ቅዱሳን ኅሩያን የዲ°ን ዮርዳኖስ ትምህርቶች
4.96K subscribers
919 photos
5 videos
33 files
239 links
የዲ.ን ሄኖክ ሀይሌን ስብከት በድምጽ እንለቃለን
ለአስተያየት @EMNE_TSYON @unitte_bot
በቴሌግራም ከፈለጉን @henokhailee
በfacebook ከፈለጉን https://www.facebook.com/tewahidosewhone/
በyoutube ከፈለጉን https://youtube.com/channel/UCq2ueVG6O3ZuKHJ485y7hfg
Download Telegram
=>+"+ እንኩዋን ለአጋእዝተ ዓለም #ሥላሴ እና ለቅዱሳን
አበው #አብርሃም: #አባ_ሲኖዳ እና #አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋሥጫ
ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+

+"+ #ሥሉስ_ቅዱስ +"+

=>በአንድነቱ ምንታዌ (ሁለትነት): በሦስትነቱ ርባዔ (አራትነት)
የሌለበት የዘለዓለም አምላክ: የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ
#እግዚአብሔር ነው:: #አብ : #ወልድ : #መንፈስ_ቅዱስ
በስም: በአካል: በግብር ሦስትነት: በባሕርይ: በሕልውናና
በፈቃድ አንድነት የጸኑ ናቸው:: በዚህ ጊዜ ተገኙ: በዚህ ጊዜ
ያልፋሉ አይባሉም:: መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸውና::

+ርሕሩሐን ናቸውና በእናት ሥርዓት " #ቅድስት_ሥላሴ "
እንላቸዋለን:: የሚጠላቸው (የማያምንባቸውን) አይጠሉም::
የሚወዳቸውን ግን እጽፍ ድርብ ይወዱታል:: በቤቱም መጥተው
ያድራሉ::

+ከፍጥረታት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የአብርሃምን ያህል
በሥላሴ ዘንድ የተወደደ ፍጡር የለም:: አባታችን
#ቅዱስ_አብርሃም የደግነት ሁሉ አባት ነውና በኬብሮን
በመምሬ ዛፍ ሥር ሥላሴን ተቀብሎ አስተናግዷል:: ሥላሴ
አኀዜ ዓለም (ዓለምን በእጁ የያዘ) ነው:: ነገር ግን በፍቅር
ለሚሻው በፍቅር ይመጣል::

+አባታችን አብርሃም በ99 ዓመቱ: እናታችን ሣራ በ89 ዓመቷ
ሥላሴን በድንኩዋናቸው አስተናገዱ:: አብርሃም እግራቸውን
አጠበ:: (ወይ መታደል!) በጀርባውም አዘላቸው:: (ድንቅ አባት!)
ምሳቸውንም አቀረበላቸው:: እንደሚበሉ ሆኑለት:: በዚያው
ዕለትም የይስሐቅን መወለድ አበሠሩት:: #ቅድስት_ሣራ ሳቀች::
እንደ ዘንድሮ ወገኖቻችን የማሾፍ አይደለም:: ደስታና ጉጉት
የፈጠረው እንጂ:: ሥላሴ "ምንት አስሐቃ ለሣራ በባሕቲታ"
ብለው ነበርና በዚህም ምክንያት ነው " #ይስሐቅ" የተባለው::

+ሥላሴን ያስተናገደች ድንኩዋን (ሐይመት) የድንግል
እመቤታችን ማርያም ምሳሌ ናት:: በድንግል ላይ #አብ
ለአጽንኦ: #መንፈስ_ቅዱስ ለአንጽሖ: #ወልድ በተለየ አካሉ
ለሥጋዌ በእርሷ ላይ አርፈዋል / አድረዋልና::

+"+ #ታላቁ_አባ_ሲኖዳ +"+

=>የባሕታውን ሁሉ አለቃቸው ታላቁ ቅዱስ ሲኖዳ:-
¤በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የተወለደ
¤በእናቱ ማሕጸን ሳለ መላእክት በሰይፈ እሳት ይጠብቁት የነበረ
¤የታላቅነት ትንቢት የተነገረለት
¤ገና ሳይወለድ ሥውራን አበው የሰገዱለት
¤በሕጻን ሰውነቱ ጾምና ጸሎትን የጀመረ
¤የልጅነት ቁርስና ምሳውን ለነዳያን ያካፍል የነበረ
¤በ9 ዓመቱ ወደ በርሃ የመነነ
¤የአባ አብጐል ደቀ መዝሙር የሆነ አባት ነው::

+ሲመነኩስም በእግዚአብሔር ትእዛዝ #የሠለስቱ_ደቂቅ
አስኬማ: #የኤልያስ ቆብዕ እና የመጥምቁ #ዮሐንስ ቅናትን
(መታጠቂያ) ከያሉበት መላእክት አምጥተውለት የመነኮሰ
¤ዓለምን በሙሉ በጸሎቱ ይጠብቅ የነበረ
¤የግብፅን በርሃ በብርሃን የሞላ
¤በርካታ ድርሰቶችን የደረሰ
¤ያለ ማቇረጥ በየቀኑ ከ100 ዓመታት በላይ ከጌታችን ክርስቶስ
ጋር የተነጋገረ
¤ደመናትን ተጭኖ ይሔድ የነበረና
¤ያለ ዕረፍት ለ111 ዓመታት ከ2 ወራት ፈጣሪውን ያገለገለ
አባት ነው::

+በዚህም ምክንያት አንድ ቀን ገዳማውያን ሁሉ እየሰሙ
እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ መጣ:: "ሲኖዳ ተሠይመ
#አርሲመትሪዳ " (ሲኖዳ አርሲመትሪዳ ሆኗል:: ማለትም
ለባሕታውያን ሁሉ አለቃ ሁኖ ተመርጧል ማለት ነው:: )

+ቅዱሱ የጌታችንን እግር እያጠበም ይጠጣ ነበር::
+በዚህች ዕለት በ120 ዓመቱ ጌታችን ወርዶ ሲያሳርገው
#አቡነ_ኪሮስ "ታላቅ ምሰሶ (ታላቅ ዛፍ) ወደቀ" ብለው
አልቅሰዋል:: #ሲኖዳ ማለት "ደግ ሰው" ማለት ነው::

+"+ #አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ ( #GIYORGIS_OF_SEGLA )
+"+

=>ታላቁ ኢትዮዽያዊ ሊቅና ጻድቅ የተወለደው ወሎ #ጋስጫ
ውስጥ በ1358 ዓ/ም ነው:: ከልጅነቱ ትምሕርት አልገባሕ
ቢለውም በልቡናው ግን ቅን እና ታዛዥ ነበር:: መምሕሩ
"ትምሕርት አይገባውምና ውሰዱት" ቢላቸው "የእግዚአብሔር
ነውና ያገልግላችሁ" ብለው መለሱት:: መገፋቱን የተመለከተ
#አባ_ጊዮርጊስ #እመቤታታችንን ከልቡ ይወዳት ነበረና
ይማጸናት ገባ::

+ቀን ቀን ገዳሙን ሲረዳ: እሕል ሲፈጭና ሲከካ: ላቡንም
ሲያፈስ ውሎ ሌሊት ደግሞ ሲጸልይ ያነጋ ነበር:: ድንግል
እመቤታችን ጸሎቱን ሰምታለችና #ቅዱስ_ዑራኤልን አስከትላ
መጣችለት:: በንጹሐት እጆቿ ባርካው ምሥጢርንም ነገረችው::
"ወነገረቶ ሐምስተ ቃላተ" እንዲል:: ጽዋዐ ልቡናን አጠጥታው
ተሠወረችው::

+ከዚህች ሰዓት ጀምሮ አባ ጊዮርጊስ ፍጹም ተለወጠ:: በጽድቁ
ላይ የሊቅነትን ካባ ደረበ:: ቅዱሳት መጻሕፍትን ይተነትናቸው:
መናፍቃንንም ምላሽ ያሳጣቸው ገባ:: የተረጐማቸውና
ያተታቸውን ሳይጨምር 41 ድርሰቶችን ደረሰ:: (መጽሐፈ
ሰዓታት: መጽሐፈ ምሥጢር: አርጋኖን: ኆኅተ ብርሃን: ውዳሴ
መስቀል: ወዘተ . . . የእርሱ ድርሰቶች ነበሩ)

+ስለ ሃይማኖትም ጠበቃ ነበር:: ስለ ቅድስናውና ውለታው የኢ/
ኦ/ተ/ቤ እንዲህ ትጠራዋለች:-
1. #ሊቀ_ሊቃውንት
2. #በላዔ_መጻሕፍት
3. #ዓምደ_ሃይማኖት
4. #ዳግማዊ_ቄርሎስ
5. #ጠቢብ_ወማዕምር

+ጻድቁ ሊቅ በተወለደ በ60 ዓመቱ በ1418 ዓ/ም በዚህች ቀን
ዐርፏል:: አባ ጊዮርጊስ የተወለደውም ያረፈውም ሐምሌ 7 ቀን
ነው::

=>የሥላሴ ቸርነት: የአብርሃም ደግነት: የአበው አባ ጊዮርጊስና
አባ ሲኖዳ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን::

=>ሐምሌ 7 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱሳን አብርሃምና ሣራ (ሥላሴን ያስተናገዱ)
2.ብሥራተ ልደተ ይስሐቅ
3.ታላቁ አባ ሲኖዳ (የባሕታውያን ሁሉ አለቃ)
4.አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ (ሊቀ ሊቃውንት: ኢትዮዽያዊ
የሃይማኖት ምሰሶ)
5.ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ (ምጥው ለአንበሳ)
6.አባ መቃቢስ
7.አባ አግራጥስ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
2.አባ ባውላ ገዳማዊ
3.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ

=>+"+ እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ:-
'በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ:: እያበዛሁም አበዛሃለሁ'
ብሎ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ በራሱ ማለ::
እንዲሁም እርሱ ከታገሠ በሁዋላ ተስፋውን አገኘ:: +"+ (ዕብ.
6:13)
=>+"+ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ: የእግዚአብሔርም ፍቅር:
የመንፈስ ቅዱስም ሕብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን:: አሜን:: +"+
(ቆሮ. 13:14)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

https://t.me/zikirekdusn
ሥዕልም አፍ አውጥቶ ‹‹በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?›› ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ ‹‹እንዴት አድርጌ ልሳልህ?›› ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም ‹‹ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ›› አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የ #ጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡ በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ #ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር ‹‹ፍቁረ እግዚእ›› ተባለ፡፡ የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል ‹‹ዮሐንስ ወልደ ዘብድዮስ›› ተባለ፡፡ ለ #ጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የ #ጌታችንን አምላክነት በመግለጡ ‹‹ወልደ ነጎድጓድ›› ተብሏል፡፡ ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ ‹‹ነባቤ መነኮት ወይም ታኦሎጎስ›› ተብሏል፡፡ ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ ‹‹አቡቀለምሲስ›› ተባለ፣ ይህም በግሪክኛ ባለራእይ ማለት ነው፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ ‹‹ቁዱረ ገጽ›› ተብሏል፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡  (ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርሃ ጥር፣ ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ፣ የቅዱሳን ታሪክ-30)

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በከበረ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኢያሱ_ሲራክ_ነቢይና_ጠቢብ

በዚህች ቀን ዕውቀትን ከልቡ ያፈለቀ የኢየሩሳሌሙ ሰው የአልዓዛር ልጅ ኢያሱ ሢራክ አረፈ። እርሱም በጥንተ ትንቢቱ የባሕር አሸዋን የዝናም ጠብታን የዘመንን ቁጥር ማን ቈጠረ አለ።

#አብ ጋራ ስለ አለው አንድነት የጥበብ አኗኗር ከዓለም መፈጠር በፊት ነው ለጥበብ መገኛዋ ለማን ተገለጠ የጥበብ ምክሯንስ ማን አወቀ በ #እግዚአብሔር ዙፋን ላይ የምትቀመጥ እጅግ የምታስፈራ ናት አለ።

ሁለተኛም እኔ ከልዑል አፍ ወጥቼ ምድርን አንደ ጉም ሸፍንኋት በሰማያትም እኖራለሁ ዙፋኔንም በደመና ምሰሶ ላይ ዘረጋሁ ብቻዬን በሰማይ ዳርቻ ዞርኩ በውቅያኖስም ጥልቅ ውስጥ ማረፊያ እየፈለግሁ በባሕሩ ውኃ ላይ ሁሉ ተመላለስኩ አለች አለ።

ስለ ወልደ #እግዚአብሔርም ሰው መሆን እንዲህ አለ #እግዚአብሔር በያዕቆብ ዘንድ እደሪ በእስራኤልም ዘንድ ተዋረሺ አለኝ አለች። ደግሞ ስለ #መድኃኒታችን ሞትና ስለ አይሁድ መጥፋት በወጥመዱ ይጠመዳሉ የመሞቻቸው ጊዜም ሳይደርስ ይሠጥማሉ አለ። ስለ ንስሓና ከንስሓ በኋላ ወደ ኃጢአት ስለ መመለስ እንዲህ አለ ከታጠቡ በኋላ ቆሻሻን መዳሰስ ምን ይጠቅማል።

ደግሞ ስለ ቤተክርስቲያን መታነፅና ስለ ሕዝብ እንዲህ አለ። አቤቱ በስምህ የተጠሩና በበረከት ያባዛኃቸውን ወገኖችህን ይቅር በል መመስገኛህና ማደሪያህ የሆነች ሀገርህ ኢየሩሳሌምንም ይቅር በል። የቃልህንም በረከት በጽዮንና በልጆቿ ላይ ምላ።

ስለሹማምንትና ስለ ሰባቱ መዐርጋት ሲናገር እንዲህ አለ ሰባቱን ኃይሎች የተቀበለች የሰው ሰውነቱ ጉበኛ ናት። ከዚህም ሁሉ ጋር መንገድህን ያቀናልህ ዘንድ ወደ ልዑል #እግዚአብሔር ጸልይ። ስለ ጻድቃንም እንዲህ አለ የጻድቃን ልጆች በዱር ጠል የዱር አበባ እንዲ አብብ እንዲሁ ብቀሉ አብቡም እንደ ሊባኖስም መዓዛ መዓዛችሁ እንዲሁ የጣፈጠ ይሁን።

ዳግመኛም የ #እግዚአብሔርን ሥራ ሲያስብ እንዲህ አለ የሰማይን ንጽሕናውንና ጽናቱን ብርሃኑንም ያሳይ ዘንድ በሰማይ ገጽ ላይ ፀሐይን ማውጣቱን በቀትርም ጊዜ አገሩን ማቃጠሉን አስቦ። እንደ ምድጃ እሳት የሚነድ ላቦቱን ማን ይቃወመዋል የፀሐይ ዋዕይ ሦስተኛውም ተራሮችን ያቃጥላቸዋል ከእርሱም የእሳት ወላፈን ይወጣል አለ።

ጨረቃም ለዓለም ምልክቱ ነው በእርሱም የዘመናት የበዓላት ምልክት ይታወቃል። ስለ ከዋክብትም የሰማይ ጌጦቿ የከዋክብት ብርሃናቸው ነው በ #እግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ እንዲሁ ያበራሉና በሥርዓታቸውም ጸንተው ከልካቸውም ሳይፋለሱ ሳይሳሳቱ ጸንተው ይኖራሉና አለ።

ስለ ቀስተ ደመናም ተናገረ ቀስቱን አየሁ ፈጣሪውንም አከበረ ብርሃኑ መልካም ነውና የልዑል ሥልጣንም ያዘጋጀዋል። ስለ በረድና መብረቅም ተናገረ ስለ እርሱ ትእዛዝም በረድ ይዘንማል በቃሉም መብረቅ ይፈጥናል ደመናትም እንደ አዕዋፍ ይበራሉ ነፋስም በእርሱ ፈቃድ ይነፍሳል የነጐድጓድ ድምፅና ብልጭልጭታው ምድርን ያስፈራታል ዐውሎውና ውርጩ ነፍስን ያስጨንቃታል።

ሰማይን እንደ ብረት ልብስ የሚሸፍነው እንደ ስለታም የብርጭቆ ስባሪ ይብለጨለጫል አለ። ስለ ዝናምም ተናገረ ዝናም የወረደ እንደሆነ ምድርን ድስ ያሰኛታል በትእዛዙም ባሕር ይደርቃል አለ። አባቶችንም በተሰጣቸው ሀብት ሲያመሰግናቸው ኄኖክ #እግዚአብሔርን ደስ እንዳሰኘው። ኖኅም ጻድቅ ሁኖ እንደተገኘ።

አብርሃም ታማኝ እንደሆነ ይስሐቅም ለሰው ሁሉ የሚጠቅም በረከት እንደተሰጠው ለያዕቆብም በቸርነቱ እንደ ተገለጠለት ዐሥራ ሁለቱንም ነገድ እንደወለዳቸው በሰውና በ #እግዚአብሔርም ዘንድ እንደ ተወደዱ። ሙሴንም ስም አጠራሩ የከበረ የምላእክትም ብርሃን መልኩና ስም አጠራሩ የሆነ አለ። ወንድሙ አሮንንም የዘላለም ሕግን እንደ ሠራለት በልብሰ ተክህኖና በወርቅ አክሊል እንዳስደነቀው አለ። ሹመቱ ሦስተኛ የሚሆን የአልዓዛር ልጅ ፊንሐስንም ወደሰ።

የነዌ ልጅ ኢያሱን ለእስራኤል ልጆች የርስታቸውን ምድር እንዳወረሳቸው እጁንም በአነሣ ጊዜ እንደተመሰገነ። ሳሙኤልንም በ #እግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ እንደሆነ ናታንንም በዳዊት ዘመን ትንቢት እንደተናገረ። ዳዊትንም ታናሽ ሁኖ ሳለ አርበኛውን ጎልያድን እንደገደለው አምስግኖታል ሰሎሞንንም በሰላም ወራት እንደነገሠ።

ኤልያስንም ሙት እንዳስነሣ እሳትንም ከሰማይ እንዳወረደ ራሱም በእሳት ሠረገላና በእሳት ፈረሶች እንደዐረገ። ኤልሳዕንም በዘመኑ ጠላቶች እንዳስደነገጡት ሁለት ሙታኖችንም እንዳስነሣ አንዱን በሕይወት ሳለ አንዱን ከሞተ በኋላ።

ሕዝቅያስንም አገሩን አጽንቶ እንደ ጠበቀ የፋርስንም ሠራዊት በጸሎቱ አጥፍቶ ስለ ሀገራቸው ጽዮን የሚያለቅሱትን ደስ እንዳሰኛቸው ርኵሰትንና ኃጢአትንም እንደ አስወገደ ኢዮስያስንም የኢዮስያስ ስም አጠራሩ መልካም ነው እንዳለው።

ኤርምያስንም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እንዳከበረው። ሕዝቅኤልም የእግዚአብሔርን ጌትነቱን እንዳየ። ዘሩባቤልንም በቀኝ እጅ እንዳለ ኀቲም ቀለበት ነው እንዳለው።

ዐሥራ ሁለቱ ነቢያትንም በየቦታቸው ዐፅማቸው እንደሚለመልም። ሆሴዕና ነህምያንም የወደቀች ቅጽርን አንሥተው ጠቃሚ ሥራ እንደሠሩ። ዮሴፍንም እርሱን የመሰለ ደግ ሰው እንዳልተወለደ። ኖኅና ሴምንም ክብራቸው ከሰው ሁሉ እንደሚበልጥ። አዳምንም በፍጥረት ሁሉ ላይ ንጉሥ እንደ ሆነ።

ስምዖንን በዘመኑ ቤተ መቅደስ እንደታነፀ በሕዝቡ ከምርኮ መመለስም እንደ ተመሰገነ በመጽሐፉ መጨረሻም። በሁሉ ቦታ ታላላቅ ሥራ የሚሠራና ዕድሜያችንን የሚያስረዝም #እግዚአብሔር አምላክን አመስግኑት አለ። ይህንንም ተናግሮ በፍቅር አንድነት አረፈ።

#ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሐምሌ_20

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ሃያ በዚህች ቀን #እመቤታችን_ድንግል_ማርያም ከተወለደች በኋላ በሰማንያ ቀን ከርግብ ገላግልቶች ጋራ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ነው፣ ታላቅና ክቡር የሆነው የሠራዊት አለቃ #ቅዱስ_ቴዎድሮስ በሰማዕትነት ሞተ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#በዓታ_ለእግዝእትነ_ማርያም

ሐምሌ ሃያ በዚህች ቀን እመቤታችን #ድንግል_ማርያም ከተወለደች በኋላ በሰማንያ ቀን ከርግብ ገላግልቶች ጋራ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ነው፣

ለስም አጠራሯ ክብር ይሁንና እመ ብርሃን #ድንግል_ማርያም በዚህች ቀን ወደ ቤተ መቅደስ ገብታለች:: በዓሉ ከሰላሳ ሦስቱ የእመቤታችን በዓላት እንደ አንዱ አይቆጠርም:: ምክንያቱም ቅዱሳን ሊቃውንት በዓታ ከበዓታ ጋር ይስማማል ብለው የታኅሣሥ ሦስትን በዓል ከሰላሳ ሦስቱ ደምረውታል::

#እመቤታችን ወደ ቤተ መቅደስ የገባችው ሁለት ጊዜ ሲሆን:-

1.ዛሬ የምናከብረውና በተወለደች በሰማንያ ቀኗ የገባችበት ነው:: (ከግንቦት 1 ጀምረን እናስላው 80 ቀን ይመጣል::)

ኦሪት እንዳዘዘው ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና ንጽሕት ሕፃን #ድንግል_ማርያምን ታቅፈው የርግብ ልጆች (ግልገሎች) ዋኖስም ይዘው ወደ ቤተ መቅደስ ሒደዋል::

ካህናቱ ዘካርያስና ስምዖን ወጥተው በደስታ ተቀብለዋቸዋል:: እመቤታችን ለወላጆቿ ማኅጸን የከፈተች በኩር ናትና በእግዚአብሔር ፊት አቅርበዋታል::

2.ከሦስት ዓመታት በኋላ እንደ ስዕለታቸው ወደ ቤተ መቅደስ ወስደው #ለእግዚአብሔር ሰጥተዋት ተመልሰዋል::

#እግዚአብሔር ዛሬ ያልቃል ነገ ይደቃል የማይባለውን የድንግል እናቱን ፍቅር አብዝቶ ያድለን:: በረከቷም በእኛ ላይ ጸንቶ ይኑር::

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቴዎድሮስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቅና ክቡር የሆነው የሠራዊት አለቃ ቅዱስ ቴዎድሮስ በሰማዕትነት ሞተ። የዚህ ቅዱስ አባት ስሙ ዮሐንስ ይባል ነበር። እርሱም ከላይኛው ግብጽ ሰጥብ ከምትባል መንደር ነበር። ወደ አንጾኪያ ከተማም ከሠራዊቱ ጋራ ወሰዱትና በዚያ ኖረ ከዚያች ከተማ መኳንንቶችም ያንዱን ልጅ አገባ እርሷም ጣዖትን ታመልክ ነበር። ባሏ ዮሐንስ የሚያመልከውን ግን አታውቅም ነበር።

ከዚህም በኋላ ይህን ቅዱስ ቴዎድሮስን በወለዱት ጊዜ እናቱ ወደ ጣዖቷ አቅርባ አምልኮትዋን ልታስተምረው ፈለገች አባቱ ግን አስተወው ስለዚህም ተቆጥታ ባሏ ዮሐንስን አባረረችው ሕፃኑ ቴዎድሮስም በእናቱ ዘንድ ቀረ።

አባቱ ዮሐንስም ልጁ ቴዎድሮስን ወደ እውነተኛ መንገድ ይመራው ዘንድ ወደ #እግዚአብሔር ይጸልይና ይማልድ ነበር። ሕፃኑ ቴዎድሮስም በአደገ ጊዜ ጥበብን ተማረ ጌታችንም ልቡን ብሩህ አደረገለት ስሙ አውላኪስ ወደሚባል ኤጲስቆጶስም ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። እናቱም ታላቅ ኅዘንን አዘነች።

ከዚህም በኋላ ስለ አባቱ በሕይወት እንዳለ ወይም እንደሌለ ጠየቀ ከአገልጋዮቹም አንዱ የአባቱን ሥራ በሥውር ነገረው። ቅዱስ ቴዎድሮስም ጐለመሰ እጅግም ብርቱ ሆነ ንጉሡም የሠራዊት አለቃ አድርጎ ሾመው።

የፋርስ ሰዎችንም ሊወጋቸው በወጣ ጊዜ ይህ ቅዱስ ቴዎድሮስ በረታ የፋርስ ንጉሥንም ልጅ ይዞ ማረከው ከእርሱም ጋር ምሥራቃዊው ቴዎድሮስ ነበር የፋርስንም ሠራዊት አሳደዱአቸው።

ከጥቂት ወራቶች በኋላም የፋርስና የበርበር ስዎች በሮማውያን ላይ ተነሡ። ብዙ ከተሞችንም አጠፉ ዲዮቅልጥያኖስም በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ ቴዎድሮስንም ጠርቶ ምን እናድርግ ሠራዊትህን ሁሉ የጦር መሣሪያህንም ሁሉ ይዘህ ወደ ሰልፍ ውጣ አለው።

ቅዱስ ቴዎድሮስም እንዲህ ብሎ መለሰለት አንተ የጦር መሣሪያህን ወስደህ ለአሽከሮችህ ስጣቸው እኔ ክብር ይግባውና በፈጣሪዬ #ኢየሱስ_ክርስቶስ ርዳታ እተማመናለሁና የጦር መሣሪያ አልሻም እኔም ብቻዬን ወደ ጦርነቱ እሔዳለሁ ከወታደሮችም አንድ እንኳ ከእኔ ጋራ አልወስድም። በእጄ ውስጥ ያለ ይህ ጦር የተቀመጥኩበትም ፈረስ ይበቃኛል ከእኔ ጋራ የሚወጣ ፈጣሪዬ እርሱ ይረዳኛልና። ንጉሡም እነሆ ጠላቶቻችን ወደእኛ ቀርበዋልና የወደድከውን አድርግ አለው።

በማግሥቱም ቅዱስ ቴዎድሮስ ወደ ሰልፍ ወጣ ንጉሡም የበርበርን ሰዎች ትወጋቸው ዘንድ ምን ኃይል አለህ እነርሱ ብዙ ወገኖች ናቸውና አለው። ቅዱሱም ለንጉሡ እንዲህ ብሎ መለሰለት አንተ ከሠራዊትህ ጋራ በዚህ ቁም እኔም ወደ እነርሱ ብቻዬን እሔዳለሁ በነርሱም ላይ የሚደርሰውን ታያለህ። እኔ በ #እግዚአብሔር ኃይል እንደማጠፋቸው አውቃለሁና። ከእነርሱም አንዱ እንኳ ወደቤቱ አይመለስም። ንጉሡም አደነቀ ከእርሱ ጋር ያሉትም አደነቁ።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ቴዎድሮስ ወደ ጦርነቱ ብቻውን ሔደ ንጉሡንም ከእርሱ ሩቅ በሆነ ቦታ ተወው። ወደ በርበር ሰዎችም ደርሶ ትዋጋላችሁን ወይስ በሰላም ወደ አገራችሁ ትመለሳላችሁ አላቸው። እነርሱም ከአንተ በቀር ለሰልፍ የመጣ አናይምና ከማን ጋር እንዋጋለን አሉት እርሱም ማንም ከእኔ ጋር እንዲመጣ አልሻም። እኔ ብቻዬን በ #ፈጣሪዬ ኃይል አጠፋችኋለሁ አላቸው።

ምናልባት ውሻ ልታባርር መጥተህ ይሆናል ከፈቀድህ ግን ወደ አንተ ይመጣ ዘንድ ከእኛ ውስጥ አንዱን ምረጥና ሁለታችሁ ተጋጠሙ አሉት።

ያን ጊዜ ቅዱስ ቴዎድሮስ ከፈረሱ ላይ ወረደና ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ እንዲህ እያለ ጸለየ ጣዖታትን እስከ አጠፋቸውና የባቢሎንን ከተማ ዘንዶ እስከ ገደለው ድረስ ነቢዩ ዳንኤልን ያጸናኸው ጌታዬ አምላኬ ሆይ እንዲሁም ዛሬ ከእኔ ጋራ ሁን በረድኤትህም አጽናኝ #አብ_ወልድ_መንፈስ_ቅዱስ ሆይ ምስጋና ይገባሀል ለዘላለሙ አሜን።

ጸሎቱንም በፈጸመ ጊዜ ጦሩን አንሥቶ በላዩ በመስቀል ምልክት አማተበ በፈረሱ ላይም ተቀምጦ በበርበር ሰዎች ላይ እንዲህ እያለ ጮኸ እንዋጋ ዘንድ ወደኔ ኑ ክብር ይግባውና ለ #እግዚአብሔር_ኢየሱስ_ክርስቶስ እኔ ባሪያው ነኝ እንዲህም እያለ በመካከላቸው ገብቶ የበርበርን ሰዎች አጠፋቸው ከእነርሱም ፈረሰኛንም ሆነ እግረኛን ምንም አላስቀረም የመኳንንቶቻቸውንም ቸብቸቦ ቆርጦ ወደ ንጉሡ አቀረበ። ንጉሡም ተቀበለው ሠራዊቱም ሁሉ ሰገዱለት። የአንጾኪያም ከተማ ሰዎች ሁሉም ወጥተው የበርበርን አገር ማረኩ።

አውኪስጦስ በሚባል አገርም ሰዎች የሚያመልኩት ታላቅ ዘንዶ ነበረ ይበላቸውም ዘንድ በየዕለቱ ሁለት ሁለት ሰዎችን ይሰጡት ነበር ሁለት ልጆችም ያሏት አንዲት ክርስቲያናዊት መበለት ነበረች። እንዲበላቸውም ልጆችዋን ወሰደው ለዘንዶው አቀረቧቸው።

በዚያን ጊዜም ቅዱስ ቴዎድሮስ ወደዚያ አገር ደረሰ ያች መበለትም በፊቱ ቆመች ልጆቿን ወስደው እንዲበላቸው ለዘንዶው እንዳቀረቧቸው በእርሷ ላይ የሆነውን ሁሉ አልቅሳ ነገረችው።

ክርስቲያን እንደሆነችም ባወቀ ጊዜ በልቡ ይችን ሴት በድለዋታል #እግዚአብሔርም ይበቀልላታል አለ። ወዲያውኑም ከፈረሱ ወረደና ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ጸለየ። ከዚህም በኋላ ወደ ዘንዶው ቀረበ የከተማው ሰዎችም ሁሉ ወደርሱ ይመለከቱ ነበር። በጦሩም ወግቶ ያንን ዘንዶ ገደለው። ርዝመቱም ሃያ አራት ክንድ ሆነ የመበለቷንም ልጆች አዳናቸው።

ከዚህም በኋላ አባቱን ይፈልገው ዘንድ ወደ ላይኛው ግብጽ ሔደ አባቱንም አገኘው አባቱም ልጁ እንደሆነ በምልክቶቹ አወቀው ቅዱሱም አባቱ እስከ አረፈ ድረስ በዚያ ኖረ።

ከዚህም በኋላ ወደ አንጾኪያ ከተማ ተመለሰ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስንም ክብር ይግባውና #ክርስቶስን እንደካደና ጣዖትን እንደአመለከ ክርስቲያኖችንም ሲአሠቃያቸው አገኘው።
#ሐምሌ_23

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ሃያ ሦስት በዚች ቀን #ቅድስት_መሪና ሰማዕት ሆነች፣ #ቅዱስ_ለንጊኖስ ሰማዕት ሆነ፣ የመናገሻ ገነተ ጽጌ #ቅዱስ_ጊዮርጊስ_ቤተ_ክርስቲያን (አራዳ ጊዮርጊስ) #ቅዳሴ_ቤቱ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_መሪና

ሐምሌ ሃያ ሦስት በዚች ቀን ቅድስት መሪና ሰማዕት ሆነች። የዚችም ቅድስት የአባቷ ስም ዳኬዎስ ነበር እርሱም በአንጾኪያ ሀገር ለጣዖታት ካህናት አለቃ ነበር ያን ጊዜ ንጉሡም ከሀዲው ዳኬዎስ ነበር።

አምስት ዓመትም በሆናት ጊዜ እናቷ ሞተች አባቷም ከከተማ ውጭ ለምትኖር ሞግዚት ሰጣት እርሷም ክርስቲያናዊት ነበረች የ #ክርስቶስ የሆነ የሃይማኖት ትምህርትን ሁሉ አስተማረቻት። ዐሥራ አምስት ዓመትም በሆናት ጊዜ አባቷ ሞተ።

ከዚህም በኋላ ሰዎች የሰማዕታትን ተጋድሏቸውንና መከራቸውን ሲናገሩ ሰምታ የ #ጌታ_ክርስቶስ ፍቅር በልቧ አደረ በሰማዕትነት መሞትንም ፈልጋ ሔደች።

በዚያን ጊዜም ከሀዲ መኰንን ወደዚያች አገር ደረሰ እርሷንም አይቶ ወደርሱ አስመጣትና ከወዴት ነሽ አላት #ክብር_ይግባውና_ከጌታ_ኢየሱስ ሰዎች ወገን ነኝ ስሜም መሪና ነው አለችው። ደም ግባቷንና ላሕይዋንም አይቶ መታገሥ ተሳነው እሺ ትለው ዘንድ በብዙ ነገር አባበላት። እርሷ ግን ረገመችው የረከሱ አማልክቶቹንም ረገመች።

ያን ጊዜም በብረት ዘንጎች ይደበድቧት ዘንድ ደሟ እንደ ውኃ እስኪፈስ ሕዋሳቷን ይቆራርጡ ዘንድ አዘዘ። ያን ጊዜም ወደ ጌታ #እግዚአብሔር ጸለየች የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤልም መጥቶ አዳናት። ሁለተኛም ወደ ወህኒ ቤት ያስገቧት ዘንድ አዘዘ #ጌታችንም ወደ ሰማይ አውጥቶ የቅዱሳን ሰማዕታትንና የጻድቃንን ማደሪያዎች አሳይቶ ወደ ቦታዋ መለሳት። በማግሥቱም ሥጋዋን በመጋዝ እንዲሠነጥቁ ጐኖቿንም እንዲሰነጣጥቁና በእሥር ቤት እንዲጥሏት አዘዘ ያን ጊዜም የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤል መጥቶ አዳናት።

በወህኒ ቤቱ ውስጥም ቁማ ስትጸልይ እጅግ የሚያስፈራ ታላቅ ዘንዶ ወደ ርሷ መጣ በአየችውም ጊዜ ደነገጠች ሰውነቷ ሁሉ ተንቀጠቀጠ መናገርም ተሳናት። ያን ጊዜም እጆቿ በ #መስቀል ምልክት አምሳል እንደተዘረጉ በልቧም ስትጸልይ ወደርሷ ቀርቦ ዋጣት። ያን ጊዜም ሆዱ ተሠንጥቆ ያለ ጉዳት ወጣች #እግዚአብሔርንም አመሰገነችው።

ሁለተኛም በጥቁር ሰው አምሳል ሰይጣንን አየችው እጆቹም በጉልበቶቹ ላይ ተጨብጠው ነበር። ፊቷንም በ #መስቀል ምልክት አማትባ በራሱ ጠጉር ይዛ ደበደበችው። በእግሮቿም ረገጠችው ያን ጊዜም #ክብር_ይግባውና_የጌታ_ክርስቶስ #ዕፀ_መስቀል ተገለጠላት በላዩም ነጭ ርግብ ተቀምጣ እንዲህ ብላ አነጋገረቻት መሪና ሆይ የ #መንፈስ_ቅዱስን የጸጋ አረቦን ተቀብለሻልና ደስ ይበልሽ።

በማግሥቱም መኰንኑ ልብሷን አራቁተው ዘቅዝቀው ሰቅለው እንዲአቃጥሏት ደግሞም ውኃ ከአፈሉበት ጋን ውስጥ እንዲጨምሩዋት አዘዘ። በውስጡም ሁና ስትጸልይ ከሰማይ ርግብ መጣ በአፉም ውስጥ የወርቅ አክሊል ነበር ማሠሪያዋንም ፈትቶ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም ሦስት ጊዜ አጠመቃት #እግዚአብሔርንም እያመሰገነች ከውኃው ውስጥ ወጣች።

መኰንኑም እንደ ዳነች በአየ ጊዜ ራሷን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ወደ ሰማዕትነቱ ቦታም በደረሰች ጊዜ ነፍሷን በፍቅር ይቀበል ዘንድ ወደ #ጌታችን ጸለየች። #ክብር_ይግባውና_ጌታችንም ተገለጠላት ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያዋንም ለሚያደርግ ገድሏንም ለሚጽፍ ወይም ለሚያነበውና ለሚሰማው ኃጢአቱን እንዲአስተሠርይለት ለርሷም ርሱን እንዲሰጣት ቃል ኪዳን ሰጣት።

ከዚህም በኋላ ራሷን በሰይፍ ቆረጡ ከእርሷም ብዙ ተአምር ተገለጠ ዕውራን አይተዋልና፣ ሐንካሶች በትክክል ሔደዋልና፣ ደንቆሮዎችም ሰምተዋልና፣ ዲዳዎችም ተናግረዋልና ቁጥር የሌላቸው ብዙ ሰዎችም #ክብር_ይግባውና_በጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመኑ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት መሪና ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ለንጊኖስ_ሰማዕት

በዚችም ቀን ከቀጰዶቅያ አገር ለንጊኖስ ሰማዕት ሆነ። ይህም ቅዱስ ከጲላጦስ ጭፍሮች ውስጥ ነበር #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስለ ዓለም ደኅንነት መከራ እንዲቀበል የፈቀደበት ሰዓት በደረሰ ጊዜ በእርሱ ላይ የፈለጉትን ያደርጉ ዘንድ ለዐመፀኞች ፈቅዶላቸው ነበር። ይህም ለንጊኖስ #ጌታን ይሰቅሉት ዘንድ ጲላጦስ ከአዘዛቸው ወታደሮች ውስጥ ነበር።

በመስቀል ላይ ከሞተ በኋላ #ጌታችንን የቀኝ ጐኑን ወጋው ከጐኑም ደምና ውኃ ፈሰሰ። ይህንንም አይቶ እጅግ አደነቀ ከዚህም በፊት ፀሐይ እንደጨለመ፣ ጨረቃ ደም እንደሆነ፣ ዐለቱም እንደተሠነጠቀ፣ ሙታንም እንደተነሡ አይቶ ነበር።

#ጌታችንም በተነሣ ጊዜ ስለ ትንሣኤው የሆነውን ሰምቶ ይህን ምሥጢር ይገልጽለት ዘንድ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ። ሐዋርያው ጴጥሮስንም ላከለት እርሱም ነቢያት ስለ #ጌታችን፣ ስለ መከራው፣ ስለ መሰቀሉ፣ ስለ መሞቱ፣ ስለ መነሣቱ፣ ስለ ዕርገቱም ትንቢት እንደተናገሩ ነገረው። እርሱም ከቅድስት #ድንግል በሥጋ ተወልዶ ዓለምን ለማዳን የመጣ የሕያው #እግዚአብሔር ልጅ #ክርስቶስ እንደሆነ አስረዳው።

ያን ጊዜም በቅዱስ ጴጥሮስ ቃል አመነ የምድራዊ ንጉሥ አገልግሎትንም ትቶ ወደ ቀጰዶቅያ ሔደ በውስጧም ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_በኢየሱስ_ክርስቶስ ስም እንደ ሐዋርያት ሰበከ።

አይሁድም በጠላትነት ተነሡበት በመሳፍንትም ዘንድ ከሰሱት በላዩም የሐሰት ምስክር አስነሡበት ስለዚህም ራሱን በሰይፍ አስቆረጡት የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት አፄ ምኒልክ በአደዋ ጦርነት ጊዜ ለረዳቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ መታሰቢያ ይሆን ዘንድ ከድሉ ከተመለሱ በኋላ በአዲስ አበባ መሐል ከተማ ላይ በቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ቤተክርስቲያን አሠሩ ስሟንም ገነተ ጽጌ ብለው ሰየሟት የባረኳትም ሊቀ ጳጳሱ ግብፃዊው አቡነ ማቴዎስ ናቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት የቅዱስ ጊዮርጊስ ልመናው አማላጅነቱ ከእኛ ጋር ይሁን አሜን!!! ተአምረ ጊዮርጊስ ተአምር 17 ላይ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ_23)
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን በዕለተ ቀዳሚት የሚነበብ የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዜናውን እንናገር እነሆ #የመድኃኔአለም ትእምርተ #መስቀሉ #የእግዚአብሔር ምሳሌው። ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ ከ #እግዚአብሔር ጋር ያለ ትእምርተ መስቀል የከበረ ነው።

#የእግዚአብሔር ምሳሌው የሆነ ትእምርተ #መስቀል ከሁሉ አስቀድሞ ተፈጠረ። በእሱ አምሳል አዳምን ፈጠረው። ለመላእክት የ #መስቀል ምልክት አክሊል አላቸው። እንደ መብረቅ ያለ ዘውድም አላቸው። የ #መስቀል አምሳል በትርም አላቸው። ፊታቸውን በ #መስቀል ምልክት ይሸፍናሉ። የ #መስቀል ማዕዘኑ አራት እንደሆነ የመንበሩም ጎኖቹ አራት ናቸው።

ይህ #መስቀል የሄኖስ የሽቱ እንጨት ነው። የአብርሃም የወይራ እንጨቱ የይስሐቅ የነጭ ሐረጉ የያዕቆብ የዕጣኑ እንጨት ነው።

ይህ #መስቀል የሙሴ የሃይማኖት በትሩ ነው። ይህ #መስቀል ክንድን በኤፍሬምና በምናሴ ራስ ላይ በማስተላለፍ የጥላ ምልክት ነው።

ይህ #መስቀል የኤርሚያስ የሎሚ በትሩ ነው። የኢሳይያስ የስሙ መታሰቢያ ነው። ይህ #መስቀል ሰለሞን ያለ የእንኮይ እንጨት ነው። ከእንኮይ አነሳሁህ በዚያም የወለደችህ እናትህ ታመመች ብላ ይህች ሙሽራ ስለሙሽራዋ ብዙ ተናግራለችና።

ስለ #መስቀሉም ከጥላው በታች መቀመጥን ወደድሁ አለች ስለ ሥጋውም ፍሬው ለጉሮሮዬ ጣፋጭ ነው። ስለ ጎኑ ውሃም ወዳጅ ለኔ እንደተቋጠረ ከርቤ ነው አለች። ስለ #መስቀሉም በሱ ሰላም አገኛለሁና አለች ቤተ ክርስቲያንም ሙሽራዋ #መድኃኔአለምን እንዲሁ ትለዋለች።

ያዕቆብ የሴፍን አሕዛብን የሚወጋቸው የላም ቀንድ ነውን የላም ጥጃ ነው ብሎ በባረከው ጊዜ ሙሴ የተናገረው ትንቢት ምንድነው።

ላሚቱ በችግራችን ጊዜ የምታድነን #እመቤታች_መድኃኒታችን_ድንግል_ማርያም ናት። ጥጃውም በድንግልና ከሷ የተወለደ ይህ #መድኃኒታችን ነው። የቀንዱም ትርጓሜ ይህ #መስቀሉ ነው።

ሁለት ቀንዶችም የ #መስቀሉ ግንዶች ናቸው። የናዝሬቱ #ኢየሱስ የተሸከመውና የቀራንዮ ስምዖን የተሸከመው አንዱ ወደላይ የቆመው አንዱ የተጋደመው የ #መስቀል ግንድ ነው።

ነጭ በግ በነጭ ሐረግ ተይዞ ከሰማይ እንደወረደ እነሆ የሚያስደነግጥ የላም ጥጃ #መድኃኒታችን ነው።

እንደዚሁ ሀሉ #ክርስቶስ_መስቀሉን ተሸክሞ ሔደ ይህ #መስቀል ለቅዱሳን በመንገድ የተተወ የ #መድኃኒታችን ፍለጋው ነው። መንገድም ማለት #ቅዱስ_ወንጌል ነው።

ይህ #መስቀል አጋንንትን የሚያሳድዳቸው ሰይጣናትን የሚበትናቸው ነው። ኦሪት አንዱ ሺውን ትውልድ ያሸንፋቸዋል። ሁለቱ እልፉን ያሳድዷቸዋል እንዳለች። አንዱ ማለት ይህ #መስቀል ነው። ሁለቱም የ #መድኃኒታችን ቅድስ ሥጋው ክቡር ደሙ ነው።

ይህ #መስቀል የባሕር ፀጥታው የመርከቦችም ወደብ ነው። ይህ የቀራንዮ #መስቀል የቁርባን ኅብስት ያፈራው ነው። ይህ #መስቀል የጎኑ ውሃ ያጠጣው የጎኑ ደመም ያረካው ነው።

ይህ #መስቀል መጠጊያችን ኃይላችን የድኅነታችን ምልክት የነጻነታችን ምስክር ነው።

ይህ #መስቀል እንደ #እግዚአብሔር የከበረ እንደ ድንግል #ማርያምም ከፍ ያለ ነው። ሦስትነታቸው ትክክል የሚሆን እንደ #አብ እንደ #ወልድ እንደ #መንፈስ_ቅዱስም ፈጽሞ የማይለይ ነው። እንደዚሁም #መድኃኒታችን ከእናቱና ከ #መስቀል ጋር ሦስትነታቸው ትክክል ነው።

እንዲህ እናምናለን እናመልካለንም እንዲህ እንናገራለን እናመሰግናለንም። እንዲህ የሚያምን ይድናል እንዲህ የማያምን ይደየናል። የመብዓ ጽዮን ጸሎቱ የ #መድኃኔአለም ይቅርታውና ቸርነቱ ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን።

#ድርሳነ_መድኃኔአለም_ዘቀዳሚት_ሰንበት
ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ለቅዱስ አቦሊ ተገለጠለት እንዲህም ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠው። በመከራ ውስጥ ያለ ሰው በስምህ ርዳታ ቢለምን እኔ እሰማዋለሁ ልመናውን ፍላጎቱንም እፈጽምለታለሁ። በስምህ ቤተ ክርስቲያን ለሠራም እኔ በሰማያት ብርሃናዊ ማደሪያ ቤት እሠራለታለሁ የገድልህን መጽሐፍ የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውን ወይም የሚሰማውን እኔ በኪሩቤል ክንፎች ላይ ስሙን እጽፉለሁ በአብርሃም በይስሐቅና በያዕቆብ እቅፍም አሳርፈዋለሁ ተድላ ደስታ ካለባት ከገነት ፍሬዎችም እመግበዋለሁ።

ብዙ ኃጢአትን ሠርቶ የበደለውንም በስምህ ወደኔ እየለመነ ንስሐ ቢገባ በደሉን ሁሉ ይቅር እለዋለሁ። ከጻድቃንም ጋርም እቈጥረዋለሁ ሰላሜም ካንተ ጋራ ይሁን ይህንንም ብሎ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ።

መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘ የከበረች ራሱን ቆረጡት የሕይወት አክሊልንም ተቀበለ። ሥጋውም ከምስር ከተማ ውጭ ሕንቅ በሚባል ገዳም ይኖራል ከእርሱም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ መስተጋድል ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አበው_ሐዋርያት_ዮሴፍና_ኒቆዲሞስ

በዚህችም ቀን ለአምላካዊት ምሥጢር አገልጋዮች ሊሆኑ የተገባቸው የከበሩ ሰዎች የዮሴፍና የኒቆዲሞስ መታሰቢያቸውን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶች አዘዙ።

በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ ስለ ደኅንነታችን በሞተ ጊዜ የደኅንነታችንንም ምሥጢር በፈጸመ ጊዜ የሕያው #እግዚአብሔርን ልጅ የ #መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስን ሥጋ እነርሱ ከ #መስቀል ላይ አውርደዋልና። የአይሁድም መገርመም ከጲላጦስ ዘንድ የ #መድኃኒታችንን ሥጋ እስከ ለመኑ ድረስ አላስፈራቸውም።

ጲላጦስም በፈቀደላቸው ጊዜ የእጆቹንና የእግሮቹን ችንካሮች ነቅለው ከ #መስቀል አውርደው በትክሻቸው ተሸከሙት ሲገንዙትም እንዲህ የሚል ቃል ከበድኑ ሰሙ። #ቅዱስ_እግዚአብሔር #ቅዱስ_ኃያል #ቅዱስ_ሕያው_የማይሞት#ቅድስት_ድንግል_ማርያም የተወለደ አቤቱ ይቅር በለን።

#ቅዱስ_እግዚአብሔር #ቅዱስ_ኃያል #ቅዱስ_ሕያው_የማይሞት በዮርዳኖስ የተጠመቀ በእንጨት #መስቀልም የተሰቀለ አቤቱ ይቅር በለን። #ቅዱስ_እግዚአብሔር #ቅዱስ_ኃያል #ቅዱስ_ሕያው_የማይሞት በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ የተነሣ በክብር ወደ ሰማያት ያረገ በአባቱም ቀኝ የተቀመጠ ዳግመኛም በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ የሚመጣ አቤቱ ይቅር በለን።

#አብ ምስጋና ይገባል ለ #ወልድ ምስጋና ይገባል ለ #መንፈስ_ቅዱስ ምስጋና ይገባል ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን አሜን ይሁን ይሁን። ልዩ ሦስት ሕያው #እግዚአብሔር ይቅር በለን።

ይህንንም በሰሙ ጊዜ ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖታቸው ጸናች። ዮሴፍም በፍታ ኒቆዲሞስም ሽቶዎችን አምጥተው #ጌታችንን ገነዙት በአዲስ መቃብር ውስጥም ቀበሩት።

ይህ ዮሴፍም ለሰማዕታት መጀመሪያ ለእስጢፋኖስ ዘመድ ለሆነው ለቀለዮጳ ወንድሙ ለኒቆዲሞስ ዘመዱ ነው ኒቆዲሞስም የአይሁድ አለቃ ፈሪሳዊ ነበር እርሱም ወደ #ጌታ_ኢየሱስ አስቀድሞ በሌሊት የሔደና ከ #እግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣ ያመነ ነበር። #ጌታችንም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው ወደ #እግዚአብሔር መንግሥት መግባት እንደማይችል የነገረው ነው።

ይህ ኒቆዲሞስም የ #ጌታችንን ቃል በሚአቃልሉ ጊዜ አይሁድን ይገሥጻቸው ነበር። ከተነሣ በኋላም በኢማሁስ መንገድ ሲሔድ #ጌታችን_ኢየሱስ የተገናኛቸው እሊህ ኒቆዲሞስና ቀለዮጳ ናቸው። እነርሱም ሳያውቁት በእርሱ ላይ የሆነውን ሁሉ ነገሩት። እርሱም ስለ ሞቱና ስለ ትንሣኤው ነቢያት ትንቢት እንደ ተናገሩ አስተማራቸው።

ከዘህም በኋላ እርሱ መሆኑን ባወቁት ጊዜ ተሠወራቸው እነርሱም ተመልሰው ለደቀ መዛሙርቱ ነገሩ። ክብር ይግባውና የ #ጌታችንን ሥጋ ስለ ቀበረ ሊገድሉት ፈልገው አይሁድ ዮሴፍን በወህኒ ቤት አሠሩት። የወህኒ ቤቱም በር በሊቃነ ካህናቱና በጲላጦስ ማኅተም ተቆልፎ ሳለ #ጌታችን በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጦ ዮሴፍ ወደ አለበት ገባ ከእርሱ ጋርም እልፍ አእላፋት መላእክት ነበሩ። ሱራፌልም በዙሪያው ቁመው በፊቱ ያጥናሉ በቀኝ በኩል ተሰቅሎ የነበረ ወንበዴውም ብሩህ ልብስ ለብሶ በቀኝ ቁሞአል ባለሟልነትን በልዑል ፊት አግኝቶአልና ስለ ኃጢአተኞች ይማልድ ነበር።

የወህኒ ቤት ጠባቂዎችም በአዩ ጊዜ ደነገጡ ፈርተውም መንቀጥቀጥ ያዛቸው #ጌታችንም ዮሴፍን ጠርቶ እንዲህ አለው ከአይሁድ ግርማ የተነሣ አትፍራ ከማሠሪያህ ልፈታሕ እኔ መጣሁ አንተ መከራዬን የተሳተፍከኝ የናዝሬቱ #ኢየሱስ እኔ ነኝ እኔ #ጌታህና የዓለሙ ሁሉ #ጌታ እንደሆንሁ ፈጽመህ ታውቅ ዘንድ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን የተወጋ ጐኔንም እይ።

ከዚያም ዮሴፍን ነጥቆ ወደ አገሩ አርማትያስ ወሰደው። የወህኒ ቤቱ ጠባቂዎችም ሔደው #ጌታችን ያደረገውን ሁሉ ዮሴፍንም ይዞ ከእርሱ ጋር እንደወሰደው ለካህናት አለቆች ነገሩ። የካህናት አለቆችም በሔዱ ጊዜ የወህኒ ቤቱ በር ተቆልፎ አገኙ እሽጉም አልተለወጠም ነበር። እሊህ ቅዱሳንም ከሐዋርያት ጋር ወንጌልን እየሰበኩ ኖሩ ብዙ መከራም አገኛቸው። ከዚህም በኋላ በሰላም አረፉ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሐና_ነቢዪት

በዚህም ዕለት ከአሴር ወገን የሆነች የፋኑኤል ልጅ ነቢዪት ሐና አረፈች፡፡ የእርሷም ዘመኗ አልፎ ነበር በድንግልና ከኖረች በኋላ ከባሏ ጋር ሰባት ዓመት ኖረች። ሰማንያ አራት ዓመት ፈት ሁና ኖረች በጾምና በጸሎትም እያገለገለች ቀንም ሌትም ከምኲራብ አትወጣም ነበር።

ጌታችን ኢየሱስን ከተወለደ በኋላ በአርባ ቀን ወደ ቤተ መቅደስ በአስገቡት ጊዜ በዚያን ሰዓት ተነሥታ አመነች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው። የኢየሩሳሌምን ድኅነት ተስፋ ለሚያደርጉ ሁሉ ስለርሱ ነገረች። ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈች።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_1)
#ነሐሴ_5

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን #አባ_ፊልጶስ አረፈ፣ #ቅዱስ_አባ_አብርሃም ገዳማዊ አረፈ፣ የከበረ ተጋዳይ ወታደር #ቅዱስ_ዮሐንስ_ጻድቅ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ፊልጶስ_ዘደብረ_ቢዘን

ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን አባ ፊልጶስ አረፈ። አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ቢዘን እንደ ነቢዩ ኤርምያስ በእናታቸው ማኅፀን ሳሉ የተመረጡና እንደተወለዱ ነው ሰማንያ አንዱን የብሉይ መጻሕፍትን አጠናቀው ያወቁት ናቸው፡፡ በ12 ዓመታቸውም ለመመንኮስና ገዳም ለመግባት ወስነው ወላጅ እናታቸውን አሰናብቺኝ በማለት ጠይቀዋል፡፡ ቅድስት እናታቸውም መርቀው ሸኟቸውና ትግራይ ውስጥ ወደሚገኘውና ደብረ ጸራቢ ወደሚባለው ገዳም ገቡ፡፡ የገዳሙ አስተዳዳሪ አቡነ በኪሞስም የምንኩስና ቀንበሩና ሸክሙ እጅግ ከባድ መሆኑን በመንገር ወደ እናታቸው እንዲመለሱ ቢመክሯቸውም አቡነ ፊልጶስ ግን ለምንኩስና የታጩ ሙሽራ መሆናቸውን ነገሯቸው፡፡ ከብዙ ፈተናም በኋላ አመነኮሷቸው፡፡

በገዳሙም እንጨት እየለቀሙና እየፈለጡ፣ ውኃ እየቀዱ፣ የክርስቶስን ሕማሙን ሞቱን እያሰቡ በጾምና ጸሎት ሲጋደሉ ከኖሩ በኋላ ጌታችን ተገልጦላቸው ወደ ሽሬ እንዲሄዱ ነገራቸውና ሽሬ አደያቦ ወደሚባለው ስፍራ ሄዱ፡፡ ብዙ አስደናቂ ተአምራት እያደረጉ ወንጌልን በሀገሩ ዞረው ሰበኩ፡፡ እንደ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላቸው ድውያንን ይፈውሱ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ደብረ ቢዘን እንዲሄዱ ተነግሯቸው የእርሳቸውን በረከት ለመቀበል ከመጡ 16 ደጋግ መነኮሳት ጋር ወደ ደብረ ቢዘን ሄዱ፡፡ ይኸውም በኤርትራ ክፍለ ሀገር በሐማሴን አውራጃ ከአሥመራ ከተማ በስተምሥራቅ 25 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘው አስደናቂው ገዳም ነው፡፡

ጻድቁ የሐይቅ እስጢፋኖስን ባሕር በተአምራት ያቃጠሉት አባት ናቸው፡፡ በንጉሡ በዐፄ ዳዊት ዘመን ሰንበትን አንድ ብቻ ናት እያሉ በአንደኛዋ ሰንበት ሥራ ሲሠሩ ጻድቁ አቡነ ፊልጶስ ይህን ሰምተው አንዲት ሰንበት የሚሉትን ሁሉ ተቃወሟቸው፡፡ ከግብፅ የመጡት ጳጳስም ቀደም ብሎ ከአቡነ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አሁንም ከአቡነ ፊልጶስ ጋር ንጉሡ ዐፄ ዳዊት አከራክረዋቸው ጳጳሱም በክርክሩ ተረቱ፡፡ ክፉዎችም በአቡነ ፊሊጶስ ላይ በክፋት ተነሱባቸው፡፡ በአቁማዳ ጠቅልለው ሐይቅ ባሕር ውስጥ ጣሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እሳቸው የተጣሉበት ባሕር በእሳት ተቃጥሎ ጽድቃቸውን መስክሮላቸዋል፡፡ ዛሬም ድረስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ባሕር ዳርቻ ላይ የተቃጠለው ድንጋይ ምልክቱ በግልጽ ይታያል፡፡ በወቅቱ የንጉሡ ሚስት በዋናተኛ አስፈልጋ ከሐይቁ ውስጥ አስወጣቻቸው፡፡ እግራቸውንም አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ጠጣችው፡፡ ወዲያውም ‹‹ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል›› ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡ በወቅቱ በተፈጠረው አለመግባባትና ክፉዎችም በባሕር ውስጥ ስለጣሏቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም አቡነ ፊልጶስን ከልብ ይቅርታ ጠይቀው ወዲያው ታርቀዋል፡፡ በዘመናቸውም ርኃብ ስለነተሳ ጻድቁን ከገዳማቸው አስጠርተው ‹‹ምን ባደርግ ይሻለኛል?›› ብለው አማክረዋቸዋል፡፡ አቡነ ፊልጶስም ‹‹የ #ጌታችንን መስቀል ያስመጡ›› ብለው መከሯቸው፡፡

ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም በአቡን ፊልጶስ ምክር መሰረት ከኢየሩሳሌም፣ ከቍስጥንጥንያና ከእስክንድርያ መንግሥታት ጋር ተጻጽፈው ዓሥሩን ታላላቅ ቅዱሳን ይዘው ሄደው መስቀሉን መስከረም 10 ቀን አምጥተውታል፡፡ ቅዱስ መስቀሉን ያመጡት ዓሥሩ ቅዱሳንም የደብረ ቢዘኑ አቡነ ፊልጶስ ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ ኂሩተ አምላክ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ እንድርያስ፣ አቡነ በትረ ማርያም፣ አቡነ ዮሐንስ፣ አቡነ ታዴዎስ፣ አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ፣ አቡነ ዘካርያስ፣ አቡነ ያሳይና አቡነ ቶማስ ናቸው፡፡ አቡነ ፊሊጶስ ዘደብረ ቢዘን በታላቅ ተጋድሎ ኖረው ከ #ጌታችን ዘንድ ታላቅ ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ነሐሴ 5 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_አብርሃም_ገዳማዊ

በዚህች ቀን ሌላው አብርሃም አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ባለጸጎች ናቸው በተግሣጽና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በማስተማር አሳደጉት ። በአደገ ጊዜም ያለ ፈቃዱ አጋቡት #እግዚአብሔርም ወደሚፈቅደው ይመራው ዘንድ ሲለምን ኖረ።

በሰባተኛውም ቀን በዐልጋው ላይ ሳለ የ #እግዚአብሔር ቸርነት አነሳሥቶት ከጫጉላ ቤቱ ወጣ ብርሃን እየመራው ሒዶ ባዶ ቤት አግኝቶ በውስጡ ገብቶ ኖረ ምግቡን ከሚቀበልባት ከጥቂት መስኮት በቀር መዝጊያ ሠርቶ ደጁን ዘጋ።

ዓለምን ከተወ በዓሥረኛው ዓመት አባትና እናቱ ብዙ ጥሪት ትተውለት ሞቱ እርሱ ግን ለድኆችና ለችግረኞች በትኖ በጾምና በጸሎት ተወስኖ እየተጋደለ ኖረ ከአንድ ዐጽፍና ሰሌን በቀር ምንም ምን ጥሪት አላኖረም እንዲህም ሆኖ ዐሥር ዓመት ተጋደለ።

#እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አየ በአንዲት አገርም አረማውያን ነበሩ ከታናሾቻቸው እስከ ታላላቆቻቸው ወደ ሃይማኖት ሊመልሳቸው የሚችል የሌለ። በአንዲት ቀንም አባ አብርሃምን ጳጳሱ አሰበው ብርታቱንና ብልህነቱንም አይቶ ቄስ እንዲሆንና እነዚያን አረማውያን እንዲመልሳቸው አስገደደው በግድ አስጨንቆም ቅስና ሾመው ። ወደዚያም ቦታ ደርሶ ቤተ ክርስቲያን ሠራ እነዚያን አረማውያን እርሱን ፈጣሪያቸውን ወደ ማወቅ ይመልሳቸው ዘንድ በውስጧ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ።

በአንዲት ቀንም ወደ ጣዖቶቻቸው ቤት ገባ ያን ጊዜ ጣዖታቱን ከመቀመጫቸው ጣላቸው የአገር ሰዎችም በአዩ ጊዜ ቁጣን ተመልተው አብዝተው ደበደቡትና ከአገር አበረሩት በጥዋትም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጸልይ አገኙት።

ሁለተኛም በገመድ አሥረው ወደ ከተማው ውጭ ጐትተው በላዩም አፈር ቆልለው እንዳይሞት ጥቂት መተንፈሻ ትተው አልፈው ከዚያ ሔዱ። በ #እግዚአብሔርም ኃያል ተነሥቶ ሔደ ስለ መመለሳቸውም ሲጸልይ አገኙት በእንዲህ ያለ ሥራም እየተጋደለ ዐሥር ዓመት ኖረ።

የክብር ባለቤት #እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ልባቸውን መለሰ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም ከታናናሾች እስከ ታላላቆች ድረስ ሁሉንም አጠመቃቸው
የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖትም ጸኑ።

ከዚህም በኋላ በሃይማኖታቸው መጽናታቸውን ባየ ጊዜ ከንቱ ውዳሴ እንዳያመጣበት ፈርቶ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ አገሪቱንም በ #መስቀል ምልክት አማተበባትና ማንም ሳያውቅ ወጥቶ ወደ ሌላ አገር ሔደ ።

ሰይጣንም በሚያስፈራው በብዙ ሥራ ይፈታተነው ነበር ቅዱሱም የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን ኃይል አሸነፈው ። ጽኑ በሆነ ተጋድሎም ኖረ ያለ ዕንባም ሰዓት አላለፈችውም በጥርሶቹም አልሳቀም በከንፈሮቹም ፈገግ አላለም ስጋውን ቅባት አልነካውም ስጋውንና ደሙን ከሚቀበልበት ጊዜ በቀር ፊቱንና እግሩን አልታጠበም ።

እናትና አባቱ በስድስት ዓመቷ ትተዋት የሞቱ እኅት ነበረችው ስሟም ማርያ ይባላል ዘመዶቿም ወደ አብርሃም አምጥተዋት ፈሪሀ #እግዚአብሔር ሃያ ዓመት ሆናት ድረስ ትሕትናንም እያስተማራት በእርሱ ዘንድ አደገች።

ከዚህም በኋላ ሰይጣን ቀንቶባት ከአንድ መነኩሴ ጋር አፋቀራት ድንግልናዋንም አጠፉች ልብሷንና አስኬማዋን ለውጣ ወደ ሌላ አገር ሔደች።
#ነሐሴ_10

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ #አባ_ዓቢየ_እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው፣ #ቅዱስ_መጥራ በሰማዕትነት ሞተ፣ #ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ የከበሩ #ቅዱሳን_ቢካቦስና_ዮሐንስ በሰማዕትነት ሞቱ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዓቢየ_እግዚእ_ኢትዮዽያዊ

ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ አባ ዓቢየ እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው። አባ ዓቢየ እግዚእ የተወለዱት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ትግራይ ተንቤን (መረታ) ውስጥ ነው። የተባረኩ ወላጆቻቸው ያፍቅረነ እግዚእ እና ጽርሐ ቅድሳት ይባላሉ። አጥምቀው "ዓቢየ እግዚእ" ሲሉ ስም ያወጡላቸው የወቅቱ ጳጳስ ሰላማ መተርጉመ መጻሕፍት ናቸው። ትርጉሙም 'በጌታ ዘንድ ታላቅ ሰው' ማለት ነው።

ዓቢየ እግዚእ በሕፃንነታቸው ሌሊት ሌሊት ባሕር ውስጥ ሰጥመው ሲጸልዩ አድረው ቀን ቀን እየተማሩ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቁ። ገና በወጣትነታቸው ወደ ታላቁ መነኮስ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ (ደብረ በንኮል) ሔደው መንኩሰዋል።

በገዳሙ በጾም በጸሎትና በስግደት ተወስነው ከኖሩ በኋላ ወደ ዋልድባ ሔደው የተሰወረች ቤተ ክርስቲያን አግኝተዋል። በጊዜው በአርባ ቀን አንዲት ቅጠል ብቻ ለቁመተ ሥጋ ይበሉ ነበር።

ከዚያም ወደ ሃገራቸው ተንቤን ተመልሰው ዛሬም ድረስ ድንቅ ሆኖ የሚታየውን ገዳም መሥርተው ብዙ መናንያንን አፍርተዋል። ዓቢየ እግዚእ ገዳማዊና ጻድቅ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያዊ አባትም ነበሩ። ከትግራይ እስከ ደንቢያ ደግሞ ሃገረ ስብከታቸው ነው።

አንድ ጊዜ ደቀ መዛሙርትን አስከትለው ለስብከት ሲንቀሳቀሱ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ደረሱ። ቀኑ ነሐሴ ዐሥር ነውና ተከዜ እስከ ገደፉ ሞልቶ ለሦስት ቀናት ባለመጉደሉ ከአንድ ሺ በላይ ሰዎች ሲያለቅሱ ደረሱ። ጻድቁ በአካባቢው የነበሩት ኢ-አማንያን (አሕዛብ) ቢሆኑም ራርተዋልና "አምላከ ሙሴ" ብለው ጸልየው ወደ ጥልቁ ውስጥ ገቡ።

ቅዱስ ሚካኤል አብሯቸው ነበርና ተከዜ ግራና ቀኝ ተከፍሎ መሃሉ የብስ ሆነ። ይሕን ድንቅ ያዩ ከዘጠኝ መቶ አርባ በላይ አሕዛብም አምነው በጻድቁ እጅ ተጠምቀዋል። ይሕም ዘወትር ነሐሴ ዐሥር ቀን በቤተ ክርስቲያናቸው (ጐንደር) ይከበራል።

ከዚያም እያስተማሩ ጐንደር ደረሱ። ያኔ ጐንደር በቀሃና አንገረብ ወንዞች የታጠረች አንዲት መንደር ነበረች። ጻድቁ ቀን ቀን እየሰበኩ ማታ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናቸው የታነጸበት ሥፍራ ላይ ሲጸልዩ ያድሩ ነበር።

በዚያ ዘመን ጐንደር ውስጥ ጅብ እባብና መሠል አራዊት ገብተው ሕዝቡን ጨረሱት። ይሕንን የተመለከቱት አባ ዓቢየ እግዚእ ወደ እግዚአብሔር አለቀሱ። በፍጹም ልባቸውም ስለ ሕዝቡ ለመኑ። የለመኑትን የማይነሳ ጌታ ወደ ጻድቁ ቀርቦ "በስምሕ የተማጸኑ በቃል ኪዳንህ ያመኑ: በምድር አራዊት አይሠለጥኑባቸውም። በሰማይም እሳትን አያዩም። ጐንደርንም አራዊት ገብተው ሰውን አይጐዱም።" ብሏቸው አርጓል።

አባ ዓቢየ እግዚእ በገዳማቸው ተንቤን ለብዙ ዘመናት በቅድስና ኑረው ሦስት ሙታንን አስነስተው ብዙ ድውያንን ፈውሰው ብሔረ ብጹዓንን ጎብኝተው የድኅነት ቃል ኪዳንም ተቀብለው በመቶ አርባ ዓመታቸው ግንቦት ዐሥራ ዘጠኝ ቀን አርፈዋል። የጻድቁ ክብር ለሁሉ ነውና እናስባቸው።

ይህች ዕለት ባሕረ ተከዜን ከፍለው ሕዝቡን ያሻገሩባት አሕዛብንም ያጠመቁባት ናትና በገዳማቸው ጐንደር ውስጥ በሚገኘው ቤተ ክርስቲያናቸውም ይከበራል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መጥራ

በዚህች ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በቅዱስ ዲሜጥሮስ ዘመንና በከሀዲው ንጉሥ በዳኬዎስ ዘመነ መንግሥት ቅዱስ መጥራ በሰማዕትነት ሞተ።

ይህም ቅዱስ የክብር ባለቤት #ክርስቶስን ክደው ለጣዖት መስገድን የሚያዝ የንጉሡን ደብዳቤ በሰማ ጊዜ ይህ ቅዱስ ወዲያውኑ ሒዶ ከወርቅ የተሠራ የአጵሎንን ክንድ ሰረቀ በየጥቂቱም ሰባብሮና ቆራርጦ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጣቸው።

የጣዖቱም አገልጋዮች ክንዱ ተቆርጦ አጵሎንን በአገኙት ጊዜ ስለርሱ ብዙዎችን ሰዎች ያዟቸው። በዚያንም ጊዜ ወደ መኰንኑ ቀርቦ ክርስቲያን እንደሆነ በፊቱ ታመነ ሁለተኛም የአጵሎንን የወርቅ ክንድ የወሰድኩ እኔ ነኝ ለድኆችና ለችግረኞችም ሰጠኃ ኋቸው አለው።

መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ አስጨናቂ የሆነ ታላቅ ሥቃይንም አሠቃየው ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጨመሩት #እግዚአብሔርም አዳነው ያለ ጥፋትም በጤና አወጣው።

ከዚህም በኋላ እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ ብዙ ደም ከአፍንጫው ወደ ምድር እስከ ሚወርድ ዘቅዝቀው በዕንጨት ላይ ሰቀሉት።

በዚያንም ጊዜ የ #እግዚአብሔር መልአክ ወርዶ ቅዱስ መጥራንን ፈታው ከተሰቀለበትም አውርዶ በመዳሠሥ አዳነው። አንድ ዕውር ሰውም መጣ ከአፍንጫው ከወረደውም ደም ወስዶ ዐይኖቹን ቀባ ወዲያውኑ አየ። መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀዳጀ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ መጥራ ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ

በዚህችም ቀን ዳግመኛ በከሀዲ መክስምያኖስ እጅ ቅዱስ ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ። በንጉሥ መክስምያኖስ ፊት በአቆሙት ጊዜ ለአማልክት ሠዋ አለው። የከበረ ሐርስጥፎሮስም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ #እግዚአብሔር_ኢየሱስ_ክርስቶስን አመልከዋለሁ ለእርሱም እሠዋለሁ። ንጉሡም ተቆጥቶ ሥጋው ተቆራርጦ በምድር ላይ እስቲወድቅ በበትር ይደበድቡት ዘንድ አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት።

ከዚህም በኋላ ወደ ወህኒ ቤት ጣሉት በላህያቸውም እንዲአስቱት ሁለት ሴቶችን ንጉሡ ወደርሱ ላከ ቅዱሱ ግን የ #ክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራቸው የዛሬ የሆነ የዚህንም ዓለም ኃላፊነት አስገነዘባቸው ወደ መክስምያኖስም በተመለሱ ጊዜ እንዴት አደረጋችሁ አላቸው።

እነርሱም እንዲህ አሉት በከበረ ሐርስጥፎሮስ አምላክ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ክርስቶስ እኛ እናምናለን ንጉሡም ሰምቶ አንዲቱን በዕንጨት ላይ ሰቅለው እንዲአቃጥሏት ሁለተኛዋን በአንገቷ ደንጊያ አንጠልጥለው ቊልቊል እንዲሰቅሏት አዘዘና ምስክርነታቸውን እንዲህ ፈጸሙ።

ከዚህም በኋላ ዕንጨቶችን ሰብስበው በማንደጃው ውስጥ አድርገው አነደዱ የከበረ ሐርስጥፎሮስን እጅና እግሩ እንደ ታሠረ ከውስጡ ጨመሩት ያን ጊዜም በስመ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ አለ እሳቱ ከቶ ምንም አልነካውም። ሕዝቡም ይህን አይተው የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ዐሥር ሺህ ያህል ሰዎች አምነው በሰማዕትነት ሞቱ።

ሁለተኛም የብረት ሠሌዳዎችን በእሳት አግለው አመጡ ቅዱሱንም በላያቸው በአስተኙት ጊዜ ምንም ምን የነካው የለም። ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው በክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃያ ሺህ አንድ መቶ ሰዎችና አርባ ሕፃናት አምነው ምስክር ሁነው ሞቱ።

ንጉሥ መክስምያኖስም አይቶ እጅግ ተቆጣ የቅዱስ ሐርስጥፎሮስንም ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ከንጉሡም ዘንድ በወጣ ጊዜ ጸሎትን አደረገ ፊቱንም በ #መስቀል ምልክት አማተበ ከዚህም በኋላ ምስክርነቱን ፈጸመ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሐርስጥፎስ እና በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።
#ነሐሴ_13

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ሦስት በዚህች ቀን #ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን #በደብረ_ታቦር የገለጠበት ዕለት ነው፣ #የቅዱስ_ሙሴ_ሊቀ_ነቢያት ልደቱ ነው፣ ተጋዳይ #አባ_ጋልዩን አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ደብረ_ታቦር

ነሐሴ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን ክብር ይግባውና የ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ታላቅና ክቡር በዓል ነው።

በዚች ቀን #መድኃኒታችን ሦስቱን ደቀ መዛሙርቶቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ላይ አወጣቸው። መልኩም በፊታቸው ተለወጠ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ሆነ። ስለ እነርሱም #ጌታችን የሰው ልጅ በጌትነቱ ሲመጣ እስከሚያዩት ድረስ በዚህ ከቆሙት መካከል ሞትን የማይቀምሱት አሉ አለ።

ሰዎች ሁሉ እርሱ ለሙሴ #ጌታውና ከሞት ያስነሣው እንደሆነ ለኤልያስም ፈጣሪው እንደሆነና ካሳረገበትም ያወረደው እርሱ እንደሆነ ያውቁ ዘንድ እነሆ ከ #ጌታ_ከኢየሱስ ጋራ እየተነጋገሩ ሙሴና ኤልያስ ወደርሱ መጡ። ስለዚህም ጴጥሮስ ጌታችንን እንዲህ አለው አቤቱ በዚህ ትኖር ዘንድ ትወዳለህን ሦስት ሰቀላዎችንም አንድ ላንተ፣ አንድ ለሙሴ፣ አንድ ለኤልያስ እንሠራ ዘንድ።

በዚህም ቃል የደካማነትና የትሕትና ምልክት አለበት። ደካማነት የተባለ ጴጥሮስ #ጌታችን ከሰማይ የወረደበትን ሥራ ትቶ በተራራ ላይ ይኖር ዘንድና ራሱን የሚሠውርበትን ቤት ይሠራለት ዘንድ የተናገረው ነው። ትሕትና ያልነውም ጴጥሮስ ለራሱና ለባልንጀሮቹ ሐዋርያት ቤት ይሠራ ዘንድ ስለ አላሰበ ነው። ራሱንና ባልንጀሮቹ ሐዋርያትን እንደ ባሮች ነቢያትን ደግሞ እንደ #ጌቶች አድርጎ አስቧልና።

ስለ ሐዋርያትም የእውቀት ማነስ አታድንቅ በዚያን ጊዜ ፍጹማን አልሆኑምና። እንዲህም በሚልበት ጊዜ #ጌታችን በሰው እጅ የተሠራ ማደሪያን የማይሻ መሆኑን ለጴጥሮስ ያሳየው ዘንድ እነሆ ደመና ጋረዳቸው።

#ጌታችንን ጌትነቱን የሚገልጽ በሐዋርያትም ልቡና እምነትን የሚያጸና እንዲህ የሚል ቃል ከደመና ውስጥ መጣ። ይህ የምወደው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱንም ስሙት።

ሙሴና ኤልያስም ከእርሱ ጋራ ሲነጋገሩ ተሰሙ ስለ ርሱ መምጣት የተናገሩትን ትንቢታቸውንም በቸርነቱ አረጋገጠ። ወደ ተራራ ላይ በመውጣቱም ነቢያትና ሐዋርያት ደስ አላቸው።

ሁለተኛም የ #አብን ቃል በሰሙ ጊዜ ከእነርሱ ሥውር የነበረ የ #ወልድ ዋሕድን በእውነት ሰው መሆን በዚያን ጊዜ ተረዱ ያን ጊዜ የጌትነቱ ክብር ተገልጦአልና። ሐዋርያትም ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው የሆነ እርሱ ሙሴን ከመቃብር ያስነሣው ኤልያስንም ያሳረገው አውርዶም ያመጣው እርሱ እንደሆነ አወቁ። ከእርሱ በቀር ማንም ማን የሙሴን መቃብር የሚያውቅ የለምና ከዐሳረገው ከእርሱ በቀር ማንም ማን ኤልያስ ያለበትን የሚያውቅ የለምና። በሰማይና በምድር ሥልጣን ካለው ከሁሉ #ጌታ በቀር ሙታንን አድኖ ሊአስነሣቸው ማንም አይችልም።

ደብረ ታቦርም የቤተ ክርስቲያን አምሳል ሆነች ከብሉይና ከሐዲስ በውስጧ ሰብስባለችና። የ #አብንም ቃል በሰሙ ጊዜ በግምባራቸው ፍግም ብለው በምድር ላይ ወደቁ እንደ ሙታንም ሆኑ። ከዓለም አስቀድሞ ከእርሱ ጋራ በህልውና እንዳለ ለልጁ #አብ ምስክርን ሆነ ወዲያውኑ ሙሴ ወደ መቃብሩ ኤልያስም ወደ ቦታው ተመለሱ።

ሐዋርያትንም በአነቃቸው ጊዜ ከብቻው #ጌታችን በቀር ማንንም አላገኙም። ከባሕርያችን የተዋሐደና ሥጋችንን የለበሰ ፍጹም አምላክ እንደሆነ በዚህ ሐዋርያት አስተማሩ።

እንግዲህ እናስተውል ሰው ካልሆነ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታቸንን ድንግል #ማርያምን በአበሠራት ጊዜ #እግዚአብሔር ከአንቺ ጋራ ነው እንዴት አላት። አምላክ ካልሆነስ ለመንግሥቱ ፍጻሜ የለውም እንዴት አላት። ሰው ካልሆነ በበረት እንዴት አስተኙት። አምላክስ ካልሆነ መላእክት ከሰማይ ወርደው ለ #እግዚአብሔር በሰማያት ምስጋና በምድርም ሰላም ለሰውም ግዕዛኑ ሊሰጠው እያሉ እንዴት አመሰገኑ።

ሰው ካልሆነ ዮሐንስ በውኃ እንዴት አጠመቀው አምላክስ ካልሆነ አልዓዛርን ከመቃብር እንዴት ሊያስነሣው ቻለ። ይህ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው እንድ ልጅ አካላዊ ቃል #እግዚአብሔር እርሱ ያለ መለወጥ ያለ መለየት አንድ አካል አንድ ባሕርይ በመሆን ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው እንደሆነ እናምንበታለን። እርሱም ከ #አብ#መንፈስ_ቅዱስ ጋራ ሁል ጊዜ አንድ ህላዌ ነው ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሙሴ_ሊቀ_ነቢያት

በዚችም ቀን የቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት ልደቱ ነው።

ዓለም በተፈጠረ በ3,600 ዓመት እሥራኤል በረሃብ ምክንያት ያዕቆብ ወደ ምድረ ግብፅ ወረደ:: በዚያም ልጆቹና የልጅ ልጆቹ ለ215 ዓመታት ተከብረው ለ215 ዓመታት ደግሞ በባርነት በድምሩ ለ430 ዓመታት በምድረ ግብፅ ኑረዋል። በባርነት ዘመናቸውም 'ራምሴና ጋምሴ' የሚባሉ 2 ከተሞችን (ዛሬ ፒራሚዶች የምንላቸውን) በደም ገንብተዋል። ግፋቸው እየበዛ ሲሔድ ግን ጩኸታቸው ቅድመ #እግዚአብሔር ደረሰ። ያድናቸውም ዘንድ አንድ ቅዱስ ሰው እንዲወለድ አደረገ። ይኽም ሰው ሙሴ ይባላል።

ወላጆቹ መታመናቸውን በፈጣሪያቸው ያደረጉ ዮካብድና እንበረም ሲሆኑ ከሌዊ ነገድ ናቸው፡፡ ከሙሴ ውጪም አሮንና ማርያምን ወልደዋል። ቅዱስ ሙሴ በተወለደበት ወራት ወንድ የእሥራኤል ሕጻናት ይገደሉ ነበር። #ጌታ ግን በገዳዮቹ ልቡና ርሕራሔን አምጥቶ አትርፎታል።

በተወለደ በ3 ወሩ ወንዝ ላይ ጥለውት ተርሙት (የፈርኦን ልጅ) ወስዳ በቤተ መንግስት አሳድጋዋለች:: ሙሴ ያለችውም እርሷ ናት። 'ዕጓለ ማይ (ከውሃ የተገኘ) ለማለት ነው። ወላጆቹ ያወጡለት ስም ግን 'ምልክአም' ይባላል። ገና ሲወለድ ፊቱ እንደ መልአክ ያበራ ነበርና።

ቅዱስ ሙሴ 5 ዓመት በሆነው ጊዜ ፈርኦንን በጥፊ በመማታቱ ለፍርድ ቀርቦ እሳትን በመብላቱ አንደበቱ ኮልታፋ ሆኖ ቀርቷል። እናቱ ዮካብድ ሞግዚት ሆና ስላሳደገችው 40 ዓመት በሆነው ጊዜ የፈርኦንን ቤት ምቾትና የንጉሥ ልጅ መባልን ናቀ። ቅዱስ ዻውሎስ እንደሚለው በአሕዛብ ቤት ካለ ምቾት ከ #እግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን ሊቀበል ወዷልና። (ዕብ. 11÷24)

አንድ ቀንም ለዕብራዊ ወገኑ ተበቅሎ ግብጻዊውን ገድሎት ወደ ምድያም ሸሸ። በዚያም ለ40 ዓመታት የካህኑን ዮቶርን በጐች እየጠበቀ ኢትዮዽያዊቱን ሲፓራን አግብቶ ኖረ። ልጆንም አፈራ። 80 ዓመት በሞላው ጊዜ #እግዚአብሔር በደብረ ሲና ተናገረው። ሕዝቡንም ከባርነት ቀንበር እንዲታደግ ላከው፡፡ ሙሴም ከወንድሙ ጋር ግብጻውያንን በ9 መቅሰፍት በ10ኛ ሞተ በኩር መታ። እሥራኤልንም ነጻ አወጣ፡፡

ሊቀ ነቢያት የሠራቸው ሥራዎች ተዘርዝረው የሚያልቁ አይደሉም፦ እርሱ ባሕረ ኤርትራን ከፍሎ ሕዝቡን በደረቅ አሻግሯል፣ ግብጻውያንን ከነሠረገሎቻቸው በባሕር ውስጥ አስጥሟል፣ ለሕዝቡ መና ከደመና አውርዷል፣ ውሃን ከጨንጫ (ከዓለት) ላይ አፍልቁዋል፣ በብርሃን ምሰሶ መርቷቸዋል፣ በ7 ደመና ጋርዷቸዋል፣ ጠላቶቻቸውን ሁሉ ድል ነስቶላቸዋል፣ ቅዱስ ሙሴ ለ40 ዓመታት ሕዝቡን ሲመራ ከ #እግዚአብሔር ጋር ለ570 ጊዜ ተነጋግሯል።
#ነሐሴ_14

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ አራት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በእስክንድርያ ሀገር ድንቅ ተአምርን አደረገ፣ #የአባ_ስምዖንና የወዳጁ #የአባ_የዮሐንስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ሆነ፣ #ቅዱስ_ባስሊቆስ በሰማዕትነት ሞተ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መስቀለ_ክርስቶስ

ነሐሴ ዐሥራ አራት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በእስክንድርያ ሀገር ድንቅ ተአምርን አደረገ። ስለርሱም ከአይሁድ ብዙዎች አምነው በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ቴዎፍሎስ እጅ ተጠመቁ እርሱም ለቅዱስ ቄርሎስ የእናቱ ወንድም ነው። ይህም እንዲህ ነው በእስክንድርያ አገር ስሙ ፈለስኪኖስ የሚባል አይሁዳዊ ባለጸጋ ሰው ይኖር ነበር እርሱም እንደ አባቶቹ የኦሪትን ሕግ የሚጠብቅና #እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው።

ዳግመኛም ሙያተኛዎች ሁለት ድኃዎች ክርስቲያኖች አሉ በአንደኛውም ላይ ሰይጣን የስድብ መንፈስ አሳድሮበት ጓደኛውን ወንድሜ ሆይ #ክርስቶስን ለምን እናመልከዋለን እኛ ዶኆች ነን ይህ #ክርስቶስን የማያመልክ አይሁዳዊ ፈለስኪኖስ ግን እጅግ ባለጸጋ ነው አለው።

ጓደኛውም እንዲህ ብሎ መለሰለት ዕወቅ አስተውል የዚህ ዓለም ገንዘብ ከ #እግዚአብሔር የሆነ አይደለም ምንም አይጠቅምም ጥቅም ቢኖረው ጣዖትን ለሚያመልኩ ለአመንዝራዎች ለነፍሰ ገዳዮች ለዐመፀኞች ሁሉ ባልሰጣቸውም ነበር።

አስተውል የከበሩ ነቢያት ድኆች ችግረኞችም እንደነበሩ ሐዋርያትም እንደርሳቸው ችግረኞች እንደነበሩ። #ጌታችንም ድኆችን ወንድሞቼ ይላቸው እንደነበረ። ሰይጣን ግን የጓደኛውን ምክር እንዲቀበል ምንም ምን አልተወውም ሃይማኖቱን ምንም ምን አልተወውም ሃይማኖቱን ለውጦ ነፍሱን እስከማጥፋት ድረስ አነሣሣው ቀሰቀሰው እንጂ።

ከዚህም በኋላ ወደ ፈለስኪኖስ ሒዶ በአንተ ዘንድ እንዳገለግል ተቀበለኝ አለው። ፈለስኪኖስም እንዲህ ብሎ መለሰለት በሃይማኖቴ የማታምን አንተ ልታገለግለኝ አይገባም ከቤተ ሰቦቼም ጋራ የማትተባበር ልቀበልህ አይገባኝም። ሁለተኛም ይህ ጐስቋላ ወዳንተ ተቀበለኝ እኔም ወደ ሃይማኖትህ እገባለሁ ያዘዝከኝንም ሁሉ አደርጋለሁ አለው።

አይሁዳዊው ባለጸጋም ከመምህሬ ጋር እስከምማከር ጥቂት ታገሠኝ ብሎ ከዚያም ወደ መምህሩ ሒዶ ድኃው ክርስቲያናዊ ያለውን ሁሉ ነገረው መምህሩም #ክርስቶስን የሚክድ ከሆነ ግረዘውና ተቀበለው አለው።

አይሁዳዊውም ተመልሶ መምህሩ የነገረውን ለዚያ ድኃ ነገረው ያም ምስኪን የምታዙኝን ሁሉ አደርጋለሁ አለ። ከዚህም በኋላ ወደ ምኵራባቸው ወሰደው የምኵራቡም አለቃ በሕዝቡ ሁሉ ፊት እንዲህ ብሎ ጠየቀው። ንጉሥህ #ክርስቶስን ክደህ አይሁዳዊ ትሆናለህን እርሱም አዎን እክደዋለሁ አለ።

የምኵራቡም አለቃ #መስቀል ሠርተው በላዩ የ #ክርስቶስን ሥዕል እንዲአደርጉ መጻጻንም የተመላች ሰፍነግ በዘንግ ላይ አሥረው ከጦር ጋራ እንዲሰጡት አዘዘ ከዚያም ከተሰቀለው ላይ ምራቅህን ትፋ መጻጻውንም አቅርብለት #ክርስቶስ ሆይ ወጋሁህ እያልህ ውጋው አሉት።

ሁሉንም እንዳዘዙት አድርጎ በወጋው ጊዜ ብዙ ውኃና ደም ፈሰሰ ለረጂም ጊዜም በምድር እየፈሰሰ ነበር በዚያን ጊዜም ያ ከሀዲ ደርቆ እንደ ደንጊያ ሆነ። በአይሁድ ሁሉ ላይ ታላቅ ፍርሀት ወደቀባቸው በእውነት የአብርሃም ፈጣሪ ስለእኛ ተሰቅሏል እኛም ዓለምን ለማዳን የመጣ የሕያው #እግዚአብሔር ልጅ እርሱ እንደሆነ አመንበት እያሉ ጮኹ።

ከዚህም በኋላ አለቃቸው ከዚያ ደም ወስዶ የአንድ ዕውር ዐይኖችን አስነካው ወዲያውኑ አየ ሁሉም አመኑ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ ሒደው የሆነውን ሁሉ ነገሩት። ሊቀ ጳጳሳቱም ከካህናቱ ሁሉ ጋራ ተነሣ አባ ቄርሎስ ከእርሱ ጋራ አለ። ወደ አይሁድ ምኵራብም ሒዶ ውኃና ደም ከእርሱ ሲፈስ #መስቀሉን አገኘው ከዚያም ደም ወስዶ በግንባሩ ላይ ቀብቶ በረከትን ተቀበለ ሕዝቡንም ሁሉ ግንባራቸውን በመቀባት ባረካቸው።

ያንንም #መስቀል አክብረው ተሸክመው እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወስደው ያኖሩት ዘንድ አዘዘ። ደም የፈሰሰበትንም ምድር አፈሩን አስጠርጎ ለበረከትና ለበሽተኞች ፈውስ ሊሆን በሸክላ ዕቃ ውስጥ አኖረው።

ከዚህም በኋላ ፈለስኪኖስ ከቤተ ሰቦቹ ሁሉ ጋራ ሊቀጳጳሳት ቴዎፍሎስን ተከተለው ከአይሁድም ብዙዎቹ የቀደሙ አባቶቻቸው በሰቀሉት የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አጥምቋቸው ከእርሱ ጋራ አንድ አደረጋቸው ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው። ከዚህም በኋላ ለዘላለሙ ክብር ምስጉን የሆነ #እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ወደየቤታቸው ገቡ። እኛንም ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን በ #መስቀሉ ኃይል ያድነን አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳን_አባ_ስምዖንና_አባ_ዮሐንስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የአባ ስምዖንና የወዳጁ የዮሐንስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ሆነ። እሊህ ቅዱሳንም በአማኒው ዮስጦንስ ዘመን መንግሥት የነበሩ ናቸው እሊህም ወንድሞች የከበሩ ክርስቲያን ናቸው።

ከዚህ በኋላ ለከበረ #መስቀል በዓል ቅዱሳት መካናትን ሊሳለሙ ወደ ኢየሩሳሌም ሔዱ ሥራቸውንም አከናውነው ወደ አገራቸው ሲመለሱ በፈረሶቻቸው ተቀምጠው ወደ ኢያሪኮ ቀረቡ።

ዮሐንስም በዮርዳኖስ በረሀ ያለውን የመነኰሳቱን ገዳም አይቶ ወንድሙ ስምዖንን ወንድሜ ሆይ በእሊህ ገዳማት እኮ የ #እግዚአብሔር መላእክት ይኖራሉ አለው ዮሐንስም ከእርሳቸው ጋራ ከሆን አወን ልናያቸው እንችላለን አለው።

ከዚያም ከፈረሶቻቸውን ወርደው ለሰዎቻቸው ሰጥተው እስከምናገኛችሁ በየጥቂቱ ተጓዙ ብለው እንደሚጸዳዱ መስለው ወደ ዱር ገቡ።

የዮርዳኖስንም ጐዳና ተጒዘው ከሰዎቻቸው በራቁ ጊዜ እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ ጸሎት እናድርግ ከእኛም አንዳንችን ወደ መነኰሳቱ ገዳም በምታደርስ ጐዳና ቁመን ዕጣ እንጣጣል #እግዚአብሔር ከፈቀደ ዕጣችን ወደ ወጣበት እንሔዳለን።

ከዚህም በኋላ ስምዖን በዮርዳኖስ ጐዳና ቆመ ዮሐንስም ወደ ሀገራቸው በሚወስድ ጐዳና ላይ ቆመ ዕጣውንም በአወጡበት ጊዜ ዮርዳኖስ ጐዳና ላይ ወጣ እጅግም ደስ አላቸውና ስለ ደስታቸው ብዛት እርስ በእርሳቸው ተያይዘው ተሳሳሙ።

አንዱም አንዱ ወደኋላ እንዳይመለስ ስለጓደኛው ይጠራጠርና ይፈራ ነበር አንዱም ሁለተኛውን ይመክረውና ለበጎ ሥራ ያተጋው ነበር።

ዮሐንስ ስለ ስምዖን ይፈራ ነበር ስለ ወለላጆቹ ፍቅር አንዳይመለስ ስምዖንም ስለ ዮሐንስ ይፈራ ነበር እርሱ በዚያ ወራት መልከ መልካም የሆነች ሚስት አግብቶ ነበርና።

ከዚህም በኋላ ወደ #እግዚአብሔር ጸለዩ እንዲህም አሉ በውስጧ እንመነኵስ ዘንድ ለኛ የተመረጠች ገዳም ደጃፍዋ ክፍት ሆኖ ብናገኝ ምለክት ይሆናል።

የገዳሙም አለቃ ኒቆን የሚሉት በተሩፋት ፍጹም የሆነ ድንቆች ተአምራትን የሚያደርግ ሀብተ ትንቢት የተሰጠጠው ሲሆን በዚያች ሌሊት በጎቼ ይገቡ ዘንድ የገዳሙን በር ክፈተት የሚለውን ራእይ አየ።

ወደርሱም በደረሱ ጊዜ የ #ክርስቶስ በጎች ሆይ መምጣታችሁ መልካም ነው አላቸውና ከ #እግዚአብሔር ዘንድ እንደ ተላኩ ሰዎች አድርጎ ተቀበላቸው።

ከዚህም በኋላ አበ ምኔቱን የምንኵስናን ልብስ ያለብሳቸው ዘንድ ለመኑት እነርሱ በቆቡ ላይ የብርሃን አክሊል አድርጎ መላእክትም ከበውት አንዱን መነኰስ አይተዋልና ስለዚህም ፈጥነው ይመነኵሱ ዘንድ ተጉ።
አስቆረጣቸው እርሷን ግን ምንም ምን አልነካትም ሕዝቡም ይህን ተአምር አይተው የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሠላሳ ሺህ ዐሥራ ሁለት ሰዎች አምነው በሰማዐትነት ሞቱ ከሀዲው መኰንን ድዮስም በድንገት ሞተ።

ሦስተኛም መኰንን መጣ የከበረች ክርስጢናንም ይዞ ለአማልክት ትሠዋ ዘንድ አባበለት እርሷም እንዲህ አለችው። አንተና አማልክቶችህ ለዘላለም ወደ ማይጠፋ የገሀነም እሳት ትወርዳላችሁ። እጅግም ተቆጥቶ ወደ እሳት ማንደጃ ውስጥ እንዲጨምርዋት አዘዘ ምንም የነካት የለም።

ዳግመኛም ለአራዊት ይጥሏት ዘንድ አዘዘ እነርሱም የእግርዋን ትቢያ ላሱ እባቦችንም የሚያጠምደውን ነከሱትና ወዲያውኑ ሞተ።

ሁለተኛም ምላሷንና ጡቶቿን ቆረጡ የምላሷንም ቁራጭ አንሥታ ከመኰንኑ ዐይኖች ላይ ጣለችውና ዐይኖቹን አሳወረችው ። ቁጣውንም ተመልቶ ለእባቦች እንዲጥሏት አዘዘ አንዲቷም እባብ ልቧን ነደፈቻት አንዲቱ ደግሞ ጐኗን እንዲህም የምስክርነቷን ተጋድሎ ፈጸመች ነፍሷንም አሳልፋ የድል አክሊልን ተቀዳጀች ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስቷ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ለውረንዮስ_ሰማዕት

በዚህችም ዕለት በንጉሥ ዳስዮስ ቄሣር ዘመን ቅዱስ ለውረንዮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ በሃይማኖት የጸና ነው የክብር ባለቤት ስለ ሆነ ስለ #ክርስቶስ ሃይማኖት ሊቀ ዲቁና ተሹሞ የሊቀ ጵጵስናውን ገንዘብ ይጠብቅ ነበር።

ንጉሥ ስለርሱ ሰምቶ አምጥተው ከወህኒ ቤት እንዲአስገቡት አዘዘ በአስገቡትም ጊዜ በዚያ ዕውር ሰውን አገኘና አይኖችህ ይገለጡ ዘንድ በሕያው #እግዚአብሔር ልጅ አምነህ በስሙ ትጠመቃለህን አለው ዕውሩም አዎን ጌታዬ አለ።

ያን ጊዜም በውኃው ላይ ጸልዮ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አጠመቀው ያን ጊዜም አይኖቹ ተገለጠ። እንዲህም ብሎ ጮኸ በአገልጋዩ ለውረንዮስ ጸሎት ዐይኖቼን የገለጠ የክብር ባለቤት #ጌታ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ይክበር ይመስገን ብሎ ጮኸ። ይህንንም ድንቅ አይተው ብዙዎች አመኑ።

ንጉሡም በሰማ ጊዜ የከበረ ለውረንዮስን ወደርሱ ያቀርቡት ዘንድ አዘዘ በአቀረቡትም ጊዜ ለአማልክት እንዲሰዋ አግባባው እምቢ ባለውም ጊዜ ጥርሶቹን በደንጊያ ሰበሩ ልብሶቹንም ገፈው በብረት ዐልጋ ላይ አስተኝተው ሥጋው እስከሚቀልጥ ከበታቹ እሳትን አነደዱ።

እርሱም ነፍሱን እስከአሳለፈ ድረስ ወደ ፈጣሪው ይጸልይ ነበር። መላእክትም ሃሌ ሉያ እያሉ ተቀብለው ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አስገቡት።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_15)
#ነሐሴ_18

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_እለእስክንድሮስ አረፈ፣ የከበረና የተመሰገነ ሐዋርያ #ቅዱስ_እንድራኒቆስ መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እለእስክንድሮስ

ነሐሴ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን ቁጥሩ ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ጋር የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስ አረፈ። ይህም አባት ከአርዮስ ወገኖች ብዙ ችግር ደርሶበታል እርሱ ከወገኖቹ ጋር ሁኖ አርዮስን አውግዞ ከቤተክርስቲያን አሳዶት ነበርና።

በታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመን በኒቅያ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ሊቃውንት አርዮስን በጉባኤ አውግዘው ከቤተ ክርስቲያን ለይተው በአሳደዱት ጊዜ ወደ ንጉሡ ቈስጠንጢኖስ ጓደኞቹን ይዞ ገብቶ በእለእስክንድሮስና በአትናቴዎስ ላይ ነገር ሠራ ሁለተኛም እለእስክንድሮስ ከካህናቱ ጋር ይቀበለው ዘንድ እንዲያዝለት ንጉሡን ለመነው።

ንጉሡም ልመናውን ተቀብሎ መልእክተኞችን ልኮ አባት እለእስክንድሮስን አስመጥቶ እንዲህ አለው "አትናቴዎስ ትእዛዛችንን በመተላለፍ አርዮስን አልቀበልም ብሏል፤ እኛም አንተን እንዳከበርንህ አንተ ታውቃለህ አሁንም ትእዛዛችንን አትተላለፍ አርዮስንም ከውግዘቱ ፈትተህ ልባችንን ደስ አሰኝ" አለው ።

ቅዱስ እለእስክንድሮስም ለንጉሥ እንዲህ ብሎ መለሰለት "አርዮስን እኮን ቤተክርስቲያን አልተቀበለችውም። ልዩ ሦስትነትን አያመልክምና" ንጉሡም "አይደለም እርሱ በ #ሥሉስ_ቅዱስ ያምናል እንጂ" አለው ቅዱስ እለእስክንድሮስም " #ወልድ በመለኮቱ ከ #አብ#መንፈስ_ቅዱስ ጋራ ትክክል እንደሆነ የሚያምን ከሆነ በእጁ ይጻፍ" ብሎ መለሰለት።

ንጉሥም አርዮስን አስቀርቦ "ትክክለኛ ሃይማኖትህን ጻፍ" አለው አርዮስም በልቡ ሳያምን ' #ወልድ#አብ ጋራ በመለኮቱ ትክክል ነው' ብሎ ጻፈ በሐሰትም የከበረ ወንጌልን ይዞ ማለ። ንጉሡም ቅዱስ እለእስክንድሮስን "አሁን በአርዮስ ላይ ምክንያት አልቀረህም ትክክለኛ ሃይማኖቱን ጽፎአልና በከበረ ወንጌልም ምሎአልና" አለው ።

አባ እለእስክንድሮስም ንጉሡን እንዲህ አለው "በአባትህ በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እጅ የተጻፈ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ አባቶች በእጆቻቸው የጻፉትን እርሱንና ወገኖቹን ከቤተ ክርስቲያን እንዳሳደዷቸው የአርዮስን ክህደቱንና ውግዘቱን አትናቴዎስ አንብቦታል። ነገር ግን አንድ ሱባዔ በእኔ ላይ ታገሥ በዚህ ሱባዔ በአርዮስ ላይ አንዳች ነገር ካልደረሰ ይህ ካልሆነ ሃይማኖቱ መሐላውም እውነት ነው እኔም ተቀብዬ ከካህናቱ ጋር እቀላቅለዋለሁ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎትም ከእሳቸው ጋራ አንድ ይሆናል።"

ንጉሡም አባት እለእስክንድሮስን እንዲህ አለው "እወቅ እኔ ስምንቱን ቀኖች እታገሥሃለሁ አርዮስን ካልተቀበልከው በአንተ ላይ የፈለግሁትን አደርጋለሁ።" ከዚህም በኋላ ከንጉሡ ዘንድ ወጥቶ ወደ ማደሪያው ሔደ ቤተክርስቲያንን ከአርዮስ መርዝ ያድናት ዘንድ በዚያ ሱባዔ እየጾመና እየጸለየ ወደ #እግዚአብሔር ሲለምን ሰነበተ።

ከዚያም ሱባዔ በኋላ አርዮስ መልካም ልብስን ለበሰ ወደ ቤተክርስቲያንም ገብቶ በመሠዊያው ፊት ከካህናቱ ጋራ ተቀመጠ። ከዚህም በኋላ አባ እለእስክንድሮስ እያዘነና እየተከዘ ገባ ከኀዘኑም ብዛት የተነሣ የሚሠራውን አላወቀም የቅዳሴውንም ሥርዓት ሊጀምር ቆመ። ያን ጊዜ የአርዮስ ሆዱ ተበጠበጠና ወጥቼ ልመለስ አለ ይህንንም ብሎ ወደ መጸዳጃ ቦታ ወጣ። ሊጸዳዳም በተቀመጠ ጊዜ አንጀቱና የሆድ ዕቃው ሁሉ ወጣ በዚያውም ላይ ሞተ።

በዘገየም ጊዜ ሊፈልጉት ወጡ በመጸዳጃውም ቦታ ሬሳውን ወድቆ አገኙት። ለዚህም ለአባት እለእስክንድሮስ ነገሩት እርሱም አደነቀ የከበረች ቤተክርስቲያኑን ያልጣላት ምስጉን የሆነ #ክርስቶስንም አመሰገነው።

ንጉሡም በሰማ ጊዜ አደነቀ ከሀዲ አርዮስም በሐሰት እንደማለና በሽንገላ እንደጻፈ አወቀ። የዚህንም አባት የእለእስክንድሮስን ቅድስናውን ዕውነተኛነቱ ሃይማኖቱም የቀናች መሆኗን የአርዮስንም ሐሰተኛነቱንና ከሀዲነቱን ተረዳ።

አንድ የሆነ #አብ_ወልድ_መንፈስ_ቅዱስንም አመሰገነው መለኮታቸውም አንድ እንደሆነ ታመነ።

ይህም አባት በበጎ ሥራ ጸንቶ ኖረ ለምለም ወደ ሆነ እርጅናም ደርሶ ወደ ወደደው #ክርስቶስ ሔደ የሕይወት አክሊልንም አገኘ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እንድራኒቆስ

በዚህችም ቀን የከበረና የተመሰገነ ሐዋርያ እንድራኒቆስ መታሰቢያው ነው። ይህንንም ሐዋርያ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ መረጠው። እርሱም የ #እግዚአብሔርን መንግሥት እንዲሰብኩ ጌታ ከመከራው በፊት ከላካቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቆጠረ ነው።

በጽርሐ ጽዮንም #መንፈ_ቅዱስ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ የ #መንፈስ_ቅዱስን ስጦታ ተቀብሎ በብዙ አገሮች ውስጥ ሰበከ። በኒውብያ አገር ላይም ሐዋርያት በአንብሮተ እድ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት በውስጧም ሰበከ በጨለማ በድንቁርና የሚኖሩ ብዙዎች አረማውያንንም የክብር ባለቤት ወደሆነ ወደ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖት አስገባቸው።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያ ዮልዮስን ወሰደው በአንድነትም በብዙ አገሮች ዙረው አስተማሩ። ብዙ ሰዎችንም አጠመቁ ተአምራትንም በማድረግ ከሰዎች ላይ አጋንንትን አባረሩ። ብዙዎች በሽተኞችንም ፈወሱአቸው የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሰው የክብር ባለቤት የሆነ የ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አብያተ ክርስቲያናትን አነፁ። አገልገሎታቸውንም በፈጸሙ ጊዜ #ጌታችን ከድካም ወደ ዕረፍት ከኀዘንም ወደ ደስታ ሊወስዳቸው ወደደ።

ከዚህ በኋላ ሐዋርያ እንድራኒቆስ ታመመና ግንቦት ሃያ ሁለት ቀን አረፈ ቅዱስ ዮልዮስም ገንዞ በመቃብር አኖረው።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_18 ና_ዘወርኀ_ግንቦት_22)
ይስሐቅም ልጁን ልጄ ሆይ ፈጥነህ ያገኘህ ይህ ምንድነው አለው እርሱም ፈጣሪህ #እግዚአብሔር በፊቴ የሰጠኝ ነው አለው። ይስሐቅም ልጄ ቅረበኝ ልዳሥሥህ አንተ ኤሳው እንደሆንክ ወይም እንዳልሆንክ አለው በቀረበም ጊዜ ዳሠሰውም ቃልህ የያዕቆብ እጆችህ አድነህ ያመጣህልኝን በልቼ ነፍሴ ትመርቅህ ዘንድ አምጣልኝ አለው አቅርቦለት በላ ወይንም አመጣለት ጠጣ።

ይስሐቅም ልጄ ቅረበኝና ሳመኝ አለው ቀርቦም ሳመው የልብሱን ሽታ አሸተተው እነሆ የልጄ ልብስ ሽታው #እግዚአብሔር እንደባረከው እንደዱር አበባ ሽታ ነው አለ። እንዲህም ብሎ መረቀው ከሰማይ ጠል ከምድር ስብ ይስጥህ ሥንዴህን ወይንህንና ዘይትህን ያብዛልህ አሕዛብም ይገዙልህ አለቆችም ይስገዱልህ ለወንድሞችህም ጌታ ሁን የአባትህም ልጆች ይስገዱልህ። የሚረግምህም የተረገመ ይሁን ይህም በ #እግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ።

ይህም አባት ይስሐቅ ወደ መቶ ሰማንያ ዘመን ደረሰ አባታችን ይስሐቅም እንዲህ ብሎ ተናገረ ከዚህም በኃላ መልአክ ወደ ሰማይ ወሰደኝ አባቴ አብርሃምን አየሁትና ሰገድሁለት እርሱም ሳመኝ ንጹሕን ሁሉ ስለ አባቴ ተሰበሰቡና ወደ ውስጠኛው የአብ መጋረጃ ከበውኝ ከእኔ ጋራ ሔዱ እኔም ወድቄ ከአባቴ ጋራ ሰገድኩ።

የሚያመሰግኑ መላእክት ሁሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ የሚመሰገን አሸናፊ #እግዘአአብሔር ምስጋናው በሰማይና በምድር የመላ ነው እያሉ ጮኹ።

አባቴ አብርሃምን እኔ በቦታዬ ልዩ ነኝ ሰው ሁሉ ልጁን በወዳጄ ይስሐቅ ስም ቢሰይም በቤቱ ውስጥ በረከቴ ለዘላለም ይኖራል የቡሩክ ወገን የሆንክ አንተ ቡሩክ አብርሃም ሆይ መምጣትህ መልካም ነው። አሁንም በወዳጄ በልጅህ ይስሐቅ ስም የሚለምን ሁሉ በረከቴ በቤቱ ውስጥ ለዘላለም እንዲኖር ቃል ኪዳኔን አጸናለታለሁ አለው።

ትሩፋቱን ቅንነቱን ገድሉን የሚጽፍ ካለ ወይም በስሙ የተራበ የሚያጠግብ በመታሰቢያው ቀን የተራቆተ የሚያለብስ እኔ የማያልፈውን መንግሥት እሰጠዋለሁ።

አብርሃምም እንዲህ አለ አቤቱ ዓለሙን ሁሉ የያዝክ #አብ ሆይ ቃል ኪዳኑን ገድሉን ይጽፍ ዘንድ ካልተቻለው ቸርነትህ ትገናኘው አንተ ቸር መሐሪ ነህና አንጀራ የሌለው ችግረኛ ቢሆንም። #ጌታም እንዲህ ብሎ መለሰለት በወዳጄ በይስሐቅ በመታሰቢያው ዕለት ከሌሊት ጀምሮ በጸሎት ይትጋ አይተኛ እኔም መንግሥቴን ከሚወርሱ ጋራ ከበረከቴ እሰጠዋለሁ።

አባቴ አብርሃምም ሁለተኛ እንዲህ አለ በሽተኛ ድውይ ከሆነ ቸርነትህ ታግኘው #ጌታም እንዲህ አለ ጥቂት ዕጣን ያግባ ዕጣንን ካላገኘ የቃል ኪዳኑን መጽሐፍ ፈልጎ በልጅህ በወዳጄ በይስሐቅ መታሰቢያ ቀን ያንብበው። ማንበብም የማያውቅ ከሆነ ወደሚያነቡለት ሒዶ እሷን አስነብቦ ይስማ። ከእነዚህም ይህን ማድረግ ካልቻለ ወደ ቤቱ ገብቶ ደጁን ይዝጋ እየጸለየ መቶ ስግደቶችን ይስገድ እኔም የሰማይ የመንግሥት ልጅ አደረገዋለሁ።

ለቁርባን የሚሆነውንና መብራትን ያገባ እኔ ያልኩትን ሁሉ የሚያደርግ እርሱ የመንግሥተ ሰማያትን ርስት ይቀበላል። ቃል ኪዳኑንና ገድሉን ትሩፋቱን ለመጻፍ ልቡን ያበረታውን እኔ ስሙን በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ በሺው ዓመት ምሳ ላይም ይገኛል።

#እግዚአብሔርም ይህን ብዙ ነገርን በተናገረ ጊዜ ያዕቆብ አይቶ በመደንገጥ ነፍሱ ተመሠጠች ይስሐቅም ያዕቆብን አንሥቶ ልጄ ሆይ ዝም በል አትደንግጥ ብሎ ጠቀሰው ከዚህም በኃላ ሳመውና በሰላም አረፈ። ከኤሞር ልጆች በገዛው እናቱ ሣራ በተቀበረችበት በአብርሃም መቃብር ተቀበረ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ይስሐቅ አማላጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያዕቆብ

በዚችም ቀን ደግሞ #እግዚአብሔር እስራኤል ብሎ ስም ያወጣለትን የአባቶች አለቃ የሆነ የያዕቆብን የዕረፍቱን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶቻችን አዘዙን። ይህም ቅዱስ በበጎ ሥራ ሁሉ በመራራት በቅንነት በትሕትና በለጋስነት የአባቶቹን የአብርሃምንና የይስሐቅን መንገድ የተከተለ ሆነ።

ወንዱሙ ኤሳውም ብኩርናውን በምስር ንፍሮ ደግሞ በረከቱን ስለወሰደበት አብዝቶ ስለጠላው ሊገድለው ይፈልግ ነበር ስለዚህም አባቱ ይስሐቅና እናቱ ርብቃ ያዕቆብን ወደ ርብቃ ወንድም ወደ ላባ ሰደዱት።

እየተጓዘም ሳለ በአደረበት በረሀ ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ መሰላል የ #እግዚአብሔርም መላእክት በውስጡ ሲወርዱ ሲወጡ በሕልሙ አየ እንዲህም አለ ይህ የሰማይ ደጅ ነው ከዚህም የ #እግዚአብሔር ቤት ይሠራል።

በሶርያ ምድር ወደሚኖር ወደእናቱ ወንድም ወደ ላባ በደረሰ ጊዜ ሁለቱን ልጆቹን ልያንና ራሔልን አጋባው በዚያም የላባን በጎች እየጠበቀ ሃያ አንድ ዓመት ያህል ኖረ። ላባም የምሰጥህ ምንድን ነው አለው ያዕቆብም ምንም የምትሰጠኝ የለም አሁን ወደፊት የምነግርህን ነገር ካደረግህልኝ ዳግመኛ በጎችህን ፈጽሜ እጠብቃለሁ።

አሁን በጎችህ በፊት ይለፉና ከበጎችህ ሁሉ ጠጉራቸው ነጫጭ የሆኑትንና መልካቸው ዝንጉርጉር የሆነውንም ስለዋጋዬ ለይልኝ አለው። ዓይነቱ ዝንጉርጉር ያልሆነውና መልኩ ነጭ ያልሆነው ሁሉ ግን ላንተ ይሁን አለው። ላባም እንዳልክ ይሁን አለ።

በዚያችም ቀን ነጩንም ቀዩንም ዝንጉርጉሩንም መልኩ ዳንግሌ የሆነውንም የፍየሉንም አውራ ለይቶ ለልጆቹ ሰጠ። በእነርሱና በያዕቆብ መካከል ሦስት ቀን የሚያስኬድ ጎዳና ርቀው ሔዱ ያዕቆብ ግን የቀሩትን የላባን በጎች ይጠብቅ ነበር።

ያዕቆብም የልምጭ በትርንና ታላቅ የሎሚ በትርን ወስዶ ቅረፍቱን ልጦ ጣለው ያዕቆብ የላጣቸው በትሮች ነጫጭ ሁነው ታዩ። እነዚያንም በትሮች በጎች ከሚጠጡበት ገንዳ ላይ ጣላቸው በጎች ውኃ ሊጠጡ በመጡ ጊዜ እነዚያ በትሮች በፊታቸው ሁነው ይታዩ ዘንድ። መጥተውም በጠጡ ጊዜ እነዚያን በትሮች አስመስለው ፀንሰው ነጩንና ሐመደ ክቦውን ዝንጉርጉሩን ወለዱ።

ያዕቅብም አውራ አውራዎቹን በጎች ለየ አውራ አውራውን ከለየ በኃላ እንስት እንስቶቹን በጎች ለይቶ ዝንጉርጉር ሐመደ ክቦና ነጭ በሆኑ አውራዎች ፊት አቆማቸው የራሱንም በጎች ለያቸው እንጂ ከላባ በጎች ጋራ አልቀላቀላቸውም።

ያዕቆብም እጅግ ፈጽሞ ባለጸጋ ሆነ ሴቶችንም ወንዶችንም አገልጋዩችን ገዛ ብዙ ከብት ላሞችን በጎችን ግመሎችንና አህዮችን ገዛ። ያዕቆብም ወደአገሩ በተመለሰ ጊዜ እስከ ንጋት ድረስ አንድ ሰው ሲታገለው አደረ ከእርሱም ጋራ ሲታገል እንዳልቻለው ባየ ጊዜ እርም የሚሆንበት ሹልዳውን ያዘው ጎህ ቀድዷልና ልቀቀኝ አለው ካልመረቅከኝ አልለቅህም አለው።

ስምህ ማን ይባላል ቢለው ስሜ ያዕቆብ ነው አለው እንግዲህ ስምህ ያዕቆብ አይባል እስራኤል ይባል እንጂ አለው ከ #እግዚአብሔርና ከሰው ጋራ መታገልን ችለሃልና።

ከዚህም በኃላ ስለ ልጁ ዮሴፍ ብዙ ኀዘን አገኘው ወንድሞቹ ወደ ግብጽ ሸጠውታልና በጠየቃቸውም ጊዜ ክፉ አውሬ በልቶታል አሉት ከልቅሶውም ብዛት የተነሣ ዐይኖቹ ታወሩ።

ከዚህም በኃላ ታላቅ ረሀብ ሆነ በግብጽ አገር እህል የሚሸጥ መሆኑን ያዕቆብ ሰማ ሥንዴ ይሸምቱ ዘንድ ልጆቹን ላካቸውና ወደ ዮሴፍ ደረሱ ንጉሥ ሆኖም አግኘተውት ሰገዱለት ወንድማቸው እንደሆነም አላወቁትም እርሱ ግን አውቋቸዋል ሥንዴውንም ሰጥቶ አስናበታቸው ሁለተኛም በተመለሱ ጊዜ ራሱን ገለጠላቸውና ወደዚህ ስለ ሸጣችሁኝ አትፍሩ እመግባችሁ ዘንድ በፊታችሁ #እግዚአብሔር ለሕይወት ልኮኛልና አላቸው።

አሁንም ፈጥናችሁ ሒዱና ለአባቴ ንገሩት ልጅህ ዮሴፍ እንዲህ ይላል በሉት ለግብጽ አገር ሁሉ #እግዚአብሔር ጌታ አድርጎኛል ፈጥነህ ና በዚያ ልኑር አትበል።
"በስመ #አብ_ወወልደ_ወመንፈስ_ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

እንኳን #የጌታችን_የአምላካች_የመድኃኒት #የኢየሱስ_ክርስቶስ_ዳግም_ምጽአት_ስለ_ዓለም_መጨረሻ#ስለ_ምሥጢረ_ትንሣኤ ለሚነገርበት ለዓመቱ የመጨረሻ #ዕለተ_ሰንበት (እሑድ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላም በጤና አደረሰን።

#በዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፪ "ከመ እንተ መብረቅ ዘይወጽእ እምጽባሕ ወያስተርኢ እስከ ዓረብ ከማሁ #ምጽአቱ_ለወልደ_እግዚአብሔር ምስለ ኃይል ሰማያት በንጥረ መባርቅት (ከማሁ) ምስለ አዕላፍ መላእክት ወኵሎሙ ሊቃነ መላክት (ከማሁ) አክሊለ አክሊላት ዲበ ርእሶሙ ለካህናት። ትርጉም፦ መብረቅ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ እንዲታይ ከመላእክት አለቆች ሁሉ ጋር ከሰማያት ኃይል ጋር በመብረቆች ብልጭታ በካህናት ራስ ላይ አክሊልን የሚቀዳጅ #የወልደ_እጓለ_እመሕያው_የክርስቶስ ምጽአት እንዚሁ ነው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ

#የኢትዮጵያ_ኦርቶዶክስ_ተዋሕዶ_ቤተ_ክርስቲያን #ስለ_ዳግም_ ምጽአትና_ስለ_ዓለም_መጨረሻ፣ ስለ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንም ሁልጊዜ የምታስተምር ቢሆንም በተለይ በዐቢይ ጾም ውስጥ "ደብረ ዘይት" በሚለው ዕለት ሰንበትና በዓመቱ መጨረሻም በወርኃ ጳጒሜን ስለ ዳግም ምጽአትና ስለ ዓለም ፍጻሜ ከቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን የሚመለከቱ ጥቅሶችን እያነበበችና ምዕመናንን እያስጠነቀቀች በየጊዜም ትኵረት ሰጥታ ታስተምራለች። በእነዚህ ወቅቶች በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው መዝሙር፣ ቅዳሴና ትምህርቱም ሁሉ ይህንኑ የተመለከተ ነው።