መዝገበ ቅዱሳን
24.2K subscribers
1.97K photos
9 videos
6 files
26 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
#መስከረም_26

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሃያ ስድስት በዚች ቀን #መጥምቁ_ዮሐንስ የተጸነሰበት፣ የዮስጦስ ልጅ #ቅዱስ_አቦሊ የስጋው ፍልሰት የሆነበት ቀን ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ_ጽንሰቱ

መስከረም ሃያ ስድስት በዚች ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ገብርኤልን ወደ በራክዩ ልጅ ዘካርያስ ልኮት መጥምቁ ዮሐንስ ከእርሱ ስለ መወለዱ አበሠረው።

ስሙ የተመሰገነ እግዚአብሔር ልጅን ይሰጠው ዘንድ አስቀድሞ ሁል ጊዜ በመጸለይ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ነበር። ልጅ ያልወለደውን እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ምድርን ምሉዋት ያለውን በረከት ያጣ ነው በማለት እስራኤል ይገዳደሩት ነበርና።

ልመናውንም ሰማ በቤተ መቅደስም ቁሞ ዕጣንን ሲያሳርግ መልአኩን ላከለት በከበረ ወንጌልም እንደተባለ መንገዱን ይጠርግ ዘንድ በንጉሥ ክርስቶስ ፊት እንደሚሔድ የተነገረለት ታላቅ ነቢይ ዮሐንስ ከእርሱ መወለዱን አበሠረው።

ዘካርያስም የሰውነቱን መድከም የመውለጃውም ዘመን እንዳለፈና ፈጽሞ እንዳረጅ የሚስቱም እንዲሁ ዘመኗ እንዳለፈና ፈጽማ እንዳረጀች መካንም እንደሆነች ያውቃልና ስለዚህ ይህ ነገር እንዴት ይሆንልኛል እኔ ያረጀሁ ሽማግሌ ነኝ ሚስቴም እንዲሁ ዘመኗ አልፎ መካን ሁናለች ብሎ የእግዚአብሔርን መልአክ ተከራከረው።

መልአኩም እኔ ይህን ልነግርህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወዳንተ ተልኬ ነበር ልትጠራጠር ባልተገባህም ነበር አሁንም ይህ በጊዜው እስቲፈጸም ዲዳ ሁነህ መናገር ይሳንሃል ብሎ ገሠጸው። ዘካርያስም የወልደ እግዚአብሔርን መንገድ የሚጠርግ ዮሐንስ እስከሚወለድበት ጊዜ ድረስ ዲዳ ሆነ።

በሚገረዝበትም ቀን የሕፃኑን አባት ዘካርያስን የሕፃኑን ስም ምን ብለው እንደሚሰይሙት ጠየቁት እርሱም ብራና ለምኖ ስሙ ዮሐንስ ነው ብሎ ጻፈ በዚያም ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው። ስለ ልጁ ዮሐንስም እርሱ የልዑል ነቢይ እንዲባል መንገዱንም ይጠርግ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት እንደሚሔድ ትንቢት ተናገረ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቦሊ

በዚችም ቀን የዮስጦስ ልጅ ቅዱስ አቦሊ የስጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም ቅዱስ አቦሊ ከመንግሥት ልጆች ውስጥ ነበር ዐላውያንን ወግቶ በተመለሰ ጊዜ ዲዮቅልጥያኖስን ክብር ይግባውና ክርስቶስን ክዶ አገኘው።

ያም አቦሊና አባቱ ዮስጦስ ሌሎችም የመንግሥት ልጆች ሁሉ ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስን ሊያጠፉትና መንግሥትን ከእርሱ ሊወስዱ ችሎታ ሲኖራቸው የማታልፍ ሰማያዊት መንግሥትን አሰቡ።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ አቦሊ ወደ ንጉሡ ቀርቦ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም አብዝቶ አባበለው። እንዲሁም አባቱ ዮስጦስንና የከበረች እናቱ ታውክልያን አባበላቸው እነርሱ ግን አልሰሙትም ልባቸው በመድኅን ክርስቶስ ፍቅር ተነድፏልና።

ንጉሡም እነርሱን በዚያ ማሠቃየትን ፈራ ስለዚህም ከመልእክት ደብዳቤ ጋር ወደግብጽ ስሙ ኄርሜኔዎስ ወደሚባል የእስክንድርያ ገዥ ላካቸው በመልእክቱም እንዲህ አለው ዮስጦስና ሚስቱ ታውክልያ ልጃቸው አቦሊም ወደአንተ በሚደርሱ ጊዜ አባብላቸው አለዚያም እየአንዳንዳቸውን ለያያቸው።

በዚያችም ሌሊት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዮስጦስና ለሚስቱ ታውክልያ ለልጃቸው አቦሊም ተገልጦላቸው አጽናናቸው ከእነርሱም የሚሆነውን ነገራቸው የጸና ቃል ኪዳንም ሰጣቸው።

ወደ መኰንኑ ኄርሜኔዎስም በደረሱ ጊዜ ስለእነርሱ እጅግ አደነቀ እነርሱ መንግሥታቸውን ትተዋልና ክፋ ነገርንም ሊናገራቸው አልደፈረም ከምክራቸው ይመለሱ ዘንድ በለሰለሰ ቃል ሸነገላቸው እንጂ ነገር ግን አልሰሙትም።

ከዚህም በኋላ በእነርሱ ላይ ተቆጥቶ ለእየብቻቸው ለያያቸው ቅዱስ ዮስጦስን ወደ እንዴናው ከተማ ሚስቱን ታውክሊያን ፃ ወደ ሚባል አገር ልጃቸው አቦሊንም ብስጣ ወደ ሚባል አገር ሰደዳቸው ለእያንዳንዳቸውም የሚአገለግላቸው አንዳንድ አገልጋይ ሰጣቸው።

ቅዱስ አቦሊም ወደ ሀገር ብስጣ በደረሰ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመኰንኑ ፉት ታመነ። መኰንኑም ጽኑ ሥቃይን በእሳት ቃጠሎና በመንኰራኵር አሰቃየው ሕዋሳቱንም ቆራርጦ ለአንበሶች ጣለው ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስም ከሥቃዩ ሁሉ አድኖ ያለ ጉዳት በጤና አነሣው።

ብዙዎች ሰዎችም ስቃዩንና ዳግመኛ መዳኑን በአዩ ጊዜ እጅግ አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም አምነው ሰማዕታት ሆኑ።

መኰንኑ ግን እጅግ ተቆጥቶ የቅዱስ አቦሊን ቆዳውን እንዲገፍፉትና ጨውና መጻጻን በማቅ አምጥጠው ቍስሉን እንዲያሹ አዘዘ ይህንንም ሁሉ አደረጉበት።

ከዚህም በኋላ ቆዳውን አሸክመው በከተማ ውስጥ ሁሉ አዞሩት ወደ ጌታችንም እንዲህ ብሎ ጸለየ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ርዳኝ ከዚህ ሥቃይም አድነኝ። ያን ጊዜም የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ወደርሱ መጣ ሁለመናውንም ዳስሶ አዳነው።

መኰንኑም በእርሱ ላይ የሚያደርገውን እስኪያስብ ከእሥር ቤት እንዲጨምሩት አዘዘ። ቅዱስ አቦሊም ቁሞ ጸለየ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ተገለጠለትና የመረጥኩህ አቦሊ ሰላም ለአንተ ይሁን እኔም ከአንተ ጋር እኖራለሁ አለው ጌታችንንም በአየው ጊዜ እጅግ ደስ አለው ክብር ይግባውና ለጌታችንም ሰገደለት።

ስሙ አብስኪሮን የሚባል አንድ ባለ ጸጋ ነበር የቤቱንም ግድግዳ አፍርሰው አዲስ ይሠሩለት ዘንድ ሠራተኞችን አመጣ ሥራቸውንም እስኪጨርሱ ከዚያ ይቆሙ ዘንድ ሁለቱን ልጆቹን አዘዛቸው።

ከግርግዳውም ላይ በወጡ ጊዜ ግርግዳው ተደርምሶ ዐሥራ ስድስት ሰዎችና ሁለቱ ልጆቹ ሞቱ። ባለጸጋውም የሆነውን በአየ ጊዜ ልብሱን ቀደደ ጩኾም አለቀሰ ወደ ቅዱስ አቦሊም ሒዶ ከእግሩ በታች ሰገደለት እንዲህም አለው ራራልኝ ሁለቱ ልጆቼ ሙተዋልና ከእነርሱም ጋራ ዐሥራ ስድስት ሰዎች ሞቱ። ከሞትም ብታሥነሣቸው እኔ በአምላክህ አምናለሁ።

ያን ጊዜም ቅዱስ አቦሊ ተነሣ እንዲህ ብሎ ጸለየ ስለ ቅዱስ ስምህ መከራን እቀበል ዘንድ የመረጥከኝ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በእኒህ በሞቱ ሰዎች ላይ ኃይልህን ግለጥ። እኒህ ሰዎች ሁሉ እንዲአምኑ ያለ አንተም ሌላ አምላክ እንደሌለ ያውቁ ዘንድ ከሞት አንሣቸው። ላንተም ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን።

ከዚህም በኋላ የተገፈፈ ቆዳውን ወስዶ በሞቱት ሰዎች ላይም ዘረጋውና በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከሞት ተነሡ አለ። ወዲያውም ሁሉም ድነው ተነሡ በዚያ ያሉ ሕዝብም ይህን ድንቅ ሥራ በአዩ ጊዜ የክርስቲያን አምላክ የቅዱስ አቦሊም አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ነው እኛም እናምንበታለን ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ የለምና እያሉ ጮኹ።

ባለ ጸጋው አብስኪሮንም መጥቶ ለቅዱስ አቦሊ እንዲህ እያለ ሰገደ ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ይግባውና እውነተኛ አምላክ እንደሆነ ዛሬ አወቅሁ እኔም አምንበታለሁ። ከቤተሰቦቹም ሁሉ ጋር አመኑ መኰንኑም አፈረ።

ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ አቦሊ ተገለጠለት እንዲህም ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠው። በመከራ ውስጥ ያለ ሰው በስምህ ርዳታ ቢለምን እኔ እሰማዋለሁ ልመናውን ፍላጎቱንም እፈጽምለታለሁ። በስምህ ቤተ ክርስቲያን ለሠራም እኔ በሰማያት ብርሃናዊ ማደሪያ ቤት እሠራለታለሁ የገድልህን መጽሐፍ የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውን ወይም የሚሰማውን እኔ በኪሩቤል ክንፎች ላይ ስሙን እጽፉለሁ በአብርሃም በይስሐቅና በያዕቆብ እቅፍም አሳርፈዋለሁ ተድላ ደስታ ካለባት ከገነት ፍሬዎችም እመግበዋለሁ።
#ጥቅምት_21

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሃያ አንድ በዚህችም ቀን #እመቤታችን_ተአምራትን_አድርጋ_ሐዋርያው_ማትያስን ከእሥራት ቤት ያወጣችበት፣ #የነቢይ_ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ፣ የማርታና የማርያም ወንድም #የቅዱስ_አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት፣ የቅዱስ አባት #አባ_ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም እረፍት ነው፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#እመቤታችን_ለሐዋርያው_ማትያስ_ያደረገችለት_ተአምር

በዚህችም ቀን እመቤታችን ማርያም ተአምራትን አድርጋ ደቀ መዝሙር ማትያስን ከእሥራት ቤት አዳነችው።

የከበሩ ቅዱሳን ወንጌልን በዓለም ዞረው ይሰብኩ ዘንድ ዕጣ ሲጣጣሉ ለቅዱስ ማትያስ ዕጣ የደረሰው ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ነበር፡፡ ይህችም ሀገር እስኩቴስ የተባለች ሩሲያ እንደሆነች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ፍንጭ ሰጥተዋል፡፡

ማትያስም እነዚህ ሰውን የሚበሉ ሰዎች አገራቸው እንደደረሰ ዐይኑን አውልቀው አሠሩት፡፡ ምግባቸውም የመጻተኛ ሰው ሥጋ ነው፡፡ በልማዳቸው መሠረት መጻተኛን ሰው ገና እንደያዙት ዐይኖቹን ዐውልቀው በእሥር ቤት ያኖሩታል፡፡ እስከ 30 ቀንም ድረስ ሳር እያበሉ ያስቀምጡትና በ30ኛው ቀን አውጥተው አርደው ይበሉታል፡፡

ሐዋርያው ማትያስንም በልማዳቸው መሠረት ዐይኖቹን አውልቀው አሠሩት፡፡ ሐዋርያውም በእሥር ቤት ሆኖ በዚያ ላይ ዐይኖቹን ታውሮ ሳለ በጭንቅ ወደ ጌታችንና ወደ እመቤታችን ይለምን ነበር፡፡ ነገር ግን እመብርሃንና ልጇ መድኃኔዓለም 30ኛው ቀን ሳይፈጸም ሐዋርያው እንድርያስን ወደ እርሱ ላኩለት፡፡ ማትያስም ዐይኑን ፈወሱለትና ማየት ቻለ፡፡

እንድርያስም በተዘጋው በር በተአምራት ገብቶ አሥርቤቱ ውስጥ ያሉ እሥረኞችን በስውር አውጥቶ ከከተማው ውጭ ካስቀመጣቸው በኋላ ሁለቱ ሐዋርያት ተመልሰው ሰውን ለሚበሉት ሰዎች ተገለጡላቸው፡፡ እነርሱም ይዘው በአንገታቸው ገመድ አግብተው ለ3 ቀን በሀገራቸው ጎዳናዎች ላይ ሁሉ ጎተቱዋቸው፡፡ ሁለቱም ሐዋርያት በጸሎታቸው ከእሥር ቤቱ ምሰሶ ሥር ውኃ አፈለቁና ውኃው ሀገራቸውን ሁሉ እስኪያጥለቀልቅና ሰዎቹንም እስከ አንገታቸው ድረስ እስከሚደርስ ሞላ፡፡ ሁሉም በተጨነቁ ጊዜ ሁለቱ ሐዋርያት በፊታቸው ተገለጡና ‹‹በጌታችን እመኑ ትድናላችሁ›› በማለት ወንጌልን ሰብከውላቸው አሳመኗቸው፡፡ ምሥጢራትንም ሁሉ ገለጡላቸው፡፡ ደግሞም የአራዊት ጠባይን ከሰዎቹ ያርቅላቸው ዘንድ ወደ ጌታችንና ወደ ተወደደች እናቱ ከጸለዩ በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው፡፡ ያ የአውሬነት ጠባያቸውም ጠፍቶላቸው የዋህ፣ ቅንና ሩኅሩኆቸ ሆኑ፡፡ ሐዋርያትም ሃይማኖትን እያስተማሯቸው 30 ቀን አብረዋቸው ከተቀመጡ በኋላ አገልጋይ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ካህናትንና ዲያቆናትን ሾመውላቸው ወደ ሌላ ሀገር ሄዱ፡፡

ለሐዋርያት ሞገሳቸው ጣዕመ ስብከታቸው የኾነች ክብርት እመቤታችን ለእኛም ትለመነን!

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኢዩኤል_ነቢይ

ዳግመኛም በዚህችም ቀን የነቢይ ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም የእስራኤልን ልጆች የሚያስተምርና የሚገሥጻቸው ነበር ስለ ክርስቶስም በኢየሩሳሌም መኖርና ማስተማር ትንቢት ተናገረ። ደግሞም ስለ መከራው በሐዋርያትና በሰባ ሁለቱ አርድእት በሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ላይ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ እንዲህ ሲል ተናገረ።

ከዚህ በኋላ በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ ከመንፈሴ አሳድርበታለሁ ሴቶች ልጆቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ ትንቢትን ይናገራሉ አለቆቻችሁ ሕልምን ያልማሉ ጎልማሶቻችሁም ራእይን ያያሉ። ሁለተኛም እንዲህ አለ ያን ጊዜ ከተራራው ማር ከኮረብታውም ወተት ይፈሳል በቤተ እግዚአብሔር አጠገብ ካሉ ከይሁዳ አገሮች ሁሉ ምንጩ ከላይ ወደታች ይፈሳል።

ሙታን በሚነሡ ጊዜ ስለሚሆነው የፍርድ ሰዓት እንዲህ አለ ፀሐይና ጨረቃ ይጨልማሉ የከዋክብትም ብርሃናቸው ይጠፋል። የትንቢቱንም ወራት አድርሶ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አልዓዛር የማርታና የማርያም ወንድም

በዚችም ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው የቅዱስ አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት ሆነ።

ከክርስቲያን ነገሥታትም አንዱ ሥጋው በቆጵሮስ እንዳለ በሰማ ጊዜ ከቆጵሮስ ደሴት ወደ ቊስጥንጥንያ አፈለሰው። ሊአፈልሱትም በወደዱ ጊዜ በከበረ የደንጊያ ሣጥን ውስጥ ሁኖ በምድር ውስጥ ተቀብሮ አገኙት በላዩም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ነበረ ይህ በመቃብር ውስጥ አራት ቀን ከኖረ በኋላ ከሙታን ለይቶ ላስነሣው ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ የሆነ የቅዱስ አልዓዛር ሥጋ ነው።

ይህንንም በአዩ ጊዜ ደስ ተሰኙበት ተሸክመውም ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ወሰዱት ካህናቱም ሁሉ ወጥተው በታላቅ ክብር በመዘመርና በማመስገን ተቀበሉት በአማረ ቦታም አኖሩት በዚችም ቀን በዓልን አደረጉለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘኢየሩሳሌም

በዚህችም ቀን ለከበረች አገር ኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ እግዚአብሔርን በሚወድ የንጉሥ ሰይፈ አርዕድ ደግሞ ቈስጠንጢኖስ ለሚባል ልጁ በሆነ በንጉሣችን በዳዊት ዘመን አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከምስር አገር ታላላቆች እግዚአብሔርን የሚፈሩ የክርስቲያኖች አባቶች ልጅ ነው። የዲቁና መዓረግንም ለመሾም እስከ ተገባው ድረስ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። ከዚህም በኋላ በዲቁናው ሹመት አገልግሎቱን በአሳመረ ጊዜ የቅስና መዓረግ የሚገባው ሁኖ ቅስና ተሾመ።

በጾም በጸሎት እግዚአብሔርንም በመፍራት የተጠመደ ሁኖ ድኆችንና ችግረኞችን የሚወዳቸው የሚረዳቸው ሆነ ያን ጊዜ የሐዋርያት የሆነች የጵጵስና ሹመት የምትገባው ሁና በከበረች አገር በኢየሩሳሌም በእግዚአብሔር ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ሕዝቡንም በፈሪሀ እግዚአብሔርና በትሕትና የሚያስተምራቸው ሆነ።

እነርሱም ስለ ቅድስናው እጅግ የሚወዱት ሆኑ መልኩና የአንደበቱ አገላለጥ እንደ እግዚአብሔር መልአክ ያማረ ነበር። በሹመቱም ጥቂት ዘመናት ከኖረ በኋላ ከመንበረ ሢመቱ እስከ አራቀው ድረስ በላዩ ሰይጣን ምክንያትን አመጣ።

ይህም እንዲህ ነው በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ማርቆስ ዘመን በግዛቱ ውስጥ ያሉ እስላሞች ስለ ዐመፁበት የኢትዮጵያ ንጉሥ ፈጅቷቸው ነበርና ስለዚህ በግዛቱ ውስጥ በሚኖሩ እስላሞች ላይ ክፉ እንዳያደርግ ለኢትዮጵያ ንጉሥ መልእክት እንዲልክ ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን የምስር ንጉሥ አዘዘው።

አባ ማርቆስም ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥ ስለሚላኩ ሰዎች ከመኳንንቱ ከኤጲስ ቆጶሳቱና ከሀገር ታላላቆች ሽማግሌዎች ጋር ተማክሮ እሊህን ብሩሀን ከዋክብት የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስን የምስር ኤጲስቆጶስ አባ ሳዊሮስን በእውቀታቸው በአስተዋይነታቸውና በቅድስናቸው መረጡአቸው ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥም ይሔዱ ዘንድ ግድ አሏቸው።

እነርሱም ታዛዦች ሁነው ወደ ኢትዮጵያ መጡ የኢትዮጵያ ንጉሥም መምጣታቸውን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው እሊህንም ቅዱሳን አባቶች ይቀበሏቸው ዘንድ አሽከሮቹን በቅሎዎችን አስይዞ ላከ በመጡም ጊዜ በታላቅ ደስታ ሰላምታ አቀረበላቸው ከእርሳቸውም ቡራኬን ተቀበለ ታላቅ ክብርንም አከበራቸው ። እነርሱም የሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ተቀብሎ አንብቦ ለሊቀ ጳጳሳቱ ቃል ታዛዥ መሆኑን ገለጠላቸው።
#ጥቅምት_30

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሠላሳ በዚህች ቀን ወንጌልን የጻፈ ሐዋርያው #ቅዱስ_ማርቆስ የተወለደበት ነው፣ #የመጥምቁ_ዮሐንስ ቅድስት ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በግልጽ የታየችበት ነው፣ በገድል የተጸመደ #ቅዱስ_አባት_ባሕታዊ_አብርሃም ያረፈበት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ማርቆስ_ወንጌላዊ

ጥቅምት ሠላሳ በዚህች ቀን ለእስክንድርያ ሊቃነ ጳጳሳት አለቃ የሆነ ወንጌልን የጻፈ ሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ የተወለደበት ነው።

የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አርስጦቡሎስ ነው እርሱም ከአምስቱ አገሮች የሆነ የእናቱም ስም ማርያም ነው እርሷም በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ተጽፋለች እርሱም አስቀድሞ ስሙ ዮሐንስ ነው። በግብረ ሐዋርያት ማርቆስ በተባለ በዮሐንስ እናት ቤት ሐዋርያት ይጸልዩ ነበር ተብሎ እንደ ተጻፈ። እርሷም ባለጸጋ ነበረችና የዮናናውያንን የሮማይስጥን የዕብራይስጥን ትምህርት ለልጅዋ ለማርቆስ አስተማረችው።

በአደገም ጊዜ በርናባስ ወንጌልን ለመስበክ ከጳውሎስ ጋራ ሲሔድ ይዞት ሔደ በእነርሱም ላይ የሚደርስባቸውን መከራ አይቶ በጵንፍልያ ከተማ ሳሉ ትቷቸው ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።

ሐዋርያትም በተመለሱ ጊዜ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን አሕዛብ እንደ ተመለሱ እግዚአብሔርም በእጆቻቸው ላይ ድንቅ ተአምራትን እንዳደረገ ተናገሩ። ይህ ብላቴና ማርቆስም ከእርሳቸው ስለ መለየቱ አዘነ ተጸጸተ።

ከዚያም አብሮአቸው ሊሔድ ፈለገ አስቀድሞ ትቷቸው ስለተመለሰ ጳውሎስ ሊአስከትለው አልወደደም በርናባስ ግን ወሰደው አጎቱ ነውና። በርናባስም ከአረፈ በኋላ ወደ ሮሜ አገር ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ሒዶ ለእርሱ ደቀ መዝሙሩ ሆነ በዚያም ቅዱስ ጴጥሮስ የተረጐመለትን ወንጌልን ጻፈ በሮሜ አገርም አስተማረበት። ከዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዝና በሐዋርያትም ትእዛዝ ወደ እስክንድርያ አገር ሔደ። በውስጥዋም የከበረ ወንጌልን አስተማረ ደግሞም በአፍራቅያና በአምስቱ አገሮች በርቃ በሚባልም አገር ወደ እስክንድርያ ከተማ በገባ ጊዜ ጫማው ተቆረጠ።

በዚያም በከተማው መግቢያ ጫማ ሰፊ ነበረ። ቅዱስ ማርቆስም እንዲሰፋለት ለርሱ ሰጠው ሲሰፋም ጣቱን ወግቶ ሰነጠቀው ከእርሱም ደም ፈሰሰ በዮናኒም ቋንቋ ኢታስታዖስ አለ ትርጓሜውም አንድ እግዚአብሔር ማለት ነው። ቅዱስ ማርቆስም ስሙን የምትጠራው አውቀኸው ነውን አለው እንጠራዋለን እንጂ አናውቀውም አለ።

እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ አባታችን አዳም ትእዛዙን እንደተላለፈ የጥፋት ውኃም እንደ መጣ ሙሴንም እንደላከውና እስራኤልን ከግብጽ እንዳወጣቸው ሕግንም እንደ ሠራላቸው ናቡከደነጾርም ወደ ባቢሎን ማርኮ እንደወሰዳቸውና ከሰባ ዓመት በኋላ ወደ አገራቸው ኢየሩሳሌም እንደ ተመለሱ ክርስቶስ ሥጋ በመልበስ ወደ ዓለም ስለ መምጣቱ ነቢያት ትንቢት እንደ ተናገሩ ያስተምረው ዘንድ ጀመረ።

ከዚያም በኋላ ወደ ምድር ምራቁን ትፍ ብሎ ጭቃ አድርጎ ጣቱን ቀባው ወዲያው ዳነ በጌታችንም አመነ። ያም ሰፊ ስሙ አንያኖስ ነው። ቅዱስ ማርቆስንም ወደ ቤቱ ወስዶ ልጆቹን ዘመዶቹንም ወደ ርሱ አቀረበ እርሱም አስተምሮ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።

በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑ ሰዎች በበዙ ጊዜ የቅዱስ ማርቆስን ዜና ሰምተው የአገር ሰዎች ሊገድሉት ተሰበሰቡ እርሱም አንያኖስን ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሹሞ ልጆቹን ቄሶችና ዲያቆኖች አድርጎ ከዚያም ወደ በርቃ ወደ አምስቱ አገሮችም ወጥቶ አስተማረ። በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው በእርሳቸውም ዘንድ ሁለት ዓመት ኖረ ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው።

ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ተመለሰ ምእመናንም ተጨምረው በዝተው በታወቁ ቦታዎች ሁሉ በባሕሩም ዳር በላሞች መካበቢያ በሚባለውም አብያተ ክርስቲያን ሠርተው አገኛቸው።

ከሀድያንም የከበረ ሐዋርያን ይገድሉት ዘንድ በብዙ ድካም ፈለጉት እርሱም አምስቱን አገሮች ሲጐበኝ በሥውር ወደ እስክንድርያ ከተማ ይገባ ይወጣ ነበር። በአንዲትም ዓመትም ከአምስቱ አገሮች ተመልሶ ሚያዝያ ዐሥራ ሰባት ቀን በመድኃኒታችን የትንሣኤ በዓል ወደ ቤተክርስቲያን ገባ ሕዝቡም ሁሉ በዙሪያው አሉ። ከሀድያንም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው በአንገቱ ውስጥ ገመዶችን አድርገው በከተማው ሁሉ ጎተቱት። እነርሱም ገና እንደፍየል ሙክት እንጎትተዋለን እያሉ ይጮኹ ነበር ። በላሞች መካበቢያና በሀገሪቱ አደባባይ በከተማውም ዙሪያ በየቀኑ ሲጎትቱት ኖሩ።

ሌሊትም በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት ጋራ በነበረበት አርአያ ሁኖ ተገለጠለት ሰላምታም ሰጥቶ አጽናናው ቃል ኪዳንም ሰጠው። እነሆ አንተ ከወንድሞችህ ሐዋርያት ጋር ተካከልህ አለው። እርሱም በልቡናው ፈጽሞ ደስ አለው። በማግሥቱም ሁለተኛ ገመዶችን በአንገቱ አድርገው በአገሮች ሁሉ ጎተቱት በቀኑም መጨረሻ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።

ከሀዲዎችም ታላቅ እሳትን አንድደው የቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ከውስጡ ጨመሩ ። በክብር ባለቤት ጌታችን ፈቃድም ንውጽውጽታ ጨለማ ቀዝቃዛ ነፋስ መብረቅና ነጐድጓድ ሆነ። ፀሐይም ጨለመ ከሀዲዎችም ሸሹ ምእመናንም መጥተው የሐዋርያ ቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ወሰዱ ምንም ጥፋት ሳይደርስበት ደኀና ሆኖ አገኙት በመልካም ልብስም ገንዘው በጥሩ ቦታ አኖሩት መታሰቢያውንም አደረጉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቀ_መለኮት

ዳግመኛም በዚህች ቀን የመጥምቁ ዮሐንስ ቅድስት ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየበረረች 15 ዓመት ስታስተምር ከኖረች በኋላ በዐረቢያ ምድር በግልጽ ታይታለች፡፡

ይኸውም የሆነው እንዲህ ነው፡- ሄሮድያዳ ልጅ ርጉም የሆነ ንጉሥ ሄሮድስን በዘፈኗ በጣም አድርጋ ስላስደሰተችው እርሱም በተራው ሊያስደስታት ፈለገና እስከ መንግሥቱ እኩሌታ ድረስም ቢሆን የለመነችውን ይሰጣት ዘንድ በሕዝቦቹና በመኳንንቱ ሁሉ ፊት እንዳይከዳት በፅኑ ቃልኪዳን ማለላት፡፡ እርሱም አስቀድሞ "የፈለግሽውን ጠይቂኝ፣ የመንግሥቴንም እኩሌታ ቢሆን እሰጥሻለሁ ምን ላድርግልሽ?" እያለ በመሐላ ባላት ጊዜ በእናቷ ምክር የዮሐንስን አንገት ቆርጦ ይሰጣት ዘንድ ለመነችው፡፡ እርሱም ስለማሐላው የዮሐንስን አንገት እንድትቆረጥ አደረገ፡፡ በመጀመሪያም የሄሮድስ ወታደሮች ሠይፍ ይዘው የዮሐንስን አንገት ይቆርጡ ዘንድ ወደ መኅኒ ቤት ሲሄዱ ቅዱስ ዮሐንስም የሄሮድስ ጭፍሮች ሊገድሉት እንደመጡ በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ስላወቀ ከጨለማው ቤት ውስጥ አንገቱን በመስኮት አውጥቶ እንደሚመቻቸው አድርጎ ጠበቃቸው፡፡ የንጉሡም ጭፍሮች የመጥምቁን ራስ በወጪት አድርገው ለንጉሣቸው ሄሮድስ ሰጡት፡፡ ሄሮድስም ለሄሮድያዳ ልጅ ሰጣት፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ግን በወጪት ላይ ሆና ሕዝቦቹና የመንግሥቱ ታላላቅ ሰዎች እየሰሟት በየመኳንንቱ ፊት ንጉሥ ሄሮድስን "የወንድምህን የፊሊጶስን ሚስት ማግባት አይገባህም" እያለች መጀመሪያ ትዘልፈው እንደነበረው ሁሉ አሁንም ዘለፈችው፡፡ መዓዛዋም እጅግ ደስ የሚያሰኝ ነበር፣ ዐይኖቹም እንደፀሐይ ያበሩ ነበር፡፡
#ኅዳር_7

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ኅዳር ሰባት በዚህችም ቀን #የቅዱስ_ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕት ቅዳሴ ቤቱ፣ ከእስክንድርያ አገር የሆነ #ቅዱስ_ጊዮርጊስ በሰማዕትነት አረፈ፣ #አቡነ_ገብረ_እንድርያስ_ዘወለቃ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው፣ #አባ_ናህርው በሰማዕትነት አረፈ፣ #የአባ_ሚናስ_ዘተመይ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #ቅዱሳን_ዘኖቢስ እና እናቱ #ቅድስት_ዘኖብያ እንዲሁም #ቅዱስ_ሐዲስ_መርቆሬዎስ እና ወንድሙ #ቅዱስ_ዮሐንስ በሰማዕትነት አረፉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ጊዮርጊስ_ሊቀ_ሰማዕት

ኅዳር ሰባት በዚህችም ቀን የልዳ ሀገር የሆነ የሰማዕታት አለቃ የታላቁ መስተጋድል የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት ነው ዳግመኛም ጌታችን በውስጧ ላደረገው ድንቅ ተአምር መታሰቢያ ሆነ።

ይህም እንዲህ ነው በውስጧ ድንቆች ተአምራት እንደሚሠሩ ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስ በሰማ ጊዜ ሊአፈርሳት አሰበ ስሙ አውህዮስ የሚባለውንም መኰንን ከብዙ ሠራዊት ጋር ላከው፤ ያም መኰንን በደረሰ ጊዜ የቅዱስ ጊዮርጊስ ሥዕል ወዳለበት አዳራሽ በትዕቢት ሆኖ ገባ። በሥዕሉም ፊት በብርጭቆ መቅረዝ መብራት ነበረ በቤተ ክርስቲያኒቱና በቅዱስ ጊዮርጊስ ላይ እየዘበተ በእጁ በያዘው በትር የመብራቱን መቅረዝ መትቶ ሰበረው የመቅረዙም ስባሪ ወደ ከሀዱው ራስ ደርሶ መታው ራሱንም ታመመ ፍርሃትና እንቅጥቅጥም መጣበት ወድቆም ተዘረረ ባልንጀሮቹም ወደ አገሩ ሊወስዱት ተሸከሙት በክፉ አሟሟትም ተጐሳቊሎ ሞተ ወስደውም ከባሕር ጣሉት ወገኖቹም ወደ ሀገራቸው አፍረው ተመለሱ።

ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስም ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ በልዳ ሀገር ያለች የቅዱስ ጊዮርጊስን ቤተ ክርስቲያን ያፈርሳት ዘንድ ራሱ ተነሥቶ ሔደ በዚያንም ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መታው ሰባት ዓመት ያህልም ዐይኖቹ ታውረው አእምሮውንም አጥቶ ቁራሽ እንጀራም እየለመነ ኑሮ ሞተ።

ክብር ይግባውና ጌታችንም የቤተ መንግሥቱን ሰዎች አስነሣበት እርሱን አስወግደው ጻድቅ ሰው ቁስጠንጢኖስን በእግዚአብሔር ፈቃድ አነገሡት እርሱም በአዋጅ የጣዖታትን ቤቶች ዘግቶ አብያተ ክርስቲያናትን ከፈተ ለክርስቲያን ወገኖችም በሁሉ ዓለም ተድላ ደስታ ሆነ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ጊዮርጊስ_እስክንድርያ

በዚህች ቀን የእስክንድርያ አገር የሆነ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሰማዕትነት አረፈ።

የዚህም ቅዱስ አባቱ በእስክንድርያ አገር በንግድ ሥራ የሚኖር ነው ልጅም አልነበረውም የልዳዊው ቅዱስ ጊዮርጊስም ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት የበዓልዋ መታሰቢያ ኅዳር ሰባት በደረሰ ጊዜ ልጅን ይሰጠው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲማልድለት ቅዱስ ጊዮርጊስን ለመነው ጌታችንም ልመናውን ተቀብሎ ይህን ልጅ ሰጠው ስሙንም በታላቁ ሰማዕት ስም ጊዮርጊስ ብሎ ስም አወጣለት።

የዚህም ልጅ እናቱ ለእስክንድርያ አስተዳዳሪ ለአርማንዮስ እኅቱ ናት ከዚህም በኋላ እናትና አባቱ አረፉ እርሱም ከእናቱ ወንድም ዘንድ ተቀመጠ ሃያ አምስት ዓመትም በሆነው ጊዜ በጎ ሥራ የሚሠራ ሆነ ድኆችን እጅግ ይረዳቸው ይወዳቸውም ነበረ የሚራራና የሚመጸውት ሆነ ወደ ቤተክርስቲያን መገሥገሥንም ይወዳል። ለመኰንን አርማንዮስም አንዲት ብቻዋን ሴት ልጅ አለችው ቦታዎችንም በመጐብኘት ደስ ይላት ዘንድ ከባልንጀሮቿ ጋር ወጣች ወደ ደብረ ቊስቋምም ስትደርስ ጣዕም ባለው ድምጽ በመዘመር ሲያመሰግኑ የተሰበሰቡ መነኰሳትን አገኘቻቸው ምስጋናቸውና መዝሙራቸውም ወደ ልቡዋ ገብቶ ተቀረጸ።

የአባቷ እኅት ልጅ የሆነ ጊዮርጊስንም መነኰሳቱ ስለሚዘምሩት ያስረዳት ዘንድ ጠየቀችው እርሱም ወደማይጠፋ ዕረፍትና ተድላ እንደሚያደርሳቸው ትርጓሜውንና ጥቅሙን ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀመረ።

ወደ አባቷም አርማንዮስ በተመለሰች ጊዜ በፊቱ ቁማ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነች አባቷም ሊሸነግላት ጀመረ ልጄ ሆይ ይህን አታድርጊ አላት ነገሩን ባልተቀበለች ጊዜ ራሷን በሰይፍ አስቆረጠ በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች።

ከዚህም በኋላ ልጅህን ያሳታት የእኅትህ ልጅ ጊዮርጊስ ነው ብለው ለመኰንኑ ነገሩት እርሱም ሰምቶ ቅዱስ ጊዮርጊስን ይዞ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው ጭካኔውንም አይቶ ወደ ሀገረ እንጽና ሰደደው በዚያም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃይተው ቅድስት ራሱን በሰይፍ ቆረጡ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ።

በዚያም ሳሙኤል የሚባል ዲያቆን ነበር የቅዱስ ጊዮርጊስንም ሥጋ አንሥቶ ወደ ሀገረ መኑፍ ወሰደው። የአርማንዮስም ሚስት በአወቀች ጊዜ መልእክተኞችን ልካ አስመጣችው ከልጅዋም ሥጋ ጋር በአንድነት በእስክንድርያ አገር አደረገችው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ገብረ_እንድርያስ_ዘወለቃ

ዳግመኛም በዚህች ቀን አቡነ ገብረ እንድርያስ ዘወለቃ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው። የትውልድ ሀገራቸው ወሎ ቦረና ጋስጫ ነው፡፡ አባታቸው ተንሥአ ክርስቶስ እናታቸው አርሴማ ይባላሉ፡፡ ሁለቱም ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ ለመምህር ሰጧቸው፡፡ መምህሩም ጸጋ እግዚአብሔር እንዳደረባቸው ዐውቀው ‹‹ብዙዎችን የምታድን ጻድቅ ትሆናለህ›› ብለው ትንቢት ነግረዋቸዋል፡፡ የመጻሕፍትንም ትርጓሜ በሚገባ ካስተማሯቸው በኋላ ንፍታሌም ይባል የነበረውን ስማቸውን ለውጠው ገብረ እንድርያስ አሏቸው፡፡

ጻድቁ በአቡነ ዮሐንስ ከማ ገዳም ለረጅም ጊዜ በታላቅ ተጋድሎ አገልግለዋል፡፡ አባታችን ሙታንን በማስነሣትና ድውያንን በመፈወስ ብዙ ተአምራትን ሲያደርጉ ኖረዋል፡፡ ብዙ አባቶች ሱባኤ ይይዙበት በነበረው በሰኮሩ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ጸሎት ሲያደርጉ ቅዱስ ዑራኤል በወርቅ ጽዋ ሰማያዊ ወይንና ኅብስት መግቧቸዋል፡፡ እመቤታችንም ሦስት ጽዋ ማየ ሕይወት ሰጥታቸው በእርሱ ብዙ ሕሙማንን ፈውሰውበታል፡፡

ጻድቁ በስማቸው የፈለቀው ጸበል እጅግ አስገራሚ ነው፡፡ ጸበሉ ውስጥ እንጨት ሲነከርበት እንጨቱ በተአምራት ነጭ መቁጠሪያ
ሆኖ ይወጣል፡፡ ይህም እስከዛሬ ድረስ በግልጽ ይታያል፡፡ ጸበሉ ውስጥ ማታ የነከሩትን እንጨት ጠዋት ላይ መቁጠሪያ ሆኖ ያገኙታል፡፡ እጅግ አስገራሚ ነው በእውነት! መቁጠሪያውም ለእንቅርትና ለልዩ ልዩ ሕመሞች መድኃኒት ነው፡፡ ነገር ግን ጸበሉ ያለበት አካባቢው በመርዛማና አደገኛ እባቦች የተሞላ ነው፡፡ ሆኖም ግን እባቦቹ የጻድቁ ግዝት ስላለባቸው በገዳሙ ውስጥ ብቻ ማንንም አይነኩም፡፡ ጸበሉ ደግሞ የሚገኘው ከገዳሙ የአንድ ሰዓት ተኩል መንገድ ርቀት ላይ ነው፡፡

አባታችን እግዚአብሔር ኃጥአንን እንድምርላቸው ጣቀት ወንዝ ከተባለው ቦታ በአንገታቸው ላይ በጣም ትልቅ ድንጋይ እየተሸከሙ ይጸልዩ ነበር፡፡ በዚህ ይጸልዩበት ከነበረው ወንዝ ውስጥ ነው በተዓምራት መቁጠሪያ የሚሠራው ጸበል የፈለቀላቸው፡፡ ደቡብ ወሎ ወግዲ ወረዳ የሚገኘው አቡነ ገብረ እንድርያስ ገዳም ከአባ ጽጌ ድንግል ገዳም በእግር የ3 ሰዓት መንገድ ያስኬዳል፡፡

ጻድቁ አቡነ ገብረ እንድርያስ ዓርብ ዓርብ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ወደ ኢየሩሳሌም ይመላለሱ የነበረው በትልቅ ድንጋይ ላይ እንደ ደመና ተጭነው ነበር፡፡

ጻድቁ በአየር ላይ ሲጓዙ ድንጋዩን እንደ ሠረገላ ዋርካውን እንደ ጥላ ይጠቀሙበት ነበረ፡፡ ያ እንደ ሠረገላ ሆኖ ያገለግላቸው የነበረው ትልቅ ድንጋይ ዛሬም ድረስ በገዳማቸው ውስጥ ይገኛል፡፡ ታሪኩም በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፎ ይገኛል፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ናህርው
#ኅዳር_16

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ኅዳር ዐሥራ ስድስት በዚህች ቀን #የቅዱስ_አቡናፍር ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ነው፣ የእስክንድርያ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ዮሐንስ ያረፈበት ነው፣ #ቅዱስ_ኪስጦስ በሰማዕትነት ያረፈበት ነው፣ #ቅድስት_ጣጡስ በሰማዕትነት ያረፈችበት ነው፣ የመነኰስ #አባ_ዳንኤልና_የንጉሥ_አኖሬዎስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቡናፍር

ይኸውም ቅዱስ አቡናፍር ጥቂት የሰሌን ፍሬዎችን ብቻ እየተመገበ በበረሃ ውስጥ 60 ዓመት የኖረ ታላቅ ጻድቅ ነው፡፡ በእነዚህ ድፍን 60 ዓመታት ውስጥ ከቶ የሰውን ፊት አላየም፡፡ ዛሬ ከምስር ከተማ ውጪ የተሠራች ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ዕለት ነው፡፡

አቡነ አቡናፍር መልካም ሽምግልና ያለው ስም አጠራሩ የከበረ በገዳም የሚኖርና በገድል የተጠመደ አባት ነው፡፡ ከላይኛው ግብፅ የተገኘ ሲሆን ታሪኩን የተናገረለት ጻዲቁ አባ በፍኑትዮስ ነው፡፡ ይኸውም አባ በፍኑትዮስ ወደ በረሃ ውስጥ በገባ ጊዜ አንዲት የውኃ ምንጭና አንዲት የሰሌን ምንጣፍ አግኝቶ በዚያ እየተጋደለ ብዙ ዘመን የኖረ ነው፡፡

በአንዲት ዕለት አባ በፍኑትዮስ ወደ እርሱ ሲመጣ አባ አቡናፍር አየው፡፡ አባ በፍኑትዮስም የሰይጣንን ምትሐት የሚያይ መስሎት ደነገጠ፡፡ አባ አቡናፍር ፀጉሩና ጽሕሙ ሰውነቱን ሁሉ ሸፍኖታል እንጂ በላዩ ላይ ልብስ አልነበረውም፡፡ አባ በፍኑትዮስንም በመስቀል ምልክት ባርኮ አጽናናው፡፡ አቡነ ዘበሰማያትንም ከጸለየ በኋላ ‹‹አባ በፍኑትዮስ ሆይ ወደዚህ መምጣትህ መልካም ነው›› ብሎ በስሙ ከጠራው በኋላ ፍርሃቱን አራቀለት፡፡

ከዚህም በኋላ ሁለቱም በጋራ ጸልየው የእግዚአብሔርን ገናናነት እየተነጋገሩ ተቀመጡ፡፡ አባ በፍኑትዮስም አኗኗሩንና እንዴት ወደዚህ በረሃ እንደመጣ ታሪኩን ይነግረው ዘንድ አባ አቡናፍርን ለመነው፡፡ አባ አቡናፍርም ታሪኩን እንዲህ ብሎ ነገረው፡- "እኔ ደጋጎች እውነተኞች መነኮሳት በሚኖሩበት ገዳም ውስጥ እኖር ነበር፡፡ የገዳማውያንን ልዕልናቸውን ሲናገሩ ሲያመሰግኗቸውም ሰማሁ፡፡ እኔም ‹ከእናንተ የሚሻሉ አሉን?› ብዬ ጠየኳቸው፡፡ እነርሱም ‹አዎን እነርሱ በበረሃ የሚኖሩ በእግዚአብሔር ዘንድ የከበሩ ናቸው፤ እኛ ለዓለም የቀረብን ስለሆንን ብንተክዝና ብናዝን የሚያረጋጋን እናገኛለን ብንታመም የሚጠይቀንና የፈለግነውን ሁሉ እናገኛለን፣ በበረሃ የሚኖሩ ግን ከዚህ ሁሉ የራቁ ናቸው› አሉኝ፡፡ ይህንንም ስሰማ ልቤ እንደ እሳት ነደደና ወደ ፈቀደው መንገድ ይመራኝ ዘንድ በእኩለ ሌሊት ተነሥቼ ጸለይኩ፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥቼ ወጥቼ ስጓዝ አንድ አባት አገኘሁና የገዳማውያንን ገድላቸውን እያስተማረኝ ከእርሱ
ጋር ተቀመጥኩኝ፡፡ ከዚያም ወደዚህ ቦታ ደረስኩ፡፡ እግዚአብሔር ያዘጋጀልኝን ይህችን ሰሌን አገኘኋት፡፡ በየዓመቱ 12 ዘለላ ታፈራለች፤ ለየወሩም የምመገበው አንዱ ዘለላ ይበቃኛል ውኃም ከዚህች ምንጭ እጠጣለሁ፡፡ በዚህችም በረሃ እስከዛሬ 60 ዓመት ኖርኩ፡፡ ከአንተም በቀር የሰው ፊት ከቶ አይቼ አላውቅም" ብሎ አቡነ አቡናፍር ጣፋጭ ታሪኩን በዝርዝር ነገረው፡፡ ይህንንም ሲነጋገሩ የታዘዘ መልአክ መጥቶ የጌታችንን ሥጋና ደም አምጥቶ አቆረባቸው፡፡ ቀጥለውም ጥቂት የሰሌን ፍሬ ተመገቡ፡፡ ወዲያውም የአቡነ አቡናፍር መልኩ ተለወጠ፤ እንደ እሳትም ሆነ፡፡ ወደ እግዚአብሔርም በተመስጦ እየጸለየ ሳለ ቅድስት ነፍሱ ከሥጋው ተለየች፡፡

አቡነ በፍኑትዮስም በፀጉር ልብሱ በክብር ገንዞ ቀበረው፡፡ ከዚህም በኋላ አባ በፍኑትዮስ በዚያች ቦታ ይኖር ዘንድ ወደደ ነገር ግን ያቺ የሰሌን ዛፍ ወደቀች፤ የውኃዋም ምንጭ ደረቀች፡፡ አባ በፍኑትዮስም ወደ ዓለም ተመልሶ የገዳማውያንን ዜና ይልቁንም የአባ አቡናፍርን ዜና ይሰብክ ዘንድ የእግዚአብሔር ፍቃድ ሆነ፡፡

የአቡነ አቡናፍር ዕረፍታቸው ሰኔ 16 ቀን ነው፡፡ ኅዳር 16 ደግሞ ከምስር ከተማ ውጪ የተሠራች ቤተ ክርስቲያናቸው የከበረችበት ዕለት ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባት_አባ_ዮሐንስ

በዚህችም ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ስምንተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ አረፈ። ይህም ቅዱስ አባት የቆጵሮስ ሀገር ሰው ነው እጅግም ባለጸጋ ነው በእስክንድርያ አገርም የሚኖር ሆነ አባቱ አገረ ገዥ ነበርና ሚስትም አግብቶ ልጆችን ወለደ ከዚህም በኋላ ሚስቱም ልጆቹም ሞቱ።

በዚያንም ጊዜ ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጠ መጸወተ እርሱም መንኵሶ በታላቅ ገድል የተጠመደ ሁኖ በጎ ሥራዎችን ትሩፋትን ጨምሮ በመሥራት እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው።

ከበጎ ሥራዎቹና ከትሩፋቱም ከቀናች ሃይማኖቱ ከአገልግሎቱና ከደግነቱ ከጽድቁ ማማር የተነሣ በግብጽ አገር የሚኖሩ ኤጲስቆጶሳት ሁሉም ተሰማምተው ይዘው ወሰዱት ያለ ፈቃዱም በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙትና በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ላይ አስቀመጡት ። ያን ጊዜ የከበረ ወንጌልን አነበበ በሹመቱና በክህነቱም ብርሃን ተገለጸ ብዙዎች ድንቆች የሆኑ ተአምራትንም አደረገ።

ለድኆችና ለችግረኞች ሁልጊዜ ያለማቋረጥ የሚሹትን የሚሰጣቸው ሆነ ስለዚህም የሚራራ ዮሐንስ ተብሎ ተጠራ ። በአይሁድና በአረማውያን ዘንድ የሚአስፈራ ሆነ በመጸሐፈ ገድሉ እንደተጻፈ እጅግ ይፈሩትና ያከብሩት ነበርና መንጋዎቹንም በበጎ አጠባበቅ ጠበቃቸው እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኪስጦስ

በዚችም ቀን ቅዱስ ኪስጦስ በመኰንኑ በመክሲሞስ እጅ በሰማዕትነት አረፈ ። ይህንንም ቅዱስ ኪስጦስን መኰንኑ በያዘው ጊዜ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ ቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ጣጡስ

በዚችም ዕለት በሮሜ አገር በከሀዲ መኰንን በእስክንድሮስ እጅ ቅድስት ጣጡስ በሰማዕትነት አረፈች። ወደርሱም በአቀረቧት ጊዜ እስክንድሮስ ለአማልክት ሠዊ አላት እርሷም ከፈጠረኝ ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር አልሠዋም ብላ መለሰች።

መኰንኑም የፊቷን መሸፈኛ እንዲገልጡ አዘዘ ውበቷንም አይቶ አደነቀ ዐይኖቿ እንደ አጥቢያ ኮከብ ናቸውና ቁመቷም እንደ ዘንባባ ደም ግባቷም እንደ ጽጌረዳ ነው በዚያንም ወራት የሚመሳሰላት የለም ነበር።

ንጉሡም በአያት ጊዜ እርሷን በመውደዱ ልቡ ተነጠቀ እንዲህም አላት እሺ በይኝና ለታላቅ አምላክ ለአጵሎን ሠዊ እኔም ለቤተ መንግሥቴ እመቤት አደርግሻለሁ አላት። ቅድስት ጣጡስም እኔ ክብር ይግባውና ከክርስቶስ ከመንጋዎቹ ውስጥ ነኝ ከእርሱ በቀር ለሌላ አልሠዋም ነገር ግን ወደ አማልክቶችህ መሠዊያ ቤት ገብቼ ኃይላቸውን እንዳይ ፍቀድልኝ አለችው።

በዚያንም ጊዜ ወሰዷት በገባችም ጊዜ ጣዖታቱ ይጠፉ ዘንድ ክብር ይግባውና የኃይል ባለቤት ወደ ሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየች ወዲያውኑ ንውጽውጽታ ሁኖ ጣዖታቱ ከመቀመጫቸው ወድቀው ተሰባበሩ ታላቁ አምላካቸው አጵሎንም ቊልቊል ወድቆ ተቀጠቀጠ ከጣዖቱ አገልጋዮችም ብዙዎች ሞቱ በአጵሎን ላይ አድሮ የሚኖር ርኩስ መንፈስ እንዲህ ብሎ ጮኸ።
#ኅዳር_17

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ኅዳር ዐሥራ ሰባት በዚህችም ዕለት የከበረ አባት #ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ #የቅድስት_ወለተ_ጴጥሮስ እረፍቷ ነው፣ #የአቡነ_ሲኖዳ_ዘደብረ_ጽሙና የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

ኅዳር ዐሥራ ሰባት በዚህችም ዕለት የዓለሙ ሁሉ መምህር የሆነ የከበረ አባት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የሥጋው ፍልሰት ሆነ።

ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ሰዎች ወገን ነው የአባቱም ስም አስፋኒዶስ የእናቱም ስም አትናሲያ ነው እሊህም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህንንም ልጃቸውን በመልካም አስተዳደግ አሳደጉት ትምህርትንና ጥበብንም ሁሉ አስተማሩት እርሱ ወደ አቴና ሒዶ በመምህራን ቤት ተቀምጦ ትምህርትን ሁሉ ተምሮ በዕውቀቱ ከብዙዎች በላይ ከፍ ከፍ ብሏልና። ከዚህም በኋላ ገና በታናሽነቱ መነኰሰ የዚህንም የኃላፊውን ዓለም ጣዕም ንቆ ተወ ከእርሱም ቀድሞ በዚሁ ገዳም ቅዱስ ባስልዮስ መንኵሶ ነበር በአንድነትም ተስማምተው ብዙ ትሩፋትን ሠሩ ወላጆቹም በሞቱ ጊዜ ከተውለት ገንዘብ ምንም ምን አልወሰደም ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ እንጂ ከዚያም በምንኵስና ሥራ በመጠመድ ፍጹም ገድልን እየተጋደለ ኖረ።

በዚያም ገዳም ሶርያዊ ጻድቅ ሰው ስሙ ሲሲኮስ የሚባል መነኰስ ነበረ እርሱም ወደፊት የሚሆነውን በመንፈስ ቅዱስ ያይ ነበር በአንዲት ሌሊትም ለጸሎት እየተጋ ሳለ ሐዋርያትን ጴጥሮስንና ዮሐንስን አያቸው ወደ ዮሐንስ አፈወርቅ ገብተው ጴጥሮስ መክፈቻ ሰጠው ወንጌላዊ ዮሐንስም ወንጌልን ሰጠው እንዲህም አሉት በምድር ያሠርከው በሰማይ የታሠረ ይሆናል በምድርም የፈታኸው ደግሞ በሰማያት የተፈታ ይሆናልና በውስጥህ መንፈስ ቅዱስ ያደረብህ አዲስ ዳንኤል ሆይ የክብር ባለቤት ከሆነ ከታለቅ መምህር ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ወደ አንተ ተልከናልና ዕወቅ እኔም የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻ የተሰጠኝ ጴጥሮስ ነኝ ።

ሁለተኛውም እኔም በመጀመሪያው ስብከቴ በከበረ ወንጌል ቃል አስቀድሞ ነበረ ያልኩ ይህም ቃል በጠላት ላይ የእሳት ሰይፍ የሆነ ዮሐንስ ነኝ ። ለአንተም ከክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ወገኖችህ ምእመናንን በቀናች ሃይማኖት ታሳድጋቸው ዘንድ ዕውነተኛ አእምሮ ደግሞ ተሰጥቶሃል ።

ጻድቅ ሲሲኮስም ይህን ራእይ በአየ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ቸር ታማኝ እረኛ ሁኖ እንደሚሾም ዐወቀ። ከዚህም በኋላ በቅዱስ ዮሐንስ ላይ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በላዩ ወርዶ አደረበትና ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ ዲያቆን ሁኖ ሳለም የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ብሉያትንና ሐዲሳትን ተረጐመ ። በአንዲት ሌሊትም ቅዱስ ዮሐንስ ሲጸልይ የእግዚአብሔር መልአክ በድንገት እንደ በረድ ነጭ በሆነ ልብስ ተገለጠለት ቅዱስ ዮሐንስም ሲያየው ደንግጦ በምድር ላይ ወደቀ መልአኩም አርአያውን ለውጦ እንደ ሰው ሁኖ ታየው ወዳጄ አዲስ ዳንኤል ሆይ አትፍራ ተነሣ አለው የቅዱስ ዮሐንስም ልቡ ተጽናንቶ ጌታዬ አንተ ማነህ ግርማህ አስፈርቶኛልና አለው የእግዚአብሔር መልአክም ትሠራው ዘንድ የሚገባህን ልነግርህ ወዳንተ የተላክሁ ነኝ።

አሁንም እግዚአብሔር አምላክ ያዘዘህን ለመሥራት ልብህን አበርታ ቃልህ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ በአራቱ ማእዘን ይደርሳልና እልፍ አእላፋትም ትምህርትህን ተቀብለው ትእዛዝህን ሰምተው ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር ተመልሰው ይድናሉና በእግዚአብሔር መንግሥትም ውስጥ የጸና የብርሃን ዐምድ ትሆናለህና። እነሆ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አንተ ይመጣል ከእርሱም ጋራ ሁሉም ካህናትና ዲያቆናት በየማዕረጋቸው የሚያዝህንም አድርግ የእግዚአብሐር ትእዛዝ ነውና ልትተላለፍ አይገባህም አለው። ከዚህም በኋላ ያ መልአክ ለአባ ፊላትያኖስ ተገልጦ ቅዱስ ዮሐንስን ቅስና እንዲሾመው አዘዘው በማግሥቱም ሊቀ ጳጳሳቱ መጣ ከርሱ ጋራም ካህናት አሉ ይህን ቅዱስ ዮሐንስንም ይዞ ቅስና ሾመው።

የቍስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳትም በአረፈ ጊዜ ንጉሥ አርቃድዮስ ልኮ አስመጥቶ ቅዱስ ዮሐንስን በቍስጥንጥንያ ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾመው አባቶቻችን ሐዋርያት እንደሚአደርጉት በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ላይ ጸና ሕይወትነት በአላቸው ትምህርቶችና ተግሣጾች ሕዝቡን ሁልጊዜ የሚአስተምር ሆነ።

ከኤጲስቆጶሳትም ሆነ ከመንግሥት ወገን ሕግን የሚተላለፉትን ሁሉ ይገሥጻቸዋል ማንንም አይፈራም ፊት አይቶም አያደላም። የንጉሥ አርቃድዮስ ሚስት አውዶክስያም ገንዘብ ወዳጅ ስለሆነች የአንዲት ድኃ መበለት ቦታዋን በግፍ ወሰደች ያቺ መበለትም ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥታ ንግሥት አውዶክስያ ቦታዋን እንደነጠቀቻት ነገረችው እርሱም የደኃዋን ቦታዋን መልሺላት ብሎ ከብዙ ምክር ጋር እንድትመልስላት ንግሥት አውዶክስያን ለመናት እርሷ ግን እምቢ በማለት አልታዘዘችለትም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብታ ሥጋውን ደሙን እንዳትቀበል አውግዞ ለያት።

ቍጣንና ብስጭትንም ተመልታ ስለ ክፉ ሥራቸው ከሹመታቸው እርሱ የሻራቸውን ኤጲስቆጶሳት ሰበሰበች እነርሱም ንግሥቲቱን ስለ ተቃወመ ስደት እንደሚገባው በእርሱ ላይ ተስማምተው ጻፉ እርሷም አጥራክያ ወደ ሚባል ደሴት ሰደደችው ። ከዚያም በደረሰ ጊዜ የዚያች ደሴት ሰዎች በክፉ ሥራ ጸንተው የሚኖሩ ከሀድያን ሁነው አገኛቸው ቅዱስ ዮሐንስም አስተማራቸው ገሠጻቸውም በፊታቸው ስለ አደረጋቸው ድንቆች ተአምራት ወደ ቀናች ሃይማኖት አስገባቸው።

የሮሜ ንጉሥ አኖሬዎስና ሊቀ ጳጳሳቱ ዮናክኒዶስ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ስደት በሰሙ ጊዜ እጅግ አዘኑ በንጉሥ አርቃድዮስ ላይም በመቆጣት እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጽፈው ላኩ ከዚህ ከክፉ ሥራ ተጠበቅ ትእዛዛችንንም ተቀብለህ የከበረ
ዮሐንስን ከስደቱ ከአልመለስከው በአንተና በእኛ መካከል ሰላም አይኖርም። መልእክታቸውንም በአነበበ ጊዜ እጅግ አዘነ ሚስቱንም አግዶ ልኮ ቅዱስ ዮሐንስን ከስደቱ መለሰው በተመለሰ ጊዜም የቍስጥንጥንያ ሰዎች በመመለሱ ታላቅ ደስታ አደረጉ። ከጥቂት ቀኖች በኋላም ንግሥቲቱ ወደ ክፋቷ ተመልሳ ሁለተኛ ወደ አጥራክያ ደሴት ሰደደችውና በዚያው አረፈ።

ንጉሥ አኖሬዎስና ሊቀ ጳጳሳት ዮናክኒዶስም በሰሙ ጊዜ መልእክትን ላኩ ሊቀ ጳጳሳቱም የከበረ ዮሐንስን ከስደቱ እስከምትመልሰው ድረስ ሥጋውንና ደሙን እንዳትቀበል አውዶክስያን አወገዛት። ከዚህም በኋላ የከበረ ዮሐንስን ይመልሱት ዘንድ ንጉሥ ላከ ግን ሙቶ አገኙት ሥጋውንም ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ አደረሱት። የከበረ ዮሐንስም በተሰደደበት አገር እንደአረፈና ሥጋውንም ወደ ቍስጥንጥንያ ከተማ እንደአመጡ ወደ አባ ዮናክኒዶስ መልእክት ጽፈው አስረዱት። ሁለተኛም የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብታ ሥጋውንና ደሙን እንዳትቀበል ልኮ አውድክስያን አወገዛት እየለመነችውም ስምንት ወር ያህል ኖረች በብዙ ልመናም ፈታት።

ነገር ግን ጭንቅ በሆነ ደዌ እግዚአብሔር አሠቃያት ያድኗት ዘንድ ገንዘቧን ለባለ መድኃኒቶች ጥበበኞች እስከ ሰጠች ድረስ ግን አልዳነችም ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መቃብርም ሔዳ በእርሱ ላይ ያደረገችውን በደል ይቅር ይላት ዘንድ እየሰገደችና እያለቀሰች ለመነችው እርሱም ይቅር አላት ከደዌዋም ፈወሳት። ጌታችንም ከሥጋው ታላላቅ ድንቆች ታአምራትን ገለጠ።
በዚህችም ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት ቆዝሞስ አረፈ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ አራተኛ ነው። ይህም አባት ብዙ መከራና ኀዘን ደረሰበት በዘመኑም በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ላይ መከራና ችግር ደረሰባቸው በእነዚያም ወራት የክርስቲያን ወገኖችና አይሁዳውያን ልብሳቸውን በሰማያዊ ቀለም እንዲያቀልሙት እንጂ ነጭ ልብስ እንዳይለብሱ የእስላሞች ንጉሥ ጋዕፊር አዝዞ ነበርና።

በዚህም አባት ዘመን ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ በአስቄጥስ ገዳም በቅዱስ ሳዊሮስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ነበረች ጐኗም ተገልጦ ከእርሷ ብዙ ደም ፈሰሰ በግብጽ አገር ከአሉ ከሌሎች ሥዕሎችም ከዐይኖቻቸው ብዙ ዕንባ ፈሰሰ ይህም የሆነው በሊቀ ጳጳሳቱና በክርስቲያን ወገኖች ላይ ስለ ደረሰው መከራ እንደ ሆነ በመራቀቅ የሚያስተውሉ አወቁ።

ከዚህም በኋላ ስለእነዚያ የከፉ ወራቶች ፈንታ በጎ የሆኑ ወራቶችን እግዚአብሔር ሰጠው ሁል ጊዜም ምእመናንን የሚያስተምራቸውና የሚያጽናናቸው በቀናች ሃይማኖትም የሚያበረታታቸው ሆነ ። በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም ላይ ሰባት ዓመት ከአምስት ወር ከኖረ በኋላ በአምስት መቶ ሰባ አምስት ዓመተ ሰማዕታት ኅዳር ሃያ አንድ ቀን አረፈ ይንሶር በሚባል ዋሻውም ተቀበረ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘአስዩጥ

በዚችም ቀን ደግሞ የብርሌ የብርጭቆ ሠሪዎች ልጅ የሆነ ከአስዮጥ አገር ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ አረፈ ። ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ በበጎ ተግሣጽ አሳድገውታል የጥርብ ሥራንም አስተማሩት ከጥቂት ዘመናትም በኋላ አባቱና እናቱ አረፉ። ያን ጊዜ ወደ ቅዱስ አባ ኢስድሮስና ወደ አባ ባይሞን ዘንድ ሒዶ መነኰሰ በጾምና በጸሎት በገድል ሁሉ ተጠምዶ ተጋደለ ዜናውም በራቁ ገዳማት ሁሉ ተሰማ ።

ከዚህም በኋላ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጠለት ወደ ሀገሩ ሒዶ ወገኖቹን የጽድቅን ጎዳና ይመራቸው ዘንድ አዘዘው። ቅዱስ ቊርባንንም ሳይቀበል ከበዓቱ የማይወጣ ሆነ። በአንዲት ዕለትም ሁለት ቅዱሳን አረጋውያን አባ አብዢልና አባ ብሶይ ወደርሱ መጡ ገና ወደርሱ ሳይቀርቡ ከሩቅ ሳሉ ስማቸውን በመጥራት ሳያውቃቸው አባቶቼ ለመምጣታችሁ ሰላምታ ይገባል ብሎ ተናገረ እጅግም አደነቁት አባ ሲኖዳም ከግብጽ አገር እየመጣ ብዙ ጊዜ ይጎበኘው ነበር።

የከዳተኞችም ጠብ በግብጽ አገር ላይ በተነሣ ጊዜ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ የላከው የጦር መኰንን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጣ። በጸሎቱም ይራዳው ዘንድ ለመነው ቅዱስ ዮሐንስም መስቀሉን አንሥቶ መኰንኑን አይዞህ አትዘን አንተ ጠላቶችህን ድል ታደርጋለህና አለው እንደ ቃሉም ሆነ።

ዳግመኛም በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ላይ ጠላት በተነሣበት ጊዜ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ላከ እርሱም አትዘን አንተ ጠላትህን ታሸንፋለህ አለው ያን ጊዜም ጠላቶቹን አሸነፈ ።

ከዚህም በኋላ በእነዚያ ወራት ንጉሥ ቴዊዶስዮስ የርኲሰትን ሥራ ስለ ሠሩ የአስዮጥን ሰዎች እንዲገድሏቸው ሀገራቸውንም እንዲአጠፉ አዘዘ። ንጉሡም የላከው መኰንን ሳይደርስ የእግዚአብሔር መልአክ ይህን ነገር ለአባ ዮሐንስ አሳወቀው የሀገርም ሰዎች የንጉሡን ትእዛዝ በሰሙ ጊዜ ወደ አባ ዮሐንስ ገዳም ወጥተው ስለ መጥፋታቸው በፊቱ አለቀሱ አባ ዮሐንስም አትጨነቁ አይዟችሁ እግዚአብሔር ያድናችኋልና አላቸው።

መኰንኑም በመጣ ጊዜ ከእርሱ በረከትን ይቀበል ዘንድ ወደ አባ ዮሐንስ ደረሰ አባ ዮሐንስም ንጉሡ ያዘዘውን ሁሉ ነገረው መኰንኑም ሰምቶ ደነገጠ ለቅድስናውም ተገዢ ሆነ ለመኰንኑም ርኩስ መንፈስ ያደረበት የዐሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ነበረው ያድንለት ዘንድ ቅዱስ ዮሐንስን ለመነው በዚያንም ጊዜ ዘይትን ቀብቶ አዳነው።

ከዚህም በኋላ የአስዩጥ ሰዎችን መገደላቸውን እንዲተው ወደ ንጉሥ ይጽፍለት ዘንድ መኰንኑን አባ ዮሐንስ ለመነው መኰንኑም ጽፎ ለአባ ዮሐንስ ሰጠው አባ ዮሐንስም ተቀብሎ ወደ ዋሻው ገባ ወደ ጌታችንም ጸለየ ብርህት ደመናም መጣች ተሸክማም ወደ ንጉሡ አደረሰችው ያን ጊዜም ንጉሥ ከማዕድ ላይ ነበረ ያንንም ደብዳቤ ከወደላይ ጣለለት ንጉሡም አንሥቶ በአነበበው ጊዜ ከመኰንኑ የተጻፈ እንደሆነ በመካከላቸው በአለ ምልክት ተጽፎ አገኘው የተጻፈውም ቃል ስለ አባ ዮሐንስ ልመና ሀገሪቱን ማጥፋትን እንዲተው የሚል ነበር ቀና ባለ ጊዜም ደመና አየ ንጉሡም አደነቀ።

ከዚህም በኋላ ሀገሪቱን ማጥፋትን ስለ አባ ዮሐንስ ይተው ዘንድ መልሱን ለመኰንኑ ንጉሡ ጽፎ ደብዳቤዋን ወደ ደመናው ወረወራት የተሰበሰቡትም እያዩ እጅ ተቀበለችውና ወደ ደመናው ገባች ወዲያውኑ አባ ዮሐንስ በዚያች ደመና ወደበዓቱ ተመለሰና በማግሥቱ ያቺን ደብዳቤ ለመኰንኑ ሰጠው በላይዋም የንጉሡ ፊርማውና ማኅተሙ አለ በአያትና በአነበባት ጊዜ ደነገጠ አደነቀም ስለ ሀገሪቱ ድኅነትም እግዚአብሔርን እያመሰገነ ወደአገሩ ተመለሰ።

የንጉሥ ዘመድ የሆነች የከበረች ሴት ዜናውን በሰማች ጊዜ ከደዌዋ ይፈውሳት ዘንድ ወደርሱ መጣች በጸሎቱም ተፈወሰች። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ በሞተ ጊዜ መናፍቁ መርቅያን ነገሠ ። ቅዱስ አባ ዲዮስቆሮስንም አሠቃየው ። የቀናች ሃይማኖትን ስለመለወጡ አባ ዮሐንስ እየዘለፈና እየረገመው ወደ ርሱ ደብዳቤ ላከ ከጥቂት ወራትም በኋላ እግዚአብሔር ቀሠፈው።

ለእርሱም ዕድሜው መቶ ሃያ አምስት ዓመት ሲሆነው ዕረፍቱ እንደ ደረሰ አወቀ እየጸለየም ግምባሩን ምድር አስነክቶ ሰገደ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን በጸሎቷ የሚገኝ በረከቷም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ይኑር። በቅዱሳኑም ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ጥር_4

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር አራት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚወደው የሐዋርያው #ቅዱስ_ዮሐንስ የፍልሰቱ መታሰቢያ ነው፣ #አባ_ናርዶስ_ዘደብረ_ቢዘን እና #የአቡነ_መልከጼዴቅ_ዘዋሸራ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሐዋርያው_ቅዱስ_ዮሐንስ_ወልደ_ነጎድጓድ

ጥር አራት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚወደው የከበረና የተመሰገነ ወንጌልን የጻፈ የሐዋርያው ዮሐንስ የፍልሰቱ መታሰቢያ ሆነ።

ለዚህም ቅዱስ ወደ እስያ ሀገር ይሔድ ዘንድ ዕጣው በወጣ ጊዜ እጅግ አዝኖ አለቀሰ እነርሱ ክፉዎች ከሀዲዎች ልባቸው የደነደነ መሆናቸውን አውቋልና ግን ከጌታችን ኃይልን መጽናናትን አግኝቶ ከደቀ መዝሙሩ ከአብሮኮሮስ ጋር ወጥቶ ወደ ክፍሉ ሔደ።

ወደ ኤፌሶንም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ላይ ተሳፈረ መርከቡም ተሰበረ እየአንዳንዱ በመርከብ ስባሪ ሠሌዳ ላይ ተንጠለጠለ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስንም የባሕሩ ማዕበል ወደአንዲት ደሴት አደረሰው ቅዱስ ዮሐንስ ግን በባሕሩ ማዕበል መካከል አርባ መዓልት አርባ ሌሊት ኖረ።

ከዚህም በኃላ ደቀ መዝሙሩ አብሮኮሮስ ወዳለበት ወደ የብስ ባሕሩ ተፋው ስለ መገናኘታቸውም እግዚአብሔርን አመሰገኑት በዚያን ጊዜም ተነሥተው ወደ ኤፌሶን ከተማ ገቡ ግን በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይሰብኩ ዘንድ አልተቻላቸውም እነዚያ ያገር ሰዎች እጅግ የከፉ ናቸውና።

ስለዚህም ምክንያት ፈጥረው ዮሐንስ ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤት እሳትን የሚያነድ ሆነ ረድኡ አብሮኮ ሮስም አጣቢ ሆነ ያቺ ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ነበር መጻተኞችም ስለሆኑ ታጉሳቁላቸዋለች ትደበድባቸዋለች ትረግማቸዋለች ባሮቿም እንደሆኑ ጽፈውላታልና ለእርሷ ባሮች አደረገቻቸው በዚህ በታላቅ ጒስቊልና ውስጥ ኖሩ።

ከዚህም በኃላ በአንዲት ዕለት ይታጠብ ዘንድ የአገረ ገዥው ልጅ ገባ በዚያም የውሽባ ቤት ከተሠራ ጀምሮ የሰይጣን ኃይል አለ የመኰንኑንም ልጅ አንቆ ገደለው በዚያንም ጊዜ የአገር ሰዎች ለዚያ ለሞተው ሊያለቅሱለት ተሰበሰቡ የከበረ ዮሐንስም ከእርሳቸው ጋር መጥቶ እንደ ሰው ሁሉ ሊያይ በዚያ ቆመ።

ሮምናም በአየችው ጊዜ ረገመችው አንተስ በጌታዬ ልጅ ሞት ደስ ብሎህ ልትዝትብኝ መጣህ አለችው ቅዱሱ ግን በቅንነት አይዞሽ አትዘኝ አላት ይህንንም ብሎ ወደ ሞተው ቀረብ ብሎ በመስቀል ምልክት አማተበበት በፊቱም ላይ እፍ አለበት። በዚያንም ጊዜ ያ ሞተው ድኖ ተነሣ የአገር ሰዎችም ደነገጡ ሮምናም ወዮልኝ እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን አለች። እርሱም አይደለሁም እኔ አገልጋይ ሐዋርያው ነኝ እንጂ አላት በእነርሱ ላይ የሠራችውን በደል ሁሉ ይቅር ይሏት ዘንድ መሪር ልቅሶ በማልቀስ ሐዋርያትን ለመነቻቸው እነርሱም አረጋጓት አጽናኗትም።

ከሀገሩም ሰዎች ብዙዎቹ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው በፊታቸውም ብዙዎች የሆኑ ድንቆች ተአምራትን አደረገ ይህንንም አይተው የሀገሩ ሰዎች ሁሉም በጌታችን አመኑ። ከጣዖታቱ አገልጋዮች በቀር እነርሱም ሰይጣን በእርሱ ላይ ስለሚያነሣሣቸው ሊገድሉት ይሹ ነበር ነገር ግን ምርጦቹን እግዚአብሔር ጠበቃቸው።

የከበረ ዮሐንስም ሁሉንም እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ እስከመለሳቸው ድረስ ታላቅ ድካምና ጭንቅ የሆነ መከራ ደረሰበት። የከበረ ሐዋርያ ጳውሎስም ስለ ልቡናቸው ደንዳናነት ጣዖታትን ስለመውደዳቸውም ስለ እነርሱ መስክሮአል። እርሱም ዮሐንስ በታላቅ ድካም ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው። ከዚህም በኋላ ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትን ዲያቆናትን ሾመላቸው።

ከዚህም በኃላ ከእስያ በዙርያዋ ወዳሉ አገሮች ሁሉ ወጥቶ አስተማረ እግዙአብሔርንም ወደማወቅ መለሳቸው።ይህም የከበረና የተመሰገነ ዮሐንስ በዚህ ዓለም ዘጠና ዓመት ኖረ እጅግም ሸመገለ ግን እንደ ባልንጀሮቹ ሐዋርያት በመሰየፍ ሞትን አልቀመሰም። ስለ ድንግልናውና ስለ ንጽሕናው ይህ ሆነ ሁሉም በክብር ይስተካከሉ ዘንድ እርሱም ወንጌልን ቀለም ሲስ የሙባለውን ራእይ ሦስት መልእክታትን የጻፈ ነው።ራት ሲበሉ በጌታ ኢየሱስ አጠገብ የተቀመጠውና አቤቱ የሚያሲዝህ ማነው ያለው ይህ እርሱ ነው።

ጌታችንም በተሰቀለ ጊዜ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር በመስቀሉ አጠገብ የቆመ እናቱንም እነሆ ልጅሽ ያላት እርሱን ደቀ መዝሙሩንም እነኋት እናትህ ያለው ነው።

ጴጥሮስም እርሱን ሲከተለው በአየው ጊዜ ስለርሱ ጌታ ኢየሱስን አቤቱ ይህስ እንዴት ነው ብሎ የተናገረ ጌታ ኢየሱስም እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ከወደዱኩ አንተ ምን አለህ አንተ ግን ተከተለኝ ያለለት ይህ ነው ።

የተመሰገነ ዮሐንስም ከዚህ ዓለም የሚወጣበት ሰዓት እንደ ቀረበ በአወቀ ጊዜ ሕዝቡን ጠራቸው ጸሎትንም ጸለየና ኅብስቱን ባርኮ ቆረሰ ይህም የጌታችን ሥጋውንና ደሙን ሰጣቸው በቀናች ሃይማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው ባረካቸው አጽናናቸውም።

ከዚህም በኃላ ደቀ መዝሙሩ አብሮኮስን ከወንድሞችም ሌሎች ሁለትን መቆፈሪያ ይዘው ይከተሉት ዘንድ አዘዘ።ከኤፌሶንም ከተማ ውጭ ወጣ ጐድጓድ እንዲቆፍሩም አዘዘ ከውስጥዋም ወርዶ ቆመ ልብሱንም አስወገደ ከአንድ የበፍታ ቀሚስ በቀር አላስቀረም። እጆቹንም አንሥቶ ጸለየና ወደ ከተማ ይመለሱ ዘንድ አሰናበታቸው በክርስቶስም ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ለሕዝቡ ይነግሩአቸው ዘንድ አዘዛቸው በጎ ሥራዎችንም ይሠሩ ዘንድ ጌታችን ለሁሉም እንደ ሥራው ይከፈለው ዘንድ አለውና።

ሁለተኛም እንዲህ አላቸው እኔ ከሁላችሁም ደም ንጹሕ ነኝ ከእግዚአብሔር ትእዛዝና ሕግ ሳልነግራችሁ የተውኩት ምንም ምን የለምና እናንተም ከእንግዲህ ከቶ ፊቴን አታዩኝም።

ይህንንም በተናገረ ጊዜ አለቀሱ እጆቹንና እግሮቹን ስመው በጒድጓዱ ውስጥ ትተውት ወደ መንገድ ተመለሱና የሆነውን ሁሉ ለሰዎች ነገሩዋቸው ሁሉም ደንግጠው መጡ ግን ልብስና ጫማ እንጂ መቃብሩን አላገኙም እጅግም አደነቁ ደቀ መዝሙሩ ዮሐንስን በዚህ በጎ ዕረፍት ያሳረፈው እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ናርዶስ_ዘደብረ_ቢዘን

ዳግመኛም በዚኽች ዕለት ስንክሳሩ ‹‹ተጋዳይ የሆነ በጥላው ብቻ ከይሲን የገደለ የደብረ ቢዘኑ አባ ናርዶስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እርሱም እግሮቹ እስኪያብጡ ድረስ ቆሞ በመጸለይ የተጋደለ ነው›› በማለት በአጭሩ የገለጸው ጻድቁ አባ ናርዶስ ዕረፍቱ ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_መልከጼዴቅ_ዘዋሸራ

መርሐቤቴ ያሉት ማለትም በደጃቸው የተቀበረውን ሰው ዐፈር የማስበሉት ጻዲቅ የሚዳው አቡነ መልከጼዴቅና የዋሸራው አቡነ መልከጼዴቅ ሁለቱ የተለያዩ ናቸው፡፡ እኚህኛው የዋሸራው አቡነ መልከጼዴቅ ከአባታቸው ከዘካርያስና ከእናታቸው ስነ ክርስቶስ የተወለዱት አቡነ መልከጼዴቅ ዘዋሸራ ትውልድ ሀገራቸው ጎጃም ዋሸራ ሲሆን በታላቅ ተጋድሎና በሹመት ያገለገሉትም በዚሁ ነው፡፡

ዲቁናንና ቅስናን ከግብፅ ተቀብለው በዋሽራ 30 ዓመት በሹመት አገልግለዋል፡፡ ጻድቁ የሚታወቁበት ትልቁ ተጋድሎአቸው በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ ሁልጊዜ ዓርብ ዓርብ ያከፍሉ ነበር፡፡ የመድኃኔዓለምን 13ቱን ሕመማተ መስቀሎች በማሰብ አናታቸውን በድንጋይ እያቆሰሉ ቁስሉ ሲተላ ትሉን ለወፎች ይመግቡ ነበር፡፡ በ40 ቀን ውስጥ አንዷን ቀን ብቻ ነው ውኃ ይጠጡ የነበረው፡፡ ጻድቁን የቅኔ ተማሪዎች በዋሸራ ይዘክሯቸዋል፡፡
#የካቲት_30

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቀ_መለኮት

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሠላሳ በዚህች ዕለት የመጥምቁ ዮሐንስ የከበረች ራሱ ተገኘች። ይህም እንዲህ ነው ከሀዲ ኄሮድስ የከበረ ዮሐንስን ራሱን ይቆርጡት ዘንድ በአዘዘ ጊዜ በእሥር ቤት ራሱን ቆርጠው ወደ ኄሮድስ አቀረቧት እርሱም ለወገኖቹ በማሳየት በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ስለ አደረገው ሥራ እንደሚያዝን ገለጠላቸው የክቡር ዮሐንስንም ራስ በቤቱ ውስጥ አስቀራት።

የፊተኛዪቱ ሚስቱ የንጉሥ አርጣ ልጅ ግን በአበረራት ጊዜ ወደ አባቷ መጥታ በፊቱ አለቀሰች ኄሮድስ በእርሷ ላይ ያደረገውን ሁሉ እርሷን አሳዶ የወንድሙን ሚስት ኄሮድያዳን እንዳገባ ነገረችው። በዚያንም ጊዜ ንጉሥ አርጣ ተቆጥቶ ተነሣ ሠራዊቱንም ሰብስቦ ወደ ገሊላ ዘመተ የገሊላንም ሀገሮች ሁሉ አጠፋ በእሳትም አቃጠለ።

ንጉሥ ጢባርዮስ ቄሣር ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ኄሮድስ በአባረራት በልጁ ምክንያት ንጉሥ አርጣ ይህን እንዳደረገም በአስረዱት ጊዜ ስለዚህ ንጉሥ ጢባርዮስ ቄሣር ተቆጣ ኄሮድስንም ወደ ሮሜ ከተማ ወደርሱ አስቀረበው በእርሱም ምክንያት የሀገሮች ጥፋት በመደረጉና ታላቁን ነቢይም ስለ መግደሉ ከሹመቱ ሻረውና እንድልኩ ወደሚባል አገር አጋዘው በዚያም በክፉ አሟሟት ሞተ።

የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ግን በኄሮድስ ቤት ተቀብራ ትኖር ነበር ከዚህም በኋላ ንጉሥ ጢባርዮስ ጭፍሮቹን ልኮ የኄሮድስን ቤት አስፈረሰ ጥሪቱን ሁሉ ወሰደ ለሚያየውም ሁሉ አርአያና ተረት ሆነ ያለ ጣሪያና ያለ ደጃፍ ቀርቷልና ነጋዴዎችም መነሃሪያ አድርገው ያድሩበት ነበር።

በዚያንም ወራት በገንዘብ ድኆች በሃይማኖት ባለጸጎች የሆኑ ሁለት ሰዎች ነበሩ እነርሱም ሊሰግዱ የከበረች የአርባ ቀን ጾምንም ሊጾሙ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዙ ይህም ከብዙ ዘመን በኋላ ነው።

ምሽትም በሆነ ጊዜ ምድረ በዳ በሆነ በኄሮድስ ቤት ውስጥ አደሩ ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሳቸው ለአንዱ በሕልም ተገለጠለትና የከበረች ራሱ ያለችበትን ቦታ አስረዳው ወደቤቱም ተሸክሞ ይወስዳት ዘንድ አዘዘው በነቃም ጊዜ ራእይን እንዳየ ለባልንጀራው ነገረው።

ቅዱስ ዮሐንስም ወደአመለከተው ወደዚያ ቦታ ተነሥተው በአንድነት ሔዱ በቆፈሩም ጊዜ የሸክላ ዕቃ አግኝተው ከፈቷት ያን ጊዜ እጅግ የሚመስጥ በጎ መዓዛ ወጣ የቅዱስ ዮሐንስንም ራስ አገኙዋት ከእርሷም ተባረኩ ወደ ሸክላውም ዕቃ መለሱዋትና በፊት እንደ ነበረ አፉን ዘጉ ያም ሰው ከእርሱ ጋር ወደ ቤቱ ወሰዳት ታላቅ ክብርንም አከበራት ሁል ጊዜም የሚያበሩ መብራቶችን በፊቷ አኖረ።

የዚያም ሰው ዕረፍቱ በቀረበ ጊዜ ለእኅቱ ነገራት እርሷ ቅድስና ስለአላት እርሱ ሲሠራው እንደነበረ ትሠራ ዘንድ አዘዛት እርሷም የምታከብራትና ሁል ጊዜ መብራትንም የምታበራ ሆነች።

የቅዱስ ዮሐንስም ራስ ወደ አርዮሳዊ ሰው እስከ ደረሰች ድረስ ከአንዱ ሰው ወደ አንዱ ሰው የምትፋለስ ሆነች ይህም ሰው በከሀዲው አርዮስ እምነት ውስጥ እያለ የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ድንቆች ተአምራቶችን እንደምታደርግ ያስብ ነበር።

የከበረ ዮሐንስም ከእርሱ የሚበልጥ ሰው በላዩ አስነሣበትና ከዚያ ቦታ አሳደደው ያም ቦታ አባ ቄርሎስ በኢየሩሳሌም ሀገር አባ አንያኖስ በሀገረ ኀምዳ ኤጲስቆጶስነት እስከ ተሾሙ ድረስ ፈጽሞ ሰው የማይኖርበት ምድረ በዳ ሆነ።

ቅዱስ ዮሐንስም ለአባ አንያኖስ በሕልም ተገልጦ የከበረች ራሱ ያለችበትን ቦታ ነግሮ አመለከተው አባ አንያኖስም ሒዶ እንደ ዛሬው ግንቦት ሠላሳ ከዚያ አወጣት ይህም የካቲት ሠላሳ ቀን ከአገኙዋት በኋላ ዳግመኛ ያገኙበት ነው።

እንዲህም የሚል አለ የከበረ ዮሐንስ አፈወርቅ ተናገረ ይህም ኄሮድስ በአዘዘ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ በእሥር ቤት ሳለ ራሱን በሰይፍ ቆርጠው በጻሕል አድርገው ወደ ኄሮድስ አመጡለት እርሱም ለኄሮድያዳ ልጅ ሰጣት እርሷም ለእናቷ ወስዳ ሰጠች።

ይቺም የረከሰች አመንዝራ ልትዳስሣት በወደደች ጊዜ በወጭቱ ውስጥ ጠጒሩዋ ተዘርግቶ ወደ አየር በረረች በአየርም ሁና የወንድምህን ሚስት ልታገባ አይገባህም እያለች የምትጮኽ ሆነች እንዲህም እያለች ዐሥራ አምስት ዓመት ኑራ በዓረቢያ ምድር ዐረፉ በዚያ ተቀበረች።

ነጋድያንም በዚያ ቦታ የሚያድሩ ሆነ በእግዚአብሔርም ፈቃድ ሁለት አማንያን ነጋዴዎች ወደዚያ ቦታ ደርሰው አደሩ ቅዱስ ዮሐንስም በሕልም ተገለጠላቸውና የከበረች ራሱን ያወጡ ዘንድ አዘዛቸው እነርሱም አወጡዋት ከእርሳቸውም ጋር ወደ ቤታቸው ወስደው ታላቅ ክብርን አከበሩዋት።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም መለኮትን በአጠመቀ በከበረ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን፤ ልዩ የሆነች በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት)
#ሐምሌ_16

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌሉ_ዘወርቅ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ስድስት በዚች ቀን ቅዱስ አባት ወንጌሉ ዘወርቅ የተባለ ዮሐንስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከሮሜ አገር ነበር አባቱም አጥራብዮስ የሚባል ባለጠጋ ነው። የእናቱም ስም ብዱራ ይባላል። እንዲማርም ለመምህር ሰጡት ቅዱሳት መጻሕፍትንም ተማረ።

ከዚህም በኋላ ገበታው የወርቅ የሆነ ወንጌልን ያሠራለት ዘንድ አባቱን ለመነው አባቱም እንደፈለገው አሠራለት ሁል ጊዜም ያነበው ነበር። በሚያነብ ጊዜም አባቱና እናቱ ደስ ይላቸው ነበር።

በዚያም ወራት ወደ ኢየሩሳሌም የሚጓዝ መነኵሴ ወደ እነርሱ መጣ በእነርሱም ዘንድ አደረ ከቅዱስ ዮሐንስም ጋራ ተነጋግሮ የምኵስናን ሥራ አመሰገነለት ይህን ዓለም እስከ ናቀና እንደ እርሱ መነኰስ ይሆን ዘንድ እስከ ወደደ ድረስ ልቡን ማረከው።

ያን ጊዜም ያ መነኰስ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ ሁለተኛም ተመልሶ እንደ ልማዱ በእነርሱ ዘንድ አደረ። ቅዱስ ዮሐንስም መነኵሴው ወደ ገዳሙ ይወስደው ዘንድ ፈለገ መነኲሴውም አባትህን እፈራዋለሁ ልወስድህ አይቻለኝም አለው። ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሱ ጋራ እንዲወስደውና ነፍሱን እንዲያድን አማለው።

ከዚህም በኋላ በስውር ወሰደው በመርከብም ተጭነው ያ መነኰስ ወደሚኖርበት ገዳም ደረሱ የገዳሙም አበ ምኔት የወጣቱን ዮሐንስን መልኩን አይቶ አደነቀ። ቅዱስ ዮሐንስም የምንኵስናን ልብስ ያለብሰው ዘንድ አበ ምኔቱን ለመነው አበ ምኔቱም ልጄ ሆይ የምንኵስና ሕግ እጅግ ጭንቅ ናት እኮ አለው። አብዝቶም በለመነውና ግድ ባለው ጊዜ ራሱን ላጭቶ አመነኰሰው።

ከዚህም በኋላ ከጾም ከትጋትና ከኀዘን የተነሣ ሥጋው ደርቆ አጥንቶቹ እስከሚታዩ ድረስ በብዙ ተጋድሎ ተጸመደ። አበ ምኔቱም ልጄ ሆይ ለሰውነትህ እዘን ድካምህንም ቀንስ መነኰሳቱም ሁሉ እንደሚሠሩት ሥራ እያለ ያጽናናውና ይመክረው ነበር።

በዚህ ተጋድሎም ሰባት ዓመት በሆነው ጊዜ ከእነርሱ በረከትን ትቀበል ዘንድ ከመሞትህ በፊት ወደ አባትህና እናትህ ሒድ የሚል ራእይ አየ። ይህንንም ራእይ በሦስት ሌሊቶች ውስጥ አየ ለአበ ምኔቱም እንዴት እንዳየ ነገረው አበ ምኔቱም ይህ ራእይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለ ሆነ ልትሔድ ይገባሃል አለው። ከገዳሙም በወጣ ጊዜ አንድ ምስኪን ሰው ጨርቅ ለብሶ አገኘ። የእርሱንም ልብስ ሰጥቶት ጨርቁን ወሰደ።

ወደ አባቱ ቤትም በደረሰ ጊዜ በትንሽ ጎጆ ውስጥ በአባቱ ደጅ በጾም በጸሎትና በስግደት እየተጋደለ ባሮች ከአባቱ ማዕድ የሚጥሉለትን ፍርፋሪ እየተመገበ ሰባት ዓመት ኖረ። እናቱም በአንጻሩ ስታልፍ የሚከረፋ ሽታው ያስጨንቃት ነበር። ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰባት ቀን በኋላ ከዚህ ዓለም ትወጣለህ ብሎ ነገረው።

ያን ጊዜም ወደ እናቱ ልኮ ልመናውን ልትሰማ ወደ እርሱ መጣች ልጅዋም እንደሆነ ፈጥኖ አልነገራትም ነገር ግን በዚያች በታናሽ ማደሪያ ውስጥ በላዩ ባለ ጨርቅ እንድትቀብረው የለበሰውንም ጨርቅ እንዳትለውጥ አማላት። ከዚህም በኋላ ያንን የወርቅ ወንጌል ሰጣት። እንዲህም አላት ይህን መጽሐፍ አንብቡ እኔንም አስቡኝ።

አባቱም በመጣ ጊዜ ያንን የወርቅ ወንጌል አሳየችው እርሱም ለልጁ ያሠራለት ወንጌል እንደሆነ አወቀ። አባቱና እናቱም ወደ እርሱ ሔደው ስለ ልጃቸው ጠየቁት እርሱም ከዚህ ጨርቅና ከዚህ ትንሽ ማደሪያዬ ውስጥ በቀር በሌላ እንዳትቀብሩኝ ማሉልኝ አላቸው።

በአማላቸውም ጊዜ እርሱ ልጃቸው እንደሆነ ነገራቸው ያን ጊዜም ጮኹ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ የሮሜ ከተማ ሽማግሌዎችና ሕዝቡ ሁሉ ተሰበሰቡ ሰባቱ ቀንም ሲፈጸም ቅዱስ ዮሐንስ አረፈ። እናቱም መሐላዋን ረስታ አስቀድማ ለሠርጉ ያዘጋጀቻቸውን ያማሩ ልብሶች አውጥታ ገነዘችው። በዚያችም ጊዜ ታመመች አባቱ ግን መሐላውን አስታውሶ እነዚያን ያማሩ ልብሶች አስወገደ በጨርቆቹም ገነዙት በዚያ በትንሹ ማድሪያም ውስጥ ቀበሩት ከሥጋውም በሽተኞች የሚፈወሱበት ታላቅ ድኅነት ተገኘ።

ከዚህም በኋላ በስሙ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ሥጋውን በውስጧ አኖሩ። ከእርሱም ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ)
ስንክሳር ዘተዋሕዶ:
#መስከረም_29

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሃያ ዘጠኝ በዚህችም ቀን #ከቅድስት_አርሴማና_ከእመምኔቷ_ከአጋታ ጋር ደናግላን በሰማዕትነት አረፉ፤ ዳግመኛም #የቅዱስ_ዮሐንስ_ነባቤ_መለኮት (ወንጌላዊው) እንደ ንስር መጥቆ "ቀዳሚሁ ቃል.." (ዮሐ. ፩፥፩) ብሎ ወንጌሉን የጻፈበት ዕለት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሰማዕት_ቅድስት_አርሴማ

በዚችም ቀን ከቅድስት አርሴማና ከእመምኔቷ ከአጋታ ጋር ደናግል በሰማዕትነት አረፉ። ይህም እንዲህ ነው በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን እርሱ መልኳ ውብ የሆነ ብላቴና ድንግል ሊአገባ ሽቶ በየሀገሩ ሁሉ ሒደው መርጠው ያመጡለት ዘንድ አሽከሮቹን አዘዘ።

ይችንም የሚመስላት የሌለ ቅድስት አርሴማን በሮሜ አገር በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ አገኙዋት። ሥዕሏንም ሥለው ለንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ላኩለት ንጉሡም ሥዕሏን በአየ ጊዜ እጅግ ደስ አለውና ለሠርግ እንዲመጡ ወደ መኳንንቱ ላከ።

እሊያ ደናግልም ይህን ነገር በአወቁ ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ ድንግልናቸውንም ይጠብቅ ዘንድ አልቅሰው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ። ከዚህም በኋላ ተነሥተው በሥውር ሸሹ የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደ ሆነ ወደ አርማንያ ሀገርም ደርሰው በአንድ ቦታ ተቀመጡ ከእርሳቸውም ጋር የተሰደዱ ቁጥራቸው ሰባ አምስት የሆነ ወንዶች፣ ሴቶችም ሠላሳ ዘጠኝ የሆኑ ከእርሳቸው ጋራ አሉ። ምግባቸውን አያገኙም ነበርና በታላቅ ችግር ውስጥ ኖሩ ከእነርሱም መብራት የምትሠራ አንዲት ሴት ነበረች ከእርሷም የእጅ ሥራ ከሚገኘው በየጥቂቱ ይመገባሉ።

ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም የከበረች አርሴማን በፈለጋት ጊዜ አላገኛትም ግን በአርማንያ አገር እንዳለች ስለርሷ ሰማ። ደግሞ ለአርማንያ ንጉሥ ለድርጣድስ ስለርሷ ከዲዮቅልጥያኖስ ሸሽታ እንደ መጣች የአርሴማን ሥራ ነገሩት እርሱም አንዱን የአርማንያ መኰንን ለእኔ ጠብቃት ወደ እኔም ላካት ብሎ አዘዘው።

ደናግሉም ይህን በሰሙ ጊዜ ወደ ሌላ ቦታ ተሠወሩ ወደ ንጉሥም ወነጀሉአቸው ንጉሡም ቅዱስት አርሴማን በክብር አድርገው ያመጧት ዘንድ አዘዘ እርሷም ወደ እርሱ መምጣትን እምቢ በአለች ጊዜ እየጎተቱ ወስደው ወደርሱ አደረሷት።

የቅድስት አርሴማንም ላህይና ደም ግባቷን በአየ ጊዜ ድንግልናዋን ሊያረክስ ሽቶ እናቷ አጋታን አባብላ እሺ ታሰኝለት ዘንድ አዘዛት አጋታም ወደርሷ ሒዳ ልቧን አስጨከነች እንዲህም አለቻት። ዕወቂ ይህ ርኲስ አረሚ እንዳያረክስሽና ሰማያዊ ሙሽራሽን እንዳትተዪ እርሱም ክብር ይግባውና የእግዚአብሔር ልጅ ሕያው ክርስቶስ ነው።

ንጉሡም ይዞ ወደ እልፍኙ ሊአስገባት ከአደባባይ መካከል ተነሥቶ ድንግል አርሴማን ያዛት። በዚያንም ጊዜ በቅድስት አርሴማ ላይ የእግዚአብሔር ኃይል አደረባትና በምድር ላይ ጣለችው እርሱ ግን በጦርነት እጅግ የጸና አርበኛ ስለ ነበር በታናሽ ሴት ብላቴና ስለተሸነፈ ያን ጊዜ አፈረ። ራሷንም በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጧት ከዚህም በኋላ ደናግሉን ሁሉ ከእናታቸው አጋታ ጋር ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ።

አንዲት የታመመች ድንግል ነበረች በዐልጋዋ ላይም እንደተኛች ወደ ወታደሮች ጮኸች መጥተውም እንደ እኅቶቿ ራሷን ቆረጡ ሁሉም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ እነዚያንም ከሮሜ አገር አብረው የመጡ ወንዶችን ገደሏቸው ቁጥራቸውም ሰባ አምስት ናቸው ሥጋቸውም በተራራ ላይ የተጣለ ሁኖ ቀረ።

ሰማዕታትም ከተገደሉ በኋላ በንጉሡ ላይ ጋኔን ተጫነበት መልኩም ተለውጦ እንደ እርያ ሆነ። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ወደርሱ መጥቶ በላዩ ጸልዮ እስከ አዳነው ድረስ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። የቅዱሳን ሰማዕታትንም ሥጋቸውን ከተጣለበት ሰብስበው በአማረ ቦታ አኖሩአቸው ያማረች ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንም ተሠራችላቸው። ከእነርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌላዊ_ነባቤ_መለኮት

ዳግመኛም በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ እንደ ንስር መጥቆ "ቀዳሚሁ ቃል.." (  ዮሐ. ፩፥፩) ብሎ ወንጌሉን የጻፈበት ዕለት እንደሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ፡- ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን መዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ፡፡ የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡

እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ "በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን" እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም "አይዞሽ አትዘኚ" አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ "እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን" ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም "በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ" አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በጌታችን አመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡

በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስዶታል።
#ጥቅምት_10

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ዐሥር በዚህች ቀን የቅዱስ ባኮስ ባልንጀራ የሆነ #ቅዱስ_ሰርጊስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_አውማንዮስ አረፈ፣ መስተጋድል የሆነ #ቀሲስ_ዮሐንስ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሰርጊስ_ሰማዕት

ዳግመኛም በዚችም ቀን ከከሀዲ ንጉሥ መክስምያኖስ ሠራዊት ውስጥ የቅዱስ ባኮስ ባልንጀራ የሆነ ቅዱስ ሰርጊስ በሰማዕትነት አረፈ። ንጉሥ መክስምያኖስም ወደ ሶርያ አገር ወደ አንጥያኮስ በላካቸው ጊዜ ቅዱስ ባኮስን ከውኃ በማስጠም በዚህ ወር በአራተኛ ቀን ገደሉት። ቅዱስ ሰርጊስን ግን አሥሮ በወህኒ ቤት አኖረው።

ከዚህም በኋላ በእግሮቹ ውስጥ ረጃጅም የብረት ችንካሮችን ቸንከረው ከፈረሰኞች ጋር ሩጻፋ ወደሚባል አገር እንዲወስዱት መኰንኑ አዘዘ።

ሲወስዱትም ያስሮጡት ነበር ደሙም በምድር ላይ እንደ ውኃ ይፈስ ነበር በጐዳናም አንዲት ድንግል ብላቴና አገኘ ከእርሷም ዘንድ ውኃን ጠጣ ሥጋዬን ትወስጂ ዘንድ እስከ ሩጻፋ ተከተይኝ አላት እርሷም ራራችለት ለጒልምስናውም አዘነችለትና ተከተለችው።

አንጥያኮስም እንዲህ ብሎ ጽፎአልና ሰርጊስ ትእዛዜን ተቀብሎ ለአማልክት ካልሠዋ ራሱን በሰይፍ ይቁረጡ። እርሱም ለቅዱስ ሰርጊስ ወዳጅ ነበርና ስለርሱም ይችን ሹመት አግኝቷት ነበርና በዚያንም ጊዜ ወታደሩ የቅዱስ ሰርጊስን ራስ ቆረጠው ያቺም ብላቴና ቀርባ ከእርሷ ጋር በነበረ የፀጕር ባዘቶ ከአንገቱ የፈሰሰውን ደሙን ተቀበለች። የስደቱም ወራት እስከ አለፈ ድረስ ሥጋውን ጠበቀች።

ከዚህም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ተሠራችለት ዐሥራ አምስት ኤጲስቆጶሳትም አከበሩዋት የቅዱስ ሰርጊስንም ሥጋ በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ እጅግ ሽታው ጣፋጭ የሆነ በሽተኞችን የሚፈውስ የሽቱ ቅባት ከሥጋው ይፈስ ነበርና።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሊቀ_ጳጳሳት_ቅዱስ_አውማንዮስ

ጥቅምት ዐሥር በዚች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባተኛ የሆነ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት አውማንዮስ አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ትሑት የሆነ ለዕውነተኛ ሥራ ሁሉ የሚያገለግል ነበር ቅዱስ አብርምዮስም ትሩፋቱን አይቶ ዲቁና ሾመው በዲቁና አገልግሎትም ዐሥር ዓመት ኖረ።

ዮስጦስም ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ ትሩፋቱንና የሃይማኖቱን ቅንነት ተመለከተ ምእመናንንም ማስተማር እንደሚችል አውቆ ቅስና ሾመው። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ዮስጦስ በአረፈ ጊዜ ይህን አባት አውማንዮስን መርጠው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት የአብያተ ክርስቲያናትንም ሥራ ሁሉ ተረከበ።

መናፍቃንንም ተከራክሮ የሚረታቸው ሆነ ብዙዎችንም ከስሕተታቸው መለሳቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመለኮቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ትክክል እንደሆነ ግልጽ አድርጎ አስተማራቸው። በሹመቱም ዐሥራ ሦስት ዓመት ከኖረ በኋላ በአንስጣዮስ ሰባተኛ ዘመነ መንግሥት በዚች ቀን አረፈ። በዘመኑም የሶፍያ ሦስቱ ልጆቿ በሰማዕትነት አረፉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ቀሲስ

ዳግመኛም በዚችም ቀን መስተጋድል የሆነ ቀሲስ ዮሐንስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከተጋድሎው ብዛት የተነሣ ራሱን በሚላጭ ጊዜ በውኃ አያርሰውም ነበር።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይግባው እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት)
#ጥቅምት_21

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሃያ አንድ በዚህችም ቀን #እመቤታችን_ተአምራትን_አድርጋ_ሐዋርያው_ማትያስን ከእሥራት ቤት ያወጣችበት፣ #የነቢይ_ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ፣ የማርታና የማርያም ወንድም #የቅዱስ_አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት፣ የቅዱስ አባት #አባ_ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም እረፍት ነው፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#እመቤታችን_ለሐዋርያው_ማትያስ_ያደረገችለት_ተአምር

በዚህችም ቀን እመቤታችን ማርያም ተአምራትን አድርጋ ደቀ መዝሙር ማትያስን ከእሥራት ቤት አዳነችው።

የከበሩ ቅዱሳን ወንጌልን በዓለም ዞረው ይሰብኩ ዘንድ ዕጣ ሲጣጣሉ ለቅዱስ ማትያስ ዕጣ የደረሰው ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ነበር፡፡ ይህችም ሀገር እስኩቴስ የተባለች ሩሲያ እንደሆነች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ፍንጭ ሰጥተዋል፡፡

ማትያስም እነዚህ ሰውን የሚበሉ ሰዎች አገራቸው እንደደረሰ ዐይኑን አውልቀው አሠሩት፡፡ ምግባቸውም የመጻተኛ ሰው ሥጋ ነው፡፡ በልማዳቸው መሠረት መጻተኛን ሰው ገና እንደያዙት ዐይኖቹን ዐውልቀው በእሥር ቤት ያኖሩታል፡፡ እስከ 30 ቀንም ድረስ ሳር እያበሉ ያስቀምጡትና በ30ኛው ቀን አውጥተው አርደው ይበሉታል፡፡

ሐዋርያው ማትያስንም በልማዳቸው መሠረት ዐይኖቹን አውልቀው አሠሩት፡፡ ሐዋርያውም በእሥር ቤት ሆኖ በዚያ ላይ ዐይኖቹን ታውሮ ሳለ በጭንቅ ወደ ጌታችንና ወደ እመቤታችን ይለምን ነበር፡፡ ነገር ግን እመብርሃንና ልጇ መድኃኔዓለም 30ኛው ቀን ሳይፈጸም ሐዋርያው እንድርያስን ወደ እርሱ ላኩለት፡፡ ማትያስም ዐይኑን ፈወሱለትና ማየት ቻለ፡፡

እንድርያስም በተዘጋው በር በተአምራት ገብቶ አሥርቤቱ ውስጥ ያሉ እሥረኞችን በስውር አውጥቶ ከከተማው ውጭ ካስቀመጣቸው በኋላ ሁለቱ ሐዋርያት ተመልሰው ሰውን ለሚበሉት ሰዎች ተገለጡላቸው፡፡ እነርሱም ይዘው በአንገታቸው ገመድ አግብተው ለ3 ቀን በሀገራቸው ጎዳናዎች ላይ ሁሉ ጎተቱዋቸው፡፡ ሁለቱም ሐዋርያት በጸሎታቸው ከእሥር ቤቱ ምሰሶ ሥር ውኃ አፈለቁና ውኃው ሀገራቸውን ሁሉ እስኪያጥለቀልቅና ሰዎቹንም እስከ አንገታቸው ድረስ እስከሚደርስ ሞላ፡፡ ሁሉም በተጨነቁ ጊዜ ሁለቱ ሐዋርያት በፊታቸው ተገለጡና ‹‹በጌታችን እመኑ ትድናላችሁ›› በማለት ወንጌልን ሰብከውላቸው አሳመኗቸው፡፡ ምሥጢራትንም ሁሉ ገለጡላቸው፡፡ ደግሞም የአራዊት ጠባይን ከሰዎቹ ያርቅላቸው ዘንድ ወደ ጌታችንና ወደ ተወደደች እናቱ ከጸለዩ በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው፡፡ ያ የአውሬነት ጠባያቸውም ጠፍቶላቸው የዋህ፣ ቅንና ሩኅሩኆቸ ሆኑ፡፡ ሐዋርያትም ሃይማኖትን እያስተማሯቸው 30 ቀን አብረዋቸው ከተቀመጡ በኋላ አገልጋይ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ካህናትንና ዲያቆናትን ሾመውላቸው ወደ ሌላ ሀገር ሄዱ፡፡

ለሐዋርያት ሞገሳቸው ጣዕመ ስብከታቸው የኾነች ክብርት እመቤታችን ለእኛም ትለመነን!

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኢዩኤል_ነቢይ

ዳግመኛም በዚህችም ቀን የነቢይ ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም የእስራኤልን ልጆች የሚያስተምርና የሚገሥጻቸው ነበር ስለ ክርስቶስም በኢየሩሳሌም መኖርና ማስተማር ትንቢት ተናገረ። ደግሞም ስለ መከራው በሐዋርያትና በሰባ ሁለቱ አርድእት በሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ላይ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ እንዲህ ሲል ተናገረ።

ከዚህ በኋላ በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ ከመንፈሴ አሳድርበታለሁ ሴቶች ልጆቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ ትንቢትን ይናገራሉ አለቆቻችሁ ሕልምን ያልማሉ ጎልማሶቻችሁም ራእይን ያያሉ። ሁለተኛም እንዲህ አለ ያን ጊዜ ከተራራው ማር ከኮረብታውም ወተት ይፈሳል በቤተ እግዚአብሔር አጠገብ ካሉ ከይሁዳ አገሮች ሁሉ ምንጩ ከላይ ወደታች ይፈሳል።

ሙታን በሚነሡ ጊዜ ስለሚሆነው የፍርድ ሰዓት እንዲህ አለ ፀሐይና ጨረቃ ይጨልማሉ የከዋክብትም ብርሃናቸው ይጠፋል። የትንቢቱንም ወራት አድርሶ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አልዓዛር የማርታና የማርያም ወንድም

በዚችም ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው የቅዱስ አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት ሆነ።

ከክርስቲያን ነገሥታትም አንዱ ሥጋው በቆጵሮስ እንዳለ በሰማ ጊዜ ከቆጵሮስ ደሴት ወደ ቊስጥንጥንያ አፈለሰው። ሊአፈልሱትም በወደዱ ጊዜ በከበረ የደንጊያ ሣጥን ውስጥ ሁኖ በምድር ውስጥ ተቀብሮ አገኙት በላዩም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ነበረ ይህ በመቃብር ውስጥ አራት ቀን ከኖረ በኋላ ከሙታን ለይቶ ላስነሣው ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ የሆነ የቅዱስ አልዓዛር ሥጋ ነው።

ይህንንም በአዩ ጊዜ ደስ ተሰኙበት ተሸክመውም ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ወሰዱት ካህናቱም ሁሉ ወጥተው በታላቅ ክብር በመዘመርና በማመስገን ተቀበሉት በአማረ ቦታም አኖሩት በዚችም ቀን በዓልን አደረጉለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘኢየሩሳሌም

በዚህችም ቀን ለከበረች አገር ኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ እግዚአብሔርን በሚወድ የንጉሥ ሰይፈ አርዕድ ደግሞ ቈስጠንጢኖስ ለሚባል ልጁ በሆነ በንጉሣችን በዳዊት ዘመን አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከምስር አገር ታላላቆች እግዚአብሔርን የሚፈሩ የክርስቲያኖች አባቶች ልጅ ነው። የዲቁና መዓረግንም ለመሾም እስከ ተገባው ድረስ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። ከዚህም በኋላ በዲቁናው ሹመት አገልግሎቱን በአሳመረ ጊዜ የቅስና መዓረግ የሚገባው ሁኖ ቅስና ተሾመ።

በጾም በጸሎት እግዚአብሔርንም በመፍራት የተጠመደ ሁኖ ድኆችንና ችግረኞችን የሚወዳቸው የሚረዳቸው ሆነ ያን ጊዜ የሐዋርያት የሆነች የጵጵስና ሹመት የምትገባው ሁና በከበረች አገር በኢየሩሳሌም በእግዚአብሔር ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ሕዝቡንም በፈሪሀ እግዚአብሔርና በትሕትና የሚያስተምራቸው ሆነ።

እነርሱም ስለ ቅድስናው እጅግ የሚወዱት ሆኑ መልኩና የአንደበቱ አገላለጥ እንደ እግዚአብሔር መልአክ ያማረ ነበር። በሹመቱም ጥቂት ዘመናት ከኖረ በኋላ ከመንበረ ሢመቱ እስከ አራቀው ድረስ በላዩ ሰይጣን ምክንያትን አመጣ።

ይህም እንዲህ ነው በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ማርቆስ ዘመን በግዛቱ ውስጥ ያሉ እስላሞች ስለ ዐመፁበት የኢትዮጵያ ንጉሥ ፈጅቷቸው ነበርና ስለዚህ በግዛቱ ውስጥ በሚኖሩ እስላሞች ላይ ክፉ እንዳያደርግ ለኢትዮጵያ ንጉሥ መልእክት እንዲልክ ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን የምስር ንጉሥ አዘዘው።

አባ ማርቆስም ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥ ስለሚላኩ ሰዎች ከመኳንንቱ ከኤጲስ ቆጶሳቱና ከሀገር ታላላቆች ሽማግሌዎች ጋር ተማክሮ እሊህን ብሩሀን ከዋክብት የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስን የምስር ኤጲስቆጶስ አባ ሳዊሮስን በእውቀታቸው በአስተዋይነታቸውና በቅድስናቸው መረጡአቸው ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥም ይሔዱ ዘንድ ግድ አሏቸው።

እነርሱም ታዛዦች ሁነው ወደ ኢትዮጵያ መጡ የኢትዮጵያ ንጉሥም መምጣታቸውን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው እሊህንም ቅዱሳን አባቶች ይቀበሏቸው ዘንድ አሽከሮቹን በቅሎዎችን አስይዞ ላከ በመጡም ጊዜ በታላቅ ደስታ ሰላምታ አቀረበላቸው ከእርሳቸውም ቡራኬን ተቀበለ ታላቅ ክብርንም አከበራቸው ። እነርሱም የሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ተቀብሎ አንብቦ ለሊቀ ጳጳሳቱ ቃል ታዛዥ መሆኑን ገለጠላቸው።
🌻 እንኩዋን ለታላቁ #ነቢይና_ሰማዕት_ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ 🌻

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ

=>ቅዱስ ወንጌል ላይ ከእመቤታችን ቀጥሎ የነ ዘካርያስን ቤተሰብ ያህል ክብሩ የተገለጠለት ፍጡር ይኖራል ብሎ መናገሩ ይከብዳል:: #ቅዱስ_ሉቃስ ወንጌሉን የጀመረው በዚህ ቅዱስ ቤተሰብ ነውና መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ሲል አጽፎታል:: "#ዘካርያስ ካህኑና #ቅድስት_ኤልሳቤጥ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ የሚኖሩ ጻድቃን ነበሩ" ይላቸዋል:: (ሉቃ. 1:6)

¤የሰውን እንተወውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ መኖር ምን ይረቅ? ለዚህ አንክሮ (አድናቆት) ይገባል!

¤እሊህ ቅዱሳን ባልና ሚስት ግን መካኖች በመሆናቸው ልጅ ሳይወልዱ ዘመናቸው አልፎ ነበር:: እንደ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ዕድሜአቸው የኤልሳቤጥ 90 የዘካርያስ 100 ደግሞ ደርሶ ነበር::

¤ፍጹም መታገሳቸውን የተመለከተ ጌታ ግን በስተ እርጅናቸው ከሰው ሁሉ በላይ የሆነ: ትንቢት ለብቻው የተነገረለት (ኢሳ. 40:3, ሚል. 3:1) ታላቅ ነቢይን ይሰጣቸው ዘንድ መልአከ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤልን ላከላቸው::

¤ቅዱስ ዘካርያስ ሰው ነውና ከደስታ ብዛት በመከራከሩ ድዳ ሆነ:: ቅድስቲቷ ግን መስከረም 26 ቀን ታላቁን ሰው ጸንሳ ለ6 ወራት ራሷን ሠወረች:: በ6ኛው ወር የፍጥረት ሁሉ ጌታ በተጸነሰ ጊዜ የአርያም ንግሥት ድንግል #እመቤታችን ደጋ ደጋውን ወደ ኤልሳቤጥ መጣች:: ሁለቱ ቅዱሳት የእህትማማች ልጆች ናቸው::

¤የአምላክ እናቱ ስትደርስና "#ሰላም" ስትላቸው መንፈስ ቅዱስ በእናትና ልጅ ወርዶ ኤልሳቤጥ በምስጋና: ዮሐንስ ደግሞ ገና በማሕጸን ሳለ በደስታ ዘለለ (ሰገደ):: ከዚህ በሁዋላ ሰኔ 30 ተወልዶ: አባቱ ዘካርያስ "ዮሐንስ" ሲለው አንደበቱ ተፈትቶለታል::

¤ቅዱስ ዮሐንስ ከተወለደ 2 ዓመት ከ6 ወር በሆነው ጊዜ #ሰብአ_ሰገል በመምጣታቸው በእሥራኤል ምድር የሚገኙ ሕጻናትን ሔሮድስ ቁዝ አስፈጀ:: ትንሽ ቆይቶም አይሁድ ለሔሮድስ ስለ ቅዱሱ ሕጻን ነገሩት:: "ሲጸነስ የአባቱን አንደበት የዘጋ: ሲወለድ ደግሞ የከፈተ 'ዮሐንስ' የሚባል ሕጻን አለና እሱንም ግደል" አሉ::

¤እናቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ ይዛው ስትሸሽ ካህኑን ዘካርያስን ግን በቤተ መቅደስ መካከል ገድለውታል:: አረጋይት ኤልሳቤጥም ሕጻኑን እያሳደገች በገዳመ ዚፋታ ለ3 (5) ዓመታት ቆይታለች:: ቅዱስ ዮሐንስ 5 (7) ዓመት ሲሞላው ግን እዚያው በበርሃ እናቱ ዐረፈች:: ከሰማይ ዘካርያስና #ስምዖን ወርደው ቀበሯት::

¤ሕጻኑ ዮሐንስ ሲያለቅስ #ድንግል_ማርያም ስንት አገር አልፋ ሰማችው:: እርሷም ስደት ላይ ነበረችና:: ከጌታ ጋር በደመና ሒደው ድንግል አቅፋ አጽናናችው:: ጌታንም "እንውሰደው ይሆን?" አለችው:: ጌታችን ግን "ለአገልግሎት እስክጠራው እዚህ ይቆይ" አላት:: ባርካው: አጽናንታውም ተለያዩ::

¤ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ በሁዋላ በዚያ ቆላ የግመል ጠጉር ለብሶ: ጠፍር ታጥቆ ተባሕትዎውን ቀጠለ:: ለ25 (23) ዓመታትም በንጽሕና ሲኖር ከምድር አራዊትና ከሰማይ መላእክት በቀር ማንንም አላየም:: ይሕችን ዐመጸኛ ዓለምም አልቀመሳትም::

¤ከዚህ በሁዋላ 30 ዘመን ሲሞላው እግዚአብሔር ከሰማይ ተናገረው:: "ሒድ! የልጀን ጐዳና ጥረግ" አለው:: ነቢያት ስለዚህ ነገር ተናግረው ነበርና:: (ኢሳ. 40:3, ሚል. 3:1) አባቱ ዘካርያስም "ወአንተኒ ሕጻን ነቢየ ልዑል ትሰመይ: እስመ ተሐውር ቅድመ እግዚአብሔር ከመ ትጺሕ ፍኖቶ" (ሉቃ. 1:76) ብሎ መንገድ ጠራጊነቱን ተናግሮ ነበርና::

¤ቅዱስ ዮሐንስ በዚያ ጊዜ በኃይለ #መንፈስ_ቅዱስ እየገሰገሰ ከበርሃ ወደ ይሁዳ መጣ:: ያዩት ሁሉ ፈሩት: አከበሩት:: ቁመቱ ቀጥ ያለ: ጽሕሙ እንደ ተፈተለ ሐር የወረደ: ጸጉሩ የቁራ ያህል የጠቆረ: መልኩ የተሟላ: ግርማው የሚያስፈራ ገዳማዊ ነውና::

¤ፈጥኖም ሕዝቡን ለንስሃ ሰበከ:: ለንስሃም በርካቶችን አጠመቃቸው:: በዚህ አገልግሎት ለ6 ወራት ቆይቶ ጌታችን ወደ እርሱ ዘንድ መጣ:: ዮሐንስ ሰማይን ከነግሱ: ምድርን ከነ ልብሱ የያዘ ፈጣሪ 'አጥምቀኝ' ብሎ ሲመጣ ደነገጠ:: የሚገባበትም ጠፋው::

¤"እንቢ ጌታየ! አንተ አጥምቀኝ" አለው:: ጌታ ግን "ፈቅጄልሃለሁ" አለው:: አጠመቀው:: በዚህ ምክንያት ይሔው እስከ ዛሬም "#መጥምቀ_መለኮት" ሲባል ይኖራል:: ቅዱስ ዮሐንስ በመጨረሻ ሔሮድስን ገሰጸው:: ንጉሡም ተቀይሞ ለ7 ቀናት አሠረው::

¤በዚህች ቀንም ልደቱን ባከበረ ጊዜ ወለተ ሔሮድያዳ በዘፈን አጥምዳ አስማለችው:: እርሱም የታላቁን ነቢይ ራስ አስቆርጦ በወጪት አድርጐ ሰጣት:: አበው "እምሔሶ ለሔሮድስ ይብላዕ መሐላሁ - ሔሮድስ መሐላውን በበላ በተሻለው ነበር" ይላሉ:: የቅዱስ ዮሐንስ ራሱ በርራ ስትሔድ አካሉን ግን ደቀ መዛሙርቱ ቀብረውታል:: (ማቴ. 3:1, ማር. 6:14, ሉቃ. 3:1, ዮሐ. 1:6)

¤ርጉም ሔሮድስ አንገቱን ካስቆረጠው በሁዋላ የመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ራሱ የጸጋ ክንፍ ተሰጥቷት ጌታችን ወዳለበት #ደብረ_ዘይት ሔዳ በፊቱ ሰገደች:: #ቅዱሳን_ሐዋርያት በአዩት ነገር ተገርመው ራሱን እጅ ነሷት::

¤ከዚሕ በሁዋላ ጌታችን #ኢየሱስ_ክርስቶስ ለቅዱስ ዮሐንስ ራስ የማስተማር ስልጣን ሰጥቶ አሰናበታት:: በመላው ዓለም ለ15 ዓመታት ስትሰብክ ኑራ ሚያዚያ 15 ቀን ዓረቢያ ውስጥ ዓርፋለች::

<<¤ አስማተ-ዮሐንስ መጥምቅ (የመጥምቁ ዮሐንስ ስሞች) ¤>>
1.ነቢይ
2.ሐዋርያ
3.ሰማዕት
4.ጻድቅ
5.ካሕን
6.ባሕታዊ/ገዳማዊ
7.መጥምቀ መለኮት
8.ጸያሔ ፍኖት (መንገድ ጠራጊ)
9.ድንግል
10.ተንከተም (የብሉይና የሐዲስ መገናኛ ድልድይ)
11.ቃለ አዋዲ (አዋጅ ነጋሪ)
12.መምሕር ወመገሥጽ
13.ዘየዐቢ እምኩሉ (ከሁሉ የሚበልጥ)

=>ጌታችን #መድኃኔ_ዓለም የመጥምቁ ዮሐንስን ምትረት አስቦ ይቅር ይበለን:: ጸጋውን: በረከቱንና ክብሩንም ያሳድርብን::

=>መስከረም 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ዮሐንስ ነቢይ (መጥምቀ መለኮት)
2.ቅዱስ ዳስያ ሰማዕት
3.ቅዱስ ዲዲሞስ ሰማዕት
4.ቅድስት መሪና

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ (ከ12ቱ ሐዋርያት)
2.ቅዱስ ኢዮብ ጻድቅ ተአጋሲ
3.ቅዱስ አቤል ጻድቅ
4.ቅዱስ አባ ዻውሊ ገዳማዊ (ታላቁ)
5.ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ
6.አባ ሕርያቆስ ዘሃገረ ብሕንሳ

=>+"+ #ጌታ_ኢየሱስ ለሕዝቡ ስለ #ዮሐንስ ሊናገር ጀመረ . . . ምን ልታዩ ወጣችሁ? ነቢይን? አዎን እላችሁአለሁ ከነቢይም የሚበልጠውን . . . እውነት እላቹሃለሁ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሳም . . . ነቢያት ሁሉና ሕጉ እስከ ዮሐንስ ድረስ ትንቢት ተናገሩ:: ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው #ኤልያስ ይሕ ነው::
የሚሰማ ጀሮ ያለው ይስማ:: +"+ (ማቴ. 11:7-15)

   <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
@Nigatu5
@Nigatu5
@Nigatu5