መዝገበ ቅዱሳን
24.2K subscribers
1.97K photos
9 videos
6 files
26 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡

እንኳን አደረሳችሁ

ርክበ ካህናት

=>ይህቺ ዕለት በቤተ ክርስቲያን "ርክበ ካህናት" : "ዕለተ ጥብርያዶስ" በመባል ትታወቃለች:: "ዳግሚት ዕለተ አግብኦተ ግብር" የሚሏትም አሉ::

+ #ርክበ_ካህናት በቁሙ "የካህናት ኖሎት (እረኞች) መገናኘትን" የሚመለከት ቃል ነው:: #የክብር_ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጐ ከተነሳ በሁዋላ ለደቀ መዛሙርቱ በየጸጋቸው መጠን እየተገለጠ ያጽናናቸው ያጸናቸው : ያስተምራቸው : ይባርካቸውም ነበር::

+እስከ ዕርገቱ ባሉ 40 ቀናትም መጽሐፈ ኪዳንን : ትምሕርተ ኅቡዓትን : ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን አስተምሯቸዋል:: በልቡናቸውም አሳድርድሮባቸዋል::

+#ቅዱስ_መጽሐፍ እንደሚል ደግሞ ከዕርገቱ አስቀድሞ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ 3 ጊዜ በጉባኤ ተገልጧል::
1.የትንሳኤ (ዮሐ. 20:19)
2.የአግብኦተ ግብር {ዳግም ትንሳኤ} (ዮሐ. 20:26)
3.የጥብርያዶስ /ዛሬ/:: (ዮሐ. 21:1)

+በተረፈው ግን ለድንግል ማርያም ሁሉን ዕለታት መገለጡን አበው ያስተምራሉ::

+በዚህች ዕለት በቅዱስ ዼጥሮስ መሪነት ሐዋርያቱ ወደ ጥብርያዶስ ሔዱ:: አሶችን ሊያጠምዱም በብዙ ደከሙ:: ነገር ግን ጌታችን በረድኤት አብሯቸው አልነበረምና አንዳች አሣ በመረባቸው ሊገባ አልቻለም::

+ማጥመድ (አስተምሮ ከክህደት ወደ ሃይማኖት : ከኃጢአት ወደ ጽድቅ መመለስ) የሚቻለው በረድኤተ እግዚአብሔር እንጂ በእውቀት ብዛት ወይም በአንደበተ ርቱዕነት ብቻ አይደለምና::

+ሲነጋ ግን #መድኃኒታችን ወደ ቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱ መጣ:: በጥብርያዶስ ባሕር ዳርቻም ቆሞ ታያቸው:: ከሚወደው ደቀ መዝሙሩ #ቅዱስ_ዮሐንስ በቀር የለየው ግን አልነበረም::

+ቸሩ አባት "ልጆቼ! አንዳች የሚበላ ነገር አላችሁ?" ሲል ጠየቀ:: "ጌታ ሆይ! የለም" አሉት:: "የለንም" ብሎ የሌለንን ነገር በጌታ ፊት ማመኑ እጅግ መልካም ነው:: ምክንያቱም ያጣነውን ነገር ያን ጊዜ ሊጠቁመን ቸርነቱ ብዙ ነውና::

+ያን ጊዜ ሐዋርያቱን መረባቸው በመርከብ ቀኝ እንዲጥሉ አዘዛቸው:: እነርሱም በደስታ ጣሉ:: በአግራሞት እስኪሞሉ ድረስ : መረባቸውም ሊቀደድ እስኪደርስ ድረስ 153 ዓሦች ተያዙላቸው::

+ያን ጊዜም የሚወደው ደቀ መዝሙሩ ቅዱስ ዮሐንስ ምስጢር አወጣ:: ለቅዱስ ዼጥሮስ "#ጌታ እኮ ነው" አለው:: ሽማግሌው ቅዱስ ግን ራቁቱን ነበርና ወደ ባሕሩ ተወረወረ::

+ከአፍታ በሁዋላም ጌታችን ከሐዋርያቱ ጋር በድጋሚ (ለ2ኛ ጊዜ) ለምሳ ተቀመጠ:: ባርኮ ሰጥቶ : ልባቸውን ሊያጸና አብሯቸው በላ::
*በዚያች ሰዓት ቅዱስ ዼጥሮስን 3 ጊዜ "ትወደኛለህን?" ሲል ጠየቀው:: ቅዱሱ አረጋዊም እየደጋገመ "ለሊከ ተአምር ከመ አነ አፈቅረከ (እንድወድህ አንተ ታውቃለህ)" ሲል መለሰ::

+ጌታም በበጐች ሐዋርያት (ካህናት) : በጠቦቶች አርድእት (ዲያቆናት) : በአባግዕት 36ቱ ቅዱሳት አንስት (ምዕመናን ወምዕመናት) ላይ ሁሉ እረኛ እንዲሆን ሾመው::

+ቀጥሎም የሰማዕትነቱን ምስጢር ገልጦለት "ተከተለኝ" (ለጊዜው በእግር : በሁዋላ ግን በግብር ምሰለኝ) ብሎታል:: ወልደ ነጐድጉዋድ ወፍቁረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስም ሞትን እንደማይቀምስ እንዲሁ ተናግሮለታል::

+ይህች ዕለትም እነዚህ ሁሉ ተግባራት የተከናወኑባት ናትና በእጅጉ ትከበራለች:: አባቶቻችን ዻዻሳትም ከጌታና ከደቀ መዛሙርቱ አብነትን ነስተው በዚህች ቀን 2ኛውን ታላቅ ሲኖዶስ ያደርጋሉ:: መንፈስ ቅዱስ እየተራዳቸው ለቤተ ክርስቲያንና ለኛ ለልጆቿ የሚጠቅም መመሪያን ያወጣሉ ብለን እንጠብቃለን::

+በተለይ ደግሞ በአምናው ርክበ ካህናት ስለ #28ቱ_ኢትዮዽያውያን_ሰማዕታት የሚባለውን ሁሉ ተስፋ አድርገን ነበር:::: #ከከዋክብት_ሰማዕታት ጋር ዜናቸውን ለመደመር (ለመመስከር) እጅጉን ናፍቀንም ነበር:: ዘንድሮም አዲስ ነገር ካለ ብንሰማ ደስ ይለናል::

+በተረፈው ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን የወረራት የጠላትን ጦር የሚሰብር : ምክራቸውን የሚመክት : ክፋታቸውን የሚያኮላሽ ውሳኔ ከአባቶቻችን እንጠብቃለን:: መንጋው ባዝኗልና:: እረኝነት የተሰጣቸው አባቶቻችን እንዲነቁልንም ከተስፋ ጋር እንማጸናለን::

=>የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ መንፈሱ ከአባቶቻችንና ከእኛ ከኃጥአኑ ጋር በረድኤት ይኑር::

ከበዓሉ በረከትም ያድለን !!

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
#መጋቢት_26

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት #የክብር_ባለቤት_ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ፣ የሐዲስ ኪዳንንም የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው፣ የከበረችና የተመሰገነች #ድንግሊቱ_ኢዮጰራቅስያ አረፈች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ምሴተ_ሐሙስ

መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ እንዲህም አላቸው። እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ።

ደግሞ የሐዲስ ኪዳንን የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው። አሁንም በዚች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችንን ለአይሁድ ይሁዳ አሳልፎ ሰጠው።

ነቢያት ትንቢት እንደተናገሩ የሽያጩን ዋጋ ሠላሳ ብር ተቀበለ። ይቅርታው ቸርነቱ ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ለዘላለሙ ይኑር አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ኢዮዸራቅስያ

በዚህች ቀን የከበረችና የተመሰገነች ድንግሊቱ ኢዮጰራቅስያ አረፈች። ይችም የተቀደሰች ብላቴና የንጉሥ አኖሬዎስ ዘመዱ ለሆነ በሮሜ ከተማ ከቤተ መንግሥት የአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ናት።

የሚሞትበትም ቀን በደረሰ ጊዜ እርሷን ልጁን ለንጉሥ አኖሬዎስ ይጠብቃት ዘንድ አደራ ሰጠው። አባቷም ካረፈ በኋላ ለአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ንጉሥ አኖሬዎስ አጫት።

በዚያም ወራት እናቷ የመሬቷን ግብር ልትቀበል በሏ የተወላትን የአትክልት ቦታዎቿም ያፈሩትን ይችንም ቅድስት ብላቴናዋን ከእርሷ ጋር ወሰደቻት። ዕድሜዋ ዘጠኝ ዓመት ሁኖ ሳለ አስከትላት ወደ ግብጽ ሔደች።

ወደ ግብጽ አገርም በደረሱ ጊዜ ሥራቸውን እስከሚፈጽሙ በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ ኖሩ። በዚያ ገዳም ውስጥ የሚኖሩ ደናግል ለገድል የተጸመዱ ናቸው። የሥጋ መብልን ቅባትም ቢሆን ጣፋጭ ፍሬዎችንም ምንም ምን አይበሉም ወይንም ቢሆን ከቶ አይቀምሱም ያለ ምንጣፍም በምድር ላይ ይተኛሉ።

ኢዮጰራቅስያም በዚያ ገዳም ውስጥ መኖርን ወደደች ገዳሙን ከምታገለግል መጋቢዋ ጋር ተፋቅራለችና። መጋቢዋም አንቺ ከዚህ ገዳም ወጥተሽ ተመልሰሽ እጮኛሽን ላትፈልጊ ቃል ግቢልኝ አለቻት ኢዮጰራቅስያም በዚህ ነገር ቃል ገባችላት።

እናቷ ሥራዋን በፈጸመች ጊዜ ወደ አገርዋ ልትመለስ ወደደች ልጅዋ ግን እኔ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ሙሽርነት ስለማልሻ ራሴን ለክብር ባለቤት ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰማያዊ ሙሽራ ሰጥቻለሁ ብላ ከእርሷ ጋር መመለስን አይሆንም አለች።

ብላቴናዋ ከእርሷ ጋር እንደማትመለስ በተረዳች ጊዜ ገንዘቧን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች መጽውታ ከልጁዋ ጋር በዚያ ገዳም ብዙ ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አረፈችና በዚያው ቀበርዋት።

ንጉሥ አኖሬዎስም የኢዮጰራቅስያ እናቷ እንደሞተች ሰምቶ ለአጫት ያጋባት ዘንድ ኢዮጰራቅስያን እንዲአመጧት መልእክተኞችን ላከ። ቅድስቲቱም ንጉሥ ሆይ እወቅ የክብር ባለቤት ለሆነ ለሰማያዊ ሙሽራ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ራሴን ሰጥቻከሁና ቃል ኪዳኔን መተላለፍ አይቻለኝም ብላ ወደ ንጉሡ ላከች።

ንጉሥ አኖሬዎስም መልእክቷን በሰማ ጊዜ አደነቀ ስለርስዋም አለቀሰ እርስዋ በዕድሜዋ ታናሽ ብላቴና ናትና። ይህች የከበረች ኢዮጰራቅስያ ግን ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ለመንፈሳዊ ሥራ እጅግ የተጠመደች ሆነች በየሁለት ቀን ሁለት ሁለት ቀን እያከፈለች መጾም ከዚያም በየሦስት ቀን ሦስት ሦስት ቀን ትጾም ጀመር ከዚያም በየሰባት ቀን ሰባት ሰባት ቀን የምትጾም ሆነች።

በተለየች በከበረች አርባ ጾም ምንም ምን የምትበላ አልሆነችም። ሰይጣንም በእርሷ ላይ ቀንቶ አስጨናቂ በሆነ አመታት እግርዋን መታት ብዙ ቀኖችም በሕማም ኖረች ከዚያም እግዚአብሔር ራርቶላት ከደዌዋ አዳናት በሽተኞችንም ታድናቸው ዘንድ በሽተኞችን የምትፈውስበትን ሀብት ሰጣት።

ለእመ ምኔቷና ለእኀቶቿ ደናግል በመታዘዝ ታገለግላቸው ነበር በእኀቶች ደናግል ሁሉ ዘንድ የተወደደች ናት። በአንዲት ዕለትም እመ ምኔቷ አክሊላትንና አዳራሾችን እንደ አዘጋጁ ራእይን አየች እርሷም እያደነቀች ከልጆቼ ለማን ይሆን ይህ የሚገባት ስትል እሊህ አክሊላትና አዳራሾች የተዘጋጁላት ለልጅሽ ለኢዮጰራቅስያ ነው እርሷም ወዲህ ትመጣለች አሏት።

ይህንንም ራእይ ለደናግሎች ነገረቻቸው እግዚአብሔርም ከዚህ ዓለም መከራ ሊያሳርፋት እስከ ወደደበት ቀን ለኢዮጰራቅስያ እንዳይነግሩዋት አዘዘቻቸው።

ከዚህ በኋላ በሆድ ዝማ ሕማም ጥቂት ታመመች ሁሉም ደናግል ከእመ ምኔቷ ጋር ወደ እርሷ ተሰበሰቡ ያቺ ቃል ኪዳን ያስገባቻት የምትወዳት መጋቢዋም መጣች በእግዚአብሔርም ዘንድ እንድታስባቸው ለመንዋት እርሷም በጸሎታቸው እንዲአስቧት ለመነቻቸው ከዚያም አረፈች ።

የተቀደሰችና የተከበረች እርሷን እኅታቸውን አጥተዋታልና ደናግሉ እጅግ አዝነው አለቀሱ። ከዚህም በኋላ የምትወዳት የገዳሙ መጋቢ የነበረች አረፈች ከእርስዋም በኋላ እመ ምኔቷ ጥቂት ቀን ታመመች ደናግሎችንም ሰብስባ በላያችሁ የምትሾሙትን እመ መኔት ምረጡ ስለ እኔ ኢዮጰራቅስያ ለምናለችና እኔ ወደ ጌታዬ ኢየሱስ እሔዳለሁ አሁን ግን ደጁን በላዬ ዘግታችሁ ሔዱ አለቻቸው እነርሱም እነዳዘዘቻቸው አደረጉ። በማግሥቱም ማለድ ብለው ሲደርሱ አርፋ አገኟት፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)