ቅዱሳን ኅሩያን የዲ°ን ዮርዳኖስ ትምህርቶች
4.96K subscribers
919 photos
5 videos
33 files
239 links
የዲ.ን ሄኖክ ሀይሌን ስብከት በድምጽ እንለቃለን
ለአስተያየት @EMNE_TSYON @unitte_bot
በቴሌግራም ከፈለጉን @henokhailee
በfacebook ከፈለጉን https://www.facebook.com/tewahidosewhone/
በyoutube ከፈለጉን https://youtube.com/channel/UCq2ueVG6O3ZuKHJ485y7hfg
Download Telegram
#ነሐሴ_9

#አባ_ኦሪ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዘጠኝ በዚች ቀን ስጥኑፍ ከሚባል አገር የከበረ ቄስ አባ ኦሪ ምስክር ሁኖ ሞተ። ይህ ቅዱስ ብዙ ርኅራኄ ያለው በሥጋው በነፍሱም ንጹሕ የሆነ ነው ብዙ ጊዜም አምላካዊ ራእይን ያያል። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በመሠዊያው ላይ ታይቶ ብዙ ምሥጢራትን ገለጠለት።

ከዚህም በኋላ የአባ ኦሪ ዜናው በኒቅዮስ አገር መኰንን ዘንድ ተሰማ ወደርሱም አስቀርቦ ለአማልክት ዕጣን አቅርብ አለው እርሱም ለረከሱና ለተሠሩ አማልክት አልሠዋም ብሎ እምቢ አለው።

መኰንኑም ተቆጥቶ በብዙ ሥራ አስፈራራው ቅዱስ ኦሪም ሥቃዩን ምንም ምን አልፈራውም ጹኑ ሥቃይንም አሠቃየው። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ አገር ላከው በዚያም ጽኑዕ የሆነ ሥቃይን አሠቃይተው በወህኒ ቤት ጣሉት። በዚያም ድንቆች ተአምራቶችን በማድረግ በሽተኞችን ፈወሳቸው ።

ዜናውም በተሰማ ጊዜ ደዌ ያለባቸው ሁሉ ከየአገሩ ብዙዎች ሰዎች ወደርሱ መጥተው አዳናቸው። ይህንንም መኰንኑ ሰምቶ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ በመንግስተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ።

ከዚህም በኋላ የከበረ ዮልዮስ ሥጋውን አንሥቶ ገንዘው ወደ ሀገሩ ስጥኑፍም ላከው። የመከራውም ወራት ካለፈ በኋላ ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት ሥጋውን በውስጧ አኖሩ ከሥጋውም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። በማመንም ለሚመጡ በሽተኞች ሁሉ ታላቅ ፈውስ ሆነ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሱ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_9)
#ነሐሴ_10

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ #አባ_ዓቢየ_እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው፣ #ቅዱስ_መጥራ በሰማዕትነት ሞተ፣ #ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ የከበሩ #ቅዱሳን_ቢካቦስና_ዮሐንስ በሰማዕትነት ሞቱ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዓቢየ_እግዚእ_ኢትዮዽያዊ

ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ አባ ዓቢየ እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው። አባ ዓቢየ እግዚእ የተወለዱት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ትግራይ ተንቤን (መረታ) ውስጥ ነው። የተባረኩ ወላጆቻቸው ያፍቅረነ እግዚእ እና ጽርሐ ቅድሳት ይባላሉ። አጥምቀው "ዓቢየ እግዚእ" ሲሉ ስም ያወጡላቸው የወቅቱ ጳጳስ ሰላማ መተርጉመ መጻሕፍት ናቸው። ትርጉሙም 'በጌታ ዘንድ ታላቅ ሰው' ማለት ነው።

ዓቢየ እግዚእ በሕፃንነታቸው ሌሊት ሌሊት ባሕር ውስጥ ሰጥመው ሲጸልዩ አድረው ቀን ቀን እየተማሩ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቁ። ገና በወጣትነታቸው ወደ ታላቁ መነኮስ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ (ደብረ በንኮል) ሔደው መንኩሰዋል።

በገዳሙ በጾም በጸሎትና በስግደት ተወስነው ከኖሩ በኋላ ወደ ዋልድባ ሔደው የተሰወረች ቤተ ክርስቲያን አግኝተዋል። በጊዜው በአርባ ቀን አንዲት ቅጠል ብቻ ለቁመተ ሥጋ ይበሉ ነበር።

ከዚያም ወደ ሃገራቸው ተንቤን ተመልሰው ዛሬም ድረስ ድንቅ ሆኖ የሚታየውን ገዳም መሥርተው ብዙ መናንያንን አፍርተዋል። ዓቢየ እግዚእ ገዳማዊና ጻድቅ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያዊ አባትም ነበሩ። ከትግራይ እስከ ደንቢያ ደግሞ ሃገረ ስብከታቸው ነው።

አንድ ጊዜ ደቀ መዛሙርትን አስከትለው ለስብከት ሲንቀሳቀሱ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ደረሱ። ቀኑ ነሐሴ ዐሥር ነውና ተከዜ እስከ ገደፉ ሞልቶ ለሦስት ቀናት ባለመጉደሉ ከአንድ ሺ በላይ ሰዎች ሲያለቅሱ ደረሱ። ጻድቁ በአካባቢው የነበሩት ኢ-አማንያን (አሕዛብ) ቢሆኑም ራርተዋልና "አምላከ ሙሴ" ብለው ጸልየው ወደ ጥልቁ ውስጥ ገቡ።

ቅዱስ ሚካኤል አብሯቸው ነበርና ተከዜ ግራና ቀኝ ተከፍሎ መሃሉ የብስ ሆነ። ይሕን ድንቅ ያዩ ከዘጠኝ መቶ አርባ በላይ አሕዛብም አምነው በጻድቁ እጅ ተጠምቀዋል። ይሕም ዘወትር ነሐሴ ዐሥር ቀን በቤተ ክርስቲያናቸው (ጐንደር) ይከበራል።

ከዚያም እያስተማሩ ጐንደር ደረሱ። ያኔ ጐንደር በቀሃና አንገረብ ወንዞች የታጠረች አንዲት መንደር ነበረች። ጻድቁ ቀን ቀን እየሰበኩ ማታ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናቸው የታነጸበት ሥፍራ ላይ ሲጸልዩ ያድሩ ነበር።

በዚያ ዘመን ጐንደር ውስጥ ጅብ እባብና መሠል አራዊት ገብተው ሕዝቡን ጨረሱት። ይሕንን የተመለከቱት አባ ዓቢየ እግዚእ ወደ እግዚአብሔር አለቀሱ። በፍጹም ልባቸውም ስለ ሕዝቡ ለመኑ። የለመኑትን የማይነሳ ጌታ ወደ ጻድቁ ቀርቦ "በስምሕ የተማጸኑ በቃል ኪዳንህ ያመኑ: በምድር አራዊት አይሠለጥኑባቸውም። በሰማይም እሳትን አያዩም። ጐንደርንም አራዊት ገብተው ሰውን አይጐዱም።" ብሏቸው አርጓል።

አባ ዓቢየ እግዚእ በገዳማቸው ተንቤን ለብዙ ዘመናት በቅድስና ኑረው ሦስት ሙታንን አስነስተው ብዙ ድውያንን ፈውሰው ብሔረ ብጹዓንን ጎብኝተው የድኅነት ቃል ኪዳንም ተቀብለው በመቶ አርባ ዓመታቸው ግንቦት ዐሥራ ዘጠኝ ቀን አርፈዋል። የጻድቁ ክብር ለሁሉ ነውና እናስባቸው።

ይህች ዕለት ባሕረ ተከዜን ከፍለው ሕዝቡን ያሻገሩባት አሕዛብንም ያጠመቁባት ናትና በገዳማቸው ጐንደር ውስጥ በሚገኘው ቤተ ክርስቲያናቸውም ይከበራል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መጥራ

በዚህች ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በቅዱስ ዲሜጥሮስ ዘመንና በከሀዲው ንጉሥ በዳኬዎስ ዘመነ መንግሥት ቅዱስ መጥራ በሰማዕትነት ሞተ።

ይህም ቅዱስ የክብር ባለቤት #ክርስቶስን ክደው ለጣዖት መስገድን የሚያዝ የንጉሡን ደብዳቤ በሰማ ጊዜ ይህ ቅዱስ ወዲያውኑ ሒዶ ከወርቅ የተሠራ የአጵሎንን ክንድ ሰረቀ በየጥቂቱም ሰባብሮና ቆራርጦ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጣቸው።

የጣዖቱም አገልጋዮች ክንዱ ተቆርጦ አጵሎንን በአገኙት ጊዜ ስለርሱ ብዙዎችን ሰዎች ያዟቸው። በዚያንም ጊዜ ወደ መኰንኑ ቀርቦ ክርስቲያን እንደሆነ በፊቱ ታመነ ሁለተኛም የአጵሎንን የወርቅ ክንድ የወሰድኩ እኔ ነኝ ለድኆችና ለችግረኞችም ሰጠኃ ኋቸው አለው።

መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ አስጨናቂ የሆነ ታላቅ ሥቃይንም አሠቃየው ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጨመሩት #እግዚአብሔርም አዳነው ያለ ጥፋትም በጤና አወጣው።

ከዚህም በኋላ እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ ብዙ ደም ከአፍንጫው ወደ ምድር እስከ ሚወርድ ዘቅዝቀው በዕንጨት ላይ ሰቀሉት።

በዚያንም ጊዜ የ #እግዚአብሔር መልአክ ወርዶ ቅዱስ መጥራንን ፈታው ከተሰቀለበትም አውርዶ በመዳሠሥ አዳነው። አንድ ዕውር ሰውም መጣ ከአፍንጫው ከወረደውም ደም ወስዶ ዐይኖቹን ቀባ ወዲያውኑ አየ። መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀዳጀ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ መጥራ ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ

በዚህችም ቀን ዳግመኛ በከሀዲ መክስምያኖስ እጅ ቅዱስ ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ። በንጉሥ መክስምያኖስ ፊት በአቆሙት ጊዜ ለአማልክት ሠዋ አለው። የከበረ ሐርስጥፎሮስም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ #እግዚአብሔር_ኢየሱስ_ክርስቶስን አመልከዋለሁ ለእርሱም እሠዋለሁ። ንጉሡም ተቆጥቶ ሥጋው ተቆራርጦ በምድር ላይ እስቲወድቅ በበትር ይደበድቡት ዘንድ አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት።

ከዚህም በኋላ ወደ ወህኒ ቤት ጣሉት በላህያቸውም እንዲአስቱት ሁለት ሴቶችን ንጉሡ ወደርሱ ላከ ቅዱሱ ግን የ #ክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራቸው የዛሬ የሆነ የዚህንም ዓለም ኃላፊነት አስገነዘባቸው ወደ መክስምያኖስም በተመለሱ ጊዜ እንዴት አደረጋችሁ አላቸው።

እነርሱም እንዲህ አሉት በከበረ ሐርስጥፎሮስ አምላክ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ክርስቶስ እኛ እናምናለን ንጉሡም ሰምቶ አንዲቱን በዕንጨት ላይ ሰቅለው እንዲአቃጥሏት ሁለተኛዋን በአንገቷ ደንጊያ አንጠልጥለው ቊልቊል እንዲሰቅሏት አዘዘና ምስክርነታቸውን እንዲህ ፈጸሙ።

ከዚህም በኋላ ዕንጨቶችን ሰብስበው በማንደጃው ውስጥ አድርገው አነደዱ የከበረ ሐርስጥፎሮስን እጅና እግሩ እንደ ታሠረ ከውስጡ ጨመሩት ያን ጊዜም በስመ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ አለ እሳቱ ከቶ ምንም አልነካውም። ሕዝቡም ይህን አይተው የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ዐሥር ሺህ ያህል ሰዎች አምነው በሰማዕትነት ሞቱ።

ሁለተኛም የብረት ሠሌዳዎችን በእሳት አግለው አመጡ ቅዱሱንም በላያቸው በአስተኙት ጊዜ ምንም ምን የነካው የለም። ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው በክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃያ ሺህ አንድ መቶ ሰዎችና አርባ ሕፃናት አምነው ምስክር ሁነው ሞቱ።

ንጉሥ መክስምያኖስም አይቶ እጅግ ተቆጣ የቅዱስ ሐርስጥፎሮስንም ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ከንጉሡም ዘንድ በወጣ ጊዜ ጸሎትን አደረገ ፊቱንም በ #መስቀል ምልክት አማተበ ከዚህም በኋላ ምስክርነቱን ፈጸመ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሐርስጥፎስ እና በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።
ከዚያም በማግስቱ አበ ምኔቱ የምንኲስናን ልብስ አለበሳቸው በቀን እንደሚተያዩ በሌሊትም እርስበርሳቸው የሚተያዩ እስቲሆኑ በፊታቸው ላይ የመንፈስ ቅዱስ ብርሃን በራ ሁለተኛም በዚህ መነኵስ ላይ እንደሰዩ በራሶቻቸው ላይ የብርሃን አክሊል አዩ።

ከዚህም በኋላ ከመነኰሳቱ መካከል ተለይተው ወደ በረሀ ይገቡ ዘንድ ኀሳብ መጣባቸው። በዚያችም ሌሊት ብርሃንን የለበሰ ሰው ለአበ ምኔቱ ተገልጾ የ #ክርስቶስ በጎች እንዲወጡ የገዳሙን በር ክፈት አለው በነቃም ጊዜ ወደ በሩ ሒዶ ተከፍቶ አግኝቶት እያዘነና እየተከዘ ሳለ ሊወጡ ፈለገው እሊህ ቅዱሳን መጡ በፊታቸውም በትረ መንግስትን አየ።

በአያቸውም ጊዜ ደስ ብሎት ተገናኛቸው እነርሱም በልባቸው ያሰቡትን ነግረውት እንዲጸልይላቸው ለመኑት ለረጅም ጊዜም አለቀሰ ከዚህም በኋላ ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ በቀኙና በግራው አቆማቸው እጆቹንም ወደ ሰማይ ዘርግቶ ጸሎት አድርጎ ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቃቸው ዘንድ ወደ #እግዚአብሔር አደራ አስጠበቃቸው። ከዚያም በፍቅር አሰናበታቸው።

ከዚህም በኋላ አርጋኖን ወደ ምባል ወንዝ ሔዱ በዚያም አንድ ገዳማዊ በዚያን ወራት ያረፈ በውስጡ የኖረበትን በዓት አገኙ በውስጡም ያ ሽማግሌ ገዳማዊ ሲመገበው የነበረ ለምግባቸው የሚያስፈልጋቸውን የእህል ፍሬዎችን አገኙ ምግባቸውን በአዘጋጀላቸው በ #እግዚአብሔርም እጅግ ደስ አላቸው።

በድንግያ ውርወራ ርቀት መጠን አንዱ ከሁለተኛው የተራራቁ ሁነው ሰፊ በሆነ ተጋድሎ ቡዙ ዘመናት ኖሩ። ሰይጣንም ቡዙ ጊዜ ይፈታተናቸው ነበር ግን አባታቸው ቅዱስ ኒቅዮስ በራእይ ወደ እሳቸው መጥቶ ስለ እነርሱ ይጸልያል ተኝተውም ሳሉ የዳዊትን መዝሙር ያስተምራችዋል በነቁም ጊዜ ያስተማራቸውን ሁሉ በትክክል ያነቡታል እጅግም ደስ ይላቸዋል።

አምላካዊ ራእይም ተሰጣቸው ተአምራትንም ያደርጋሉ በዚያችም በረሀ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ክርስቶስ ኃይል ሰይጣንን ድል እስከ አደረጉት ድረስ የቀኑን ሐሩር የሌሊቱን ቊር ታግሠው ሃያ ዘጠኝ ዓመት ነሩ።

ከዚህም በኋላ ስምዖን ወንድሙ ዮሐንስ እንዲህ አለው በዚህ በረሀ በመኖራችን ምን እንጠቃማለን ና ወደ አለም ወጥተን ሌሎችን እንጥቀማቸው እናድናቸውም ዮሐንስም መልሶ እንዲህ አለው ወንድሜ ሆይ ይህ ኀሳብ ከሰይጣን ቅናት የተነሣ ይመስለኛል።

ስምዖን እንዲህ አለው ከሰይጣን አይደለም በዓለም ላይ እንድዘበትበት #እግዚአብሔር አዞኛልና ነገር ግን ና እንጸልይ ያን ጊዜም በአንድነት ጸለዩ ልብሳቸውንም እስከ አራሱት ድረስ እርስበርሳቸው ተቃቅፈው አለቀሱ። ከዚህም በኋላ ስምዖን እስከሚሞትባት ቀን ሥራውን ይሠውርለት ዘንድ ወደ #እግዚአብሔር እየጸለየ ጎዳናውን ተጓዘ።

ወደ ዓለምም ገብቶ ራሱን እንደ እብድ አደረገ እብዶችንም የፈወሰበት ጊዜ አለ እሳትን በእጁ የሚጨብጥበትም ጊዜ አለ። ከዚህም በኋላ ከከተማው በር የሞተ ውሻ አግኝቶ በመታጠቂያውም አሥሮ እየጐተተ እንደሚጫወት ሆነ ሰዎች እስከሚሰድቡትና እስከሚጸፉት ድረስ።

በአንዲት ቀን እሑድ ከቅዳሴ በፊት የኮክ ፍሬ ይዞ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ መቅረዞችንም ሰበረ። ሴቶችንም መትቶ ከእርሳቸው ጋራ እንደሚተኛ ጐተታቸው ባሎቻቸውም ደበደቡት።

ዕረፍቱም ሲቀርብ የ #እግዚአብሔር መልአክ የእርሱንም የወንድሙ የዮሐንስንም የዕረፍታቸውን ጊዜ ነገረው ወደ ወይን ሐረግ ሥር ገብቶ ከወንድሙ ዮሐንስ ጋራ ነፍሱን በ #እግዚአብሔር እጅ ሰጠ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ባስሊቆስ

በዚህችም ቀን ቅዱስ ባስሊቆስ በሰማዕትነት ሞተ። በእሥር ቤትም እርሱ ሳለ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ተገልጦለት እንዲህ አለው የምስክርነትህ ፍጻሜ ደርሷልና ሒደህ ዘመዶችህን ተሰናበታቸው።

ከዚህም በኋላ ወታደሮችን ከእርሱ ጋራ ወደ ቤቱ ይሔዱ ዘንድ ለመናቸው ሒደውም ወደ ቤቱ ገቡ እናቱንና ዘመዶቹንም ተሰናበታቸው። በማግሥቱም የከበረ ባስሊቆስን ወደ ፍርድ ሸንጎ አቀረቡትና በሁለት ምሰሶዎች መካከልም አሥረው ሲደበድቡት ዋሉ በእግሮቹም ችንካሮችን አደረጉበት ደሙም በምድር ላይ ፈሰሰ ያየው ሁሉ አለቀሰለት።

ከዚህም በኋላ ከደረቀ ዕንጨት ላይ አሠሩት ዕንጨቱም በቀለና ቅርንጫፍና ቅጠሎችን አወጣ። ሰዎችም የልብሱን ጫፍ ለመንካት የሚጋፉ ሆኑ በበሽተኞችና በዚህ ዕንጨት ላይ ያደረገውን ተአምር አይተዋልና።

ከዚህም በኋላ ዋርሲኖስ ወደሚባል አገር በመርከብ ወሰዱት ወታደሮችም እንዳትሞት እህልን ብላ አሉት እርሱም እኔ ከሰማያዊ መብል የጠገብኩ ነኝ ምድራዊ መብልን አልመርጥም አላቸው።

ወደ መኰንኑም በአቀረቡት ጊዜ ለአማልክት መሥዋዕትን አቅርብ አለው የከበረ በባስሊቆስም እኔ አንድ ለሆነ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ የምስጋና መሥዋዕትን አቀርባለሁ አለው።

ሁለተኛም ወደ ጣዖታቱ ቤት እንዲአስገቡት አዘዘ እርሱም ቁሞ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ ያን ጊዜ እሳት ወርዶ ጣዖታቱን አቃጠላቸው መኰንኑም ፈርቶ ሸሽቶ ወደውጭ ወጣ። ቁጣንም ተመልቶ ይገድሉት ዘንድ ያ መኰንን አዘዘ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ባስሊቆስ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ መከራውን ይሳተፍ ዘንድ ስለ አደለውም አመሰገነው።

ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ ቆረጡት ብዙዎችም መላእክት ነፍሱን ሲያሳርጓት አዩዋት #ጌታችን_ኢየሱስም ወዳጄ ባስሊቆስ ወደ እኔ ና እኔ የምዋሽ አይደለሁም ተስፋ ያስደረግሁህን እፈጽምልሃለሁ ብሎ ጠራው። እንዲህም ተጋድሎውን ፈጸመ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_14)
#ነሐሴ_17

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን አሞራዊ #ቅዱስ_እንጣዎስ በሰማዕትነት ሞተ፣ ከደቡብ ግብጽ አቡስ ከሚባል አውራጃ መኑፍ ከሚባል ታናሽ መንደር #ቅዱስ_ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እንጣዎስ_አሞራዊ

ነሐሴ ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን አሞራዊ ቅዱስ እንጣዎስ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ አስቀድሞ #ክርስቶስን የካደ ነበር ገንዘብ ለማከማቸትም የሚተጋ ነበር።

በአንዲትም ዕለት ወደ ደማስቆ ከተማ ሔደ የበዓላቸው ቀን ነበርና ሕዝቡ ተሰብስበው ሳሉ ወደ ምሥራቃዊው ቅዱስ ቴዎድሮስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገባ ገብቶም ዕቃዎችን ማቃጠል ጀመረ #መስቀልንም ሰበረ።

ከዚህም በኋላ በሰማይ ውስጥ የእሳት ፍላፃዎችን ይዘው ከሀዲዎችን ሲነድፏቸው አየ እርሱንም የቀኝ ጐኑን አንዲት ፍላፃ ነደፈችው። ያን ጊዜም ተጨንቆ ላቡ ተንጠፈጠፈ ከጥልቅ ልቡም እንዲህ ብሎ ጮኸ የቅዱስ ቴዎድሮስ አምላክ የሕያው #እግዚአብሔር ልጅ #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመንኩብህ ከእንግዲህ ዳግመኛ ሌላ አምላክ እንዳያመልክ በልቡናው ቃል ገባ።

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ ክርስቲያኖችም በእርሱ ላይ የሆነውን አላወቁም ነገር ግን ጩኸቱንና የሚናገረውን ሰምተው አደነቁ እምነታቸውም ጠነከረ እጅግም ጸና። እንጣዎስም #ኤልያስ ወደ ሚባል ጳጳስ ሒዶ በርሱ ላይ የሆነውን ሁሉ ነገረው የክርስትና ጥምቀትንም ያጠምቀው ዘንድ ለመነው።

ጳጳሱም በውኃው ላይ በጸለየ ጊዜ የብርሃን ምሰሶ እንደ ቀስተ ደመና ሁኖ ሕዝቡ ሁሉ እያዩት ወረደ ቅዱስ እንጣዎስም ተጠመቀ። ከእርሱም ጋራ ከአይሁድና ከአረሚ ዐሥር ሽህ ሰባት መቶ ዘጠና ስምንት ያህል ሰዎች ተጠመቁ። ክብር ይግባውና የ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስን ሥጋውንና ደሙን ተቀበሉ።

ቅዱስ እንጣዎስም እንዲህ አለ እነሆ ይህን እያደነቅሁ ሳለ በእንቅልፌ ሕልምን አየሁ። ብርሃንን የለበሰች ሴት እጄን ያዘችኝ ወስዳም ወደ ኢየሩሳሌም አደረሰችኝ ወደ መሠዊያውም አቀረበችኝ እኔም ቅዱስ ቊርባንን ለመቀበል ተዘጋጀሁ በመሠዊያውም ውስጥ ነጭ በግን አየሁ ካህኑም በዕርፈ #መስቀል በሠዋው ጊዜ ደሙ ጽዋው ውስጥ ተጨመረ ከእርሱም የ #ክርስቶስን ሥጋና ደም በተቀበልሁ ጊዜ ሥጋው ንጹሕ ኅብስት ደሙም ጥሩ ወይን ሆነ።

ከዚህም በኋላ በደማስቆ ጐዳና ሲጓዝ አስቀድሞ የሚያውቁት ያዙት ወደ ንጉሡም ወሰዱት ንጉሡም #ክርስቶስን በማመን እንደጸና አይቶ ጥርሶቹ እስቲበተኑ አፉን በበሎታ እንዲመቱት አዘዘ አፉም ደምን ተመላ። ከዚህም በኋላ እህል ውኃን ሳይሰጡ በተበሳ ግንድ ውስጥ ሰባት ቀን ያህል አሠሩት ከዚያም አውጥተው ዲን፣ ሙጫ፣ ዝፍት ከስብ ጋራ ባፈሉበት እሳት ውስጥ ጨመሩት ከእርሱም የመልካም መዓዛ ሽታ ወጣ።

ወታደሮችም ከእሳት ውስጥ ቁሞ ሲጸልይ አገኙት። እሳቱም አልነካውም ወደ ንጉሥም ወሰዱት ንጉሡም የሥራይን ኃይል መቼ ተማርክ አለው ቅዱስ እንጣዎስም ንጉሡን እንዲህ አለው ሥራይንስ አላውቅም ነገር ግን ክብር ይግባውና በ #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ኃይል አሳፍርሃለሁ።

ንጉሡም ቁጣን ተመልቶ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ከዚህም በኋላ ቅዱስ እንጣዎስ ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ቆመ እጆቹንም ዘርግቶ ነፍሱን ወደ #እግዚአብሔር አማፀነ ሲጸልይም ወደርሱ እንዲህ የሚል ቃል መጣ ከእስጢፋኖስና ከጊዮርጊስ ጋራ ታርፍ ዘንድ አገልጋዬ በሰላም ና። ጸሎቱንም በፈጸመ ጊዜ ራሱን ቆረጡት ምስክርነቱንም ፈጸመ ከሥጋውም ቁጥር የሌላቸው ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሰማዕት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያዕቆብ_ግብጻዊ

በዚህችም ቀን ከደቡብ ግብጽ አቡስ ከሚባል አውራጃ መኑፍ ከሚባል ታናሽ መንደር ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ #እግዚአብሔርን የሚፈሩ ክርስቲያኖች ነበሩ ከእርሱ መወለድም በፊት ሦስት ሴቶች ልጆችን ወልደው ነበር።

ጥቂትም በአደጉ ጊዜ እንዲያስተምሩአቸውና በፈሪሀ #እግዚአብሔር እንዲአሳድጓቸው በገዳም ለሚኖሩ ደናግል ሰጧቸው። የብሉይና የሐዲስ መጻሕፍትንም ተማሩ። ወላጆቻቸውም ሊወስዷቸው በወደዱ ጊዜ እነርሱ ከደናግል ገዳም መውጣትን አልወደዱም። ነገር ግን ለ #ድንግል_ማርያምና ለልጅዋ ለ #ክርስቶስ ሙሽሮች ይሆኑ ዘንድ መረጡ ወላጆቻቸውም ከእርሳቸው በመለየታቸው አዘኑ።

መሐሪ ይቅር ባይ #እግዚአብሔርም በዚህ ቅዱስ ያዕቆብ መወለድ አጽናናቸው። ሰባት ዓመትም በሆነው ጊዜ አባቱ ዐውሎ ወደ ሚባል አገር ጥበብን ይማር ዘንድ ላከው ትምህርትንም ተምሮ በትምህርት ሁሉ ፍጹም ሆነ።

አባቱም ለገንዘቡና ለጥሪቱ ለእንስሶቹም ሁሉ ተቈጣጣሪ አደረገው በዚያም አንድ በሥውር ብዙ ትሩፋትን የሚሠራ የበጎች ጠባቂ ነበረ በክረምትም በበጋም ብዙ ጊዜ ወደ ውኃ ጒድጓድ እየወረደ መላዋን ሌሊት ሲጸልይ ያድር ነበር።

ቅዱስ ያዕቆብም ሽማግሌው የበግ ጠባቂ በሚያደርገው አምሳል እያደረገ በዚህ ሥራ ብዙ ዘመን ኖረ። ከዚህም በኋላ ሰይጣን በክርስቲያን ወገኖች ላይ መከራን አስነሣ ብዙዎች ክርስቲያኖችም በሰማዕትነት ሞቱ።

በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት ይሞት ዘንድ ከዚያ ሽማግሌ ጋራ ተስማማ ቅዱስ ያዕቆብም ከሽማግሌው ጋራ ሒዶ ይመለስ ዘንድ አባቱን ፈቃድ ጠየቀ እርሱም ሒድ አለው።

በሔዱም ጊዜ በላይኛው ግብጽ የንጉሥ ልጅ ቅዱስ ዮስጦስን መኰንኑ ሲአሠቃየው አገኙት ሽማግሌውም ልጄ ሆይ ይህ የንጉሥ ልጅ መንግሥቱን ትቶ እውነተኛውን ንጉሥ #ክርስቶስን እንደ ተከተለ ከሚስቱና ከልጆቹም እንደተለየ ተመልከት። እኛ ድኆች ስንሆን ለምን ችላ እንላለን ልጄ ሆይ እንግዲህ ተጽናና ከወላጆችህም በመለየትህ አትዘን አለው።

ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ ቀርበው ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ታመኑ የረከሱ አማልክቶቹንም ረገሙ ያን ጊዜም መኰንኑ አስቀድሞ ሽማግሌውን ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው ራሱንም በሰይፍ ፈጥኖ አስቆረጠው ምስክርነቱንም ፈጸመ።

ቅዱስ ያዕቆብን ግን ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው ከገመድ በተሠራ ጅራፍ ገረፈው ድንጋይም በእሳት አግለው በሆዱ ላይ አኖሩ። ዐይኖቹንም አቅንቶ ክብር ይግባውና ወደ #ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ጸለየ #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሆይ ከዚህ መከራ ርዳኝ አጽናኝም ያን ጊዜም ያለ ምንም ጉዳት አስነሣው።

ከዚህም በኋላ በማቅ ውስጥ አስጠቅልሎ በባሕር ውስጥ አስጣለው የ #እግዚአብሔርም መልአክ አውጥቶ ያለ ጉዳት በመኰንኑ ፊት አቆመው። መኰንኑንም አሳፈረው የረከሱ አማልክቶቹንም ረገመ።

ከዚህም በኋላ ፈርማ ወደሚባል አገር ላከው በዚያም የፈርማ መኰንን ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው ምላሱን ቆረጠው፣ ዐይኖቹንና ቅንድቦቹንም አወጣ፣ በመንኰራኩርም ውሰጥ አኬዱት፣ በመጋዝም መገዙት፣ ሕዋሳቱ ሁሉም ተሠነጣጠቁ። ደሙም እንደ ውኃ ፈሰሰ የእግዚአብሔር መልአክ ሱርያል ወርዶ ቊስሎቹን አዳነለት።

መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በሠለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘና ቆረጡት የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ። ከገምኑዲ ሀገር የሆኑ አብርሃምና ዮሐንስም ከእርሱ ጋራ ሰማዕታት ሆነው ሞቱ።

#ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን ።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_17+)
#ነሐሴ_18

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_እለእስክንድሮስ አረፈ፣ የከበረና የተመሰገነ ሐዋርያ #ቅዱስ_እንድራኒቆስ መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እለእስክንድሮስ

ነሐሴ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን ቁጥሩ ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስ አረፈ። ይህም አባት ከአርዮስ ወገኖች ብዙ ችግር ደርሶበታል እርሱ ከወገኖቹ ጋር ሁኖ አርዮስን አውግዞ ከቤተክርስቲያን አሳዶት ነበርና።

በታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመን በኒቅያ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ሊቃውንት አርዮስን በጉባኤ አውግዘው ከቤተ ክርስቲያን ለይተው በአሳደዱት ጊዜ ወደ ንጉሡ ቈስጠንጢኖስ ጓደኞቹን ይዞ ገብቶ በእለእስክንድሮስና በአትናቴዎስ ላይ ነገር ሠራ ሁለተኛም እለእስክንድሮስ ከካህናቱ ጋር ይቀበለው ዘንድ እንዲያዝለት ንጉሡን ለመነው።

ንጉሡም ልመናውን ተቀብሎ መልእክተኞችን ልኮ አባት እለእስክንድሮስን አስመጥቶ እንዲህ አለው "አትናቴዎስ ትእዛዛችንን በመተላለፍ አርዮስን አልቀበልም ብሏል፤ እኛም አንተን እንዳከበርንህ አንተ ታውቃለህ አሁንም ትእዛዛችንን አትተላለፍ አርዮስንም ከውግዘቱ ፈትተህ ልባችንን ደስ አሰኝ" አለው ።

ቅዱስ እለእስክንድሮስም ለንጉሥ እንዲህ ብሎ መለሰለት "አርዮስን እኮን ቤተክርስቲያን አልተቀበለችውም። ልዩ ሦስትነትን አያመልክምና" ንጉሡም "አይደለም እርሱ በ #ሥሉስ_ቅዱስ ያምናል እንጂ" አለው ቅዱስ እለእስክንድሮስም " #ወልድ በመለኮቱ ከ #አብ#መንፈስ_ቅዱስ ጋራ ትክክል እንደሆነ የሚያምን ከሆነ በእጁ ይጻፍ" ብሎ መለሰለት።

ንጉሥም አርዮስን አስቀርቦ "ትክክለኛ ሃይማኖትህን ጻፍ" አለው አርዮስም በልቡ ሳያምን ' #ወልድ#አብ ጋራ በመለኮቱ ትክክል ነው' ብሎ ጻፈ በሐሰትም የከበረ ወንጌልን ይዞ ማለ። ንጉሡም ቅዱስ እለእስክንድሮስን "አሁን በአርዮስ ላይ ምክንያት አልቀረህም ትክክለኛ ሃይማኖቱን ጽፎአልና በከበረ ወንጌልም ምሎአልና" አለው ።

አባ እለእስክንድሮስም ንጉሡን እንዲህ አለው "በአባትህ በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እጅ የተጻፈ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ አባቶች በእጆቻቸው የጻፉትን እርሱንና ወገኖቹን ከቤተ ክርስቲያን እንዳሳደዷቸው የአርዮስን ክህደቱንና ውግዘቱን አትናቴዎስ አንብቦታል። ነገር ግን አንድ ሱባዔ በእኔ ላይ ታገሥ በዚህ ሱባዔ በአርዮስ ላይ አንዳች ነገር ካልደረሰ ይህ ካልሆነ ሃይማኖቱ መሐላውም እውነት ነው እኔም ተቀብዬ ከካህናቱ ጋር እቀላቅለዋለሁ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎትም ከእሳቸው ጋራ አንድ ይሆናል።"

ንጉሡም አባት እለእስክንድሮስን እንዲህ አለው "እወቅ እኔ ስምንቱን ቀኖች እታገሥሃለሁ አርዮስን ካልተቀበልከው በአንተ ላይ የፈለግሁትን አደርጋለሁ።" ከዚህም በኋላ ከንጉሡ ዘንድ ወጥቶ ወደ ማደሪያው ሔደ ቤተክርስቲያንን ከአርዮስ መርዝ ያድናት ዘንድ በዚያ ሱባዔ እየጾመና እየጸለየ ወደ #እግዚአብሔር ሲለምን ሰነበተ።

ከዚያም ሱባዔ በኋላ አርዮስ መልካም ልብስን ለበሰ ወደ ቤተክርስቲያንም ገብቶ በመሠዊያው ፊት ከካህናቱ ጋራ ተቀመጠ። ከዚህም በኋላ አባ እለእስክንድሮስ እያዘነና እየተከዘ ገባ ከኀዘኑም ብዛት የተነሣ የሚሠራውን አላወቀም የቅዳሴውንም ሥርዓት ሊጀምር ቆመ። ያን ጊዜ የአርዮስ ሆዱ ተበጠበጠና ወጥቼ ልመለስ አለ ይህንንም ብሎ ወደ መጸዳጃ ቦታ ወጣ። ሊጸዳዳም በተቀመጠ ጊዜ አንጀቱና የሆድ ዕቃው ሁሉ ወጣ በዚያውም ላይ ሞተ።

በዘገየም ጊዜ ሊፈልጉት ወጡ በመጸዳጃውም ቦታ ሬሳውን ወድቆ አገኙት። ለዚህም ለአባት እለእስክንድሮስ ነገሩት እርሱም አደነቀ የከበረች ቤተክርስቲያኑን ያልጣላት ምስጉን የሆነ #ክርስቶስንም አመሰገነው።

ንጉሡም በሰማ ጊዜ አደነቀ ከሀዲ አርዮስም በሐሰት እንደማለና በሽንገላ እንደጻፈ አወቀ። የዚህንም አባት የእለእስክንድሮስን ቅድስናውን ዕውነተኛነቱ ሃይማኖቱም የቀናች መሆኗን የአርዮስንም ሐሰተኛነቱንና ከሀዲነቱን ተረዳ።

አንድ የሆነ #አብ_ወልድ_መንፈስ_ቅዱስንም አመሰገነው መለኮታቸውም አንድ እንደሆነ ታመነ።

ይህም አባት በበጎ ሥራ ጸንቶ ኖረ ለምለም ወደ ሆነ እርጅናም ደርሶ ወደ ወደደው #ክርስቶስ ሔደ የሕይወት አክሊልንም አገኘ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እንድራኒቆስ

በዚህችም ቀን የከበረና የተመሰገነ ሐዋርያ እንድራኒቆስ መታሰቢያው ነው። ይህንንም ሐዋርያ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ መረጠው። እርሱም የ #እግዚአብሔርን መንግሥት እንዲሰብኩ ጌታ ከመከራው በፊት ከላካቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቆጠረ ነው።

በጽርሐ ጽዮንም #መንፈ_ቅዱስ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ የ #መንፈስ_ቅዱስን ስጦታ ተቀብሎ በብዙ አገሮች ውስጥ ሰበከ። በኒውብያ አገር ላይም ሐዋርያት በአንብሮተ እድ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት በውስጧም ሰበከ በጨለማ በድንቁርና የሚኖሩ ብዙዎች አረማውያንንም የክብር ባለቤት ወደሆነ ወደ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖት አስገባቸው።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያ ዮልዮስን ወሰደው በአንድነትም በብዙ አገሮች ዙረው አስተማሩ። ብዙ ሰዎችንም አጠመቁ ተአምራትንም በማድረግ ከሰዎች ላይ አጋንንትን አባረሩ። ብዙዎች በሽተኞችንም ፈወሱአቸው የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሰው የክብር ባለቤት የሆነ የ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አብያተ ክርስቲያናትን አነፁ። አገልገሎታቸውንም በፈጸሙ ጊዜ #ጌታችን ከድካም ወደ ዕረፍት ከኀዘንም ወደ ደስታ ሊወስዳቸው ወደደ።

ከዚህ በኋላ ሐዋርያ እንድራኒቆስ ታመመና ግንቦት ሃያ ሁለት ቀን አረፈ ቅዱስ ዮልዮስም ገንዞ በመቃብር አኖረው።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_18 ና_ዘወርኀ_ግንቦት_22)
#ነሐሴ_19

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ በዚች ቀን የታላቁ #አባ_መቃርስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ የደግነት የምጽዋት የፍቅር አባት የሆነው #ደጉ_አብርሃም ጣዖት የሰበረበት፣ የአልዓዛር ልጅ #የቅዱስ_ፊንሐስ መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ቅዱስ_መቃርስ

ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሳስዊር ከሚባል አገር ወደ አስቄጥስ ገዳም የታላቁ አባ መቃርስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ።

ከዕረፍቱ በኋላ ከሀገሩ ከሳስዊር ሰዎች መጥተው ሥጋውን ሰርቀው ወደ ሀገራቸው ወሰዱት ቤተ ክርስቲያንም ሠርተውለት ሥጋውን በዚያ አኖሩት እስላሞች እስከ ነገሡበት ዘመንም በዚያ ኖረ።

ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ ቦታ አፍልሰውት በዚያም ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት። ለአባ መቃርስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ አባ ዮሐንስ እስከ ተሾመበት ዘመን ኖረ።

ሊቀ ጳጳሳቱም የከበረች ጾመ አርብዓን ሊጾም ወደ አባ መቃርስ ገዳም በወጣ ጊዜ ፈጽሞ አለቀሰ እንዲህም ብሎ ጸለየ። #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሆይ የከበረ የአባ መቃርስ ሥጋ በዚህ ገዳም በመካከላችን ይሆን ዘንድ እንድትረዳኝ እመኛለሁ።

ከጥቂት ቀኖችም በኋላ አባ ሚካኤል ሔደ ከእርሱ ጋራም ስለ ገዳሙ አገልግሎት አረጋውያን መነኰሳት አሉ ልቦናቸውም በመንፈሳዊ ሁከት ተነሣሥቶ ያመጡት ዘንድ የአባ መቃርስ ሥጋ ወደ አለበት ቦታ ደረሱ።

የአገር ሰዎችም በአዩአቸው ጊዜ በትሮቻቸውንና ሰይፎቻቸውን በመያዝ ከመኰንናቸው ጋራ ተሰብስበው ከለከሏቸው። በዚያቺም ሌሊት በልባቸው ፈጽሞ እያዘኑ አደሩ። አባ መቃርስም በዚያች ሌሊት ለመኰንኑ በራእይ ተገለጠለትና ከልጆቼ ጋራ መሔድን ለምን ትከለክለኛለህ እንግዲህስ ተወኝ ከእሳቸው ጋራ ወደ ቦታዬ ልሒድ አለው።

ያ መኰንንም በጥዋት ተነሣ እየፈራና እየተንቀጠቀጠ የከበሩ አረጋውያን መነኰሳትን ጠርቶ የከበረ የአባ መቃርስን ሥጋ ሰጣቸው። እነርሱም ደስ ብሏቸው ተቀበሉት በመርከብም ተሳፍረው ተርኑጥ ወደሚባል አገር ደረሱ ከእርሳቸውም ጋራ የሚሸኙአቸው ከየአገሩ የመጡ ብዙ ሕዝቦች ነበሩ። በዚያችም ሌሊት በዚያ አደሩ ጸሎትንም አደረጉ ቀድሰውም ለሕዝቡ ሥጋውንና ደሙን አቀበሉ።

ከዚህም በኋላ ተሸክመው ወደ ገዳም ተጓዙ ሲጓዙም ከበረሀው እኵሌታ ደርሰው ከድካማቸው ጥቂት ሊአርፉ ወደዱ። አባ ሚካኤልም የከበረ የአባታችን የአባ መቃርስን ሥጋ የምናሳርፍበትን #እግዚአብሔር እስከ ገለጠልን ድረስ እንደማናርፍ ሕያው #እግዚአብሔርን ብሎ ማለ።

ከዚህም በኋላ የከበረ የአባ መቃርስን ሥጋ የተሸከመ ገመል ወደ አንድ ቦታ ደርሶ በዚያ በረክ አለ። የከበረ የአባ መቃርስ ሥጋ ያለበትንም ሣጥን ይጥል ዘንድ በራሱ ወዲያና ወዲህ ይዞር ጀመረ። አረጋውያን መነኰሳትም #እግዚአብሔር የፈቀደው ያ ቦታ እንደሆነ አወቁ እጅግም አደነቁ #እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ያም ቦታ እስከ ዛሬ የታወቀ ነው።

ወደ ገዳሙም በቀረቡ ጊዜ መነኰሳቱ ሁሉም ወጡ ወንጌልና መስቀሎችን ይዘው መብራቶችን እያበሩ እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን እስከ አስገቡት ድረስ በታላቅ ክብር በራሳቸው ተሸክመው ወሰዱት።

#እግዚአብሔርም በዚያች ሌሊት ተአምራትን አደረገ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ አባቶቻችን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አበ_ብዙሃን_ቅዱስ_አብርሃም

በዚህችም ቀን የሃይማኖት የደግነት የምጽዋት የፍቅር አባት የሆነው ደጉ አብርሃም ጣዖት የሰበረበት እለት ይታሠባል።

በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የአብርሃም አባቱ ታራ ጣዖትን ይጠርብና ይሸጥ ነበር። ሽጦ ገንዘብ የሚያመጣለት ደግሞ ልጁ አብርሃም ነበር። በዚያ ወራት አብርሃም እውነተኛውን አምላክ ፍለጋ ገብቶ ነበር። አንድ ቀን ጣዖቱን ሊሸጥ ወደ ገበያ እየሔደ የተሸከመውን እንጨት ይመራመረው ገባ። "አሁን ይሔ ምኑ ነው አምላክ!" እያለም ያደንቅ ገባ። መንገድ ላይም ደክሞት ካረፈበት "ለምን አልጠይቀውም" በሚል አናገረው።

"እርቦኛል አብላኝ" አለው:: መልስ የለም:: "እሺ አጠጣኝ" አለው:: አሁንም ያው ነው:: "ባይሆን እሺ አጫውተኝ" አለው:: ጣዖቱ ተራ እንጨት ነውና መልሱ ዝምታ ነበር:: ከዚያ ተነስቶ ወደ ገበያው ሲደርስ "ዐይን እያለው የማያይ: ጀሮ እያለው የማይሰማ አምላክ የሚገዛ" እያለ ይጮህ ጀመር::

ይህን ሲሰሙ አንዳንዶቹ "የታራ ልጅ አብዶ" ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ "እሱ ያቀለለውን ማን ይገዛዋል" ብለውት ሔደዋል:: ከገበያ ሲመለስም ጣዖቱን ተመልክቶ አብርሃም እንዲህ አለ:: "አንተ ቀድሞውን በዕለተ ሠሉስ የተፈጠርክ ዕፅ ነህ" ብሎ ሰባበረው።

ወደ ቤቱ ሲመለስም ሁሉንም ጣዖታት ሠባበራቸው:: ይህ የተደረገው ከ2,000 ዓመታት በፊት በዚህች ቀን ነው። የመንግስተ ሰማያት አበጋዝ የ #እግዚአብሔር ወዳጅ አባታችን አብርሃም በመጨረሻው በውሃ፣ በነፋስ፣ በእሳትና በፀሐይ ተመራምሮ ፈጣሪውን አግኝቷል።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አብርሃም ጸሎት ይማረን በረከቱም ይድረሰን ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ፊንሐስ_ካህን

በዚህች ቀን የአልዓዛር ልጅ የፊንሐስ መታሰቢያው ነው። ካህኑ ፊንሐስ የብሉይ ኪዳን ዘመን አገልጋይ: ከነገደ ሌዊ: የሊቀ ካህናቱ የአሮን የልጅ ልጅ ነው:: አባቱም ሊቀ ካህናቱ አልዓዛር ነው:: ፊንሐስ እሥራኤል ከግብጽ ሲወጡ ሕጻን የነበረ ሲሆን አድጐ በመጀመሪያ ካህን፤ አባቱ አልዓዛርና አያቱ አሮን ሲያርፉ ደግሞ ሊቀ ካህንነትን ተሹሟል::

አንድ ቀን በጠንቅዋዩ በበለዓም ክፉ ምክር እሥራኤላውያን ከሞዐብ ሴቶች ጋር በኃጢአት በመሳተፋቸው #እግዚአብሔር ተቆጥቶ ነበር:: ያጠፋቸው ዘንድም መቅሰፍት ተጀምሮ ሳለ ፊንሐስ ወንድና ሴት: በደብተራ ኦሪቱ አንጻር የማይገባውን ሲሠሩ አያቸው::

ለፈጣሪው ቀንቶ በአንድ ጦር ሁለቱንም በአንድ ላይ ጥሏቸዋል:: ያን ጊዜ ጌታ "አስተንፈስካ ለነፍስየ" ብሎታል:: መቅሰፍቱም ተከልክሏል:: በዚህም ምክንያት ካህኑ ፊንሐስ የ300 ዓመት ዕድሜ ተጨምሮለት: #እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: (ዘኁ. 25፥7, መዝ. 105፥30)

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ አባቶቻችን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_19 እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ነሐሴ_22

#ነቢዩ_ሚክያስ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ታላቅ ነቢይ የሞራት ልጅ ሚክያስ አረፈ። ይህም ነቢይ በይሁዳ ነገሥታት በኢዮአታም፣ በአካዝና በሕዝቅያስ ዘመን ትንቢት በመናገር አስተማረ።

ስለ #ጌታችን መውረድም እንዲህ አለ። እነሆ #እግዚአብሔር ከልዑል መንበሩ ወደዚህ ዓለም ይወርዳል ።

ሁለተኛም ስለ ልደቱ እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ የኤፍራታ ዕጣ የምትሆኚ አንቺም ቤተ ልሔም የእስራኤል ነገሥታት ከነገሡባቸው አገሮች አታንሺም ወገኖቼ እስራኤልን የሚጠብቃቸው ንጉሥ ከአንቺ ይወጣልና ።

ስለ ምኵራብ መቅረት፣ ስለ ቤተክርስቲያን በዓለም ሁሉ መታነፅ ትንቢት ተናግሯል። ዳግመኛም ስለ ሕገ ወንጌል መሠራት ሕግ ከጽዮን የ #እግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣል አለ። የትንቢቱም ወራት ሲፈጸም ወደ በጎ ሽምግልና ደርሶ ወደ ወደደው #እግዚአብሔር ሔደ።

የትንቢቱም ዘመን ከ #ጌታችን መምጣት በፊት በስምንት መቶ ዓመት ነው። ማርታ በምትባልም ቦታ ተቀበረ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_ነሐሴ)
ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርቶስ ወደርሱ መጣ ከእርሱም ጋራ እመቤታችን #ቅድስት_ድንግል_ማርያም ደግሞ የከበሩ ነቢያትና ሐዋርያት ሁሉም ሰማዕታትና ጻድቃን የጳጳሳት አለቆች የመላእክት አለቆችም ከሠራዊቶቻቸው ጋራ አሉ።

#መድኃኒታችንም እንዲህ አለው ወዳጄ ሆይ አንተ በመከራዬ መሰልከኝ እኔም በመንግሥቴ ከእኔ ጋራ እንድትመስለኝ አደርግሃለሁ። እነሆ የዚህ ዓለም ድካምህ ተፈጸመልህ በእኔ ዘንድም የምቀበለው ሆነ ከእንግዲህስ መንግሥተ ሰማያትን ትወርስ ዘንድ ና። እነሆ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ ገድልህን ለሚጽፍ ለሚያነበውና ለሚሰማውም ቤተ ክርስቲያንህን ለሚሠራ በስምህ መባ ለሚሠጥ ለድኆችም በስምህ ለሚመጸውት በመታሰቢያህም ቀን ለሚቆርብ ስለ አንተ በጎ ሥራ ለሚሠራ ሁሉ እኔ እስከ ዐሥር ትውልድ እምርልሃለሁ።

አባታችንም እጅግ ደስ አለው ለ #ጌታችንም ሰገደ #ጌታችንም ከእርሱ ዘንድ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ከዚህም በኋላ አባታችን በንዳድ በሽታ ታመመ ዕድሜውም ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከስምንት ወር ከአንድ ቀን ሆኖት በለመለመ ዕርጅና አረፈ። በመዘመርና በማመስገን አክብረው ገንዘው በዋሻው ውስጥ ቀበሩት።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን በአቡነ ተክለ ሐይማኖት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።


✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ

በዚህች ቀን ደግሞ ኢትዮጵያዊት የሆነች ተጋዳይ የከበረች ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው፡፡ በሸዋ ከፍለ አገር በቡልጋ አውራጃ ልዩ ስሟ ቅዱስ ጌዬ የተባለች አገር ነበረች ይህችም የእናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የትውልድ አገሯ ናት። በዚህም አገር በወርቅና በብር በሐር እና በልዩ ልዩ ልብስ በወንድና በሴት አገልጋዮች በፈረስና በበቅሎ የከበረ አንድ ስሙ የታወቀ ሰው ነበር። የዚህ ሰው ስሙ ቅዱስ ደረሳኒ ሲሆን የሚስቱም ስም ቅድስት ዕሌኒ ይባላል ሁለቱም ባልና ሚስቱ እግዚአብሔር የሚፈሩ ደጋግ ሰዎች ስለነበሩ በጎ ሥራቸው በዓለም ሁሉ የታወቀ ነበር። እሊህም ሰዎች በእግዚአብሔር ዘንድ የተመረጠችና የከበረችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራን ወልደው በደም ግባቷና በጠባይዋ እየተደሰቱ አሳደጓት ከዚያም የእግዚአብሔርን ሕግጋትና ሥርዓቶችንም ሁሉ አስተማሯት። ባደገችና ለአቅመ ሔዋን በደረሰች ጊዜ የንጉሥ ባለሟል የሆነ ትውልዱ፤ ነገዱ ከአባ ፃሠርጓ ወገን የሆነ ለኢየሱስ ሞዓ ልጅ ለሠምረ ጊዮርጊስ በሕግ አጋቧት። እሱም በዚህ ዓለም ገንዘብ በጣም የከበረ ከመሆኑም በላይ በይበልጥ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ነበረ። ከደም ግባቷ የተነሣ ሙሽራይቱ ማለት እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራን እጅግ አድርጎ ወደዳት። አሟቷ ኢየሱስ ሞዐም ይህች ብላቴና "በታላቅ ቁም ነገር የተመረጠች ነች" በማለት ትንቢት ይናገርላታል ስለዚህ እንደ እመቤቱ አድርጐ ያከብራት ነበር። ከዚህም በኋላም ለሕጋዊ ባሏ ለሠምረ ጊዮርጊስ ዓሥራ አንድ ልጆች ወለደችለት ከነዚህም መካከል ዘጠኙ ወንዶች ሁለቱ ሴቶች ነበሩ። ልጆችዋንም ሕገ እግዚአብሔርን እያስተማረች በክብር በሥርዓት አሳደገቻቸው።

በዚያን ዘመን የእግዚአብሔር ባለሟል የሚሆን ዓፄ ገብረ መስቀል የሚባል የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ነበር። እርሱም ዝናዋን ሰምቶ ሥነ ምግባሯን ተመልክቶ ይልቁንም በሷ ላይ ያደረውን ኃይለ መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር ስለገለጸለት እጅግ አድርጐ ይወዳትና ያከብራት ነበር። ከዕለታት ባንድ ቀን በጸሎትሽ አስቢኝ በማለት በራሱ በንጉሡ ቤተ መንግሥት ከሚያገለግሉ አገልጋዮች ወይም ሠራተኞች መካከል እንዲያገለግሏት 174 አገልጋዮች ላካላት። ዳግመኛም ፈረስና በቅሎ ከነሥራታቸው እንደዚሁም ለነሥታት ሚስቶች የሚገባ ከሐርና ከወርቅ የተሠራ ልብስና የወርቅ ጫማ ላከላት። ነገር ግን እሷ ይህን ሁሉ ክብር አልፈለገችም ይልቁንም ለዓላማየ ዕንቅፋት ወይም ከንቱ ውዳሴ ይሆንብኛል በዚያውስ ወርቁ ጌጡ ልብሱ ተሸጦ ለነዳያን ይመጸወታል ለቤተ ክርስቲያን መባዕ ይሰጣል እኒህን አገልጋዮች ግን ምን አደርጋቸዋለሁ በማለት ወደ እግዚአብሔር እያመለከተች ቆየች።

ከአገልጋዮችዋ መካከል ምግባሯ የከፋ የምታናድዳትና የምታበሳጫት አገልጋይ ነበረች። #እግዚአብሔርም አገልጋይዋን ቀሰፋት ብፅዕት ክርስቶስ ሠምራም ደንግጣ ካለችበት ቤት ውስጥ ወደ ሌላው ክፍል ገባችና ወደ ሰማይ አቅንታ "ወይኔ ወዮልኝ ወዮታ አለብኝ የካህን ሚስት ስሆን ነፍስ ገዳይ ሆኛለሁና። ሰውስ ምን ይለኛል ለነፍሴስ ምን እመልስላታለሁ ከእግዲህ ከክርስቲያን ወገን ልቆጠር አይገባኝም በደሌንስ እንደምን አድርጌ ልሸሸሽጋት እችላለሁ" እያለች አለቀሰች።

ከዚህ በኋላ እንዲህ ስትል ለ #እግዚአብሔር ብፅዓት አደረገች "አቤቱ ይህችን በእኔ እጅ የሞተችውን አገልጋይ ነፍስዋን ከሥጋዋ አዋህደህ ብታሥነሣልኝ ልጆቼን ቤቴን ንብረቴን ትቼ ባለ ዘመኔ ሁሉ አንተን እከተላለሁ። አንተን ከመከተል ከቶ ወደኋላ አልልም። ለሰውነቴ ጌጥ ወይም ግርማ ሞገስ የሚሆናት ወይም የሚሞቃት ልብስ ከቶ አልለብስም ሥጋዬን የሚያረካ ምግብም አልመገብም። አቤቱ ጌታዬ ሆይ ጸሎቴን ስማኝ ልመናዬም በፊትህ ፈጥኖ ይድረስ አቤቱ ፊትህን ከኔ ከባሪያህ አትመልስ"። እንዲህ እንዲህ እያለች በልቅሶና በኀዘን ለብዙ ሰዓት ከጸለየች በኋላ ድካም ተሰማትና ዕረፍት አደረገች። ከዚህ በኋላ ቤተሰቦችዋ እስዋ ወዳለችበት ክፍል መጥተው "እመቤታችን ሆይ ሙታ የነበረችው አገልጋይሽ በ #እግዚአብሔር ኃይልና በአንቺ ጸሎት ተነሥታለችና ደስ ይበልሽ" አሏት። በዚህ ጊዜ ፈጥና ተነሥታ ደስ እያላት ሙታ የነበረችው አገልጋይ ካለችበት ቦታ ደረሰችና ሕይወት አገኘቻት ከዚያም ቃሏን ከፍ አድርጋ "ልመናዬን ቸል ያላለ ቸርነቱንም ከኔ ከባሪያው ያላራቀ ፈጣሪ ይክበር ይመስገን" ብላ በታላቅ ምስጋና #እግዚአብሔር አመሰገነች።

ከዚህ በኋላ አስቀድሞ ከአፏ የወጣውን ከአንደበቷ የተነገረውን ቃል አስባ ልብሰ ምንኵስናዋን ማለት ቆቧን ቀሚሷን አጽፏን መታጠቂያዋን አዘጋጀች። ቤተሰቦቿና አገልጋዮቿም "እመቤታችን ሆይ ይህ የምታዘጋጂው የምናኔ ልብስ ለምንሽ ነው ወይስ ለማን ነው የምታዘጋጂው" አሏት። እርሷም " ሃይማኖት ያስተማሩኝ አባቴ ልብስ አልቆባቸዋል ሲሉ ሰምቼ ለሳቸው ነው የማዘጋጀው" አለቻቸው።

ከዚህም በኋላ ከዕለታት ባንደኛው ቀን እናታችን ክርስቶስ ሠምራ አገልጋዮቿን ወደ ቤተ ክርስቲያን እንሄድ ዘንድ ተዘጋጁ አለቻቸውና እነሱም አሺ በጎ ብለው አጅበዋት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሄዱ። ከዚያም እንደደረሱ "በሉ እንዲህ እኔ ከዚህ ጥቂት እቆያለሁና እናንተ ወደ ቤታችሁ ተመለሱ ለኔ ይህች አንድዲት አገልጋይና ይህ ሕፃን ልጅ ብቻ ይበቁኛል አለቻቸው። በዚያኑ ጊዜ አገልጋዮቿ እጅ እየነሱ ወይም እየተሰናበቱ ወደቤታቸው ተመለሱ። ከዚያም ከዳዊት መዝሙር "ልቤ ጽኑ ነው አቤቱ ልቤ ጽኑ ነው #እግዚአብሔርን ፈጽሜ አመሰግነዋለሁ #እግዚአብሔር የደህንነቴ መብራት ስለሆነ ምን ያስደነግጠኛል #እግዚአብሔር የሕይወቴ መተማመኛ ነው ምንስ ያስፈራኛል የሚለውን እየጸለየች የሚያልፈን ዓለም በማያልፈው ዓለም ለመተካት ወይም ለመለወጥ አውጭኝ እግሬ ብላ ገሠገሠች። ያ በልስላሴና በእንክብካቤ የኖረ እግር ከመንገዱ ብዛት እንደዚሁም ከቅርቅፍቱና ከእንቅፋቱ የተነሣ ፈለግ ሲያወጣ ሥጋውን እየቆረጠች ስትጥለው ደሙ እንደጒርፍ ውሃ ይወርድ ነበር። ያች የተከተለቻት አገልጋይ ግን ከእመቤቷ እግር እየተቆረጠ የሚወድቀውን የአካል ቊራጭ እያነሳች በልብሷ
"በምን ሥራዬ ለኔ ተሰጡኝ" አለችው። "ዐሠርቱ ቃላት ኦሪትን ስድስቱን ቃላተ ወንጌል ጠብቀሽ ቤትሽን ጥለሽ ይህን ዓለም ንቀሽ አጥቅተሽ የ #ክርስቶስን ቀምበር ተሸክመሽ ፈጣሪሽን ስለተከተልሽው ነው" አላት። ይህንንም በአላት ጊዜ እጅግ አድርጋ ተደሰተች ሁሉን ማድረግ የሚችል #እግዚአብሔርንም ፈጽማ አመሰገነች።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም እኛንም በቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቶማስ_ዘመርዓስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የ #ክርስቶስ ምስክሩና ሐዋርያው የሆነ የመርዓስ ኤጲስቆጶስ ተጋዳይ ቅዱስ አባት ቶማስ አረፈ። የዚህንም አባት ትሩፋቱንና ገድሉን ሰው ተናግሮ ሊፈጽመው አይችልም እርሱ አስቀድሞ በጾም በጸሎት በስጊድ ቀንና ሌሊትም በመራራት ተጠምዶ የሚኖር ነው ። ከዚህም በኃላ መርዓስ ለሚባል አገር ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ የክብር ባለቤት #ጌታችን መረጠው መንጋውንም እንደ ሐዋርያት ጠበቀ ። ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስም በነገሠ ጊዜ ክርስቲያኖችን ያሠቃያቸው ዘንድ ከመኳንቶቹ አንዱ ወደዚያች አገር ደረሰ እርሱም ቅዱስ ቶማስን ወደርሱ ያቀርቡት ዘንድ ጭፍሪቹን ላከ እነርሱም እየደበደቡ በምድር ላይ እየጎተቱ ወሰዱት ደሙም እንደውኃ ፈሰሰ ።

ከዚህም በኃላ መኮንኑ ቅዱስ ቶማስን ለአማልክት ስገድ አለው ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ ከሕያው #እግዚአብሔር ልጅ ከ #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ በቀር ለረከሱ ጣዖታት የሚሰግድ ሁሉ የተረገመ ነውና ።

መኰንኑም ተቆጥቶ እጅግ የበዛና ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው የነዳጅ ድፍድፍና አፍልተው በላዩ በአፉና በአፍንጫው ውስጥ ጨመሩ እንዲህም እያደረጉበት እስከ ብዙ ዘመናት ኖረ።

የእሊህ ከሀዲያን ልባቸው እንደ ድንጊያ የጸና ስለሆነ ቅዱስ ቶማስ ቶሎ እንዲሞት አልፈለጉም። ሌሎች ብዙዎች ሰዎችን ያሰፈሩአቸው ዘንድ የክብር ባለቤት #ክርስቶስንም ይክዱት ዘንድ የሥቃዩን ዘመን አስረዘሙ እንጂ።

እርሱ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ኃይል የጸና ነውና ማሠቃየቱን ከሀድያን በተቸነፉ ጊዜ ስለ ስሕተታቸውም ይዘልፋቸው ስለነበር ስለዚህ በጨለማ ቦታ ጣሉት በዚያም ሃያ ሁለት ዓመት ኖረ።

ከሀድያንም በየዓመቱ ወደርሱ ገብተው ከሕዋሳቱ አንዱን ይቆርጣሉ። በዚያም ቦታ አፍንጫውን ከንፈሮቹን ጆሮዎቹን እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ መንጋዎቹም ያረፈ መስሏቸው በየዓመቱ መታሰቢያውን ሲያደርጉ ኖሩ። ነገር ግን አንዲት ክርስቲያናዊት ሴት በጣሉት ጊዜ ስለአየችው ቦታውን ታውቅ ነበር እርሷ በሌሊት ወደርሱ ተሠውራ በመሔድ ትመግበዋለች ። ጻድቅ ቁስጠንጢኖስም እስከ ነገሠና የቀናች የ #ክርስቶስን ሃይማኖት ክብር እስከ ገለጠ ድረስ እንዲህ ሲሠቃይ ኖረ።

ይህም ንጉሥ #ክርስቶስን በመታመን የታሠሩ እሥረኞችን ሁሉ በሀገሮች ሁሉ በወህኒ ቤት ያሉትን ይፈቷቸው ዘንድ አዘዘ።

ይችም ሴት ሒዳ ስለ ቅዱስ ቶማስ ከእርሱ የሆነውን ሃያ ሁለት ዓመት ተጥሎ እንደኖረ ለካህናቱ ነገረቻቸው በውስጡ ወደሚኖርበትም ቦታ መራቻቸው። እነርሱም አንሥተው ተሸከሙት እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አደረሱት በቤተ መቅደሱም ፊት ለፊት በወንበሩ ላይ አስቀመጡት ምእመናንም ሁሉ ወደርሱ እየመጡ ከእርሱ ይባረኩና የተቆረጡ ሕዋሳቱን ይሳለሙ ነበር።

ንጉሥ ቂስጠንጢኖስም የከበሩ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳትን የአንድነት ጉባኤን በኒቅያ አገር በሰበሰበ ጊዜ ይህ የከበረ ቶማስ ከእሳቸው አንዱ ነው።

ንጉሡም ወደ እንርሱ ገብቶ ሰላምታ ሰጣቸውና ከእርሳቸውም ቡራኬ ተቀበለ። የዚህ የቅዱስ ቶማስን ተጋድሎውን በነገሩት ጊዜ ወደርሱ ቀርቦ ሰገደለት ሕዋሰቱም ከተቆረጡበት ላይ ተሳለመው አዝኖና እጅግም አድንቆ ሕዋሳቱን ዳሠሠው ፊቱንና ዐይኖቹን አሻሸው።

ከሀዲ አርዮስንም ተከራክረው ከረቱ በኃላ አውግዘው ለይተው ከወገኖቹ ጋር ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። ከዚህም በኃላ #መንፈስ_ቅዱስ እንደ አስተማራቸውና እንደመራቸው የሃይማኖትን ትምህርት በአንደበታቸው ተናገሩ ሕግና ሥርዓትን ሥጋዊና መንፈሳዊ ፍርድንም ሠሩ።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ቶማስ ወደ መንበረ ሢመቱ ሔደ ካህናቱንና መንጋዎቹን ሁሉ ሰብስቦ አነበበላቸው እርሱንም እንዲአስተውሉት እንዲጠብቁትም በመጠበቅም እንዲጸኑ አዘዛቸው። ጥቂት ዘመናትም ከኖረ በኃላ በሰላም በፍቅር አረፈ የሹመቱም ዘመን አርባ ዓመት ነው በዚህም #እግዚአብሔርን አገለገለው።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቶማስ ጸሎት ይማረን። በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_ነሐሴ_24 እና #ገድለ_ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ)
#ነሐሴ_25

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሃያ አምስት በዚች ቀን #ቅዱስ_እንድርያኖስ በሰማዕትነት ሞተ ከእርሱም ጋር የነበሩ ሃያ አራቱ ባልንጀሮቹ በሰማዕትነት ሞቱ፣ ቅዱሱ አባት #አባ_ቢጻርዮን አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እንድርያኖስ

ነሐሴ ሃያ አምስት በዚህች ቀን ቅዱስ እንድርያኖስ በሰማዕትነት ሞተ ከእርሱም ጋር የነበሩ ሃያ አራቱ ባልንጀሮቹ በሰማዕትነት ሞቱ። ይህም እንድርያኖስ ከመክስምያኖስ መኳንንቶች አንዱ ነበር እርሱም የጐልማሶች አለቃ ነበረ። ለጣዖት መስገድን እምቤ ስለአሉ ንጉሡ ምእምናንን ሲአሠቃያቸው ቅዱስ እንድርያኖስ የሰማዕታትን የልባቸውን ቆራጥነትና በመከራቸው ላይ መታገሣቸውን ተመልክቶ አደነቀ።

እንዲህም አላቸው ይህን ያህል ስትታገሡ ምን ታገኛላችሁ ቅዱሳን ሰማዕታትም የሚጠብቀንን ተሰፋ ለመናገር አንደበታችን አይችልም አሉት ስለ ዓለም ድኅነትም #ክርስቶስ መከራ እንደ ተቀበለ ከብሉይና ከሐዲስ መጽሐፍ ነገሩት።

እንድርያኖስም በሰማ ጊዜ ጽሕፈትን ወደ ሚያውቁ ብልሆች ሰዎች ሔደና እኔ ከዛሬ ጀምሮ ክርስቲያን ነኝ ስሜን ከገድለኞቹ ጋራ ጻፉ አላቸው።

ለንጉሥ መክስምያኖስም እንዲህ እንዳለ በነገሩት ጊዜ ጠርቶ እንድርያኖስ ሆይ አበድክን አለው እንድርያኖስም ከቀድሞው እብደቴ ተመለስኩ እንጂ እኔ አላበድኩም ብሎ መለሰለት።

ንጉሡም ሰምቶ ወደ ወህኒ ቤት ከንጹሐን ሰማዕታት ጋራ እንዲጨምሩት አዘዘ። ከአገልጋዮቹም አንዱ ሒዶ ለሚስቱ እንጣልያ ነገራት በሰማችም ጊዜ ደስ እያላት ወደ ወህኒ ቤት ሔደች ሃያ አራቱ ቅዱሳን ሰማዕታት የታሠሩበትን ማሠሪያቸውን ሳመች በሥቃዩ እንዲታገሥ የባሏን ልብ ያጽናኑ ዘንድ ለመነቻቸው። እርሱንም እንዲህ አለችው ላህይህ ደምግባትህም ርስትህም ጥሪትህም አያስትህ ሁሉም ከንቱ ነውና ነገር ግን በእርሱ ዘንድ የማያልፍ መንግሥትን ትወርስ ዘንድ የክብር ንጉሥ #ክርስቶስን ተከተለው ይህንንም ብላ ወደቤቷ ገባች።

ከዚህም በኃላ እንድርያኖስ ለፍርድ እንደ ሚአቀርቡት በአወቀ ጊዜ ሊሰናበታት ወደ ሚስቱ ሔደ መምጣቱንም ሰምታ የሸሸ መሰላት ደጇንም ዘግታ በውስጥ ሁና እንዲህ እያለች ዘለፈችው ትላንት ሰማዕት ተብለኽ ዛሬ #ክርስቶስን ካድከውን እንድርያኖስም ሰምቶ የሃይማኖቷን ጽናት አደነቀ እንዲህም አላት እኅቴ ሆይ እንድስናበትሽ ክፈችልኝ አላት።

በሰማችም ጊዜ ከፈተችለት ከዚህም በኃላ ሁሉን እያነጋገራት እስከ እሥር ቤት ወሰዳት እንጣልያም ከዚያ በደረሰች ጊዜ የታሠሩትን ቅዱሳን ተሳለመቻቸው ቁስላቸውንም አጠበች።

ከዚህም በኃላ ንጉሡ ቅዱሳኑን ከእሥር ቤት እንዲአመጧቸው አዘዘ በመጡም ጊዜ ከሥቃይ ብዛት የተነሣ እንደደከሙ አያቸው። እንድርያኖስንም በፊቱ አቁሞ ለአማልክት ሠዋ አለው ቅዱሱም እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ ንጉሡም የሆድ ዕቃው እስኪፈስስ ሆዱን እንዲደበድቡት አዘዘ በዚያን ጊዜም የእንድርያኖስ ዕድሜው ሃያ ስምንት ዓመት ነበር።

ከዚህም በኃላ እንድርያኖስን ከባልንጀሮቹ ሰማዕታት ጋራ ወደ እሥር ቤት መለሱት እንጣልያም መጥታ የቅዱሳንን ደማቸውን ጠራረገችላቸው። እሊህ ቅዱሳንም እንድርያኖስን እንዲህ ብለው ተሳለሙት እንድርያኖስ ሆይ ስምህ ተሳለሙት በሕይወት መጽሐፍ ተጽፎአልና ደስ ይበልህ ።

ንጉሡም መሰፍ አምጥተው የቅዱሳኑን ሁሉ ጭናቸውን በድጅኖ ይሰብሩ ዘንድ አዘዘ እንጣልያም የእንድርያኖስን እጆቹንና እግሮቹን በመስፍ ላይ ለማኖር ቀደመች ነፍሱንም በ #እግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠ ድረስ የእንድርያኖስን ዐጥንቶቹን ወታደሮች ቀጠቀጡ የቅዱሳኑንም ሁሉ ጭናቸውን ሰብረው ወደ እሳት ወረወሯቸው እሳቱ ግን ከቶ አልነካቸውም ።

ምእመናንም መጥተው በጭልታ ወደ ሌላ ቦታ ወሰዱአቸው የመከራውም ወራት እስቲያልፍ ሠወሩአቸው። እንጣልያም የእንድርያኖስን የእጁን ቁራጭ ወስዳ በትርአሷ ውስጥ አኖረችው።

ከዚህም በኃላ የሀገሩ ገዥ እንጣልያን ሊአገባት ወደደ በአወቀችም ጊዜ የባሏን የእጅ ቁራጭ ይዛ በመርከብ ሸሸች የቅዱሳኑ ሥጋ ወዳለበትም ደርሶ ወደ እነርሱ ይቀበሏት ዘንድ ለመነች #ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ አሳረፋት ከእነርሱም ጋራ ተቀበረች።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ቢጻርዮን

በዚህችም ቀን ቅዱሱ አባት አባ ቢጻርዮን አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ #እግዚአብሔርን የሚፈሩ ምእመናን ነበሩ። በአደገም ጊዜ የምንኵስና ልብስን ለብሶ #እግዚአብሔርን ሊአገለግል ወደደ ዓለምንም ንቆ ወደ አባ እንጦንስ ሔደ ለእርሱም ደቀ መዝሙር ሆኖ ብዙ ዘመናት አገለገለው።

ከዚህም በኃላ ወደ አባ መቃርስ ሒዶ ቅዱሳን አረጋውያን መነኰሳትንም አገለገላቸው። በአስቄጥስም ገዳም ይዘዋወር ነበር በቤት ውስጥም አያድርም ነበር። ምንጣፍና ልብስ እስኪአጣ ድረስ ምንም ምን ጥሪት አልነበረውም መነኰሳቱም የማቅ ጨርቅ ይሰጡት ነበር። ወገቡንም ታጥቆ በመነኰሳቱ መንደር ይዞር ነበር በቤቶቻቸውም ደጃፍ እያለቀሰ ይቀመጥ ነበር።

የማያውቀውም ወደርሱ በደረሰ ጊዜ አባቴ ሆይ ምን ያስለቅስሃል ይለው ነበር። እርሱም ንብረቴን ስለዘረፉኝ እንዳልሞት ሸሸሁ ከወገኔም ክብር ተለይቼ በጉስቁልና ወደቅሁ ይለው ነበር። የቃሉንም ምልክት የማያውቅ የጠፋውን ገንዘብህን #እግዚአብሔር ይመልስልህ ብሎ ካለው ይሰጠው ነበር። እርሱም ተቀብሎ ይሔድና ለሌለው ይሰጥ ነበር።

የቃሉን ምልክት የሚያውቅ ግን በፈቃደ ነፍስ የሚሠሩ ትሩፋትን ሰይጣን ከሰዎች የማረካቸው መሆኑን ልብ ብሎ ያስተውል ነበር። አባቶችም ጭንቅ የነበረ ተጋድሎውን ስለርሱ ይናገሩ ነበር። እርሱ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ከቶ ሳይተኛ ቁሞ ኖሮአልና ።

በምንኩስናውም ወራት ብዙ ጊዜ በየአርባ ቀን ጾመ እነሆ እንዲህ እየተጋደለ ድንቆችንም እያደረገ ኀምሳ ሰባት ዓመታት ኖረ። ቅዱሳን አባ ዱላስና አባ ዮሐንስም ከተአምራቱ ተናገሩ እነርሱ ከርሱ ጋር ወደ ኤርትራ ባሕር ዳርቻ ሔዱ። እጅግም በተጠሙ ጊዜ እንደተጠሙ አውቆ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ መራራውንም ውኃ ጣፋጭ አድርጎላቸው ጠጥተዋል።

በሁለተኛም ጊዜ ወደ ፈሳሽ ውኃ ደርሶ መሸጋገሪያ አጣ ወደ #ጌታችንም ጸለየ ያን ጊዜም እንደ የብስ በባሕሩ ላይ ሔደ። በአንዲት ቀንም የከበሩ አባቶች በጸሎታቸው ያድኑት ዘንድ ጋኔን ያደረበትን ሰው ወደ አስቄጥስ ገዳም ሰዎች አመጡ አባቶችም እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ እርሱ ከከንቱ ውዳሴ ስለሚሸሽ ብንነግረው ይህን ጋኔን የያዘውን አያድነውም ።

አባ ቢጻርዮን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጸሎት ወደሚቆምበት ቦታ ያንን ጋኔን ያደረበትን ሰው አስተኙት። አባ ቢጻርዮንም በገባ ጊዜ ያን ጋኔን ያደረበትን ሰው ተኝቶ አገኘውና ቀሰቀሰው እጁንም ይዞ ተነሥ አለው ያን ጊዜም ድኖ ተነሣ አእምሮውም ተመለሰ። ያዩትም እጅግ አደነቁ ለሚፈሩት ስለሚሰጠው ጸጋውም #እግዚአብሔርን አመሰገኑት።

የዚህም ቅዱስ ተአምራቶቹ ከነገርናችሁ የበዙ ናቸው #እግዚአብሔርንም አገልገሎ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን። በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_ነሐሴ_25)
#ነሐሴ_27

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሃያ ሰባት በዚህችም ቀን #የመላእክት_አለቃ_ሱርያል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ #የቅዱስ_ብንያሚንና_እኅቱ_አውዶክስያ በሰማዕትነት ሞቱ፣ በሊቀ ካህናት ኤሊ ዘመን #ነቢይ_ሳሙኤል ለመጠራቱ መታሰቢያ ሆነ፣ታላቁ ሰማዕት #ቅዱስ_ፊቅጦርና_እናቱ_ቅድስት_ሣራ መታሰቢያቸው ነው፣ አባቶቻችን #12ቱ_የያዕቆብን_ልጆች ያስቧቸዋል፣ ታላቁ ጻድቅ ተአምረኛው #አቡነ_ዘርዐ_ቡሩክ ልደታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሱርያል_ሊቀ_መላእክት

ነሐሴ ሃያ ሰባት በዚህችም ቀን ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አራተኛ የሆነ የመላእክት አለቃ የሱርያል የበዓሉ መታሰቢያ ነው።

ከታላላቅ ሊቃናት አንዱ የሆነው ቅዱስ ሱርያል ክብሩ ብዙ ቢሆንም ብዙ ምዕመናን አያውቁትም። የመላእክት መዓርግ ሲነገር ሚካኤል፣ ገብርኤል፣ ሩፋኤል ብሎ ቀጥሎ የሚመጣው ሱርያል ነው።

በ3ቱ ሰማያት ካሉት 9ኙ ዓለመ መላእክት የአንዱ (የሥልጣናት) መሪ (አለቃ) ነው። መልአኩ እጅግ ርሕሩሕ እና ተራዳኢ ነውና አንዘንጋው። ለኖኅ መርከብርን ያሳራው ከጥፋት ውሃም ያዳነው ይህ ቅዱስ መልአክ ነው።

በገድለ ሰማዕታትም ላይ እንደተጠቀሰው የሰማዕታት ረዳትና አዳኝም ነው። ቅዱስ ሱርያል በሌላ ስሙ "እሥራልዩ" ይባላል። "የእሥራኤል ረዳት" እንደ ማለት::

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን አማላጅነቱም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ብንያሚንና_እህቱ_አውዶከስያ

በዚህች ቀን ሰብሲር ከሚባል አገር ብንያሚንና እኅቱ አውዶክስያ በሰማዕትነት ሞቱ።

የእነዚህም ቅዱሳን ወላጆቻቸው እንግዳና መጻተኛን የሚወዱ ደጎች ክርስቲያኖች ናቸው ደግሞ ለክርስቲያኖች በሚገባ በበጎ ሥራ ሁሉ የተጠመዱ ቅድስና ያላቸው ናቸው። እሊህንም ቅዱሳን በወለዱዋቸውና በአሳደጓቸው ጊዜ ክርስቲያናዊት ትምህርትን አስተማሩአቸው።

ከዚህም በኋላ ወደዚያች አገር ከሀዲ መኰንን መጣ ቅዱስ ብንያሚንም በሰማ ጊዜ የክብር ባለቤት ስለሆነ #ክርስቶስ ደሙን ያፈስ ዘንድ ወደደ። በመኰንኑም ፊት ቁሞ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ታመነ ጽኑ የሆነ ሥቃይንም አሠቃይቶ ከዚያ በኋላ አሠረው።

ወላጆቹና እኅቱ በሰሙ ጊዜ ወደርሱ መጡ አለቀሱ እጅግም አዘኑ እርሱም የዚህ ዓለም ኑሮ እንደ ጥላ ፈጥኖ ያልፋል የወዲያኛው ኑሮ ግን ፍጻሜ የለውም እያለ ያጽናናቸው ጀመረ።

እኅቱ አውዶክስያም ይህን መልካም ትምህርቱን ከወንድሟ ሰምታ ወንድሜ ሆይ ካንተ እንዳልለይ #እግዚአብሔር ሕያው ነው አንተ የምትሞተውንም ሞት እኔም ከአንተ ጋራ እሞታለሁ አለችው።

ይህንንም ብላ ወደ መኰንኑ ሒዳ በክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በመኰንኑ ፊት ታመነች መኰንኑም ያሠቃያት ጀመረ። ከዚህ በኋላም ያለ መብልና ያለ መጠጥ በጨለማ ቤት ሃያ ቀን ከወንድሟ ጋር አሥረው እንዲያኖሩዋት አዘዘ።

ከዚህም በኋላ ከዚያ አውጥቶ ከባድ የሆኑ ደንጊያዎችን በአንገታቸው አንጠልጥሎ ከጥልቅ ባሕር ጣላቸው የ #እግዚአብሔር መልአክም ወርዶ ከአንገታቸው ደንጊያዎቹን ፈታላቸው እነርሱም ከወደብ እስቲደርሱ በባሕሩ ላይ ዋኝተው ብጥራ ከምትባል ቦታ ደረሱ አንዲት ብላቴና ድንግልም አግኝታቸው ስባ አወጣቻቸው።

ያን ጊዜም ወደ መኰንኑ ሔደው እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገሙ ብዙ ቀኖችም ጭንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃያቸው። ሥቃያቸውም በአደከመው ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘና ቆረጡአቸው። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸው ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሳሙኤል_ነቢይ

በዚችም ቀን በሊቀ ካህናት ኤሊ ዘመን ነቢይ ሳሙኤል ለመጠራቱ መታሰቢያ ሆነ።

የዚህ ቅዱስ አባቱ ሕልቃና ይባላል የእናቱም ስሟ ሐና ነው። እነርሱም ከሌዊ ነገድ ከካህኑ አሮን ወገን ናቸው። ሐናም መካን ነበረች ክብር ይግባውና ወደ #እግዚአብሔር እያለቀሰች አዘውትራ ስለ ማለደች ይህን የተባረከ ልጅ ሰጣት በቤቷም ሦስት ዓመት አሳደገችው።

ከዚህም በኋላ ገና ስትፀንሰው እንደተሳለች ወደ #እግዚአብሔር መቅደስ አቀረበችው ካህኑ ኤሊንም በመላላክ የሚያገለግለው ሆነ። የካህኑ የኤሊ ልጆች ግን ክፉዎች ነበሩ #እግዚአብሔርንም አይፈሩም ነበር በቅዱስ መሥዋዕቱም ላይ በደሉ። ይህ ሕፃን ሳሙኤል ግን በኤሊ ፊት ለ #እግዚአብሔር ሲያገለግል ኖረ በነዚያ ወራቶችም ቃለ #እግዚአብሔር ውድ ነበር የሚታይ ራእይም አልነበረም።

ከዚህም በኋላ በአንዲት ሌሊት እንዲህ ሆነ ኤሊ በመኝታው ተኝቶ ሳለ ዐይኖቹም መፍዘዝ ጀምረው ነበር ማየትም አይችልም ነበር። የ #እግዚአብሔርንም መብራት አብርቶ ለማሳደር ገና አላዘጋጁም ነበር ሳሙኤል ግን በቤተ መቅደስ በ #እግዚአብሔር ማደሪያ ታቦት አጠገብ ተኝቶ ነበር።

#እግዚአብሔርም ሳሙኤልን ሳሙኤል ሳሙኤል ብሎ ጠራው እነሆ እኔ አለሁ አለ። ወደ ኤሊም ፈጥኖ ሔደ ስለጠራኸኝ እነሆ እኔ መጣሁ አለው ኤሊም አልጠራሁህም ተመልሰኽ ተኛ አለው ሔዶም ተኛ።

#እግዚአብሔርም ዳግመኛ ሳሙኤል ሳሙኤል ብሎ ጠራው ሳሙኤልም ተነሥቶ ወደ ኤሊ ሔደ ስለጠራኸኝ እነሆ መጣሁ አለው። ኤሊም አልጠራሁህም ተመልሰህ ተኛ አለው። ሳሙኤልም ከዚህ አስቀድሞ #እግዚአብሔርን በራእይ ገና አላወቀውም ነበር ቃለ #እግዚአብሔርም አልተገለጠለትም ነበር።

ዳግመኛም #እግዚአብሔር ሳሙኤልን ሦስተኛ ጊዜ ጠራው ተነሥቶም ወደ ኤሊ ሔደ ስለጠራኸኝ እንሆ መጣሁ አለው ኤሊም ያንን ልጅ #እግዚአብሔር እንደጠራው አሰበ። ልጄ ተመልሰህ ተኛ የሚጠራህ ካለ እኔ ባርያህ እሰማለሁና #ጌታዬ ተናገር በለው አለው ሳሙኤልም ሒዶ በመኝታው ተኛ።

#እግዚአብሔርም መጥቶ እንደ መጀመሪያው በፊቱ ቁሞ ጠራው። ሳሙኤልም እኔ ባሪያህ እሰማሃለሁና #ጌታዬ በል ተናገር አለው #እግዚአብሔርም ሳሙኤልን የሰማው ሁሉ ሁለቱን ጆሮዎቹን ይይዝ ዘንድ እነሆ እኔ በእስራኤል ላይ የተናገርሁት ቃሌን አደርጋለሁ።

በዚያችም ቀን በኤሊና በወገኑ ላይ የተናገርኹትን ሁሉ አጸናለሁ እጀምራለሁ እፈጽማለሁም። ልጆቹ የ #እግዚአብሔርን ቃል አቃልለዋልና እርሱም አልገሠጻቸውምና በልጆቹ ኃጢአት እኔ ወገኑን ለዘላለም እንደምበቀለው ነገርሁት። ስለዚህም ነገር በዕጣንም ቢሆን በመሥዋዕትም ቢሆን የኤሊ የወገኑ ኃጢአት እስከ ዘላለሙ ድረስ እንዳይሠረይ ራሴ እንዲህ ብዬ ማልሁ። በኤሊ ወገኖችና ልጆች ላይ #እግዚአብሔር የተናገረው ሁሉ ተፈጸመ።

ከዚህም በኋላ የቂስ ልጅ ሳኦልን ቀብቶ ለእስራኤል ልጆች ያነግሠው ዘንድ #እግዚአብሔር ሳሙኤልን አዘዘው እንዲአነግሥላቸው ለምነዋልና። ሳኦልም የልዑልን ትእዛዝ በተላለፈ ጊዜ ዳግመኛ ለእስራኤል ንጉሥ ሊሆን የዕሴይ ልጅ ዳዊትን ይቀባው ዘንድ ይህን ነቢይ ሳሙኤልን ዳግመኛ አዘዘው። ይህም ነቢይ ሳሙኤል በሕይወት በኖረበት ዘመን ሁሉ እስራኤልን አስተዳደራቸው። ከዚህም በኋላ ሰኔ ዘጠኝ ቀን በሰላም አረፏል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እና በቅዱስ ሳሙኤል ነብይ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ፊቅጦርና_እናቱ_ሣራ

በዚህች ቀን ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፊቅጦርና እናቱ ቅድስት ሣራ መታሰቢያቸው ነው፡፡
የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ ባለሟል በነበረው በገዛ አባቱ እጅግ ተሠቃይቶ ምስክርነቱን የፈጸመው ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፊቅጦር፡- ኅርማኖስ የተባለው ወላጅ አባቱ የክርስቲያኖችን ደም እንደ ውኃ ያፈስ የነበረው የዲዮቅልጥያኖስ ልዩ አማካሪና የሠራዊቱ አለቃ ነበር፡፡ እናቱ ሣራ ግን በ #ክርስቶስ አምና የተጠመቀች ክርስቲያን ነበረች፡፡

እንዲያውም ልጇን ቅዱስ ፊቅጦርን ከመውለዷ በፊት የአምላክ እናት የቅድስት #ድንግል_ማርያም ሥዕል ወዳለበት ሄዳ "እመቤቴ ማርያም ለ #ኢየሱስ_ክርስቶስ ደስ የሚያሰኘውን ልጅ ስጪኝ፡፡ #ኢየሱስ_ክርስቶስን ደስ የማያሰኝ ልጅ ከሆነ ግን ማኅፀኔን ዝጊልኝ" ብላ በጸለየችው ጸሎት ነው ቅዱስ ፊቅጦርን ያገኘችው፡፡

ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር በዓለም ላይ ያሉ በ #ክርስቶስ ያመኑ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ በግፍ ያስገድል በነበረበት ወቅት የተገኘ ታላቅ ሰማዕት ነው፡፡ ፊቅጦርን ገና 15 ዓመት እንደሆነው ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ "ከፍ ባለ ስልጣን አስቀምጥሃለሁ፣ እጅግ ብዙ ወርቅና ንብረትም እሰጥሃለሁ፣ በእስክንድርያም ላይ ገዥ አድርጌ እሾምሃለሁ #ክርስቶስን ማመንህን ተውና ወደ ቤተ መንግሥቴ ግባ" ቢለውም ቅዱስ ፊቅጦር ግን ብዙ መከራንና ሥቃይን ተቀብሎ ሰማዕት መሆንን መረጠ፡፡ ቅዱስ ፊቅጦርም ዲዮቅልጥያኖስን " #ክርስቶስን በምታፈቅረው ጊዜ አፈቀርኩህ ወደ አንተም መጣሁ፤ #ክርስቶስን በጠላኸው ጊዜ ግን እኔም ጠላሁህ፣ ቤትህንም ጠላሁ" ብሎታል፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ ዲዮቅልጥያኖስ ቅዱስ ፊቅጦርን በመንግሥቱ ውስጥ ሦስተኛ ማዕረግ አድርጎ ሾመው፡፡ እርሱ ግን ይጾማል ይጸልያል እንጂ በንጉሡ ቤት አይበላ አይጠጣም ነበር፡፡ ዕድሜውም 27 ነበር፡፡ አባቱንም ከጣዖት አምላኪነቱ እንዲመለስ ቢመክረው ሄዶ ለንጉሡ ከሰሰው፡፡ ፊቅጦርም "ለአንተ ለጣዖት አምላኩ አገልጋይ አልሆንም" በማለት በንጉሡ ፊት ትጥቁን ፈቶ ጣለ፡፡ የቅዱስ ፊቅጦር ወላጅ አባቱ ኅርማኖስ የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ የቅርብ እንደራሴና መስፍን ስለነበር ልጁ ፊቅጦርን የንጉሡን ሹመትና ልመና እንዲቀበል ብዙ ሲያግባባው ነበር፤ አባቱም ልጁ በሀሳቡ እንዳልተስማማለት ሲያውቅ ከዲዮቅልጥያኖስ ጋር ተማክሮ ልጁን ቅዱስ ፊቅጦርን ወደ እስክንድርያና ወደ ተለያዩ ሀገሮች በግዞት ተልኮ በዚያም ተሠቃይቶ እንዲሞት ፈደበት፡፡

ወደ ግብፅም ልከው በዚያ እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ነጥቆ ወስዶ በሰማያት የሰማዕታትን ክብር አሳይቶት ወደ ምድር መለሰው፡፡ ክፉዎቹም በብረት አልጋ አስተኝተው ከሥሩ እሳት አነደደዱበት፡፡ በሌላም ልዩ ልዩ በሆኑ ማሠቃያዎች እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ተገልጦ ፈወሰው፡፡ ወደ እንዴናም አጋዙትና በዚያም ብዙ አሠቃዩት፡፡ ምላሱን ቆረጡት፤ በችንካርም ጎኖቹን በሱት፤ ቁልቁል ሰቅለውም ቸነከሩት፤ በእሳትም ውስጥም ጨመሩት፤ ዐይኖቹን አወጡት፤ እሬትና መራራ ሐሞትንም አጠጡት፡፡ ደግመውም ዘቅዝቀው ሰቀሉት፡፡ ጌታችንም ተገልጦ ካጽናናው በኋላ ፈወሰውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ፊቅጦር፣ ፋሲለደስ፣ ቴዎድሮስ በናድልዮስ፣ አውሳብዮስና መቃርዮስ እነዚህ ሰማዕታት በአንድነት በአንድ ዘመን አብረው ኖረው ተሰውተው ሰማዕት የሆኑ የሥጋም ዝምድና ያላቸው የነገሥታት ልጆች ናቸው። ዲዮቅልጥያኖስም የቅዱስ ፊቅጦርን ዐይኑን አስወለቀው፣ ነገር ግን የታዘዘ መልአክ መጥቶ የዓይኑን ብርሃን መልሶለታል፡፡ ሰማዕቱ በመዝለል ባሕር የሚሻገር እንደ አሞራ የሚመስል ፈረስ ነበረው፡፡ ከዚህም በኋላ ማሠቃየቱ ቢሰለቻቸው ሚያዝያ 27 ቀን አንገቱን ሰይፈው በሰማዕትነት እንዲያርፍ አድርገውታል፡፡

ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር አንድ የሚነገር ትልቅ ታሪክ አለው፡፡ እርሱም በሰማዕትነት ካረፈ ከብዙ ዘመን በኋላ በራእይ ተገልጦ በ8ኛው ሺህ ዘመን በሀገራችን በኢትዮጵያና በግብፅ እንዲሁም በቁስጥንጥንያና በሮም ወደፊት የሚሆነውን ነገር ሁሉ በግልጽ የተናገረ መሆኑ ነው፡፡ ‹‹ስለ ሃይማኖት ቅዱስ ፊቅጦር ያየው ራእይ›› የሚል መጠሪያ ያለው ይህ ራእይ በሀገራችን ጎጃም ደብረ ጽሞና ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#12ቱ_ደቂቀ_ያዕቆብ

በዚችም ቀን ዳግመኛ አባቶቻችን ዐሥራ ሁለቱን የያዕቆብን ልጆች ያስቧቸዋል።

እነዚህ አበው የአብርሃምና የይስሐቅ የልጅ ልጆች የያዕቆብ ደግሞ ልጆች ናቸው። ትውልድ ከአዳም እስከ ቅዱስ ያዕቆብ አንድ ሐረግ ይዞ መጥቶ እዚህ ላይ ሲደርስ ይበተናል። አባታችን ያዕቆብን #እግዚአብሔር ሲባርከው እሥራኤል አለው። ትርጉሙም "ሕዝበ #እግዚአብሔር ወልድ ዘበኩር (የበኩር ልጅ) ከሃሊ ነጻሪ (አስተዋይ) እንደ ማለት ነው።

ይህ ቅዱስ አባት ለ #ድንግል_ማርያም ቅድመ አያት ከመሆኑ ባሻገር ነቢያትን፣ ካህናትን፣ ነገሥታትንና መሣፍንትን ወልዷል። ከወንድሙ ኤሳው ጋር ተጣልቶ ወደ ሶርያ በሔደ ጊዜ ከ2ቱ ሚስቶቹ (ልያና ራሔል) 8 ልጆችን፣ ከ2ቱ የሚስቶቹ ደንገጥሮች (ዘለፋና ባላ) 4 ልጆችን በድምሩ 12 ልጆችን ወልዷል።

#ከልያ የተወለዱት፦ ሮቤል፣ ስምዖን፣ ሌዊ፣ ይሁዳ፣ ይሳኮር እና ዛብሎን ይባላሉ።
#ከራሔል የተወለዱት፦ ዮሴፍና ብንያም ይባላሉ።
#ከባላ የተወለዱት፦ ዳን እና ንፍታሌምን ሲሆኑ
#ከዘለፋ የተወለዱት ደግሞ፦ጋድ እና አሴር ይባላሉ። 12ቱ ደቂቀ እሥራኤል (ያዕቆብ) ማለት እኒህ ናቸው::

ከ12ቱ በቅድስና ዮሴፍ ከፍ ቢልም #እግዚአብሔር ለክህነት ሌዊን፣ ለመንግስት ደግሞ ይሁዳን መርጧል። ከእነሱ ዘርም ዓለምን ለማዳን ተወልዷል። 10ሩ አበው በተለይ በዮሴፍ ላይ ግፍ ሠርተው የነበረ ቢሆንም በኋላ ተጸጽተዋል።
እነሆ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ታስባቸዋለች (ዘፍጥረት ከምዕራፍ 28 እስከ 31)

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቡነ_ዘርዐ_ቡሩክ

በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ ተአምረኛው አቡነ ዘርዐ ቡሩክ ልደታቸው ነው፡፡ ከመወለዳቸው አስቀድሞ ትንቢት ተነግሮላቸው ነበር፡፡ አባታቸው ደመ ክርስቶስ ዐይነ ሥውር የነበረ ሲሆን አቡነ ዘርዐ ቡሩክ በተወለዱ ጊዜ ግን የአባታቸውን ዐይን አብርተውለታል፡፡ አባታችን ዘርዐ ቡሩክ ገና በሰባት ዓመታቸው ነው ረቡዕና ዓርብ መጾም የጀመሩት፡፡ በዚሁ በሰባት ዓመታቸውም ‹‹ይህን ዓለም ክፋቱን እንዳላይ ዐይኖቼን አሳውርልኝ›› በማለት ዐይናቸውን እንዲያጠፋላቸው አምላካቸውን ለምነው እንደፈቃዳቸው ዐይነ ሥውር ሆነዋል፡፡ ነገር ግን ከሰባት ዓመት በኋላ በ12 ዓመታቸው #ጌታችን "ለዓለም የምታበራ ብርሃን አደርግሃለሁና ዐይንህም ይብራ" በማለት ዐይነ ብርሃናቸውን መልሶላቸው እንዲያዩ አድርጓቸዋል፡፡ በዚህም ዕድሜያቸው (በ12 ዓመታቸው) ሰባቱንም አጽዋማት ይጾሙ ነበር፡፡

ከዚህም በኋላ #ጌታችን የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ሁሉ ገለጠላቸው፡፡ መጻሕፍተ ብሉያትን፣ መጻሕፍተ ሐዲሳትን፣ መጻሕፍተ ሊቃውንትን፣ መጻሕፍተ መነኮሳትን፣ አዋልድ መጻሕፍትን ሁሉ ገልጦላቸዋል፡፡ ከሟርት መጻሕፍት በቀር ያስቀረባቸው ነገር አልነበረም፤ የቅዱስ ያሬድንም ዜማ እንዲሁ ገለጠላቸው፡፡
አብርሃምም ወደ #እግዚአብሔር ለመነ #እግዚአብሔርም አቤሜሌክን ፈወሰው ሚስቱንም ባሮቹንና ቤተሰቦቹንም ልጆቹንም ሁሉም ወለዱ ስለ አብርሃም ሚስት ስለሣራ #እግዚአብሔር ማሕፀንን ሁሉ በአፍአ በውስጥ ዘግቶ ነበርና።

ከዚህም በኃላ በጎ ተጋድሎውን ፈጽሞ #እግዚአብሔርንም አገልገሎ በመቶ ሰባ አምስት ዕድሜው ወደ ወደደው #እግዚአብሔር ሔደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን በቅዱስ አብርሃም ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ይስሐቅ

በዚህችም ቀን ዳግመኛ የአባቶች አለቃ ለሆነ ለአብርሃም ልጅ ለይስሐቅ የዕረፍቱን መታሰቢያ እንድናደርግ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶቻችን አዘዙን። ይህ ጻድቅ ይስሐቅም በልዑል አምላክ ብሥራት ተወለደ።

ይህንንም ንጹሕ ይስሐቅን #እግዚአብሔር ለልጁ ክርስቶስ ምሳሌው አደረገው። አብርሃምን እንዲህ ብሎታልና የምትወደው ልጅህ ይስሐቅን ከአንተ ጋራ ውሰደውና ወደላይኛው ተራራ ሒደረ እኔ ወደ እምነግርህ ወደ አንዱ ተራራ ላይ አውጥተህ በዚያ ሠዋው።

አብርሃምም በጥዋት ተነሥቶ አህያውን ጫነ ልጁ ይስሐቅንና ሁለቱ ብላቴኖቹንም ወሰደ ለመሥዋዕትም ዕንጨትን ፈልጦ አሸክሞ ሔደ። በሦስተኛም ቀን #እግዚአብሔር ወዳለው ወደዚያ ቦታ ደረሰ አብርሃምም በዐይኑ ቃኘ ቦታውንም ከሩቅ አየ።

አብርሃምም ብላቴኖቹን እናንተ አህያውን ይዛችሁ ከዚህ ቆዮ እኔና ልጄ ግን ወደ ተራራ እንሔዳለን ሰግደንም ወደ እናንተ እንመለሳለን አላቸው። አብርሃምም መሥዋዕት የሚቃጠልበትን ዕንጨት አምጥቶ ለልጁ ለይስሐቅ አሸከመው እሱም ወቅለምቱንና እሳቱን በጁ ያዘ ሁለቱም በአንድነት ሔዱ።

ይስሐቅም አባቱ አብርሃምን አባ አለው እርሱም ልጄ ምነው አለው እነሆ እሳትና እንጨት አለ መሥዋዕት የሚሆነው በጉ ወዴት ነው አለው አብርሃምም መሥዋዕት የሚሆነውን በግ #እግዚአብሔር ያዘጋጃል አለው።

አብረውም ሔደው #እግዚአብሔር ወዳለው ወደዚያ ቦታ ደረሱ አብርሃምም በዚያ መሠዊያን ሠራ ዕንጨቱን ደረደረ ልጁ ይስሐቅንም አሥሮ ጠልፎ በመሠዊያው በዕንጨቱ ላይ በልቡ አስተኛው። አብርሃምም ልጁን ያርደው ዘንድ እጁን ዘርግቶ ወቅለምቱን አነሣ።

#እግዚአብሔርም አብርሃምን አብርሃም አብርሃም ብሎ ጠራው እርሱም አቤት አለ በልጅህ ላይ እጅህን አትዘርጋ ምንም ምን አታድርግበት አንተ #እግዚአብሔርን እንደምትፈራው አሁን አወቅሁ ለምትወደው ለልጅህ አልራራህለትምና አለው።

አብርሃምም በተመለከተ ጊዜ ቀንድና ቀንዱ በዕፀ ሳቤቅ የተያዘ አንድ በግ አየ አብርሃምም ሔደና ወስዶ በልጁ በይስሐቅ ፈንታ ሠዋው። ይህም ንጹህ ይስሐቅ ጎልማሳ ሲሆን አባቱ ሊሠዋው በአቀረበው ጊዜ #እግዚአብሔር በበግ እስከ አዳነው ድረስ ለአባቱ በመገዛት ለመታረድ አንገቱን ዘርግቶ ሰጠ።

እርሱም በአባቱ በአብርሃም ሕሊና ፍጽም መሥዋዕተ ሆነ። ከዚህም በኃላ ይስሐቅን መቸገርና ስደት አግኝቶታል በአባቱ በአብርሃም ዘመን ከሆነው ሌላ በሀገር ረኃብ ሁኖ ነበርና የፍልስጥዔም ንጉሥ አቤሜሌክ ወዳለበት። ወደ ጌራራ ይስሐቅ ሔዶ በዚያ ተቀመጠ።

የአገር ሰዎችም ይስሐቅን የሚስቱን የርብቃን ነገር ጠየቁት እርሱም እኅቴ ናት አላቸው ስለ ሚስቱ ስለ ርብቃ የዚያች አገር ሰዎች እንዳይገድሉት ሚስቴ ናት ብሎ መናገርን ፈርቷልና መልከ መልካም ነበረችና። በዚያም ብዙ ዘመን ኖሩ አቤሜሌክም በመስኮት በተመለከተ ጊዜ ይስሐቅን ከርብቃ ጋር ሲጫወት አየው።

አቤሜሌክም ይስሐቅን ጠርቶ እኅቴ ናት አልከኝ እንጂ እነሆ ሚስትህ ናት አለው ይስሐቅም በርሷ ምክንያት ይገድሉኛል ብዬ ነው አለው። አቤሜሌክም ይህ ያደረግኽብኝ ነገር ምንድን ነው ከዘመዶቼ የሚሆን አንድ ሰው ከሚስትህ ጋር ሊተኛ ጥቂት ቀርቶት ነበር ባለማወቅም ኃጢአትን ልታመጣብኝ ነበር።

ንጉሡም የዚህን ሰው ሚስቱን የነካ ሁሉ ፍርዱ ይሙት በቃ ነው ብሎ ሕዝቡን አዘዛቸው። ይስሐቅም በዚያች ምድር ዘርን ዘራ መቶ ዕጽፍም ሆነለት #እግዚአብሔርም ባረከው ከፍ ከፍም አለ እጅግም ገነነ ወንድ ባርያን ሴት ባርያን ላምን በግን አብዝቶ ገዛ የፍልስጥኤም ሰዎችም ቀኑበት።

በአባቱም ዘመን የአብርሃም ብላቴኖች የቆፈሩአቸውን ጉድጓዶች የፍልስጥኤም ሰዎች ደፈኑዋቸው አፈርንም መሏቸው። አቤሜሌክም ይስሐቅን ፈጽመህ በርትተህብናልና ከእኛ ተለይተህ ሒድ አለው።

ይስሐቅም ከዚያ ተነሥቶ በጌራራ ሸለቆ ሰፍሮ በዚያ ተቀመጠ። ይስሐቅም ያባቱ አገልጋዮች የቆፈሩዋቸውን አባቱ አብርሃምም ከሞተ በኃላ የፍልስጥኤም ሰዎች የደፈኗቸውን የውኃ ጉድጓዶች እንደገና ቆፈራቸው አብርሃም እንደጠራቸው ጠራቸው።

የይስሐቅም አገልጋዮች በጌራራ ቆላ ጉድጓድ ቆፍረው የሚጣፍጥ የውኃ ምንጭ አገኙ የይስሐቅ እረኞችና የጌራራ እረኞች ይህ ውኃ የኛ ነው የኛ ነው በማለት ተጣሉ ያችንም የውኃ ጉድጓድ የዓመፅ ጉድጓድ ብሎ ጠራት ዐምፀውበታልና።

ይስሐቅም ከዚያ ተጎዞ ሒዶ በዚያ ሌላ ጉድጓድ ቁፈረ በርሷም ምክንያት ተጣሉት ስሟንም ጠብ ብሎ ምክንያት ተጣሉት ስሟንም ጠብ ብሎ ጠራት። ከዚያም ተጎዞ ሒዶ ሌላ ጉድጓድን ቁፈረ በርሱም ምክንያት ግን አልተጣሉትም ስሙንም ሰፊ አለው ዛሬ #እግዚአብሔር አሰፋልን በምድርም አበዛን ሲል።

ከዚህም በኃላ ሁለት ልጆችን ኤሳውንና ያዕቆብን ወለደ። ይስሐቅም ኤሳውን ጽኑዕ ኃይለኛ ስለሆነ ይወደዋል። ይስሐቅም አርጅቶ ዐይኖቹ ፈዘው የማያይ ከሆነ በኃላ እንዲህ ሆነ ታላቁ ልጁ ኤሳውን ጠርቶ እነሆ አረጀሁ የምሞትበትንም ቀን አላውቅም ማዳኛ መሣሪያህን የፍላፃ መንደፊያህን ይዘህ ወደ በረሃ ውጣ። ሳልሞት ነፍሴ እንድትመርቅህ እበላ ዘንድ እንደምወደው አድርገህ አምጣልኝ አለው።

ርብቃም ልጁ ኤሳውን እንዲህ ሲለው ይስሐቅን ሰማችው ኤሳውም ወደ አደን ሔደ። ርብቃም ታናሹ ልጇ ያዕቆብን እንዲህ አለችው እነሆ አባትህ ወንድምህን ኤሳውን ሳልሞት በ #እግዚአብሔር ፊት እንድመርቅህ ከአደንከው አዘጋጅተህ የምበላውን አምጣልኝ ሲለው ሰምቼዋለሁ።

አሁንም ልጄ ሆይ በማዝህ ነገር እሽ በለኝ ወደ በጎቻችንም ሒደህ ያማሩ ሁለት ጠቦቶችን አምጣልኝና አባትህ እንደሚወደው አዘጋጃቸው ዘንድ ሳይሞት በልቶ እንዲመርቅህ ወስደህ ለአባትህ እንድትሰጠው አለችው።

ያዕቆብም እናቱ ርብቃን እንዲህ አላት እነሆ ወንድሜ ኤሳው ጠጉራም ነው እኔ ግን ጠጉራም አይደለሁም ምናልባት አባቴ ቢዳስሰኝ በፊቱ እንደምዘብትበት እሆናለሁና ምርቃን ያይደለ በላዬ መርገምን አመጣለሁ።

እናቱም ልጄ ሆይ መርገምህ በእኔ ይሁን ቃሌን ብቻ ስማኝ ሒድና የምልህን አምጣልኝ አለችው ሒዶም ለእናቱ አመጣላትና አባቱ እንደሚወደው አድርጋ መብሉን አዘጋጀች።

ርብቃም ከርሷ ዘንድ የነበረ ያማረውን የታላቅ ልጅዋ የኤሳውን ልብስ አምጥታ ለታናሽ ልጅዋ ለያዕቆብ አለበሰችው ያንንም የሁለቱን ጠቦቶች ለምድ በትከሻውና በአንገቱ ላይ አደረገች ያንን ያዘጋጀችውን እንጀራና ጣፋጭ መብልን ለያዕቆብ በእጁ ሰጠችው።

ወደ አባቱ ገብቶ አባቴ ሆይ አለው አባቱም እነሆኝ ልጄ ሆይ አንተ ማነህ አለው ያዕቆብም እኔ የበኩር ልጅህ ኤሳው ነኝ ያልከኝን አዘጋጅቻለሁ ተነሥና ተቀመጥ ከአደንኩልህም ብላና ነፍስህ ትመርቀኝ ዘንድ አለው።
ይስሐቅም ልጁን ልጄ ሆይ ፈጥነህ ያገኘህ ይህ ምንድነው አለው እርሱም ፈጣሪህ #እግዚአብሔር በፊቴ የሰጠኝ ነው አለው። ይስሐቅም ልጄ ቅረበኝ ልዳሥሥህ አንተ ኤሳው እንደሆንክ ወይም እንዳልሆንክ አለው በቀረበም ጊዜ ዳሠሰውም ቃልህ የያዕቆብ እጆችህ አድነህ ያመጣህልኝን በልቼ ነፍሴ ትመርቅህ ዘንድ አምጣልኝ አለው አቅርቦለት በላ ወይንም አመጣለት ጠጣ።

ይስሐቅም ልጄ ቅረበኝና ሳመኝ አለው ቀርቦም ሳመው የልብሱን ሽታ አሸተተው እነሆ የልጄ ልብስ ሽታው #እግዚአብሔር እንደባረከው እንደዱር አበባ ሽታ ነው አለ። እንዲህም ብሎ መረቀው ከሰማይ ጠል ከምድር ስብ ይስጥህ ሥንዴህን ወይንህንና ዘይትህን ያብዛልህ አሕዛብም ይገዙልህ አለቆችም ይስገዱልህ ለወንድሞችህም ጌታ ሁን የአባትህም ልጆች ይስገዱልህ። የሚረግምህም የተረገመ ይሁን ይህም በ #እግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ።

ይህም አባት ይስሐቅ ወደ መቶ ሰማንያ ዘመን ደረሰ አባታችን ይስሐቅም እንዲህ ብሎ ተናገረ ከዚህም በኃላ መልአክ ወደ ሰማይ ወሰደኝ አባቴ አብርሃምን አየሁትና ሰገድሁለት እርሱም ሳመኝ ንጹሕን ሁሉ ስለ አባቴ ተሰበሰቡና ወደ ውስጠኛው የአብ መጋረጃ ከበውኝ ከእኔ ጋራ ሔዱ እኔም ወድቄ ከአባቴ ጋራ ሰገድኩ።

የሚያመሰግኑ መላእክት ሁሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ የሚመሰገን አሸናፊ #እግዘአአብሔር ምስጋናው በሰማይና በምድር የመላ ነው እያሉ ጮኹ።

አባቴ አብርሃምን እኔ በቦታዬ ልዩ ነኝ ሰው ሁሉ ልጁን በወዳጄ ይስሐቅ ስም ቢሰይም በቤቱ ውስጥ በረከቴ ለዘላለም ይኖራል የቡሩክ ወገን የሆንክ አንተ ቡሩክ አብርሃም ሆይ መምጣትህ መልካም ነው። አሁንም በወዳጄ በልጅህ ይስሐቅ ስም የሚለምን ሁሉ በረከቴ በቤቱ ውስጥ ለዘላለም እንዲኖር ቃል ኪዳኔን አጸናለታለሁ አለው።

ትሩፋቱን ቅንነቱን ገድሉን የሚጽፍ ካለ ወይም በስሙ የተራበ የሚያጠግብ በመታሰቢያው ቀን የተራቆተ የሚያለብስ እኔ የማያልፈውን መንግሥት እሰጠዋለሁ።

አብርሃምም እንዲህ አለ አቤቱ ዓለሙን ሁሉ የያዝክ #አብ ሆይ ቃል ኪዳኑን ገድሉን ይጽፍ ዘንድ ካልተቻለው ቸርነትህ ትገናኘው አንተ ቸር መሐሪ ነህና አንጀራ የሌለው ችግረኛ ቢሆንም። #ጌታም እንዲህ ብሎ መለሰለት በወዳጄ በይስሐቅ በመታሰቢያው ዕለት ከሌሊት ጀምሮ በጸሎት ይትጋ አይተኛ እኔም መንግሥቴን ከሚወርሱ ጋራ ከበረከቴ እሰጠዋለሁ።

አባቴ አብርሃምም ሁለተኛ እንዲህ አለ በሽተኛ ድውይ ከሆነ ቸርነትህ ታግኘው #ጌታም እንዲህ አለ ጥቂት ዕጣን ያግባ ዕጣንን ካላገኘ የቃል ኪዳኑን መጽሐፍ ፈልጎ በልጅህ በወዳጄ በይስሐቅ መታሰቢያ ቀን ያንብበው። ማንበብም የማያውቅ ከሆነ ወደሚያነቡለት ሒዶ እሷን አስነብቦ ይስማ። ከእነዚህም ይህን ማድረግ ካልቻለ ወደ ቤቱ ገብቶ ደጁን ይዝጋ እየጸለየ መቶ ስግደቶችን ይስገድ እኔም የሰማይ የመንግሥት ልጅ አደረገዋለሁ።

ለቁርባን የሚሆነውንና መብራትን ያገባ እኔ ያልኩትን ሁሉ የሚያደርግ እርሱ የመንግሥተ ሰማያትን ርስት ይቀበላል። ቃል ኪዳኑንና ገድሉን ትሩፋቱን ለመጻፍ ልቡን ያበረታውን እኔ ስሙን በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ በሺው ዓመት ምሳ ላይም ይገኛል።

#እግዚአብሔርም ይህን ብዙ ነገርን በተናገረ ጊዜ ያዕቆብ አይቶ በመደንገጥ ነፍሱ ተመሠጠች ይስሐቅም ያዕቆብን አንሥቶ ልጄ ሆይ ዝም በል አትደንግጥ ብሎ ጠቀሰው ከዚህም በኃላ ሳመውና በሰላም አረፈ። ከኤሞር ልጆች በገዛው እናቱ ሣራ በተቀበረችበት በአብርሃም መቃብር ተቀበረ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ይስሐቅ አማላጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያዕቆብ

በዚችም ቀን ደግሞ #እግዚአብሔር እስራኤል ብሎ ስም ያወጣለትን የአባቶች አለቃ የሆነ የያዕቆብን የዕረፍቱን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶቻችን አዘዙን። ይህም ቅዱስ በበጎ ሥራ ሁሉ በመራራት በቅንነት በትሕትና በለጋስነት የአባቶቹን የአብርሃምንና የይስሐቅን መንገድ የተከተለ ሆነ።

ወንዱሙ ኤሳውም ብኩርናውን በምስር ንፍሮ ደግሞ በረከቱን ስለወሰደበት አብዝቶ ስለጠላው ሊገድለው ይፈልግ ነበር ስለዚህም አባቱ ይስሐቅና እናቱ ርብቃ ያዕቆብን ወደ ርብቃ ወንድም ወደ ላባ ሰደዱት።

እየተጓዘም ሳለ በአደረበት በረሀ ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ መሰላል የ #እግዚአብሔርም መላእክት በውስጡ ሲወርዱ ሲወጡ በሕልሙ አየ እንዲህም አለ ይህ የሰማይ ደጅ ነው ከዚህም የ #እግዚአብሔር ቤት ይሠራል።

በሶርያ ምድር ወደሚኖር ወደእናቱ ወንድም ወደ ላባ በደረሰ ጊዜ ሁለቱን ልጆቹን ልያንና ራሔልን አጋባው በዚያም የላባን በጎች እየጠበቀ ሃያ አንድ ዓመት ያህል ኖረ። ላባም የምሰጥህ ምንድን ነው አለው ያዕቆብም ምንም የምትሰጠኝ የለም አሁን ወደፊት የምነግርህን ነገር ካደረግህልኝ ዳግመኛ በጎችህን ፈጽሜ እጠብቃለሁ።

አሁን በጎችህ በፊት ይለፉና ከበጎችህ ሁሉ ጠጉራቸው ነጫጭ የሆኑትንና መልካቸው ዝንጉርጉር የሆነውንም ስለዋጋዬ ለይልኝ አለው። ዓይነቱ ዝንጉርጉር ያልሆነውና መልኩ ነጭ ያልሆነው ሁሉ ግን ላንተ ይሁን አለው። ላባም እንዳልክ ይሁን አለ።

በዚያችም ቀን ነጩንም ቀዩንም ዝንጉርጉሩንም መልኩ ዳንግሌ የሆነውንም የፍየሉንም አውራ ለይቶ ለልጆቹ ሰጠ። በእነርሱና በያዕቆብ መካከል ሦስት ቀን የሚያስኬድ ጎዳና ርቀው ሔዱ ያዕቆብ ግን የቀሩትን የላባን በጎች ይጠብቅ ነበር።

ያዕቆብም የልምጭ በትርንና ታላቅ የሎሚ በትርን ወስዶ ቅረፍቱን ልጦ ጣለው ያዕቆብ የላጣቸው በትሮች ነጫጭ ሁነው ታዩ። እነዚያንም በትሮች በጎች ከሚጠጡበት ገንዳ ላይ ጣላቸው በጎች ውኃ ሊጠጡ በመጡ ጊዜ እነዚያ በትሮች በፊታቸው ሁነው ይታዩ ዘንድ። መጥተውም በጠጡ ጊዜ እነዚያን በትሮች አስመስለው ፀንሰው ነጩንና ሐመደ ክቦውን ዝንጉርጉሩን ወለዱ።

ያዕቅብም አውራ አውራዎቹን በጎች ለየ አውራ አውራውን ከለየ በኃላ እንስት እንስቶቹን በጎች ለይቶ ዝንጉርጉር ሐመደ ክቦና ነጭ በሆኑ አውራዎች ፊት አቆማቸው የራሱንም በጎች ለያቸው እንጂ ከላባ በጎች ጋራ አልቀላቀላቸውም።

ያዕቆብም እጅግ ፈጽሞ ባለጸጋ ሆነ ሴቶችንም ወንዶችንም አገልጋዩችን ገዛ ብዙ ከብት ላሞችን በጎችን ግመሎችንና አህዮችን ገዛ። ያዕቆብም ወደአገሩ በተመለሰ ጊዜ እስከ ንጋት ድረስ አንድ ሰው ሲታገለው አደረ ከእርሱም ጋራ ሲታገል እንዳልቻለው ባየ ጊዜ እርም የሚሆንበት ሹልዳውን ያዘው ጎህ ቀድዷልና ልቀቀኝ አለው ካልመረቅከኝ አልለቅህም አለው።

ስምህ ማን ይባላል ቢለው ስሜ ያዕቆብ ነው አለው እንግዲህ ስምህ ያዕቆብ አይባል እስራኤል ይባል እንጂ አለው ከ #እግዚአብሔርና ከሰው ጋራ መታገልን ችለሃልና።

ከዚህም በኃላ ስለ ልጁ ዮሴፍ ብዙ ኀዘን አገኘው ወንድሞቹ ወደ ግብጽ ሸጠውታልና በጠየቃቸውም ጊዜ ክፉ አውሬ በልቶታል አሉት ከልቅሶውም ብዛት የተነሣ ዐይኖቹ ታወሩ።

ከዚህም በኃላ ታላቅ ረሀብ ሆነ በግብጽ አገር እህል የሚሸጥ መሆኑን ያዕቆብ ሰማ ሥንዴ ይሸምቱ ዘንድ ልጆቹን ላካቸውና ወደ ዮሴፍ ደረሱ ንጉሥ ሆኖም አግኘተውት ሰገዱለት ወንድማቸው እንደሆነም አላወቁትም እርሱ ግን አውቋቸዋል ሥንዴውንም ሰጥቶ አስናበታቸው ሁለተኛም በተመለሱ ጊዜ ራሱን ገለጠላቸውና ወደዚህ ስለ ሸጣችሁኝ አትፍሩ እመግባችሁ ዘንድ በፊታችሁ #እግዚአብሔር ለሕይወት ልኮኛልና አላቸው።

አሁንም ፈጥናችሁ ሒዱና ለአባቴ ንገሩት ልጅህ ዮሴፍ እንዲህ ይላል በሉት ለግብጽ አገር ሁሉ #እግዚአብሔር ጌታ አድርጎኛል ፈጥነህ ና በዚያ ልኑር አትበል።
#ነሐሴ_29

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ከእመቤታችን ከቅድስት #ድንግል_ማርያም መድኃኒታችን #ኢየሱስ_ክርስቶስ በሥጋ ለመወለዱ መታሰቢያ በዓል ሆነ ለእርሱም ምስጋና ክብር ይሁን ለዘላለሙ አሜን፣ #የአባ_ዮሐንስ_ሐጺር ወደ አስቄጥስ ገዳም የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ #ቅዱስ_አትናቴዎስ #ገርሲሞስና_ቴዎዶጦስ ከሚባሉ ሁለት አገልጋዮቹ ጋር በሰማዕትነት አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዮሐንስ_ሐጺር

ነሐሴ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን የአባ ዮሐንስ ሐጺር ወደ አስቄጥስ ገዳም የሥጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም የአባ እንጦንዮስ በሆነ በቊልዝም ገዳም ከአረፈ በኋላ ነው። ለእስክንድርያ አባ ዮሐንስ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ስምንተኛ የሆነ ነው። እርሱም ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ የከበሩ መነኰሳትም እንዲህ አሉት የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ በዚህ በቤተ ክርስቲያኑ ቢሆን እኛም ሥጋው በአለበት ለፈጣሪያችን #እግዚአብሔር እንሰግድ ዘንድ እንሻ ነበር።

ያን ጊዜ የ #እግዚአብሔር ቸርነት አነሣሣችውና ስሙ ቆዝሞስ ለሚባል ለአንድ አበ ምኔት መልእክትን ጻፈ ከእርሱም ጋር የቊልዝም አገር የሆነ አረጋዊ አለ በደረሱም ጊዜ በዚያን ሰዓት ሥጋውን መውሰድ አልተቻላቸውም። የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ የኬልቄዶንን ጉባኤ በተቀበሉ መለካውያን ዘንድ ይጠበቅ ስለነበረ ነገር ግን ቦታውን አወቁ ተረዱ ወደ ቦታቸውም ተመልሰው ሃይማኖታቸው የቀና ምእመናን ሰዎችን አገኙ እነርሱም በዚያች አገር የሚኖሩ ናቸው ስለርሱ የመጡበትን ነገሩአቸው።

ከጥቂት ቀኖች በኋላም ከታላላቅ ዐረቦች ወገን ለቊልዝም አገር መኰንን ተሾመ እርሱም ለኤጲስቆጶስ አባ ሚካኤል ወዳጁ ነው ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስም ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ ወደ ኤጲስቆጶሱ መልእክትን ጻፈ። በመልእክቱም የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺርን ሥጋ ከከሐድያን መለካውያን እጅ እስከ አፈለሱት ድረስ መልእክተኞች አእሩግ መነኰሳትን ምክንያት ፈልጎ እንዲረዳቸው በማሳሰብ አዘዘው።

ኤጲስቆጶሱም በሰማ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለው ሒዶም ወዳጁ ለሆነ ለመኰንኑ ጸሐፊ ነገረው። ጸሐፊውም ለመኰንኑ ነገረው። እነሆ መኰንኑም ከመነኰሳቱ ጋራ ሔደ ጸሐፊውም መነኰሳቱ ወደዚያ ቦታ እንዲገቡ ምክንያት እንዴት እናገኛለን አለ። መኰንኑም በልብሶቻቸው ላይ የዓረቦችን ልብሶች ያልብሱአቸውና ከእኔ ጋራ ወደዚያ ቦታ ይምጡ አለ እንዲሁም እንዳላቸው አደረጉ።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሔደ ከእርሱም ጋራ ብዙ ፈረሰኞች ሰዎች ብዙ ሕዝብም የአስቄጥስ ገዳም የከበሩ አረጋውያን አሉ ወደቊልዝም ገዳምም ደረሱ። መኰንኑም በዚያ የሚኖራውን የመለካውያን ኤጲስቆጶስ እንዲህ ብሎ አዘዘው ያንተን ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስወጣቸው በዚች ሌሊት እኔ በውስጧ አድራለሁና ያ መለካዊም መኰንኑ እንዳዘዘው አደረገ።

መነኰሳቱም እንስሶቻቸውን ከከተማ ውጭ አዘጋጅተው በሌሊት ወደዚያ ገብተው የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺርን ሥጋ ይዘው ወደ ምስር ደረሱ ከዚያም ወደ አስቄጥስ ገዳም ደረሱ የአባ መቃርስ ገዳም መነኰሳትም መስቀሎችን፣ ወንጌሎችን፣ ማዕጠንቶችንና መብራቶችን በመያዝ እየዘመሩና እያመሰገኑ ተቀበሏቸው ወደ አባት መቃርስ ሥጋም አቀረቡትና ከእርሱ ተባረኩ በላዩም ብዙ ሽቱዎችን ነሰነሱ የቊርባን ቅዳሴንም ቀደሱ የከበረ ወንጌልም በሚነበብ ጊዜ ታላቅ ድንቅ ተአምር ተገለጠ ቤተ ክርስቲያኒቱ ሁለመናዋ በሰማያዊ ብርሃን በራች። ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ በጎ መዓዛ ሸተተ ታላቅ ደስታም ሆነ በዚያም ቦታ ሰባት ቀን ኖረ።

ከዚህም በኋላ ወደ ራሱ ቤተ ክርስቲያን ተሸክመው ወሰዱት ዕብራውያንም በ #እግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እያሉ #መድኃኒታችንን እንደተቀበሉት ልጆቹ መነኰሳት ተቀበሉትና ወደ ቦታው አኖሩት ከእርሱም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ።

ከዚህም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስ በወጣ ጊዜ ወደ አባ ዮሐንስ ሐጺር ቤተ ክርስቲያን ገባ። ከእርሱም ጋር ብዙዎች ኤጲስቆጶሳትና የእስክንድርያ አገር ታላላቆች ከግብጽ አገር ሁሉ አሉ። የአባ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ የተጠቀለለበትን ሰሌን ገልጦ ከእርሱ ተባረከ መሪር ልቅሶንም አለቀሰ ያን ጊዜ ሥጋው ሲገለጥ መብረቅና ነጐድጓድ ሆነ። በቤተ ክርስቲያኑም ውስጥ ያሉት ሁሉም ደንግጠው ወደቁ ሊቀ ጳጳሳቱም ሰሌኑን መልሶ በፍጥነት ሥጋውን ጠቀለለ በሽብሸባ እየዘመሩና እያመሰገኑ እንደቀድሞው ሸፈነው።

ከዚህም በኋላ ዳግመኛ እንዲህ እያሉ ሊያመሰግኑ ጀመሩ ፈጣን ደመና ሁነህ የ #መንፈስ_ቅዱስን ዝናም የተሸከምክ ሠለስቱ ደቂቅ ወዳሉበት ወደ ባቢሎን የሔድክ በላይህ በአደረ በ #መንፈስ_ቅዱስ ኃይል ወደ እስከንድርያ አገር የተመለስክ ሁለተኛም ወደ ቊልዝም የሔድክ የጣዖታትን ቤቶች አፍርሰህ ሃይማኖትን የሰበክ በሽተኞችን የፈወስክ አጋንንትን ያስወጣህ ወደርስትህም የተመለስክ አንተ የበረከት ማደሪያ ነህና። የአባ ዮሐንስ ሐጺር የሥጋው ፍልሰት ከንጹሐን ሰማዕታት ዘመን በአምስት መቶ ሃያ ዓመት ሆነ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አትናቴዎስ_ሰማዕት

በዚህችም ቀን ኤጲስቆጶስ አትናቴዎስ በሰማዕትነት ሞተ ከእርሱም ጋር ስማቸው ገርሲሞስና ቴዎዶጦስ የሚባል ሁለት አገልጋዮች በሰማዕትነት አረፉ።

ይህንንም ቅዱስ አትናቴዎስን የእንጦኒቆስን የጭፍራ አለቃውን ልጅ እርሱ እንዳጠመቃት በንጉሥ ዘንድ ወነጀሉትና ንጉሥ አርስያኖስ ያዘው እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ታመነ ብዙ ሥቃይንም አሠቃየው።

በሃይማኖቱም ጸና እንጂ ሃይማኖቱን ባልካደ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ እንዲሁም እሊህን ሁለቱን አገልጋዮች ገርሲሞስንና ቴዎዶጦስን በግርፋትና በስቅላት ከቀጣቸው በኋላ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጠ ሦስቱም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።

አማንያን ሰዎችም መጡ ለወታደሮችም ገንዘብ ሰጥተው የቅዱሳኑን ሥጋቸውን ወሰዱ በአማሩ ልብሶችም ገንዘው በሣጥን ውስጥ አኖሩአቸው ከሥጋቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_29)
#ነሐሴ_30

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሠላሳ በዚች ቀን ከዐሥራ ስድስቱ ነቢያት አንዱ #ታላቅ_ነቢይ_ሚልክያስ ያረፈበት እና ጌታ ባሕር ውስጥ #ለሐዋርያ_እንድርያስ በሊቀ ሐመር አምሳል ተገልጦ ድንቅ ተአምር ያደረገለት ቀን ነው፣ የእናታችን #ቅድስት_ዜና_ማርያም የእረፍቷ መታሰቢያ ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ነቢዩ_ሚልክያስ

ነሐሴ ሠላሳ በዚች ቀን ከዐሥራ ስድስቱ ነቢያት አንዱ ታላቅ ነቢይ ሚልክያስ አረፈ። ይህም ነቢይ የእስራኤል ልጆች ከተሰደዱበት ከባቢሎን ሀገር በተመለሱ ጊዜ የ #እግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፋቸው ገሥጿቸዋል።

ሁለተኛም ነቋር ስለሆነ መሥዋዕት ስለ አሥራትና በኵራት ገሥጿቸዋል። በዚህ ነቢይ አንደበት #እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ተናግሯልና ርኅራኄ አድርጋችሁ ምጽዋትን መጽውቱ፣ ዐሥራቴንና በኵራቴንም አስገቡና እስቲ ፈትኑኝ እኔ ከሰማይ ዝናሙን ባላወርድላችሁ በረከትንም አስቲበቃችሁ ባልጨምርላችሁ የምድራችሁንም ፍሬ ነቀዝና መሰክ እንዳይበሉት እከለክላለሁ።

ዳግመኛም ከክብር ባለቤት #መድኃኒታችን_ክርስቶስ አስቀድሞ መጥምቁ ዮሐንስ ስለ መምጣቱ ስለ ነቢዩ ኤልያስም ተናገረ። ደግሞ ስለ አይሁድ የሥርዓተ ክህነት ፍጻሜ ተናገረ በአሕዛብም አገር ውስጥ ለ #እግዚአብሔር የሚቀበላቸውን መሥዋዕት የሚያሳርጉ ዕውነተኞች ንጹሐን ካህናት እንዳሉ ገለጠላቸው።

በበጎ ተጋድሎውም #እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ ከዚህ ዓለም በመፍለስ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ነብይ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።


✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሐዋርያው_ቅዱስ_እንድርያስ

በዚችም ቀን #ጌታችን በባሕር ውስጥ ለሐዋርያ እንድርያስ በሊቀ ሐመር አምሳል ተገልጦ ድንቅ ተአምር አደረገለት።

እንድርያስም #ጌታችንን በመርከብህ አሳፍረን ነገር ግን የምንከፍልህ የመርከብ ዋጋ የለንም አለው። በሊቀ ሐመር የተመሰለ #ጌታችንም ስለምን የላችሁም አለው እንድርያስም በከረጢታችን ወርቅን፣ ብርን እንዳንይዝ ስለአዘዘን ነው አለው። #ጌታችንም እንዲህ ከሆነ ወደ መርከቤ ወጥታችሁ ተሳፈሩ አላቸው ያንጊዜም ወደ መርከብ ወጥተው ተሳፈሩ።

ከዚህም በኋላ #ጌታችን እንድርያስንና ደቀ መዛሙርቱን ከባሕሩ ማዕበል የተነሣ መታገሥ እንድትችሉ ተነሥታችሁ እንጀራ ብሉ አለ። እንድርያስም አድንቆ እንዲህ አለው በመንግሥተ ሰማያት የሕይወት እንጀራ #እግዚአብሔር ይስጥህ። ደቀ መዛሙርቱ ግን በባሕር ላይ ጉዞ ስለአልለመዱ ከባሕሩ ማዕበል ፍርሀት የተነሣ መብላት መነጋገርም ተሳናቸው ።

#ጌታችንም እንድርያስን ደቀ መዛሙርትህን ወደ ምድር እንዲወርዱ እዘዛቸው ሲፈሩ አያቸዋለሁና ይህ ካልሆነ እንዳይፈሩ አንተ የ #ኢየሱስ ደቀ መዝሙሩ ከሆንክ ጣዕም ባለው ቃል አስተምራቸው እነሆ ከየብስ ርቀናልና አለው። #ጌታችንም መርከቡን መቅዘፍ ጀመረ እንድርያስም ማስተማርና ማጽናናት ያዘ በልቡም ጸለየ ያን ጊዜም ከባድ እንቅልፍን አንቀላፉ ስለተኙለትም እንድርያስ ደስ አለው።

እንድርያስም ወደ #ጌታችን ተመልሶ እንዲህ አለው ዐሥራ አራት ጊዜ በባሕር ላይ ጒዞ አድርጌአለሁ እንዳንተ የሚቀዝፍ አላገኘሁም። #ጌታም መልሶ እንዲህ አለው እኛስ በባሕር ላይ ስንጓዝ ሁል ጊዜ እንቸገራለን። ነገር ግን አንተ የክብር ባለቤት የ #ኢየሱስ_ክርስቶስ ደቀ መዝሙር እንደሆንክ ባሕር ስለአወቀችህ ማዕበሏን በአንተ ላይ አላነሣችም እንድርያስም በታላቅ ቃል እንዲህ ብሎ ጮኸ። የክብር ባለቤት #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመሰግንሃለሁ ከሚያከብርህ ሰው ጋር ተገናኝቼ ተነጋግሬአለሁና።

ከዚህም በኋላ #ጌታችን እንድርያስን እንዲህ አለው አንተ የ #ክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ነህና ንገረኝ። አይሁድ የ #እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ስለምን አላመኑም የሠራውን ብዙ ድንቅ ተአምርን ሰምተናልና አለው። እንድርያስም እንዲህ አለው አዎን ወንድሜ እርሱ የ #እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ገልጦልናል አንካሶችንም በትክክል እንዲሔዱ አድርጓልና፣ ደንቆሮዎችንም አሰምቷልና፣ ዲዳዎችንም አናግሮአልና፣ ለምጻሞችንም አንጽቷልና፣ ውኃውንም ወይን አድርጓልና፣ አምስት እንጀራና ሁለት ዓሣን አንሥቶ ያዘ ሕዝቡንም በመስክ ሣር ላይ እንዲቀመጡ አዘዘ ሣሩም እንጀራ እስቲለብስ ድረስ በልተው ጠገቡ የተረፈውንም በብዙ ቅርጫቶች አነሣን ይህም ሁሉ ሲሆን አላመኑም።

#ጌታ_ኢየሱስም እንዲህ አለው ይህን ያደረገ በግልጥ ነው ወይስ በሥውር። እንድርያስም እንዲህ አለው ይህንስ በግልጥ ነው ያደረገ በሥውር ያደረገውም አለ ግን የምትፈትነኝ መሰለኝ #ጌታችንም እንዲህ አለው ወንድሜ ሆይ ልቤን ደስ ስለሚላት ነውና ንገረኝ።

እንድርያስም እንዲህ አለው ልጄ ሆይ በጎ ሥራህን ሀሉ #እግዚአብሔር ይፈጽምልህ አሁንም ስማ #ጌታችን ያደረገውን ተአምር እኛ ዐሥራ ሁለታችን ሐዋርያቶቹ ከእርሱ ጋራ ስንጓዝ ከሊቃነ ካህናትና ከሕዝቡ ብዙዎች አሉ። ወደ ምኵራብም ደረስን #ጌታችንም እንዲህ አለ በሰማይ ባሉ በኪሩቤልና በሱራፌል አምሳል በምድር ላይ ሰው የሠራትን ይቺን የተቀረጸች ሥዕል ታያላችሁን።

ከዚህም በኋላ ወደሥዕሊቱ ተመልሶ ብልህ ሰው የተጠበበብሽ የሰማያውያን መልክን ያደረግሽ አንቺን እላለሁ ከቦታሽ ተነቅለሽ ውረጂ የካህናት አለቆችንም ወቀሻቸው እኔም ዕሩቅ ብእሲ ወይም #እግዚአብሔር እንደሆንኩ መስክሪ አላት። ወዲያውኑ ከቦታዋ ተነቅላ ወረደች እንደሰውም በመናገር እንዲህ አለች እናንተ የደነቆራችሁ አይሁድ የራሳችሁ መደንቆር ያልበቃችሁ ሌሎችንም ለማደንቆር የምትሹ ለድኅነታችሁ ሰው የሆነ #እግዚአብሔርን እንዴት ዕሩቅ ብእሲ ትሉታላችሁ አስቀድሞ ሰውን የፈጠረው በንፍሐት ልጅነትንም የሰጠው ይህ ነው።

አብርሃምን የተናገረው፣ ይስሐቅንም ከመታረድ ያዳነው፣ ያዕቆብንም ወደ አገሩ ያስገባው ይህ ነው ለሚፈሩት በረከትን የሚሰጥ ለማይታዘዙለት ቅጣትን የሚያዘጋጅ ይህ ነው ።

እውነት እነግራችኋላሁ እናንተ ስለምትክዱት ሕጉንና ሥርዓቱንም ትለውጣላችሁና ስለዚህ እነሆ መስዋዕታችሁ ይሻራል ምኵራቦቻችሁም በዋሕድ ወልደ #እግዚአብሔር ስም አብያተ ክርስቲያናት ይሆናሉ። ይህንንና የሚመስለውን ተናግራ ዝም አለች።

እኛም የካህናት አለቆችን መልሰን እንዲህ አልናቸው እነሆ ቅርጺቱ ሥዕል ተናግራ ወቀሰቻችሁ ታምኑ ዘንድ ይገባችኋል። የካህናት አለቆችና አይሁድም እንዲህ አሉን ይህ የሚያናግረው በሥራይ ነው አብርሃምን በወዴት አገኘው ከሞተ ዘመኑ ብዙ ነውና።

#ጌታ_ኢየሱስም ወደ ቅርጺቱ መለስ ብሎ እንዲህ አላት አብርሃምን እንዳነጋገርኩት አላመኑምና ሔደሽ እንዲህ በይው። አስቀድሞ አዳምን የፈጠረው፣ አንተንም ወዳጁ ያደረገህ፣ አንተ ልጆችህ ይስሐቅና ያዕቆብን ይዘህ ተነሥ ከመቃብርም ወጥተህ ወደዚህ ኑ የካህናት አለቆችን ትወቅሱአቸው ዘንድ እኔ የማውቃችሁና የተነጋገርኳችሁ መሆኔን አስረዷቸው። ቅርጺቱም ሥዕል ይህን ሰምታ እያየናት ሔደች ወደ አብርሃምም መቃብር ደርሳ በውጭ ቁማ ጠራቻቸው። ወዲያውኑ ከሦስቱ አርእስተ አበው ጋር ዐሥራ ሁለቱ ወጡ ከእኛ ውስጥ ወደ ማን ነው የተላክሽ አሏት። ቅርጺቱም እንዲህ ብላ መለሰች ወደ ሦስቱ የአባቶች አለቆች ነው እናንተ ግን እስከ ትንሣኤ ሙታን ድረስ ተኙ ያን ጊዜም ወደ መቃብራቸው ተመለሱ።
እሊህ ሦስቱ አባቶችም የካህናት አለቆችና እኛ ወደ አለንበት ከቅርጺቱ ሥዕል ጋር መጥተው ወቀሷቸው የ #እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ነገሩአቸው።

ከዚህም በኋላ #ጌታችን አባቶችን ወደቦታችሁ ሒዱ አላቸው ወዲያው ተመለሱ ቅርጺቱንም ወደቦታሽ ተመለሽ አላት እርሷም ወደ ቀደመው አኗኗርዋ ተመለሰች ይህንንም አይተው የካህናት አለቆች አላመኑም ሌላም ብዙ አለ ብነግርህ መወሰን አትችልም ነገር ግን ለብልህ ጥቂት ቃል ትበቃዋለች ለሰነፍ ግን ቢነግሩት በቁም ነገር ላይ አይታመንም።

ከዚህም በኋላ #ጌታችን ማነጋገሩን ገታ ራሱንም እንደሚያንቀላፋ አደረገ እንድርያስም አንቀላፋ እንድርያስንና ደቀ መዛሙርቱን እንዲሸከሙአቸውና ሊገቡበት ወደሚሹት አገር በውጭ እንዲአኖሩዋቸው መላእክትን አዘዛቸው።

ከዚህም በኋላ እንድርያስ በነቃ ጊዜ ዐይኖቹን ገለጠ የከተማውንም በር ተመለከተ በየብስም ላይ እንዳለ አውቆ ደነገጠ አደነቀም። ደቀ መዛሙርቱንም አነቃቸውና እንዲህ አላቸው #ጌታችንን በባሕር ላይ ሳለን ያላወቅነው ምን አደረገብን ሲፈትነን መልኩን ለውጦ እንደ ሰው ሁኖ ታይቶናልና።

ደቀ መዛሙርቱም እንዲህ አሉት እኛም በጌትነቱ ዙፋን ላይ ሁኖ የመላእክት ሠራዊት ሁሉ በዙሪያው ሁነው #ጌታችንን አየነው አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብንም ቅዱሳንን ሁሉ አየናቸው ንጉሥ ዳዊትም በመሰንቆ ይዘምር ነበር። እናንተንም ዐሥራ ሁለት ሐዋርያት በፊቱ ቁማችሁ ዐሥራ ሁለቱንም የመላእክት አለቆች በፊታችሁ ሌሎች መላእክት በኋላችሁ ሁነው አየናችሁ። #እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስንም መላእክትን እንዲህ ብሎ ሲያዛቸው ሰማነው የሚሉአችሁን ሁሉ ሐዋርያትን ስሟቸው።

እንድርያስም በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው ይህን ድንቅ ምሥጢር ያዩ ዘንድ ደቀ መዛሙርቱ የሚገባቸው ሆነዋልና። ከዚህም በኋላ እንድርያስ ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ እንዲህ ብሎ በታላቅ ድምጽ ጮኸ #ጌታዬ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሆይ ከእኛ ከባሮችህ ሩቅ እንዳልሆንክ አወቅሁ። ነገር ግን በመርከብ ላይ እኔ እንደማስተምረው ሰው መስለኸኝ በድፍረት ተናግሬሃለሁና #ጌታዬ ይቅር በለኝ ።

በዚያንም ጊዜ የክብር ባለቤት #መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ለእንድርያስ ዳግመኛ ተገለጠለት እንዲህም አለው። አዎን እኔ ነኝ በሊቀ ሐመር አምሳል በባሕር ውስጥ የተገለጥኩልህና መርከቡን የቀዘፍኩልህ። አትፍራ አትደንግጥ እኔ ከአንተ ጋራ እኖራለሁ ይህንንም ብሎ ወደ ሰማያት በክብር ዐረገ እንድርያስም መንገዱን ሄደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጌቶቻችን ሐዋርያት በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ጻድቋ_ቅድስት_ዜና_ማርያም

በዚህች ዕለት የእናታችን ቅድስት ዜና ማርያም የእረፍቷ መታሰቢያ ነው፡፡ ከአባቷ ከገብረ ክርስቶስ ከእናቷ አመተ ማርያም በ11መቶ ክፍለ ዘመን በቅዱስ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት በምድ ነጋሲ በጎጃም ምድር ግንቦት 30 ቀን የተወለደች ሲሆን ለአቅመ ሔዋን በደረሰች ጊዜ በንፅህ ድንግልና በምድረ ሂንፍራንስ ጣራ ገዳም አካባቢ በሚገኘው በአቡነ እንድርያስ ዋሻ ለ25ዓመት በጾም በፀሎት ምንም አይነት የላመ የጣፈጠ እህል ሳትቀምስ በቅል ውስጥ የሚገኘውን መራራ ፍሬ ከኮሶ ጋር በአንድነት ደርጣ (አዋህዳ) በመዘፍዘፍ ከ3 ቀን በኃላ በመመገብ እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ #ጌታችን_አምላካችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በቀራንዮ አደባባይ ላይ የቀመሰውን መራራ ሐሞትን በማሰብ ሙሉ ሕይወቶን እየተመገበች ታላቅ ተጋድሎዋን ፈፅማለች፡፡ ከዚህ የተነሳ ሸክላ ማርያም ተብላ ትጠራ የነበረችው ቦታ ስያሜ ተቀይሮ ደሪጣ ዜና ማርያም ዋሻ ተብሎ እስከ አሁን ድረስ በስሞ እየተጠራ ይገኛል፡፡

ከአቡነ እድርያስ ዋሻ በመቀጠል ከአዲስ አበባ ተነስተን ስንጓዝ አዲስ ዘመን ከተማ በስተቀኝ በኩል ተገንጥለን 15ኪሜ ያክል የጥርጊያ መንገድ እንደተጓዝን በስሞ የተሰየመውን ደሪጣ ጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ገዳም ላይ ቀሪ ሕይወቷን ምንም አይነት ዋሻ ባልነበረበት በከፍተኛ ተራራ ላይ እጅግ አስቸጋሪ ቀዝቃዛ አየር ባለበት ብርዱን፣ ፀሐዩን፣ ቁሩን፣ ረኃቡንና ጥሙን በመቋቋም ራቁቶን በመሆን መራራ ምግቦችን አዋህዳ በመመገብ በጾም በፀሎት በመትጋት አስቸጋሪ የሆነውን ተጋድሎዋን በመፈፀም በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ በዚህች ቀን በታላቅ ክብር አርፋለች፡፡

በዚህም ወቅት #ጌታችን_አምላካችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት #ድንግል_ማርያምና ከእልፍ አላፋት ቅዱሳ መላዕክት ጋር እንዲሁም ከሐዋርያት ፣ ከሰማዕታት ፣ ከጻድቃን ፣ ከደናግል ጋር በመሆን ከሰማይ በመውረድ በታላቅ ክብር ዕረፍቷን አክብሮላታል ታላቅ ኪዳንም ገብቶላታል፡፡

በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ ላይ ወይንም በአሁኑ ሰዓት መቃብሯ በሚገኝበት ዋሻ ቤተመቅደስ አካባቢ በተጋድሎዋ ጊዜ ራቁቷን በሆነች ሰዓት መላ ገላዋን የሸፈነላት ፀጉር በእየ ዛፎቹ ላይ እስከ አሁን ድረስ አለ ፡፡ ይህም የጸጉር አምሳያ ከገዳሙ በመውሰድ ብዙ ሰዎች በቤታቸው በመታጠን ከአስም እንዲሁም ከተለያዩ በሽታዎች እየተፈወሱና እየዳኑ ሲሆን ታላላቅ ታምራትን እያደረገ ይገኛል፡፡

በዚህ ገዳም ከሌሎች ገዳማት ለየት የሚያደርገው ታሪክ #ጌታችን_አምላካችን_መድኃኒታችንን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከሰማይ በመውረድ ራሱ የባረከው ልዩ ታሪክ ያለው ጠበል የሚገኝ ሲሆን ይህም ጠበል በቦታው ላይ ሆኖ የተጠመቀ ፣ የጠጣ ፣ አልያም በአለበት ቦታ ሆኖ የተጠቀመ እስከ አሁን ድረስ መካን የሆኑ ሰዎች በፍጥነት ልጅ የሚያገኙ ከመሆናቸው ባሻገር ከማንኛውም ከተለያዩ በሽታዎች በመፈወስ ታላላቅ ታምራትን እየሰራ ይገኛል፡፡

በ11ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቅዱስ ላሊበላ በ #ጌታችን_በአምላካችን_በመድኃኒታችን_በኢየሱስ_ክርስቶስ ትዕዛዝ መሰረት ወደዚሁ ታላቅ ስፍራ በመምጣት የጻድቋ ማረፈያ/መታሰቢያ ዋሻ ቤተ መቅደስ በመፈልፈል የሰራላት ሲሆን በመቀጠል አፄ ይስሐቅ በ14ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ይህን ገዳም በስሟ በመገደም በዚሁ ዋሻ ውስጥም የጻድቋ የቅድስት ዜና ማርያም መቃብሯ እንዲሁም የመታሰቢያዋ ፅላት የሚገኝ ከመሆኑ አንጻር በአካባቢው ያሉት ሕዝበ ክርስትያን ከካህናት ጋር በመሆን ሥርዓተ አምልኮ በመፈፀም እየተገለገሉበት ይገኛሉ፡፡

ይህ ዋሻም አስቀድሞ ሦስቱ ቅዱሳን ማለትም አቡነ እንድርያስ ዘጣራ ገዳም ፣አቡነ ተክለኃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስ፣ ጻድቋ ቅድስት ዜናማርያም ዘደሪጣ ውስጥ ለውስጥ በ #መንፈስ_ቅዱስ ገላጭነት በፀጋ #እግዚአብሔር ይገናኙበት የነበረ ሲሆን በአሁን ሰዓትም #እግዚአብሔር የመረጣቸው ቅዱሳን ይመላለሱበታል፡፡

ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም የተሰጠ ቃል ኪዳን #እግዚአብሔር አምላክ መርጦና ፈቅዶ በጻድቋ አማላጅነት ካለበት ስፍራ ተነስቶ የጻድቋ ደጃን የረገጠ ለ3 ግመል ጭነት ጤፍ ወይም የሦስት አህያ ጤፍ ያህል ነፍሳትን እምርልሻለሁ፤ ከሲዖልም እሳት ነፍሳትን አወጣልሻለሁ የሚል ቃል ኪዳን ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ተሰቶታል።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጌቶቻችን ሐዋርያት በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_30#ከገድላት_አንደበት_ግንቦት_30)
#ጳጒሜን_1

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተባረከ የጳጒሜን ወር ባተ። በዚህች ቀን ጳጒሜን አንድ #ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ የታሰረበት፣ የወንጌላዊ የቅዱስ #ዮሐንስ ረድእ #የዑቲኮስ_ሐዋርያና #ቀሲስ_አባ_ብሶይ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ

ጳጒሜን አንድ ቀን በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ወደ እሥር ቤት ገብቷል። ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦ ንጉሡ ሔሮድስ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሔሮድያዳን በማግባቱና በመሰል ክፋቶቹ ቅዱስ ዮሐንስ ይገስጸው ነበር። ቅዱስ ዮሐንስ "መምሕር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገጽ" "ፊት አይቶ የማያዳላ" ነውና ገሰጸው።

ሔሮድስ ቅዱሱን ይፈራው ያከብረውም ነበር። በኋላ ግን ፈቃደ ሥጋው ስላየለበት በተለይ ደግሞ ከሰባት ቀናት በኋላ ልደቱን ሲያከብር እንዳይረብሸው በመስጋት በዚህች ቀን በወታደሮቹ አስይዞ እሥር ቤት ውስጥ
ጥሎታል። ለሰባት ቀናት በጨለማ ውስጥ አሥሮ መስከረም 2 ቀን አስቆርጦታል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዑቲኮስ_ሐዋርያ

በዚህች ቀን የወንጌላዊ ዮሐንስ ረድእ ሐዋርያና ሰማዕት የከበረ ዑቲኮስ አረፈ ።

ይህም ቅዱስ ወንጌላዊ ዮሐንስን ሲያገለግለውና ሲታዘዘው ኖረ። ከዚያም ከሐዋርያ ጳውሎስ ጋራ ሔደ እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስም እንዲሰብክ አዘዘው በአረማውያንና በዮናናውያንም መካከል ሰበከ። የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስንም ወደማወቅ ብዙዎችን መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።

የጣዖታት ቤቶችን አፍርሶ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራ። ከከሀድያንም ብዙ መከራ ደረሰበት መታሠርና ብዙ ቀኖች ግርፋቶችን በመቀበል፤ የ #እግዚአብሔርም መልአክ ወደ እሥር ቤት ከምግብ ጋር መጥቶ ይመግበዋል።

ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጣሉት እሳቱም ከቶ አልነካውም ሁለተኛም ለአንበሶች ጣሉት እነርሱም እንደ በጎች ሆኑለት። ከዚህም በኋላ ወደቍስጥንጥንያ ሀገር ሔደ። ሲሔድም የ #እግዚአብሔር መልአክ ይመራውና ያጸናናው ነበር ተጋድሎውንም ፈጽሞ በበጎ ሽምግልና ወደ እግዚአብሔር ሔደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቀሲስ_ብሶይ_ሰማዕት

በዚችም ቀን የአባ ሖር ወንድም ቀሲስ ብሶይ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ ከአንፆኪያ አገር ክብር ካላቸው ወገኖች ውስጥ ነው ስለ ዕውቀቱና ስለ ሃይማኖቱ ጽናት ቅስና ተሾመ።

ወንድሙ አባ ሖርና እናቱ ወደ ግብጽ አገር ሔደው በሰማዕትነት ከሞቱ በኋላ እርሱም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ ሥጋቸውን ያይ ዘንድ ሔደ። ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ሰጠ ከሦስት እንጀራና ከሚመረጐዛት ከአንዲት የሰኔል በትር በቀር ምንም አልያዘም ነበር።

ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰ ጊዜ የዘመዶቹ በድን ወዳለበት ሰዎች መርተው አደረሱት የእናቱንና የወንድሙንም ሥጋ በአየ ጊዜ ከእርሳቸው ስለ መለየቱ መሪር ልቅሶን አለቀሰ። ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ ሒዶ በፊቱ ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ።

ለመኰንኑም የአባ ሖር ወንድም እንደሆነ ነገሩት መኰንኑም ታላቅ የደንጊያ ምሰሶ በሆዱ ላይ እንዲአቆሙበት አዘዘ ይህንንም በአደረጉበት ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ።

ከዚህም በኋላ ደግሞ ሥጋውን ከወንድሙና ከእናቱ ሥጋ ደግሞ ቍጥራቸው ሰማንያ ስምንት ከሆነ ከሌሎች ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአንድነት ያቃጥሉ ዘንድ መኰንኑ አዘዘ ወደ እሳት በጨመሩአቸውም ጊዜ ከቶ እሳቱ አልነካቸውም።

ምዕመናን ሰዎችም መጥተው የከበሩ የአባ ሖርንና የወንድሙ የአባ ብሶይን የእናታቸውንም ሥጋ ወሰዱ። ሀገሯ ዲብቅያ የሚባል የቅድስት ዳሞንንም ሥጋ፣ ሀገሩ በረሞን የሚባል የቅዱስ ቢማኮስንም ሥጋ፣ ጡልያ ከሚባል አገር የመጣ የውርሱኑፋን ሥጋም፣ አብስላሲ ወደሚባል አገር እስከሚያደርሷቸው በመርከብ ጫኗቸው። የስደቱ ወራት እስከሚፈጸም አክብረው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩዋቸው።

ከዚህም በኋላ አብያተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ ከእርሳቸውም ተአምራት ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኑ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእኒህ ቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጉሜን_1#ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ጳጒሜን_2

#ቅዱስ_ቲቶ_ሐዋርያ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጳጒሜን ሁለት በዚህች ቀን ሐዋርያ ጳውሎስ መልእክት የጻፈለት የከበረ ሐዋርያ ቲቶ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው።

ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም።

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የ #መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው።

ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የ #መድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ።

ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በ #ጌታችን_ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት #ጌታ_ኢየሱስ_ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው።

#ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። #ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ።

የከበረ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው #እግዚአብሔር ሔደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጒሜን_2)
ጽላተ ማርያምን ይዘው በቅዱሳን መላእክት ታጥራ ወደምትገኘው ምድረ ቀብጽያ መጥተው መቶ ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ።

አቡነ አሞፅ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን የእመቤታችን መከራ የሚተርከውን ድንቅ ድርሰት ሙሉውን ክፍል በብራና ላይ በሥዕል ገልጸው በክብር አስቀምጠውታል፡፡ ከሰማይ የወረደላቸው የወርቅ መስቀላቸውም በገዳሙ ይገኛል፡፡

አቡነ አሞፅ በ1592 ግንቦት 26 አርብ ቀን ሲያርፉ ጌታችን ከድንግል እናቱ ጋር ተገልጾላቸው ከላይ ያየናቸውን አስደናቂ ቃልኪዳኖች ከሰጣቸው በኋላ ነፍሳቸውን እመቤታችን አቅፋ አሳረገቻቸው፡፡ ዐፅማቸው ያረፈበትን መካነ መቃብር ታላላቅ ዘንዶዎች ይጠብቁታል፡፡ ጠበላቸውም የፈለቀው ከመቃብራቸው ሥር ነው፡፡ ቦታው በስውራን ስለሚገለገል የከበሮ ድምፅ የሚሰማ ሲሆን የእጣንም ሽታ ይሸታል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን!።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በመልአኩና በቅዱሳኑ አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጉሜን_3#ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ እና #ከገድላት_አንደበት)