መዝገበ ቅዱሳን
19.2K subscribers
1.91K photos
9 videos
5 files
28 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
††† እንኳን ለታላቁ ክርስቲያናዊ ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ †††

††† ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ለቤተ ክርስቲያን የፈፀመውን መልካም ተግባር ያሕል መሥራት የቻለ ንጉሥ በሐዲስ ኪዳን የለም:: ጻድቁ ንጉሥ ከቅድስት እናቱ እሌኒና ከአረማዊ አባቱ ቁንስጣ በበራንጥያ ተወለደ::

ዘመኑ ዘመነ ዐጸባ (የመከራ ጊዜ) ወይም የሰማዕታት ዘመን በመሆኑ ክርስቲያኖች በግፍ የሚጨፈጨፉበት ወቅት ነበር:: ክርስቲያኖችን ከምድረ ገፅ ለማጥፋት በተደረገው የ40 ዓመታት ዘመቻ አብያተ መቃድስና መጻሕፍት ተቃጠሉ:: ብዙዎቹ በየበርሃው ተሰደዱ:: ሚሊየኖች በግፍ አለቁ::

የዚሕን ዘመን መከራ በውል ያልተረዳ ሰው ቅዱስ ቆስጠንጢኖስን ሊያከብር አይችልም:: ምክንያቱም ይህን የመከራ ዘመን በፈቃደ እግዚአብሔር አስቁሞ : ቀርነ ሃይማኖት የቆመው : ብዙ ሥርዓት የተሠራው : ቤተ ክርስቲያንም ያበራችው በዘመኑ ነውና::

ቅዱሱ ንጉሥ ለሁሉም ነቢያት : ሐዋርያትና ሰማዕታት አብያተ ክርስቲያናትን ራሱ በመሠረታት በቁስጥንጥንያ አንጿል:: በዘመኑ ቤተ ክርስቲያን በሰላም ኖራለት : በኃይለ መስቀሉ ጠላት ጠፍቶለት ኑሮ በዚህች ቀን አርፏል:: "ቆስጠንጢኖስ" ማለት "ሐመልማል" ማለት ነው::

††† ዳግመኛ በዚሕ ቀን የዓለማት ፈጣሪ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ በሆነው ሞቱ በመቃብር ውስጥ አድሯል::

††† ጌትነት ያለው አምላካችን በይቅርታው ይጐብኘን:: መልካም መሪንም ይስጠን::

††† መጋቢት 28 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ታላቁ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ (ጻድቅ ንጉሥ)
2.ቅድስት እሌኒ ንግስት

††† ወርኀዊ በዓላት
1.አማኑኤል ቸር አምላካችን
2.ቅዱሳን አበው (አብርሃም: ይስሐቅና ያዕቆብ)
3.ቅዱስ እንድራኒቆስና ሚስቱ ቅድስት አትናስያ
4.ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ
5.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ (ሰማዕት)

††† "እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ: ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር: ልመናና ጸሎት: ምልጃም: ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ: ስለ ነገሥታትና መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ:: ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው::" †††
(፩ጢሞ. ፪፥፩-፬)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
እንኳን ለጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዓመታዊ የጽንሰት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን።

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †

††† በዓለ ጽንሰት †††

††† ይሕች ቀን ለቤተ ክርስቲያን በእጅጉ ልዩ ናት:: በዓመቱ ከሚከበሩ በዓላትም አንደኛውን ሥፍራ ትይዛለች::

በዚሕ ዕለት አምላካችን እግዚአብሔር:-

1.ሰማይና ምድርን ፈጠረ:: (ዘፍ. 1:1)

2.በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት በድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ (ተጸነሰ):: በዓሉም "በዓለ ትስብእት" ይባላል:: "አምላክ ሰው : ሰው አምላክ የሆነበት" ማለት ነው:: (ሉቃ. 1:26)

3.የክብር ባለቤት መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ ተነሳ:: (ማቴ. 28:1፣ ማር. 16:1፣ ሉቃ. 24:1፣ ዮሐ. 20:1)

4.ጌታችን ዳግመኛ ለፍርድ በዚሕች ቀን ይመጣል:: (ማቴ. 24:1)

††† በነዚሕ ታላላቅና ድርብርብ በዓላት ምክንያት ቀኑ "ርዕሰ በዓላት" (የበዓላት ራስ) : "በኩረ በዓላት" እየተባለም ይጠራል::

††† ቸሩ እግዚአብሔር ዓለምን ከመፍጠሩ : ከጽንሰቱ : ልደቱና ትንሣኤው በረከትን ይክፈለን:: በጌትነቱም ሲመጣ በርሕራሔው ያስበን::

††† ዳግመኛ በዚህች ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እልዋሪቆን ገብቷል:: ይህች ሃገር የምድራችን መጨረሻ ናት:: ከዚያ በኋላ ሰውና ሃገር የለም:: እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን የሰበከ ሐዋርያ የለም::

††† ከቅዱሱ ሐዋርያ ትጋት : ቅናት : መንፈሳዊነትና ንጽሕና አምላካችን ይክፈለን::

††† መጋቢት 29 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ በዓላት
1.ጥንተ ዕለተ ፍጥረት (ዓለም የተፈጠረችበት)
2.በዓለ ትስብእት (የጌታችን ጽንሰቱ)
3.ጥንተ በዓለ ትንሣኤ
4.ዳግም ምጽዐት
5.ቅድስት ማርያም መግደላዊት
6.ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ
7.ቅዱሳት አንስት (ትንሣኤውን የሰበኩ)
8.ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ (ጽንሰታ)
9.አብርሃ ወአጽብሐ (ጽንሰታቸው)
10.ቅዱስ ኢያሱ ነቢይ (ጽንሰቱ)
11.ቅዱስ ላሊበላ (ጽንሰቱ)
12.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ (ጽንሰታቸው)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.የፈጣሪያችንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት
2.ቅድስት አርሴማ ድንግል
3.ቅዱስ ጴጥሮስ ተፍጻሜተ ሰማዕት
4.ቅዱስ ማርቆስ ዘቶርማቅ
5.ቅዱስ ዘርዐ ክርስቶስ (ጻድቅና ሰማዕት)

††† "እነሆ ከደመና ጋር ይመጣል:: ዓይንም ሁሉ: የወጉትም ያዩታል:: የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ:: አዎን አሜን::
ያለውና የነበረው: የሚመጣውም: ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ: አልፋና ኦሜጋ እኔ ነኝ ይላል::" †††
(ራእይ ፩፥፯)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
† እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ሶምሶን (መስፍነ እስራኤል) ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ገብርኤል †††

††† ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል:-

*ከ7ቱ ሊቃናት አንዱ::
*በራማ አርባብ በሚባሉ 10 ነገደ መላእክት ላይ የተሾመ::
*በመጀመሪያዋ የፍጥረት ቀን መላእክትን ያጸና::
*ቅዱሳንን ሁሉ የሚረዳ::
*ሠለስቱ ደቂቅን : ዳንኤልን : ሶስናን ከሞት የታደገ ታላቅ መልዐክ ነው::

ከምንም በላይ ግን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅዱሱን መልዐክ "መጋቤ-ሐዲስ" ብላ ታከብረዋለች:: ቅዱስ ገብርኤል የስሙ ትርጉዋሜ "አምላክ ወሰብእ - እግዚእ ወገብር" ነውና ለሥነ ፍጥረት ሁሉ የሚሆን ሐዲስ ዜናን ወደ እመቤታችን ድንግል ማርያም አምጥቷል::

መልዐኩ እመቤታችንን ከመጸነሷ ጀምሮ ባይለያትም መጋቢት 29 ቀን ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ አብስሯታል:: ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በማግስቱ በድምቀት እንዲከበር በወሰኑት መሠረት ዛሬ (በ30) ይከበራል::

††† ሶምሶን ረዓይታዊ †††

††† እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን: ሀያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረትን ፈጥሮ አዳምን ገዢ አደረገው:: አክሎም በነፍስ ሕያው አድርጐ: በመንፈስ ቅዱስ አክብሮ: ነቢይና ካህን አድርጐ: ካንዲት ዕፀ በለስ በቀር በፍጥረት ሁሉ ላይ አሰለጠነው::

አባታችን አዳም ግን ስህተት አግኝቶት ከገነት ወጣ:: መከራና ፍዳም አገኘው:: በኋላም ለ100 ዓመት አልቅሶ ንስሃ ገባ:: ጌታም ንስሃውን ተቀብሎ "ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ተስፋ ድህነትን ሰጠው::

ስለዚህም ምክንያት ለ5,500 ዓመታት ትንቢት ሲነገር: ሱባኤ ወደ ታች ሲቆጠር: ምሳሌም ሲመሰል ኖረ:: ከደግ ፍጥረት አዳም እስከ ኖኅ ድረስ: የሴት ልጆች እግዚአብሔርን በንጽሕና ሁነው በደብር ቅዱስ አመለኩ::

ትንሽ ቆይተው ግን ስለተቀላቀሉ ከቃየን ልጆች ጋር በማየ ድምሳሴ ጠፉ:: በጻድቅ ሰው ኖኅ የተጀመረው ትውልድም እግዚአብሔርን ለመዘንጋት ጊዜ አልፈጀበትም:: ነገር ግን ከሴም ዘር ቅንና ጻድቅ ሰው አብርሃም ተገኘ::

ከእርሱም ይስሐቅ: ከዚያም ያዕቆብ (ደጋጉ) ተገኙ:: ያዕቆብም "እሥራኤል" ተብሎ: በልጆቹ "ሕዝበ እግዚአብሔር" የተባለ ነገድ ተመሠረተ:: በተስፋይቱ ምድር በከነዓን እንዳይኖሩም ርሃብ ምድረ ግብጽ አወረዳቸው::

በዚያም ለ215 ዓመታት በጭንቅ የባርነትን ሕይወትን አሳለፉ:: እግዚአብሔርም ስለ ወዳጁ አብርሃም ሲል እሥራኤልን አሰባቸው:: የዋሕና ጻድቅ ሰው ሙሴን አስነስቶ እሥራኤልን ከግብጽ ባርነት አዳናቸው::

ይኸውም በጸናች እጅ: በበረታችም ክንድ: በ9 መቅሰፍት: በ10ኛ ሞተ በኩር: በ11ኛ ስጥመት ግብጻውያንን አጥፍቶ ነው:: በየመንገዱም ጠላቶቻቸውን እየተበቀለላቸው ነው:: ከዚህ ዘመን ጀምሮም እሥራኤል በመሳፍንትና በካህናት የሚተዳደሩ ሆኑ::

አስቀድሞ ሙሴ በምስፍና: አሮን በክህነት መሯቸው:: ቀጥሎም በቅዱስ ሙሴ ኢያሱ: በአሮን አልዓዛር ተተኩ:: እንዲህ እንዲህ እያለም ከኃያል ሰው ሶምሶን ረዓይታዊ ደረሱ:: ይኸውም ከዓለም ፍጥረት 4,200 ዓመታት በኋላ መሆኑ ነው::

በጊዜው እሥራኤል ጣዖትን እያመለኩ እግዚአብሔርን ስላሳዘኑት ለጠላቶቻቸው አሳልፎ ይሰጣቸው ነበር:: የአካባቢው መንግስታት እነ አሞን: አማሌቅ: ኢሎፍሊ ስንኳ ያኔ ዛሬም ቢሆን እንደምትመለከቱት ዶሮና ጥሬ ናቸው::

በጊዜውም የእሥራኤል ኃጢአት ስለ በዛ ኢሎፍላውያን (ፍልስጤማውያን) 40 ዓመት በባርነት ገዟቸው:: ንስሃ ሲገቡ ደግሞ ልጅ በማጣት ያዘኑ ማኑሄ እና ሚስቱ (እንትኩይ) : በቅዱስ ሚካኤል ተበሥረው ኃያሉን ሶምሶንን ወለዱላቸው::

እርሱም ናዝራዊ (ከእናቱ ማኅጸን ለጌታ የተለየ) ነበርና ፍልስጤማውያንን ቀጥቶ ወገኖቹን እስራኤልን ከባርነት : በአምላኩ ኃይል ታደገ:: ከኃይሉ ብዛት የተነሳም:-
¤አንበሳን እንደ ጠቦት ይገድል (መሣ. 14:5)
¤300 ቀበሮዎችን አባሮ ይይዝ (መሣ. 15:3)
¤በብርቱ ገመዶች ሲያስሩት እንደ ፈትል ይበጣጥሰው (መሣ. 15:14)
¤በአህያ መንጋጋ ሽህ ሰው ይገድል (መሣ. 15:15)
¤ጠባቂዎችን ከነ መቃናቸው ተሸክሞ ይወረውር ነበር:: (መሣ. 16:3)

ውኃ ሲጠማውም ከአህያ መንጋጋ ላይ ፈልቆለት ጠጥቷል:: (መሣ. 15:18) በፍጻሜው ግን ደሊላ በምትባል ሴት ተታልሎ ምሥጢሩን በመግለጡና ጸጉሩ በመላጨቱ ኃይሉን አጥቷል:: ጠላቶቹም ዐይኑን አውጥተው መዘባበቻ አድርገውታል::

በፍጻሜው ግን ኃይሉ እንዲመለስለት ፈጣሪውን ለምኖ : አሕዛብ ለጣኦት በዓል እንደተሰበሰቡ የአዳራሹን ምሰሶ አፍርሶ አጥፍቷቸው ዐርፏል:: (መሣ. 13--16)
ቅዱስ ሶምሶን የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥላ (ምሳሌ) ነው::

††† "ክፉ ናችሁ: ኃጢአታችሁ በዝቷል" የማይል ጌታ በመከራችን ሁሉ ተራዳኢ መልዐክን (ቅዱስ ገብርኤልን) ይዘዝልን:: ወርኀ መጋቢትን በሰላም እንዳስፈጸመ ወርኀ ሚያዝያን በምሕረቱ ይባርክልን::

††† መጋቢት 30 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት (እመቤታችንን ያበሠረበት መታሠቢያ)
2.ቅዱስ ሶምሶን (መስፍነ እስራኤል)
3.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ (ፍልሠቱ)
4.ቅዱስ ዮሐንስ ዘአክሱም (ድርሳነ ሚካኤልን መጻፉ የሚነገርለት አባት)
5.እግዚአብሔር ውሃን ከ3 ከፈለው (ጠፈርን ፈጠረ)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
2.ቅዱስ ማርቆስ ዘአንበሳ (ሐዋርያ)
3.አባ ሣሉሲ ክቡር
4.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት
5.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት

††† ". . . በአምላኬም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ተቀደሰው ስለ አምላኬ ተራራ ስለምን: ገናም በጸሎት ስናገር አስቀድሜ በራእይ አይቼው የነበረው ሰው ገብርኤል እነሆ እየበረረ መጣ:: በማታም መሥዋዕት ጊዜ ዳሰሰኝ:: አስተማረኝም . . ." †††
(ዳን. 9:20)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
✞✞✞ እንኩዋን ከተባረከ ወር "ሚያዝያ" እና ከጻድቁ አባታችን "ቅዱስ ስልዋኖስ" "ወቅዱስ አሮን ካህን" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

+*" አባ ስልዋኖስ "*+

=>ጻድቁ አባ ስልዋኖስ ግብፃዊ ሲሆኑ ከታላቁ መቃርስ
መንፈሳዊ ልጆች አንዱ ናቸው:: ገና በሕጻንነታቸው ወደ
ገዳም ገብተው ጾምን : ጸሎትን : ትሕርምትን ገንዘብ
በማድረግ ታላቅ የንጽሕና ሰው ሁነዋል::

+ከመካከለኛ እድሜአቸው ጀምረው ደግሞ የገዳመ
አስቄጥስ አበ ምኔት ሆነው በመልካም እረኝነት
አገልግለዋል:: ጻድቁን ለየት የሚያደርጉዋቸው አንዳንድ
ተግባራት ነበሩ::

+እርሳቸውን ጨምሮ ሁሉም ገዳማዊ ከጾምና ከጸሎት
ባሻገር ሥራ ሠርቶ ማታ መመጽወት አለበት:: ያ ማለት
ያለ ምጽዋት ውሎ ማደር አይፈቀድም ነበር:: ይሕም
መነኮሳቱን ከጽድቅ ባለፈ ታታሪና ባተሌ አድርጉዋቸዋል::

+አባ ስልዋኖስ በተሰጣቸው ጸጋ መላእክትን : ገነትና
ሲዖልን ያዩ ነበር:: በዚሕ ምክንያት ስለ ኃጥአን ከማልቀስ
ዐይናቸው ቦዝኖ አያውቅም:: የዚሕን ዓለም ብርሃን
አላይም ብለው ቆባቸውን ዓይናቸው ላይ ጥለው
በመልካም ሽምግልና በዚሕች ቀን አርፈዋል::

=>አምላካችን ከጻድቁ በረከት ያሳትፈን::

+*" ቅዱስ አሮን ካህን "*+

=>ቅዱስ አሮን:-
~የሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴ ወንድም::
~የነቢዪት ማርያም ታናሽ::
~የዮካብድና ዕንበረም ልጅ::
~የእግዚአብሔር ካህን እና
~የብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናት ነው::

+እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን የነበረው የክህነት
አገልግሎት ከእርሱ ዘር እንዳይወጣ ምሎለታል:: ዳታን :
አቤሮንና ቆሬ ይህንን ቢቃወሙ ከነ ሕይወታቸው መሬት
ተከፍታ ውጣቸዋለች:: በድፍረት "እናጥናለን" ብለው ወደ
ደብተራ ኦሪት የገቡትንም እሳት ከሰማይ ወርዶ
በልቷቸዋል::

+ቅዱስ አሮንም በጌታ ትእዛዝ በትሩ ለምልማ : አብባና
አፍርታ ተገኝታለች:: ይህም ለጊዜው ክህነት ከሱ ልጆች
እንዳይወጣ ሲያደርግ በፍጻሜው ለድንግል ማርያም
ምሳሌ ሆኗል::

+የአሮን በትር ሳይተክሏት : ሳይደክሙባትና ውሃ
ሳያጠጣት አብባና አፍርታ እንደተገኘች ድንግል ማርያምም
የወንድ ዘር ምክንያት ሳይሆናት ፍሬ አፍርታለች
(ክርስቶስን ወልዳለችና)::

+አባ ሕርያቆስ "ጸናጽል ዘውስተ ልብሱ ለአሮን ካህን::
ወዓዲ በትር እንተ ሠረጸት : ወጸገየት : ወፈረየት" እንዳለ::
(ቅዳሴ ማርያም)

+ቅዱስ አሮን በማዕጠንቱና በመስዋዕቱ ፈጣሪውን
አገልግሎ : ድውያንንም ፈውሶ : እስራኤል በበርሃ ሳሉ
አርፎ ተቀብሯል:: (ዘኁ. 20:25)

(ለተጨማሪ ንባብ 3ቱን ብሔረ ኦሪት (ከኦሪት ዘጸአት
ምዕራፍ 4 ጀምረው እስከ ኦሪት ዘኁልቁ ምዕራፍ 20
ድረስ) ያንብቡ)

=>ክብሩ : በረከቱ ይደርብን::

=>ሚያዝያ 1 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አሮን ካህን (የሊቀ ነቢያት ሙሴ ወንድም)
2.አባ ስልዋኖስ ጻድቅ
3.ቅዱሳን መነኮሳት
4.ቅድስት መጥሮንያ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ልደታ ለማርያም ድንግል እግዝእትነ
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱስ ራጉኤል ሊቀ መላዕክት
4.ቅዱስ በርተሎሜዎስ ሐዋርያ
5.ቅዱስ ሚልኪ ትሩፈ ምግባር

=>+"+ ስለ ሕዝብ እንደሚያቀርብ እንዲሁ ስለ ራሱ
ደግሞ መስዋዕትን ስለ ኃጢአት ሊያቀርብ ይገባዋል::
እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም
ክብሩን ለራሱ የሚወስድ የለም:: +"+ (ዕብ. 5:3)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
††† እንኳን ለሰማዕቱ ቅዱስ ክርስቶፎሮስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ክርስቶፎሮስ †††

††† ክርስቶፎሮስ ትርጉሙ "ለባሴ ክርስቶስ" እንደ መሆኑ በሐዋርያት ዘመን የነበሩ ብዙ ቅዱሳን በዚህ ስም ይጠሩ ነበር:: ከነዚህ አንዱ ቅዱስ ክርስቶፎሮስ ሃገሩ በላዕተ ሰብእ (ሰውን የሚበሉ) ውስጥ ነበር::

ይህች ሃገር አሁን የት እንዳለች በውል ባይታወቅም የቅዱስ ማትያስ ሃገረ ስብከት በመሆኗ አውሮፓና እስያ ድንበር አካባቢ እንደሆነች ይገመታል::

የአካባቢው ሰዎች ከሰው ሥጋ ውጪ እህልን አይቀምሱም ነበር:: ቅዱስ ማትያስ በነርሱ ያደረውን ርኩስ መንፈስ አስወጥቶ አሳምኗቸዋል::

ከሃገሩ ሰዎችም አንዳንዱ ገጻተ ከለባት (የውሻ መልክ ያላቸው) ነበሩ:: ክርስቶፎሮስም ከነርሱ አንዱ ነበር:: በክርስቶስ አምኖ ከተጠመቀ በሁዋላ በስብከቱ ብዙዎችን አሳምኖ : ስለ ሃይማኖትም ብዙ ጸዋትወ መከራ ተቀብሎ በዚህች ቀን በሰማዕትነት አርፏል::

††† ከሰማዕቱ በረከት አምላኩ ያድለን::

††† ሚያዝያ 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ክርስቶፎሮስ (ሐዋርያና ሰማዕት)
2.አባ ስምዖን ዘሃገረ ሐሊባ
3.ቅዱስ መላልኤል (የያሬድ አባት - ከአዳም 5ኛ ትውልድ)
4.እግዚአብሔር ፀሐይን : ጨረቃን : ከዋክብትን ፈጠረ

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
2.ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ
3.ቅዱስ ኢዮብ ጻድቅ ተአጋሲ
4.ቅዱስ አቤል ጻድቅ
5.ቅዱስ አባ ዻውሊ ገዳማዊ (ታላቁ)
6.ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ
7.አባ ሕርያቆስ ዘሃገረ ብሕንሳ

††† "ስለዚሕ ወንድሞቼ ሆይ ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ:: ልባሞች እንደመሆናችሁ እላለሁ:: በምለው ነገር እናንተ ፍረዱ:: የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? . . . እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን:: ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና::" †††
(1ቆሮ. 10:14-18)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
እንኩዋን ለጻድቁ አባታችን "ቅዱስ መርቄ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ጻድቁ ቅዱስ መርቄ "*+

=>ቅዱስ መርቄ በሁለት ዓለም የተሳካለት ደግ ሰው ነው:: ነገሩ እንዲህ ነው:-

+ቅዱሱ በዓለም የሚኖር ታዋቂ ነጋዴ ነው:: ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር እንደ አስቸጋሪ ከሚታዩ የሥራ ዘርፎች አንዱ የንግድ ሥራ ቢሆንም እርሱ ግን "ቅዱሱ ነጋዴ" ለመባል በቅቷል::

+ለዚህም ምክንያቱ 2 ነገሮች ናቸው:-
1.በንግድ ሕይወቱ ማንንም ሳያጭበረብር ከመኖሩ ባለፈ ፍጹም ጸሎትን ጾምንና ምጽዋትን ያዘወትር ነበር::
2.ለንግድ በተዘዋወረባቸው ሃገራት ሁሉ ስለ ክርስቶስ ያለማቁዋረጥ የሚሰብክ በመሆኑ በርካቶችን አሳምኖ ሐዋርያዊ ክብርን አግኝቷል::

+ቅዱስ መርቄ በሕይወቱ ይሕንን ከፈጸመ በሁዋላ አንድ አረማዊ ጉዋደኛ ነበረውና : ሐብት ንብረቱን ሰብስቦ "ጌታችን ክርስቶስ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስላለ ለርሱ ስጥልኝ" ብሎ ላከው::

+አረማዊው ጉዋደኛውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፍፁም ግርማ አግኝቶ ንብረቱን ከእጁ ተቀብሎታል::

+አረማዊውም በዚህ ምክንያት ከ75 ቤተሰቦቹ ጋር አምኖ ተጠምቁዋል:: ቅዱስ መርቄ በርሃ ውስጥ ባረፈ ጊዜ ቅዱስ ዳዊት ከሰማይ ወርዶ ዘምሮለታል:: መላዕክት በምስጋና ገንዘውት አንበሶች ቀብረውታል::

=>አምላክ ከቅዱሱ በረከትን ያድለን::

=>ሚያዝያ 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ መርቄ ጻድቅ (ክርስቲያናዊ ነጋዴ)
2.ቅዱስ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም
3.አባ ሚካኤል ዘእስክንድርያ
4.እግዚአብሔር:- በእግር የሚራመዱ : በክንፍ የሚበሩና በልብ የሚሳቡ : በየብስ የሚኖሩ ፍጥረታትን ፈጠረ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱሳን ሊቃነ ካህናት አበው (ዘካርያስና ስምዖን)
4.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
5.አቡነ ዜና ማርቆስ
6.አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ዘደብረ በንኮል

=>+"+ እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ:: በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሰወር አይቻላትም:: መብራትንም አብርተው በዕንቅብ በታች አይደለም እንጂ በመቅረዙ ላይ ያኖሩታል:: በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል:: መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ:: +"+ (ማቴ. 5:14-16)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
ገብርኄር
Forwarded from 🟢ናታኒም ፖሮሞሽን🟢
🔹 ✥● ከሚከተሉት ውስጥ ቅድስት ሃገራችን ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ከሚለው መጠርያ ስሟ ሌላ በየትኛው ትጠራ ነበር?? ✥●
† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን †

እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን።

† ሚያዝያ 6 †

=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚህች ዕለት እነዚህን ታላላቅ ቅዱሳን ታስባለች:-

† ቅድስት ማርያም ግብፃዊት †

† በዚች ቀን በበረሀ የምትኖር ግብፃዊት ማርያም አረፈች። ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ሁና ወላጆቿ ክርስቲያን ናቸው። እድሜዋ አስራ ሁለት አመት በሆናት ጊዜ የመልካም ስራና የሰው ሁሉ ጠላት ሸንግሎ አሳታት በእርሷም የማይቆጠሩ የብዙዎችን ነፍስ አጠመደ እርሱ ሰይጣን ስለ ዝሙት ፍቅር ያለ ዋጋ ስጋዋን እስከ መስጠት አድርሷታልና ።

በዚህም በረከሰ ስራ ውስጥ ኖረች በየእለቱም የኃጢአት ፍቅር በላይዋ ይጨመርባት ነበር። ሰውን የሚወድ የእግዚአብሄርም ቸርነት ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ሊባረኩ ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ የሚሹ ሰዎችን ገለጠላት።

ከእሳቸውም ጋራ ትሄድ ዘንድ ልቧ ተነሳሳ ከብዙ ሰዎችም ጋራ በመርከብ ተሳፈረች። ባለ መርከቦችም የመርከብ ዋጋ በጠየቋት ጊዜ ስለ መርከብ ዋጋ ያመነዝሩባት ዘንድ ሰውነቷን ሰጠቻቸው ኢየሩሳሌምም እስከ ደረሰች ይህን ስራ አልተወችም።

የክብረ ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ወደ አለች ቤተ ክርስቲያን ትገባ ዘንድ በወደደች ጊዜ መለኮታዊት ኃይል መግባትን ከለከለቻት። እርሷም ከሚገቡ ሰዎች ጋራ ትገባ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደከመች ነገር ግን ከለከላት እንጂ የጌታ ኃይል አልተዋትም።

ከዚህም በኃላ ስለ ረከሰ ስራዋ አሰበች በልቧም እያዘነችና እየተከዘች ወደ ሰማይ ወደ እግዚአብሄር አይኖቿን አቀናች በማንጋጠጥዋም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ስእል አየች።

በፊቷም አለቀሰች ፍጥረቶችን ሁሉ የምትረጅአቸው አምላክን የወለደሽ እመቤቴ ተዋሽኝ ከሁሉ ሰዎች ጋራ ገብቼ የመጣሁበትን ስራዬን የፈፀምኩ እንደሆነ ያዘዝሽኝን ሁሉ እኔ አደርጋለሁ ብላ በማመን ለመነቻት።

ቤተ ክርስቲያን ፈጥና ገባች በገባችም ጊዜ የበአሉን ስራ ፈፀመች። ከዚህም በኃላ አምላክን ወደ ወለደች ወደ እመቤታችን ወደ ከበረች ድንግል ማርያም ስእል ተመልሳ ወደ እርሷ መሪር ልቅሶ እያለቀሰች ረጅም ፀሎትን ፀለየች ነፍሰዋን ለማዳን እርስዋ ወደ ወደደችው ትመራት ዘንድ አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ስእል ከዮርዳኖስ በረሀ ብትገቢ አንቺ እረፍትንና ድኀነትን ታገኚ አለሽ የሚል ቃል ወጣ።

ከእመቤታችን አምላክን ከወለደች ከቅድስት ድንግል ማርያም ስእል ይህን ቃል ተቀብላ ወድያውኑ ወጣች። በውጪም አንድ ሰው አግኝታ ሁለት ግርሽ ሰጣትና አምባሻ ገዛችሸት።

ከዚያም በኃላ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግራ ፅኑእ ተጋድሎ እየተጋደለች በበረሀው ውስጥ አርባ ሰባት አመት ኖረች ሰይጣንም አስቀድማ በነበረችበት በዝሙት ጦር ይዋጋት ነበር።

እርሷ ግን በተጋድሎ ፀናች ከዚያም ከገዛችው አምባሻ ብዙ ቀን ተመገበች። ሁለት ሁለት ቀን ሶስት ሶስት ቀን ፁማ ከዚያ አምባሻ ጥቂት ትቀምስ ነበር በአለቀም ጊዜ የዱር ሳር ተመገበች።

በዚያችም በዮርዳኖስ በረሀ እየተዘዋወረች አርባ አባት አመት ሲፈፀምላት እንደ ገዳሙ ልማድ የከበረች አርባ ፆምን ሊፈፅም ቅዱስ ዘሲማስ ወደዚያች በረሀ መጣ። በሱ ደብር ላሉ መነኲሳት ልማዳቸው ስለሆነ በየአመቱ ወደ በረሀ ወጥተው የከበረች የአርባ ቀን ፆም እስከ ምትፈፀም በፆምና በፀሎት ተፀምደው በገድል ይቆያሉ ።

ስለዚህም ዘሲማስ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ በወጣ ጊዜ የሚፅናናበትን ያሳየው ዘንድ እግዚአብሄርን ለመነው። በበረሀውም ውስጥ ሲዘዋወር ይቺን ቅድስት ሴት ከሩቅ አያት የሰይጣን  ምትሀት መሰለችው በፀለየም ጊዜ ከሰው ወገን እንደሆነች ተገለጠለችለት።

ወደርሷም ሄደ እርሷ ግን ከእርሱ ሸሸች ወደርሷም ይደርስ ዘንድ ከኃላዋ በመሮጥ ተከተሉት። ከዚህም በኃላ ዘሲማስ ሆይ ከእኔ ጋራ መነጋገር ከፈለግህ ጨርቅን በምድር ላይ ጣልልኝ እከለልበት ዘንድ ብላ በስሙ ጠራችው።

በስሙ በጠራችውም ጊዜ እጅግ አድንቆ ጨርቁን ጣለላት ያን ጊዜም ለብሳ ሰገደችለት እርሱም ሰገደላት እርስበርሳቸውም ሰላምታ ተሰጣጥተው በላዩዋ ይፀልይላት ዘንድ ለመነችው እርሱ ካህን ነውና ካህን ሰለሆነ።

ከዚህም በኃላ ገድሏን ታስረዳው ዘንድ ቅዱስ ዘሲማስ ለመናት ከእርሷ የሆነውን ሁሉ ከመጀመሪያው እስከመጨረሻው ነገረቸው። እርሷም በሚመጣው አመት የክብር ባለቤት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስጋውንና ደሙን ከእርሱ ጋራ ያመጣላት ዘንድ ለመነችው እርሱም እሺ አላት።

አመትም በሆነ ጊዜ ስጋውንና ደሙን በፅዋ ውስጥ ያዘ ደግሞ በለስ ተምርንና በውኃ የራሰ ምስርን ይዞ ወደርሷ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ቅድስት ማርያምን በዮርዳኖስ ወንዝ ዳር ስትሄድ አያት ወደርሱም ደርሳ እርስበርሳቸው ሰላምታ ተሰጣጡ በአንድነትም ፀለዩ ከዚህም በኃላ ስጋውንና ደሙን አቀበላት።

በለሱን ተምሩንና ምስሩንም አቀረበላትና ትመገብለት ዘንድ ለመናት ስለ በረከት ከምስሩ በእጇ ጥቂት ወሰደች። ደግሞም በሁለተኛው አመት ወደእርሷ ይመለስ ዘንድ ለመነችው ።ሁለተኛ አመትም በሆነ ጊዜ ወደዚያ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ያቺ ቅድስት ሴት ሙታ አገኛት በራስጌዋም ድኀዪቱን ግብፃዊት ማርያምን ከተፈጠረችበት አፈር ውስጥ ቅበራት የሚል ፅሁፍ አገኘ።ከፅሁፉ ቃልም የተነሳ አደነቀ።

ያን ጊዜም ከግርጌዋ አንበሳን ሲጠብቃት አየ እርሱ መቃብርዋን በምን እቆፍራለሁ ብሎ ያስብ ነበር በዚያም ጊዜ ያ አንበሳ በጥፍሮቹ ምድሩን ቆፈረ የከበረ ዘሲማስም በላይዋ ፀሎት አድርጎ ቀበራት ።

ወደ ገዳሙም ተመልሶ ለመነኮሳቱ የዚችን የከበረች ግብፃዊት ማርያምን ገድሏን እንዳስረዳችው ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ነገራቸው እጅግም አደነቁ ምስጉን ልኡል እግዚአብሄርንም አመስገኑት። መላው እድሜዋም ሰማንያ አምስት ሆኗታል።

ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ †

በዚች እለት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሳኤው ሳምንት ለሀዋርያው ቶማስ ተገለጠለት በእጆቹና በእግሮቹ ውስጥ የችንካሮቹን ምልክትም አሳየው የቶማስንም እጅ ይዞ በመለኮታዊ ጉኑ ውስጥ አኖረውና በጦር የተወጋበትን ቦታ አሳየው ቶማስም  ጌታዬና ፈጣሪዬ መነሳትህን አመንኩ አለ።

ጌታችንም ብታየኝ አመንከኝ የሚመሰገንስ ሳያየኝ የሚአምንብኝ ነው ብሎ መለሰለት። በትርጓሜ ወንጌልም እንዲህ ይላል ቶማስ በመድኀኒታችን ጐን ውስጥ እጁን በአስገባ ጊዜ እጁ በመለኮት እሳት ተቃጠለ ፣በመለኮቱም ደግሞ በታመነ ጊዜ እጁ ከመቃጠል ዳነች ።

" አባታችን አዳም "

=>አባታችን አዳም የመጀመሪያው ፍጥረት (በኩረ ፍጥረት) ነው:: አባታችን አዳም:-

*በኩረ ነቢያት
*በኩረ ካኅናት
*በኩረ ነገሥትም ነው::
*በርሱ ስሕተት ዓለም ወደ መከራ ቢገባም ወልድን ከዙፋኑ የሳበው የአዳም ንስሃና ፍቅር ነው::

+አባታችን ለ100 ዓመታት የንስሃ ለቅሶን አልቅሷል:: ስለዚህ አባታችን አዳም ቅዱስ ነው:: ከሌሎቹ ቅዱሳን ቢበልጥ እንጂ አያንስም::

+ለአባታችን አዳም የተናገርነው ሁሉ ለእናታችን ሔዋንም ገንዘቧ ነው:: ዛሬ የሁለቱም የዕረፍታቸው መታሠቢያ ነው::

=>አባታችን ቅዱስ ኖሕም ከላሜሕ የተወለደው በዚሁ ቀን ነው::
=>አምላካችን እግዚአብሔር ለሰማይ ለምድሩ በቅድስናቸው ከከበዱ ወዳጆቹ በረከትን ያድለን::=>ሚያዝያ 6 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱሳን አዳምና ሔዋን (የዕረፍታቸው መታሠቢያ)
2.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት (ልደቱ)
3.አባታችን ቅዱስ ኖኅ (ልደቱ)
4.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ (የጌታችንን ጐኑን የዳሰሰበት)
5.ቅድስት ማርያም ግብፃዊት (ከኃጢአት ሕይወት ተመልሳ በፍፁም ቅድስናዋ የተመሠከረላት እናት)

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም
2.እናታችን ሐይከል
3.ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ
4.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
5.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
6.ቅድስት ሰሎሜ
7.አባ አርከ ሥሉስ
8.አባ ጽጌ ድንግል
9.ቅድስት አርሴማ ድንግል

=>+"+ እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ: ስለ ሶምሶንም: ስለ ዮፍታሔም: ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም: ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና::

እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ:: ጽድቅን አደረጉ:: የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ:: የአንበሶችን አፍ ዘጉ:: የእሳትን ኃይል አጠፉ:: ከሰይፍ ስለት አመለጡ:: ከድካማቸው በረቱ:: በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ:: የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ:: +"+ (ዕብ. 11:32-35

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
✝️ቅዱስ ዳዊት ልበ አምላክ✝️

=>ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ ይላል:- "እግዚአብሔር ለዳዊት በእውነት ማለ: አይጸጸትም::" (መዝ. 131:11) አሁን በእግዚአብሔር መጸጸት ኑሮበት አይደለም:: ቅዱስ ዳዊት የማያጸጽት ፍጹም ወዳጅ መሆኑን ሲገልጥ ነው እንጂ:: ጌታ ቅዱስ ዳዊትን "እንደ ልቤ የሆነ: ፈቃዴን የሚፈጽም: ባሪያየን ዳዊትን አገኘሁት" (መዝ. 88:20) ብሎ ሲናገር ሰምተን እጅግ አደነቅን::

+እንደ አምላክ ልብ ሆኖ መገኘት ምን ይረቅ?! ምንስ ይደንቅ?! ለዚህ አንክሮ ይገባል !! ጌታ ይቀጥልና ደግሞ "ዳዊትን እንዳልዋሸው አንድ ጊዜ በቅዱስነቴ ማልሁ" (መዝ. 88:35) ይላል:: አቤት አባታችን ዳዊት ክብር: የክብር ክብር: ውዳሴና ስግደትም ላንተ በጸጋ ይገባል እንላለን::

+ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ዳዊት 7 ሃብታት ሲኖሩት:-
1.ሃብተ ትንቢት
2.ሃብተ መንግስት
3.ሃብተ ክህነት
4.ሃብተ በገና (መዝሙር)
5.ሃብተ ፈውስ
6.ሃብተ መዊዕ (ድል መንሳት)
7.ሃብተ ኃይል ተብለው ይታወቃሉ::

+በ7ቱ ስሞቹም:-
1.ጻድቅ
2.የዋህ
3.ንጹሕ
4.ብእሴ እግዚአብሔር
5.ነቢየ ጽድቅ
6.መዘምር እና
7.ልበ አምላክ ተብሎ ይጠራል::

+"+ ልደት +"+

=>ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ስለ ልደቱ ሲናገር "እስመ ናሁ በኃጢአት ተጸነስኩ-በኃጢአት ተጸነስኩ" ይላል (መዝ. 50:5) አበው እንደ ነገሩን የቅዱስ ዳዊት አባት ደጉ እሴይ ከነገደ ይሁዳ የኢዮቤድ ልጅ ነው::

+ሚስቱን ሰሊብን አንድ ጐልማሳ በዝሙት ዐይን ሲፈልጋት ተመልክቶ ነበር:: አንድ ቀንም መንገድ ሔድኩ ብሎ ግን ያንን ጐልማሳ መስሎ ተመልሶ አብሯት አድሯል:: በዚያች ሌሊትም ቅዱስ ዳዊት ተጸንሷልና እንዲህ ብሏል::

+"+ ዕድገት +"+

=>ቅዱስ ዳዊት ከሕጻንነቱ ጀምሮ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ነበር:: ሕጸን ሳለ በእረኝነት በጐቹን አያስነካም ነበር:: አንበሳውን በጡጫ: ድቡን በእርግጫ: ነብሩን በሩጫ የያዙትን ያስጥላቸው ነበር:: በጥቂቱ በበግ እረኝነት ስለ ታመነ ለእሥራኤል እረኛ ሊሆን ተመርጧል::

+"+ መቀባት +"+

+እግዚአብሔር ሳዖልን ከናቀው በሁዋላ ከእሴይ ልጆች መካከል "እንደ ልቤ የሆነውን ቀብተህ አንግስልኝ" ቢለው ነቢዩ ሳሙኤል ቤተ ልሔም ገብቷል::

+በዚያም ከኤልያብ እስከ አሚናዳብ: 7ቱን የእሴይን ልጆች ቢፈትን አልሆነም:: በቅዱስ ሚካኤል ጠቁዋሚነት ግን ከእረኝነቱ ዳዊት ተጠራ:: ገና ከርቀት ሲመጣ የዘይት ቀርኑ ቦግ ብሎ ተከፈተ::

+በቅዱስ ዳዊት ራስ ላይም እንደ እሳት ፈላ:: በአምላክ ምርጫም በ12 ዓመቱ ንጉሥ ተባለ::

+"+ ዳዊትና ጐልያድ ++

=>ኢሎፍላውያን በጠላትነት በተነሱባቸው ጊዜም ጐልያድ የሚሉት የጌት ሰው እሥራኤልን ሲያስጨንቅ ለ40 ቀናት ቆይቶ ነበር:: ለአምላኩ ስምና ክብር የሚቀና ቅዱስ ዳዊት ግን በድፍረት ገጥሞ በፈጣሪው ኃይል: በጠጠር ጥሎታል:: ከእሥራኤልም ሽሙጥን አርቁዋል:: ግን ቅዱሱ ብላቴና: ጐልያድ ደግሞ 6 ክንድ (3 ሜትር) የሚረዝም ሰው ነበር::

+"+ ስደት +"+

=>ቅዱስ ዳዊት ንጉሥ እንዲሆን ተቀብቶ ዙፋን አልጠበቀውም:: ጠላታቸውን ጥሎ ስላዳናቸው ፈንታ: ሳዖልን በገና እየደረደረ ስለ ፈወሰው ፈንታም ሊገደል ተፈለገ:: ፈጣሪው ከእርሱ ጋር ባይሆንም ይገድሉት ነበር::

+እርሱ ግን ለ18 ዓመታት በትእግስት ተሰደደ:: ከአንዴም ሁለት ሦስቴ ጠላቱን ሳዖልን አሳቻ ሥፍራ ላይ አግኝቶ በምሕረት ተወው:: በዚህ የዋሕነቱም በብሉይ ሆኖ "ጠላቶቻችሁን ውደዱ" የምትለውን ሕግ ፈጸማት:: (ማቴ. 7:45, መዝ. 16:4)

+"+ ንግሥና +"+

=>ቅዱስ ዳዊት የስደት ዘመኑ ሲፈጸም ሳዖል ሞተ:: ምን ጠላቱ ቢሆን 'የሳዖል ገዳይ ነኝ' ያለውን ተበቀለ:: ስለ ጠላቱም አለቀሰ:: 30 ዓመት ሲሆነው ነግሦ ለ7 ዓመታት በኬብሮን: ለ33 ዓመታት በኢየሩሳሌም (ጽዮን) ሕዝበ እግዚአብሔርን ጠብቁዋል::

+በዘመኑም ጠላቶቹን ሁሉ ድል አድርጉዋል:: በልጁ አቤሴሎም እጅ መሰደድን: በሳሚ ወልደ ጌራ መሰደብንም ታግሷል::

+"+ ንስሃ +"+

=>ቅዱሱ ንጉሥ ሁሉ ነገር የተሰጠው አባት ነው:: ሁሉ ሕይወቱም ለእኛ ት/ቤት ነው:: ሰው ነውና የኦርዮን ሚስት ቀምቶ: ኦርዮን አስገድሎ ነበር:: ጉዳዩን ነቢዩ ናታን በምሳሌ ሲነግረው ፍጹም ተጸጸተ::

+ማቅ ለብሶ: አመድ ነስንሶ አለቀሰ:: መሬትንም በእንባው ክንድ አራሳት:: ሐረግ እስከ ማብቀልም ደረሰ:: እግዚአብሔርም ንስሃውን ተቀብሎ ከፍ ከፍ አደረገው:: በንስሃ ለምትገኝ ጸጋም ምሳሌ ሆነ::

+"+ ነቢይነት +"+

=>በቤተ ክርስቲያን ትምሕርት ቅዱስ ዳዊትን የሚያህል ነቢይ (ምሥጢር የበዛለት) አልተገኘም:: 'ከዓለም በፊት እንዲህ ነበረ' ብሎ: ከዚያ ከስነ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽዓት የተናገረ እርሱ ነው::

+ስለ መላእክት: ነቢያት: ሐዋርያት: ጻድቃን: ሰማዕታት: ደናግልና መነኮሳት ሁሉ መናገሩ ይደነቃል:: ስለ ድንግል ማርያምና ስለ መድኃኒታችን ክርስቶስም አምልቶ: አስፍቶ ተናግሯል:: 150 ምዕራፎች ባሉት መጽሐፈ ትንቢቱ ኃላፍያትንና መጻዕያትን ተመልክቷል::

+ስለዚህም አበው:-
"አልቦ ምስጢር ወአልቦ ትንቢት:
ዘኢተናገረ አቡነ ዳዊት" ይላሉ::

+"+ መዝሙር +"+

=>ቅዱሱ ነቢይና ንጉሥ በጣም የሚታወቀው በዝማሬው ነው:: ለራሱ ባለ 10 አውታር : ለመዘምራኑ ደግሞ ባለ 8 አውታር በገናን አዘጋጅቶ ፈጣሪውን ያመሰግን ነበር:: 24 ሰዓት ሙሉ ስብሐተ እግዚአብሔር እንዳይቁዋረጥ 288 መዘምራንን በአሳፍ መሪነት መድቦ ነበር::

+ራሱም በፍጹም ተመስጦ: ማር ማር እያለው እግዚአብሔርን ያመሰግነው ነበር:: "ቃልህ ለጉረሮየ ጣፋጭ ነው" እንዲል:: (መዝ. 118:103) የዳዊት መዝሙሩ ለአጋንንት ትልቅ ጠላት ነው:: ቅዱሳን መላእክትም በዳዊት መዝሙር ይዘምራሉ::
"በዘቦቱ ይሴብሑ ሰማያውያን ወምድራውያን" እንዲል::

+"+  #‎ዳዊትና  ጽዮን +"+

=>ቅዱስ ዳዊት ጽዮንን አንጾ ጽላተ ኪዳኑን አመጣ:: ለአምላከ ያዕቆብ ማደሪያን ሊፈልግም ዐይኑ ከእንቅልፍ ተከለከለ:: (መዝ. 131:2) የፈጣሪውን ፈቃድ ሊጠይቅ ሱባኤ ቢገባ "አኮ አንተ ዘትነድቅ ሊተ ቤተ - አንተ ሳትሆን የሚሠራልኝ ልጅህ ነው" አለው::

*አያይዞም የምሥጢረ ሥጋዌን ነገር ቢገልጥለት "ናሁ ሰማዕናሁ በኤፍራታ - እነሆ በኤፍራታ ሰማነው" ሲል ተናግሯል:: (መዝ. 131:6) የኪዳኑ ጽላት (ጽዮን) ከአቢዳራ ቤት ስትመጣ ከዙፋኑ ወርዶ: ከተራው ሕዝብ ጋርም ተቀላቅሎ በበገናና በመሰንቆ ተጫወተ::

*ስለ ፈጣሪው ክብሩን ተወ:: ከዳን እስከ ቤርሳቤህ የሚገዛ ኃያል ንጉሥ ነበርና:: በጽዮን ፊት እየወደቀ: እየተነሳ: እየታጠቀ: እየፈታ ሲዘምርም ሚስቱ ሜልኮል ናቀችው:: እግዚአብሔር ግን ከፍ ከፍ አደረገው:: (ሳሙ. 6:16)

+"+ ክብረ  #‎ዳዊት  +"+

=>እግዚአብሔር ስለ ዳዊት ሲል ኢየሩሳሌምን ብዙ ጊዜ ታድጉዋል:: ሰሎሞንና ሕዝቅያስን (ነገሥታቱን) ይቅር ያላቸው ስለ ባለሟሉ ስለ ዳዊት ነው::

*የሐዲስ ኪዳን የመጀመሪያዋ ቃል "የዳዊት ልጅ . . . " የምትል ናት:: (ማቴ. 1:1) ጌታችን "ወልደ ዳዊት" መባልን ወዷልና:: እንዲያውም ራሱ "እኔ የእሴይ ሥርና የዳዊት ዘር ነኝ" ሲል ተናግሯል:: (ራዕ. 22:16)

+"+ ዕረፍት +"+=>ነቢየ ጽድቅ: ልበ አምላክ ቅዱስ #ዳዊት እሥራኤልን ለ40 ዓመታት መርቶ አረጀ:: 'ምነው ያ ኃያል የእግዚአብሔር ሰው ቶሎ አረጀ?' ቢሉ ከገድሉ ጽናት ሰውነቱ ተቀጥቅጦ ነበርና::
*በዚያውም ላይ አንድ ቀን ስለ ሕዝበ አሥራኤል ቤዛ ይሆናቸው ዘንድ በቀሳፊ መልአክ ፊት ቆሞ ነበርና (ዜና. 21:16) ሰውነቱ ደከመ:: በዚህ ጊዜም ልጁን ሰሎሞንን አንግሦ በ70 ዓመቱ ከክርስቶስ ልደት ሺህ ዓመት በፊት ዐርፏል::

+"+ #ዳዊት በሰማይ +"+

=>በራዕየ ጐርጐርዮስ እንደ ተጻፈው ቅዱስ ዳዊትን በሰማይ 99ኙ ነገደ መላእክት ከበውት ያመሰግናል:: ከርሱ ዝማሬ ግርማ የተነሳ የሰማያት ግዘፋቸው ይናወጻል:: በገድለ አቡነ ኪሮስ እንደ ተጻፈው ደግሞ ቅዱሳን ነፍሳቸው ከሥጋቸው የምትለየው በዳዊት በገና ጣዕመ ዝማሬ ነው::

*በነገረ ማርያም ትምሕርት ደግሞ የቅዱስ ዳዊት ቤቱ ከልዑል አምላክ መንበር ሥር ነው::

*እንግዲህ ምን እላለሁ! ስለ ቅዱስ ዳዊት ከዚህም በላይ መጻሕፍት ብዙ ይላሉ:: ክብሩ ታላቅ ነውና::

<< በእውነት . . . በእውነት . . . በእውነት . . . ያለ ሐሰት ለዳዊት ክብርና ምስጋና ይገባል >>

=>+"+ እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ: ስለ ሶምሶንም: ስለ ዮፍታሔም: ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም: ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና::

እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ:: ጽድቅን አደረጉ:: የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ:: የአንበሶችን አፍ ዘጉ:: የእሳትን ኃይል አጠፉ:: ከሰይፍ ስለት አመለጡ:: ከድካማቸው በረቱ:: በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ:: የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ:: +"+ (ዕብ. 11:32-35

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን †††

††† እንኩዋን ለጻድቅ ሰው "ቅዱስ ኢያቄም" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ †††

+*" ቅዱስ ኢያቄም "*+

=>ቅዱስ ሰው ኢያቄም የሰማይና የምድር ንግስት እመቤታችን ድንግል ማርያም አባት ነው:: ቅዱሱ ከቅስራ አባቱ የተወለደ የቅዱስ ዳዊት ዘመድ ሲሆን "ኢያቄም : ሳዶቅ እና ዮናኪር" በሚባሉ 3 ሰሞቹ ይታወቃል::

+ቅዱስ ኢያቄም እንደ ኦሪቱ ሥርዓት አድጎ : ከነገደ ሌዊ የተወለደች : የማጣትና ("ጣ" ጠብቆ ይነበብ) ሔርሜላን ልጅ ሐናን አግብቷል:: ሁለቱም በንጽሕናና በምጽዋት እንደ ሕጉ ቢኖሩም መውለድ የማይችሉ መካኖች ነበሩ::

+በዚሕ ምክንያት ከወገኖቻቸው ሽሙጥን ታግሰው በታላቅ ሐዘን ኑረዋል:: ከጊዜ በሁዋላ ግን ስም አጠራሯ የከበረ : ደም ግባቷ ያማረ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔር መረጣቸውና ከተባረከ ሰውነታቸው ድንግል ማርያምን ወለዱ::

+እርሷ "ወላዲተ አምላክ" ተብላ እነርሱን "የእግዚአብሔር የሥጋ አያቶች" አሰኘቻቸው:: ቅዱስ ኢያቄም እመቤታችንን ቤተ መቅደስ ካስገቡ ከጥቂት ዓመታት በሁዋላ በመልካም ሽምግልና አርፎ ከቅድስት ሐና ጋር በጌቴሴማኒ ተቀብሯል::

+ቅዱሱ ሰው ያረፈበት ዓመት ግልጽ ባይሆንም ድንግል እመቤታችን 8 ዓመት ሲሞላት 2ቱም ቅዱሳን ወላጆቿ በሕይወተ ሥጋ እንዳልነበሩ አበው ነግረውናል:: በማረፍ ደግሞ ቅድስት ሐና ትቀድማለች:: መቃብሩ ዛሬ ድረስ አለ:: ያደለው ከቦታው ደርሶ ይሳለመዋል::

=>አምላካችን ከቅዱስ ኢያቄም በረከት ያሳትፈን::

=>ሚያዝያ 7 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ኢያቄም (የድንግል ማርያም አባት)
2.ቅዱስ አጋቦስ ሰማዕት
3.ቅድስት ቴዎድራ ሰማዕት
4.ቅዱስ አባ መቅሩፋ ጻድቅ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ሥሉስ ቅዱስ (አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ)
2.አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
3.አባ ሲኖዳ (የባሕታውያን አለቃ)
4.አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
5.አባ ባውላ ገዳማዊ
6.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
7.ቅዱስ አግናጥዮስ (ለአንበሳ የተሰጠ)

=>+"+ መሠረቶቿ በተቀደሱ ተራሮች ናቸው::
ከያዕቆብ ድንኩዋኖች ይልቅ እግዚአብሔር የጽዮንን ደጆች ይወዳቸዋል::
የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ በአንቺ የተደረገው ነገር ድንቅ ነው . . .
ሰው እናታችን ጽዮን ይላል::
በውስጥዋም ሰው ተወለደ::
እርሱ ራሱም ልዑል መሠረታት:: +"+ (መዝ. 86:1-6)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
እንኩዋን ለቅዱሳት ደናግል ዓመታዊ የሰማዕትነት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱሳት ደናግል "*+

=>ቅዱሳት ደናግሉ አጋሊዝ (አጋሊስ): ኢራኒና ሱስንያ ይባላሉ:: በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ አካባቢ ተሰሎንቄ የምትባል ሃገር ውስጥ ይኖሩ ነበር:: ሦስቱም እጅግ ቆንጆዎችና ከብዙ ወንዶች ዐይን የሚገባ መልክ ቢኖራቸውም የእነርሱ ምርጫ ግን ሰማያዊ ሙሽርነት ነበርና በጾምና በጸሎት ተወሰኑ::

+ለብዙ ዓመታትም ደናግሉ በሚኖሩበት ደብር ውስጥ በቅድስና ኑረዋል:: ከቆይታ በሁዋላ ያ የመከራ ዘመን (ዘመነ ሰማዕታት) ሲመጣ ለጊዜውም ቢሆን ወደ በርሃ ሸሽተው ተቀመጡ::

+ያሉበትን ቦታ የምታውቅ አንዲት ደግ ባልቴት እየሔደች ትጎበኛቸው : በእጃቸው የሚሠሩዋቸውን የተለያዩ እቃወችንም እየሸጠች እኩሉን በስማቸው መጽውታ በተረፈው ለራት የሚሆን ደረቅ ቂጣ ትገዛላቸው ነበር::

+አንድ ቀን ግን አንድ አረማዊ ሰው ተከትሏት መጥቶ በማየቱ 3ቱንም ደናግል ወደ ከሐዲው ንጉሥ አቀረባቸው:: ንጉሡ ሃይማኖታቸውን ቢክዱ የሐብትና የስልጣን ተስፋ እንዳላቸው ነገራቸው:: ደናግሉ ግን በፍቅረ ክርስቶስ በመጽናታቸው ከብዙ ስቃይ በሁዋላ በዚሕች ቀን አስገድሏቸዋል::

=>የጌታችን በጐ ምሕረቱ በሁላችን ትደርብን:: ከደናግሉ በረከትን ያሳትፈን::

=>ሚያዝያ 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱሳት ደናግል አጋሊዝ: ኢራኒና ሱስንያ
2."150" ቅዱሳን ሰማዕታት (ፋርስ (ኢራን) ውስጥ የተሰየፉ)
3.አባ ጢሞቴዎስ ሊቀ ዻዻሳት

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት
2.ኪሩቤል (አርባዕቱ እንስሳ)
3.አባ ብሶይ (ቢሾይ)
4.አቡነ ኪሮስ
5.አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን
6.ቅዱስ ማትያስ ሐዋርያ (ከ12ቱ ሐዋርያት)

=>+"+ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ: ወይስ ጭንቀት: ወይስ ስደት: ወይስ ራብ: ወይስ ራቁትነት: ወይስ ፍርሃት: ወይስ ሰይፍ ነውን?
'ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን:: እንደሚታረዱ በጐች ተቈጠርን'
ተብሎ እንደ ተጻፈ ነው::
በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን:: +"+ (ሮሜ. 8:35-38)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

https://t.me/zikirekdusn
††† እንኳን ለብጹዐን ጻድቃን: ቅዱስ ዞሲማስ እና አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ብጹዐን ጻድቃን †††

††† በዚህ ቀን ብሔረ ብጹዐን ውስጥ የሚኖሩ ጻድቃን ይታሠባሉ::
በሃይማኖት ትምሕርት 5 ዓለማተ መሬት አሉ:: እነሱም አቀማመጣቸው ቢለያይም ከላይ ወደ ታች:-
1.ገነት (በምሥራቅ)
2.ብሔረ ሕያዋን (በሰሜን)
3.ብሔረ ብጹዐን (ብሔረ - አዛፍ - እረፍት) {በደቡብ}
4.የእኛዋ ምድር (ከመሐል) እና
5.ሲዖል (በምዕራብ) ናቸው::

††† ከእነዚሕ ዓለማት ባንዱ የሚኖሩ የብሔረ ብጹዐን ጻድቃን:-
*ኃጢአትን የማይሠሩ::
*ለ1,000 ዓመታት የሚኖሩ::
*ሐዘን የሌለባቸው::
*በዘመናቸው 3 ልጆችን ወልደው (2 ወንድና አንድ ሴት) ሁለቱ ለጋብቻ: አንዱን ለቤተ እግዚአብሔር አገልግሎት የሚያውሉ ሰዎች ናቸው::

††† ቅዱሳኑ ወደዚሕ ቦታ የገቡት በነቢዩ ኤርምያስ እና በቅዱስ እዝራ ዘመን ሲሆን አንዴ የተወሰኑት በዘመነ ሰማዕታት ወጥተው በዚሕ ቀን ተሰይፈዋል::

††† በመጨረሻ ግን በሐሳዌ መሲሕ ዘመን ወጥተው ሰማዕትነትን ይቀበላሉ::

††† የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሕረቱና ይቅርታው ለምናምን ሁሉ ይደረግልን:: ከደግነታቸውም በረከትን አይንሳን::

+*" አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ "*+
=>አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ :
እናታቸው ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ
ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለት
ተነስተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ "ስብሐት ለአብ
: ስብሐት ለወልድ : ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ" ብለው
አመስግነዋል፡፡
+የስማቸው ትርጓሜ "የአብ : የወልድ : የመንፈስ ቅዱስ
እስትንፋስ" : አንድም "የክርስቶስ እስትንፋስ" ማለት ነው፡፡
ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ
እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን
ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጽሐፍት
ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው
ዐውቀዋል፡፡
+በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ
ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን
ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ
መጥቶ ባህሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተክርስቲያን
ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመትም በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት
እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት : ለአባቶች
መነኮሳት ምግብ ሊሆናቸው ከባህር ውስጥ አሳን
በማውጣት አገልግለዋል፡፡
+አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት
ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ
ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው
ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና
ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት
ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡
+አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ
ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና
ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተ ክርስቲያን
አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመስዋዕት
ወይኑን ለቁርባን በታምራት አድርሰዋል፡፡
+አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል
ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን
ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡
ጌታንም በቅዱሳኖቹ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ
መልአኩን ‹‹ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ
ኢየሩሳሌም አድርሰው›› ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ
ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡ ሁሉንም የኢትዮጵያን
ቅዱሳት ገዳማትንም ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ
የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው
ነበር፡፡
+ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን
እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያስነሱ
ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ
ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው
የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ
ጌታችን መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ
እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን
ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ›› በማለት በሞት
የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡
+ጻድቁ ወደ ደብረ አስጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ
ልትገባ ስትል ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም
አውግዤሻለሁ፡፡ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ
አሁን ቀጥ ብለሽ ቁሚ›› ብለው ገዝተው ፀሐይን
አቁመዋል፡፡
+አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አስጋጅ ሲደርሱ
ፀሐይ አፍ አውጥታ ‹‹አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ
ዘንድ ፍታኝ›› ስትላቸው ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ባሏት
ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት
አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡
+በአምላክ ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ፣
በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ
መልክአ ኢየሱስ ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤
እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል
ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች
በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ
የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡
በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት
ይደግማሉ፡፡
+ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ
እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን
ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ
ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔ ዓለምን
የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን
የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም
የሆነች ጸሎት "ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም" ብሎ
የሚጠራጠር ቢኖር ግን መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡
+ጻድቁ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ታህሳስ 9 ቀን ተወልው
ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ (ገድለ አቡነ
እስትንፋሰ ክርስቶስ)
=>አምላከ ቅዱሳን በጻድቁ አማላጅነት ሃገራችንን
ይጠብቅልን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

††† ሚያዝያ 9 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱሳን የብሔረ ብጹዐን ጻድቃን
2.አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ጻድቅ (ኢትዮዽያዊ)
3.ቅዱስ ዞሲማስ ገዳማዊ (ብሔረ ብጹዐንን ያየ እና ዜናቸውን የጻፈ አባት)
4.ቅዱስ ኤስድሮስ ሕጻን ሰማዕት (ገና በ10 ወር ዕድሜው ሰማዕት የሆነ)
5.አባ ሱንቱዩ ሊቀ ዻዻሳት

††† ወርሐዊ በዓላት
1.አባ በርሱማ ሶርያዊ (ለሶርያ መነኮሳት ኁሉ አባት)
2."318ቱ" ቅዱሳን ሊቃውንት (ርቱዐነ ሃይማኖት ዘኒቅያ)
3.አባ መልከ ጼዴቅ ዘሚዳ (ኢትዮዽያዊ)

††† "ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና በመጠን ኑራችሁ: ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ:: እንደሚታዘዙ ልጆች ባለ ማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ምኞት አትከተሉ:: ዳሩ ግን 'እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ' ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሯችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ::" †††
(1ዼጥ. 1:13-15)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
†††  እንኳን ለአባ ይስሐቅ ጻድቅ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† አባ ይስሐቅ ጻድቅ †††

††† ጻድቁ ግብጻዊ ሲሆኑ የነበሩት በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: በጊዜው ዝነኛ ከነበሩት ከታላቁ አባ ዕብሎ (ቅዱስ ዕብሎይ) ተምረዋል:: መማር ብቻ ሳይሆንም ለ25 ዓመታት ያለ መታከት በተልዕኮ አገልግለዋል::

በእነዚህ ጊዜያትም ትሕርምትን : ተጋድሎን : ትምህርተ ቅድስናንና ሌሎች አስፈላጊ መንፈሳዊ ስንቆችን ሰንቀዋል:: በመታዘዛቸው በምድር አበውን : በሰማይ እግዚአብሔርን አስደስተዋል:: በዚህም ከእግዚአብሔር ጸጋውን : ከአበው ምርቃትን አትርፈዋል::

ጊዜው ደርሶም ታላቁ ዕብሎ ሲያርፉ አባ ይስሐቅ በዓት ለይተው ደንበኛውን ተጋድሎ ጀምረዋል:: አምላካቸውን ለማስደሰትና በቅድስና ለመዝለቅም የአርምሞ ሰው ሁነዋል:: ለሚገባው ነገር ካልሆነ በቀር አያወሩም:: ምላሽም አይሰጡም:: "ለምን?" ሲባሉ
1."ለሁሉም ጊዜና ቦታ አለው::"
2."ሰው በከንቱ በማውራቱ ከጸጋ እግዚአብሔር ይርቃል" ይሉ ነበር::

አባ ይስሐቅ የክርስቶስ መድኃኒታችንን ሕማማት ለማዘከር ሁሌ ያነቡ (ያለቅሱ) ነበር:: ቅዳሴ ሲያስቀድሱ እጃቸው የሁዋሊት ታስሮ ነበር:: ቅዱሱ ሰው ለአዝማናት እንዲህ ተመላልሰው በመልካም ዕርግና ያረፉት በዚህ ቀን ነው::

††† አምላከ ቅዱሳን ከበረከታቸው አይለየን::

††† ሚያዝያ 10 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ አባ ይስሐቅ ገዳማዊ (የታላቁ ዕብሎይ ደቀ መዝሙር)
2.አባ ገብርኤል ሊቀ ዻዻሳት

††† ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ናትናኤል ሐዋርያ
2.ቅዱስ ኒቆላዎስ ዘሃገረ ሜራ
3.ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ጻድቅ ንጉሥ
4.አቡነ መልክዐ ክርስቶስ
5.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ እልፍዮስ)
6.ቅድስት ዕሌኒ ንግስት
7.ቅዱስ ዕፀ መስቀል

††† "የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ: የያዕቆብም ወንድም የሆነ ይሁዳ በእግዚአብሔር አብ ተወደው: ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀው ለተጠሩ:
ምሕረትና ሰላም: ፍቅርም ይብዛላችሁ::
ወዳጆች ሆይ! ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኩዋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ::" †††
(ይሁዳ. 1:1)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Forwarded from 🟢ናታኒም ፖሮሞሽን🟢
🔹 ✥● ከሚከተሉት ውስጥ ቅድስት ሃገራችን ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ከሚለው መጠርያ ስሟ ሌላ በየትኛው ትጠራ ነበር?? ✥●
Forwarded from 🟢ናታኒም ፖሮሞሽን🟢
💍ከጋብቻ በፊት ሩካቤ (sex) መፈጸም ምን ችግር አለው⁉️

💁‍♂ከትዳር በፊት መሳም (ከንፈር ወዳጅ /kiss) ይቻላልን⁉️

👨‍🦱🧑‍🦳ፍቅረኛሞቹ እጅግ በጣም ስለሚውዋደዱ (ሩካቤ/sex) ቢፈጽሙ ምን ችግር አለው⁉️

⛪️በቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ ከተዋደዱ በኋላ ስሜታቸው ይገደባል⁉️

🤵‍♂የስሜት መግለጫዎች መፈጸም ይቻላል⁉️

በነዚህ ትምህርቶች ዙሪያ እየተማርን እንገኛለን
እርሶም እውቀቱ እዲኖርዎ ከፈለጉ ይህን ማስፈንጠሪያ Link ጠቅ ያድርጉት
                👇👇👇
     @EOTC_-OPEN_channel
     @EOTC_-OPEN_channel
     @EOTC_-OPEN_channel
     @EOTC_-OPEN_channel



👇🏽🔻 𝒔𝒖𝒃𝒔𝒄𝒓𝒊𝒃𝒆 𝒏𝒐𝒘 🔻👇🏽
         የይቱብ ቻናላችን
             🔔
  🔺 𝒔𝒖𝒃𝒔𝒄𝒓𝒊𝒃𝒆 𝒏𝒐𝒘🔺‌‌

❤️በናታኒም ቲዩብ❤️
         👇🏽👇🏽
https://youtu.be/PYhgHxupzLI?si=pQaqogjyjDUcNXW
https://youtu.be/PYhgHxupzLI?si=pQaqogjyjDUcNXW