መዝገበ ቅዱሳን
20.7K subscribers
1.92K photos
9 videos
6 files
24 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞

❖ መስከረም ፳፫ (23) ❖

✞✞✞ እንኩዋን ለቅዱሳን #ጻድቃን_ወሰማዕት
#አውናብዮስና_እንድርያስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል
በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

+"+ #ቅዱሳን_አበው_አውናብዮስ_ወእንድርያስ +"+

=>4ኛው መቶ ክ/ዘ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ዘመነ
ከዋክብት ይባላል:: ምናልባትም በዓለም ላይ ላለፌት
1,500 ዓመታት ያንን ዘመን መልሶ ማየት አልተቻለም::

*ያ ዘመን ብዙ #ሰማዕታት ነበሩበት::
*ያ ዘመን ብዙ #ሊቃውንት ነበሩበት::
*ያ ዘመን ብዙ #ጻድቃን ነበሩበት::
*ያ ዘመን ብዙ #ደናግል ነበሩበት::
*ያ ዘመን ብዙ #መነኮሳት ነበሩበት::
*ያ ዘመን ብዙ #ባህታውያን (ግኁሳን) ነበሩበት::

+ዘመኑ #ዘመነ_ብርሃን ነው:: እልፍ አእላፍ ቅዱሳን
በዚህ ዘመን አብርተዋልና:: ጠላት ሰይጣንን ከቦታው
አሳድደው አስጨንቀውታል:: በዚህ ዘመነ ብርሃን ከወደ
ምሥራቅ ካበሩ ከዋክብት መካከል ደግሞ በዚህ ዕለት
አባቶቻችን ቅዱሳን አውናብዮስና እንድርያስን
እናዘክራለን::

+ቅዱሳኑ ባለ ብዙ ሃብት ነበሩ:: ከሰማዕታት: ከጻድቃን:
ከደናግል: ከሊቃውንቱም አሉበት:: ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

¤በተጠቀሰው ዘመን በቅዱስ #ጊዮርጊስ ሃገር በልዳ
ከከበሩ ወገኖች ተወልደዋል::

+የቅዱሳኑ ወላጆች ክርስቲያኖች: በዚያውም ላይ ባለ
ሥልጣኖችና ሃብታሞች ነበር:: ልጆቻቸውን
(አውናብዮስንና እንድርያስን) ሥጋዊውንም:
መንፈሳዊውንም ትምሕርት አስተምረዋቸዋል:: ወጣት
በሆኑ ጊዜ ወላጆቻቸው የዚህን ዓለም ነገር
ሲያስቡላቸው: እነሱ ግን የተሻለውን እድል ያስቡ ነበር::

+ዘወትር ገድላተ ቅዱሳንን ያነቡ: ዜና አበውን ይሰሙ
ነበርና ይመንኑ ዘንድ ልቡናቸው አወካቸው:: በአንዲት
ሌሊት ግን በመንፈስ ቅዱስ አጋዘዥነት ወስነው:
ከሃገራቸው #ልዳ ወጥተው ወደ ገዳም ሔዱ::

+ክብር ለቅዱሳኑ #አባ_ሮማኖስና #አባ_በርሶማ ይሁንና
በወቅቱ በሶርያ ምድር ገዳማዊ ሕይወት ተስፋፍቶ: ብዙ
አድባራት በበርሃ ውስጥ ነበሩ:: 2ቱ ቅዱሳንም በአንዱ
ገዳም ውስጥ ገብተው አገለገሉ::

+ተጋድሏቸውን እያበረቱ እስከ ምንኩስና ደረጃም ደረሱ::
ተጋድሏቸው በጾም: በጸሎትና በትእግስት ብቻ
አይደለም:: በትሕትና በፍቅር በደግነትና በመታዘዝም
ጭምር ነበር እንጂ::

+የምንኩስናና የገዳማዊ ሕይወት ጠላት 'ፍቅረ ዓለምና
ፍትወት እንስሳዊት' ናቸው:: አንድ ሰው ከዚህ ዓለም
ቁሳቁስ ሳይርቅ መናኝ መሆን አይችልም:: ቅዱሳኑ ግን
በመንኖ ጥሪት ይህችን ዓለም ከነኮተቷ ናቁዋት:
አቃለሏት::

+የሥጋ ፈቃዳቸውን ያጠፉ ዘንድ ሰውነታቸውን በጾምና
በጸሎት: ዕረፍትም በማሳጣት ቀጧት:: #እግዚአብሔር
ደግሞ ስለዚህ ፈንታ ጸጋውን አበዛላቸው:: ቅዱሳኑ
በሶርያ ገዳማት ለዘመናት ከተጋደሉ በሁዋላ ወደ ግብጽ
ለመውረድ ወሰኑ:: ምክንያታቸው ደግሞ:-

1ኛ.ከውዳሴ ከንቱ ለመራቅ
2ኛ.ከቅዱሳን አበው ለመባረክ እና
3ኛ.ለተሻለ ተጋድሎ ለመብቃት ነበር:: እየጸለዩ
እያመሰገኑም ግብጽ: ቀጥሎም ገዳመ አስቄጥስ ደረሱ::

+ታላቁ #ርዕሰ_መነኮሳት_አባ_መቃርስን ፊት ለፊት
ቢያገኙት ደስ አላቸው:: ሐሴትንም አደረጉ::
እግዚአብሕርን በማደሪያዎቹ ማግኘት ይቻላልና:: የታላቁ
ቅዱስ ደቀ መዝሙር ሆነው: በድንግልና ተጠብቀው:
በተጋድሎ በርትተው በቦታው ለ3 ዓመታት ቆዩ::

+እግዚአብሔር ደግሞ ለሌላ አገልግሎት ፈልጐአቸው
ነበርና በዚያ ሰሞን በከተማ የነበሩ ሊቃውንት ወደ ገዳም
መጡ:: ገዳማውያንንም ዻዻስ ስላረፈብን "የምንሾመው
መልካም እረኛን ስጡን" አሏቸው::

+ገዳማውያኑ ሱባኤ ገብተው ቢጠይቁ መንፈስ ቅዱስ
ቅዱስ አውናብዮስን መረጠ:: አበውም ቅዱሱን ዽዽስና
ሲሾሙት ወንድሙን እንድርያስን ረዳት አደረጉት:: 2ቱ ቅዱሳን ከበርሃ ወደ
ከተማ መውጣታቸውን ተከትሎ ተጋድሏቸውን ለማበርታት
ወሰኑ::

+ምክንያቱም ለአንድ ገዳማዊ ከተማ ውስጥ ከመኖር
በላይ ፈተና የለምና:: ቅዱሳኑ ቀን ቀን ድውያንን
ሲጠይቁ: ሙታንን ሲቀብሩ: ሕዝቡን ሲያስተምሩ:
ሥጋውን ደሙን ሲያቀብሉ ውለው ሌሊት ይጋደላሉ::

+ለፈቃደ ሥጋቸው ሳያደሉ እንዲህ ባለ ቅድስና ኖረው
ደግሞ ሌላ ፈተና መጣ:: የከተማው ሃገረ ገዢ አረማዊ
በመሆኑ "ለጣዖት ስገዱ: ክርስቶስን ካዱ" ይል ጀመር::
ቅዱሳኑ ሕዝቡን በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባርም
ሊያስተምሩ ወደዋልና መኮንኑን "ተው! ተሳስተሃል"
አሉት::

+በዚህ ምክንያትም ብዙ ስቃይ ገጠማቸው::
በመጨረሻም በዚህች ዕለት ሰማዕት ሆነዋል:: ጌታም
ስለ ድንግልናዊ ሕይወታቸው: ስለ ወንጌል
አገልግሎታቸውና ስለ ሰማዕትነታቸው 3 አክሊላትን
አቀዳጅቷቸዋል::

=>አምላከ አበው ቸርነቱን ይላክልን:: የቅዱሳኑን
በረከትም ያሳድርብን::

=>መስከረም 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን
በዓላት=
1.ቅዱሳን ጻድቃን አውናብዮስ ወእንድርያስ (ሰማዕታት)
2.ቅዱስ ጐርጐርዮስ መንክራዊ
3.ቅድስት ቴክላ ድንግል
4.ቅዱስ ኤዎስጣቴዎስ ሰማዕት

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት
2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
3.ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን (ንጉሠ እሥራኤል)
4.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
5.ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ
6.አባ ሳሙኤል
7.አባ ስምዖን
8.አባ ገብርኤል

=>+"+ በጐንም ለማድረግ ብትቀኑ የሚያስጨንቃችሁ
ማን ነው? ነገር ግን ስለ #ጽድቅ እንኩዋ መከራን
ብትቀበሉ #ብጹዓን ናችሁ:: ማስፈራራታቸውንም አትፍሩ:
አትናወጡም:: ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስን
በልባችሁ ቀድሱት:: +"+ (1ዼጥ.3:13)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
@petroswepawulos