TIKVAH-ETHIOPIA
1.4M subscribers
54.8K photos
1.37K videos
198 files
3.65K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#update BBC-ቤንሻንጉል⬇️

በቤንሻንጉል ጉምዝ በተፈጠረ ግጭት ከ50 ሺህ ሰዎች በላይ #ሲፈናቀሉ የሰዎች ሕይወት መጥፋቱ ተሰማ።

መስከረም 16/2011 ዓ.ም የካማሼ ዞን አመራሮች ከምዕራብ ኦሮሚያ አስተዳደር ጥምር ኮሚቴ ጋር የነበራቸውን ስብሰባ አጠናቅቀው እየተመለሱ በነበሩ የዞን፣ የወረዳ አመራሮችና የፀጥታ ኃይሎች ላይ በተከፈተው ተኩስ የ4 ሰዎች ሕይወት ማለፉን ተከትሎ በተወሰኑ ከኦሮሚያ ጋር በሚዋሰኑ ስፍራዎች በተከሰተ ግጭት ሰዎች #መሞታቸውን፣ መፈናቀላቸውን ቤቶች መቃጠላቸውን የቤንሻንጉል ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አበራ ባይታ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

በተለይ በበሎይ ጅጋንፎይ ወረዳ ስር ሳይ ዳለቻ ቀበሌ ግጭት የነበረ ሲሆን በግጭቱም 75 ቤቶች ተቃጥለዋል ብለዋል። በዚሁ ወረዳ ጅጋንፎይ ቀበሌ በጭበጭ በምትባል አካባቢ ላይ ቤቶች መቃጠላቸውን ጠቅሰው ሌሎች ቀበሌዎችም ላይ ተመሳሳይ ግጭቶች መከሰሰታቸውን ተናግረዋል።

በበሎይ ጅጋንፎ ሶቤይ ከተማ ላይ በርካታ ሰዎች ተፈናቅለዋል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በሶጌ ዙሪያ ባሉ ቀበሌዎች ልቢጋ፣ ሳይ ዳላቻ፣ ታንካራ ቀበሌዎች በርካታ ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን አስረድተዋል።

"በተንካራ 105 ቤቶች ተቃጥለዋል 3 ሰዎችም ህይወታቸው አልፏል" ያሉት መስተዳድሩ በበጭበጭ 1 ሰው መሞቱንና አንገርባጃ ቀበሌ 2 ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው አስረድተዋል። እንደ ክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ገለፃ ወደ ኦሮሚያ ክልል የተፈናቀሉ እና በስጋት ምክንያት ወደ ጫካ የገቡ ሰዎች ያሉ ሲሆን ቁጥራቸው ምን ያህል ነው የሚለውን ግን የተጠናቀረ መረጃ የለኝም በማለት ሳይናገሩ ቀርተዋል።

የተፈናቀሉት ሰዎች ከቤንሻንጉል ብቻ ሳይሆን ክልሉን ከሚያዋስኑት የኦሮሚያ ቀበሌዎችም እንደሆነ የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ሳስጋ ወረዳ ዱራበሎ፣ ካምፕ፣ በሎበሬዳ፣ ስምንተኛ ከሚባሉት ቀበሌዎች በስጋት ምክንያት ወደ ነቀምትና በሎበሬዳ ወደሚገኙ ማዕከሎች #ተፈናቅለው እንደሚገኙ ተናግረዋል።

የምሥራቅ ወለጋ ዞን አስተዳደርና ፀጥታ ኃላፊ የሆኑት አቶ ታከለ ቶሎሳ ለቢቢሲ እንደተናገሩት በቤንሻንጉል ክልል የኦሮሚያ አዋሳኝ ቀበሌዎች በተከሰተው ግጭት የሞቱት ሰዎች ቁጥር 12 ደርሷል። ከዚህ በተጨማሪም 14 ሰዎች የቆሰሉ ሲሆን እነዚህም በሳስጋ ወረዳ ጤና ጣቢያና በነቀምት ሆስፒታል ህክምና እያገኙ መሆናቸውን ገልፀዋል።

እንደ ኃላፊው ገለፃ ከሆነ ቀያቸውን ጥለው ወደ ኦሮሚያ የተሰደዱ ሰዎች ቁጥር 50 ሺህ ደርሷል። እነዚህ ሰዎች የተፈናቀሉት ከበሎይ ጅጋንፎና ያሶ ሲሆን ከኦሮሚያ አዋሳኝ ወረዳዎች ደግሞ ሀሮ ሊሙ፣ ሶጌና ሳስጋ አካባቢዎች ነው።

አቶ ታከለ ጨምረውም ከእነዚህ አካባቢዎች የሚፈናቀሉ የኦሮሞ እና የአማራ ተወላጆችች ቁጥር በየእለቱ እየጨመረ መሆኑን ገልፀዋል። የተፈናቀሉት ሰዎች ሳስጋ ወረዳ፣ ነቀምት ከተማ፣ ሀሮ ሊሙ ወረዳና ጉቶ ጊዳ ወረዳ ውስጥ ኡኬ ከተማ ተጠልለው እንደሚገኙ ጨምረው አስረድተዋል።

በምሥራቅ ወለጋ የሀሮ ሊሙ ወረዳ ኮሙኑኬሽን ፅህፈት ቤት ኃላፊ በበኩላቸው አቶ #ዱጋሳ_ጃለታ ከቤንሻንጉል ክልል 7 ቀበሌዎች 20 ሺህ ሰዎች መፈናቀላቸውን ለቢቢሲ የተናገሩ ሲሆን እስካሁን ባላቸው መረጃ በወረዳው ብቻ 5 ሰዎች ሞተዋል።

2 #ነፍሰጡር እናቶች መንገድ ላይ መውለዳቸውን የተናገሩት አቶ ዱጋሳ ህፃናት፣ እናቶችና አቅመ ደካሞች የመኪና መንገድ ባለመኖሩ የተነሳ ለመሸሽ አዳጋች እንደሆነባቸውም ጨምረው አስረድተዋል።

በቤንሻንጉል ክልል #ግጭት በተከሰተባቸው በበሎይ ጅጋንፎይ ወረዳ #ሦስት አካባቢዎች እንዲሁም በካማሼ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ሰፍረው እንደሚገኙ የተናገሩት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በተለያየ ጊዜ ምርት በሚደርስበት አካባቢ በክፍፍል ወቅት በተደጋጋሚ ግጭቶች እንደሚነሱ ነገር ግን እነዚህን ወስዶ #ብሄር ተኮር ግጭት ነው ማለት እንደማይቻል አስረድተዋል።

የምሥራቅ ወለጋ ዞን አስተዳደርና ፀጥታ ኃላፊ የሆኑት አቶ ታከለ ቶሎሳ በበኩላቸው እስካሁን ድረስ 40 ሰዎች ከቤንሽንጉል 5 ሰዎች ደግሞ ከኦሮሚያ #በመከላከያ ሰራዊት ቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን ለተፈናቀሉ ሰዎች የአካባቢው ማህበረሰብ #እርዳታ እያደረገላቸው መሆኑን ከመንግሥት ደግሞ አስፈላጊው ድጋፍ እየተጠበቀ እንደሆነ ተናግረዋል።

ምንጭ፦ BBC የአማርኛው አገልግሎት

@tsegabwolde @tikvahethiopia
በነጆው ጥቃት ከተገደሉት አንዱ የማዕድን ኩባንያው ባለቤት ነበር፦
.
.
ትናንት በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ነጆ ወረዳ ሁምነ ዋቀዮ በተባለ ቀበሌ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት #የአምስት ሰዎች መገደላቸውን የኦሮሚያ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ አስታውቆ ነበር።

ማክሰኞ ዕለት በታጠቂዎቹ ጥቃት የተገደሉት አምስት ሰዎች ሰንራይዝ በሚባል በአካባቢው የማዕድን ማውጣት ሥራ ላይ ለተሰማራ ኩባንያ የሚሰሩ እንደነበር ታውቋል።

በጥቃቱ የተገደሉት ሦስት ኢትዮጵያዊያን እና ሁለት የውጪ ሀገራት ዜጎች ሲሆኑ እነሱም የህንድና የጃፓን ዜግነት ያላቸው እንደሆ የአካባቢው ኮማንድ ፖስት አባል የሆኑት አቶ #አደም_ኢስማኤል ለቢቢሲ አረጋግጠዋል። ከተገደሉት አራቱ ወንዶች ሲሆኑ አንዷ የውጪ ዜጋ ሴት ናት።

እነዚህ የጥቃቱ ሰለባዎች ከማዕድን ኩባንያው ጋር ይሰሩ የነበሩ ሲሆን አንደኛው የኩባንያው ባለቤት እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።

አቶ #አለማየሁ_በቀለ ይህንን የማዕድን ማውጣት ሥራ ለመጀመር #ሦስት ዓመታትን የፈጀ ጥናት ማከናወኑንና የምርት ሥራውን ለመጀመር በተቃረበበት ወቅት ከአራት ባልደረቦቹ ጋር በታጣቂዎቹ መገደሉን የቅርብ ጓደኛው አቶ አቦማ አምሳሉ ለቢቢሲ ተናግሯል።

አቶ አለማየሁ ከአንድ ወር በፊትም በሥራው አካባቢ በድንጋይ በተፈጸመ ጥቃት በመኪናው ላይ የመሰባበር ጉዳት የደረሰበት ሲሆን፤ ከአካባቢው ወጣቶችና ህብረተሰብ ጋር ለመግባባትና ከሥራው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማድረግ ለመወያየት ዕቅድ እንደነበረው ጓደኛው አቶ አቦማ ያስታውሳል።

አቶ አለማየሁ በቀለ ተወልዶ ያደገው ጊምቢ ውስጥ ሲሆን ነዋሪነቱ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ነበር። እንዲሁም ባለትዳርና የሦስት ልጆች አባት፤ የመጀመሪያ ልጁም ገና አምስት ዓመቱ እንደሆነ አብሮ አደግ ጓደኛው ጨምሮ ገልጿል።

ከአቶ አለማየሁ ጋር አብረው በጥቃቱ ከተገደሉት አንደኛው የመኪናው ሹፌር ሲሆን ሌሎቹ ግን በማዕድን ሥራው የሚረዱት ባለሙያዎች ነበሩ። ጃፓናዊቷና ሕንዳዊው ሥራውን ለማቀላጠፍ በዕውቀትና በልምዳቸው እንዲያግዙት የቀጠራቸው ባለሙያዎች እንደሆኑም ተገልጿል።

ግድያው ከተፈጸመ በኋላ የወጡ መረጃዎች የድርጊቱ ፈጻሚዎች ማንነታቸው እንዳልታወቀ የያመለከቱ ቢሆንም አመሻሽ ላይ የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር በብሔራዊው ቴሌቪዥን ላይ ቀርበው ታጣቂዎቹ "ኦነግ ሸኔ" የተባለው ቡድን አባላት መሆናቸውን ገልጸዋል።

ምክትል ኮሚሽነሩ ጀነራል ረታ በላቸው እንደተናገሩት፤ አምስቱን ሰዎች በመግደል መኪናቸውን ያቃጠሉት "በአካባቢው እየተዳከመ የመጣው የሸኔ ቡድን አባላት ናቸው" በማለት የጸጥታ ኃይሉም አስፈላጊውን እርምጃ ይወስዳል ብለዋል።

ግድያውንና ምክትል ኮሚሽነሩ የተናገሩትን በተመለከተ ምላሽ እንዲሰጡ የኦነግ ቃል አቀባይ የሆኑትን አቶ ቶሌራ አደባን ቢቢሲ ጠይቆ "የድርጅቱን ወታደሮች በተመለከተ የዕርቅ ኮሚቴው የያዘው ጉዳይ በመሆኑ ሃሳብ መስጠት አንችልም" ብለዋል።

ነገር ግን በተፈጸመው ግድያ እጅጉን ማዘናቸውንና አስፈላጊው ማጣራት መደረግ እንዳለበት አቶ ቶሌራ ጨምረው ተናገረዋል።

ቀደም ባሉት ጊዜያት በምዕራብ ኦሮሚያ ከሚፈጸሙ ጥቃቶችና የጸጥታ ችግሮች ጋር በተያያዘ የኦነግ ስም በሚነሳበት ጊዜ ድርጅቱ በሚሰጠው ምላሽ ላይ መንግሥት ላይ ክስ ያቀርብ የነበረ ሲሆን አሁን ግን ከዚህ ተቆጥቧል።

ምንጭ፦ ቢቢሲ
@tsegabwolde @tikvahethiopia
" ታዳጊዎቹ በአሁኑ ወቅት በፖሊስ ስር ነው የሚገኙት " - የአዲስ አበባ ፖሊስ

የአዲስ አበባ ፖሊስ በአንድ አካባቢ የሚኖሩ 7 ታዳጊዎች #እንደጠፉ እና #እንደታገቱ ተደርጎ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን እና ማህበራዊ ሚዲያዎች እየተሰራጨ ያለው መረጃ እውነትነት የጎደለውና የተዛባ ነው አለ።

ፖሊስ መረጃው እውነትነት የጎደለውና የተዛባ ስለመሆኑ #አረጋግጥላችኃለሁ ብሏል።

ታዳጊዎቹ በአሁኑ ወቅት በፖሊስ ስር እንደሚገኙም ገልጿል፡፡

ፖሊስ ምን አለ ?

- #አራት ወንድ እና #ሦስት ታዳጊ ሴቶች በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 2 " መካኒሳ ቆሬ " አካባቢ ከሚገኘው የወላጆቻቸው መኖሪያ ቤት እንደጠፉ እና ታግተዋል በሚል በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን እና ማህበራዊ ሚዲያዎች የተሰራጨው መረጃ ትክክል አይደለም።

- ታዳጊዎቹ ለመጥፋት በማሰብ ከወላጆቻቸው መኖሪያ ቤት ልብሶቻቸውን ይዘው እንደወጡ እና በልዩ ልዩ ምክንያቶች ከቤተሰቦቻቸው ተነጥለው መኖር እንደሚፈልጉ በሰጡት ቃል ገልፀዋል።

- በልመና ተግባር ላይ ተሰማርተውም ባገኙት ገንዘብ የተወሰኑ የቤት ቁሳቁስ በማሟላት ሰባቱም በቦሌ ክ/ከተማ ወረዳ 12 ልዩ ቦታው " ቡልቡላ " አካባቢ በ1 ሺ 800 ብር መኖሪያ ቤት ተከራይተው #ሦስቱ ወንዶችና #ሦስቱ ሴቶች #የፍቅር_ግንኙነት በመመስረት በጋራ እየኖሩ እንደሚገኙ እራሳቸው በሰጡት ቃል ተናግረዋል።

- የጉዳዩን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባትና ከተለያዩ ቦታዎች መረጃ በማሰባሰብ በተደረገው ክትትል ያሉበትን ቦታ እና ሁኔታ ማወቅ ተችሏል።

- ታዳጊዎቹ የስነ-አእምሮና ተያያዥ የጤና ምርመራ እንዲያገኙ እንዲሁም ማህበራዊ ችግራቸው ሊፈታ በሚችልበት ሁኔታ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተሰራ ነው።

- አንዳንድ መገናኛ ብዙኃንና ማህበራዊ ሚዲያዎች መረጃን ስላገኙ ብቻ  የሚያስከትለውን አሉታዊ ጫና ታሳቢ ሳያደርጉ ዜናውን ማሰራጨታቸው በህብረተሰቡ የእለት ከእለት እንቅስቃሴ ላይ አሉታዊ ጫና የሚያስከትል መሆኑን ግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚጠበቅባቸው ሊገነዘቡ ይገባል።

- ወንጀልን በማጣራት እውነትን የማፈላለግ የምርመራ ስራ ጊዜን የሚጠይቅ ተግባር መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።

(አዲስ አበባ ፖሊስ)

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#አማራ : ለወራት የቀጠለው የትጥቅ ግጭት ዐውድ እና አሉታዊ የሰብአዊ መብቶች እንድምታው " ተፋላሚ ኃይሎች ሲቪል ሰዎችንና ንብረቶችን፣ የሕዝብ አገልግሎቶችን እና መሠረተ ልማቶችን ዒላማ ከማድረግ ሊቆጠቡ፣ መንግሥት የማኅበራዊ አገልግሎቶች እዲቀጥሉ አስቻይ ሁኔታ ሊፈጥር ይገባል። " በአማራ ክልል ጉዳይ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዛሬ የተላከልን መግለጫ ከላይ ተያይዟል። መግለጫው በክልሉ በተለያዩ…
#አማራ

በአማራ ክልል ለወራት ከቀጠለው የትጥቅ ግጭት ጋር በተያያዘ በርካቶች በድሮን ጥቃት መገደላቸው እና በክልሉ ከፍርድ ውጭ ግድያዎች መቀጠላቸውን ዛሬ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከተላከልን መግለጫ መረዳት ችለናል።

ከኢሰመኮ በደረሰን መግለጫ ፤ ከሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም. ጀምሮ ባለው ጊዜ ውስጥ የአማራ ክልል ሁሉም ዞኖች በተለያየ ደረጃና ጊዜ የትጥቅ ግጭት ተካሂዶባቸዋል።

በተጨማሪም እነዚህ አካባቢዎችና ወረዳዎች በአንድ ወቅት ላይ በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች በሌላ ወቅት ደግሞ በታጣቂው ቡድን (በተለምዶ ፋኖ በመባል የሚታወቀው) በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የትጥቅ ግጭቱ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ በከባድ መሣሪያ እና አልፎ አልፎ በአየር / ድሮን ድብደባ ጭምር የታገዘ ነው።

በግጭቱ ዐውድ ውስጥ #የአየር /#ድሮን መሣሪያን ጨምሮ በከባድ መሣሪያዎች ጥቃት የተነሳ በሲቪል ሰዎች ላይ ሞት እና የአካል ጉዳት የደረሰ ሲሆን ፣ ሰዎች መኖሪያ አካባቢያቸውን ጥለው ለመሸሽ ተገደዋል።

ለምሳሌ ፦

- በሰሜን ሸዋ ዞን፣ በረኸት ወረዳ፣ ' መጥተህ ብላ ' ከተማ ጥቅምት 5 ቀን 2016 ዓ.ም. በተፈጸመ የድሮን ጥቃት የአንድ ዓመት ከሰባት ወር ሕፃንን ጨምሮ በርካታ ሲቪል ሰዎች #ተገድለዋል፤ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

- በደብረ ማርቆስ ከተማ ጥቅምት 8 ቀን 2016 ዓ.ም. በተፈጸመ የድሮን ጥቃት  ቢያንስ 8 ሲቪል ሰዎች ተገድለዋል።

- በደንበጫ ከተማ ጥቅምት 3 ቀን 2016 ዓ.ም. በከባድ መሣሪያ ድብደባ ምክንያት ሲቪል ሰዎች ላይ የሞትና የአካል ጉዳት ደርሷል።

ኮሚሽኑ እነዚህን መረጃዎች ያገኘው የአካባቢውን ነዋሪዎች እና የዓይን ምስክሮችን በማነጋገር ነው።

በአንዳንድ አካባቢዎች ጥቃትን አልያም ግጭትን በመሸሽ ነዋሪዎች ሙሉ በሙሉ ከቀያቸው ተፈናቅለው በአሳሳቢ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ለማረጋገጥ ተችሏል።

በምንጃር ወረዳ ውስጥ የአውራ ጎዳና ጎጥ ነዋሪዎች ከመስከረም 6 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ ከቀያቸው ተፈናቀለው ቢያንስ 3ዐዐዐ የሚሆኑት አሞራ ቤቴ ቀበሌ በሚገኝ አንድ ትምህርት ቤትና ክፍት ሜዳ ላይ (በዛፍ ሥር) ተጠልለው የሚገኙ ሲሆን፣ ሌሎች ቁጥራቸው ያልታወቀ መተሃራና አዋሽን ጨምሮ ወደ የተለያዩ አካባቢዎች ተፈናቅለዋል።

ለተፈናቃዮች የተወሰነ ድጋፍ በማኅበረሰቡና እና በአንድ ተራድዖ ድርጅት የተደረገ ቢሆንም፣ በቂ ባለመሆኑ በአሳሳቢ ሁኔታ እንደሚገኙ ለመረዳት ተችሏል።

የነዋሪዎችን መፈናቀል ተከትሎ ሰብላቸው እንደወደመ፣ ንብረታቸው እንደተዘረፈ፣ የቤቶቻቸው ጣራያ እና በር እየተነቀለ እንደተወሰደ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ቤቶቻቸውን ከአጎራባች ክልል በመጡ ኃይሎች በኮንስትራክሽን መሣሪያዎች ጭምር ማፍረስ እንደተጀመረ ኢሰመኮ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎችና የመንግሥት ኃላፊዎች አስረድተዋል።

በመንግሥት የጸጥታ ኃይል አባላት የሚፈጸሙ ከሕግ ውጪ የሆኑ ግድያዎች አሁንም መቀጠላቸውን ኢሰመኮ ተዓማኒ መረጃዎችን እየተቀበለ እንደሚገኝ ገልጿል።

ግጭቱ በተካሄደባቸው አካባቢዎች የመንግሥት የጸጥታ አካላት በመንገድ ላይ ወይም ቤት ለቤት ፍተሻ በማድረግ ከያዟቸው በርካታ ሲቪል ሰዎች ውስጥ ፦

- " ፋኖን ትደግፋላችሁ "

- " ለፋኖ መረጃ ትሰጣላችሁ "

- " መሣሪያ አምጡ "


- " የተኩስ ድምጽ ስለተሰማበት አቅጣጫ መረጃ ስጡ " በሚልና ይህንን በመሰሉ ምክንያቶች ከሕግ ውጭ የሆኑ ግድያዎች መፈጸማቸውን የሚያሳዩ ተዓማኒ መረጃዎች ተገኝተዋል።

እንደማሳያ ፦

▪️በባሕር ዳር ሰባታሚት አካባቢ መስከረም 29 እና 30 ቀን 2016 ዓ.ም. #ሦስት_ወንድማማቾችን ጨምሮ በርካታ ሲቪል ሰዎች ተገድለዋል።

▪️በሰሜን ጎጃም ዞን፣ አዴት ከተማ መስከረም 29 ቀን 2016 ዓ.ም. ፍልሰታ ደብረ ማሪያም የሚኖሩ 12 የአብነት ተማሪዎችን ጨምሮ ሌሎች ሲቪል ሰዎች ተገድለዋል።

▪️ በምሥራቅ ጎጃም ዞን፣ አማኑኤል ከተማ ጥቅምት 3 ቀን 2016 ዓ.ም. ቢያንስ 8 ሲቪል ሰዎች በቤት ለቤት ፍተሻ እንደተገደሉ ለማወቅ ተችሏል።

▪️በምሥራቅ ጎጃም ዞን፣ ጎንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ፣ ግንደወይን ከተማ ሞጣ በር ተብሎ በሚጠራ አካባቢ መስከረም 18 ቀን 2016 ዓ.ም. አንድ በጥይት የቆሰለን ግለሰብ እናቱና እህቱ በባጃጅ አሳፍረው ወደ ሕክምና ተቋም በመውሰድ ላይ እያሉ፣ የመንግሥት የጸጥታ አካላት ባጃጁን አስቁመው ሁሉንም ተሳፋሪዎች ካስወረዱ በኋላ " የቆሰለው እኛን ሲዋጋ ነው " በሚል ምክንያት የባጃጅ አሽከርካሪውን ጨምሮ አራቱን ሰዎች በጥይት እንደገደሏቸው ኮሚሽኑ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች አስረድተዋል።

በባሕር ዳር፣ በፍኖተሰላም፣ በጎንደር እና በወልድያ ከተሞች በትጥቅ ግጭቱ ቆስለው ሕክምና ሲከታተሉ የነበሩ የተወሰኑ ሲቪል ሰዎች እና የታጣቂ ቡድኑ አባላት በመሆን በመንግሥት የጸጥታ አካላት የተጠረጠሩ ሰዎች ሕክምናቸው እዲቋረጥ ተደርጎ #ወዳልታወቀ_ስፍራ ከተወሰዱ በኋላ ፣ ከፊሎቹ ከተወሰኑ ቀናት በኋላ ወደ ሕክምና ተቋማቱ ሲመለሱ ቀሪዎቹ ያሉበት ሁኔታ ይህ መግለጫ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ ማረጋገጥ አልተቻለም።
 
በሌላ በኩል በየደረጃው የሚገኙ ሲቪል የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች፣ ግድያዎችና እገታዎች በታጠቁ ኃይሎች ተፈጽመዋል።

ለምሳሌ ፦

መስከረም 28 ቀን 2016 ዓ/ም የአማራ ክልል ምክር ቤት የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢን ጨምሮ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ከባሕር ዳር ወደ ደብረ ታቦር ሲሄዱ ' አለምበር ከተማ ' አካባቢ በታጣቂዎች ተገድለዋል።

በተለያዩ የክልሉ አካባቢዎች ማረሚያ ቤቶችና ፖሊስ ጣቢያዎች ላይ ጥቃት በመሰንዘር ታራሚዎችና ተጠርጣሪዎች እንዲያመልጡ ተደርጓል። 
 
ኮሚሽኑ ባደረገው ክትትል ፤ በተለይም ከመንግሥት ተቋማት ጭምር በሚደርሱት መረጃዎች መሠረት በግጭቱ ዐውድ የሚፈጸሙ የአስገድዶ መድፈር ድርጊቶች በጣም አሳሳቢ እና በአፋጣኝ ተገቢው ምርመራ ተደረጎ አርምጃ ሊወሰድበት የሚገባው ነው፡፡

የሕክምና አገልግሎት ለማግኘት በተለያዩ የጤና ተቋማት መድረስ የቻሉትን ተጎጂዎች ቁጥር ብቻ መሠረት በማድረግ ከሐምሌ ወር 2016 ዓ.ም. ጀምሮ ይህ መግለጫ እስከ ወጣበት ጊዜ ድረስ ቢያንስ #2ዐዐ_የአስገድዶ_መድፈር ተጎጂዎች በጤና ተቋማት ተመዝግበዋል፤ ከተጎጂዎች መካከልም የሀገር ውስጥ ተፈናቃይ ሴቶች እና የጤና ባለሞያ ሴቶች ጭምር ይገኙበታል።

ከትጥቅ ግጭቱ መስፋፋት ጋር ተያይዞ ፦
🔹ሲቪል ሰዎች እና የሲቪል የንግድ እና የመሠረተ ልማት ተቋማት ላይ ዝርፊያ ተፈፅሟል።
🔹የማሳ ላይ ሰብል ውድመት ጨምሮ በሲቪል ሰዎች፣ በሕዝብ እና በመሠረተ ልማት ላይ ጉዳት ደርሷል።
🔹ሕፃናት ከትምህርት ውጪ ሆነዋል በአንዳንድ አካባቢዎች የትምህርት ተቋማት ለወታደራዊ አገልግሎት ውለዋል። ይህ ደግሞ አፋጣኝ ትኩረት የሚሻ ነው።

በክልሉ ውስጥ በተለየ ሁኔታ ከተፈቀደላቸው ተቋማት በስተቀር ይህ መግለጫ እስከ ወጣበት ጊዜ ድረስ የኢንተርኔት አገልግሎት የተቋረጠ ሲሆን፣ በተለይም በግጭት ላይ ባሉ አካባቢዎች የስልክ አገልግሎትም ጨምሮ ተቋርጧል።

(ዛሬ ከ #ኢሰመኮ የተላከል ሙሉ መግለጫ በዚህ ታገኛላችሁ ፦ https://t.me/tikvahethiopia/82609?single)

@tikvahethiopia
#ኦዲት

#ለተከታታይ_ዓመታት ለተገኘበት በርከት ያለ የኦዲት ክፍተት ማስተካከያ ማድረግ እንደተሳነው የተገለፀው የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ከአመራር መቀያየር ባለፈ ጥብቅ ሪፎርም እንደሚስፈልገው የፌደራል ዋና ኦዲተር አስታውቋል።

ይህንን ያስታወቀው፤ የሕ/ተ/ምክር ቤት የመንግሥት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በ2014 / 15 በጀት ዓመት ሒሳብ ኦዲት ላይ የዋና ኦዲተር መ/ቤት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ውይይት ሲደረግ ነው፡፡

መስሪያ ቤቱ ምን አለ ?

ኮሚሽኑ ፦
📄ለሚፈጽማቸው ክፈያዎች ደረሰኝ ባለማቅረብ፣
📄ኮፒ ደረሰኝ መጠቀም፣
📃በኮፒ ደረሰኝ ሂሳብ ማወራረድ፣
📄ያልተፈቀደ ክፈያ በመፈጸም፣
📄ለተከፈለ ገንዘብ ማስረጃ ባለማቅረብ፣ እንዲሁም #በቢሊዮኖች ብር የሚቆጠር ተከፋይ እና ተሰብሳቢ ውዝፍ የኦዲት ሪፖርት ተገኝቷል።

- ከሳዑዲ ከስደት ለተመለሱ 102 ሺህ ኢትዮጵያውያን ለኪስ አበል እንዲሁም ለቤት ኪራይ 5.2 ሚሊዮን ብር ማስረጃ ሳይቀርብ ተከፍሏል። ተከፈለ ለተባለው ለዚህ ገንዘብ ሰነድ ማግኘት ባለመቻሉ ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ አልታቻለም።

- ለምግብ ዝግጅት ድርጅት ተብሎ የተከፈለና በወጪ የተመዘገበ 2.9 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ዋጋው ከ65.3 ሚሊዮን ብር በላይ የሆነ 14 ሺህ ኩንታል ዱቄት " ናህሊ ዱቄት ፋብሪካ " ለተስኘ ድርጅት የተከፈለ ተብሎ የቀረበ ቢሆንም የቀረበው ደረሰኝ ግን ኮፒ ነው።

- በወጪ ሒሳብ ለተመዘገበ 79 ሚሊዮን ብር ለኦዲት ሥራ የሚፈለጉ የወጪ ማስመስከሪያዎች (ቫውቸሮች) ከደጋፊ ሰነዶች ጋር እንዲቀርቡ በተደጋጋሚ ቢጠየቅም ማስረጃ ሊቀርብ አልቻለም።

- ያልተወራረደ 881.5 ሚሊዮን ብር ተሰብሳቢ ሒሳብ መኖሩ በኦዲት ሪፖርት ቢረጋገጥም፣ ከኦዲት ግኝት በኋላ የተወሰደ ማስተካከያ የለም።

➡️ በወቅቱ ያልተወራረደ 39.7 ሚሊዮን ብር ተከፋይ ሒሳብና ያልተከፈለ ሲሆን ከኮሚሽኑ መደበኛ በጀት 37.6 ሚሊዮን ብር በሥራ ላይ አልዋለም።

በተጨማሪም ፦

* ውኃ የሚያስገቡ እና ጣሪያቸው የሚያፈሱ መጋዘኖች ተገኝተዋል።

* በቆይታ ብዛት የተበላሸ ብስኩት ሳይወገድ በግምጃ ቤት ተገኝቷል።

* የቆይታ ጊዜያቸው የማይታወቅና በውስጣቸው ምን እንዳለ የማይታወቅ የታሸጉ 9 ኮንቴነሮች በመጋዘን ግቢ ውስጥ ተገኝቷል።

* የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ያለፈ ፦
🔹ሴሪላክ የዱቄት ወተት፣
🔹የወይራ ዘይት፣
🔹የምግብ ዘይት፣
🔹ብዛት ያላቸውና ጊዜያቸው ያለፈባቸው ቴምሮች፣
🔹የንፅህና መጠበቂያ ሞዴስ ተገኝቷል።

* በእህል መጋዘኖች ውስጥ የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ሊያልፍ #ሁለት እና #ሦስት ወራት የቀራቸው አልሚ ምግቦች፣ ሳሙናዎችና እህሎች ተገኝቷል።

የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተ/ማርያም የኦዲት ሪፖርት ላይ ለመምክር በተጠራው ውይይት አለመገኘታቸው ቋሚ ኮሚቴውን አስቆጥቷል።

በወቅቱ ውይይቱ ላይ የተገኙት ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ኮሚሸነሩ የቀሩት ሌላ ተልዕኮ ስለነበራቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወይዘሮ መሠረት ዳምጤ ምን አሉ ?

° ኮሚሽኑ ኃላፊዎችን #ከመቀያየር ባለፈ መሠረታዊ የአስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልገዋል።

° በ2014 ዓ/ም የዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ኦዲተሮች ለጊዜያዊ የኦዲት ሥራ የተረከቡትን ቢሮ ኦዲት አድርገው በሚወጡበት ጊዜ የኮሚሽኑ ሠራተኞች በመግባት #ሰነድ እያወጡ መሆኑን መረጃ አለኝ።

° ይህ ኮሚሽን ለፈጸማቸው ክፍያዎች ሰነድ ማቅረብ አለመቻሉ መሠረታዊ ችግሩ ነው።

° ከዚህ በፊት የበላይ ኃላፊው ቢታሰሩም ኮሚሽኑ ግን አሁንም ሰንኮፉ አልተነቀለም፣ በመሠረታዊነት ችግሩ አልተቀረፈም።

° በመጋዘኖች ውስጥ በሚገኙ ንብረቶች ከፍተኛ ችግር አለ። ገንዘቡ አንዴት እንደሚመጣ እናውቀዋለን ነገር ግን እዚህ ያለው ሥራ የተዝረከረከ ነው፡፡

° በ2013 ዓ.ም. #ድሬዳዋ እና #ሻሸመኔ በሚገኙ መጋዘኖች ከታዩ ችግሮች በመነሳት የኦዲት አስተያየት የተሰጠንባቸው ጉዳዮች በ2014 ዓ.ም በድጋሚ ኦዲት ሲደረግ በነበሩበት እንጂ ተስተካክለው አልተገኙም።

° " ደመወዝ የምንበላበት ተቋም ነው፣ ስለዚህ እዚያ ያለውንም ሥራ ልክ እንደ ቤታችን ማየት አለብን፡፡ ይህ ሁሉ ቁሳቁስ የሚገዛው በብድር ነው እናውቃለን፡፡ እዚህ አምጥተን በአግባቡ የማይውል ከሆነ፣ መሬት ላይ የሚደፋና ከጋዝ ጋር ተቀላቅሎ የሚበላሽ ከሆነ ሥራው ትርጉም አልባ ነው "

° በዚህ ውይይት ላይ ያልተገኙት #ኮሚሽነሩ የቀሩት ዕርዳታ ለማፈላለግ ሊሆን ይችላል ፤ ነገር ግን ተቋሙ የተገኘውን ንብረት በተገቢው መንገድ ማስተዳደር ካልተቻለ፣ ዕርዳታ ማፈላለጉ ብቻ ትርጉም የሌለውና በቀዳዳ በርሜል ውኃ እንደመሙላት የሚቆጠር ነው።

የገንዘብ ሚኒስቴር ፤ የኢንስፔክሽን መምርያ ኮሚሽኑ በኮፒ ደረሰኝ ሒሳብ እንደሚያወራረድ በተደጋጋሚ ቢነገርም ሊስተካከል ባለመቻሉ ይህንን ያደረገ ኃላፊ መጠየቅ አለበት ብሏል።

More - https://telegra.ph/Reporter-12-14-2

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ይህ መረጃ ባለቤትነቱ የ "ሪፖርተር ጋዜጣ " መሆኑን ያሳውቃል።

@tikvahethiopia