጨረሻ ከሙሴ መኀልይ ቀጥላ ተጽፋለች።

ከዚህም በኋላ እግዚአብሔርን አገልግላ በሰላም አረፈች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ጰንጠሌዎን

ዳግመኛም በዚችም ቀን በዋሻ ውስጥ የሚኖር ቅዱስ አባት አባ ጰንጠሌዎን አረፈ። ይህም ቅዱስ በሮሜ አገር በንጉሥ ቀኝ ከሚቀመጡ ከከበሩ ሰዎች ወገን የተወለደ ነው ። በታናሽነቱም ጊዜ ወደ መነኰሳት ገዳም ወስደውት በበጎ ምክር ዕውቀትን እየተማረ በመጸለይና በመጾም በዚያ አደገ።

ከዚህም በኋላ ከቅዱሳን ከስምንቱ ባልንጀሮቹ ጋር ወደ ኢትዮጵያ በንጉሥ አልዓሜዳ ዘመን መጣ በአንድነትም ጥቂት ዘመናት ኑረው ከዚህም በኋላ እርስበርሳቸው ተለያዩ ቅዱስ ጰንጠሌዎንም ከታናሽ ተራራ ላይ ወጥቶ ርዝመቱ አምስት ክንድ አግድመቱ ሁለት ስፋቱ ሦስት ክንድ የሚሆን ዋሻ ለራሱ ሠራ ጠፈሩም አንድ ደንጊያ ነው ከጥቂት ቀዳዳ በቀር በር የለውም።

በውስጡም ሳይቀመጥ ሳይተኛ ያለመብልና ያለ መጠጥ አርባ አምስት ዓመት ኖረ ቆዳው ከዐጥንቱ እስከሚጣበቅ በዕንባ ብዛትም ቅንድቡ ተመለጠ። በሽተኞችን በማዳን የዕውሮችንም ዐይኖች በመግለጥ ብዙ ተአምራትን አደረገ።

በአንዲትም ቀን በማታ ጊዜ ዕንጨት ተከለ አሰከሚነጋ ድረስም አድጎ ትልቅ ዛፍ ሆነ ወዲያውም ደረቀና ደቀ መዝሙሩ ፈልጦ አነደደው ፍሙንም በልብሱ ቋጥሮ ለማዕጠንት ወሰደው።

የናግራንን አገር ያጠፋትን ምእመናኖችንም የገደላቸውን አይሁዳዊ ንጉሥ ሒዶ ሊወጋው ንጉሥ ካሌብ በአሰበ ጊዜ በጸሎቱ ይረዳው ዘንድ ይህን አባት ጰንጠሌዎንን ለመነው እርሱም በሥራው ሁሉ ላይ ችሎታ ያለው እግዚአብሔር በጠላቶችህ ላይ ድል አድራጊነትን ሰጥቶህ በደኀና በፍቅር አንድነት ትመለሳለህ አለው።

ንጉሥ ካሌብም ከናግራን ሀገር በደረሰ ጊዜ ከከሀዲው ንጉሥ ከፊንሐስ ጋር ተዋጋ ድል አድርጓቸውም ከሀድያንን ሁሉ እንደ ቅጠል እስቲረግፉ አጠፋቸው አባ ጰንጠሌዎንንም በጦርነቱ መካከል ጠላቶችን ሲአሳድዳቸው እንዳዩት ብዙዎች ምስክሮች ሆኑ።

ከዚህም በኋላ ንጉሥ ካሌብ ከድል አድራጊነት ጋር በተመለሰ ጊዜ መንግሥቱን ትቶ በዚህ አባት እጅ መነኰሰ ከዋሻ ውስጥም ገብቶ በጾምና በጸሎት እየተጋደለ ኖረ።

ይህም ቅዱስ አባ ጰንጠሌዎን ተጋድሎውን በፈጸመ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ መጣ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን የሚያደርግ ገድሉንም ለሚጽፍ ቃል ኪዳን ሰጠው እንግዲህስ ድካም ይበቃሀል ዕረፍ ያን ጊዜም ዐጥንቶቹ ተነቃነቁ በፍቅር አንድነትም አረፈና በዚያ በዋሻው ውስጥ ተቀበረ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዕንባቆም_ነቢይ

በዚችም ቀን የስሙ ትርጓሜ አዋቂ የሆነ የዕንባቆም ነቢይ መታሰቢያው ነው። ይህም ቅዱስ በአንዲት ዕለት እህሉን ለሚያጭዱለት ምሳቸውን አዘጋጅቶ ተሸክሞ ሲሔድ መልአክ ተገልጾለት ይህን መብል በባቢሎን አገር በአንበሶች ጕድጓድ ውስጥ ላለ ለነቢዩ ዳንኤል ውሰድ አለው።

ዕንባቆምም ጌታዬ ሆይ ባቢሎንን አላየኋት ጉድጓዱንም አላውቀው አለው። የእግዚአብሔር መልአክም በራሱ ጠጉር ያዘው ምግቡን በእጁ እንደያዘ ወሰደውና ጉድጓዱ እንደተዘጋ አስገባው ምግቡንም ሰጥቶ መገበው ወዲያውኑ ዕንባቆምን ወደ ይሁዳ አገር መለሰው።

በአረጀና በሸመገለም ጊዜ የእስራኤል ልጆች ከተማረኩበት ተመልሰው ቤተ መቅደስን ሠሩ። ዕንባቆምም ኢየሩሳሌም ደርሶ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ በታላቅ ደስታም ተቀበሉት ትንቢቱንም ሊሰሙ ወደርሱ ተሰበሰቡ አፉንም ከፍቶ በመንፈስ ቅዱስ እንዲህ አለ።

አቤቱ ድምፅህን ሰማሁ ሰምቼም ፈራሁ ሥራህንም አይቼ አደነቅሁ አለ። ስለ መድኃኒታችንም መውረድና በይሁዳ ክፍል በሆነች በቤተ ልሔም ስለመወለዱ ሲናገር የተመሰገነ እግዚአብሔር ግን ከፋራን ተራራ ከቴማን ከይሁዳ አውራጃ ይመጣል ብሎ እስከ መጨረሻው ተናገረ ከነቢያት መጻሕፍትም ጋራ ደመርዋት።

ከዚህ በኋላ ከእስራኤል ልጆች አንዲት ሴት ወደርሱ መጣች እያለቀሰችም እንዲህ አለችው። ሁለት ልጆች ነበሩኝ ጣዖት እንዲአመልኩ ፈለጉአቸው እምቢ በአሉ ጊዜም ገድለው በጐዳና ላይ ጣሉአቸው። ተገድለው ወደ አሉበትም አብሮዋት ሔደ ነፍሳቸውንም ይመልስላቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው ልመናውንም ተቀበሎ በሕይወት አነሣቸው።

ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ዘመዶቹን ጠራቸው። እንደሚሞትም ነገራቸውና አንዲት ሰዓት ያህል ወደላይ እየተመለከተ ተቀመጠ ። እነሆ እንደ ሰው ክንድ ያለች ታላቅ ክንድ የቤቱን ጣሪያ ሠንጥቃ ወረደች ወደ አፉም ተዘርግታ ነፍሱን ወሰደች ያን ጊዜም አረፈ።

በክርስቲያናዊ ንጉሥ በአንስጣስዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ ገድሉን በአነበበ ጊዜ አድንቆ በግብጽ ደቡብ ቀርጣስ በሚባል ቦታ በስሙ ቤተ ክርስቲያን ተሠራለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ኤጲስቆጶስ_ቅዱስ_ዲዮናስዮስ
በዚችም ቀን የሀገረ አቴና ኤጲስቆጶስ ቅዱስ ዲዮናስዮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ በአቴና አገር በእውቀቱና በመራቀቁ የከበረና ከፍ ከፍ ያለ ነው። በአቴናው ከተማ በዐዋቂዎች የመሳፍንት አንድነት ከአማካሪዎች አንዱ እርሱ ነው።

ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስም ወደዚያ በደረሰ ጊዜ ሃይማኖትን አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጥምቆ በአቴና አገር ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመው።

ብዙ ድርሳናትንም ደረሰ ከእርሳቸውም አንዱ ክብር ይግባውና ስለ መድኃኒታችን ስቅለት የደረሰው በዕለተ ዐርብ የሚነበብ አንዱ ነው።

የእምነቱም ምክንያት እንዲህ ነው ከዕለታት በአንዱ በፍልስፍናው ቤት ተቀምጦ ሳለ የአቴናም ፈላስፎች በእርሱ ዘንድ ተሰብስበው ነበር እርሱ ለሁሉም አለቃ ስለሆነ በዐርብ ቀንም ቀትር ሲሆን ፀሐይ ጨለመ ታላቅ ንውጽውታም ሆነ አሕዛብ ሁሉ ደንግጠው እጅግ ፈሩ ቅድስ ዲዩናስዩስንም በዓለም ውስጥ የሆነውን ጌታችን ሆይ አስረዳን ብለው ጠየቁት።

አርሱም ፀሐይን ጨረቃንና ከዋክብትን መረመረ ጸጥ ብለው አገኛቸው ደግሞ ባሕሮችን ትልቁንም በዓለም ዙሪያ ያለውን የውቅያኖስን ባህር መረመረ እሱንም ጸጥ ብሎ አገኛው።

ከዚህም በኋላ አርስጣላባ የሚባል የፍልስፍና መጽሐፍን አንስቶ ሲመረምር በውስጡ እልመክኑን የሚል አገኘ ይህም ኀቡእ አምላክ ወረደ ወገኞቹም በእርሱ ላይ ተነስተው ሰቀሉት ማለት ነው በዚያችም ጊዜ ልብሱን ቀዶ ታላቅ ሀዘንን አዘነ ከበታቹ ምሁራን ያየውን ያስርዳቸው ዘንድ ለመኑት እርሱም ሁሉን ነገራቸው እነርሱም ይህን ሰምተው ታላቅ ፍርሃት ፈሩ።

ደቀ መዝሙሩ ኡሲፎስንም የሆነውን ሁሉ የዚያችንም ቀን ስሟን ሰዐቷን ወርዋን ዘመኑንም እንዲጽፍ አዘዘው ዳግመኛም በጣዖታቱ ቤቶች በደጃፋቸው እልመክኑን እያሉ እንዲጽፉ አዘዘ።

ከዐሥራ አራት ዓመትም በኋላ ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ ወደ አቴና አገረ መጣ ክብር ይግባውና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መውረዱን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከስጋዋ ስጋ ከነፍሷ ነፍስን ነስቶ መወለዱን መከራ መቀበሉን መሰቀሉንና መሞቱን በሶስተኛው ቀን መነሳቱን ማረጉንም በሕያዋንና በሙታን ለምፍረድ ዳግመኛ መምጣቱን አስተማረ።

የአቴና ሰዎችም የሐዋርያዉን ስብከት በሰሙ ጊዜ እጅግ አደነቁ ወደ ዲዩናስዩስም ሩጠው እንዲህ ብለው ነገሩት አንድ ሰው ዛሬ ወደ አገራችን መጥቶ እኛ የማናውቀውን ወይም ከእኛ በፊት የነበሩ አባቶቻችን የማያውቁትን በአዲስ አምላክ ስም አስተማረን።

ዲዮናስዮስም ልኮ ሐዋርያ ጳውሎስን ወደርሱ አስመጥቶ በሀገራችን ውስጥ በአዲስ አምላክ ስም የምታስተምረው ምንድን ነው አለው።

ቅዱስ ጳውሎስም በአደባባያችሁ መካከል አልፌ ስሔድ በአማልክቶቻችሁ ቤቶች በደጃፋ ላይ እልመክኑን የሚል ጽሑፍ አየሁ ይህም የማይመረመር አምላክ ወረደ ማለት ነው እኔም ለእናንተ የምሰብከው ይህንኑ ነው ብሎ መለሰ።

በዚያንም ጊዜ ከዐሥራ አራት ዓመት በፊት ያጻፈውን ያን መጽሐፍ ያመጣው ዘንድ ኡሲፎስን አዘዘው ሁለተኛም ጊዜውንና ወራቱን ሐዋርያውን ጠየቀው እርሱም በመጋቢት ወር በሃያ ሰባት ዓርብ ቀን በስድስት ሰዓት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርሶቶስ ያን ጊዜ እንደ ተሰቀለ ፀሐይም እንደ ጨለመ ምድርም እንደተናወጠች አስረዳው።

የአቴና ሰዎችም ይህን በስሙ ጊዜ ከቅዱስ ዲዮናስዮስ ጋር ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ዲዮናስዮስንም በእነርሱ ላይ ኤጲስቆጶስን አድርጎ ሾመው የቤተ ክርስቲያንንም ሥርዓት የተረጐመ እርሱ ነው።

ከዚህም በኋላ በባሕር አቅራቢያ ወደ አለ አገር በመሔድ በሐዋርያት ዘመን አስተማረ ብዙ ወገኖችንም ክብር ይግባውና በጌታችንም አሳመነ ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራትን አደረገ።

ከሀዲ ንጉሥ ጠማትያኖስም ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሰቃየው ከዚያም የከበረች ራሱን በሰይፍ ቆረጠው የተቆረጠች ራሱንም በእጁ ይዞ ሁለት ምዕራፍ ያህል ጐዳና ተጓዘ ሁለተኛም የደቀ መዛሙርቱን የኡሲፎስንና የኡርያኖስን ራሳቸውን ቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሄኖስ

በዚችም ቀን የሴት ልጅ የሄኖስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው የእግዚአብሔርንም ስም መጥራት የጀመረ ይህ ሄኖስ ነው። ሄኖስም መቶ ዘጠና ዓመት ኖረ ቃይናንም ወለደው ቃይናንንም ከወለደው በኋላ ሰባት መቶ አሥራ አምስት አመት ኖረ ወንዶች ልጆችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ በቅዳሜ ቀንም አረፈ። መላ ዕድሜውም ዘጠኝ መቶ አምስት ነው።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_7

#አባ_ባውላ

ጥቅምት ሰባት በዚች ቀን ጠመው ከሚባል አገር የሆነ የከበረ አባት አባ ባውላ አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ መስተጋድል መነኲሴ ሆነ የሚኖረውም በላይኛው ግብጽ በአለ በእንጽና ገዳም ነው ስሙ ሕዝቅኤል የሚባል ረድእ አለው። እርሱም ስለ ትሩፋቱና ስለ ተጋድሎው ምስክር ሆነ ይህ አባ ባውላ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ራሱን ሰባት ጊዜ ገድሏልና።

#መጀመሪያው ራሱን በዕንጨት ላይ ዘቅዝቆ በመስቀል አርባ መዓልት አርባ ሌሊት እንደ ተሰቀለ ኖረ። ደሙም በአፍንጫው ፈሰሰ ነፍሱንም አሳለፈ እግዚአብሔርም ከሞት አነሣው።

#ሁለተኛው ዓሣዎችና ዓንበሪዎች እንዲበሉት ራሱን ከባሕር ጨመረ እነርሱ ግን አልነኩትም በባሕርም ሠጥሞ ብዙ ወራት ኑሮ ሞተ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዳግመኛ ከሞት አስነሣው።

#ሦስተኛም ጊዜ ራሱን በአሸዋ ውስጥ ደፍኖ ሞተ ጌታችንም አስነሣው።

#አራተኛም በውስጡ ስለታሞች ድንጋዮች ካሉት ረጅም ተራራ ላይ ወጥቶ ራሱን ከተራራው ላይ ወደ ታች ወርውሮ ተንከባለለ የተሳሉ ደንጊያዎችም በሥጋው ሁሉ ገብተውበት ሞተ። ረድኡም ያለቅስለት ነበረ ጌታችንም መጥቶ ከሞት አሥነሣው አጽናናውም ።

#አምስተኛ ከረጅም ዛፍ ላይ ወጥቶ ከስለታም ደንጊያ ላይ ራሱን ወረወረ ከሁለትም ተከፈለና ሞተ ያን ጊዜም ጌታችን አስነሣው።

#ስድስተኛ ራሱን በእግሮቹ ውስጥ አሥሮ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት እንዲህ ሁኖ ሞተ እግዚአብሔርም መልአኩን ልኮ ከሞት አነሣው አጽናናውም።

#ሰባተኛ ከውኃ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ እጆቹን ዘርግቶ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት በመቆም ሞተ ክብር ይግባውና ጌታችንም አስነሣው እንዲህም ብሎ አጽናናው ወዳጄ ባውላ ሆይ ራስህን ሰባት ጊዜ እስከምትገድል ድረስ ሰውነትህን አደከምክ እንግዲህ ድካምህ ይብቃህ።

አባ ባውላም ለመድኃኒታችን እንዲህ ብሎ መለሰለት ጌታዬ ሆይ ስለ ከበረው ስምህ እደክም ዘንድ ተወኝ አንተ አምላክ ስትሆን ስለኛ በመከራ ደክመህ ስለ ሰው ወገን ሞትክ ለእኛ ይህ አይገባንም ነበር በቸርነትህ ይህን የማዳንህን ሥራ ሠራህልን እንጂ። ጌታችንም ከአጽናናው በኋላ ከእርሱ ወደ ሰማይ ወጣ።

ከዚህም በኋላ አባ ብሶይ ወደ እንጽና ገዳም ሒዶ ከአባ ባውላ ጋር ተገናኘ ጌታችንም ለአባ ባውላ ተገልጾለት ሥጋህ ከአባ ብሶይ ሥጋ ጋር በአንድነት ይኑር አለው ሁለቱም በአረፉ ጊዜ ሥጋቸውን በአንድነት አኖሩ።

ወገኖቹም የአባ ብሶይን ሥጋ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊወስዱ በወደዱ ጊዜ በመርከብ ጫኑት መርከቢቱ ግን መንቀሳቀስን እምቢ አለች። ከዚህም በኋላ ተመልሰው የአባ ባውላን ሥጋ አምጥተው በመርከብ ላይ ጫኑት ያን ጊዜ መርከቢቱ ተጓዘች። እንዲህም የቅዱሳኑን ሥጋቸውን ወደ አስቄጥስ ገዳም አድርሰው በአባ ብሶይ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በአንድነት አኖሩ እስከ ዛሬም በዚያ ይኖራሉ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_8

ጥቅምት ስምንት በዚች ቀን ታላቁ አባት #አባ_አጋቶን መታሰቢያው ነው፣ ሽማግሌው #አባ_መጥራ በሰማዕትነት አረፈ፣ በላይኛው ግብጽ ከሚኖሩ ሰዎች ወገን የሆነ ቅዱስ አባት #አባ_ሖር መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_አጋቶን_ባህታዊ

ዳግመኛም በዚህ ቀን ታላቁ አባት አባ አጋቶን መታሰቢያው ነው፡፡ ይህን ቅዱስ ታላቅ ጻድቅ ገዳማዊና የእግዚአብሔር ሰው ሲሆን አንደበቱን ከክፋት ይከለክል ዘንድ ለ30 ዓመታት ድንጋይ ጐርሶ ኖሯል። ይህንን ቅዱስ ሊቃውንት ሲገልጹት "ክምረ ክምር ጽድቁ እስከ አስተርአየ" ይሉታል። ትእግስቱ ደግነቱ አርምሞው ትሩፋቱ ከመነገር በላይ ነው። በነበረበት በ4ኛው መቶ ክ/ዘመንም እንደ ኮከብ ያበራ ታላቅ አባት ነው።

ታላቁ ገዳማዊ አባት አጋቶን የታላቁ መቃርዮስ የመንፈስ ልጅ ነው። ገዳመ አስቄጥስ እልፍ አእላፍ ቅዱሳንን ስታፈራ ይህ አባት ቅድሚያውን ይይዛል። ምንም በብዛት የሚታወቀው በአርምሞው (በዝምታው) ቢሆንም ባለ ብዙ ትሩፋት አባት ነው። የሚገርመው የቀደሙ አባቶቻችን የፈለገውን ያህል መናኝ ቢሆኑም የሰው ጥገኛ መሆንን አይፈልጉም። "ሊሠራ የማይወድ አይብላ" የሚለውን መለኮታዊ ትዕዛዝ መሠረት አድርገው ከተጋድሎ በተረፈቻቸው ሰዓት ሥራ ይሠራሉ። አንዳንዶቹ እንደሚመስላቸው ምናኔ ሥራ መፍታት አይደለምና ሰሌን ዕንቅብ ሠፌድ የመሳሰለውን ይሠፋሉ። ታላቁ አባ አጋቶንም በአንደበቱ ድንጋይ ጐርሶ በእግሮቹ ቀጥ ብሎ ቆሞ እንቅቦችን ይሠፋ ነበር። ቅዱሱ የሰፋውን ወደ ገበያ ይወጣል በጠየቁትም ዋጋ ሽጦት አንዲት ቂጣ ይገዛል። የተረፈውን ገንዘብ ግን እዚያው ለነዳያን አካፍሎት ይመጣል እንጂ ወደ ገዳሙ አይመልሰውም።

አንድ ቀን እንደልማዱ የሠፋቸውን እንቅቦች ተሸክሞ ወደ ገበያ ሲሔድ መንገድ ላይ አንድ የኔ ቢጤ ወድቆ ያገኛል። እንደ ደረሰም ስመ እግዚአብሔር ጠርቶ ይለምነዋል። አባ አጋቶን ከእንቅቦቹ ውጪ ምንም ነገር አልነበረውምና "እንቅቡን እንካ" አለው። ነዳዩ ግን ወይ የሚበላ ካልሆነም ገንዘብ እንደሚፈልግ ይነግረዋል። ወዲያው ደግሞ "የምትሠጠኝ ነገር ከሌለህ ለምን ወደ ገበያ ተሸክመህ አትወስደኝም?" አለው። የነዳዩ አካል እጅግ የቆሳሰለ በመሆኑ እንኩዋን ሊሸከሙት ሊያዩትም የሚከብድ ነበር። ጻድቁ ግን ደስ እያለው ያለማመንታት አንስቶ ተሸከመው። ከረጅም መንገድ በኋላ ከገበያ በመድረሳቸው አውርዶ ከጐኑ አስቀመጠው። ያ ነዳይ አላፊ አግዳሚውን ሁሉ ቢለምንም የሚዘከረው አጣ። አባ አጋቶን አንዷን እንቅብ ሲሸጥ "ስጠኝ?" ይለዋል። ጻድቁም ይሠጠዋል። እንዲህ "ስጠኝ" እያለ የእንቅቦችን ዋጋ ያ ነዳይ ወሰደበት። አባ አጋቶን ግን ምንም ቂጣ ባይገዛም በሆነው ነገር አልተከፋምና ሊሔድ ሲነሳ ነዳዩ "ወደ ቦታየ ተሸክመህ መልሰኝ" አለው። አባቶቻችን ትእግስታቸው ጥግ የለውምና ጐንበስ ብሎ በፍቅር አንስቶት አዘሎት ሔደ። ካነሳበት ቦታ ላይ ሲደርሱ ይወርድለት ዘንድ ጻድቁ ቆመ። ነዳዩ ግን አልወርድም አለ። ትንሽ ቆይቶ ግን ለቀቀው ሊያየው ዞር ቢል መሬት ላይ የለም። ቀና ሲል ግን ያየውን ነገር ማመን አልቻለምና ደንግጦ በግንባሩ ተደፋ። ነዳይ መስሎ እንዲያ ሲፈትነው የነበረው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ነበርና ክንፎቹን ዘርግቶ በብርሃን ተከቦ በግርማ ታየው ከወደቀበትም አነሳው። "ወዳጄ አጋቶን ፍሬህ ትእግስትህ ደግነትህ ግሩም ነውና ዘወትር ካንተ ጋር ነኝ" ብሎት ተሰወረው፤ ጻድቁም በደስታ ወደ በዓቱ ሔደ። አባ አጋቶን ተረፈ ዘመኑን በአርምሞ ኑሮ ዐርፏል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መጥራ_አረጋዊ (ሰማዕት)

ጥቅምት ስምንት በዚች ቀን ሽማግሌው አባ መጥራ በሰማዕትነት አረፈ። ከእርሱም ጋር ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት አረፉ። ይህም ቅዱስ ከእስክንድርያ አገር አማኒ ክርስቲያን ነው። ከሀዲ ንጉሥ ዳኬዎስ በነገሠ ጊዜ የጣዖትን አምልኮ አቁሞ የክርስቲያንን ወገኖች አሠቃያቸው።

ትእዛዙም ወደ እስክንድርያ አገር ደርሶ ሰዎቿን ሁሉንም አሠቃያቸው የብዙዎች ምእመናንንም ደማቸውን አፈሰሰ። ያን ጊዜ ክርስቲያን እንደ ሆነ ቅዱስ መጥራን በመኰንኑ ዘንድ ወነጀሉት፤ መኰንኑም ወደርሱ አስቀረበው እርሱም ብቻውን እውነተኛ አምላክ እንደ ሆነ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ።

መኰንኑም ለአማልክት ስገድ እኔም ብዙ ገንዘብን እሰጥሃለሁ ታላቅ ክብርንም አከብርሃለሁ አለው። እርሱም ቃል ኪዳኑን አልተቀበለም ኪዳንህና ገንዘብህ ካንተ ጋራ ወደ ጥፋት ይሒድ አለው እንጂ። መኰንኑም በእርሱ ላይ ተቆጥቶ እኔ በጽኑዕ ሥቃይ እቀጣሃለሁ አለው።

ቅዱስ መጥራም ፈርቶ ከበጎ ምክሩ አልተመለሰም እንዲህም አለው እንጂ እኔ ሰማይና ምድርን ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር እሰግዳለሁ። ለረከሱ ጣዖታት ከደንጊያና ከዕንጨት ለተሠሩ ለማያዩ ለማይሰሙ ለማይናገሩ ለማያሸቱ ለማይንቀሳቀሱ እንሰግድ ዘንድ እንዴት ይገባል አለው።

መኰንኑም በሰማ ጊዜ አፈረ። ጽኑ ግርፋትንም እንዲገርፉት አዘዘ። ከዚህም በኋላ በክንዱ ሰቀሉት በደረቀች ሽመልም ጎኖቹን ሠነጠቁ ቀደዱትም ክብር ይግባውና ጌታ ኢየሱስም አዳነው። ያለ ጥፋትም በጤንነት አስነሣው መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ከከተማውም አውጥተው የከበረች ራሱን ቆረጡ። ሌሎች ብዙዎች ሰማዕታትንም ከእርሱ ጋር ራሶቻቸውን ቆረጡ። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ሖር

ዳግመኛም በዚችም ቀን በላይኛው ግብጽ ከሚኖሩ ሰዎች ወገን የሆነ ቅዱስ አባት አባ ሖር መታሰቢያው።

ደግነት ያለው መነኰስ በመሆን ጽኑዕ ገድልን ተጋደለ በአምልኮቱና በተጋድሎው ከቅዱሳን ሁሉ ተለይቶ በብዙዎች ላይ ከፍ ከፍ አለ ለብቻ መኖርን ስለወደደ ወደ በረሀ ወጥቶ በገድል ተጠምዶ ብዙ ዘመናት ኖረ። የበጎ ሥራ ጠላት የሆነ ሰይጣንም ቀንቶበት በግልጥ ታየውና በበረሀ ውስጥ ግን አንተ ድል ትነሣናለህ በዚህ ሰው የለምና ጽኑ ኃይለኛ ከሆንክ ወደ እስክንድርያ ከተማ ና ብሎ ተናገረው።

አባ ሖርም ይህን በሰማ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኃይል ተማምኖ ወደ እስክንድርያ ከተማ ሒዶ ለእሥረኞችና ለችግረኞች ደካሞች ውኃ የሚቀዳ ሆነ በአንዲት ዕለት ሦስት ፈረሶች በከተማው ውስጥ እየዘለሉ ሲያልፉ አንዱ ፈረስ አንዱን ሕፃን ረገጠውና ወዲያውኑ ሞተ ሰይጣንም በሰዎች ልብ አደረና ይህን ሕፃን ያለዚህ አረጋዊ መነኵሴ የገደለው የለም ብለው አሰቡ አባ ሖርም መጣና ሕፃኑን አንሥቶ ታቀፈው በልቡም በመጸለይ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ማለደ በመስቀል ምልክትም በላዩ አማተበ የሕፃኑም ነፍስ ተመለሰች ድኖም ተነሣ ለአባቱም ሰጠው ወደ ከተማ ውጭ ሸሽቶ በመሔድ ወደ በዓቱ ገባ ፈልገውም አላገኙትም ጽድቅንና ትሩፋትንም በመሥራት ብዙ ዘመናት በገድል ተጠምዶ ኖረ።

የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ ብዙዎች ቅዱሳንን ሲጠሩት አያቸው እጅግም ደስ አለው ልጆቹንም ሰብስቦ በምንኲስና ሥርዓት ጸንተው ትሩፋትን እንዲሠሩ አዘዛቸው ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እርሱ እንደሚሔድ ነገራቸው እነርሱም እጅግ አዘኑ ጥቂት ቀንም ታሞ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_ጥቅምት እና #ከገድላት_አንደበት)
#ጥቅምት_10

ጥቅምት ዐሥር በዚህች ቀን የቅዱስ ባኮስ ባልንጀራ የሆነ #ቅዱስ_ሰርጊስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_አውማንዮስ አረፈ፣ መስተጋድል የሆነ #ቀሲስ_ዮሐንስ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሰርጊስ_ሰማዕት

ዳግመኛም በዚችም ቀን ከከሀዲ ንጉሥ መክስምያኖስ ሠራዊት ውስጥ የቅዱስ ባኮስ ባልንጀራ የሆነ ቅዱስ ሰርጊስ በሰማዕትነት አረፈ። ንጉሥ መክስምያኖስም ወደ ሶርያ አገር ወደ አንጥያኮስ በላካቸው ጊዜ ቅዱስ ባኮስን ከውኃ በማስጠም በዚህ ወር በአራተኛ ቀን ገደሉት። ቅዱስ ሰርጊስን ግን አሥሮ በወህኒ ቤት አኖረው።

ከዚህም በኋላ በእግሮቹ ውስጥ ረጃጅም የብረት ችንካሮችን ቸንከረው ከፈረሰኞች ጋር ሩጻፋ ወደሚባል አገር እንዲወስዱት መኰንኑ አዘዘ።

ሲወስዱትም ያስሮጡት ነበር ደሙም በምድር ላይ እንደ ውኃ ይፈስ ነበር በጐዳናም አንዲት ድንግል ብላቴና አገኘ ከእርሷም ዘንድ ውኃን ጠጣ ሥጋዬን ትወስጂ ዘንድ እስከ ሩጻፋ ተከተይኝ አላት እርሷም ራራችለት ለጒልምስናውም አዘነችለትና ተከተለችው።

አንጥያኮስም እንዲህ ብሎ ጽፎአልና ሰርጊስ ትእዛዜን ተቀብሎ ለአማልክት ካልሠዋ ራሱን በሰይፍ ይቁረጡ። እርሱም ለቅዱስ ሰርጊስ ወዳጅ ነበርና ስለርሱም ይችን ሹመት አግኝቷት ነበርና በዚያንም ጊዜ ወታደሩ የቅዱስ ሰርጊስን ራስ ቆረጠው ያቺም ብላቴና ቀርባ ከእርሷ ጋር በነበረ የፀጕር ባዘቶ ከአንገቱ የፈሰሰውን ደሙን ተቀበለች። የስደቱም ወራት እስከ አለፈ ድረስ ሥጋውን ጠበቀች።

ከዚህም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ተሠራችለት ዐሥራ አምስት ኤጲስቆጶሳትም አከበሩዋት የቅዱስ ሰርጊስንም ሥጋ በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ እጅግ ሽታው ጣፋጭ የሆነ በሽተኞችን የሚፈውስ የሽቱ ቅባት ከሥጋው ይፈስ ነበርና።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሊቀ_ጳጳሳት_ቅዱስ_አውማንዮስ

ጥቅምት ዐሥር በዚች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባተኛ የሆነ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት አውማንዮስ አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ትሑት የሆነ ለዕውነተኛ ሥራ ሁሉ የሚያገለግል ነበር ቅዱስ አብርምዮስም ትሩፋቱን አይቶ ዲቁና ሾመው በዲቁና አገልግሎትም ዐሥር ዓመት ኖረ።

ዮስጦስም ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ ትሩፋቱንና የሃይማኖቱን ቅንነት ተመለከተ ምእመናንንም ማስተማር እንደሚችል አውቆ ቅስና ሾመው። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ዮስጦስ በአረፈ ጊዜ ይህን አባት አውማንዮስን መርጠው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት የአብያተ ክርስቲያናትንም ሥራ ሁሉ ተረከበ።

መናፍቃንንም ተከራክሮ የሚረታቸው ሆነ ብዙዎችንም ከስሕተታቸው መለሳቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመለኮቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ትክክል እንደሆነ ግልጽ አድርጎ አስተማራቸው። በሹመቱም ዐሥራ ሦስት ዓመት ከኖረ በኋላ በአንስጣዮስ ሰባተኛ ዘመነ መንግሥት በዚች ቀን አረፈ። በዘመኑም የሶፍያ ሦስቱ ልጆቿ በሰማዕትነት አረፉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ቀሲስ

ዳግመኛም በዚችም ቀን መስተጋድል የሆነ ቀሲስ ዮሐንስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከተጋድሎው ብዛት የተነሣ ራሱን በሚላጭ ጊዜ በውኃ አያርሰውም ነበር።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይግባው እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_12

ጥቅምት አስራ ሁለት በዚህች ዕለት ሊቀ መላእክት #ቅዱስ_ሚካኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ #ቅዱስ_ዳዊትን በሳኦል ፈንታ እንዲሾመው ለሳሙኤል የነገረበት እና በጎልያድ ላይ ኃይልን የሰጠበት እንዲሁም የወንጌላዊው #ቅዱስ_ማቴዎስ እና #የቅዱስ_ድሜጥሮስ የዕረፍት ቀን ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዳዊት_ልበ_አምላክ (የነገሠበት)

ጥቅምት ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ የሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚችም ቀን ወደ ነቢይ ሳሙኤል እግዚአብሔር ልኮታልና የዳዊት አባት ወደሆነ በቤተ ልሔም ወደሚኖር ወደ እሴይ ቤት ይሔድ ዘንድ በቂስ ልጅ በሳኦልም ፈንታ ለእስራኤል ልጆች እንዲነግሥ ልጁ ዳዊትን ይቀባው ዘንድ አዘዘው።

ሳሙኤልም ወደ እሴይ ቤት ሔዶ ልጆችህን ሁሉንም አቅርብልኝ ብለው እሴይም ከዳዊት በቀር ሁሉንም አቀረባቸው እርሱ በእርሻ ውስጥ በጎችን ይጠብቅ ነበርና።

ሳሙኤልም የመንግሥት ቅባት ያለበትን ብልቃጥ በራሳቸው ላይ ከፍ ከፍ በአደረገ ጊዜ እግዚአብሔር አልመረጣቸውም ። ሳሙኤልም እሴይን ልጆችህ እነዚህ ብቻ ናቸውን አለው ዕሴይም በጎች የሚጠብቅ አንድ ትንሽ ልጅ አለ አለው።

ሳሙኤልም ደግሞ ዕሴይን እሱ ሳይመጣ ምሳ አልበላምና ልከህ አስመጣው አለው። እሱም ልኮ አስመጣው መልኩም ቀይ ዐይኖቹም የተዋቡ አርአያውም ያማረ ነው እግዚአብሔርም ሳሙኤልን ይህ ይበልጣቸዋልና ተነሥተህ ቅባው አለው። በዚያንም ጊዜ ሳሙኤል የመንግሥት ቅባት ያለበትን ቀንድ አምጥቶ በወንድሞቹ መካከል ቀባው ከዚያችም ቀን ጀምሮ ለሁል ጊዜ የእግዚአብሔር መንፈስ በዳዊት ላይ አደረበት በእስራኤል ልጆችም ላይ ነገሠ።

ደግሞ ሁለተኛ በዚች ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ሚካኤልን ወደ ዳዊት ላከው ረዓይታይ ጎልያድን እስኪገድለውና የእስራኤልን ልጆች እስከሚያድናቸው ረድቶ ኃይልን ሰጠው።

ስለዚህም የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን እናደርግ ዘንድ የቤተክርስቲያን መምህራን አዘዙን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ማቴዎስ_ወንጌላዊ

ዳግመኛም በዚችም ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የአንዱ የወንጌላዊ ማቴዎስ የዕረፍቱና የምስክርነቱ መታሰቢያ ነው። ይህም እንዲህ ነው በብዙ አገሮች ውስጥ አስተምሮ ብዙዎች ሰዎችን እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ ከመለሰ በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ወደ ካህናት አገር እንዲሔድ አዘዘው።

ተጒዞም ወደ ከተማው መግቢያ ደጅ በደረሰ ጊዜ አንድ ወጣት ብላቴና አገኘ ወደ ከተማው ለመግባት እንዴት እንደሚችል ጠየቀው ወጣቱ ብላቴናም እንዲህ ብሎ መለሰለት አንተ ግን ራስህንና ጽሕምህን ካልተላጨህ በእጅህም ዘንባባ ካልያዝክ መግባት አትችልም። ይህም ነገር ለሐዋርያ ማቴዎስ አስጨንቆት ሲያዝን አስቀድሞ ያነጋገረው ያ ወጣት ብላቴና ዳግመኛ በስሙ ጠራው። ሐዋርያውም ወዴት ታውቀኛለህ አለው እርሱም እኔ ጌታህ ኢየሱስ ነኝ አሁንም እንደ ነገርኩህ አድርግ እኔም ከአንተ ጋር አለሁ ከአንተም አልርቅም አለው።

ከዚህም በኋላ ጌታችን እንዳዘዘው አድርጎ ወደ ካህናት አገር ገባ ለአማልክት ካህናት አለቃቸው ከሆነ ከአርሚስ ጋር ተገናኘ ከእርሱም ጋር ስለ አማልክቶቻቸው ተነጋገረና ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ጣዖቶቻቸውን አቃጠላቸው እንዲህም አላቸው። ራሳቸውን ማዳን ያልቻሉ ሌላውን እንዴት ያድናሉ በዚያንም ጊዜ ከአርሚስ ጋር ብዙዎች ሰዎች አምነው አጠመቃቸው ከሰማይም ማዕድ አውርዶ መገባቸው።

የሀገሩም ንጉሥ ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ ከአርሚስ ጋር ሐዋርያውን ወደ እሳት ጨመረው ጌታችንም አዳናቸው። ከዚህም በኋላ በሚአሠቃያቸው ነገር ሲአስብ እነሆ ልጁ እንደ ሞተ ነገሩት እጅግም አዘነ። ሐዋርያ ማቴዎስም ልጅህን እንዲያስነሡት ወደ አማልክትህ ለምን አትለምንም አለው ንጉሡም የሞተ ማንሣት እንዴት አማልክት ይችላሉ ብሎ መለሰ። ቅዱስ ማቴዎስም ብታምንስ የእኛ አምላክ ልጅህን ማሥነሣት ይችላል አለው። ንጉሡም ልጄ ከተነሣ እኔ አምናለሁ አለ በዚያን ጊዜ ሐዋርያው ክብር ይገባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየና የንጉሡን ልጅ ከሞት አስነሣው።

ንጉሡም ክብር ይግባውና በጌታችን አመነ የአገር ሰዎች ሁሉም አመኑ የቀናች ሃይማኖትንም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ካህናትንም ሾመላቸው ከዚህም በኋላ ወደ ሌሎች አገሮች ሒዶ ወንጌልን አስተማረ። ከዚህም አስቀድሞ በደመና ተነጥቆ ብሔረ ብፁዓን ገብቷል ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስን ሁል ጊዜ በየበዓላቸው ወደ እነርሱ ሲመጣ አየው ከእርሱም ጋር መቶ አርባ ሽህ ሕፃናት አሉ መላእክትም ሁሉ በዙሪያው ቁመው ያመሰግኑታል።

በብሔረ ብፁዓን ስለ ሚኖሩ ወገኖችም ድንቅ ስለሆነ ሥራቸው ሁሉ ከሐዋርያው በኋላ ወደርሳቸው የገባ ዘሲማስ ቀሲስ ምስክር ሆነ። ከዚህም በኋላ የሐዋርያው የተጋድሎውና የምስክርነቱ ፍጻሜ ሲቀርብ ወደ አንዲት ከተማ ገብቶ አስተማረ ብዙዎችንም አሳመነ አገረ ገዢውም ይዞ ከወህኒ ቤት ጨመረው። በዚያም አንድ እጅግ የሚያዝን እሥረኛ አይቶ ስለኀዘኑ ጠየቀው እርሱም ብዙ የሆነ የጌታው ገንዘብ ከባሕር እንደ ሠጠመበት ነገረው ሐዋርያ ማቴዎስም ወደ ዕገሌ ባሕር ዳርቻ ሒድ ወርቅን የተመላ ከረጢትንም ታገኛለህ ያንንም ወርቅ ወስደህ ለጌታህ ስጥ አለው።

ስለዚህም ድንቅ ተአምር ብዙዎች ክብር ይግባወና በጌታችን አመኑ። መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ቅዱስ ማቴዎስንም ራሱን እንዲቆርጡ ሥጋውንም ለሰማይ ወፎች እንዲጥሉ አዘዘ። ከከተማውም አውጥተው ቈረጡት ምእመናንም በሥውር መጥተው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ድሜጥሮስ

ዳግመኛም በዚችም ቀን ንጹህ ድንግል የጠባይን ፍላጎት ድል የነሳ አባት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዐሥራ ሁለተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ድሜጥሮስ አረፈ።

ይህም አባት አስቀድሞ መጻሕፍትን ያልተማረ ሕዝባዊ ገበሬ ነው በወላጆቹ የወይን አታክልት ቦታዎች ውስጥ የሚሠራ ሆነ ከታናሽነቱም ሚስት አጋብተውት ከእርሷ ጋር አርባ ስምንት ዓመት ኖረ ድንግልናቸውን በንጽሕና የጠበቁ ናቸው የተሠወረውን ከሚያውቅ እግዚአብሔር በቀር ይህን የሚያውቅ የለም።

ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ዮልያኖስ ዕረፍቱ በቀረበ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለት ። ከእርሱ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆነውን በምልክት ገለጠለት እንዲህም አለው ነገ የወይን ዘለላ ይዞ ወደ አንተ የሚገባ ሰው አለ ከአንተ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆን እርሱ ነውና ያዘው አትተወው።

በዚያችም ቀን ድሜጥሮስ ወደ አታክልቱ ቦታ ገባ ያለ ጊዜው ያፈራ የወይን ዘለላ አገኘ ያንንም የወይን ዘለላ በረከት ሊቀበልበት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮልዮስ ይዞት ሔደ። በዚያንም ጊዜ አባ ዮልዮስ ድሜጥሮስን በእጁ ይዞ ለሕዝቡ ሁሉና ለኤጲስቆጶሳት አሳልፎ ሰጠው ከእኔ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆናችሁ ይህ ነው ስለ ርሱ ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ ነግሮኛልና ይዛችሁ ሹሙት አላቸው።
ከዚህም በኋላ አባ ዮልዮስ በአረፈ ጊዜ የጸሎቱን ሥርዓት ፈጽመዉለት ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ያን ጊዜ መንፈስ ቅዱስ መላበት የቤተ ክርስየቲያን የሆኑ የብሉያትና የሐዲሳት መጻሕፍትን አንብቦ ተረጐማቸው ብዙዎች ምሥጢራትም ተገለጡለት።

ከዚህም በኋላ ባሕረ ሐሳብ የተባለውን የዘመን መቊጠሪያ ሠራ ከእርሱ በፊት የነበሩ የክርስቲያን ወገኖች የመድኃኒታችን የጥምቀቱን በዓል ጥር ዐሥራ አንድ ቀን አክብረው በማግስቱ የከበረች አርባ ጾምን ጀምረው እስከ የካቲት ሃያ ሁለት ቀን ድረስ ይጾማሉ። ከዚያም በኋላ መጋቢት ሃያ ሁለት ቀን የሆሣዕናን በዓል አክብረው በማግስቱ የሕማማትን ሰሞን ጾም ጀምረው ይጾማሉ። ከሐዋርያትም ዘመን ጀምሮ እስከርሱ ዘመን እንዲህ እያደረጉ ኖሩ።

እርሱም እንዲህ ሠራ የከበረች የጌታችን ጾም መግቢያዋ ከሰኞ ቀን እንዳይፋለስ ፍጻሜውም በዐረብ ቀን ከዚህም የሆሣዕናን በዓል አያይዞ ሠራ በሚቀጥለው ሰኞ ቀን የሕማማት ጾም ተጀምሮ እንዲጾም የስቅለቱም በዓል ከዐርብ ቀን እንዳይፋለስ የከበረች የትንሣኤውና የጰራቅሊጦስም በዓል ከእሑድ ቀን የዕርገቱም በዓል ከሐሙስ እንዳይፋለስ።

እንዲሁም አዘጋጅቶ ለኢየሩሳሌም አገር ለሮሜ ሀገር ለኤፌሶንና ለአንጾኪያ ሀገር ሊቃነ ጳጳሳት ለየአንዳንዳቸው ላከላቸው። እነርሱም በደስታ ተቀብለው ሠሩበት እስከዚችም ቀን ጸንቶ ኖረ።

በቊርባን ቅደሴ ጊዜም ዘወትር ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያየው ሆነ። የሕዝቡ ኃጢአታቸው በፊቱ ግልጥ ሆነ ስለዚህም የማይገባቸውን ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል ይመልሳቸዋል እንዲህም ይላቸዋል ሒዱ ንስሐ ግቡ ከዚያም በኋላ መጥታችሁ ሥጋውና ደሙን ተቀበሉ ።

ሰለዚህም ነገር ብዙ ሕዝቦች ኃጢአት ከመሥራት የሚጠበቁ ሆኑ ልባቸው የደነደነ ሌሎች ግን ጠሉት እርስ በርሳቸውም እንዲህ ተባባሉ። ይህ ሰው ሚስት አግብቶ ሚስቱም ከእርሱ ጋር ትኖራለች ሳይገባውም በወንጌላዊው ማርቆስ ወንበር ተቀምጠ ከንጹሕ ድንግል በቀር አይሾምበትም ነበርና እኛንም ኃጢአተኞች ናችሁ ብሎ ይገሥጸናል።

በአንዲት ሌሊትም ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ወደርሱ መጥቶ ድሜጥሮስ ሆይ ራስህን ብቻ ማዳንን አትሻ ወገኖችህም ይጠፋ ዘንድ አትተው ነፍሱን ስለ መንጋዎቹ አሳልፎ ለሞት የሚሰጥ እርሱ ቸር ጠባቂ እንደሆነ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል የተናገረውን አስብ አለው።

ድሜጥሮስም መልአኩን ጌታዬ የምትለኝ ምንድን ነው አለው መልአኩም በአንተና በሚስትህ መካከል ተሰውሮ ያለውን ምሥጢር ለወገኖችህ ግለጽ ብሎ መለሰለት።

ከዚህም በኋላ ሕዝቡን አሰባሰባቸው ሊቀ ዲያቆኑንም ወጥተው ወደ ቤታቸው እንዳይገቡ ሕዝቡን ንገራቸው አለው ራሱም ቅዳሴውን ቀደሰ ሁለተኛም ዕንጨቶችን ሰብስበው እሳትን እንዲአነዱ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ። ያን ጊዜ ይህ አባት ተነሥቶ ከሚነደው እሳት መካከል ገብቶ ለረጅም ጊዜ ቁሞ ጸለየ ከእሳቱም ፍም አንሥቶ በሚከናነብበት ቀጸላ አደረገ ሚስቱንም ጠርቶ መጎናጸፊያሽን ዘርጊ አላት በዚያም የእሳቱን ፍም ጨመረ በእሳቱም መካከል በአንድነት እየጸለዩ ቆሙ ሕዝቡም እጅግ ያደንቁ ነበር።

ከዚህም በኋላ ካህናቱና ሕዝቡ እንዲህ ብለው ለመኑት አባታችን ሆይ ይህን የሠራኸውን ሥራ ታስረዳን ዘንድ ከቅድስናህ እንሻለን እርሱም ይህን ሥራ የሠራሁት ከንቱ ውዳሴን ሽቼ አይደለም እናንተ እኔን አምታችሁ ስለእኔ እንዳትጐዱ እንድትድኑ ከዚች ሴት ጋር በመካከላችን ተሠውሮ ያለውን ሚሥጢር እገልጽላችሁ ዘንድ የእግዚአብሔር መልአክ ስለአዘዘኝ ነው እንጂ አላቸው።

እርሷ የአባቴ የወንድሙ ልጅ ናት በሕፃንነቷም አባቷ ሞተ በአባቴም ቤት ከእኔ ጋር አደገች አካለ መጠንም በአደረሰን ጊዜ አባቴ እርሷን አጋባኝ ወደ ጫጉላ ቤትም በገባን ጊዜ እኔ እኅትህ ስሆን ለአንተ እንዴት አጋቡኝ አለችኝ። እኔም የምትፈቅጂ ከሆነ ድንግልናችንን ጠብቀን በአንድነት እንኑር ይህንንም በመካከላችን ያለውን ምሥጢር የሚያውቅ አይኑር አልኋት በዚህም ተስማምተን በአንድ ቤት ውስጥ በአንድ ዐልጋ እየተኛን አንድ መጐናጸፊያንም እየተጐናጸፍን አርባ ስምንት ዓመት ያህል ኖርን ይህን ሥራችንንም ያለ እግዚአብሔር የሚያውቅ የለም እኔም እርሷ ሴት እንደ ሆነች አላወቅኋትም እርሷም እኔን ወንድ እንደሆንኩ አታውቅም በየሌሊቱም ሁሉ በንስር አምሳል ወደ መኝታችን እየገባ ክንፎቹን አልብሶን ያድራል ሲነጋም ከእኛ ይሠወራል አላቸው።

በዚያንም ጊዜ በደላቸውን ይቅር ይላቸው ዘንድ ከእግሩ ሥር ወድቀው ለመኑት እርሱም ይቅር አላቸው አጽናናቸውም። ይህንንም ድንቅ ሥራ ያዩ ሁሉ ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት።

በዚህ አባት ዘመንም ስማቸው ቀሌምንጦስ አርጌንስ የሚባሉ ሌሎችም መናፍቃን ስዎች ተነሥተው ታዩ ሌሎችም በአንድነት ሁነው ስለሃይማኖት የፈጠራ መጽሐፍን ጻፉ እርሱም አውግዞ ከምእመናን ለያቸው።

እርሱም ሁል ጊዜ ያለ ዕረፍት ከጥዋት እስከ ማታ ምእመናንን የሚያስተምራቸው ሆነ። ሸምግሎ በደከመም ጊዜ በዐልጋ ላይ አስቀምጠው ተሸክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ያደርሱታል እስከማታ ድረስም ያስተምራቸዋል ሰዎችም ሁሉ ትምህርቱን ይሰሙ ዘንድ ይጨናነቃሉ መላ የሕይወቱ ዘመንም መቶ ሰባት ነው በሰላም በፍቅር አንድነትም አረፈ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_13

ጥቅምት አስራ ሦስት በዚችም ዕለት የዓለሙ ሁሉ መምህር የሆነ የከበረ አባት #ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ መታሰቢያው ነው፤ #የመነኰስ_ቅዱስ_ዘካርያስም የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

ጥቅምት አስራ ሦስት በዚችም ዕለት የዓለሙ ሁሉ መምህር የሆነ የከበረ አባት ዮሐንስ አፈወርቅ መታሰቢያው እንደሆነ ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል።

ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ሰዎች ወገን ነው የአባቱም ስም አስፋኒዶስ የእናቱም ስም አትናሲያ ነው እሊህም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህንንም ልጃቸውን በመልካም አስተዳደግ አሳደጉት ትምህርትንና ጥበብንም ሁሉ አስተማሩት እርሱ ወደ አቴና ሔዶ በመምህራን ቤት ተቀምጦ ትምህርትን ሁሉ ተምሮ በዕውቀቱ ከብዙዎች በላይ ከፍ ከፍ ብሏልና።

ከዚህም በኋላ ገና በታናሽነቱ መነኰሰ የዚህንም የኃላፊውን ዓለም ጣዕም ንቆ ተወ ከእርሱም ቀድሞ በዚሁ ገዳም ቅዱስ ባስልዮስ መንኵሶ ነበር በአንድነትም ተስማምተው ብዙ ትሩፋትን ሠሩ ወላጆቹም በሞቱ ጊዜ ከተውለት
ገንዘብ ምንም ምን አልወሰደም ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ እንጂ ከዚያም በምንኵስና ሥራ በመጠመድ ፍጹም ገድልን እየተጋደለ ኖረ።

በዚያም ገዳም ሶርያዊ ጻድቅ ሰው ስሙ ሲሲኮስ የሚባል መነኰስ ነበረ እርሱም ወደፊት የሚሆነውን በመንፈስ ቅዱስ ያይ ነበር በአንዲት ሌሊትም ለጸሎት እየተጋ ሳለ ሐዋርያትን ጴጥሮስንና ዮሐንስን አያቸው ወደ ዮሐንስ አፈወርቅ ገብተው ጴጥሮስ መክፈቻ ሰጠው ወንጌላዊ ዮሐንስም ወንጌልን ሰጠው እንዲህም አሉት በምድር ያሠርከው በሰማይ የታሠረ ይሆናል በምድርም የፈታኸው ደግሞ በሰማያት የተፈታ ይሆናልና በውስጥህ መንፈስ ቅዱስ ያደረብህ አዲስ ዳንኤል ሆይ የክብር ባለቤት ከሆነ ከታለቅ መምህር ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ወደ አንተ ተልከናልና ዕወቅ እኔም የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻ የተሰጠኝ ጴጥሮስ ነኝ።

ሁለተኛውም እኔም በመጀመሪያው ስብከቴ በከበረ ወንጌል ቃል አስቀድሞ ነበረ ያልኩ ይህም ቃል በጠላት ላይ የእሳት ሰይፍ የሆነ ዮሐንስ ነኝ። ለአንተም ከክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ወገኖችህ ምእመናንን በቀናች ሃይማኖት ታሳድጋቸው ዘንድ ዕውነተኛ አእምሮ ደግሞ ተሰጥቶሃል።

ጻድቅ ሲሲኮስም ይህን ራእይ በአየ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ቸር ታማኝ እረኛ ሁኖ እንደሚሾም ዐወቀ። ከዚህም በኋላ በቅዱስ ዮሐንስ ላይ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በላዩ ወርዶ አደረበትና ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ ዲያቆን ሁኖ ሳለም የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ብሉያትንና ሐዲሳትን ተረጐመ። በአንዲት ሌሊትም ቅዱስ ዮሐንስ ሲጸልይ የእግዚአብሔር መልአክ በድንገት እንደ በረድ ነጭ በሆነ ልብስ ተገለጠለት ቅዱስ ዮሐንስም ሲያየው ደንግጦ በምድር ላይ ወደቀ መልአኩም አርአያውን ለውጦ እንደ ሰው ሁኖ ታየው ወዳጄ አዲስ ዳንኤል ሆይ አትፍራ ተነሣ አለው የቅዱስ ዮሐንስም ልቡ ተጽናንቶ ጌታዬ አንተ ማነህ ግርማህ አስፈርቶኛልና አለው የእግዚአብሔር መልአክም ትሠራው ዘንድ የሚገባህን ልነግርህ ወዳንተ የተላክሁ ነኝ።

አሁንም እግዚአብሔር አምላክ ያዘዘህን ለመሥራት ልብህን አበርታ ቃልህ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ በአራቱ ማእዘን ይደርሳልና እልፍ አእላፋትም ትምህርትህን ተቀብለው ትእዛዝህን ሰምተው ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር ተመልሰው ይድናሉና በእግዚአብሔር መንግሥትም ውስጥ የጸና የብርሃን ዐምድ ትሆናለህና። እነሆ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አንተ ይመጣል ከእርሱም ጋራ ሁሉም ካህናትና ዲያቆናት በየማዕረጋቸው የሚያዝህንም አድርግ የእግዚአብሐር ትእዛዝ ነውና ልትተላለፍ አይገባህም አለው። ከዚህም በኋላ ያ መልአክ ለአባ ፊላትያኖስ ተገልጦ ቅዱስ ዮሐንስን ቅስና እንዲሾመው አዘዘው በማግሥቱም ሊቀ
ጳጳሳቱ መጣ ከርሱ ጋራም ካህናት አሉ ይህን ቅዱስ ዮሐንስንም ይዞ ቅስና ሾመው።

የቍስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳትም በአረፈ ጊዜ ንጉሥ አርቃድዮስ ልኮ አስመጥቶ ቅዱስ ዮሐንስን በቍስጥንጥንያ ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾመው አባቶቻችን ሐዋርያት እንደሚያደርጉት በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ላይ ጸና ሕይወትነት በአላቸው ትምህርቶችና ተግሣጾች ሕዝቡን ሁልጊዜ የሚአስተምር ሆነ። ከኤጲስቆጶሳትም ሆነ ከመንግሥት ወገን ሕግን የሚተላለፉትን ሁሉ ይገሥጻቸዋል ማንንም አይፈራም ፊት አይቶም አያደላም።

የንጉሥ አርቃድዮስ ሚስት አውዶክስያም ገንዘብ ወዳጅ ስለሆነች የአንዲት ድኃ መበለት ቦታዋን በግፍ ወሰደች ያቺ መበለትም ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥታ ንግሥት አውዶክስያ ቦታዋን እንደነጠቀቻት ነገረችው እርሱም የደኃዋን ቦታዋን መልሺላት ብሎ ከብዙ ምክር ጋር እንድትመልስላት ንግሥት አውዶክስያን ለመናት እርሷ ግን እምቢ በማለት አልታዘዘችለትም። ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብታ ሥጋውን ደሙን እንዳትቀበል አውግዞ ለያት።

ቍጣንና ብስጭትንም ተመልታ ስለ ክፉ ሥራቸው ከሹመታቸው እርሱ የሻራቸውን ኤጲስቆጶሳት ሰበሰበች እነርሱም ንግሥቲቱን ስለ ተቃወመ ስደት እንደሚገባው በእርሱ ላይ ተስማምተው ጻፉ እርሷም አጥራክያ ወደ ሚባል ደሴት ሰደደችው።

ከዚያም በደረሰ ጊዜ የዚያች ደሴት ሰዎች በክፉ ሥራ ጸንተው የሚኖሩ ከሃድያን ሁነው አገኛቸው ቅዱስ ዮሐንስም አስተማራቸው ገሠጻቸውም በፊታቸው ስለ አደረጋቸው ድንቆች ተአምራት ወደ ቀናች ሃይማኖት አስገባቸው።

የሮሜ ንጉሥ አኖሬዎስና ሊቀ ጳጳሳቱ ዮናክኒዶስ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ስደት በሰሙ ጊዜ እጅግ አዘኑ በንጉሥ አርቃድዮስ ላይም በመቆጣት እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጽፈው ላኩ ከዚህ ከክፉ ሥራ ተጠበቅ ትእዛዛችንንም ተቀብለህ የከበረ
ዮሐንስን ከስደቱ ከአልመለስከው በአንተና በእኛ መካከል ሰላም አይኖርም። መልእክታቸውንም በአነበበ ጊዜ እጅግ አዘነ ሚስቱንም አግዶ ልኮ ቅዱስ ዮሐንስን ከስደቱ መለሰው በተመለሰ ጊዜም የቍስጥንጥንያ ሰዎች በመመለሱ ታላቅ ደስታ አደረጉ። ከጥቂት ቀኖች በኋላም ንግሥቲቱ ወደ ክፋቷ ተመልሳ ሁለተኛ ወደ አጥራክያ ደሴት ሰደደችውና በዚያው አረፈ።

ንጉሥ አኖሬዎስና ሊቀ ጳጳሳት ዮናክኒዶስም በሰሙ ጊዜ መልእክትን ላኩ ሊቀ ጳጳሳቱም የከበረ ዮሐንስን ከስደቱ እስከምትመልሰው ድረስ ሥጋውንና ደሙን እንዳትቀበል አውዶክስያን አወገዛት። ከዚህም በኋላ የከበረ ዮሐንስን ይመልሱት ዘንድ ንጉሥ ላከ ግን ሙቶ አገኙት ሥጋውንም ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ አደረሱት። የከበረ ዮሐንስም በተሰደደበት አገር እንደአረፈና ሥጋውንም ወደ ቍስጥንጥንያ ከተማ እንዳመጡ ወደ አባ ዮናክኒዶስ መልእክት ጽፈው አስረዱት። ሁለተኛም የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብታ ሥጋውንና ደሙን እንዳትቀበል ልኮ አውድክስያን አወገዛት እየለመነችውም ስምንት ወር ያህል ኖረች በብዙ ልመናም ፈታት።

ነገር ግን ጭንቅ በሆነ ደዌ እግዚአብሔር አሠቃያት ያድኗት ዘንድ ገንዘቧን ለባለ መድኃኒቶች ጥበበኞች እስከ ሰጠች ድረስ ግን አልዳነችም ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መቃብርም ሔዳ በእርሱ ላይ ያደረገችውን በደል ይቅር ይላት ዘንድ እየሰገደችና እያለቀሰች ለመነችው እርሱም ይቅር አላት ከደዌዋም ፈወሳት። ጌታችንም ከሥጋው ታላላቅ ድንቆች ታአምራትን ገለጠ።
ስለርሱም እንዲህ ተባለ በአንዲት ዕለትም ከንጉሥ አርቃዴዎስ ጋር ተቀምጦ ሳለ ንጉሡ እንዲህ አለው አባቴ ሆይ ስለ አንድ ቃል እንድታስረዳኝ እለምንሃለሁ። ይህም ቃል ከብዙ ጊዜ ጀምሮ በልቤ ውስጥ ይመላለሳል ወንጌላዊ ማቴዎስ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምን የበኵር ልጅዋን እስከ ወለደች ድረስ ዮሴፍ አላወቃትም ስለምን አለ ወንዶች ሴቶችን እንደሚአውቋቸው ዮሴፍ አወቃትን አለው።

የከበረ ዮሐንስም ንጉሥ ሆይ እንዲህ አትበል እንዲህ አንተ እንደምትለው አይደለም የከበረች ድንግል እመቤታችንስ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሆድዋ ውስጥ በነበረ ጊዜ የእርሱ ኅብረ መልክ በሚለዋወጥ ጊዜ ከእርሱ ጋር መልኳ ይለወዋወጥ ነበር። በንጹሕ ብርሌ ውስጥ ውኃ በጨመሩ ጊዜ ውኃ መስሎ እንደሚታይ ወይን ጠጅም ቢጨምሩ ያንኑ መስሎ እንደሚታይ ወይም ከውስጡ በተጨመረው ቀይም ቢሆን ቀልቶ እንደሚታይ ቅጠልያም ቢገባበት ቅጠልያ መስሎ እንደሚታይ። ድንግልም በሆድዋ ውስጥ የልጅዋ መልክ በሚለዋወጥ ጊዜ ከእርሱ ጋራ መልኳ ይለዋወጥ ነበር። እንደ ሮማን አበባ የምትቀላበት ጊዜ አለ እንደ ናርዶስም የምታብለጨልጭበት ጊዜ አለ የለመለመ ቅጠል የምትመስልበትም ጊዜ አለ ከወለደች በኋላ ግን አልተለወጠችምና ዮሴፍ በአንድ በቀድሞው ኅብረ መልኳ ተወስናለት መልኳን ተረዳ ማለት ነው አለው። በዚያን ጊዜ በንጉሥ አዳራሽ ውስጥ ከወርቅ የተሠራ የእመቤታችን አምላክን የወለደች የድንግል ማርያም ሥዕል ነበረችና አፈ ወርቅ ዮሐንስ ልሳነ ወርቅ ዮሐንስ አፈ በረከት ዮሐንስ መልካም ተናገርክ የሚል ቃል ከእርሷ ወጣ።

ንጉሡና ከእርሱ ጋር ያሉት በሰሙ ጊዜ እጅግ አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት በዚያን ጊዜ ንጉሥ አዝዞ ወርቅ ሠሪ አስመጥቶ ለከበረ ዮሐንስ የወርቅ ልሳን አሠርቶ ለሚያየው ሁሉ መታሰቢያ ምልክት ሊሆን አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም ሥዕል ዘንድ ሰቀለው። ቅዱስ ዮሐንስንም ከዚያች ቀን ወዲህ ልሳነ ወርቅ ብሎ ጠራው አፈ ወርቅም ተብሎ እስከዛሬ ተጠራ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#መነኮስ_ቅዱስ_ዘካርያስ

ዳግመኛም በዚችም ቀን ደግሞ የመነኰስ ዘካርያስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። የዚህም መስተጋድል የአባቱ ስም አቃርዮስ ነው። ይህም አቃርዮስ የምንኲስና ልብስ ሊለብስ ሽቶ ለሚስቱ ነገራት እርሷም በነገራት ነገር ተስማማች። ወንድና ሴት ሁለት ልጆች አሉአቸው እነርሱንም ከእናታቸው ዘንድ ትቶ እርሱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዶ ከአንድ አረጋዊ አባት መነኰስ ዘንድ በዚያ መነኰሰ።

ከጥቂት ወራትም በኋላ በሀገር ውስጥ ረኃብ ሆነ ሚስቱም ልጆቿን ይዛ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወደባሏ አቃርዮስ መጣች በረኃብም ስለ ሆነው ችግር ነገረችው አቃርዮስም እነሆ እግዚአብሔር በመካከላችን ፍርድን አድርጎ ልጆቻችንን አካፈለን እኔም ወንዱን ልጄን እወስዳለሁ አንቺም ሴት ልጅሽን ውሰጂ አላት ይህንንም ብሎ ልጁን ወሰደ ይኸውም ዘካርያስ ነው እርሷም ሴቷን ልጅዋን ይዛ ተመለሰች።

ከዚህም በኋላ ልጁን ዘካርያስን ወደ ቅዱሳን አረጋውያን አቀረበው እነርሱም በላዩ ጸለዩ ባረኩትም እርሱ ፍጹም መነኲሴ እንደሚሆንም ትንቢት ተናገሩለት።

ዘካርያስም ከበጎ ሥራ ጋር በገዳም ውስጥ አደገ መልኩም እጅግ ያማረ ነው ስለርሱም ጉርምርምታ ሆነ መነኰሳቱም እርስበርሳቸው ይህ ወጣት ይህን ያህል እጅግ መልከ መልካም ሲሆን በገዳም ውስጥ በመነኰሳት መካከል እንዴት ይኖራል ተባባሉ።

ዘካርያስም ስለርሱ መነኰሳት እንዳንጐራጐሩ በሰማ ጊዜ ናጥራን ወደሚባል ተራራ ስር ወደአለች ዐዘቅት ሔደ ልብሱንም አውልቆ በረግረግ ውስጥ ተኛ ሥጋውም ተነፋፍቶ ጠቆረ ተመላልጦም ቈሰለ ብዙ ዘመንም በደዌ እንደኖረ ሆነ፤ ከዚህም በኋላ ልብሱን ለብሶ ወደ ገዳም መጣ ያወቀውም የለም። ከብዙ ቀኖችም በኋላ አባቱ አስተውሎ ልጁ ዘካርያስ እንደ ሆነ አወቀውና መልክህን የለወጠው ምንድን ነው ብሎ ጠየቀው አርሱም ያደረገውን ሁሉ ነገረው።

በእሑድ ቀንም ሥጋውንና ደሙን ሊቀበል ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ እግዚአብሔርም ያን ጊዜ ሥራውን ለአባ ኤስድሮስ ገለጸለት እርሱም ዘካርያስ የሠራውን ለወንድሞች መነኰሳት አስረዳቸው እነርሱም አስቀድሞ እንደ ሰው ሁነህ መጣህ ዛሬ ግን እንደ እግዚአብሔር መልአክ ሁነህ መጣህ አሉት።

ይህ አባት ዘካርያስም በብዙ ገድል ሲጋደል ኖረ ትሕትናን ቅንነትን ያማረ የትሩፋትን ሥራ ሁሉ ገንዘብ አደረገ አባቱም ስለርሱ እኔ በገድል ብዙ ደክሜአለሁ ነገር ግን ከልጄ ሥርዓተ ገድል አልደረስኩም ብሎ ተናገረ።

በዚህ ተጋድሎውም አርባ አምስት ዓመት ኑሮ እግዚአብሔርን ከአገለገለው በኋላ በፍቅር አንድነት አረፈ መላ ዘመኑም ሃምሳ ሁለት ነው። ከዚህም ሰባቱን ዓመት በወላጆቹ ቤት አርባ አምስቱን በገዳም ኖረ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳስ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_15

ጥቅምት ዐሥራ አምስት በዚች ቀን #ቅዱሳን_ሐዋርያት ዓለምን በእጣ ለ12 የተካፋፈሉበት እና ከኒቆምድያ አገር #ቅዱስ_ቢላሞን በሰማዕትነት ያረፈበት ቀን ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#12ቱ_ቅዱሳን_ሐዋርያት

ጥቅምት ዐሥራ አምስት በዚች ቀን ቅዱሳን ሐዋርያት ዓለምን በእጣ ለ12 የተካፋፈሉበት ዕለት ነው። በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከእመቤታችን በቀር ከቅዱሳን ሐዋርያት የሚበልጥ አልተነሳም። "ሐዋርያ" ማለት "ፍንው፣ ልዑክ፣ የተላከ፣ የጽድቅ መንገደኛ" እንደ ማለት ነው። በምሥጢሩ ግን "ባለሟል" ብለው ሊቃውንቱ ተርጉመውታል።

ይህስ እንደምን ነው ቢሉ:-

የፍጥረታት ሁሉ ጌታ የክብር ባለቤት መድኃኔዓለም ከድንግል ማርያም ተወልዶ፣ አድጐ፣ ተጠምቆ፣ ጾሞ ከገዳመ ቆረንቶስ ሲመለስ ቀዳሚ ሥራው ያደረገው ደቀ መዛሙርቱን መጥራት ነበር::

ከተከተሉት የ5 ገበያ ሕዝብ መካከል "ወሐረየ እምሰብአ ዚአሁ አሠርተ ወክልኤተ ሐዋርያተ" እንዲል በመጀመሪያ 12ቱን ሐዋርያት መረጠ። እሊህም:- #ዼጥሮስ የተባለ ስምኦን፣ #እንድርያስ (ወንድሙ)፣ #ያዕቆብ ወልደ ዘብዴዎስ፣ #ዮሐንስ (ወንድሙ)፣ #ፊልዾስ#በርተሎሜዎስ#ቶማስ#ማቴዎስ#ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ፣ #ታዴዎስ (ልብድዮስ)፣ #ናትናኤል (ቀናተኛው ስምዖን) እና #ማትያስ (በይሁዳ የተተካው) ናቸው። (ማቴ. 10፥1)

እነዚህን 12 አርድእቱን ከጠራ በሁዋላ ለ3 ዓመታት ከ3 ወራት ከዋለበት ሲማሩ ይውሉ ነበር። ሌሊት ደግሞ ምሥጢር ሲያስተረጉሙ ያድሩ ነበር።

ጌታ እንደሚገባ ካስተማራቸው በሁዋላ ከፍ ያለ ኃላፊነትን ሾማቸው። ለዓለም እረኞች የእርሱም ባለሟሎች ሆኑ። እጅግ ብዙ መከራ እንደሚገጥማቸው ነገራቸው። (ማቴ.10፥16, ዮሐ.16፥33) በዚያው ልክ ክብራቸውንም አከለላቸው። (ማቴ. 19፥28) ሥልጣንም "በምድር ያሠራችሁት በሰማይ የታሰረ ይሆናል፤ በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ይሆናል።" (ማቴ. 18፥18) "ይቅር ያላችኋቸው ኃጢአታቸው ይቀርላቸዋል፤ ያላላችኋቸው ግን አይቀርላቸውም።" (ዮሐ.20፥23) ብሎ ሰጣቸው።

የመንግስተ ሰማያትን መክፈቻ (ማቴ. 16፥19)፣ እረኝነትን (ዮሐ. 21፥15) ተቀበሉ። ጌታ በንጹሕ አንደበቱ ሐዋርያቱን እጅግ ሲያከብራቸው "ጨው፣ የዓለም ብርሃናት" (ማቴ. 5፥13) አላቸው። ወንድሞቹም ተባሉ። (ዮሐ.7፥5) ከዚህም በሚበልጥ በሌላ ክብር አከበራቸው።

ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላ በጌታ ሕማማት ጊዜ ገና ነበሩና አንዳንዶቹ ፈርተው ተበተኑ። ተመልሰው ግን በጽርሐ ጽዮን ሲጸልዩ ሰንብተው የጌታን ትንሳኤ ተመለከቱ። እጆቹን፣ እግሮቹንም ዳስሰው ሐሴትን አደረጉ።

ለ40 ቀናት መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትምሕርተ ኅቡዓት፣ ሌላም በፍጡር አንደበት የማይነገር ብዙ ምሥጢራትን ተምረው ጌታ ሊቀ ጵጵስናን ሹሟቸው ዐረገ።

ለ10 ቀናት በእመብርሃን ሥር ተጠልለው ሲጸልዩና በአንድ ልብ ሲተጉ ሰንብተው መንፈስ ቅዱስ ወረደላቸው። በአንዴም ከፍርሃት ወደ ድፍረት ተመልሰው ፍጹማን ብርሃናውያን ሆኑ። 71 ልሳናትን ነስተው በአንዲት ስብከት ብቻ 3ሺ ነፍሳትን ማረኩ። (ሐዋ.2፥41)

ቅዱሳን ሐዋርያት በኅብረት ለአንድ ዓመት ያህል በኢየሩሳሌምና በዙሪያዋ እየተመላለሱ አስተምረው ብዙ እሥራኤላውያንን ወደ ክርስትና ማርከዋል። ከዚህ በኋላ ግን እንደ ትውፊቱ በዚህች ቀን ዓለምን በእጣ ለ12 ተካፈሏት።

ይህ ሲሆን መንፈስ ቅዱስ አብሯቸው ነበርና ለእያንዳንዳቸው እንደሚገባቸው አሕጉረ ስብከቶች ደረሷቸው። እነርሱም ደቀ መዛሙርቶቻቸውን አስከትለው ለታላቁ መንፈሳዊ ዘመቻ ወረዱ።

በሔዱበት ቦታም ከተኩላ፣ ከአንበሳና ከነምር ጋር ታገሉ። በጸጋቸውም አራዊትን (ክፉ ሰዎችን) ወደ በግነት መልሰው ለክርስቶስ አስረከቡ። በየሃገሩ እየሰበኩ ድውያንን ፈወሱ፣ ለምጻሞችን አነጹ፣ እውራንን አበሩ፣ አንካሶችን አረቱ፣ ጐባጦችን አቀኑ፣ ሙታንንም አስነሱ፣ እልፍ አእላፍ አሕዛብንም ወደ መንጋው ቀላቀሉ።

ስለዚህ ፈንታም ብዙዎቹ በእሳት ተቃጠሉ፣ ቆዳቸው ተገፈፈ፣ በምጣድ ተጠበሱ፣ ደማቸው በምድር ላይ ፈሰሰ፣ ከአንድ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በቀር ሁሉም ይህችን ዓለም በሰማዕትነት ተሰናበቱ። ጨው ሆነው አጣፍጠዋልና ብርሃንም ሆነው አብርተዋልና እናከብራቸዋለን። "አባቶቻችን፣ መምሕሮቻችን፣ ጌቶቻችንና ሊቆቻችን" እንላቸዋለን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቢላሞን

ዳግመኛም በዚች ቀን ከኒቆምድያ አገር ቅዱስ ቢላሞን በሰማዕትነት አረፈ።

የዚህም ቅዱስ አባቱ ጣዖት አምላኪ ነው እናቱ ግን ክርስቲያን ናት ጥበብንም አስተማሩት ከዚህም በኋላ ስሙ አርማላስ ከሚባል ቄስ ጋር ተገናኘ። እርሱም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የቀናች ሃይማኖት አስተማረው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቀው ታላቅ የሆኑ ድንቆች ታምራትን የማድረግ ሀብትን እግዚአብሔር እስከ ሰጠው ድረስ በጾም በጸሎት ታላቅ ገድልን ተጋደለ።

በአንዲት ቀንም ለዓይኖቹ መድኃኒትን እንዲአደርግለት አንድ ዕውር ሰው ወደርሱ መጣ ቅዱስ ቢላሞንም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያለ በዕውሩ ዐይኖች ላይ የመስቀልን ምልክት አደረገ ያን ጊዜ ዐይኖቹ ድነው አየባቸው ጤነኛም ሆነ።

ንጉሥም ዐይኖቹ የተገለጡለትን የዚያን ዕውር ዜና በሰማ ጊዜ ወደርሱ አስቀረበውና ዐይኖችህን ማን አዳነህ ብሎ ጠየቀው እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት ቅዱስ ቢላሞን ፈወሰኝ እርሱ እጁን በዐይኖቼ ላይ አድርጎ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ እያለ በመስቀል ምልክት አማተበብኝ ያን ጊዜ አየሁ ይህንንም ብሎ እኔ ክርስቲያን ነኝ እያለ በንጉሡ ፊት በግልጽ ጮኸ።ንጉሡም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡት የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

ከዚህም በኋላ ወታደር ልኮ ቅዱስ ቢላሞንን አስቀረበው ስለ ሃይማኖቱም በጠየቀው ጊዜ እርሱም ክርስቲያን ነኝ ብሎ በፊቱ ታመነ ንጉሡም ብዙ ሽንገላን በመሸንገል አባበለው። ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት ባልሰማውም ጊዜ በእርሱ ላይ ተቆጥቶ ድምፁን ከፍ አድርጎ ካልሰማኸኝ እኔ ጽኑ ሥቃይን አሠቃይሃለሁ አለው። ቅዱስ ቢላሞንም እኔ ከሥቃይህ የተነሣ ፈርቼ ሃይማኖቴን ለውጬ ፈጣሪዬን አልክድም አለው።

ከዚያችም ቀን ጀምሮ በብዙ አይነት ሥቃይ በብዙ ቀኖች ውስጥ ማሠቃየትን ጀመረ። በግርፋት በስቃላትም በባሕር ስጥመትም ወደ እሳት በመወርወርም የሚያሠቃይበት ጊዜ አለ።

በዚህም ሥቃይ ውስጥ ሳለ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጠመቀው ቄስ በአርሜላዎስ አምሳል ተገልጾለት እንዲህ የሚል የደስታ ቃል አሰማው። የመረጥኩህ ቢላሞን ሆይ ደስ ይበልህ እኔ ሰማያዊ መንግሥትን አዘጋጅቼልሃለሁና።

የንጉሡ ጭፍሮችም ይህን የደስታ ቃል ሰሙ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው እነርሱ በሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ የአመኑ መሆናቸውን በንጉሡ ፊት ገለጡ በዚያንም ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ ንጉሡ አዘዘ። ቅዱስ ቢላሞንንም እንዲቆርጡት አዘዘ ከእሊህ ጭፍሮች ጋርም እንዲህ ገድሉን ፈጸመ ቁጥራቸውም መቶ ኀምሣ ስምንት ነው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ጥቅምት_16

#ቅዱስ_አባ_ያቃቱ

ጥቅምት ዐሥራ ስድስት በዚች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ዘጠነኛ የሆነ ቅዱስ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ያቃቱ አረፈ።

ከርሱ በፊት የነበረ አባ ብንያሚን በአረፈ ጊዜ ይህን አባት መርጠው በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት በዘመኑም ብዙ ችግር ደርሶበታል ስሙ ቴዎዶስዮስ የሚባል አንድ መለካዊ ሰው ነበረ እርሱም ወደ ደማስቆ ንጉሥ ወደ ዘይድ ሒዶ ብዙ እጅ መንሻ ሰጥቶ ለእስክንድርያ አገረ ገዥ ሁኖ ተሾመ።

ይህንንም አባት አባ ያቃቱን ሊአስጨንቀው ጀመረ በየዓመቱ ግብር ሰባት ሺህ የወርቅ ዲናር ከእርሱ እስከተቀበለ ድረስ እግዚአብሔርም እስከ አጠፋው ድረስ ይህን አባት እንዲህ አሠቃየው።

በዘመኑም የብዙዎች ቅዱሳን አባቶች አባት የሆነ የአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ሕንፃዋ ተፈጸመ።

በአንዲት ሌሊትም ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለዚህ አባት ተገለጸለት ፍዩም በሚባል አገር በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግል ዮሐንስ የሚባል ጻድቅ ሰው መነኰስ እንዳለ ነገረው። ሕዝብን በማስተማርና በመምከርም ይረዳው ዘንድ መልእክተኞችን ልኮ እንዲአስመጣውም አዘዘው ሁለተኛም ከእርሱ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት እንደሚሆን ገለጠለት።

በዚያንም ጊዜ መልእክተኞችን ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሥራውንም ሁሉ አስረከበው ይህንንም አባት ከብዙ ድካም የሚያሳርፈው ሆነ በሹመቱ ወንበር ዐሥራ ዘጠኝ ዓመት ኑሮ ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_17

ጥቅምት አስራ ሰባት በዚችም ዕለት የዲያቆናት አለቃ #ቅዱስ_እስጢፋኖስ ለተሾመባት ቀን መታሰቢያ ነው፣ የታላቁ ነቢይና ካህን ሳሙኤል እናት #ቅድስት_ነቢይት_ሐና የተወለደችበት ነው፣ ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ፊልያስ በሰማዕትነት ያረፈበት ነው፣ የከበረ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘኑሲስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ_ካልዕ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቀዳሜ_ሰማዕት_ቅዱስ_እስጢፋኖስ

ጥቅምት አስራ ሰባት በዚችም ዕለት የዲያቆናት አለቃ የሰማዕታት መጀመሪያ የሆነ የከበረ እስጢፋኖስ ለተሾመባት ቀን መታሰቢያ ናት።

ለዚህም ለከበረ እስጢፋኖስ የእግዚአብሔርን ኃይልና ጸጋ የተመላ ሰው እንደነበረና በሕዝቡም መካከል ታላላቅ ተአምራትንና ድንቅ ሥራን ይሠራ እንደነበረ የሐዋርያት ሥራ የተባለ መጽሐፍ ስለርሱ ምስክር ሆነ።

ከዚህም በኋላ አይሁድ ቀኑበት የሐሰት ምስክሮች የሚሆኑ ሰዎችንም አስነሡበት ይህን ሰው በሙሴና በእግዚአብሔር ላይ የስድብ ቃልን ሲናገር ሰምተነዋል እንዲሉ ሐሰትን አስተማሩአቸው። ሕዝቡንና ሽማግሌዎችን ጸሐፊዎችንም አነሣሡአቸው አዳርሱን ብለው ከበው እየጐተቱ ወደ ሸንጎ ወሰዱት።

የሐሰት ምስክሮችንም አቆሙበት እነርሱም ይህ ሰው በቤተ መቅደስ ላይ በኦሪትም ላይ ስድብን ሲናገር ተው ብንለው እምቢ አለ። የናዝሬቱ ኢየሱስ ቤተ መቅደሳችሁን ያፈርሰዋል ሙሴ የሰጣችሁን ኦሪታችሁንም ይሽራል ሲል ሰምተነዋል አሉ።

በአደባባይ ተቀምጠው የነበሩት ሁሉ ተመለከቱት ፊቱንም የእግዚአብሔርን መልአክ ፊት ሁኖ አዩት። ሊቀ ካህናቱም እውነት ነውን እንዲህ አልክ አለው። እርሱም እንዲህ አለ ወንድሞቻችንና አባቶቻችን ስሙ ወደ ካራን ከመምጣቱ አስቀድሞ በሶርያ ወንዞች መካከል ሳለ ለአባታችን ለአብርሃም የክብር ባለቤት እግዚአብሔር ተገለጠለት። ካገርህ ውጣ ከዘመዶችህም ተለይ እኔ ወደማሳይህ ሀገርም ና አለው።

ከዚህም በኋላ ከከላውዴዎን ወጥቶ በካራን ተቀመጠ አባቱም ከሞተ በኋላ ዛሬ እናንተ ወደ አላችሁባት ወደዚች አገር አመጣው። ከዚህም በኋላ የግዝረትን ሥርዓት ሰጠው ይስሐቅንም በወለደው ጊዜ በስምንተኛው ቀን ገዘረው እንዲሁ ይስሐቅም ያዕቆብን ገዘረው ያዕቆብም ዐሥራ ሁለቱን ነገድ አባቶችን ገዘረ።

የቀደሙ አባቶቻችንም በዮሴፍ ላይ ቀንተው ወደ ግብጽ አገር ሸጡት እግዚአብሔር ግን አብሮት ነበር። ከመከራው ሁሉ አዳነው በግብጽ ንጉሥ በፈርዖን ፊትም ዕውቀትን መወደድን ሰጠው በግብጽ አገር ሁሉና በቤቱ ሁሉ ላይ ሾመው። ነገርም በማስረዘም በሰሎሞን እጅ እስከተሠራችው ቤተ መቅደስ ያለውን ተረከላቸው።

ከዚህም በኋላ ድምፁን ከፍ ከፍ አድርጎ እናንተም እንደ አባቶቻችሁ ዘወትር መንፈስ ቅዱስን የምታሳዝኑት ዐይነ ልቡናችሁ የታወረ ዕዝነ ልቡናችሁ የደነቈረ አንገተ ደንዳኖች አላቸው። አባቶቻችሁ ከነቢያት ያላሳደዱት ያልገደሉት ማን አለ እናንተ ክዳችሁ የገደላችሁትን የአምላክን መምጣት አስቀድመው የነገሩዋችሁን ገደላችኋቸው።

በመላእክት ሥርዓት ኦሪትን ተቀብላችሁ አልጠበቃችሁም። ይህንንም ሰምተው ተበሳጩ ልባቸውም ተናደደ ተነሣሣ ጥርሳቸውንም አፋጩበት። በእስጢፋኖስም መንፈስ ቅዱስ አደረበት ሰማይም ተከፍቶ ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ የእግዚአብሔርን ክብር አየ። እነሆ ሰማይ ተከፍቶ የሰው ልጅም በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ አያለሁ አለ።

ጆሮአቸውን ይዘው በታላቅ ድምፅ ጮኹ በአንድነትም ከበው ጐተቱት። እየጐተቱም ከከተማ ወደ ውጭ አውጥተው በደንጊያ ወግረው ገደሉት የገደሉትም ሰዎች ልብሳቸውን ሳውል ለሚባል ጐልማሳ ልጅ ያስጠብቁ ነበር። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ነፍሴን ተቀበል እያለ ሲጸልይ እስጢፋኖስን በደንጊያ ወገሩት።

ዘለፍለፍ ባለ ጊዜም ድምፁን ከፍ አድርጎ አቤቱ ይህን ኃጢአታቸውን ይቅር በላቸው በደልም አታድርግባቸው ይህንንም ብሎ አረፈ። ደጋግ ሰዎችም መጥተው የእስጢፋኖስን ሥጋ ወስደው ቀበሩት ታላቅ ልቅሶም አለቀሱለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ነቢይት_ሐና

ዳግመኛም በዚህች ቀን የታላቁ ነቢይና ካህን ሳሙኤል እናት ቅድስት ነቢይት ሐና ተወለጀች።

ይችም ቅድስት ከሌዊ ነገድ ናት የታኅርም ልጅ ሕልቃና አገባት ፍናና የምትባልም ሌላ ሚስት አለችው እርሷም ወላድ በመሆኗ ሐና ልጅ ስለሌላት መካንም ስለሆነች ሁልጊዜ ትገዳደራት ነበር።

ሐና ግን ፈጽማ በማዘን አትበላም አትጠጣም ባሏ ሕልቃናም ያረጋጋታል ማረጋጋቱንም አልተቀበለችውም በሊቀ ካህናቱ በኤሊ ዘመንም ወደቤተ እግዚአብሔር ወጣች እያለቀሰችና እያዘነች በእግዚአብሔር ፊት ጸለየች እንዲህም ብላ ስለትን ተሳለች አቤቱ ልጅ የሰጠኸኝ እንደሆነ በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለአንተ የሚያገለግል አደርገዋለሁ።

ካህኑ ኤሊም አያትና እርሷ የወይን ጠጅ ጠጥታ እንደ ሰከረች አሰበ እርሷ በዝምታ በልቧ ትጸልይ ነበርና በቊጣና በግሣጼ የወይን ጠጅ ጠጥተሽ ወደዚህ ወደ እግዚአብሔር ቤት ለምን መጣሽ አሁን ሒጂ ስካርሺን በእንቅልፍ አስወግጂ አላት።

እርሷም እንዲህ አለችው የወይን ጠጅ ከቶ አልጠጣሁም ልጅ ያጣሁ በመሆኔ በልቤ አዝናለሁ እንጂ ካህን ኤሊም አጽናናት እንዲሁም ብሎ ባረካት የእስራኤል ፈጣሪ የለመንሽውን ይስጥሽ በሰላም ሒጂ በቃሉም አምና ወደ ቤቷ ገባች።

ከዚህም በኋላ ፀንሳ ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ሳሙኤል ብላ ጠራችው። ጡትንም በአስጣለችው ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ቤት ይዛው ወጣች ወደ ካህን ኤሊም አቀረበችውና እንዲህ ብላ አስረዳችው ከአሁን በፊት ልጅን ይሰጠኝ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ስጸልይና ስለምን ያየኸኝ ሴት ነኝ ልመናዬንም ሰምቶ ይህን ልጅ ሰጠኝ አሁንም በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለእግዚአብሔር አገልጋይ ይሆን ዘንድ አመጣሁት።

ከዚህም በኋላ ሐና እግዚአብሔርን አመሰገነችው። ልቤ በእግዚአብሔር አምኖ ጸና የሚለውን ጸሎትና ትንቢት እስከ መጨረሻው ተናገረች። ይቺም በዳዊት መዝሙር መጨረሻ ከሙሴ መኀልይ ቀጥላ ተጽፋለች።

ከዚህም በኋላ እግዚአብሔርን አገልግላ በሰላም ጥቅምት 6 አርፋለች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ፊልያስ_ሰማዕት

ዳግመኛም በዚች ቀን የሀገረ ቀምስ ኤጲስቆጶስ ቅዱስ ፊልያስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህንንም ቅዱስ በመኰንኑ ቊልቊልያኖስ ዘመን ወደ ፍርድ አደባባይ አቀረቡት ቊልቊልያኖስም ለአማልክት ሠዋ አለው። ፊልያስም እኔ ከብቻው እግዚአብሔር በቀር ለአማልክት አልሠዋም አለ። ቊልቊልያኖስም እግዚአብሔር ምን አይነት መሥዋዕት ይሻል አለ ፊልያስም ቅን ትሑት የሆነ ንጹሕ ልቡናን ዕውነተኛ ፍርድን ቁም ነገርን እንዲህ ያለ መሥዋዕትን እግዚአብሔር ይወዳል አለው።

ቊልቊልያኖስም የምትጋደል ስለ ነፍስ ነው ወይስ ስለ ሥጋ አለ ፊልያስም ስለ ነፍስና ስለ ሥጋ ነው እነርሱ በአንድነት ይነሣሉና አለ። ቊልቊልያኖስም የምትወዳት ሚስት የምትወዳቸው ልጆች ወይም ወንድምና ዘመድ አለህን አለው ፊልያስም ከሁሉም የእግዚአብሔር ፍቅር ይበልጣል አለ።

ቊልቊልያኖስም እግዚአብሔር ከበጎ ሥራ የሠራው ምንድን ነው አለ ፊልያስም እግዚአብሔር ያደረገልን ይህ ነው ሰማይና ምድርን በውስጣቸው ያሉትን ሁሉ ፈጠረልን። ዳግመኛም ከጠላታችን ከሰይጣን እጅ ያድነን ዘንድ ከሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ሁኖ ተወለደ የሕይወት መንገድንም በዓለም ውስጥ ተመላልሶ አስተማረ መከራንም በሥጋው ተቀብሎ ተሰቅሎ ሞተ በሦስተኛውም ቀን ተነሥቶ በአርባ ቀን ዐረገ ዳግመኛም ለፍርድ ይመጣል ይህን ሁሉ ስለ እኛ አደረገ።
ቊልቊልያኖስም አምላክ ይሰቀላልን ይሞታልን አለ ፊልያስም አዎን የዘላለም ሕይወትን ይሰጠን ዘንድ ስለ እኛ ፍቅር ሞተ አለው።

ቊልቊልያኖስም እንዲህ አለው እኔ እንዳከበርኩህ ልጣላህም እንዳልፈለግሁ አላወቅህምን አንተ በወገን የከበርክ እንደሆንክ አውቃለሁና አሁንም ለአማልክት ሠዋ በክፉ አሟሟት እንዳትሞት አለው። ፊልያስም እኔን ደስ ማሰኘት ከወደድክ እንዲያሰቃዩኝና እንዲገድሉኝ እዘዝ አለው በዚያንም ጊዜ በሰይፍ ራሱን እንዲቆርጡት አዘዘ።

ሊገድሉት ሲወስዱትም ዘመዶቹና የሀገር ታላላቆች ወደርሱ መጡ ለመኰንኑም በመታዘዝ ለአማልክት እንዲሠዋ እጆቹን እግሮቹን እየሳሙ ለመኑት። እርሱ ግን የጌታዬ ክርስቶስን መከራ መስቀልን ልሸከም እሔዳለሁና እናንተ አሳሳቾች ከእኔ ወግዱ ብሎ ገሠጻቸው።

ከሚገድሉበትም ሲደርስ ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ እጆቹን ዘርግቶ ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየ ሕዝቡን አደራ ወደ ጌታ አስጠበቀና ተሰናበተ ከዚህም በኋላ ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ሊቅ_ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘኑሲስ

በዚችም ዕለት የኑሲስ ኤጲስቆጶስ የባስልዮስ ወንድም የከበረ ጎርጎርዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

ይህም ቅዱስ ጎርጎርዮስ እጅግ የተማረ አዋቂ ነበረ በደሴቶችም ላይ ኤጲስቆጶስነት ተሾመ እነሆ በዚህ ወር በአሥራ አምስት ቀን የሆነውን ከገድሉ ጥቂት እንጽፋለን። ስለርሱም እንዲህ ተባለ እርሱ መሥዋዕቱን ለማክበር በሚቀድስ ጊዜ በመሠዊያው ላይ ሲወርድ መንፈስ ቅዱስን የሚያየው ሆነ ከዚህም በኋላ ኪሩብን አየው በደረቱም ውስጥ አቀፈው በመሠዊያውም ላይ ሳለ ወደ ዝምታና ተደሞ አደረሰው ሰዎችም ሁሉ ሥጋዊ እንቅልፍ የሚያንቀላፋ ይመስላቸው ነበር።

በኤጲስቆጶስነት ሹመት ሠላሳ ሦስት ዘመናት በተፈጸሙለት ጊዜ ወንድሙ ቅዱስ ባስልዮስ ሊጠይቀው መጣ እርሱ ከተጋድሎ ብዛት የተነሣ በጽኑ ደዌ የሚታመም ሁኖ ነበርና በቅዱስ ባስልዮስ መምጣት ደስ አለው።

ቅዱስ ጎርጎርዮስም እንደ ልማዱ ሊቀድስ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ የከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያም ተገለጸችለትና ዛሬ ወደኔ ትመጣለህ አለችው የቊርባኑንም ቅዳሴ ሲጨርስ ሕዝቡ በቀናች ሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ ይመክራቸውና ያስተምራቸው ዘንድ ወንድሙን ባስልዮስን ለመነው እርሱም እንደሚያንቀላፋ ሆነ በቀሰቀሱትም ጊዜ ሙቶ አገኙት ቅዱስ ባስልዮስም ሣጥን እንዲሠሩለት አዘዛቸው። ጸሎታትንም በመጸለይ መዝሙራትንም በመዘመር በማመስገንም እንደሚገባ ገንዞ በመቃብር ውስጥ አኖሩት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ_ካልዕ

በዚችም ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሠላሳ አንደኛ የሆነ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት ዲዮስቆሮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው ። ይህም አባት በዘመኑ ካሉ ትውልድ እርሱን የሚመስል ያልተገኘ በጠባዩ ቅን የዋህ በእውቀቱ አስተዋይ በበጎ ሥራው ፍጹም የሆነ ነው።

በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ መልእክትን ጽፎ ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጰሳት ቅዱስ ሳዊሮስ ላካት ። እርሱም ልዩ ሦስት የሆኑ ሥላሴ በመለኮት አንድ እንደሆኑ እየገለጠና እያሳሰበ ነው። ስለ ወልደ እግዚአብሔርም ሰው መሆን እርሱ ፍጹም ሥጋን ነባቢትና ለባዊት ነፍስን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ነሣ በመለኮቱና በትስብእቱም አካል ያለው አንድ ልጅ እንደሆነ ከተዋሕዶውም በኋላ በሥራው ሁሉ የማይለያይ ጭማሪ ወይም ጉድለት የሌለው ነው።

መልእክቱም ወደ ቅዱስ አባት ሳዊሮስ በደረሰች ጊዜ አነበባትና ፈጽሞ ደስ ተሰኘባት ለአንጾኪያም ሕዝብ አስተማረባት ሁሉም ደስ አለቸው።

ከዚህም በኋላ አባ ሳዊሮስ ለአባ ዲዮስቆሮስ የመልእክቱን መልስ እንዲህ ብሎ ጻፈ ። በኒቅያ ከተማ ተሰብስበው ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ ቅዱሳን አባቶቻችን በቀናች ሃይማኖት አጽንተው የሠሩዋትን ቤተ ክርስቲያኑን እንድትጠብቅ ለዚች ለከበረች አገልግሎት የመረጠህ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ። ዳግመኛም በዚሁ እንዲጸና ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ እንዳይል አስገነዘበው ደግሞም በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ ሕዝቡን ሁል ጊዜ አስተምራቸው አለው።

የአባ ሳዊሮስም መልእክት ወደ አባ ዲዮስቆሮስ በደረሰች ጊዜ ደስ ተሰኘባት በሁሉ ቦታም እንዲአስተምሩባት አዘዘ ይህም አባት ሕዝቡን ሁል ጊዜ የሚያስተምራቸው ሆነ። ሁል ጊዜም ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ ያስተምራቸዋል ኤጲስቆጶሳቱንና ካህናቱንም መንጋዎቻቸውን ስለ መጠበቅ ያዛቸዋል መልካም አገልግሎቱንም አድርሶ እግዚአብሔርንም ደስ አሰኝቶ አረፈ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_18

ጥቅምት አሥራ ስምንት ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ቴዎፍሎስ ያረፈበት፣ የከበረ #ቅዱስ_ሮማኖስ በሰማዕትነት ያረፈበት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

ጥቅምት አሥራ ስምንት በዚህች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያ ሦስተኛ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት ቴዎፍሎስ አረፈ። ይህም አባት ንጉሥ ቴዎዶስዮስ በነገሠ በስድስተኛ ዓመት ተሾመ በወንጌላዊ ማርቆስም ወንበር ሃያ ስምንት ዓመት ኖረ።

በዘመኑ ብዙ መጻሕፍትን የተረጎመ ከእሳቸውም የወንጌላዊ ዮሐንስን ራእይና የሐዋርያ ጳውሎስን መልእክት የተረጎመ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ተነሣ ዳግመኛም ለደሴተ ቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ የሆነ ኤጲፋንዮስ ነበረ።

በዘመኑም ሰባቱ ደቂቅ ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዓመት ከአንቀላፉ በኋላ ተነሡ። ይህም አባት የሐዋርያዊ ሊቀ ጳጳሳት አባት አትናቴዎስ ደቀ መዝሙር ነው የቤተ ክርስቲያንንም መጻሕፍትና ሥርዓቱን ሁሉ እየተማረ በእርሱ ዘንድ አደገ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጢሞቴዎስም በአረፈ ጊዜ ይህ አባት በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ አዋቂና አስተዋይም ስለሆነ ስለ ፍቅር ስለ ርኅራኄ ከንሰሐ በፊት ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል መጠበቅ ስለ ሚገባ ስለ ሙታን መነሣትና ለኃጥአን ስለ ተዘጋጀ ስለዘላለማዊ ሥቃይ ሌሎችም ጠቃሚ የሆኑ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ።

ቅዱስ ቄርሎስም ለዚህ አባት ቴዎፍሎስ የእኅቱ ልጅ ነው እርሱም በበጎ አስተዳደግ አሳደገው የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት አስተማረው። ከዚያም በኋላ ወደ አባ ሰራብዮን ላከው አባ ሰራብዮንም መንፈሳዊ ተግባርን ሁሉ አስተማረው።

በአትናቴዎስም ዘመን አስቀድሞ እንዲህ ሆነ በጎ ዘመን ባገኝ ይህን ኮረብታ ባስጠረግሁት ነበር። ለከበሩ ለመጥምቁ ዮሐንስና ለነቢይ ኤልሳዕም ቤተ ክርስቲያን በሠራሁም ነበር ሲል ይህ አባት ቴዎፍሎስ አባ አትናቴዎስን ይሰማው ነበር። በሹመቱ ወራትም ይህን ነገር አስታውሶ የሚያዝንና ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን የሚጸልይ ሆነ።

በዚያ ወራትም ባሏ ብዙ ገንዘብ ትቶላት የሞተ አንዲት ባለጸጋ ሴት ከሮሜ አገር መጣች ሁለት ልጆቿም ከእርሷ ጋር አሉ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስንም ሲያዝን አየችውና ክብር አባት ሆይ ምን ያሳዝንሐል አለችው። እርሱም ብዙ ወርቅ በዚህ ኮረብታ ውስጥ እያለ ድኆች ይራባሉና አላት እርሷም አንተ ስለ እኔ ጸልይ እኔም አስጠርገዋለሁ አለችው።

ይህንንም ብላ ያን ኮረብታ አስጠረገችው በውስጡም በደንጊያ ሠሌዳ እየአንዳንዱ የተከደኑ ሦስት ሣጥኖች ተገለጡ። በላያቸው ቴዳ ቴዳ ቴዳ የሚል ተጽፎባቸዋል አባ ቴዎፍሎስም በአየው ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ምሥጢራቸውን አውቆ ቴዳ ማለት የጌታ ስም ነው ይህም ለድኆች ይገባል አለ ሁለተኛውም ቴዳ የንጉሥ ቴዎዶስዮስ ነው ሦስተኛውም ቴዳ ቴዎፍሎስ ማለት ነው። የእኔ ገንዘብ ስለሆነ በዚህም አብያተ ክርስቲያናትን እሠራለሁ አለ። እሊህም ሣጥኖች በመቄዶንያዊው ፊልጶስ ልጅ በንጉሥ እስክንድር ዘመን እንደ ተቀበሩ የዘመን ቊጥር ተገኘ እርሱም ሰባት መቶ ዘመናት ነው።

ከዚህም በኋላ ያን የወርቅ ሣጥን ለንጉሥ ቴዎዶስዮስ ላከለት ስለዚያም የወርቅ መዝገብ አስረድቶ ቦታውን መጥቶ እንዲያይ አሳሰበው እርሱም በመርከብ ተጭኖ ወደ እስክንድርያ አገር መጥቶ ሁሉንም አየ የዚያንም ወርቅ እኵሌታ መለሰለት አባ ቴዎፍሎስም ብዙዎች አብያተ ክርስቲያንን ሠራ።

አስቀድሞም በቅዱሳን በመጥምቁ ዮሐንስና በነቢይ ኤልሳዕ በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራ ሥጋቸውንም ከእስራኤል አገር አፍልሶ አምጥቶ በውስጧ አኖረ እርሷም የታወቀች ናት ዴማስ በሚባል ቦታ ሁለተኛም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በሀገሩ ምሥራቅ በኩል ሠራ ከዚህም በኋላ በሊቀ መላእክት ሩፋኤል ስም በደሴት ውስጥ ሠራ ሌሎችንም ብዙዎች አብያተ ክርስቲያን አሳነፀ።

ንጉሡም አብያተ ክርስቲያናትን ለመሥራት ያለውን የሊቀ ጳጳሳቱን ፍቅር አይቶ በግብጽ አገር ያሉትን የጣዖታት ቤቶችን ሁሉንም ሰጠው እርሱም ተቀብሎ አፈረሳቸውና በቦታቸው አብያተ ክርስተከያናትንና የእንግዶች ቤቶችን ሠራ ሁለተኛም ምድራቸውን ሁሉ ሰጠው።

ይህም አባት ቴዎፍሎስ የክርስትና ጥምቀትን በሚያጠምቅ ጊዜ የብርሃን በትረ መስቀል በሚጠመቁት ላይ በመስቀል ምልክት ሲያማትብ ያይ ነበር።

ይህ አባት ቴዎፍሎስና ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ልጆች በሆኑበት ጊዜ ሁለቱም በአንዲት ሌሊት አንዲት የሆነች ራእይን እነርሱ እንጨቶችን እንደሚለቅሙ አዩ። ከእነርሱም አንዱ ንጉሥ እንደሚሆን ሁለተኛውም ሊቀ ጳጳሳት እንደሚሆን ያቺን ራእይ ተረጎሟት እንዲሁም ሆነ።

ይህም አባት ቴዎፍሎስ ሊቀ ጵጵስና በተሾመባት በመጀመሪያዪቱ ዓመት ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ሃይማኖትን እናስተምራለን የሚሉ ሁሉ ሃይማኖታቸውን በመጽሐፍ ጽፈው ወደርሱ እንዲአቀርቡ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ።

ከዚህም በኋላ ንጉሡና ሊቀ ጳጳሳቱ ተነሥተው እነዚያን ጽሑፎች በመሠዊያው ላይ አድርገው ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ ጌታም ወልድ በመለኮቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ትክክል ነው ብሎ ከሚታመን በቀር ከውስጣቸው በቀናች ሃይማኖት የጸና እንደ ሌለ ገለጠላቸው። በዚያንም ጊዜ እሊህን የመናፍቃን መጻሕፍትን እንዲአቃጥሏቸው እነዚያንም መናፍቃን ከሚገዛው አገር እንዲአሳድዷቸው ንጉሥ አዘዘ።

ዮሐንስ አፈወርቅም መጻሕፍትን ማንበብና መመርመር ያበዛ ነበር ስለዚህም የአውጋርዮስን መጻሕፍት አወገዘ ያወግዙ ዘንድም ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ወደዚህ አባት ወደ ቴዎፍሎስ ወደ ቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ወደ ኤጲፋንዮስ ወደ ኤዺስቆጶሳት ሁሉ በየሀገሩ ላከ። ከዚህም በኋላ መልካም ጒዞውን በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#መነኰስ_ቅዱስ_ሮማኖስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ክርስቲያኖችን በአሳደደ በመኰንን አስቅልጵያኖስ ዘመን የከበረ መነኰስ ሮማኖስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ የክርስቲያን ወገኖችን መኰንኑ እንዳሳደዳቸው በሰማ ጊዜ ከቀሳውስትና ከዲያቆናት ጋር የክርስቲያን ወገኖችን ሁሉ በአንድነት ሰበሰባቸው ስለ ክርስቶስ ሃይማኖትም መክሮ አጸናቸው።

አስቅልጵያኖስም ይህን ሰምቶ እንዲአመጡት አዘዘ በፊቱም በቆመ ጊዜ አስቅልጵያኖስ በወገን የከበርክ ሮማኖስ አንተ ነህን አለው ቅዱሱም የወገን ክብር ምን ይጠቅመኛል ክብሬ ግን ክርስቶስ ነው ብሎ መለሰለት። መኰንኑም ሰምቶ እንዲሰቅሉትና ጉንጮቹን ይሰነጣጥቁ ዘንድ አዘዘ ጉንጮቹንም ሲሰነጣጥቁት ምንም አልተናገረምና መኰንኑ ትዕግሥቱን አደነቀ።

በዚያንም ጊዜ ሮማኖስ መኰንኑን እንዲህ አለው እነሆ ስንፍናህን እዘልፍ ዘንድ ፈጣሪዬ አፌን ከፈተ እውነት ነገርን ብታውቅ ለእግዚአብሔር እንሰግድ ዘንድ ይገባ እንደሆነ ወይም ለአማልክት እንዲነግረን ሕፃን ልጅ እንዲአመጡ እዘዝ መኰንኑም ታናሽ ሕፃንን እንዲአመጡ አዘዘ መኰንኑም ሕፃኑን ስግደት ለማን እንዲገባ ዕውነቱን ንገረን አለው። ሕፃኑም ልብ የሌለህ ደንቆሮ መኰንን በአንዲት ቃል ዓለሙን ሁሉ ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር ስግደትና አምልኮ እንዲገባ አታውቅምን አለው።
መኰንኑም ሕፃኑን ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ የሕፃኑም እናት ልታየው መጣች ሕፃኑም እናቱን ተጠምቻለሁና ውኃ አጠጭኝ አላት። እናቱም ልጄ ሆይ ከዚህ ውኃ የለም ነገር ግን ወደ ሕይወት ውኃ ሒድ አለችው።

በዚያንም ጊዜ የሕፃኑን ራስ በሰይፍ እንዲቆርጡ የቅዱስ ሮማኖስንም ምላሱን ከግንዱ እንዲቆርጡ መኰንኑ አዘዘ። ያን ጊዜ መኰንኑን ይዘልፍ ዘንድ ለአባ ሮማኖስ ረቂቅ አንደበት ተሰጠው ሲዘልፈውም መኰንኑ ሰምቶ ምላሱ እንዳልተቆረጠ ተጠራጠረ። ወታደሩንም ጠርቶ ምላሱን ያልቆረጥክ ለምንድን ነው አለው ወታደሩም የምላሱን ቁራጭ ያመጡ ዘንድ እዘዝ አለው አምጥተውለትም አይቶ መኰንኑም ወደ ወህኒ ቤት አስገብተው በዚያ አንቀው እንዲገድሉት አዘዘ። እንዲህም ምስክርነቱን ፈጽሞ የምስክርነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእነዚህ መስተጋድል ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)