የጊንር ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
276 subscribers
864 photos
14 videos
12 files
19 links
ይህ ቻናል ዓላማውን የሰንበት ት/ ቤቱን ጠቃሚ መረጃዎች እና መልእክት ማስተላለፍ አድርጎ ጥር 19/2012ዓም ሌሊት 6:50 ላይ ተከፈተ፡፡
Download Telegram
ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት
አመራሮች ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር በወቅታዊ
የቤተክርስቲያን ጉዳይ ዙሪያ ተወያዩ
*
***

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ማደራጃ መምሪያ ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት አመራሮች በቤተክርስቲያናችን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር ውይይት አደረጉ።

በውይይቱ ወቅት የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነቱ አመራሮች የቤተክርስቲያናችንን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ጥቅል ጥናታዊ ሰነድ ከመፍትሔ አቅጣጫ ጭምር ያቀረቡ ሲሆን ያቀረቡት ሰነድ በዝርዝር ተዘጋጅቶ፣
በማስረጃና በመረጃ ዳብሮ ችግሮቹን ደረጃ በደረጃ መፍታት በሚያስችል አግባብ እንዲቀርብ ቋሚ ሲኖዶስ አቅጣጫ ሰጥቷል።

ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት አመራሮቹም ለቋሚ ሲኖዶስ ያቀረቡት ሰነድ ሁኔታዎችን ለማመላከት እንጂ ያለቀለት ሰነድ እንዳልሆነ ገልጸው ዝርዝር ጥናቱን፣የጥፋቱን መጠን፣ባለቤቱንና የመፍትሔ አቅጣጫዎቹን የሚያመለክት ዝርዝር ሰነድ በማዘጋጀት እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል።

በውይይቱ ወቅትም ከቋሚ ሲኖዶስ አባላት ጥያቄና አስተያየት ተሰጥቶ ከሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት አመራሮቹ ምላሽ ተሰጥቶበታል።

ምንጭ: የ/ኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ከቅድስት የቀጠለ #ዘምኩራብ]➥
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዴት መኖር እንዳለብን በማሰብ ነው

❖ ታላቁ ጾማችን በዘወረደ ሃይማኖትን አስረድቶን፤ በተረዳች ሃይማኖት እንዴት መኖር እንደሚገባን በቅድስት ሰብኮን፤ በሃይማኖት ጸንተን በምግባር በርትተን የምንኖርባትን መኖሪያ ደግሞ በሦስተኛው ሳምንቱ ይነግረናል - #ምኩራብ!

❖ በአንዲት ሃይማኖት ሆኖ በምግባር ጎልምሶ [ክርስቲያን ሆኖ] መኖር የሚፈልግ ሰው እንዲህ ያለው ህይወት የት እንደሚኖር ካላወቀ በከንቱ ይባዝናል እንጂ ክርስቲያናዊ ህይወትን መኖር አይቻለውም

◎ ከበረቷ ውጪ የምትባዝን በግ የተኩላ ሲሳይ ትሆናለች እንጂ አትጠቀምም ስለዚህ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በወንጌል " ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ" አለን [ዮሐ ፲፥፲፮]

◎ዛሬ በቅዳሴ ላይ በንፍቁ ካህን የተነበበው የመጽሐፍ ክፍል ይሄንኑ ያስረዳናል -ሐዋ ፲፥፩-፱
"...ቆርኔሌዎስ የሚሉት አንድ ሰው ነበረ፤ እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር እግዚአብሔርን የሚያመልክና የሚፈራ ለሕዝብም እጅግ ምጽዋት የሚያደርግ ወደ እግዚአብሔርም ሁልጊዜ የሚጸልይ ነበረ"
ቆርኔሌዎስ ምንም እንኳን እንዲህ ባለ የተመሰገነ ሕይወት ቢኖረውም ይህ አኗኗሩ ትርጉም የሚኖረው ወደ ቤተ ክርስቲያን በጥምቀት ሲጨመር ነውና መልአኩ ጴጥሮስን አስጠርቶ እንዲጠመቅ ነገረው።
ቆርኔሌዎስ በምኩራብና በቅድስት ያለ በግ ነበረና እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ወደ በረቲቱ ምኩራብ አመጣው

❖ በቤተ ክርስቲያን ስንኖር ብዙ አይነት አኗኗር አለና እንዴት ሆነን በምን አይነት አኗኗር መኖር እንዳለብን ልናውቅ ያስፈልገናል
" ብዘገይ ግን፥ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው" ፩ኛ ጢሞ ፫፥፲፭

● ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናትና በመከፋፈል ልንኖርባት አይገባም

● ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ናትና በርኩሰት ሆነን ልንኖርባት አይገባም

●  ቤተ ክርስቲያን ኩላዊት ናትና ዘረኞች ሆነን ልንገኝባት አይገባም

● ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት ናትና ከሐዋርያትና በእነርሱ እግር ከተተኩ አበው ከተቀበልነው ወግ ውጪ ልንሆንባት አይገባም

● ቤተ ክርስቲያን የበጎች በረት ናትና የተኩላ፣ የጅብ፣...... የአራዊት ጠባይ ይዘን በውስጧ መገኘት አይገባም

❖ የጸሎት ቤት በሆነች በእግዚአብሔር ቤት
◎  #ሀና_ወለተ_ፋኑኤል_በጾምና_በጸሎትም_ሌሊትና_ቀን_እያገለገለች_ከመቅደሱ_ሳትለይ_ኖረች [ሉቃ፪፥፴፯]

#ስምዖን_አረጋዊ_ትንቢቱን_በመጠባበቅ_ኖረ [ሉቃ፪፥፳፭-፴፪]

● አይሁድ ግን የጸሎቷን ቤት በንግድ ተሰማሩባት ለቤቱ የሚቀናው ጌታችንም እየገረፈ አስወጥቶ "ወኢትረስዩ ቤተ አቡየ ቤተ ምሥያጥ - የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጓት" አለ [ዮሐ ፪፥፲፮]

❖ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን "መንፈሳዊት ዓውድ መዝገበ ሥርናይ እንበለ ክርዳድ - መንፈሳዊት መመላለሻ እንክርዳድ የሌለባት የስንዴ መሰብሰቢያ" ይላታል

◉ በመንፈሳዊቷ መመላለሻ በዘረኝነት፣ በዓለማዊነት፣ በትዕቢት ለተመላለስን- ወዮ!
◉ የስንዴ መከማቻ በሆነችዋ ጎተራ እንክርዳድ ሆነን ለተገኘን ለኛ - ወዮ!

እግዚአብሔር የቤቱ ቅናት ይበላዋል ከማንም በላይ እርሱ ስለቤቱ ይቀናል። እስካሁን ጅራፉን ያላነሳብን ምን አልባት ከነፍሳችን በሽታ እንድንፈወስ መጻጉነታችንን እየታገሰን እንጂ ኃጢአታችንን ወድዶልን አይደለም! ይቆየን!
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ ከምኩራብ የቀጠለ #ዘመጻጉዕ]➥
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም ከደዌ ነፍስ በመፈወስ ነው

❖ የዓቢይ ጾም ሳምንታት እንዳስተማሩን በዘወረደ ሃይማኖቱ የጸናለት በቅድስት ምግባሩ የቀናለት በምኩራብ መኖሪያውን ያደረገ ሰው በዚህ አኗኗሩ ለመጽናት መታገል አለበት
❖ የትግሉ ምክንያት በዚህ አይነት ሕይወት እንድንኖር  የማይወድ ጠላት አለብንና ነው። እርሱም ዲያብሎስ ነው።
" መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ" እንዲል ኤፌ ፮፥፲፪

❖ ጠላት እኛን ሲያደክመን ስለሚገጥመን ደዌ የሚያስተምረን የታላቁ ጾማችን ክፍል - #መጻጉዕ ነው!

❖ ደዌ ዘሥጋ ደዌ ዘነፍስ አለ - የሥጋ የነፍስ ህመም/በሽታ።

ደዌ ዘሥጋ በልዩ ልዩ መንገድ ይመጣል [ዮሐ ፭- ትርጓሜ]
◎ እንደ ጢሞቴዎስ ለንጽሕና የሆነ ደዌ ዘንጽህ አለ [፩ኛ ጢሞ፭፥፳፫]
◎ እንደ እዮብ ለዋጋ የሆነ ደዌ ዘዕሴት አለ [ኢዮ፪]
●ሄሮድስ እንደደረሰበት ያለ ደዌ ዘመቅሰፍት አለ
●እንደመጻጉዕ ያለ ደዌ ዘኃጢአትም አለ [ዮሐ፭፥፲፬]

➥ ደዌ ዘሥጋ ለንጽህና ለዕሴት ከሆነ ቢታገሱት ዋጋን ያሰጣል
ቅዱስ ጳውሎስ የሚለውን ተመልከቱ "የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው።ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ። እርሱም። ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ" ፪ኛ ቆሮ ፲፪፥፯-፱

➥ የመቅሰፍት ኃጢአት ከሆነም በንሰሀ ይርቃል በምስጢረ ቀንዲል ይፈወሳል።

"ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽምግሌዎች ወደ እርሱ ይጥራ፤ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት። የእምነትም ጸሎት ድውዩን ያድናል ጌታም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደ ሆነ ይሰረይለታል" ይላል ያዕ፭፥፲፬-፲፭

ከደዌ ሥጋ ይልቅ የሚከፋው ደዌ ዘነፍስ ነው።
ሥጋችን በባዕድ (Bacteria ወይም Virus) ሲወረር ህመምተኛ እንደሚሆን ነፍሳችንን የዲያብሎስ ግሳት ሲወራት ህመምተኛ ትሆናለች

ተወዳጆች! መዝሙር ማድመጥ ሰልችቶናል? ቃለ እግዚአብሔር የመመገብ ፍላጎታችን ቀንሶብናል? ወደ ቤተ እግዚአብሔር ለመሄድ አቅቶናል? የአገልግሎት ሙቀታችን ቀንሶ ብርድ ብርድ ብሎናል? እንግዲህ ነፍሳችን ታማለችና ምን እንጠብቃለን?!

ለሥጋችን ምግብ ከዘጋን፣ ብርድ ብርድ ካለን፣ እንደልባችን መንቀሳቀስ ካቃተን ታመናልና ፈጥነን ወደ ሆስፒታል እንደምንሄድ የነፍሳችን ጤንነቷ ሲታወክብንም ወደ አማናዊቷ ሆስፒታል ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሄደን ከነፍሳችን ዶክተሮች ካህናት ጋር በመገናኘት እነርሱ በሚሰጡን ህክምና ወደ ጤንነታችን መመለስ ይኖርብናል

ነፍሳችን ከልዩ ልዩ ደዌያት የራቀች እንደሆነ ብዙ ነገራችን ይስተካከልልናል

በማቴ ፱፥፳፯ የተጠቀሱት ሁለቱ ዕውሮች የለመኑት ልመና #ማረን የሚል ነበር ጌታችን ግን ዓይናቸውን አበራላቸው ለነፍሳችን ምህረትን የለመንን እንደሆነ የቀረው ዳረጎት መሆኑን ይህ ታሪክ በግልጥ ያስረዳናል።

❖ምንጩን/የነፍሳችንን/ ካስተካከልን ከዚያ በኋላ ያለው የሚያስጨንቅ አይሆንም ይልቅ ከሐዋርያው ጋር "እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን" እያልን የመንዘምርበት ምክንያት ይሆነናል [ሮሜ፰፥፳፰]።

❖በእኛ ተገብቶ የተናገረ ደራሲ "ወስክኒ ክራማተ እስከ እገብር ጽድቀ - ጽድቅን እስክሠራ ዕድሜን ጨምሪልኝ" እንዳለ ዕድሜን ለጽድቅ ስራ እንለምን በተሰጠንም ዕድሜ ከደዌ ነፍስ እንፈወስበት [መልክዐ ማርያም - ለክሳድኪ]።

ያን ጊዜ ከአቡቀለምሲስ ጋር "አሜን፥ ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ና" እንላለን [ራእ ፳፪፥፳]

"ሰው የሚፈልገውን ከሠራ የሚጠብቀው ሞቱን ነው" እንዲሉ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ለነፍሳችን የሚገባትን ካደረግን #ደብረ_ዘይትን በተስፋ እንጠብቃታለን - ይቆየን!
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
አንተ አሁን ድነኃል ወይስ አልዳንክም? ለሚሉን
ለጠያቂዎቻችን መልስ አዘል ጥያቄ እናቀርብላቸዋለን

● እስራኤል ከፈርኦን ባርነት ተላቀው ከግብጽ በወጡበት ቅጽበት ከነዓን ገብተዋል ወይስ አልገቡም?

● ከግብጽ ባርነትስ ድነዋል ወይስ አልዳኑም?

● ከግብጽ መውጣታቸው ከነዓን ለመግባታቸው ማረጋገጫ ነውን?

● ከነዓን ለመግባት ከግብጽ መውጣት ብቻውን በቂ ነውን?

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
ይህን ደግሞ ምን አመጣው? ምንስ ያገናኘዋል? የሚለን ካለ "ይህም ለአሁኑ ጊዜ ምሳሌ ነው" የሚለውን አላነበብክምን? እንለዋለን። [ዕብ ፱፥፱]
የብሉይ ታሪክ ለሐዲስ ምሳሌ መሆኑን እንዲረዳ የተወሰኑ የመጽሐፍ ጥቅሶችን አስቀምጠን ንግባዕኬ ኀበ ጥንተ ነርገር እንዲል ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ ወደ ነገረ ድኀኅነትነ!!!
📖"... ይህ ምሳሌ ሆነልን. . .  እኛንም የዘመናት መጨረሻ የደረሰብንን ሊገሥጸን ተጻፈ " ፩ቆሮ ፲፥፮-፲፩
📖 ".. .  ይህም ነገር ምሳሌ ነው.. .  " ገላ፬፥፳፬
📖 ማቴ ፲፪፥፵፤ ዮሐ ፫፥፲፬ ፤ ፩ኛ ጴጥ፫፥፳፩ ፤ ...

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
እስራኤል እናቱ አገልጋዩ አገልጋዩ እናቱ በሆነችለት በሙሴ መሪነት ከአባቶቻቸው ጀምሮ ከኖሩበት ከፈርኦን አገዛዝ ከግብጽ ባርነት እንደዳኑ እኛም እናቱ እናትም አገልጋይም በሆነችለት በክርስቶስ ኢየሱስ መሪነት ከአዳም ጀምሮ አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ እየተባልን ጠላት የባሪያዬ ልጅ የላሜ ውላጅ እያለ እኛን ከገዛበት ከዲያብሎስ አገዛዝ ከሲኦል ባርነት ድነናል!

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
● የእስራኤል ከግብጽ መውጣት የበቅጽበት ከነዓን መግባት እንዳልሆነ ሁሉ ፶፭፻(5500) ዘመን ከኖርንበት ባርነት ድነናል ማለት ገነት መንግስተ ሰማያት ገብተናል ድኅነታችንንም አጠናቀናል ማለት አይደለም!

● ይህ የማይረዳው ካለ የከበረ ሐዋርያ ቅ/ጳውሎስን ይጠይቅ እርሱ "በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ" ይላልና [ፊልጵ ፪፥፲፪]
ክርስቶስ አድኖን የለምን ስለየትኛው ያልተፈጸመ መዳን ነው የምታወራው እያሉ ይጠይቁት።
እኛኮ ባመንበት ቅጽበት ድነናል የተፈጸመ እንጂ የሚፈጸም ድህነት የለንም ብለውም ይሞግቱት (ቅ/ጳውሎስ መልዕክቱን የጻፈው ላመኑት መሆኑን ልብ እንበል)

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
➥ የእስራኤል ከግብጽ መውጣት ብቻውን ከነዓን መግባት እንዳልሆነ የእኛም በአዳም በኩል ከመጣብን ዕዳ መዳን መንግስተ ሰማያት መግባት ስላልሆነ...👇👇👇

እስራኤል በእግዚአብሔርና በባሪያውም በሙሴ እንዳመኑ ማመን የግድ ያስፈልጋል[ዘፀ ፲፬፥፴፩]። የማያምን ግን የድኅነት ጎዳና ላይ የለም መንገድ ስቶ ወደ ፍርድ እየሄደ ነው።

📖 "በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል" ዮሐ 3:18
● በሚያምን #አይፈረድበትም ይላል እንጂ አሁን ተፈርዶለታል አለማለቱን እናስተውል እምነት #ብቻውን ደግሞ ለማዳን አይበቃምና
●  በማያምን ግን #አሁን_ተፈርዶበታል ይላል ያለእምነት ደግሞ ምንም ምን ለድኅነት የሚያበቃ ሥራ መስራት አይቻልምና

እስራኤል ከነዓን ለመግባት ባሕረ ኤርትራን መሻገር የግድ አስፈላጊያቸው እንደሆነ እኛም ድነን መንግስቱን ለመውረስ የግድ መጠመቅ አለብን[፩ኛ ቆሮ ፲፥፪] ባመንኩበት ቅጽበት ድኛለሁ የግድ ልጠመቅ አይገባኝም ለሚሉን  እኛ የክርስቶስ እንጂ  የሌላ ደቀ መዛሙርት አይደለንምና ከመምህራችን ከክርስቶስ የተማርነውን እንነግራቸዋለን

📖  "ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል። እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም" ዮሐ 3:5

እስራኤል ከሰማይ የወረደ መና ከዓለት የፈለቀ ውኃ መጠጣት እንደነበረባቸው ሁሉ እኛም
ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ የወረደ እንጀራ የክርስቶስን ሥጋውን
[ዮሐ፮፥፶] ከዓለት ክርስቶስ የተገኘ ክቡር ደሙን[፩ኛ ቆሮ ፲፥፬] የግድ ልንበላና ልንጠጣ ያስፈልገናል ያለ እርሱም መዳን የለም!

📖 "ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም" ዮሐ ፮፥፶፫
ይህ የሚከብዳቸው ካሉ "እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁን? " ይባላሉ እንጂ ያለቁርባን ሊድኑ አይችሉም [ዮሐ ፮:፷፯]

➥ እስራኤል ከግብጽ ወጥተው አምነው ባህረ ኤርትራን ተሻግረው ከመናው በልተው ከዓለት ላይ ከፈለቀው ውኃ ጠጥተው በሲና ተራራ የተሰጣቸውን ህግ ካልተቀበሉና በእርሱ መመራት/መኖር/ ካልቻሉ ከነዓን አይገቡም። አታመንዝር የምትለዋን በመተላለፍ ስንቶቹ በበረሃ ቀሩ! [ዘኁ፳፭]
እኛስ በተራራው ስብከት የተሰጡንን ቃላት ካልጠበቅን ከከነዓን የምትልቀዋን በዓይን ያልታየች በልብ ያልታሰበችዋን መንግስት እንዴት እንወርሳለን? [ማቴ፯፥፳፩] መንግስቱን አለመውረስ አለመዳን አይደለምን?

እስራኤል ወደ ምድረ ርስት ሲጓዙ እነርሱን ከመዳረሻቸው እንዳይደርሱ ጦር ከሚገጥሙ የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን[ዘኁ፳፩] የበሳንን ንጉስ ዐግን[ዘኀ፳፩፥፴፫] ከመሳሰሉ ጠላቶች ጋር መፋለም ነበረባቸው
እኛ የአዲስ ኪዳን እስራኤሎችም (እስራኤል ማለት ሕዝበ እግዚአብሔር ማለት ነው) ወደ ርስት መንግስተ ሰማያት በምናደርገው የመዳን ጉዞ ከመንገድ ሊያስቀሩን ውጊያ ከሚገጥሙን አጋንንት ጋር መጋደል አለብን

📖 "መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።" ኤፌ ፮፥፲፪
📖 "... መልካም ጦርነት ትዋጋ ዘንድ ይህችን ትእዛዝ አደራ እሰጥሃለሁ" ፩ኛ ጢሞ ፩፥፲፰

በዚህ ሁሉ መላእክት ሊራዷቸው[ኢያ ፭፥፲፫-፲፭] ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ሊቆምላቸው(ሊያማልዳቸው) [መዝ፻፮፥፳፫] እነኢያሱ ታቦቱ ሥር ተደፍተው ሊማጸኑላቸው [ኢያ፯፥፮-፲] ያስፈልጋቸዋል
እኛንም መዳንን ለመውረስ እንድንችል የቅዱሳት መናፍስት (መላእክት) እርዳታ፣ የአማላጆች የቅዱሳን አማላጅነት ዘወትር ያግዘናል
📖 "ሁሉ መዳንን ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚላኩ የሚያገለግሉም መናፍስት አይደሉምን?" ዕብ ፩፥፲፬
📖 "እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል። ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፥ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል" ማቴ ፲፥፵-፵፩
● የነቢያት የጻድቃን ዋጋቸው ምንድነው? መንግስቱ አይደለችምን?
"ንጉሡም በቀኙ ያሉትን እንዲህ ይላቸዋል። እናንተ የአባቴ ቡሩካን፥ ኑ፤ ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን #መንግሥት_ውረሱ" እንዲል ማቴ ፳፭፥፴፬
.
.
.
ሌላም ሌላም አለ እያንዳንዱን ለመዘርዘር ቦታውም ጊዜውም አይፈቅድልንም ዕውቀታችንም ይገድበናል።

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
ወዳጆች ሆይ መዳን በሂደት እንጂ በቅጽበት አለመሆኑን አስተዋላችሁን? ስለዚህ
" ዛሬ ድምፁን ብትሰሙት ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ. . . ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ" ዕብ ፬፥፯-፲፩

ከድኅነት የምታራቁት ድነናል የምትል ፉከራ መሳይ ከንቱ ፍልስፍናችሁን ትታችሁ እርሱ ነዋየ ህሩይ እንደመከረን በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ሆናችሁ መዳናችሁን ለመፈጸም ከቤተ ክርስቲያን ጋር አብራችሁ ትጉ!
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
" ግብዒ ነፍስየ ውስተ ዕረፍትኪ እስመ እግዚአብሔር ረዳኢኪ - ነፍሴ ሆይ፥ ወደ ዕረፍትሽ ግቢ፥ እግዚአብሔር ረዳትሽ ነውና" መዝ ፻፲፬፥፯
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ ከደብረ ዘይት የቀጠለ #ዘገብርኄር]➥

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም ቅንነት ባለበት አገልግሎት በመትጋት ነው

❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖
ዘወረደ ገብቶት በሃይማኖት የጸና፣
ቅድስት ተረድቶት መንገዱ የቀና፣
ምኩራብ መኖሪያውን ያደረገ እርሱ፣
መጻጉዕ ከመሆን የተለየች ነፍሱ፣
ደብረ ዘይት ሆኖ ጌታን የጠበቀ፣
በቅን አገልግሎት ከመትጋት ያልራቀ፣
ለእያንዳንዱ ዋጋን ሲሰጥ እግዚአብሔር፣
ያን ጊዜ ይሸለማል ነውና #ገብርኄር

❖ በገብርኄር እሁድ የተነበበው ወንጌል [ማቴ ፳፭፥፲፬- ፴] እንደሚነግረን #ለእያንዳንዳችን ጌታ መክሊት ሰጥቶናል። በዚህ ነግዶ ማትረፍ የኛ ድርሻ ነው።  ነግዶ ለማትረፍ ወደ #ማትረፊያ ገበያ መሰማራት ያስፈልጋል ወደ ምንከስርበት ከተሰማራን ግን ከስረን በእዳ መያዛችን አይቀርም

➥ስዕል የመሳል መክሊት የተሰጠው መንፈሳዊ ስዕላትን ወደሚስልበት ገበያ ተሰማርቶ ያትርፍ እንጂ ነገረ ዓለም ወደሚሳልበት ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ከመንፈሳዊነት እያወረደ አይክሰር

➥ የድምጽ መክሊት የተሰጠው በመዝሙር ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ወደ መንፈሳዊነት ማርኮ ያትርፍበት እንጂ ወደ ዘፈን ገበያ ወርዶ አይክሰር

➥ ጽሁፍ የመጻፍ መክሊት ያለው ክፉ ጽህፈትን ጽፎ ወዮታን ከሚገበይ (ኢሳ፲፥፪) የምሥራቹን ወንጌል በጽሁፍ ጥበብ አዳርሶ ሰዎችን ወደ ጥበብ ክርስቶስ ይማርክ

➥የመናገር መክሊት ያለው በአንደበቱ ጣዕም በስብከት ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ወደ በረቱ ይሰብስብ እንጂ ክፉውን ነገረ ዓለም ወደሚናገርበት ገበያ አይውረድ

ሁላችንም በየመክሊታችን ወደ ማትረፊያ ገበያ እንሰማራ!

❖ ገና ለገና እከስራለሁ ብሎ በስንፍና መቅረት አግባብ አይደለም። አለመስራትና አለማትረፍም ቅሉ መክሰር እንደሆነ የታወቀ ነው። ቸሩ ጌታችን በሚያከስር ገበያ እንድንሰማራ አልላከንም። የሚያተርፍ ውድ መክሊት እንጂ የሚያከስር መክሊትንም አልሰጠንም።

አለማገልገል የፍቅር ማጣት ነው። በሃይማኖት ጸንቶ፣ በምግባር ኖሮ፣ በቤተ ክርስቲያን ያለ ሲበድልም በንሰሀ የሚገኘውን ዕረፍት ያጣጣመ ይህን ጣዕም ሌሎቹ እንዲቀምሱ አለመጣር የፍቅር ማጣት ነው!

ሐዋርያት ወደ ዓለም ለአገልግሎት የተሰማሩት ከፍቅር ተነስተው ነው። ሰውን ሁሉ ይወዳሉና ለሰው ሁሉ የሚድኑበትን መንገድ አመለከቱ። ሰዎቹ እየደበደቧቸው እንኳ ሐዋርያቱ ግን ስለ ደብዳቢዎቻቸው ድኅነት የሚተጉበት ምክንያት ፍቅር ናት!

የከበረ ሐዋርያ ነዋየ ኅሩይ ቅ/ጳውሎስ የሚለውን ተመልከቱ "በሥጋ ዘመዶቼ ስለ ሆኑ ስለ ወንድሞቼ ከክርስቶስ ተለይቼ እኔ ራሴ የተረገምሁ እንድሆን እጸልይ ነበርና" [ሮሜ ፱፥፫] እራስን አሳልፎ እስከመስጠት ያለ ፍቅር!

ስለዚህ አገልግሎት በፍቅር ለፍቅር የሚደረግ የፍቅር መግለጫ ነው።

❖ የምናተርፍበትን ገበያ ትተን በሚያከስር ገበያ እንዳንገኝ። በምክንያተኝነት ተተብትበን፣ ከፍቅር ጎድለን፣ ዋጋ በምታሰጥ አገልግሎት ከመትጋት ተዘልለን፣ መክሊታችንን እንዳንቀብር ዛሬ ያውም አሁኑኑ ወደ አገልግሎት እንሰማራ! መልካም ንግድ ተመኘሁ.... ይቆየን!
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
        ሚያዚያ ገብርኄር ፳፻፲፮ዓም
ሰንበት ተማሪ ሌላ ሰንበት ተማሪን በመንገድ ሲያገኝ ወይም በአጋጣሚ ሲተዋወቅ የጠፋ የእናቱን ልጅ እንዳገኘ ልቡ በፍቅር ስስት ይቃጠላል፡፡ ኹለት የማይተዋወቁ ሰንበት ተማሪዎች ቢገናኙ ለመግባባት ጊዜ አይወስድባቸውም፤ ልቡናቸው ቀድሞ ይግባባል፡፡ ስማቸውን እንኳን ሳይተዋወቁ ስለ መስቀል ጥናት ፣ ስለ ጥምቀት ፣ስለ ደብረ ታቦር ፣ ስለ ፍልሰታ ፣ ወዘተ… ያወራሉ፡፡ አባባሉስ ቢሆን ‹‹አንድ ዓይነት ላባ ያላቸው ወፎች በአንድነት ይበራሉ - Birds of the same feather fly together›› አይደል የሚለው?

  ታክሲ ውስጥ ከጎን የተቀመጠው ሰው ሐመር ወይም መለከት መጽሔትን ከያዘ አለበለዚያም አንድ መንፈሳዊ መጽሐፍን እያነበበ ከኾነ ሰንበት ተማሪ አያስችለውም ‹‹ወንድሜን (እኅቴን) አገኘሁ›› ብሎ ሊያወራ ይቋምጣል፡፡ በክርስቲያናዊ አለባበስ ያሸበረቀችና አካሏን ከመራቆት የሸፈነች ‹እኅቱን› ካየም እንደዚያው፡፡ ሌላው ይቅርና አንገቱ ከክር ያልተራቆተ ሰውን ማግኘት ራሱ እንዴት እንደሚያስደስተው!

      ሰንበት ተማሪ ‹ሰንበት ትምህርት ቤት› የተባለች ውድ እናት አለችው፡፡ ብዙ ወንድሞችና እኅቶችን የሰጠችው ይህችው እናቱ ናት፡፡ እርሷ ስትነካበት አይወድም፡፡ ሰንበት ተማሪ ሳይሆኑ ፣ የሰንበት ትምህርት ቤትን ቁስል ሳያውቁ ፣ በችግሯ ሳይቸገሩ ፣ በደስታዋ ሳይፈነጥዙ ፣ ጣዕሟን ሳያጣጥሙ ፣ መዐዛዋን ሳያሸቱ ፣ አካሏን ሳይዳስሱ ፣ ቁመናዋን ሳይመለከቱ እንዲያው በሩቁ ብቻ ገምተው የሚተቿት ሰዎች እጅግ ይገርሙታል።በአንጻሩም የእናቱን ዕድገት የሚሻ ነውና በፍቅር ቀርበው ‹‹ለምን እንዲህ አታደርጉም›› የሚሉትን እጅግ ያከብራል፡፡ ‹‹ምን እናግዝ›› ብለው አብረው ለማገልገል የሚፈቅዱትን እጅግ ይወዳል፡፡

     እናቱን ካለ ምክንያት የሚተችና ዕድገቷን የማይፈልግ ከራሱ ወንድሞች እንኳን ቢነሣ ቁጣው ብርቱ ነው፡፡

    የሰንበት ተማሪ የዘወትር ጥሪው ‹‹ኑ ኹላችንም በእናት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር አንድ ቤተሰብ እንሁን፤ እናት ሰንበት ትምህርት ቤትንም እንደግፍ›› ነው፡፡

ዲያቆን ሕሊና በለጠ
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ከገብርኄር የቀጠለ #ዘኒቆዲሞስ]➥
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም አባቶቻችንን በማሰብ [እንደአባቶቻችን] ነው
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

❖ ታላቁ ጾማችን በሃይማኖት ስለመጽናት፣ በቅድስና ስለማደግ፣ በቤተክርስቲያን ስለመኖር፣ ቢወድቁ በንሰሀ ስለመነሳት አስተምሮን እንዳስተማረን ሆነን ጌታን መጠበቅ እንዳለብንና እርሱ ጌታችን ሲመጣ ዋጋን እንደሚከፍለን ከዘወረደ እስከ ገብርኄር ባሉት ሳምንታቱ አስረድቶናል።

"እንደዚህ ሆኖ መኖር እንደምን ይቻላል?" የሚል ካለ በወንጌል የተነገረንን ትምህርት ኖረው በተግባር ያሳዩንን አበው መመልከት እንደሚገባ የዓቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት ይጠቁመናል - #ኒቆዲሞስ!

❖ መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ቅዱሳን እንድንመለከት፣ እነርሱንም እንድንመስል ያስተምረናል

✟ "ወደ አባታችሁ ወደ አብርሃም፥ ወደ ወለደቻችሁም ወደ ሳራ ተመልከቱ" ኢሳ ፶፩፥፪
✟ " እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ" ፩ኛ ቆሮ ፲፩፥፩

❖ ቅዱሱ መጽሐፍ "ወሀሎ አሀዱ ብእሲ ... - ... አንድ ሰው ነበረ" እያለ ስለቅዱሳኑ የሚነግረንም እንድናዘክራቸው /እንድናስባቸው/ እና የእምነታቸውን ፍሬ እየተመለከትን በእምነት እንድንመስላቸው ነው [ዕብ፲፫፥፯]

ወንጌልን በተግባር ካሳዩን እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን ቅዱሳን አንዱ ኒቆዲሞስ ነው!
"ወሀሎ አሀዱ ብእሲ...ዘስሙ ኒቆዲሞስ - ...ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ" ዮሐ፫፥፩
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ኒቆዲሞስ በዓቢይ ጾም ሳምንታት

ኒቆዲሞስ #በዘወረደ - ኒቆዲሞስ በዘወረደ ሃይማኖት ጸንቶ የኖረ ነው። የጸናበትንም ሃይማኖት ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ተምሯል ጌታም አምስቱን አዕማደ ምሥጢራት እንደወርቅ አንከብሎ እንደሸማ ጠቅልሎ አስተምሮታል (ዘርዝሮ ለማየት ቦታው አልፈቀደም)

ኒቆዲሞስ #በቅድስት - ኒቆዲሞስ ሊቅ፣ ባለጸጋ፣ ባለሥልጣን ቢሆንም እነዚህ ሁሉ እሾኽ ሆነው ሳያንቁት በትህትና ሆኖ የመምህሩንም ተግሳጽ ታግሶ ተምሯል። አይሁድ ስህተታቸውን ሲገልጥባቸው "መርምር፣ እይ" ሲሉት ታገሳቸው እንጂ ክፉ የሆነ የትዕቢትን መልስ አልመለሰላቸውም [ዮሐ፯፥፶፪]
ትህትና፣ ትዕግስት፣... የመሳሰሉ ዕንቁዎች የተገኙበት ኒቆዲሞስን እየተመለከትን በቅድስት እንኑር

ኒቆዲሞስ #በምኩራብ፦ ኒቆዲሞስ በዘወረደ ሃይማኖት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በገባበት ጸንቶ የኖረ ነው።
ቤተ ክርስቲያን የምዕመናን ህብረት ናትና ኒቆዲሞስን ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር በኅብረት ሆኖ እናገኘዋለን
ዛሬም በሃይማኖት ጸንተው በምግባር አሸብርቀው በአንዲቷ ቤተ ክርስቲያን ያሉ ፤ ዘወትር "ቅዱሳነ ሰማይ ወምድር ማኅበረ ሥላሴ አንትሙ..." እያልን ከምንማጸንባቸው ቅዱሳን መካከል ነው- ኒቆዲሞስ!

ኒቆዲሞስ #በመጻጉዕ፦ አስቀድሞ በሌሊት መጥቶ የነበረው ኒቆዲሞስ ፍርሃት የተባለ በሽታ ነበረበት። በዚህ ህመሙ ግን ተስማምቶ መጻጉዕ እስኪባል አልጠበቀም። እነ ቅ/ጴጥሮስን ሳይቀር ከማስካድ አድርሶ የነበረውን ይህንን ክፉ በሽታ ፍርሀትን ከራሱ አራቀው ነፍሱንም ከመጻጉነት አተረፋት
በዮሐ፫ ፍርሃት አይሎበት የነበረው ኒቆዲሞስ በዮሐ፯፥፶ ተሻሽሎ በዮሐ፲፱፥፴፱ ፍርሀቱን ፍጹም አስወግዶ እናገኘዋለን
ኒቆዲሞስ #በደብረዘይት፦ ኒቆዲሞስ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በተማረው አምኖ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ የተወለደ ነውና የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ ሊገባም ደብረ ዘይትን ይጠብቃል።

ኒቆዲሞስ #በገብርኄር፦ ኒቆዲሞስ ደብረ ዘይት(ዳግም ምጽአት)ን የሚጠብቀው በሀዘንና በጭንቀት አይደለም። እርሱ በጥቂቱ የታመነ ገብርኄር ነውና በብዙ ሊሾም በተስፋ የሚጠብቅ ነው። ኒቆዲሞስ በረከትን የሚሰጥ የህግ መምህር ስለሆነ ከኃይል ወደ ኃይል እየሄደ በጎ አገልግሎትን አገልግሏል። አገልጋዮች በሸሹባት በዚያች በዓርብ ቀን ነፍስ የተለየችው መለኮት የተዋሃደውን የጌታችንን ሥጋ ከመስቀል አውርዶ ገንዞ በመቅበር ያገለገለ በእውነት ታማኝ አገልጋይ- ኒ ቆ ዲ ሞ ስ!

❖ በአርአያ ኒቆዲሞስ ተጉዘን ሆሳዕና እያልን ከህጻናቱ ጋር ለመዘመር ያብቃን። ይቆየን።

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
ከቅኔ መሀሌት ዘወረደ ወደ ቅድስት የጌታ ጾም(ከቅድስት-ሆሳዕና) ያደረሰን ከቅድስት የጌታ ጾም ወደ መቅደስ ሕማማት ያሸጋገረን ቸሩ አምላካችን

እንበለ ደዌ ወሕማም እንበለ ጻማ ወድካም ያብጽሐነ ለብርሃነ ትንሳኤሁ በሠላም
#ሥርዐተ_ጸሎት_ወስግደት_ዘሰሙነ_ሕማማት፡፡

#የሰሙነ_ሕማማት_ዕለታት_ስያሜዎች
#ሰኞ፤ መርገመ በለስ የተፈጸመበት ሰኞ፤ አንጽሖተ ቤተ መቅዳስ የተፈጸመበት ሰኞ::
#ማግሰኞ፤ የጥያቄና የትምህርት ቀን::
#ረቡዕ፤ ምክረ አይሁድ፥ የዕንባ ቀን፥ የመልካም መዓዛ ቀን::
#ሐሙስ፤ ጸሎተ ሐሙስ፥ ሕጽበተ ሐሙስ፥ የምሥጢር ሐሙስ፥ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፥ የነጻነት ሐሙስ::
#ዐርብ፤ የስቅለት ዐርብ::
#ቅዳሜ፤ ቀዳም ሥዑር (ሹር ቅዳሜ)፤ ለምለሚቱ ቅዳሜ፥ ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፥ ሰንበት ዐባይ፥ ቅዱስ ቅዳሜ፡፡

በሰሙነ ሕማማት የሚባሉትን በአጭሩ ስንቃኛቸው፡፡
(#ለዐርቡ_ጸሎት_እንደ_ዘማች_ስለሚያገለግል) ዐርብ ከምንለቀው የዐርቡ ጸሎት ጋራ አብረን የምንጠቀምበት ስለሆነ በቃል ጭምር አጥኑት፡፡
/ይህን ጽሑድ በአድካሚ ሁኔታ እንደ ንብ ቀስመንና ሰብስበን አዘጋጅተንላችኋል፤ ላልደሰረሰው አዳርሱ፤ ማተሚያ ቤት ያላችሁ አትማችሁ ስጡ፡፡/
፠የሰሙነ ሕማማት ጸሎት የሚደረገው በ7ቱ የጸሎት ጊዜያት መሠረትነት 7ት ጊዜ ነው፡፡ ለዚሁ አገልግሎት ታላቁ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በ7ቱ ጊዜያት ከፋፍሎ የደረሰው መልክአ ሕማማትም አብሮ በዜማ ይደርሳል፡፡ (መልክአ ሕማማትን ለብቻው አዘጋጅተን ለጥፈንላችኋል)
#የጸሎቱ_አደራረስ_ሥርዐትም ከዚህ እንደሚከተለው ነው፤
፠ደወልና ቃጭል ይመታል፤
፠ጸሎታት(ሙሉ ውዳሴ ማርያምና ዳዊት)ና (የኦሪትና የነቢያት) ምንባባት ይደርሳል፤
፠የተአምር መቅድምና ምንባብ ይነበባል፤ የተአምራት መርገፍ በዜማ ይባላል፡፡
፠የወንጌል አቡን በቅብብሎሽ ይደርሳል፤
፠ምስባክ ይሰበካል ፥ ወንጌል ይነበባል፡፡
#1ኛ_ስግደት፤ ‹‹ጸልዩ በእንተ ጽንዐ ዛቲ›› እያለ ቃጭል ሲያሰማ 22ት ጊዜ ‹‹እግዚኦ ተሣሃለነ›› እየተባለ ይሰገዳል፡፡
#2ኛ_ስግደት፤ ‹‹ለከ ኀይል ክብር ወስብሐት›› የሚለውን በቅብብሎሽ 6ት ፥ 6ት ጊዜ (በድምሩ 12)፤ 7ኛውን በኅብረት እየተሰገደ ይባላል፡፡
#3ኛ_ስግደት፤ ‹‹ለአምላክ ይደሉ›› የሚለውን 1ኛውን ዙር በቅብሎሽ፤ 2ኛውን ዙር እያስተዛዘሉ፤ ከስግደት ጋራ ይባላል፡፡
#4ኛ_ስግደት፤ ‹‹ክርስቶስ አምላክነ…›› የሚለውን በመሪና ‹‹ንሰብሖ ..›› ወናልዕል ስሞ የሚለውን በቅብብሎሽ ብለው በዚያው ቀጥለው፤ ‹‹ኪራያላይሶን፥ ኪራያላይሶን፥ ኪራያላይሶን›› የሚለውን በመሪ 21 ጊዜ፤ በተመሪ 20 ጊዜ (በድምሩ 41 ጊዜ) እየተሰገደ ይደርሳል፡፡
፠የየሰዓቱን (የሌሊት፣ የነግህ፣ የጠዋት 3 ሰዐት፣ የቀትር/6 ሰዐት/፣ የተሰዐት/9ኝ ሰዐት/፣ የሰርክ /11 ሰዐት/፣ የንዋም) መልክአ ሕማማት በዜማ ይደርሳል፡፡
፠ካህኑ ቡራኬ ሰጥቶ፤ ዲያቆኑ ደግሞ ‹‹ሑር በሰላም›› ብሎ ሕዝቡን ያሰናብታል፡፡

/በቀጨኔ ደ.ሰላም መድኀኔዓለምና ደ.ት.ቅ.ገብርኤል ቤ.ክ ፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ፤ ትምሕርት ዋና ክፍል ፥ ንዑስ ክፍል /ሕትመት እና ሚዲያ/ የተዘጋጀ ::
#share

.Facebook...
https://www.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
.YouTube... https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w,
.Telegram...
https://t.me/medihanaelem
http://tiktok.com/@finotehiwot
www.finotehiwotsundayschool.com
YouTube https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w
Telegram https://t.me/medihanaelem
#መልክአ_ሕማማት፤ (የ፯ቱ ጊዜያት ጸሎት)
*መልክአ ሕማማት ማለት ስለ ጌታችን መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ሕማም፥ መከራ፥ ስቃይ፥ የሚናገር መጽሐፍ ሲሆን፤ ደራሲው ታላቁ ሊቅና የደብረ ባሕርይ ጋሥጫ መምህር #አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋሥጫ_ ነው፡፡
*መልክአ ሕማማት በባለ 3ት መስመር አርኬ የተደረሰ ግጥማዊ ድርሰት ሲሆን፤ የተደረሰውም በ7ቱ የጸሎት ጊዜያት አንጻር በመሆኑ ‹‹#ጸሎት_ዘሰባዐቱ_ጊዜያት›› በሚል መጠሪያም ይጠራል፡፡ የእያንዳንዱ ጊዜ ድርሰትም በዋነኛነት 3ት ክፍሎችን የያዘ ነው፤ እነርሱም፤
1ኛ) ስብሐተ እግዝእትነ ማርያም /የእመቤታችን ምስጋና/
2ኛ) ስበሐተ ኢየሱስ ክርስቶስ /የኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና/
3ኛ) ስብሐተ ሥሉስ ቅዱስ /የሥሉስ ቅዱስ ምስጋና/
**በ7ቱ ጊዜያት ጸሎት ማድረስ እንደሚገባን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙር 118 ላይ ‹‹ሰባት ጊዜ በቀን አመሰግንሃለሁ ይላል››፤ አባቶቻችን ሐዋርያትም ይህንኑ ደንግገዋል፡፡ /ዲድስቅልያ 37፣ ቀሌምንጦስ 1ና 7፣ አቡሊዲስ 25ኛና 27ኛ፣ ባስልዮስ 28ኛ አንቀጽ፣ ፍትሐ ነገሥት ገጽ 21/፡፡
፠ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ መልክአ ሕማማትን ሲደርስም በ7ቱ የጸሎት ጊዜያት የተፈጸሙትን ድጊቶች ከ3ቱ የየጊዜያቱ የድርሰቱ ክፍሎች ምስጋና (የማርያም፣ የጌታ፣ የሥሉስ ቅዱስ ምስጋና) ጋር እያመሠጠረና እያራቀቀ፥ እያስዋበና ምሥጢር እያመጣ፤ እንደ ወርቅ እያንከባለለ፥ እንደ ሸማ እየጠቀለለ፥ በግጥም እያስጌጠ፥ በቃላት እየሰደረ፥ በዜማ እያሸበረቀ፥ መንፈስን እየመሰጠ፤ ነው የደረሰው፡፡
#የ7ቱ_የጸሎት_ጊዜያት_የሚባሉትም
፠1ኛ) መንፈቀ ሌሊት(ሌሊት 6 ሰዐት)፤ ጌታችን የተወለደበት፥ የተጠመቀበት፥ የተነሣበትና ዳግመኛ የሚመጣበት ፥ … ሰዐት ነው፡፡
፠2ኛ) ነግህ (ማለዳ፥ ጧት)፤ ጨለማን አርቆ ብርሃንን የሚያመጣበት፥ አባታችን ቅዱስ አዳም የተፈጠረበት፥ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ በጲላጦስ አደባባይ ፊት ቁሞ የተመረመረበት፥ …. ሰዐት ነው፡፡
፠3ኛ) ሠለስት (ጠዋት ሦስት ሰዐት)፤ እናታችን ሔዋን የተፈጠረችበት፥ ነቢዩ ዳንኤል ጸሎት ያደረሰበት፥ እመቤታችን ከቅዱስ ገብርኤል ብሥራትን ሰምታ የጸነሰችበት፥ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ለኛ ሲል በጲላጦስ አደባባይ የተገረፈበት፥ ….. ሰዐት ነው፡፡
፠4ኛ) ቀትር (6 ሰዐት)፤ አጋንንት የሚሰለጥኑበት ሰዐት ስለሆነ እንዳይሰለጥኑብን፥ አዳም ዕፀ በለስን በልቶ የሳተበት ስለሆነ እንዳንስት እንጸልያለን፡፡ በተጨማሪም ነቢዩ ሄኖክ ቤተ መቅደስን ያጠነበት፥ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ለኛ ሲል በመስቀል ላይ የተሰቀለበት፥ ….. ሰዐት ነው፡፡
፠5ኛ) ተስዓት (ዘጠኝ ሰዐት)፤ ቅዱስ ጴጥሮስና ዮሐንስ ለጸሎት ወደ ቤተ መቅደስ የወጡበት፥ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ በፈቃዱ ነፍሱን ከሥጋው የለየበት፥ ….. ሰዐት ነው፡፡
፠6ኛ) ሠርክ (ዐሥራ አንድ ሰዐት)፤ ነቢዩ ኤልያስ መሥዋዕት የሰዋበት፥ ዕዝራ ጸሎትን ያቀረበበት፥ ሕዝቅያስ ጸልዮ ፀሐይን ወደ ዐሥር ደረጃዎች የመለሰበት፥ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ወደ በፈቃዱ ወደ አዲስ መቃብር የወረደበት፥ …… ሰዐት ነው፡፡
፠7ኛ) ንዋም (የመኝታ ሰዐት)፤ መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ በጌቴሴማኒ የጸሎትን ሥርዐት ያስተማረበት ፥ እንዲሁም ሌሊቱን በመላእክት ጥበቃ ከርኵሳን አጋንንት እንዲጠብቀን የምንጸለይበት …… ሰዐት ነው፡፡
#ለቡ(ልዩ ማስታወሻ)!! ይህ ታላቅ ጸሎት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስር ባሉ በሁሉም ገዳማትና አድባራት በሰሙነ ሕማማት የሚደርስ ሲሆን፤ በአንዳንድ ትላልቅ ገዳማት (እንደ ዋልድባ፣ ማኅበረ ሥላሴ፣ ደብረ ባሕርይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ወደብረ ጎል አቡነ በጸሎተ ሚካኤል) ያሉ መነኰሳትና መናንያን ግን ከዓመት እስከ ዓመት ጸሎቱን በዜማ /በንባብ/ ያደርሱታል፡፡
/በቀጨኔ ደ.ሰላም መድኀኔዓለምና ደ.ት.ቅ.ገብርኤል ቤ.ክ ፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ፤ ትምሕርት ዋና ክፍል ፥ ንዑስ ክፍል /ሕትመት እና ሚዲያ/ የተዘጋጀ ::
#share
Contact: https://t.me/finotehiwot1927
.Facebook...
https://www.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
.YouTube... https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w,
.Telegram...
https://t.me/medihanaelem
http://tiktok.com/@finotehiwot
www.finotehiwotsundayschool.com
YouTube https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w
Telegram https://t.me/medihanaelem