መዝገበ ቅዱሳን
24.2K subscribers
1.97K photos
9 videos
6 files
26 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
👉🏼 #ብፁዕ_ወቅዱስ_አቡነ_ማትያስ ለብፁዕ ወቅዱስ #አቡነ_መርቆርዮስ ማረፊያ ቤት ግንባታ የመሰረት ደንጊያ አኖሩ።
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ማረፊያ ቤት ግንባታ ዛሬ ጥቅምት 19 /2014ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የመሰረት ደንጋይ አኖሩ።
•••
በተያያዘ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ መንግስት በሰጠው ከቀረጥ ነጻ እድል ለቅዱስነታቸው መገልገያ የተገዛውን ዊልቸር አክሰስ ሃይሩፍ መኪና ቁልፍ አስረክበዋል።
•••
በሥነ ሥርዓቱ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የሲዳማ ጌዴኦ ቡርጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከሀገር ውስጥ እና ከመላው ዓለም የመጡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ተገኝተዋል፡፡
@EotcLibilery
@EotcLibilery
@EotcLibilery
Channel photo updated
#ጥቅምት_21

ጥቅምት ሃያ አንድ በዚህችም ቀን #እመቤታችን_ተአምራትን_አድርጋ_ሐዋርያው_ማትያስን ከእሥራት ቤት ያወጣችበት፣ #የነቢይ_ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ፣ የማርታና የማርያም ወንድም #የቅዱስ_አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት፣ የቅዱስ አባት #አባ_ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም እረፍት ነው፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#እመቤታችን_ለሐዋርያው_ማትያስ_ያደረገችለት_ተአምር

በዚህችም ቀን እመቤታችን ማርያም ተአምራትን አድርጋ ደቀ መዝሙር ማትያስን ከእሥራት ቤት አዳነችው።

የከበሩ ቅዱሳን ወንጌልን በዓለም ዞረው ይሰብኩ ዘንድ ዕጣ ሲጣጣሉ ለቅዱስ ማትያስ ዕጣ የደረሰው ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ነበር፡፡ ይህችም ሀገር እስኩቴስ የተባለች ሩሲያ እንደሆነች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ፍንጭ ሰጥተዋል፡፡

ማትያስም እነዚህ ሰውን የሚበሉ ሰዎች አገራቸው እንደደረሰ ዐይኑን አውልቀው አሠሩት፡፡ ምግባቸውም የመጻተኛ ሰው ሥጋ ነው፡፡ በልማዳቸው መሠረት መጻተኛን ሰው ገና እንደያዙት ዐይኖቹን ዐውልቀው በእሥር ቤት ያኖሩታል፡፡ እስከ 30 ቀንም ድረስ ሳር እያበሉ ያስቀምጡትና በ30ኛው ቀን አውጥተው አርደው ይበሉታል፡፡

ሐዋርያው ማትያስንም በልማዳቸው መሠረት ዐይኖቹን አውልቀው አሠሩት፡፡ ሐዋርያውም በእሥር ቤት ሆኖ በዚያ ላይ ዐይኖቹን ታውሮ ሳለ በጭንቅ ወደ ጌታችንና ወደ እመቤታችን ይለምን ነበር፡፡ ነገር ግን እመብርሃንና ልጇ መድኃኔዓለም 30ኛው ቀን ሳይፈጸም ሐዋርያው እንድርያስን ወደ እርሱ ላኩለት፡፡ ማትያስም ዐይኑን ፈወሱለትና ማየት ቻለ፡፡

እንድርያስም በተዘጋው በር በተአምራት ገብቶ አሥርቤቱ ውስጥ ያሉ እሥረኞችን በስውር አውጥቶ ከከተማው ውጭ ካስቀመጣቸው በኋላ ሁለቱ ሐዋርያት ተመልሰው ሰውን ለሚበሉት ሰዎች ተገለጡላቸው፡፡ እነርሱም ይዘው በአንገታቸው ገመድ አግብተው ለ3 ቀን በሀገራቸው ጎዳናዎች ላይ ሁሉ ጎተቱዋቸው፡፡ ሁለቱም ሐዋርያት በጸሎታቸው ከእሥር ቤቱ ምሰሶ ሥር ውኃ አፈለቁና ውኃው ሀገራቸውን ሁሉ እስኪያጥለቀልቅና ሰዎቹንም እስከ አንገታቸው ድረስ እስከሚደርስ ሞላ፡፡ ሁሉም በተጨነቁ ጊዜ ሁለቱ ሐዋርያት በፊታቸው ተገለጡና ‹‹በጌታችን እመኑ ትድናላችሁ›› በማለት ወንጌልን ሰብከውላቸው አሳመኗቸው፡፡ ምሥጢራትንም ሁሉ ገለጡላቸው፡፡ ደግሞም የአራዊት ጠባይን ከሰዎቹ ያርቅላቸው ዘንድ ወደ ጌታችንና ወደ ተወደደች እናቱ ከጸለዩ በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው፡፡ ያ የአውሬነት ጠባያቸውም ጠፍቶላቸው የዋህ፣ ቅንና ሩኅሩኆቸ ሆኑ፡፡ ሐዋርያትም ሃይማኖትን እያስተማሯቸው 30 ቀን አብረዋቸው ከተቀመጡ በኋላ አገልጋይ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ካህናትንና ዲያቆናትን ሾመውላቸው ወደ ሌላ ሀገር ሄዱ፡፡

ለሐዋርያት ሞገሳቸው ጣዕመ ስብከታቸው የኾነች ክብርት እመቤታችን ለእኛም ትለመነን!

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኢዩኤል_ነቢይ

ዳግመኛም በዚህችም ቀን የነቢይ ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም የእስራኤልን ልጆች የሚያስተምርና የሚገሥጻቸው ነበር ስለ ክርስቶስም በኢየሩሳሌም መኖርና ማስተማር ትንቢት ተናገረ። ደግሞም ስለ መከራው በሐዋርያትና በሰባ ሁለቱ አርድእት በሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ላይ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ እንዲህ ሲል ተናገረ።

ከዚህ በኋላ በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ ከመንፈሴ አሳድርበታለሁ ሴቶች ልጆቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ ትንቢትን ይናገራሉ አለቆቻችሁ ሕልምን ያልማሉ ጎልማሶቻችሁም ራእይን ያያሉ። ሁለተኛም እንዲህ አለ ያን ጊዜ ከተራራው ማር ከኮረብታውም ወተት ይፈሳል በቤተ እግዚአብሔር አጠገብ ካሉ ከይሁዳ አገሮች ሁሉ ምንጩ ከላይ ወደታች ይፈሳል።

ሙታን በሚነሡ ጊዜ ስለሚሆነው የፍርድ ሰዓት እንዲህ አለ ፀሐይና ጨረቃ ይጨልማሉ የከዋክብትም ብርሃናቸው ይጠፋል። የትንቢቱንም ወራት አድርሶ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አልዓዛር የማርታና የማርያም ወንድም

በዚችም ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው የቅዱስ አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት ሆነ።

ከክርስቲያን ነገሥታትም አንዱ ሥጋው በቆጵሮስ እንዳለ በሰማ ጊዜ ከቆጵሮስ ደሴት ወደ ቊስጥንጥንያ አፈለሰው። ሊአፈልሱትም በወደዱ ጊዜ በከበረ የደንጊያ ሣጥን ውስጥ ሁኖ በምድር ውስጥ ተቀብሮ አገኙት በላዩም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ነበረ ይህ በመቃብር ውስጥ አራት ቀን ከኖረ በኋላ ከሙታን ለይቶ ላስነሣው ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ የሆነ የቅዱስ አልዓዛር ሥጋ ነው።

ይህንንም በአዩ ጊዜ ደስ ተሰኙበት ተሸክመውም ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ወሰዱት ካህናቱም ሁሉ ወጥተው በታላቅ ክብር በመዘመርና በማመስገን ተቀበሉት በአማረ ቦታም አኖሩት በዚችም ቀን በዓልን አደረጉለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘኢየሩሳሌም

በዚህችም ቀን ለከበረች አገር ኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ እግዚአብሔርን በሚወድ የንጉሥ ሰይፈ አርዕድ ደግሞ ቈስጠንጢኖስ ለሚባል ልጁ በሆነ በንጉሣችን በዳዊት ዘመን አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከምስር አገር ታላላቆች እግዚአብሔርን የሚፈሩ የክርስቲያኖች አባቶች ልጅ ነው። የዲቁና መዓረግንም ለመሾም እስከ ተገባው ድረስ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። ከዚህም በኋላ በዲቁናው ሹመት አገልግሎቱን በአሳመረ ጊዜ የቅስና መዓረግ የሚገባው ሁኖ ቅስና ተሾመ።

በጾም በጸሎት እግዚአብሔርንም በመፍራት የተጠመደ ሁኖ ድኆችንና ችግረኞችን የሚወዳቸው የሚረዳቸው ሆነ ያን ጊዜ የሐዋርያት የሆነች የጵጵስና ሹመት የምትገባው ሁና በከበረች አገር በኢየሩሳሌም በእግዚአብሔር ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ሕዝቡንም በፈሪሀ እግዚአብሔርና በትሕትና የሚያስተምራቸው ሆነ።

እነርሱም ስለ ቅድስናው እጅግ የሚወዱት ሆኑ መልኩና የአንደበቱ አገላለጥ እንደ እግዚአብሔር መልአክ ያማረ ነበር። በሹመቱም ጥቂት ዘመናት ከኖረ በኋላ ከመንበረ ሢመቱ እስከ አራቀው ድረስ በላዩ ሰይጣን ምክንያትን አመጣ።

ይህም እንዲህ ነው በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ማርቆስ ዘመን በግዛቱ ውስጥ ያሉ እስላሞች ስለ ዐመፁበት የኢትዮጵያ ንጉሥ ፈጅቷቸው ነበርና ስለዚህ በግዛቱ ውስጥ በሚኖሩ እስላሞች ላይ ክፉ እንዳያደርግ ለኢትዮጵያ ንጉሥ መልእክት እንዲልክ ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን የምስር ንጉሥ አዘዘው።

አባ ማርቆስም ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥ ስለሚላኩ ሰዎች ከመኳንንቱ ከኤጲስ ቆጶሳቱና ከሀገር ታላላቆች ሽማግሌዎች ጋር ተማክሮ እሊህን ብሩሀን ከዋክብት የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስን የምስር ኤጲስቆጶስ አባ ሳዊሮስን በእውቀታቸው በአስተዋይነታቸውና በቅድስናቸው መረጡአቸው ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥም ይሔዱ ዘንድ ግድ አሏቸው።

እነርሱም ታዛዦች ሁነው ወደ ኢትዮጵያ መጡ የኢትዮጵያ ንጉሥም መምጣታቸውን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው እሊህንም ቅዱሳን አባቶች ይቀበሏቸው ዘንድ አሽከሮቹን በቅሎዎችን አስይዞ ላከ በመጡም ጊዜ በታላቅ ደስታ ሰላምታ አቀረበላቸው ከእርሳቸውም ቡራኬን ተቀበለ ታላቅ ክብርንም አከበራቸው ። እነርሱም የሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ተቀብሎ አንብቦ ለሊቀ ጳጳሳቱ ቃል ታዛዥ መሆኑን ገለጠላቸው።
ከዚህም በኋላ ወደ ሀገረ ስብከታቸውና ወደ ሕዝባቸው መመለስን በአሰቡ ጊዜ ስለ ቅድስናቸውና ስለ ትምህርታቸው ጣዕም ስለ ወደዳቸው የተከበረው ንጉሥ መመለስን ከለከላቸው በእርሱ ዘንድ እነርሱ እንደ እግዚአብሔር መላእክት ሁነዋልና ፊታቸውም እንደ ፀሐይ ያበራል።

ከጥቂት ወራትም በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው እግዚአብሔር በወደደ ጊዜ በላዩ ደዌ ላከበት በዚያውም ደዌ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_አላኒቆስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አላኒቆስ የትውልድ ቦታቸው ሸዋ አንኮበር ሲሆን አባታቸው ንጉሡ ዐፄ ይኩኖ አምላክ ነው፡፡ ንጉሡ አባታቸው ‹‹አግባና መንግሥቴን ይዘህ ተቀመጥ›› ቢላቸው እርሳቸው ግን ንግሥናን በመናቅ እምቢ ብለው ሄደው ከእመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቀው ቢለምኗት እምቤታችን ተገልጣላቸው ‹‹ክፍልህ ምናኔ ነው፣ የአባትህ መንግሥት ያልፋል የልጄ መንግሥት ግን ዘላለማዊ ነው›› አለቻቸው፡፡ ጻድቁም ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ሄደው በዚያው መንኩሰው ገዳሙን እያገለገሉ ተቀመጡ፡፡ ከጸሎታቸው በኋላ ራሳቸውን ወደ ባሕሩ ይጥሉ ነበርና አንድ ቀን እንዲሁ ራሳቸውን ወደ ባሕሩ ሲጥሉ መላእክት አውጥተዋቸዋል፡፡ አቡነ አላኒቆስ ወደ አክሱም እንዲሄዱ ታዘው ከሄዱ በኋላ በዚያም የጽላተ ሙሴ የታቦተ ጽዮን አጣኝ ሆነው 40 ዓመት ተቀምጠዋል፡፡ እመቤታችንም ተገልጣላቸው በዓታቸውን እንዲያጸኑ ከነገረቻቸው በኋላ ከአክሱም ወጣ ብሎ የሚገኘውን ማይበራዝዮ ገዳምን መሠረቱ፡፡ በዚያም እጅግ አስገራሚ ተአምራትን እያደረጉ ወንጌልን እያስተማሩ አገልግለዋል፡፡

አንድ ቀን መኰንኑ ወደ ሩቅ ቦታ ሲሄድ ቤተሰባቸውን ለንስሓ አባታቸው አደራ ሰጥተው ሄዱ፡፡ የንስሓ አባታቸውም የአቡነ አላኒቆስ ጓደኛ ነበሩ፡፡ መኰንኑም ከሄዱበት ሲመለሱ ሚስታቸው ከአሽከሯ አርግዛ ጠበቀቻቸው፡፡ ‹‹ከማን አረገዝሽ?›› ብለው ጽኑ ግርፋት ቢገርፏት ዋሽታ ‹‹ያረገዝኩት ከንስሓ አባቴ ነው›› አለች፡፡ መኰንኑም መነኩሴውን እገላለሁ ብሎ ሲነሣ መነኩሴውም ወደ አቡነ አላኒቆስ ሄደው አለቀሱ፡፡ አቡነ አላኒቆስም የመኰንኑን ሚስት ቢጠይቋት ባሏን ፈርታ ‹‹አዎ ከመነኩሴው አባት ነው ያረገዝኩት›› አለች፡፡ እሳቸውም ‹‹የተረገዘው ከዚህ መነኩሴ ከሆነ በሰላም ይወለድ፣ ካልሆነ ግን አይወለድ›› ብለው በቃላቸው አስረውና ገዝተው ሸኟቸው፡፡
በግዝታቸው መሠረት ሴቲቱ ድፍን 22 ዓመት ሙሉ ሳትወልድ በጭንቅና በጣር ኖረች፡፡ በአልጋ ላይ ሆና ተጨንቃ ስትኖር በመጨረሻ ለቤተሰቦቿ ተናግራ ወደ አቡነ አላኒቆስ ዘንድ በቃሬዛ ወሰዷትና ይቅርታ ጠይቃ እውነቱን ተናገረች፡፡ እሳቸውም ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ቢሏት 22 ዓመት ሙሉ ተረግዞ የነበረው ልጅ ትልቅ ሰው ሆኖ ጥርስ አውጥቶ፣ ፂም አብቅሎ በሰላም ተወለደ፡፡ እርሱም ከተወለደ በኋላ አባቱ ማን እንደሆነ ተናገረ፡፡ ጻድቁ አባታችንም ልጁን አሳድገውት አስተምረው አመንኩሰውታል፡፡ ስሙንም ተወልደ መድኅን አሉት፡፡ በስሙ የተሠሰራ ቤተ ክርስቲያን በትግራይ ጽንብላ ወረዳ ይገኛል፡፡

ጻድቁ አቡነ አላኒቆስ ሌላም የሚታወቁበት አንድ ግብር አላቸው፡፡ የማይበራዝዮ ገዳማቸው አገልጋይ የሆነው መነኩሴ በሬ ጠምዶ ሲያርሱ አንበሳ ከጫካው ወጥቶ አንዱን በሬ በላው፡፡ መነኩሴውም መጥተው ለአቡነ አላኒቆስ ነገሯቸው፡፡ እሳቸውም ‹‹ጸሎቴን እስክጨርስ ድረስ ወደ ጫካው ሂድና አንበሳውን ‹አላኒቆስ ባለህበት ጠብቀኝ እንዳትንቀሳቀስ ብሎሃል› ብለህ ተናገር›› ብለው ለመነኩሴው ነገሯቸው፡፡

መነኩሴውም እንደታዘዙት ወደ ጫካው ሄደው ጮኸው በሉ የተባሉትን ተናገሩ፡፡ አቡነ አላኒቆስም ጸሎታቸውን ሲጨርሱ ወደ ጫካው ሄደው አንበሳውን የበላውን በሬ አስተፍተውት በሬውን ነፍስ ዘርተውበት ከሞት አስነሥተው ዕለቱን እንዲታረስ አድርገውታል፡፡ አንበሳውንም ገዝተው ወደ ገዳማቸው ወስደው ሰባት ዓመት ውኃ እያስቀዱት እንዲያገለግላቸው አድርገውታል፡፡

አቡነ አላኒቆስ አንበሳውን አስረው ያሳድሩበት የነበረው ዛፍና ውኃ ያጠጡበት የነበረው ትልቅ የድንጋይ ገበታ ዛሬም ድረስ በገዳሙ ይገኛል፡፡ ከ22 ዓመት እርግዝና በኋላ ሴቲቱ ጥርስና ፂም ያለው ልጅ እንድትወልድ ያደረጉበት ትልቅ ጠፍጣፋ ድንጋይም ከነቅርጹ በገዳሙ በግልጽ ይታያል፡፡ ጻድቁ ጥቅምት 21 ቀን ዐርፈው በዚያው በማይባራዝዮ ገዳማቸው ተቀብረዋል፡፡ ጸበላቸው እጅግ ልዩ ነው፣ ያላመነውን ሰው አስፈንጥሮና ገፍትሮ ይጥለዋል እንጂ አያስቀርበውም፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን አባቶች ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት እና #ከገድላት_አንደበት)
#ጥቅምት_22

#ቅዱስ_ሉቃስ_ወንጌላዊ

ጥቅምት ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ብልህ ጥበበኛ የሆነ ቅዱስ ወንጌላዊ ሉቃስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ የከበረ ወንጌል ከመዘገባቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቆጠረ ነው።

እርሱም ወንጌልን ስለማስተማር በሥራው ሀሉ ሐዋርያት ጴጥሮስንና ጳውሎስን የሚአገለግላቸው ሆነ ለታኦፊላም ወንጌልንና የሐዋርያትን ዜና የጻፈ ሉቃስ ነው።

ቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስም ከተገደሉ በኋላ በሮሜ ሀገር የሚያስተምር ሆነ በቀናች ሃይማኖትም ይጸኑ ዘንድ ለምእመናን መልእክትን ይጽፍ ነበር። ስለዚህም ጣዖት አምላኪዎች ከአይሁድ ጋር በመስማማት አንድ ግምባር ፈጠሩ በንጉሥ ኔሮን ፊት ቁመው ስለ ሐዋርያው ሉቃስ እንዲህ ብለው ጮኹ ይህ ሉቃስ ብዙዎች ሰዎችን በሥራዩ ወደ ትምህርቱ አስገባቸው። ንጉሥ ኔሮንም ወደ ፍርድ አደባባይ ሉቃስን እንዲአቀርቡት አዘዘ።

ሐዋርያ ሉቃስም ከዚህ ዓለም መውጫው እንደ ደረሰ በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ወደ ባሕር ዳርቻ ሔደ። በዚያም ዓሣ የሚያጠምድ አንድ ሽማግሌ ሰው አገኘ። መጻሕፍቱንና ደብዳቤዎቹን ሰጠው ወደ እግዚአብሔር መንገድ መርተው ያደርሱሃልና እሊህን መጻሕፍት ጠብቃቸው አለው።

በንጉሥ ኔሮንም ፊት ቀርቦ በቆመ ጊዜ ንጉሡ በሥራይህ ሕዝቡን የምታስት እስከመቼ ነው አለው ቅዱስ ሉቃስም እኔ ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያው ነኝ እንጂ ሥራየኛ አይደለሁም ብሎ መለሰለት።

ንጉሥ ኔሮንም ሁለተኛ እንዲህ አለው እየጻፈች ሰዎችን የምታስት ይቺን እጅህን እኔ እቆርጣታለሁ ይህንንም ብሎ የቀኝ እጁን እንዲቆርጡ አዘዘ በቆረጡትም ጊዜ ንጉሥ ሆይ እኛ የዚህን ዓለም ሞት እንደማንፈራ እወቅ ነገር ግን የጌታዬንና የፈጣሪዬን ኃይሉን ታውቅ ዘንድ አሳይሃለሁ። ይህንንም ብሎ የተቆረጠች የቀኝ እጁን በግራ እጁ አንሥቶ ከተቆረጠችበት ቦታዋ ላይ አገናኝቶ እንደ ቀድሞዋ ደኅነኛ አደረጋት። ከዚህም በኋላ ለያት በዚያም የነበሩ አደነቁ የሠራዊት አለቃውና ሚስቱ ብዙዎችም ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ቁጥራቸውም አራት መቶ ሰባ ሰባት ነፍስ ሆነ ንጉሡም ከቅዱስ ሉቃስ ጋር ራሶቻቸውን እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡአቸው የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።

ከዚህም በኋላ የቅዱስ ሉቃስን ሥጋ በማቅ አይበት ውስጥ አድርገው ወደ ባሕር ጣሉት በእግዚአብሔርም ፈቃድ ወደ አንድ ደሴት ደረሰ። ምእመናንም አግኝተው ወስደው ገነዙት በአማረ ቦታም አኖሩት።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_23

ጥቅምት ሃያ ሦስት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ዮሴፍ አረፈ፣ የከሀዲ ዱድያኖስ ንጉሥ ሚስት #ቅድስት_እለእስክንድርያ መታሰቢያዋ ነው፣ የቆሮንቶስ አገር ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ዲዮናስዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ተተክለው በደብረ ሊባኖስ የተሾሙት #አቡነ_ኤልሳ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዮሴፍ_ሊቀ_ጳጳሳት

ጥቅምት ሃያ ሦስት በዚህች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ኀምሳ ሁለተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ አረፈ ። ይህም አባት ከመኑፍ አገር ከታላላቆች ተወላጆች ወገን ነው ወላጆቹም ብዙ ገንዘብ ያላቸው ነበሩ ታናሽም ሁኖ ሳለ አባትና እናቱ ትተውት ሲሞቱ ድኃ አደግ ሆነ አንድ እግዚአብሔርንም የሚወድ ሰው አሳደገው።

አድጎ በጎለመሰም ጊዜ የወላጆቹን ገንዘብ ሁሉንም ወስዶ ለድኆችና ለምስኪኖች መጸወተ ከዚህም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጥቶ ከአንድ ፃድቅ ሽማግሌ ሰው አባት ዘንድ መነኰሰ በበጎ ገድል ሁሉ እየተጋደለ ኖረ ።

ዳግማዊ አባ ማርቆስም ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ የዚህን አባ ዮሴፍን በጎ ጠባዩንና የትሩፋቱን ዜና ሰምቶ መልእክተኞችን ልኮ ወደርሱ አስመጣው በቤቱም አኖረው ።

ከብዙ ወራትም በኋላ አባ ዮሴፍ ሊቀ ጳጳሳቱን አባ ማርቆስን ወደ አስቄጥስ ገዳም እሔድ ዘንድ ተወኝ ብሎ ለመነው ያን ጊዜም ቅስና ሹሞ አሰናበተው ሊቀ ጳጳሳት አባ ስምዖንም እስከ አረፈ ድረስ በዚያ በእስቄጥስ ገዳም ኖረ ከዚህም በኋላ የግብጽ አገር ያለ ሊቀ ጳጳሳት ብዙ ወራት ኖረች ።

ከዚህም በኋላ ኤጲስቆጶሳቱ መማለጃ ስለተቀበሉ ከአንድ ሚስቱ ከሞተችበትና መዓስብ ከሆነ ጸሐፊ ጋር ሊቀ ጵጵስና ይሾሙት ዘንድ ተስማሙ እኩሌቶቹ ግን ተቃወሟቸው እንዲህም አሏቸው የአባቶቻችን ቀኖና መማለጃ የሚቀበለውን ሁሉ ወይም ስለ ክህነት ሹመት መማለጃ የሚሰጠውን ያወግዛል ። ይልቁንም ይህ ሰው ሚስት አግብቷል እንዴት ሊሾም ይችላል በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ላይ የሚሾም ንጹሕ ድንግልም ነውና።

ይህንንም በአሏቸው ጊዜ ፈሩ ተመልሰውም ተስማሙ ለዚች ለከበረች ሹመት የሚሻለውን ይገልጽላቸው ዘንድ ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን በአንድ ምክር ሁነው ጸለዩ እግዚአብሔርም ሰምቷቸው ለዚች የከበረች ሹመት የሚሻል አባ ዮሴፍ እንደሆነ አሳሰባቸው።

ከዚህም በኋላ አባ ዮሴፍን ያመጡት ዘንድ ወደ አስቄጥስ ገዳም መልእክተኞችን ላኩ መልክተኞችም ይህን አባት ዮሴፍን የመረጥከው ከሆነ ምልክትን ትገልጥልን ዘንድ አቤቱ እንለምንሃለን የቤቱም ደጃፍ ክፍት ሁኖ ካገኘን ምልክት ይሁንልን ብለው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ።

በደረሱም ጊዜ አንዱን መነኰስ እየሸኘ የበዓቱም ደጃፍ ክፍት ሁኖ አባ ዮሴፍን አገኙት በአያቸውም ጊዜ መንፈሳዊ ሰላምታ በመስጠት እጅ ነሣቸውና በደስታ ተቀብሎ ወደ በዓቱ አስገባቸው በዚያንም ጊዜ ለአባ ዮሴፍ ሊቀ ጵጵስና ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል እያሉ ይዘው አሠሩት ። እርሱ ግን እኔ ብዙ ኃጢአትን ሠርቻለሁና ይህ የከበረ ሹመት አይገባኝም እያለ ይጮህ ነበር እነርሱም ወደ እስክንድርያ ከተማ ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት እንጂ ምንም ምክንያት አልተቀበሉትም።

በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም በተቀመጠ ጊዜ ለአብያተ ክርስቲያን እጅግ የሚያስብ ሆነ ለርሱ የሆነውን የግብሩን ገቢ ወስዶ ምድሮችን በመግዛት ለአብያተ ክርስተያን መተዳደሪያ ሊሆኑ ጉልቶች ያደርጋቸው ነበርና።

አዘውትሮም ሕዝቡን የሚያስተምራቸው ሆነ በምንም በምን ለየአንዳንዱ ቸለል አይልም ነገር ግን ሰይጣን ስለቀናበት ያለ ኀዘን አልተወውም ። ይህም እንዲህ ነው በምስር አገር የተሾሙ ሁለት ኤጲስቆጶሳት በሕዝቡ ላይ ክፉ ነገር በማድረግ በማይገባ ሥራ አስጨነቋቸው እርሱም በርኅራኄና በፍቅር መንጎቻቸውን እንዲጠብቁ አዘዛቸው ለመናቸውም እነርሱ ግን ሰምተው ከክፋታቸው አልተመለሱም።

በሕዝቡም ላይ ችግርን በአበዙ ጊዜ ሕዝቡ ሁሉም በጠቅላላ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ መጡ በፊቱም እንዲህ ብለው ጮኹ እሊህን ኤጲስቆጶሳት ከላያችን ካላነሣሃቸው እኛ ወደሌላ ሃይማኖት እንገባለን አባ ዮሴፍም በመካከላቸው ሰላምን ለማድረግ ብዙ ትግልን ታገለ ግን አልተቻለውም።

ከዚህም በኋላ በግብጽ አገር ያሉትን ኤጲስቆጶሳት ለጉባኤ ሰበሰባቸውና ስለ እሊህ ሁለት ኤጲስቆጶሳት ነገራቸው አሁንም ከመንጋዎቻቸው ጋር ሊአስታርቅ ሽቶ እሊህን ኤጲስቆጶሳት ወደ ጉባኤው አስቀረባቸው እነርሱ ግን የጉባኤውንም የእርሱንም ቃል አልተቀበሉም ስለዚህም ያ ጉባኤ ከሹመታቸው ሻራቸው።

እነርሱም ወደ ግብጽ ንጉሥ ሒደው በሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ ላይ በሐሰት ነገር ሠሩበት ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍንም ያመጡት ዘንድ ንጉሡ ወንድሙን ከጭፍራ ጋር ላከው። የንጉሡም ወንድም ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ በደረሰ ጊዜ ተበሳጨ ሊገለውም ወዶ ሰይፉን መዞ ሊቀ ጳጳሳቱን ሊመታው ሰነዘረበት ግን እጁ ወደ ሌላ አዘንብሎ ምሰሶ መትቶ ሰይፉ ተሰበረ እጅግም ተቆጥቶ ሌላ ሰይፍን መዝዞ በመላ ኃይሉ መታው ያን ጊዜም ሰይፉ ከአንገቱ ወደ ወገቡ ተመልሶ ልብሱንና ቅናቱን ብቻ ቆረጠ የንጉሡም ወንድም ከክፋት ንጹሕ እንደሆነ ስለዚህም አምላካዊት ኃይል እንደምትጠብቀው አሰበ አስተዋለም።

ወደ ንጉሡም በክብር አደረሰው ወንድሙ ለሆነ ንጉሥም በእርሱ በሊቀ ጳጳሳቱ ላይ የሆነውን ሁሉ ነገረው ንጉሡም ፈራው አከበረውም ከዚህም በኋላ ስለከሰሱት ስለ ሁለቱ ኤጲስቆጶሳት ጠየቀው እርሱም ስለ ክፉ ሥራቸው በጉባኤ እንደተሻሩ እውነቱን ለንጉሡ አስረዳው ያን ጊዜም ሐሰተኞች እንደሆኑ ንጉሥ አወቀ ይገድሏቸውም ዘንድ አዘዘ።

ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍም ንጉሡን እንዲህ ብሎ ማለደው ጌታችን በክፉ ፈንታ በጎ እንድናደርግ እኛን አዞናልና ስለ እግዚአብሔር ብለህ እሊህን ማራቸው እንጂ አትግደላቸው ንጉሡም ስለ የዋህነቱ አደነቀ ልመናውንም ተቀብሎ ማረለት።

ከዚህም በኋላ በሹማምንቱና በኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ ላይ የፈለገውን ያደረግ ዘንድ ቢፈልግ እንዲሾም ወይም እንዲሽር የሚቃወመው እንዳይኖር ደብዳቤ በመጻፍ ሥልጣንን ሰጠው።

በዚህም አባት ዘመን የኢትዮጵያ ንጉሥ ወደዚህ አባት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ እንዲህ ብሎ መልእክትን ላከ ለወንጌላዊ ማርቆስ መንበርና በላዩ ለመቀመጥ ለተገባው ቅድስናህ እጅ እነሣለሁ በእኔና በመንግሥቴ ላይ በመላው ወገኖቼ በኢትዮጵያ ሰዎች ላይ ይቅርታ እንድታደርግና አባታችንን አባ ዮሐንስን እንድትልክልን እለምንሃለሁ ከሀገራችን ሰዎች ከእውነት መንገድ የወጡና የሳቱ ጳጳሳችንን አባ ዮሐንስን እኔ ሳልኖርና ሳላውቅ አባረውታልና ስለዚህም በሀገራችን ቸነፈርና ድርቅ ሁኖ ከሰዎችም ከእንስሶችም ብዙዎች አለቁ።

አሁንም አባቴ ሆይ ስንፍናችንን ይቅር በል መሐሪና ይቅር ባይ ወደ ሆነ እግዚአብሔር ፈጽሞ ይማልድልን ዘንድ በከበረች ጸሎቱም ከዚህ መከራ እንድን ዘንድ አባታችንን አባ ዮሐንስን ላክልን።

አባቴ ሆይ የተባረረበትን ምክንያት እኔ አስረዳሃለሁ እኔ ልጅህ ከአባቴ ከጳጳስ አባ ዮሐንስ ቡራኬ ተቀብዬ እርሱ ከሠራዊቴ ጋር በፍቅር አሰናብቶኝ ወደ ጦር ሜዳ ሔድሁ ከጦር ሜዳም በተመለስኩ ጊዜ አባቴን አባ ዮሐንስ ጳጳሱን አጣሁት ስለርሱም በጠየቅሁ ጊዜ በቀድሞ ዘመን ዮሐንስ አፈ ወርቅን ንግሥት አውዶክስያ እንዳሳደደችው በክፉዎች ሰዎች ምክር ንግሥቲቱ ሚስቴ ማሳደዷን የቀኖናውንም ትእዛዝ በመተላለፍ በፈቃዳቸው ሌላ ጳጳስ እንደሾሙ ነገሩኝ።
እርሱ አባ ዮሐንስም ከኢትዮጵያ በአሳደዱት ጊዜ ወደ አስቄጥስ በመሔድ አስቀድሞ በመነኰሰባት በአባ ሙሴ ጸሊም ገዳም በዚያ ተቀመጠ። የኢትዮጵያ ንጉሥ መልእክትም ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ በደረሰች ጊዜ አነበባት ስለ ኢትዮጵያ ንጉሥ የሃይማኖት ጽናት እጅግ ደስ አለው ፈጥኖም ወደ አስቄጥስ ገዳም መልእክተኞችን ልኮ አባ ዮሐንስን ወደርሱ አስመጥቶ አረጋጋው አጽናናው ከዚያም በኋላ ከደጋጎች ሰዎች ጋር ወደ ኢትዮጵያ አገር ላከው።

አባ ዮሐንስም ወደ ኢትዮጵያ አገር በደረሰ ጊዜ ቸነፈር ተወገደ ዝናብም ዘነበ ንጉሡና መላው የኢትዮጵያ ሰዎች ደስ ብሏቸው እግዚአብሔርን አመሰገኑት። ይህም ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሴፍ መናፍቃንን የሚገሥጻቸው ሆነ ሕዝቡንም ከአባቶቻቸው በተቀበሏት በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ አስተማራቸው ከቅዱሳት መጻሕፍትም ለእነርሱም ሥውር የሆነውን ተርጉሞ ያስረዳቸዋል ያስገነዝባቸዋልም በትምህርቱና በጸሎቱም እንዲህ ጠበቃቸው ጌታችንም በእጆቹ ብዙዎች ተአምራትን አደረገ ያማረች ገድሉንም ፈጽሞ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም በፍቅር አረፈ ። መላ የሕይወቱም ዘመን ሰባ ስምንት ነው ከምንኲስና በፊት ሃያ አመት በምንኲስና ተጋድሎ ሠላሳ ዘጠኝ ዓመት በሊቀ ጵጵስና ሹመት ዓሥራ ዘጠኝ ዓመት ኖረ ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_እለእስክንድርያ_ሰማዕት

ዳግመኛም በዚህች ቀን የከሀዲ ዱድያኖስ ንጉሥ ሚስት የከበረች እለእስክንድርያ መታሰቢያዋ ነው። ይኸውም ለጣዖቶቹ እንደሚሠዋ መስሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በዘበተበት ጊዜ ዝንጉዕ ዱድያኖስም ዕውነት መስሎት ራሱን ሊስም ተነሣ። ቅዱሱ ግን ለአማልክት ከመሠዋት አስቀድሞ አይሆንም ብሎ እንዳይስመው ከለከለው።

ከዚህ በኋላም ዱድያኖስ ወደ ቤተ መንግሥቱ አዳራሽ ቅዱስ ጊዮርጊስን አስገባው በዚያም በንግሥት እለእስክንድርያ ፊት የዳዊትን መዝሙር በማንበብ ጸለየ። በሰማችም ጊዜ ይተረጒምላት ዘንድ ለመነችው ያን ጊዜም ተረጐመላት የክብር ባለቤት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጌትነቱን ገለጠላት ትምህርቱም በልቡዋ አድሮ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመነች።

ከዚህም በኋላ ሲነጋ ለአማልክት ወደሚሠዋበት ቅዱስ ጊዮርጊስን ወሰዱት እርሱም የረከሱ አማልክትን ትውጣቸው ዘንድ ምድርን አዘዛት ምድርም ዋጠቻቸው። ንጉሥ ዱድያኖስም አፈረ እየአዘነና እየተከዘ ወደ ሚስቱ ወደ እለእስክንድርያ ዘንድ ገባ። እርሷም ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነው አላልኩህምን አለችው። ይህንንም ሰምቶ በእርሷ ላይ ተቆጣ ያሠቃዩዋት ዘንድ ጡቶቿንም ሠንጥቀው ይሰቅሏት ዘንድ አዘዘ። የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዲዮናስዮስ_ኤጲስቆጶስ

በዚችም ቀን የቆሮንቶስ አገር ኤጲስቆጶስ ዲዮናስዮስ በዐላውያን ነገሥታት በዲዮቅልጥያኖስና በመክስምያኖስ ዘመን በሰማዕትነት አረፈ ይህንንም ቅዱስ በያዙት ጊዜ ብዙ ሥቃይን አሠቃዩት ማሠቃየቱንም በሰልቹ ጊዜ ራሱን በሰይፍ አስቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ጻድቁ_አቡነ_ኤልሳ

ዳግመኛም በዚህች ቀን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ተተክለው በደብረ ሊባኖስ የተሾሙት አቡነ ኤልሳ ዕረፍታቸው ነው፡፡ ጻድቁ ሀገራቸው ሸዋ ነው፡፡ በዐፄ ይኩኖ አምላክ ዘመን የነበሩ ሲሆን ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቀጥለው በደብረ ሊባኖስ ገዳም በእጨጌነት የተሾሙ የመጀመሪያ ዕጨጌ ናቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከማረፋቸው በፊት ‹‹በእኔ ወንበር ኤልሳዕ ይሾም ነገር ግን ዘመኑ ትንሽ ስለሆነ ከእርሱ ቀጥሎ ፊሊጶስን ትሾማላችሁ›› ብለው ለቅዱሳን ተከታይ ሐዋርያቶቻቸው ተናግረው ነበር፡፡

በዚህም መሠረት አቡነ ኤልሳዕ ተሹመው ብዙም ሳይቆዩ አንድ ዲያቆን ሞተና ሊቀብሩት ሲወስዱት በመንገድ ላይ ሳለ ድንገት ከሞት ተነሥቶ ‹‹አባቴ ተክለ ሃይማኖት ኤልሳዕ አሁን ወደኔ ስለሚመጣ ፊሊጶስን ሹሙት ብለህ ተናገር ብለውኝ ነው›› ብሎ ከተናገረ በኋላ ተመልሶ ዐርፎ ተቀበረ፡፡ አቡነ ኤልሳዕም ወዲያው ዐርፈው አቡነ ፊሊጶስ 3ኛ ሆነው ተሾሙ፡፡ አቡነ ኤልሳዕ ከተጋድሎአቸው ብዛት የተነሣ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ጎናቸውን አሳርፈው ተኝተው አያውቁም ነበር፡፡ ነገር ግን ማረፍ ሲኖርባቸው በወንበር ላይ ተደግፈው ትንሽ ብቻ ያርፉ ነበር፡፡ አቡነ ኤልሳዕ በሞት ያረፉትም እንደልማዳቸው ጎናቸውን ሳያሳርፉ በወንበር ላይ እንደተደገፉ ነበር፡፡ አባታችን ስለዚህም ጉዳይ ሲናገሩ እንዲህ ይሉ ነበር፡- ‹‹ነፍስ ትጋትን ትወዳለች፣ ሥጋ ግን ይደክማል፡፡ ለመነኮሳትና ለእግዚአብሔር አገልጋዮች ሁሉ መኝታ ማብዛት አይገባቸውም፡፡ መኝታ ማብዛት ሕልምን ያመጣል፣ ነፍስን ይጎዳል፣ ሰውነትንም ያደክማል፡፡››

አቡነ ኤልሳዕ በዘመናቸው ወንጌልን በማስተማርና ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ይታወቁ ነበር፡፡ እንደ ነቢዩ ኤልሳዕ እሳቸውም ሙት አስነሥተዋል፡፡ ባሕር እየከፈሉ ቀደ መዛሙርቶቻቸውን ያሻግሩ ነበር፡፡ በጸሎታቸው የዠማን ወንዝም ለሁለት የከፈሉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡

ለእግዚአብርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት እና #ከገድላት_አንደበት)
#ጥቅምት_24

ጥቅምት ሃያ አራት በዚህች ዕለት #የቅድስት_ጸበለ_ማርያም መታሰቢያዋ ነው፣ መስተጋድል መነኰስ #ቅዱስ_አባ_አብላርዮስ ያረፈበት ቀን ነው፣ የመፍቀሬ ነዳያን #አባ_ዘግሩም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው ነው፡።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ጸበለ_ማርያም

በዚህች ዕለት ታስባ የምትውለውንና ጌታችን በደሃ ሰው ተመስሎ ተገልጦ ቁራሽ እንጀራ የለመናትን በኋላም በጀርባዋ አዝላ የሸኘችው ቅድስት ጸበለ ማርያም እረፍቷ መስከረም ፲፰ ቀን ነውና ጥር ፲፰ ቀንም በዓል ነው። እርሷም በጎኗ ተኝታ የማታውቅ፣ በጌታችን ፵ ጾም ወራት ከሰንበት በቀር ምንም የማትቀምስ፣ ነብሮች የእግሯን ትቢያ ይልሱላት የነበረች ታላቅ ኢትዮጵያዊት ቅድስት ናት። ይኽችውም ከነቢያት፣ ከሐዋርያትና ከሰማዕታት ዕድል የተሰጣት እናት ናት፡፡ ከደናግል መነኮሳትም ዕድል ተሰጣት መነኩሲትም ድንግልም ናትና፡፡

እናታችን ቅድስት ጸበለ ማርያም፡- ቅድስት ጸበለ ማርያም ትውልዷ በጎንደር ጠቅላይ ግዛት ቀሐ አካባቢ ነው፡፡ ወላጆቿ አባቷ እንድርያስና እናቷ መስቀል ክብራ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እያስተማሩ በሃይማኖት በምግባር ኮትኮተው አሳደጓት፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ተከስተ ብርሃን የተባለ ደገኛ ባሕታዊ ወደ አባቷ ቤት መጥቶ ባደረበት መንፈስ ቅዱስ ኀይል የቅድስት ጸበለ ማርያምን ጸጋ አወቀ፡፡ ለወላጆቿም "ይኽቺ ልጅ ወደፊት ነፍሳት የሚድኑባት የከበረች ትሆናለች" ብሎ በእርሷ ላይ ትንቢት ተናገረ፡፡

ቅድስት ጸበለ ማርያም ለአቅመ ሄዋን ስትደርስ ወላጆቿ በጋብቻ ሕግ እንድትወሰን ፈለጉ፡፡ ነገር ግን ቅድስት ጸበለ ማርያም "ቅዱስ ጳውሎስ ለእግዚአብሔር አጭቶኛልና ፈጣሪዬን በድንግልና ለማገልገል ተስያለሁ" በማለት ተቃወመቻቸው፡፡ ወደ አንድ ደገኛ ባሕታዊም ዘንድ ሄዳ በጸሎቱ ከዚህ ነገር እንዲያድናት ተማጸነችው፡፡ እርሱም ፈቃደ እግዚአብሔርን በጸሎት ከጠየቀላት በኋላ ማድረግ የሚገባትንና ወደፊት የሚገጥማትን ሁሉ ነገራት፡፡ እርሷም ለዕጣን እንዲሆን ጌጧን ሁሉ አውጥታ ሸጠችና "መሥዋዕቴን አሳርግልኝ" ብላ ለባሕታዊው ሰጠችው፡፡ እርሱም ከጸለየላት በኋላ የጸሎቱን ምላሽ ነገራት፡፡

ወለጆቿም ያለፈቃዷ በሕግ ቢያጋቧትም ቅድስት ጸበለ ማርያም ግን በሌሊት ማንም ሳያያት ከጫጉላ ቤት ወጥታ ሄዳ በልዳው ፀሐይ በቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ወደተሠራች ቤተክርስቲያን ሄዳ እያለቀሰች ጸሎት አደረገች፡፡ እመቤታችንም ከሚካኤል ወገብርኤል እንዲሁም ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ተገለጠችላትና እንዲጠብቋት ነገረቻቸው፡፡ ቤተሰቦቿም እንዳያዝኑባት ፈርታ ተመልሳ ወደ ባሏ ዘንድ ብትገባም ባሏ በግብር እንዳያውቃት መላእክቱ ይጠብቋት ነበር፡፡ ባሏንም ሰውነቷ እንደእሳት ያቃጥለው ነበር፡፡ እርሱም አእምሮውን ከሳተ ከ3 ቀን በኋላ ሲነቃ የደረሰበትን ለቤተ ዘመዶቹ ባስዳቸው ጊዜ "ከገዳም የመጣች ከሆነች ለእኛ ልትሆን አይገባም" አሉና አስጊጠውና ሸልመው መልሰው ወደ ቤተሰቦቿ ላኳት፡፡

አባቷም ዳግመኛ ወደ ባሏ እንድትመለስ በማስገደድ ብዙ አሰቃቂ ግርፋት ቢገርፋትም በተአምራት ምንም እንዳላገኛት ሆነች፡፡ ከዚኽም በኋላ ወጥታ ወደ ምድረ በዳ ሄደች፡፡ ወደ ገዳምም ሄዳ ዋሻ ውስጥ ገብታ ስትጸልይ አድራ አረፍ ስትል ነብር መጥቶ የእግሯን ትቢያ ይልሳት ነበር፡፡ ከዚያም ወጥታ ንህበት ወደሚባል ሀገር መጥታ ቶማስ ከሚባል መነኩሴ ጋር በታላቅ ተጋድሎ ኖረች፡፡ ቆማ ስትጸልይ እንባዋ መሬቱን ያርስ ነበር ነገር ግን ሰው እንዳያውቅባት አፈር በላዩ ትጨምርበታለች፡፡ በአንድ ዕለትም በቤተክርስቲያን ቆማ ስትጸልይ በሁለቱ ማዕዘን የተቀበሩ ምውታን ሲጮኹ ሰማቻቸው፣ እነርሱ ግን በሲኦል ነበሩ፡፡ ጩኸታቸውንም በሰማች ጊዜ በእንባዋ ላይ እንባን በጸሎቷም ላይ ጸሎትን ጨምራ ስለ እነርሱ ለመነች፡፡ ስለእነርሱም ሱባኤ ያዘች፡፡ በባሕርይው ቸርና ይቅርባይ የሆነ ልዑል እግዚአብሔርም ጸሎቷን ሰምቶ እነዚያን ነፍሳት ማረላት፡፡

ቅድስት ጸበለ ማርያም በምግባርና በትሩፋት በጾም በጸሎት ጸንታ ከኖረች በኋላ የምንኩስና ቀንበርን ትሸከም (በምናኔ ትኖር) ዘንድ በብሕትውና ወደሚኖረው ታላቁ አባት ወደ አቡነ ገብረ ማርያም ዘደብረ ሐንታ ዘንድ ሄደች፡፡ እርሱም ማኅሌተ ጽጌን ከአባ ጽጌ ድንግል ጋር የደረሰው ነው፡፡

አቡነ ገብረ ማርያምም ካስተማራትና በኋላ አመነኮሳትና ስሟን "ጸበለ ማርያም" ብሎ ሰየማት፡፡ ከዚኽም በኋላ ተጋድሎዋን እጅግ በማብዛት ትሕርምትን ገንዘብ አደረገች፡፡ ከዕንጨት ፍሬዎች ውጭ የማትመገብ ሆነች፡፡ በተቀደሰችው የጌታችን ፵ ጾም ወራት ግን ከሰንበት በቀር እርሱንም ፈጽሞ አትቀምስም፣ እስከ ፋሲካም ድረስ ከበዓቷ ስለማትወጣ ማንም አያያትም ነበር፡፡ ከመነኮሰችም ጊዜ ጀምሮ በጎኗ ተኝታ አታውቅም፡፡ ባመማት ጊዜም ተቀምጣ ታንቀላፋ ነበር፡፡ በውርጭ ቅዝቃዜ መከራን እየተቀበለች በባሕር ውስጥም ቆማ እየጸለየች ታድራለች፡፡ በስግደቷም በቀን እስከ 8 እልፍ ትሰግድ ነበር፡፡ ከወንድሟ ቶማስም የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ተማረች፡፡ የዮሐንስን ወንጌልና የራእዩን መጽሐፍ ዘወትር በማንበብ ትጸልያለች፡፡ የእመቤታችን በዓል በሆነ ጊዜ አርጋኖን ውዳሴዋን በቀን ሦስት ጊዜ ታነባለች፣ አንቀጸ ብርሃንንም በየሰባቱ ጊዜ ትጸልያለች፡፡ የዳዊትንም መዝሙር በፈጸመች ጊዜ የጌታችንን መከራ ግርፋት እያሰበች ራሷን ሺህ ጊዜ ትገርፋለች፡፡ ዳግመኛም አገዛዛቸው መልካም ይሆን ዘንድ ስለ ጳጳሱና ስለ ንጉሡ አንድ አንድ ሺህ ጊዜ፣ ስለ መነኮሳትም ሺህ ጊዜ፣ ስለኃጥአንም ሺህ ጊዜ ራሷን ትገርፋለች፡፡ ዳግመኛም ነጭ ዕጣን በእጇ ይዛ ሰባት ቀን እስኪሆን ድረስ ዕንባዋን ታፈስበታለች፣ ያም ነጭ ዕጣን ከዕንባዋ ብዛት የተነሣ ጥቁር ይሆናል፡፡ በዓል በሚሆንበት በሰባተኛው ቀን አስቀድማ ዐውቃ በመሠዊያ ያሳርገው ዘንድ ያን ዕጣን ለቄሱ ትሰጠዋለች፡፡ እግዚአብሔርም እንደሱራፌል የጽናሕ መዐዛና እንደኪሩቤል ዕጣን ሽታ አድርጎ ከቄሱ እጅ ሲቀበል በግልጽ ታያለች፡፡

ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ቅድስት ጸበለ ማርያም እየጸለየች ሳለ የክብር ባለቤት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቆሰለ ችግረኛ ደሃ ሰው ተመስሎ ለቅድስት ጸበለ ማርያም ተገልጦ ወደ እርሷ በመምጣት ቁራሽ እንጀራ ለመናት፡፡ እርሷም ፈጥና ይዛ መጥታ ሰጠችው። እንጀራውንም ተቀብሎ ሲያበቃ "በመንገድ ብዛት ደክሜአለሁና በጀርባሽ አዝለሽ ትሸኚኝ ዘንድ እወዳለሁ" አላት፡፡ እርሷም ለድሆች አዛኝ ናትና አዝላው የድንጋይ መወርወሪያ ያህል እንደወሰደችው ቁስሉ ይድን ጀመር፡፡ ወዲያውም ቁስሉ ድኖ ምንም እንዳላገኘው ፍጹም ደህነኛ ሰው ሆነ፡፡ ያንጊዜም ፊቱ እንደፀሐይ አበራ፣ ሁለንተናውም ተለወጠ፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችን ከጀርባዋ ወርዶ በፊት ለፊቷ ቆመና "የከበርሽ አገልጋዬ ጸበለ ማርያም ሆይ! ምን እንዳድርግልሽ ትወጃለሽ?" አላት፡፡ እርሷም ከድንጋጤዋ የተነሣ እንደበድን ሆና መሬት ላይ ወደቀች፡፡ ጌታችንም አበረታትና እጇን ይዞ አነሣትና "የልብሽን መሻት ለምኚኝ" አላት፡፡ እርሷም "አምላኬ ሆይ! በፊትህስ ሞገስ ካገኘሁ በሲኦል ያሉ ነፍሳትን ይቅር በላቸው" አለችው፡፡ በዚኽም ምክንያት በጌታችን ቸርነትና በእርሷም አማላጅነት ብዙ ነፍሳት ከሲኦል ወጡ፡፡ ጌታችንም ሰላምታ ሰጥቷት በክብር ዐረገ፡፡
ዳግመኛም ጌታችን ለቅድስት ጸበለ ማርያም ሦስት በትሮችን ሰጥቷት በእነርሱ እየተመረኮዘች እስከሲኦል ድረስ ትሄድና ነፍሳትን ታወጣና ታስምር እንደነበር ራሷ ተናገረች፡፡ ዳግመኛም ስትናገር "ሰማያውያን ብዙ ስሞች አወጡልኝ፣ 'የወይን ፍሬ' እያሉ ይጠሩኛል፣ 'የበረከት ፍሬ' የሚሉኝም አሉ፣ 'የገነት ፍሬም' ይሉኛል" አለች፡፡ ዳግመኛም ከልዑል ዘንድ ብዙ ጸጋዎች እንደተሰጣት በሕይወት ሳለች ለአንደ ደገኛ ቄስ ነገረችው፡፡

ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አምላክን በድንግልና የወለደች ክብርት እመቤታችን ለቅድስት ጸበለ ማርያም ተገለጠችላትና "ስሜን የተሸከምሽ ጸበለ ማርያም ሆይ! ሰላም ለአንቺ ይሁን" አለቻት፡፡ እመቤታችንም ብዙ ምሥጢርን ከነገረቻት በኋላ ጡቶቿንም አጠባቻትና በጸጋ የከበረች አደረገቻት፡፡ በስሟም ብዙ ተአምራትን የምታደርግ ሆነች፡፡

ቅድስት እናታችን ጸበለ ማርያም ከነቢያት፣ ከሐዋርያትና ከሰማዕታት ዕድል የተሰጣት እናት ናት፡፡ እንደነቢያት የሚመጣውን ሁሉ እንዳለፈ አድርጋ ትናገራለች፡፡ ዳግመኛም የትምህርታቸውን ፍለጋ ስለተከተለችና ለሕጋቸው ስለተገዛች ከሐዋርያት ጋር ዕድል ተሰጣት፡፡ ሦስተኛ ግድ ሳይሏት በፈቃዷ ስለተቀበለቻቸው ግርፋቶቿና ስላገኛት መከራ የሰማዕታት ዕድል ተሰጣት፡፡ ከደናግል መነኮሳትም ዕድል ተሰጣት መነኩሲትም ድንግልም ናትና፡፡ ቅድስት እናታችን ጸበለ ማርያም መልካም የሆነውን ተጋድሎዋን ከፈጸመችና ጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ከገባላት በኋላ በሰላም ዐርፋለች፡፡ እንደ ንግሥት ዕሌኒም የሞቷን መስቀል ተሸክማ ተጠብቆላት ወዳለ ተስፋዋ በክብር ሄደች፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_አብላርዮስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን መስተጋድል መነኰስ አባ አብላርዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ጋዛ ከሚባል አገር ነው ወላጀቹም አረማውያን ናቸው የዮናናውያንንም ትምህርታቸውንና ፍልስፍናቸውን አስተማሩት ሰውነቱ ለጥበብ ማደሪያዋ እስከሆነ ድረስ በዕውቀቱ ከጓደኞቹ በላይ ሆነ።

ከዚህም በኋላ ከሀገሩ የሌለ መልካም የሆነ ጥበብን ከውጭ አገር መማርን ወዶ ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ ሀገር ሔደ መምህራንም ሁሉ ከሚኖሩበት ቦታ ገብቶ ከእሳቸው ዘንድ ብዙ ትምህርትን ተማረ በዚያንም ጊዜ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ለመማር ተነሣሥቶ ቸኰለ የቤተ ክርስቲያንንም መጻሕፍት ብዙዎቹን አነበበ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስም ይተረጕምለትና ያስረዳው ነበር።

ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ የክርስትናን ጥምቀት ተጠመቀ ከዚያም መንኵሶ በምንኵስና ሕግ ጸንቶ ገድልን ተጋደለ ወደ አባ እንጦንዮስም ሔዶ መንፈሳዊ የሆነ የትሩፋትን ሥራ እየተማረ በእርሱ ዘንድ ብዙ ወራት ኖረ።

ወላጆቹም እንደሞቱ በሰማ ጊዜ ሒዶ የተዉለትን ገንዘባቸውን ሁሉንም ወስዶ ለድኆችና ለችግረኞች መጸወተ ከዚህም በኋላ ከሶርያ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባ በዚያም በጾም በጸሎት በስግደት በመትጋት ፍጹም ገድልን ተጋደለ በየሰባት ቀን እስቲመገብ ድረስ ምግቡም የዱር ሣር ነበር።

እግዚአብሔርም ሀብተ ትንቢትን ሰጥቶት ልቡናው ብሩህ ሆነ ድንቆች ተአምራትንም የሚያደርግ ሆነ ኤጲፋንዮስንም ያመነኰሰውና ለደሴተ ቆጵሮስም ኤጲስቆጶስ እንደሚሆን ትንቢት የተናገረለት እርሱ ነው።

የዚህም አባት መላ ዕድሜው ሰማንያ ዓመት ነው ከክርስትናውና ከምንኵስናው በፊት ዐሥራ ሰባት ዓመት በምንኵስናም ስልሳ ሦስት ዓመት ነው ክብር ይግባውና እግዚአብሔርንም ካገለገለ በኋላ በሰላም አረፈ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም አመስግኖታል ሁለተኛም ቅዱስ ባስልዮስ በመጻሕፍቱ አመስግኖታል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#መፍቀሬ_ነዳያን_አባ_ዘግሩም

ዳግመኛም በዚህች ቀን የመፍቀሬ ነዳያን አባ ዘግሩም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው ነው፡፡ አባታቸው ገርዜነ ጸጋ የተባለ ደገኛ ካህን ሲሆን እናታቸው ደግሞ ነፍስተ እግዚእ ትባላለች፡፡ እነዚህም ደገኛ ክርስቲያኖች በእግዚአብሔር ሕግ ጸንተው ብዙ ዘመን ሲኖሩ የተባረከ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ይለመኑት ነበር፡፡ ልዑል እግዚአብሔርም መልአኩን ልኮ የተባረከ ልጅ እንደሚወልዱ አበሰራቸው፡፡ አባ አብርሃምም በመልአኩ ብሥራት ግንቦት ሃያ አራት ቀን በተወለዱ ጊዜ ወላጆቻቸው ብርሃነ መስቀል ብለው ጠሩት፡፡ በኋላ የተጠራበት ስመ ጥምቀቱ ግን ማኅፀንተ ሚካኤል ነው፡፡ ወላጆቹም በመንፈሳዊ አስተዳደግ ስላሳደጉት ከልደቱ ጀምሮ ጸጋ እግዚአብሔር አደረበት፡፡ በመንፈስ ቅዱስ አደገ፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያንም መሄድን አላስታጎለም፡፡ እንደ ነቢዩ ሳሙኤል ከታናሽነቱ ጀምሮ በእግዚአብሔር ቤት አድጓልና፡፡

አድጎ ለትምህርት በደረሰ ጊዜ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን፣ መጻሕፍተ ነቢያትን፣ መዝሙረ ዳዊትን ይማር ዘንድ አባቱ ለመምህር ሰጠው፡፡ ሕፃኑም በትምህርቱ አስተዋይ ሆነ፡፡ ሳያቋርጥ ሁልጊዜ ከመምህሩ መረዳትን ያበዛ ነበር፡፡ በመንፈስ ቅዱስም ኃይል የጸና ሆነ፡፡ ዲቁናም ከተሾመ፡፡

ከዚህም በኋላ እናቱና አባቱ ያለ ፈቃዱ ሚስት ያጩለት ዘንድ ወደዱ፡፡ በመጽሐፍ ‹‹የልጅ ልጅህን ታያለህ፣ አንተ ብፁዕ ነህ፣ መልካምም ይሆንልሃል›› የሚል በመጽሐፍ ተጽፏልና፡፡ ስለዚህም ያጋቡት ዘንድ አቻኮሉት፤ እርሱ ግን ዓለመን ፍጹም ንቆ በምንኩስና በተጋድሎ መኖርን ወደደ፡፡

ለምንኩስናም ስሙ አባ ክርስቶስ ይባርከነ ወደተባለ አንድ መነኩሴ ወዳለበት ገዳም ሲሄድ በመንገድ መደራ በተባለች ቦታ በታላቅ ገዳም ውስጥ ከእንግዶች ጋር አደረ፤ በሌሊት በነቃ ጊዜ አንድ ድኃ በዚያች ቤት ውስጥ አገኘ፤ የድኃውን ልብስ ወስዶ የእርሱን ልብስ ሰጥቶተ በሌሊት ወጥቶ መንገዱን ሔደ፡፡ በነጋም ጊዜ ያ ድኃ ያደረገለትን ለሰዎቹ ተናገረ፡፡ ‹‹በእንግዳ ማደሪያ ከእኔ ጋር አብሮ ያደረ አንድ ሰው እኔ የለበስሁትን ልብስ ወስዶ የእርሱን መልካም ልብስ ተወልኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹… የእግዚአብሔር ሰው ነውና መልካም ሥራ አደረገልህ አንተ ግን ሔደህ ስለ እርሱ ጸልይለት›› አሉት፡፡

አባ አብርሃም ግን ከአባ ክርስቶስ ይባርከነ ከቀድሞ ቤቱ በደረሰ ጊዜ በዚያም አላገኘውም፤ ውኃ ከሌለበት፤ ፀጥታ ከሰፈነበት ምድረ በዳም ሔደ፡፡ የፀሐይ ወቅት ነበረና በዚያ ሲመላለስ ሳለ ውኃ ጥም ያዘው፡፡ ያን ጊዜም በገዳሙ ውስጥ ባዶ ወጭት አገኘና በፊቱ አስቀምጦ ወደ እግዚአብሔር በጸለየ ጊዜ ወዲያው ብዙ ዝናም ዘነመ፤ በወጭቷም አጠራቀመና እስኪበቃው ድረስ ከእርሷ ጠጣ፡፡ ከዚያም አባታችን ክርስቶስ ይባርከነን አገኘውና ሊያደርግ የሚፈልጋቸውን ምሥጢሩን ሁሉ ነገረው፡፡
የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ አባታችንን ‹‹…በደመና ተጭነህ ወደ ዳሞት አገር ሂድ›› አለው፤ አባታችንም በደመና ተጭኖ ፍራጽ ከተባለ ገዳም ደረሰ፤ በዚያም ምድርን ባረኮ ውሃ አፈለቀ፤ መልአኩም ወደ ቀኝህ ተመልከት አለው፡፡ ወደ ቀኙ ሲያይ ዐደልን ብርሃን ከቧት ተመለከተ፤ ዕፅዋትም ጭፍቅ ያሉ ነበሩ፤ አባ ዘግሩምም ይህች ቦታየ ናት አለ፤ የጻሕናንን ምድር እየባረከም ይሄድ ዘንድ ወደደ፡፡ ብዙ ውሃ አፈለቀ፤ ዐደልም ደረሰ፤ በዚያም ውሃ አፈለቀ፤ አባታችን ዘግሩም ወደ ውስጧ ገባ በዚያም ተቀመጠ፣ የገዳሙ አራዊትም በዚህ ተደሰቱ፡፡ ሙሴ ጽላትን እንደተቀበለ ሁሉ ጥቅምት ሃያ አራት ቀን የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ አመጥቶ የብርሃን መስቀልና የመድኃኔዓለምን ታቦት ሰጠው፡፡ ዳግመኛም የእግዚአብሔር መልአክ የተዘጋጀ ኅብስትና የተቀዳ ጽዋን፤ ለመሥዋዕት የሚሆነውንም ሁሉ ሰጠው፤ አባታችንም ከካህናት ጋር በዚያች ቤተ ክርስቲያን ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ሰጣቸው፡፡
በቤተ ክርስቲያን አጠገብ አንዲት የዋንዛ ዛፍ ነበረች፤ ሕዝቡም ይሰበሰቡባትና በሥሯ ተቀምጠው ክፉ ሥራ ይሠሩ ነበር፤ አባታችንም ‹‹ለምን እንዲህ የማይገባ ሥራ ትሠራላችሁ? ሲላቸው እነርሱ ግን አልሰሙም፡፡ በዚህም ጊዜ አባታችንም ያቺን ዛፍ ‹‹ከበታችሽ ካሉት ሕዝብ ጋር ተነሥተሽ ሒጂ›› ብሎ በቃሉ አዘዛት፡፡ ያን ጊዜም ያች ዛፍ ከሕዝቡ ጋር ተነሥታ የሁለት ጦር ውርወራ ያህል ሔደች፡፡ ጌታችን በቅዱስ ወንጌሉ ‹‹የሰናፍጭ ቅንጣት ታህል እምነት ቢኖራችሁና ይችን ሾላ ተነስተሽ ወደዚህ ነይ ብትሏት ትመጣለች፤ ይህን ተራራ ከዚህ ሂድ ብትሉት ይሄዳል›› እንዳለ አባታችን አባ ዘግሩምም ይህንን አደረጉ፡፡

ከአባታችን ይባረኩ፤ እጅ ይነሡም ዘንድ አርባ አራት ቅዱሳን በደመና ተጭነው አባታችን ካለበት ቦታ ወደ ዐደል መጡ፡፡ ሶምሶን ከአህያ መንጋጋ፤ ሙሴ ከዐለት ውሃ እንዳፈለቁ ሁሉ ለሚያስፈልጋቸው ነገር ይጠቀሙበት ዘንድ አባታችንም በጸሎቱ በአንድ ጊዜ አርባ አራት የውሃ ምንጮችን አፍልቆ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ይህን አይተው አደነቁ፤ ስምህ ዘግሩም ይሁን አሉት፤ ስለዚህም አባታችን አባ ዘግሩም ተባለ፤ ምንጮቹም ድውያንንና ሕሙማንን የሚፈውሱ ሆኑ፡፡

ዳግመኛም ለአባታችን የሚገለገልበት አንድ አህያ ነበረው፤ የሚጭነው ሰው ሳይከተለው ለሁለት ቀናት ሔዶ ወደ ጫነው ሰው ቤት ይመለስ ነበር፤ የአገሩ ሰዎችም ይህን አይተው ያላቸውን ሁሉ ይጭኑትና ብቻውን ሔዶ ወደ አባታችን ይመለስ ነበር፡፡

የአቡነ ብርሃነ መስቀልን ተአምራቱን ዜናውን በሰማ ጊዜ ከንጉሡ ባለሟሎች አንዱ መጣ፡፡ ሌላም በቤቱ አጠገብ የሚኖር አንድ ሰው መጣና ‹‹ጨው ጭኜ ወደ ገበያ እወስድበት ዘንድ አህያህን ስጠኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ የተቸገሩትን ለመርዳት የሚልከው አንድ አህያ ነበረውና አባ አብርሃምም ‹‹የጨው መጠን ምን ያህል ነው?›› አለው፡፡ ያ ሰውም ‹‹በሰቅል ስሳ ይሆናል›› አለው፡፡ አባታችን አብርሃምም ‹‹ውሰደው ከተናገርኸው በላይ ግን አትጫነው›› አለው፡፡ ሰውየውም አህያውን ወስዶ አባታችን እንዳለው ጫነው፤ ለአባታችን ያልነገረውን በቤቱ የተረፈውን ግን ያ ሰውና ወንድሙ ተሸከሙት፡፡
እነርሱም ተካፍለው ተሸክመው መንገዳቸውን እየሄዱ ሳለ ከአገር ብዙ በራቁ ጊዜ ወንድሙን ‹‹ና አህያውን እንጫነውና እንደፈቀድነው እንሒድ የሚያየን የለምና›› አለው፡፡ በዚሀመ ምክራቸው መሠረት ተሸክመውት የነበረውነ በአህያው ላይ ጫኑት፡፡ ነገረ ግን አህያው መንቀሳቀስን ፈጽሞ እምቢ አለ፤ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አላለም፤ ሲገፉትና ሲደበድቡት ብዙ ደከሙ፤ እንዲህ እያደረጉ ሳሉ አንድ አገልጋይ የንጉሥ መልእክት ይዞ መጣ፡፡ እኒህን ስሕተተኞችም አገኛቸውና ‹‹ጌቶቼ ለምን ትደክማላችሁ?›› አላቸው፡፡
እነርሱም ‹‹ይህ አህያ አልሄድም አለን›› አሉት፤ የንጉሡ መልእክተኛም መንፈስ ቅዱስ አነሳሳውና ከፊታቸው ቆመና ‹‹የዚህ ነገር ምክንያቱ ምንድን ነው?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ይህን አህያ ከአንድ መንፈስ ቅዱስ ካደረበት ቀሲስ አመጣነው፤ በዚህ ቀሲስ ቃል ላይ በጨመርን ጊዜ መሔድን እምቢ አለን›› በማለት የሠሩትን ነገሩት፡፡ ‹‹እስኪ የጨመራችሁትን ቀንሱለት›› አላቸው፤ ቀነሱለትና ያን ጊዜ አህያው ተነሥቶ እነርሱም ወደሚፈልጉበት ቦታ ሔዱ፡፡ ይህንንም ሁለት ጊዜ ሦስት ጊዜ ደጋግመው አደረጉ እምቢም አላቸው፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የቅዱሱን ቃል በመተላለፋቸው እንደሆነ አወቁ፤ ያም የንጉሡ አገልጋይ ተደንቆ ‹‹ኑ ይህ ቅዱስ ካለበት አድርሱኝ›› አላቸው፡፡ አባታችን ካለበት ቦታም ደርሶ ከእርሱ ዘንድ ተባረከ፡፡

ያም አህያውን የወሰደው ሰው ከአቡነ ብርሃነ መስቀል እግር ሥር ተንበርክኮ ‹‹በፊትህ በድያለሁና ቃልህንም አሳብያለሁና አባቴ ሆይ ይቅር በለኝ፤ አህያውም መሄድን እምቢ አለ፤ የጨመርንበትን ሸክም በቀነስንለት ጊዜ ግን ይሄዳል›› አለው፡፡ ዳግመኛም ‹‹…እኔ ግን እንደ እኔ አይነት ሰው ነህ መስሎኝ ቃልህን አፈረስሁ፤ አንተ ግን በፍቅርህ ገመድ ሳብኸኝ›› አለው፡፡ አባታችን ብርሃነ መስቀልም ‹‹ለምን ሐሰት ተናገርህ? መጽሐፍ ‹ሐሰት የኀጢአት መጀመሪያ ናት፤ ሐሰተኞችም የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም› ይል የለምን?›› በማለት ከመከረው በኋላ በሰላም ወደቤቱ እንዲሔድ ነገረው፡፡

ያም ሰው ከአቡነ ብርሃነ መስቀል ዘንድ ወጥቶ መንገዱን ሔደ፤ ያ የንጉሡ መልእክተኛም አብርሃም ከተባለ ከአቡነ ዘግሩም ዘንድ ተባርኮ ወጣ፤ የቤተ ክርስቲያኗንም አሠራር አይቶ የአባታችን የአብርሃምን ተአምር አደነቀ፤ የንጉሡን ትእዛዝ ይፈጽም ዘንድም መንገዱን ሄደ፡፡ ከብዙ ቀናት በኋላ ያ መልእክተኛ ከንጉሡ ዘንድ ደረሰ፤ ስመ መንግሥቱ ቆስጠንጢኖስ ለተባለ የእግዚአብሔር ወዳጅ ለሆነ ለንጉሥ ዳዊት ነገሩን ነገረው፡፡ ‹‹ጻድቅ ንጹሕ የሆነ ቀሲስ አለ፤ በዚህ ዘመን በመንግሥትህ ሀገር ሁሉ እንደርሱ ያለ ሰው የለም፤ ሥራው ሁሉ እንደቀደሙት አባቶች ነውና›› አለው፡፡

በዐይኑ ያየውን፤ በጆሮው የሰማውን ሁሉ ስለሠራት ቤተ ክርስቲያንም ነገረው፤ ንጉሡም ይህን ሁሉ በሰማ ጊዜ በልቡ ተደሰተ፤ በመንፈሱም ሐሴትን አደረገ፤ እግዚአብሔርንም አመሰገነው፤ እንዲህም አለ፡- ‹‹በዘመነ መንግሥቴ የተሰወረውን የሚያውቅ፤ ተአምራትን የሚያደርግ እንዲህ ያለ ጻድቅ ሰውን የሰጠኝ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ስሙ ይክበር፡፡ አባቴ ቤተ ክርስቲያን ማነጽ በፈለግህ ጊዜ ወደ እኔ ለምን አልላክህም ብሎ ላከበት፤እኔ ከደቀ መዛሙርትህ እንደ አንዱ አይደለሁምን በረከትህን በተቀበልሁ ነበር አለ፡፡ በዚህ የመንግሥት ዙፋን ላይ ያለሁ በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው እንጂ በራሴ ፈቃድ ይመስልሃልን በእስረኞች መካከል ሳለሁ ከእስረኞች መካከልም ተኝቼ ሳለ ከዚያ አውጥቶ በአባቶቼ በሰይፈ አርዕድና በዐምደ ጽዮን ዙፋን ላይ አስቀመጠኝ፡፡ አንተ ግን በኀጢአቴ አትናቀኝ፤ ለቤተ ክርስቲያን የምትፈልገውን ይህን ገንዘብ ውሰድ፡፡›› ዳግመኛም ለአባታችን ልብስ ላከለት፤ ሚስቱም እንዲሁ ላከች ‹‹በጸሎትህ አትርሳን›› አሉት፡፡

ከዚህም በኋላ ይመነኩስ ዘንድ ወደደ፤ የመላእክትና የቅዱሳን ልብስ የምትሆን የምንኩስና ልብስን ያለብሰው ዘንድ የአቡነገብረ መንፈስ ቅዱስ ረድእ ወደ ሆነው ወደ አባ ብሶይ መጣ፡፡ ወደ እርሱ ደርሶ ሥርዐተ ምንኩስና ከፈጸመለት በኋላ አባታችን አብርሃም ‹‹የቀድሞ ስሜን ተውልኝ›› አለው፤ አባ ብሶይም ‹‹ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን ስም እንደ ለወጠላቸው ስምህን እለውጣለሁ እንጂ አይሆንም›› አለው፡፡ ‹‹ስምህንም አብርሃም፣ ጳውሎስ፣ ዮሐንስ ከሚሉት መካከል ዕጣ በማጣጣል እሰይምሃለሁ›› አለው፡፡

ሦስት ጊዜም ዕጣ ጣሉ፤ አብርሃም የሚለውም ስም ወጣ፤ ይህ ነገር ከእግዚአብሔር እንደሆነ አወቀ፡፡ከታናሽነቱ ጀምሮ የአብርሃም ምግባር የሆነውን እንግዳ መቀበልን፣ እግር ማጠብንና የተራበውን ማብላት ጀመረ፤ ስለዚህ አብርሃም መባል ተገባው፡፡ ‹‹ከታናሽነቴ ጀምሮ የአብርሃምን ሃይማኖት እንደወደድሁ፣ እንግዳ በመቀበል እንደ ኖርሁ ይህን ስም የሰጠኝ እግዚአብሔር ይመስገን›› አለ፡፡ መንኩሶ በፈቃዱ አብርሃም ተብሎ ተጠርቷልና በብዙ ገድልና በትሕርምት በዚያች ቦታ ኖረ፡፡
የነዳያን ፍቅር በልቡ ውስጥ አለ፤ ሁል ጊዜ ስለ ምግባቸውና ስለ ልብሳቸው ያስብ ነበር፤ ለሚያስፈልጋቸው ነገርም ገንዘብ ይሰጣቸው ነበር፡፡ ለድኆች ልብሱን ያካፍላል፤ ለእነርሱም ሰጥቶ እርሱ ራቁቱን ይቆማል፤ ልጆቹም ይመጣሉ፤ ‹‹ልብስህ ወዴት ነው?›› ይሉት ነበር፤ እርሱም ‹‹ሌቦች በማያገኙበት ቦታ አለ›› ይላቸው ነበር፡፡ ልጆቹ ግን ሥራውን አያውቁም ነበር፤ ውዳሴ ከንቱ እንዳይሆንበት ሁሉን ይሠውር ነበር፤ አይገልጥላቸውም ነበር፤ ድኃ ባየ ጊዜ አጽፉን ይሰጥ ነበር፤ አጽፉን ይቅርና ምንም ልብስ አያስቀርም ነበር፡፡

አንድ ቀን አንድ ድኃ መጥቶ ስለ እግዚአብሔር ስም ምግብና ልብስ ለመነው፡፡ አባታችን ያን ድኃ ባየው ጊዜ አጽፉን ሰጠው፤ ዳግመኛ አንድ ድኃ መጣ፤ በቤቱም የሚሰጠውን አጣ፤ መጠምጠሚያውን አውርዶ እርሷንም ለድኃው ሰጠውና በቤቱ ተቀመጠ፡፡ አንድ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ መጥቶ ራቁቱን አገኘውና ተቆጣበት፤ ‹‹ክቡር አባቴ ሆይ! ለምን እንዲህ ትሆናለህ? አለው፡፡ ‹‹ለምትበላውና ለምትለብሰው ሳታስቀር ያለ አቅምህ ለምን ምጽዋት ትሰጣለህ? ልብስህንና መጎናጸፊያህን ሰጥተህ አንተ ራቁትህን ትሆናለህ፡፡›› አባታችንም ‹‹ልጄ ሆይ! ፈጽሞ ስለሚያረጅና ስለሚጠፋ የዚህ ዓለም ልብስ ፈንታ የብርሃን መጎናጸፊያ የሚያለብሰኝ አምላኬ አለልኝ›› አለ፤ ልጆቹም ሌላም ልብስ አምጥተው አለበሱ፡፡ ‹‹ይህንም እንደ ቀደመው አታድርግ›› አሉት፤ እርሱ ግን ስለ ድኆችና ስለ ችግረኞች ፍቅር ብዙ ጊዜ ምጽዋት ያደርግ ነበር፤ ቅብዓት በሰውነት፣ ውሃ በአንጀት እንዲገባ የነዳያን ፍቅር ወደ ልቡ ገባ፡፡

የነዳያንን የጩኸት ድምፅ በሰማ ጊዜ ከልቡ ደስታ የተነሣ ለመነሣት ይፈልጋል፤ ከማእድ ላይ ቢሆንም እንኳን ድምፃቸውን ከሰማ እጁን ወደ ማእድ አያወርድም ነበር፤ ይሰጣል እንጂ ምንም ነገር አያተርፍም ነበር፡፡ ነዳያን ግን ዘወትር ጩኸትና ልመናን አያቋርጡም ነበር፤ አባታችን ስለ ምግባቸውና ስለ ልብሳቸው እንደሚያስብ አውቀው ከቤቱ አይርቁም ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ወደ አንዲት ታላቅ ሀገር ሔዶ ከዚያ ደረሰ፤ በሰንበት ምሽት ለእሑድ አጥቢያ ከዚያ አደረ፤ ሥርዓተ ቁርባን ከተፈጸመ በኋላ ደቀ መዝሙሩን ‹‹ልጄ የምንበላው ነገር አለህ ወይስ የለህም?›› አለው፤ ያ ደቀ መዝሙርም ‹‹አባቴ አዎን አለኝ›› አለው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ያያቸውን ታላላቅ መነኮሳት ሰበሰበ፤ ቁጥራቸውም ዐራት መምህራን ነበሩ፡፡ የተዘጋጀ ምግብና ጠላ ያን ጊዜ እነርሱም ከቤታቸው እንጀራ አመጡ፤ ሁለት ያመጣ አለ፤ ሦስትም ያመጣ አለ፤ ሁላቸውም እንደ አቅማቸው አመጡ፤ አባታችንም ጸሎት ያደርግ ዘንድ ተነሣ፤ ባረከላቸውም፡፡

ደቀ መዝሙሩንም ‹‹ጠላውን አምጣው›› አለው፤ ሁለት መነኮሳትም እንሥራውን አመጡት፤ ከመካከላቸው አንዱን ጠጣ አለው፤ ቀምሶም ለአባታችን ሰጠው፤ ጣዕሙ ደስ ባሰኘው ጊዜ አባታችን ከሩቅ ሀገር የመጡ የተራቡ ሰዎች ከቤቱ ደጃፍ እንዳሉ አወቀ፡፡ መነኮሳቱንም ‹‹አባቶቼ፣ ወንድሞቼና ልጆቼ ፈቃዳችሁ ከሆነስ ለክርስቶስ እንሰጠው ዘንድ ለነዳያንና ለችግረኞች እንስጣቸው›› አላቸው፡፡

በቤተ ክርስቲያን የተሰበሰቡ ወንድሞች መነኮሳት፣ ክቡራን ካህናት፣ ዲያቆናትና ሕዝቡ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሆነ፣ በወንጌል ወተት ያደገ፣ የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የአባታችንን ትሕትና፣ ትሩፋትና ቅድስና ባዩ ጊዜ አዘኑበት፡፡ ምንም ቃል አልመለሱለትም፤ በቦታቸው ወይም በቤታቸው አልነበሩምና፤ በልባቸው ‹‹እኛስ ከሩቅ ሀገር የመጣን አይደለምን?›› አሉ፡፡ እነርሱ ግን ከዚያው ይኖሩ ነበር፤ አባታችን ግን ነዳያንን ሰብስቦ ያንን ምግብ ሰጣቸው፡፡

ወደ ቤቱ ተጠርተው የመጡ እነዚያ መነኮሳትም አንዲት ቃል አልተናገሩም፤ ነገር ግን በልባቸው ተቆጡ፤ በጣምም አዘኑ፤ አባታችን ግን ደቀ መዛሙርቱን ሌላ ማእድ ያቀርቡ ዘንድ አዘዘ፤ ከመንገድ ስንቅ ይመገቡ ነበርና ጥቂት አመጡ፡፡ ገና ሳይቀምሱም ከሕዝብ አንዱ ‹‹አባቴ ሆይ! ጸልይልኝ፤ ይህን ጥቂት በረከትም ተቀበል›› ብሎ ብዙ ጠላ ላከ፤ እነዚህ መነኮሳት ግን ይህን ባዩ ጊዜ ፈጽመው ተደነቁ፤ ፈጽመው ፈሩ፤ ተንቀጠቀጡም፡፡ አባታችንም ተነሥቶ ለክርስቶስ ሰጠሁት፤ ለተራቡትም አስቀደምሁ፤ ለድኆች የሚሰጥ ለእግዚአብሔር ያበድራል የሚል ተጽፏልና አላቸው፡፡

እነዚህ መነኮሳትም ‹‹አባታችን መምህራችን ሆይ! ይቅር በለን አንተ ብዙ ሐዘንን ታውቃለህና፤ እኛ ስለሆዳችንና ስለልብሳችን አዘንን፤ አንተ ግን እንደ ጌታህ ክርስቶስ የድኆችና የችግረኞች ወዳጅ ነህና›› አሉት፡፡ ‹‹አላወቅንምና አባታችን ይቅር በለን፤ አንተ ፈቃደ እግዚአብሔርን ትፈጽማለህ፤ እርሱም ልመናህን ይሰማልና›› አሉት፡፡ ‹‹እንዲሰጥህ አላወቅንም፤ ነገር ግን ጎተራህን ሁሉ እንደሚሞላልህ ሰምተን ነበር፤ የተዘጋጀ ምግብንም እንዳወረደልህ ሰምተን ረሳን፤ አሁንም አባታችን ይቅር በለን፤ ባንተ ላይ ተቆጥተን ነበር፤ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር እንደሆነ አላወቅንም፤ አንተ ግን አስቀድመህ ለተራቡት ሰጠህ፤ ቀጥሎም ከአምላክህ በረከት ለእኛ ለመብላት ለተዘጋጀን ሰጠኸን›› አሉት፡፡ አባታችን ዘግሩምም ‹‹ወንድሞቼና ልጆቼ ይህን የማደርገው ለሰው ልታይ ብዬ አይደለም፤ ለትምክህትም አይደለም፤ እግዚአብሔር የሰጠኝ ሀብት ነው እንጂ›› አላቸው፡፡ ‹‹እኔ እሰጣለሁ፤ እርሱም የሚያስፈልገኝን ነገር አላሳጣኝም›› አላቸው፤ እነርሱም ከእርሱ ተባረኩ፤ ከዚህም በኋላ ታላላቅ ተአምራትና ድንቅ ነገርን የሚያደርግ የእግዚአብሔርን ገናናነት ተነጋገሩ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀንም አባ ዘግሩም ቆሞ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ መጣ፤ ቅድስት የሆነች የጎኑን መወጋትና ቁስሎቹን ሁሉ አሳየው፡፡ በደሙ መፍሰስም ተደሰተ፤ ሰግዶም እንዲህ አለ፤ ‹‹ጌታየ የሚፈሰውን ደምህን እዳስስ ዘንድ ፍቀድልኝ›› አለው፤ ጌታችንም ቅዱስ የሆነ ደሙን ይዳስስ ዘንድ ፈቀደለት፤ እንደ ቶማስም ጎኑን ዳሰሰ፤ ቶማስስ ደቀ መዛሙርቱን ስላላመነ ነበር፤ ይህ አባታችን ግን ጌታችን ‹‹ሳያዩኝ የሚያምኑኝ ብፁዓን ናቸው›› ብሎ እንደተናገረው ሳያይ ያመነ ነው፡፡ ይህ አባታችን ግን ሳያይ አመነ፤ በቅዱስ ደሙ መፍሰስም ደስ አለው፤ ወንድሞቼ ሆይ ለአባታችን የተሰጠውን ጸጋ ተመልከቱ፤ የመድኃኒታችንን ቁስሎች ዳስሷልና፤ ለድኆች የማዘን ፍሬው ይህ ነው፤ ‹‹ለድኆች የሚራራ ለእግዚአብሔር ያበድራል›› ተብሏልና፡፡

ለሰው ልጅ የሚሰጥ ታላቅ ጸጋን አገኘ፤ ከሀገሮች ሲመለስም ወደ ደብረ ጽዮን ለመሄድ ግባ ከተባለ ታላቅ ወንዝ ደረሰ፤ ከፈሳሹ ብዛት የተነሣ ስትበረታታ አገኛት፡፡ ብዙ ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበሩ፤ የሚያደርጉትንም አጡ፤ ብፁዕ አባታችን ግን ከወንዙ ዳር ቆመ፤ በምርጉዙም በባሕሩ ላይ አማተበ፤ ያን ጊዜ ወንዙ ወዲያና ወዲህ ተከፈለ፤ በዚያ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ተሻገሩ፡፡ ነቢዩ ሙሴ የኤርትራን ባሕር በከፈላት ሕዝቡንም በመራ ጊዜ እንደ ተሻገሩ ሁሉ ተሻግረዋልና እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ይህም አባታችን ባሕርን በየብስ አሻገራቸው፤ ከዚህ በኋላ በሰላም ወደ ቤቱ ደረሰ፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ገድለ_ቅድስት_ጸበለ_ማርያም እና #ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት #ከገድላት_አንደበት)
#ጥቅምት_25

ጥቅምት ሃያ አምስት በዚህች ቀን #ቅዱስ_አቡነ_አቢብ (አባ ቡላ) አረፈ፣ የመላእክት አምሳል የሆነ #አባ_እብሎይ አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_ዮልዮስ_ሰማዕት ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቡነ_አቢብ (አባ ቡላ)

ጥቅምት ሃያ አምስት በዚህች ቀን ታላቅና ክብር የሆነ አቢብ የተባለ መስተጋድል አባ ቡላ አረፈ።

የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሐሪክ ነው እነርሱም ከሮሜ አገር ሉፊ ከሚባል አውራጃ ናቸው በዘመናቸውም ከሀዲው ንጉሥ መክስምያኖስ በክርስቲያን ወገኖች ላይ መከራ ስለ አመጣ ስደት ሁኖ ነበርና እነርሱም በስደት ብዙ ዘመን ኖሩ።

ልጅንም በአጡ ጊዜ የተባረከ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ በጾም በጸሎት ተወስነው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ የእግዚአብሔርም መልአክ በሕልም ተገለጠላቸውና ፍሬ የመላበትን ዘለላ ሰጣቸው።

ይህም ቅዱስ በተፀነሰ ጊዜ በቤታቸው አጠገብ ታላቅ ዛፍ በቀለ በቅጠሉም ላይ በሮማይስጥ ቋንቋ ቡላ የእግዚአብሔር አገልጋይ በጽዮንም አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ ያከበረው የሚል ጽሑፍ ነበረበት።

በተወለደም ጊዜ ክርስትና ሳያስነሡ ዓመት ሙሉ አኖሩት እመቤታችን ማርያምም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትርዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት ሒዶ ሕፃኑን እንዲአጠምቀው አዘዘችው እርሱም ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው ስሙንም ቡላ ብሎ ሰየመው እናትና አባቱም ሳይነግሩት ቡላ ስለ ሰየመው አደነቁ ዕፁብ ዕፁብ አሉ።

ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ በጸለየ ጊዜ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ወረደ እርሱም ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ከሕፃኑ ጋር አቀበላቸው በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በሰም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት በአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው ብሎ ተናገረ።

ከጥቂት ዘመንም በኋላ አባትና እናቱ ኅዳር ሰባት ቀን ሙተው ሕፃኑ ብቻውን ቀረ።

ሕፃኑም ዐሥር ዓመት በሆነው ጊዜ ለጣዖት መስገድን የሚያዝ ከሀዲ መኰንን መጣ ቅዱስ ቡላም በሰማ ጊዜ ወደ መኰንኑ ሒዶ የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ መኰንኑም በአካል ታናሽነቱን አይቶ እጅግ አደነቀ በዚያንም ጊዜ በችንካር እንዲቸነክሩት ሥጋውንም እንዲሠነጣጥቁት ቆዳውንም ከዐጥንቱ እንዲገፉ እጆቹንና እግሮቹንም በመጋዝ እንዲቆርጡ ጀርባውንም እንዲገርፉ በሾተሎችና በጦሮች መካከል አድርገው ከመንኰርኵር ውስጥ እንዲጨምሩት ዳግመኛም በመንገድ ላይ እንዲጐትቱት አዘዘ የመላእክት አለቃ ሚካኤልም መጥቶ አዳነው ያለ ጉዳትም ጤነኛ አደረገው።

ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ መኰንን ሒዶ እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገመ መኰንኑም ተቆጥቶ በሚያዝያ ወር ዐሥራ ስምንት ቀን ራሱን በሰይፍ ቆረጠው ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው ወደ አንድ ገዳምም ወስዶ የምንኲስና ልብስንና አስኬማን በመስቀልም ምልክት አለበሰው። እንዲህም አለው ከቅዱሳን ጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞሃል።

ያን ጊዜም ቅዱስ አባ ቡላ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጣ ያለ ማቋረጥም በውስጧ እየተጋደለ ኖረ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራውንና ስቅለቱን በአሰበ ጊዜ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሱን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውር ነበር።

በአንዲትም ቀን ከዛፍ ላይ በተወረወረ ጊዜ ሰይጣን ሊገድለው ስለ በረታበት ሞተ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና መድኃኑታችን ከሞት አነሣውና እንዲህ አለው ከእንግዲህ ስምህ ቡላ አይሁን አቢብ ይባል እንጂ የብዙዎች አባት ትሆናለህና።

እርሱም የክርስቶስን ፍቅር እጅግ ጨመረ ፊቱንም እየጸፋ ሥጋውን በየጥቂቱ እየቆረጠ ጀርባውንም ሰባት መቶ ጊዜ እየገረፈ ኖረ ጌታችንም ይፈውሰው ነበር በየእሑድም ቀን ከቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም እንደተወለደ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽለት ነበር።

ስለዚህም ሳይበላ ሳይጠጣ አርባ ሁለት ዓመት ኖረ ዳግመኛም ናላው ፈስሶ እስቲአልቅ ዐሥራ ሁለት ወር በራሱ ተተክሎ ኖረ። በአንዲትም ቀን የጌታችንን መከራ በአሰበ ጊዜ ሰይፉን በአንጻሩ ተከለ ከዕንጨት ላይም ወጥቶ በላዩ ወድቆ ሞተ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ አለችው ። ከበድኑም ቃል ወጥቶ የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል አላት እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣቸው።

ዕድሜውንም ፈጽሞ ከዚህ ዓለም የሚወጣበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችንም ይዞ ተገለጠለት ወዳጄ አቢብ ሆይ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደእኔ ና ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን ለተራበም የሚያጠግበውን ለተጠማ የሚያጠጣውን የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ ይህንም ብሎ አፉን ሳመው በደረቱም ላይ አድርጎ ወደአየር አወጣው የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሱ ከሥጋው ተለየች ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_እብሎይ

ዳግመኛም በዚህችም ቀን ደግሞ አክሚም ከሚባል አገር የመላእክት አምሳል የሆነ አባ እብሎይ አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አሞኒ የእናቱ ስም ሙስያ ነው ሁለቱም በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን የሆኑ በሕጉ ጸንተው የሚኖሩ ድኆችንና መጻተኞችን የሚወዱ የሚረዱ ናቸው።

ነገር ግን ልጅ አልነበራቸውም ሙስያም ዕንጨት የያዘ ብርሃናዊ ሰው በቤቷ ውስጥ ሲተክለውና ወዲያውኑ ለምልሞ አብቦ ሲያፈራ ያ ብርሃናዊው ሰውም ከዚህ ፍሬ የሚበላ ሁሉ ለዘላለም ይኖራል ሲላት እርሷም ከፍሬው ወስዳ ስትበላና በአፏ ውስጥ ጣፋጭ ሲሆንላት በልቧም ፍሬ ይሆንልኝ ይሆን ስትል ራእይን አየች።

ከእንቅልፏም በነቃች ጊዜ ራእይን እንዳየች ለባሏ ነገረችው እርሱም እርሷ እንዳየችው ያለ ማየቱን ነገራት እግዚአብሔርንም አብዝተው አመሰገኑት ትሩፋትንና ተጋድሎን በመጨመር በየሁለት ቀን የሚጾሙ ሆኑ ምግባቸውም እንጀራና ጨው ነው።

ይህን ቅዱስ እብሎይን በፀነሰችው ጊዜ እናቱ በገድል ወንዶችን እስከምታሸንፍ ድረስ በየሌሊቱ ሁሉ አንድ ሽህ ስግደትን ትሰግዳለች ሕፃኑን እስከ ወለደችው ድረስ ዘጠኝ ወር ያህል እንዲህ ስትጋደል ኖረች።

በወለዱትም ጊዜ እብሎይ ብለው ሰየሙት በጐለመሰም ጊዜ የምንኩስናን ልብስ ሊለብስ ወደደ ምክንያትም እስቲያገኝ እንዲህ ኖረ አቢብ የሚባል ወዳጅ ነበረውና እርሱ በሌሊት ወሰደው ከላዕላይ ግብጽ በሚገኙ ገዳማት በአንዱ ገዳም ውስጥ መነኰሰ በገድልም በመጠመድ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ።
ከጥቂት ወራትም በኋላ በጥቅምት ወር ሃያ አምስት ቀን አባ አቢብ አረፈ ያን ጊዜ አባ እብሎይ አብሎግ ወደሚባል ገዳም ሔደ ወደርሱም ብዙ ሰዎች ተሰበሰቡ እርሱም በበጎ አምልኮ እግዚአብሔርን መፍራትን የሚያስተምራቸው ሆነ።

ቅዱስ አቢብም በአረፈበት ቀን መታሰቢያውን ሲያደርጉ ይህ ቅዱስ አባ አብሎይ ወንድሞች ሆይ በአባ አቢብ ስም ዛሬ ጸሎትን የሚጸልየውን ኃጢአቱን እግዚአብሔር ያስተሰርይለታል በዕረፍትህ መታሰቢያ ቀን የአባ አቢብ ፈጣሪ ሆይ ኃጢአቴን ሁሉ ተውልኝ ብሎ አንዲት ጸሎትን የሚጸልየውን ሁሉ እኔ ኃጡአቱን እተውለታለሁ ሲል ቃል ኪዳን ሰጥቶታልና አላቸው።

በዚያችም ሰዓት ከመነኰሳት አንዱ አረፈ እነርሱም ሊገንዙት በዚያ ቁመው ሳሉ አባ እብሎይ ስለ ተናገረው ቃል ከመነኰሳት አንዱ ተጠራጠረ በዚያንም ጊዜ ያ የሞተው ተነሥቶ ይናገር ዘንድ ጀመረ አባ እብሎይ ስለተናገረው ቃል ለምን ትጠራጠራላችሁ ለአባታችን አቢብ በመታሰቢያው ቀን በዚህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ሰጥቶናልና አላቸው ። ይህንንም ብሎ ተመልሶ አረፈ መነኰሳቱም አደነቁ ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።

ይህ አባ እብሎይም ብዙ ዘመናት ኖረ ልጆቹ መነኰሳትም በዙ ብዙ ገዳማትም ተሠሩለት። የኖረበትም ዘመኑ በታላቁ አባ መቃርስ ዘመን ነው የአባ እብሎይንም የትሩፋቱን ዜና አባ መቃርስ በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ተሰኘበት እርሱን እያጽናና እያረጋጋ መነኰሳት ልጆቹንም እግዚአብሔር የሚወደውን በመሥራት ያጸናቸው ዘንድ መልእክትን ጻፈለት።

ይህንንም በአስቄጥስ ገዳም ሁኖ አባ መቃርስ ሲጽፍ አባ እብሎይ በላዕላይ ግብጽ ሳለ በመንፈስ ቅዱስ አውቆ በዙሪያው ያሉትን መነኰሳት እንዲህ አላቸው። እነሆ ማጽናናትን የተመላች መልእክትን አባ መቃርስ ጻፈልን። ከዚህም በኋላ ከአባ መቃርስ ዘንድ የተላኩትን መነኰሳት ሁሉ ወጥተው በደስታ ተቀብለው አስገቧቸው መልእክቱንም በመነኮሳቱ ሁሉ ፊት አነበቡ በታላቅ ደስታም ደስ አላቸው።

ይህም አባ እብሎይ ወደ አባ አሞንዮስ የሔደ ከእርሱ ዘንድም የምትኖረውን ስሟ የዋሂት የተባለችውን የተቀደሰች ሴት ያየ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው ወዶ በየካቲት ወር በአምስተኛው ቀን አረፈ እኛ ግን የአባ እብሎይን ዜና ከወዳጁ ከአባ አቢብ ጋር ጻፍን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮልዮስ_ሰማዕት

በዚህችም ቀን ዳግመኛ አቅፋሐስ ከሚባል አገር ሰማዕት ለሆነ ለቅዱስ ዮልዮስ ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ነው።

ይህም ቅዱስ ዮልዮስ በሀገረ ጥዋ በሰማዕትነት በአረፈ ጊዜ በገድሉ እንደተጻፈ ዲዮቅልጥያኖስ ከጠፋ በኋላ ጻድቅ ሰው ቈስጠንጢኖስ ሳይጠመቅ ነገሠላቸው በጥቂት ወራትም የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ የቤተ ክርስቲያንም ሥልጣን ከፍ ከፍ አለ ከሀድያን ነገሥታት ለገደሏቸው ንጹሐን ሰማዕታት በስማቸው አብያተ ክርስቲያናት ታነፁ።

ስለ ቅዱሳን ሰማዕታትም ስለ ሥጋቸው እንዲአስብ ገንዞ በመሸከም ወደ አገራቸው እንዲአደርሳቸው ከአገልጋዮቹም ጋር ገድላቸውን እንዲጽፍ እግዚአብሔር እንደአቆመውና እንደጠበቀው ከዚህም እርሱ ራሱ በሰማዕትነት እንዴት እንደ ሞተ የቅዱስ ዮልዮስን ዜና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በሰማ ጊዜ ስለበጎ ተጋድሎው ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ቅዱስ ዮልዮስን አመሰገነው ።

ስለዚህም ለቅዱስ ዮልዮስ ያማረች ቤተ ክርስቲያን በግብጽ አገር ሠርተው ሥጋውን በውስጧ ያኖሩ ዘንድ ንጉሡ ወደ ግብጽ አገር ብዙ ገንዘብ ላከ በዚያንም ጊዜ ንጉሡ እንዳዘዘ አነፁለት ። የቅዱስ ዮልዮስንም ሥጋ አፍልሰው በውስጧ አኖሩት ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስም ከኤጲስቆጶሳቱ ጋር አከበራት እንደዛሬዪቱም ቀን በዓል አከበረባት ከሥጋውም ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ሕጻን_ሞዐ_ዘደብረ_ሊባኖስ

በዚህችም ቀን የደብረ ሊባኖሱ አባ ሕፃን ሞዐ ቃልኪዳን የተቀበሉበት ነው። በአባታቸው አርከሌድስ እናታቸው ትቤ ጽዮን ይባላሉ፡፡ የተወለዱት ጥር 25 ነው፡፡ አቡነ ሕፃን ሞዐ እና ከእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጋር የሥጋ ዝምድና አላቸው፡፡ ይኸውም አባታቸው አርከሌድስና ጸጋ ዘአብ ወንድማማቾቸ ናቸው፡፡ አርከሌድስና ጸጋ ዘአብ ሌሎች ሌሎች አራት ወንድሞች አሏቸው፡፡

እነርሱም እንድርያስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ቀሲስ ዮናስ እና ቀሲስ ዮሐንስ ናቸው፡፡ አርከሌድስ ሕፃን ሞዐን ይወልዳል፣ ጸጋ ዘአብ ተክለ ሃይማኖትን ይወልዳል፣ እንድርያስ ሳሙኤል ዘወገግን፣ ዘርዐ አብርሃም ታላቁ አኖሬዎዮስን፣ ቀሲስ ዮናስ ገላውዲዮስንና የፈጠጋሩን ማትያስን፣ እና ቀሲስ ዮሐንስ ዜናማርቆስን ይወልዳሉ፡፡ እነዚህ የከበሩ ቅዱሳን አባቶቻችን በእናታቸውም ወገን ቢሆን እንዲሁ በዝምድና የተቆራኙ ናቸው፡፡ አቡነ ሕፃን ሞዐ በሌላኛው ስማቸው ሕፃን ዘደብረ በግዕ ተብለውም ይጠራሉ፡፡ ይኸውም የደብረ በግዕን ገዳም የመሠረቱት እርሳቸው ስለሆኑ ነው፡፡

ከ47ቱ የሀገራችን ቀደምት ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ በመንዝና በተጉለት የሚገኙ ታላላቅ ገዳማትን አብዛኞቹን የመሠረቷቸው አቡነ ሕፃን ሞዐ ናቸው፡፡ ጻድቁ በክፉዎች ወሬና ሴራ ምክንያት ከበሬ ጋር ተጠምደው ሰማዕትነት የተቀበሉ አባት ናቸው፡፡ ከበሬ ጋር ሲታረሱ ውለው በእጅጉ ከደከማቸው በኋላ በኃይል የተነፈሱባት ምድሪቱ ዛሬም ድረስ ልክ እንደሰው የሚሞቅ ትንፋሽ ታወጣለች፡፡ ያም በጻድቁ እስትንፋስ አምሳል ከመሬት ውስጥ የሚወጣው እስትንፋስ ለአስም በሽታ መድኃኒት ሆኖ ብዙዎችን እየፈወ ነው፡፡

ገዳማቸው ከደብረ ብርሃን ከተማ በእግር የ2 ሰዓት መንገድ ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ ይኸውም ከወንይዬ ተክለ ሃይማኖት ገዳም አጠገብ ነው፡፡ ጻድቁ ጥር 25 ቀን ልደታቸው፣ ጥቅምት 25 ቃል ኪዳን የተቀበሉበት ዕለት ሲሆን ሐምሌ 25 ደግሞ ዕረፍታቸው ነው፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት እና #ከገደላት_አንደበት)
#ጥቅምት_26

ጥቅምት ሃያ ስድስት በዚህች ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ጢሞና በሰማዕትነት አረፈ፣ የጌታ ወንድም የተባለው #ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_ዮሴፍ መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሐዋርያ_ጢሞና

ጥቅምት ሃያ ስድስት በዚህች ቀን ጌታችን ከመረጣቸውና በሽተኞችን ሁሉ ይፈውሱ ዘንድ አጋንንትንም ያወጡ ዘንድ ሥልጣንን ከሰጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ ቅዱስ ሐዋርያ ጢሞና በሰማዕትነት አረፈ።

ይህም ቅዱስ ጢሞና ሰማያዊ ሀብትን መለኮታዊ ኃይልን ገንዘብ አድርጎ በሽተኞችን ፈወሳቸው አጋንንትም ተገዙለት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ በምድር ሳለ አገለገለው። ወደ ሰማይም ከዐረገ በኋላ ሐዋርያትን አገለገላቸው በሃምሳኛው ቀንም ጰራቅሊጦስ በወረደ ጊዜ የአጽናኝ መንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከእርሳቸው ጋር ተቀበለ።

ከዚህም በኋላ ሰባት ሁነው ከተቆጠሩት ዲያቆናት ጋር ሐዋርያት ሾሙት እነርሱ መንፈስ ቅዱስን ዕውቀትንም የተመሉ እንደሆኑ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ምስክር ሁኖአል።

በዲቁና አገልግሎትም ጥቂት ከአገለገለ በኋላ ብልቃ ከሚባል አገር በስተምዕራብ በሆነ ስብራ በሚባል አገር ላይ ኤጲስ ቆጶስነት ሾሙት በውስጧም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት አስተማረ ከዮናውያንና ከአይሁድም ብዙዎችን አጠመቃቸው።

የዚያች አገር ገዥም ይህን በሰማ ጊዜ ቅዱስ ጢሞናን ይዞ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃይቶ በእሳት አቃጠለው በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_ዮሴፍ

ዳግመኛም በዚህች ዕለት ቅዱስ ያዕቆብ ወልደ ዮሴፍ መታሰቢያ ነው፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ የጌታችን ወንድም የተባለውና የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የነበረው ነው፡፡

እርሱም የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ሲሆን ከልጆቹ ሁሉ ትንሹ ነው፡፡ ድንግልና ንጹሕ ሆኖ ከጌታችን ጋር እየተጫወተ አብሮ አድጓል፡፡ የያዕቆብ ወላጅ እናቱ በልጅነቱ ስለሞተችበትና የብርሃን እናቱ የሆነች ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያምን ዮሴፍ አረጋዊ በ83 ዓመቱ ጠባቂ ይሆናት ዘንድ ወደቤቱ ሲወስዳት ድንግል ማርያም ያዕቆብን የሙት ልጅ ሆኖ አግኝታው ከወለደችው ከመድኃኔዓለም ክርስቶስ ጋር አብራ ተንከባክባ አሳድጋዋለች፡፡

ያዕቆብ ከጌታችን ጋር አብሮ እየተጫወተ እያለ አንድ ቀን ትግል ይገጥማሉ፡፡ ያዕቆብም ጌታችንን አንስቶ ጣለው፡፡ ድጋሚ ተያያዙና አሁንም ያዕቆብ ጌታችንን ጣለው፡፡ ሦስተኛ ጊዜም እንዲሁ ሆነና ያዕቆብ የልብ ልብ ተሰማው፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ ድጋሚ ትግል ሲያያዙ ግን ጌታችን ያዕቆብን ወደ ሰማይ ወርውሮ መሬት ላይ በኃይል ጣለው፡፡ ያዕቆብም እጅግ ደንግጦ "ኃይልህን ደብቀህ ቆይተህ አሁን ምነው እንዲህ ታደርገኛለህ?" ሲለው ጌታችንም "እኔኮ ካልጣሉኝ አልጥልም" አለው፡፡

ከጌታችን ዕርገት በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ አድርገው ሾመውታል፡፡ ብዙዎችንም አስተምሮ ወደ ቀናች ሃይማኖት መልሷቸዋል፡፡ ሕዝቡም የታመሙትን ድውያንን ሁሉ እያመጡለት ይፈውሳቸው ነበር፡፡ ከኢየሩሳሌምም ውጭ እየሄደ ያላመኑትንም አስተምሮ እያጠመቀ ቤተ ክርስቲያን ይሠራላቸው ነበር፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ በጾም በጸሎት ሆኖ በመቆም ብዛት እግሮቹ አብጠው ነበር፡፡

አንድ ቀን አይሁድ ተሰብስበው መጥተው ጌታችን የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ወደ ያዕቆብ መጡ፡፡ እነርሱም ወደ ያዕቆብ የመጡት ጌታችን የዮሴፍ ልጅ እንደሆነና የእርሱም የሥጋ ወንድም እንደሆነ እንደሚነግራቸው አስበው ነበር፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ያዕቆብ ከፍ ካለው ከሦስተኛው መደብ ላይ ወጥቶ ጌታችን የራሱ የያዕቆብና የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ መሆኑን መሰከረባቸው፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ፍጹም አምላክ መሆኑን፣ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነና ከአብም ጋር ትክክል እንደሆነ መሰከረባቸው፡፡ ይህንንም በሰሙ ጊዜ አይሁድ እጅግ ተናደው በጽኑ ግርፋት ካሠቃዩት በኋላ ራሱን ቀጥቅጠው ገደሉት ሰማዕትነቱን ሐምሌ 18 ቀን በድል ፈጽሟል፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_27

ጥቅምት ሃያ ሰባት በዚህች ዕለት #የአምላካችን_የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው፣ #የጻድቁ_አባ_መብዓ_ጽዮን የቃልኪዳን ቀን፣ የማህሌተ ጽጌ ደራሲው #አባ_ጽጌ_ድንግል_ዘወለቃ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው፣ ቅዱስ አባት የሀገረ ቃው #ኤጲስቆጶስ_አባ_መቃርስ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#መድኃኔዓለም (በዓለ ስቅለት)

ጥቅምት ሃያ ሰባት በዚህች ዕለት የአምላካችን የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው።

መድኃኒታችን ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቸርነቱ ስለኹላችን ድኅነት ሲል ራሱን ወድዶ ፈቅዶ ለሞት አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ፍቅሩን አሳይቶናል። በቅዱስ ወንጌልም እርሱም መድኃኒታችን " ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም" ብሎ ነግሮናል። እውነት ነው፣ ራስን ነፍስን ስለጠላት ነፍስ አሳልፎ ከመስጠት በላይ ምን ድንቅ ነገርና ምን ድንቅ ፍቅር አለ?

ቸሩ አምላካችንን የአስቆሮቱ ይሁዳ ሊያስይዘው የሊቃነ ካህናቱን አገልጋዮች እየመራ አመጣቸው። እነርሱንም ማንን ትፈልጋላችሁ ሲላቸው የናዝሬቱ ኢየሱስን አሉት፣ እኔ ነኝ ቢላቸው የቸሩን አምላክ ድምጽ ሰምቶ አይደለም መቆም በሕይወት መጽናት የሚቻለው የለምና ወደ ኋላቸው ተስፈንጥረው ወደቁ። ደጋግሞም እንዲህ ኾነ። በኋላ ግን እኔ ነኝ ብሎ በፈቃዱ ይሁዳ ስሞ አሳልፎ ሰጣቸው።

ከያዙት በኋላ እያዳፉና እየጎተቱ በሰንሰለት አስረው ወደ ቀያፋና ሐና ግቢ ወሰዱት፣ እስከ ሦስት ሰዓትም አላሳረፉትም ሲያሰቃዩት አድረዋል፣ በራሱም ላይ ሰባ ሦስት ስቊረት ያለው ወደ ሦስት መቶ እሾኾችን የያዘ የእሾህ አክሊል ጎንጉነው ቢያደርጉበት የራስ ቅሉን ቀዶ ገብቶ እስከ ልቡ ዘልቋል። እንደምን ጭንቅ ነው? እንዲህም አድርገው ደግሞ እያፌዙ ርኲስ ምራቃቸውን ይተፉበትና በዘንግም ደጋግመው ይመቱት ነበር። እየተፈራረቁ ያለ ምንም ርኅራኄ ቸሩን አምላክ ሥጋው እየተቆረጠ እስኪወድቅ ድረስ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጽኑዕ ግርፋትን ገርፈውታል። የገረፉበትም ጅራፍ በላዩ ላይ ሥጋን እየጎመደ የሚጥል፣ ሕመሙ አንጀት ሰርሥሮ የሚገባ በስለት የተያያዘበት ነበር።

በኋላም አላሳረፉትም እንዲህ አድርገውትም በሊቶስጥራ አደባባይ ያንን ዕርጥብ መስቀል አሸክመው ወደ ቀራንዮ ወሰዱት። እርሱ ግን ይህን ኹሉ ግፍ ሲያደርሱበት አንድም አልተናገረም ነበር። በቀራንዮም በአምስት ጽኑዕ ቅንዋት (ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ) ቸንክረው ዕርቃኑን ሰቀሉት።

በዚህች ቀን ድንግል ማርያም ልቧ በሐዘን ተሰበረ መጽናናትንም አልፈለገች ነበር፤ ወዳጁ ቅዱስ ዮሐንስም ፍፁም ለቅሶን አለቀሰ እናቱንም እናት ትሆነው ዘንድ በእግረ መስቀሉ አደራን ተቀበለ። ቅዱሳት አንስት በፍጹም ሀዘንና በዋይታ ዋሉ። በስልጣኑም ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ። ሰባት ድንቅ የኾኑ ተአምራትንም አድርጎ አምላክ መኾኑን ገለጠ። ይህም ጽኑዕ የኾነ ለሰማይ ለምድር የከበደ ነገር ሲከሰት ፀሐይ አምላኬን ዕርቃኑ እንዴት አያለሁ ብላ ጨለመች። ጨረቃ ደም ኾነች፣ ከዋክብቱም ረገፉ፣ ንዑዳን ክቡራን ንጹሐን መላእክትም ትዕግስቱን እያደነቁ በጽኑዕ ሐዘንና መደነቅ ከቅዱስ ዕፀ መስቀሉ ፊት እንደሻሽ ተነጠፉ።

አስራ አንድ ሰዓት በሆነም ጊዜ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከታላቅ ክብርና ሐዘን ጋር ቅድስት ሥጋውን ከመስቀሉ አውርደው በክብር ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት። በሦስተኛውም ቀን እንደተናገረ ተነሳ።

በዛሬዋ ቀን ቤተ ክርስቲያን የመድኃኔለምን የስቅለት በዓል በደማቁ ታከብራለች፤ ይህም የለውጥ በዓል ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው ስጋውን የቆረሰው መጋቢት 27 ቀን ነው፤ ይህ በዓል ግን በዐቢይ ጾም ስለሚውል በዐቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለና በዓል ማክበር ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት 27 ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ሰርታልናለች፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_መብዓ_ጽዮን

አባ መብዓ ጽዮን በ፲፭ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ልጅ በማጣታቸው በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን ከሚለምኑ ባልና ሚስት ተወለዱ። የንቡረ እድ ሳሙኤል ረባን የሆነው መብዓ ጽዮን አባቱ እስከ ዳዊት ያለውን ትምህርት አስተማረውና ዲቁናን ተቀበለ። ልጁ የትምህርት ዝንባሌ እንዳለው አባቱ ተረድቶ ቤተ ማርያም ከሚባለው ደብር ወስዶ ተክለ አማኅጸኖ ከሚባል የቅኔ መምህር ዘንድ አስገባው። በዚያም ቅኔና እና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን እውቀቶችን ገበየ። ከዚህም በተጨማሪ ሥዕል መሳልና ጽሕፈት መጻፍ ተማረ።

መብዓ ጽዮን የልጅነቱን ዘመን ሲፈጽም ‹‹ለነፍሳቸው ድኅነት ዋጋ ያገኙ ቅዱሳን ብዙ ናቸው።በመጾም ያገኙ አሉ፤ በትምህርት ያገኙ አሉ፤ በድካም ያገኙ አሉ፤ በጸሎት በትጋት ያገኙ አሉ፤ እኔ ግን የጌታዬን የኢየሱስ ክርስቶስን የሞቱን መታሰቢያ ማድረግ ይገባኛል። በዚህም ፊቱን አያለሁ፤ እርሱ ጌታ ለደቀመዛሙርቱ "የትንሣኤዬን መታሰቢያ ብታደርጉ የሞቴን መታሰቢያ አድርጉ ብሏልና" በማለት ፍላጎቱ በምንኩስና በመኖር ፈጣሪን ማገልገል መሆኑን ለወላጆቹ ገለጸላቸው።

አባትና እናቱም "ፈጣሪህን ለማገልገል ኅሊናህ ከአሰበ እሺ፤ በጀ ደስተኛ ነን" ብለው ፈቀዱለት። ከዚያም መብዓ ጽዮን ዳሞት አባ ገብረክርስቶስ ወደሚባል መነኩሴ በመሄድ መነኮሰ። አባ መብዓ ጽዮን አባ ገብረክርስቶስ ጋር በመቀመጥ ሥርዓተ ምንኩስናን ካጠኑ በኋላ ከአባ ገብርኤል ዘንድ ሄደው የቅስናን ማእረግ ተቀበሉ። ከዚያም በኋላ በአበው ሕግ በምንኩስና ተወስነው፤ በበአታቸው ሆነው ‹‹ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የዕለተ ዓርቡን መከራህን አሳየኝ፤ ስለራሴ ፈጽሞ አለቅስ ዘንድ›› ብለው በጸልዩ ጊዜ ‹‹መከራ መስቀሉን ለማየት ትፈቅዳለህን?›› ብሎ ጠየቃቸው። ጻድቁ አባ መብዓ ጽዮንም ‹‹አዎ አይ ዘንድ እወዳለሁ›› ሲሉ ለጌታቸው መለሱለት። ያን ጊዜም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕፀ መስቀል ተተከለ። በመስቀሉ ላይም እጆቹና እግሮቹ ተቸንክረውና ተዘርግተው ታዩ ፤በራሱ ላይም የእሾህ አክሊል ደፍቶ ነበር።

እንዲህ ሆኖ በሮም አደባባይ ለቅዱስ ጴጥሮስ እንደታየው ጌታችን ለአባ መብዓ ጽዮንም ታያቸው። ከዚህም በኋላ አባ መብዓ ጽዮን የጌታችን የመድኃኔዓለምን ሕማሙን፣ መከራውን፣ ግርፋቱን፣ እስራቱን በጠቅላላ ፲፫ቱን ሕማማተ መስቀል በማሰብ ጀርባቸውን በአለንጋ ይገርፉ ፤ራሳቸውንም በዘንግ ይመቱ ነበር። የጌታን መከራ መስቀል እያሰቡ ዐይኖቻቸው አስከሚጠፉ ድረስ ያለቅሱ ነበር ። ጌታችን ግንደ መስቀሉን (የመስቀሉን ግንድ) አንደተሸከመ በማሰብ ትልቅ ድንግያ ተሸክመው ይሰግዱ ነበር። መራራ ሐሞት መጠጣቱን በማሰብ ዓርብ ዓርብ ኮሶ ይጠጡ ነበር። የጌታ ደቀመዝሙር ዮሐንስ ወንጌላዊ ጌታ በተሰቀለ ጊዜ አብሮ ስለነበርና ዐይን በዐይን ስለተመለከተ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ መስቀል እያሰበ ፸ ዘመን ፊቱን በሐዘን ቋጥሮ እንደኖረ ሁሉ ጻድቁ አባ መብዓ ጽዮንም እንደ ዮሐንስ ወንጌላዊ የጌታችንን መከራ መስቀል እያሰቡ ከዓለም ተድላና ደስታ ተለይተው በትምህርት ፣ በትሩፋት ፣ በገድል ጸንተው ኖረዋል። ጻድቁ መብዓ ጽዮን በሕይወተ ሥጋ ዘመናቸው የላመ የጣመ እንዳልተመገቡ፤በፈረስ በበቅሎ እንዳልሄዱ፤አልጋ ላይ እንዳልተኙ፤ገድላቸው ያስረዳል። የክርስትናን ትምህርት ለጋፋት ሰዎች እንዲስፋፋ ያደረጉት አባ መብዓ ጽዮን የጌታን ሕማማተ መስቀል እያሰቡ ዘወትር ስለሚያነቡ ዐይኖቻችው ጠፍተው ነበር። ነገር ግን እመ ብዙኃን የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ወደኚህ ጻድቅ አባት በአት የብርሃን ጽዋ ይዛ መጥታ ዐይኖቻቸውን
ቀብታ አድናቸዋለች። ከዚህ የተነሳ በትረ ማርያም እየተባሉ ይጠሩ አንደነበር ገድላቸው ያስረዳል።

የጻድቁ መታሰቢያ በዓል በየዓመቱ ጥቅምት ፳፯ ቀን ከመድኃኔዓለም የስቅለት በዓል ጋር ይከበራል። ጥቅምት ፳፯ ቀን ለወዳጆቹ እውነተኛውን ዋጋ የሚከፍል መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለጻድቁ አባ መብዓ ጽዮን ብዙ ቃል ኪዳን የገባበት ቀን ነው።

የአቡነ መብዓ ጽዮን ረድኤታቸው፣ በረከታቸውና አማላጅነታቸው አይለየን፤አሜን!!!

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ጽጌ_ድንግል_ዘወለቃ

በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረ ሊቅ ሲኾን፤ አባ ጽጌ ድንግል (ጽጌ ብርሃን) ሀገሩ ይፋት ሃይማኖቱ ኦሪት ነበረ፡፡ በንጉሥ ሰሎሞን ፈቃድና በካህኑ አዛርያስ መሪነት የብሉያት መጻሕፍትን ከዕብራይስጥ ወደ ግእዝ ተርጕመው ሊያስተምሩ፣ ታቦተ ጽዮንን ከኢየሩሳሌም ይዘው ወደ ኢትዮጵያ ከመጡትና የብሉያት መጻሕፍት ሊቃውንት ከነበሩት ከ318 ሌዋውያን (ከቤተ እስራኤላውያን) ነገድ ነው፡፡ የተወለደውም በሰሜን ሸዋ በይፋት አውራጃ ውስጥ ሲሆን፤ መጀመርያ ኢእማኒ (ያላመነና ያልተጠመቀ) ነበር።

ከዕለታት አንድ ቀን ይህ ሰው፤ በወጣትነት ዕድሜው አውሬ ለማድን ወደ ጫካ ሄደ፣ ጫካዋም በዚያው በይፋት አውራጃ የምትገኝና ልዩ ስሟ ደንስ (ገዳመ ደንስ) ትባላለች፣ በጫካዋ ውስጥም ፊቷ በጽጌረዳ አበባ የተከበበና ያጌጠ፣ እጅግም ደስ የምታሰኝ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል አይቶ በሥዕሏ ውበት እየተደነቀ ሥዕሏን ሲመለከት እንደ እርሱ ያልተጠመቀ ጓደኛው መጥቶ፣ "ምን እየፈለግህ ነው? የክርስቲኖችን ሥዕል ነውን?" ብሎ ለድንግል ማርያም ምስጋና ይግባትና በያዘው በትር ሥዕሏን ሲመታት ወዲያው ተቀሥፎ ሞተ። ከዚህ በኋላ ክንፎቹ በጽጌረዳ አበባ ያጌጡ የመሰለ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል በነጭ ወፍ ተመስሎ ወደ እርሱ መጥቶ አንድ ቀይ መነኩሴ እሰኪመጣ ድረስ፣ ይህችን ሥዕል ጠብቃት ብሎ በሰው አነጋገር ነግሮት ተሠወረ።

የአቡነ ዜና ማርቆስ የገድል መጽሐፍ፣ እንደሚናገረው ካህን ከነበረው ከአባቱ ከዘርዐ ዮሐንስ አና ከእናቱ ማርያም ዘመዳ በ1262 ዓ.ም. ኅዳር 24 ቀን በሰሜን ሸዋ ግዛት በሚገኘውና ልዩ ስሙ እቲሳ ቅዱስ ሚካኤል በሚባለው አጥቢያ የተወለደው አቡነ ዜና ማርቆስ ደብረ ብስራት ከሚባለው ገዳሙ ወደ ይፋት መጥቶ ከነብዩ ኢሳይያስ ትንቢት ከምዕ. 11፥1 ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ ወየዐርግ ጽጌ እምኔሃ እያለ በግእዝ ቋንቋ ሲያነብ አባ ጽጌ ድንግል በሰማ ጊዜ አባቶቼ አይሁድ የነቢያትን ትንቢት ንባቡን አስተምረውኛል አውቀዋለሁ፤ ትርጕሙን ግን አላውቀውምና ተርጕምልኝ አለው፡፡

አቡነ ዜና ማርቆስም ሲተረጕምለት እንዲህ አለ፤ ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ፣ የሚለው ንባብ ከእሴይ ነገድ የሕይወት በትር የኾነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትወለዳለች ማለት ነው፡፡ ወየዐርግ ጽጌ እምኔሃ የሚለው ንባብ ደግሞ፤ እመቤታችን ተወልዳ፣ ከእርሷም ጌታ በድንግልና ይወለዳል፣ ከጌታም ክብር ይገኛል ማለት ነው፣ ይህም ጌታ ተወልዶ ትንቢቱ በእውነት ተፈጽሟል ብሎ ተረጐመለት፡፡ ኢሳ 7፥14፣ ማቴ18፥24፡፡

ይህ ሰውም (አባ ጽጌ ድንግልም) በዚህ ትርጕም ደስ ተሰኝቶ አባት ሆይ የኢሳይያስን ትንቢት በመልካም ሁኔታ ተረጐምከው፣ መልካም ነገርንም ተናገርክ አለውና፣ ሥዕሏ ወዳለችበት ቦታ ወስዶ ታሪኩ ከላይ እንደተገለጸው፣ በጫካ ውስጥ ያያትን ሥዕል ጓደኛው በያዘው ብትር ሲመታት ወዲያውኑ እንደተቀሠፈና ክንፎቹ በጽጌረዳ አበባ ያጌጡ፣ "አንድ ነጭ ወፍ /ቅዱስ ሩፋኤል/" ወደ እርሱ መጥቶ ቀይ መነኵሴ እስኪመጣ ድረስ ይህችን ሥዕል ጠብቃት ብሎ በሰው አነጋገር ያነጋገረውን ሁሉ ነገረው፣ አቡነ ዜና ማርቆስም ከሥዕሏ የተደረገውን ተአምር ሰምቶ፣ እጅግ ደስ አለውና በል መጀመሪያ እመቤታችን በድንግልና በወለደችው በፈጣሪ ልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ እመን ይህችን ሥዕል ያስገኘ፣ ሰማይና ምድርን፣ በውስጣቸው ያለውንም ሁሉ የፈጠረ፣ እርሱ እንደኾነ እውቅ አለውና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቆ ጽጌ ብርሃን ብሎ ሰየመው፡፡

ከዚህ በኋላ ሥዕሏን በገዳመ ደንስ ደብረ ብሥራት ወደሚባለው ገዳም ወስዶ በዘመነ ጽጌ ጥቅምት አንድ ቀን በክብር አስቀመጣት የምትከብርትንም ቀን ጥቅምት 3 እና ሰኔ 8 ቀን አደረገ፡፡

አቡነ ዜና ማርቆስም ጽጌ ብርሃንን ለመዓርገ ምንኵስና አበቃው፤ የአባ ጽጌ ብርሃንም ጽጌ ድንግል የሚል ቅጽል ስም አለው፣ በማኅሌት አገልግሎት ጊዜም ታላቁ ጻድቅ አቡነ ዜና ማርቆስ ቤተ ክርስቲያኒቱንና ሥዕሏን እየዞረ ሲያጥን፣ እመቤታችን የካህናቱን አገልግሎት እንደምትባርክ፣ ካህናቱ በግልጽ ይረዱ ነበር፣ አባ ጽጌ ብርሃንም ከመጠመቁ በፊት በአባቶቹ በአይሁድ ሥርዓት እያለ የብሉያት መጻሕፍትን የተማረ ነበር፣ የሐዲሳት መጻሕፍት ትርጓሜን ግን ከአቡነ ዜና ማርቆስ ተማረ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ላሉ አሕዛብ ሁሉ የድኅነት ምክንያት ትሆኑ ዘንድ ብርሃናቸው፣ መምህራቸው አደረግኋችሁ ብሉ ጌታ ነቢዩ ኢሳይያስንና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን እንደመረጣቸው፣ ኢሳ 49፥6.፣ የሐ.ሥራ13፥47 ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ዜና ማርቆስ ስብከተ ወንጌልን እንደ ዕለት ጉርስና እንደ ዓመት ልብስ አድርጎ፣ መላ ኢትዮጵያን ዞሮ፣ አስተምሮና ባርኮ የዕድሜ ባለጸጋም ሆኖ በተወለደ በ140 ዓመት በ1402 ዓ.ም ታኅሣሥ 3 ቀን ፣ ዐርብ ጠዋት ዐረፈ፡፡

አባ ጽጌ ብርሃንም በወሎ ክፍለ ሀገር በወራይሉ አውራጃ፣ ልዩ ስሙ ደብረ ሐንታ ለሚባለው ገዳም የሕግ መምህር ሆኖ ከተሸመውና ከጓደኛው ከአባ ገብረ ማርያም ጋር እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ፣ እንደ አንድ ልብ መካሪ በመሆን፣ እመቤታችንንና ፈጣሪ ልጇን በጎ በጎ መዓዛ ባላቸው አበባዎችና ፍሬዎች እየመሰለ የሚያመሰግነውን ማኅሌተ ጽጌ የተባለውን ድርሰት፣ በአባቷ በዳዊት መዝሙር መጠን 150 አድርጎ ደረሰ፡፡ ፍሬ ከአበባ አበባም ከፍሬ እንደሚገኝ ኹሉ በማኅሌተ ጽጌ እመቤታችንን በአበባ፥ ጌታችን በፍሬ፤ ወይም እመቤታችንን በፍሬ፥ ጌታችን በአበባ እየተመሰሉ የሚመሰገኑበት ምስጋና ነው። ሰቈቃወ ድንግል ማለት እመቤታችን ከልጇ ከመድኀኔዓለም፣ ከአረጋዊ ዮሴፍና ከሰሎሜ ጋር በስደቷ ወቅት ያየችውን መከራ፥ ልቅሶ ዋይታ የሚዘከርበት የማኅሌተ ጽጌ አርኬ ነው፡፡

(የሰቈቃወ ድንግልን ደራሲ በተመለከተ አባ ጽጌ ድንግል ደረሱት የሚሉ አሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ አባ ገብረ ኢየሱስ ዘገዳመ መጕና /አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ/ ወይም /አባ አርኬላዎስ/ ነው የደረሱት የሚሉም አሉ፡፡)

ፍቅር ለባልንጀራው ክፉ የማያደርግ የሕግ ፍጻሜ ነውና፤ ሮሜ 13፥10-11፣ አባ ጽጌ ብርሃንና አባ ገብረ ማርያምም የዘመነ ጽጌ የማኅሌት አገልግሎትን ሳይለያዩ በሰላምና በፍቅር (በአንድነት) አገልግለዋል፣ ማለትም አንድ ዓመት አባ ገብረ ማርያም የክረምት መውጫና የዘመነ ጽጌ ዋዜማ በሆነው መስከረም 25፣ ቀን ከደብረ ሐንታ መጥቶ ገዳመ ጽጌ (ደብረ ብሥራት) ገብቶ ከመስከረም 26 ቀን እስከ ኅዳር 5 ቀን ያለውን የዘመነ ጽጌ የ40 ቀን አገልግሎትን ከአባ ጽጌ ብርሃን ጋር ፈጽሞ ኅዳር 8 ቀን ወደ ደብረ ሐንታ ይመለሳል፤ በሚቀጥለው ዓመት ደግሞ አባ ጽጌ ብርሃን ከገዳመ ጽጌ (ከደብረ ብሥራት) ወደ ደብረ ሐንታ ሄዶ እንደዚሁ እንደ አባ ገብረ ማርያም 40ውን ቀን አገልግሎ ይመለሳል፣ እኒህ ሁለቱ ቅዱሳን ሊቃውንትም ታሪኩ ከላይ እንደተገለጸው እንዲህ እያደረጉ እስከ ዕለተ ዕረፍታቸው ድረስ በፍቅርና በትሕትና ሲያገለግሉ ኖረዋል፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_መቃርስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባት የሀገረ ቃው ኤጲስቆጶስ አባ መቃርስ አረፈ።

ለዚህም ቅዱስ የዝንጉዎችን ምክር ተከትሎ ያልሔደ፣ በኃጢአተኞችም ጎዳና ያልተጓዘ፣ በዘባቾችም መቀመጫ ያልተቀመጠ፣ የእግዚአብሔርን ሕግ መጠበቅ ፈቃዱ የሆነ እንጂ ሕጉንም በቀንና በሌሊት የሚያነብ የሚያስተምር ብፁዕ ነው የሚለው የነቢይ ዳዊት ቃል ተፈጽሞለታል።

ይህ አባ መቃርስ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመጠበቅ በመክሊት ነግዶ ዕጥፍ አድርጎ አትርፎአልና እግዚአብሔርም በእጆቹ ያደረጋቸውን ታላላቆች ድንቆች ተአምራት ስንቱን እንናገራለን። ስለርሱም እንዲህ ተባለ እርሱ በሀገረ ቃው ተሾሞ በወንበር ተቀምጦ ሕዝብን በሚያስተምራቸው ጊዜ ዘወትር ያለቅሳል ። ከደቀ መዛሙርቱም አንዱ እጅግ የሚወደው አማለውና አባቴ ሆይ ሁል ጊዜ ለምን ታለቅሳለህ ንገረኝ አለው እርሱም ስለ መሐላው ፈርቶ ዘይት በብርሌ ውስጥ እንደሚታይ የወገኖቼን ኃጢአታቸውን የከፋች ሥራቸውንም በማይና በምመለከት ጊዜ አለቅሳለሁ ብሎ መለሰለት።

ሁለተኛ ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመሠዊያው ላይ ተቀምጦ የየአንዳንዱን የሰውን ሥራ መላእክት ሲያቀርቡለት አየው በዚያንም ጊዜ እንዲህ የሚል ቃል ሰማ ኤጲስቆጶስ ሆይ ለምን ቸለል ትላለህ ሕዝቡን አትገሥጻቸውምን አታስተምራቸውምን እርሱም አቤቱ እነርሱ ትምርቴን አይቀበሉም ብሎ መለሰ። ሁለተኛም እንዲህ አለው ለኤጲስቆጶስ ሕዝቡን ማስተማር ይገባዋል ትምርቱን ካልተቀበሉ ግን ደማቸው በራሳቸው ይሆናል።

ከዚህም በኋላ መናፍቁ ንጉሥ መርቅያኖስ ወደ ሰበሰበው ጉባኤ ከሊቀ ጳጳሳቱ ዲዮስቆሮስ ጋር ይሔድ ዘንድ ጠሩት የተሰበሰቡትም አንዱን ክርስቶስ ሁለት ባሕርይ የሚሉ ናቸው በደረሰም ጊዜ ስለ ልብሱ አዳፋነት ወደ ንጉሥ አዳራሽ መግባትን ከለከሉት አባ ዲዮስቆሮስም ከእርሱ ጋር እንዲአስገቡት ጳጳስ መሆኑን ነገራቸው።

በገቡም ጊዜ አንዱን ክርስቶስን ሁለት ባሕርይ አድርገው ትስብእቱን ከመለኮቱ እንደለዩት እምነታቸውን ሰሙ ስለዚህም ንጉሡንና ጉባኤውን አወገዙአቸው እሊህ አባቶቻችን አባ ዲዮስቆሮስና አባ መቃርስ ስለ ቀናች ሃይማኖታቸው ነፍሳቸውን ለሞት አሳልፎ ለመስጠት ቆርጠዋልና ንጉሡም ወደ ደሴተ ጋግራ አጋዛቸው።

ከዚያም ከምእመን ነጋዴ ጋር ወደ እስክንድርያ አባ ዲዮስቆሮስን ሰደደው እርሱ ለአባ መቃርስ ትንቢት ተናግሮለት ነበርና እንዲህ ብሎ አንተ ግን በእስክንድርያ አገር የሰማዕትነት አክሊል ትቀበል ዘንድ አለህ።

አባ መቃርስም ወደ እስክንድርያ ሲደርስ በዚያን ጊዜ የመናፍቁ የንጉሥ መርቅያን በውስጡ የከፋች ሃይማኖቱ የተጻፈበት የመልእክት ደብዳቤ ደረሰ መልእክተኛውንም እንዲህ ብሎ አዞታል በእኛ ሃይማኖት አምኖ በዚህ መዝገብ ውስጥ መጀመሪያ የጻፈ በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ይሁን የሚል ነው አብሮታራ የሚባል አንድ ሰው ተቀዳድሞ በውስጡ ሊጽፍ ያንን መጽሐፍ ተቀበለ ቅዱስ አባ መቃርስም እንዲህ አለው ከእስክንድርያ አገር በሔደ ጊዜ ከእኔ በኋላ አንተ በቤተ ክርስቲያን የሠለጠንክ ትሆናለህ ብሎ የነገረህን የአባ ዲዮስቆሮስን ቃሉን አስብ ያን ጊዜ አብሮታራ ያንን ቃል አስታውሶ በዚያ በረከሰ መጽሐፍ ላይ ሳይጽፍ ቀረ።

የንጉሡም መልክተኛ አባ መቃርስ በንጉሥ ሃይማኖት እንደማያምን በአወቀ ጊዜ ተቆጥቶ ከኵላሊቱ ላይ ረገጠው ያን ጊዜም ሙቶ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ ሥጋውንም ምእመናን ወስደው ከነቢይ ኤልሳዕና ከመጥምቁ ዮሐንስ ሥጋ ጋር በአንድነት አኖሩት ወደ ወደደው ክርስቶስም የመንግሥት ዘውድን ተቀዳጅቶ ሔደ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።


(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት#የማሕሌተ_ጽጌ_ትርጕምና_ታሪክ#ገድለ_አቡነ_መብዓ_ጽዮን እና #ከገድላት_አንደበት)