የጊንር ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
287 subscribers
885 photos
16 videos
12 files
19 links
ይህ ቻናል ዓላማውን የሰንበት ት/ ቤቱን ጠቃሚ መረጃዎች እና መልእክት ማስተላለፍ አድርጎ ጥር 19/2012ዓም ሌሊት 6:50 ላይ ተከፈተ፡፡
Download Telegram
This media is not supported in your browser
VIEW IN TELEGRAM
እስቲ ስለ ቅዳሴ ይችን አጭር ቅመም😘 የሆነች ትምህርት እንቅመሳት🙏
አዋጅ

አዋጅ! አዋጅ! አዋጅ! ያልሰማህ ስማ የሰማህ አሰማ።

ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ በጀኔራል ሥጋ ፈቃድ የሚመራ ሆድ በማለት የሚጠራውን ክፍለ ጦር አዝምቶ እየፎከረና እየደነፋ መጥቷል።

እናንተ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ቤተ ክርስቲያን እስካሁን አልበደለችንም አስቀይማንም አታውቅምና

ስለ ራሳችን ስለእህት ወንድሞቻችን ስለ ሀገራችን ኢትዮጵያ ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብላችሁ ይኽንን ጠላት ለመመከት ክተቱ ተብላችኋል!!!

ለጦርነቱ የሚሆናችሁን መሳሪያዎችን ከኤፌሶን ክፍለ ሃገር ከ6ኛው አውራጃ እየታጠቃችሁ እንድትዘምቱ ይሁን!!!

ዋናው ዘመቻ በመጋቢት 2 ነውና ነገ የካቲት 18 በነነዌ ከታችሁ እንድትገኙ!!!

ወስልታችሁ የቀራችሁ እንደሆነ ማርያምን! ኋላ ከንጉሣችን ጋር ትጣላላችሁ!!!

መልካም የነነዌ ፆም !!
#ጾመ_ነነዌ

#ነነዌ «ታላቋ ከተማ»

ነነዌ በጤግሮስ ወንዝ ዳርች በአሁኑ ኢራቅ አከባቢ የምትገኝ፤ በሃያሉ ናምሩድ የተመሰረተች የአሥራውያን ዋና ከተማ ነበረች (ዘፍ 10፡11)። በጊዜው ዓለም ላይ ከነበሩ ታላላቅ ከተሞች አንዷ የነበረች ነነዌ፤ ውብ ቅጥሮች ያሏት፣ ሃያላን ነገስታትን የማረከች፣ ብዙ መንግስታትን የተፈታተነች ነበረች። በሰሎሞን ልጅ በሮበዓም ዘመን ሰሜን (እስራኤል) እና ደቡብ (ይሁዳ) ተብላ ከሁለት በመከፈሏ ብርታት ያጣችውን የእስራኤልን መንግሥት ስትፈታተን እና ስትወጋም ትኖር ነበር።

ነነዌ 120ሺ ህዝብ የሚኖርባት የቅጥሯ ስፋት ወድ 12ኪ.ሜ ገደማ የሚሆን ከተማ ነበረች። ምንም እንኳን ነነዌ በዓለም ዘንድ ቁንጮ ብትሆንም፣ በእግአብሔር ዘንድ ግን ሃጢያቷ የበዛ፣ ከአምላክ መንገድ የወጣች፣ ተመዝናም ቀላ የተገኘች ነበርች። ሳይመክር ሳያስመክር የማይጣላዉ እግዚአብሔርም ቃሉን ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል ላከ፤ «ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፥ ክፉታቸውም ወደ ፊቴ ወጥቶአልና በእርስዋ ላይ ስበክ» አለ (ዮናስ 1፡1)።

#ከእግዜብሔር_የሸሸው_ነብይ

ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፤ አባቱም አማቴ ይባላል፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ከሞት ያስነሣው የሰራጵታዋ መበለት ሕፃንም፣ ይህ ልጅ እንደ ሆነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል (1ኛ ነገ 17፥19)፡፡ የዚህ ነብይ ስሙም «ዮናስ» ትርጓሜውም "ርግብ" ማለት ነው። የእግዚአብሔር ቃልም «ተነስተህ ወደ ነነዌ ሂድ፣ እንዲህም ብለህ ስበክ "ነነዌ እስከ ሶስት ቀን ትጠፋለች"» ሲል ወደሱ መጣ (ዮና 1፡1)። ዮናስ ግን «አንተ መሐሪ ነህ፣ በእሳቱ ፋንታ ምህረትን ብታወርድ፤ አንት መሐሪ፣ እኔ ደሞ ነቢየ ሐሰት እባላለው» ብሎ ከጌታ ፊት ሽሽት ጀመር።

ነብዩ ዳዊት «ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ? ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ ነህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ። እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥ በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች።» (መዝ 139፡7)። ያለውን እግዚአብሔር፤ ከደቂቀ ነብያት አንዱ የሆነው ዮናስ ግን እሱን ሽሽት ወድ ተርሴስ ኮበለለ። {ነብየ እግዚአብሔር ዮናስ ሆይ? ከእግዜር ወዴት ትሸሻለህ? ተርሴስ ከእግዜር ትሰውረሃለችን? በእግረ ዳዊት የተተካህ ነብይ ሆይ፣ ዳዊት «ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ ነህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ» ያለውን አላስተዋልክምን?}። ምንም እንኳን ነብዩ ከእግዜር ሽሽት ወደ ቴርሴስ በመርከብ ቢጓዝም፣ አምላክ ግን በዓሳ አንባሪ ሆድ ወደ ነነዌ ወሰደው። በዚህም በዓሳ አንባሪ ሆድ ዉስጥ ሶስት ቀን እና ሶስት ለሊት ቆይቶ ነነዌ ደረሰ። ይህም የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሶስት ቀን ሶስት ለሊት የመቃብር ስለመቆየቱ እና ከሙታን ተለይቶ ስለ መነሳቱ ምሳሌ ሆነን (ሉቃ 11፡30)።

#በሦስት_ቀን_ውስጥ_ነነዌ_ትገለበጣለች

ዮናስም የአንድ ቀን መንገድ ያህል ወደ ከተማይቱ ውስጥ ገባ፤ ጮኾም፦ «በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች» አለ (ዮናስ 3፡4)። እንዴት የሚጨንቅ፣ የሚከብድ ቃል ነው። የዮናስ ስብከት ምህረት የለውም፣ 'ንሰሃ ግቡ' ብሎ ለንሰሃ አይጋብዝም። እንድ ነብዩ ኤርሚያስ «ስለ ሕዝብ ስለ መንግሥትም እነቅል አፈርስም አጠፋም ዘንድ በተናገርሁ ጊዜ፥ ይህ ስለ እርሱ የተናገርሁበት ሕዝብ ከክፋቱ ቢመለስ፥ እኔ አደርግበት ዘንድ ካሰብሁት ክፉ ነገር እጸጸታለሁ» ብሎ ተስፋ የሚሰጥ ቃልም አይደለም።

የነነዌ ህዝብ ከአህዛብ ወገን ናቸው፣ ዮናስን አያቁትም የሱን አምላክ አያመልኩትም፤ ብቻ ለሃገሩ እንግዳ የሆን አንድ ዕብራዊ ወድ ከተማዋ ገብቶ «ነነዌ ትገለበጣለች» አለ። የነነዌ ሰዎች እንዴት በኛ ላይ ታሟርታለህ ብለው ዮናስን አልሰቀሉትም (አይሁድ ሊያድናቸው የመጣውን መሲህን ሰቅለውታልና)፣ በመጋዝም አልሰነጠቁትም (አይሁድ የእግዚአብሀሄርን የምህረት_ቃል ሊያቀብላቸው የመጣውን ልዑለ ቃል ኢሳያስን በመጋዝ ሰንጥቀውታልና)። የነነዌ ሰዎች እንደ ኖህ ዘመን ሰዎች በሀጥያት ውስጥ ሆነው የቀራቸውን ጊዜ አልቆጠሩም፣ ይልቁንም በደላቸውን ለመቁጠር ተፋጠኑ እንጂ።

#የምህረት_አዋጅ

ነነዌ ከቤት መንግስት እስከ ቤተ ከህነት፣ ከነጉስ እስከ አሽከር፣ ከልጅ እስከ አዋቂ፣ ከሰው እስከ እንስሳ ማቅ ለበሰች። ሃያላን መንግስታትን ያንበረከከች ነነዌ፣ በአንድ ዕባራዊ ተብረከረከች። ሊቁ ቀዱስ ኤፍሬም ሶርያዊው እንዲህ ይላል ‹‹የነነዌ ንጉሥ ወታደሮቹን ሰብስቦ እንዲህ አላቸውም፣ ይህ ድል እንደተጎናጸፍንባቸው ውጊያዎቻችን አይደለም ፤ ከባዕድ ሀገር በተሰማው ዜና ኃያላኖቻችን ሳይቀሩ ተብረክርከዋል ፤ አንድ ዕብራዊ መጥቶ በቃሉ አብረከረከን፡፡የጀግኖች እናት ነነዌ አንድን ለብቻው የመጣ ደካማ ሰው ቃል ፈርታለች፡፡ ስለዚህ ወገኖቼ ፤ የማይፈርስ አጥር እንገንባ ፤ ይህች አጥር ንስሓ ናት ፤ ሥውር ጦርነት ታውጆብናልና ራሳችንን ሥውር መሣሪያ እናድርግ››። ነነዌ ለሶስት ቀን ነሰሃ ገባች። እግዚአብሄርም በምህረት ከእሷ ተመለስ በነብዩ ኤርሚያስ እንደተናገረውም ሊያደርግባቸው ካሰበው ተጸጸተ።

#እኛስ?

ወገኖቼ! እኛስ? በደላችን ከነነዌ ሰዎች አልባሰምን? ክፋታችን በእግዚአብሄር ፊት አልወጣምን? እግዚአብሔርስ እንድ ዮናስ ነብይ አስነስቶ አልገሰጸንምን? እንደ ምህረቱ ባይሆን ኖሮ እንደ ስራችን ቢሆን ይሄኔ በእሳት አንጠፋም ነበር?

ወዳጆቼ እንደ ነነዌ ሰዎች፣ እኛም ማረን እንበለው፣ መሃሪ ነውና ይምረናል፣ በእንባ ወደሱ እንመለስ። የቀረንን ዘመን ሳይሆን በደላችንን እንቁጠር። የመዳን ቀን ዛሬ ነው ይላል መጽሐፍ፣ ዛሬን ወድሱ እንመለስ። ወዳጆቼ! ይሄን ጾም ነነዌ ስንጾም፣ በግብርም በህሊናም እነሱን እንምሰል።

📜በ፭ ኪሎ ግቢ ጉባኤ ትምህርት ክፍል ትምህርታዊ ሥነ-ጽሑፍ ንዑስ ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት 18, 2016
አዳራሽ - የምታዳርስ

አንዱ ችኩል እየሄደ መንታ መንገድ ላይ ደረሰ፤ በዚያም አንድን አዛውንት አገኘና ወደ አንድኛው መንገድ እያመለከተ "ይኼ መንገድ ያስኬዳል?" አላቸው። "አዎን" አሉት። መንገዱን መገስገስ ጀመረና ጥቂት እንደተጓዘ "ከዚያስ?" የሚለውን ለመጠየቅ መለስ ብሎ "አባቴ ከዚያስ?" አለ። "ከዚያ ወንዝ ታገኛለህ"አሉት "ከዚያስ?" አለ አሁንም። "ከዚያማ ወንዙ ይወስድሃል" አሉት።

መንገዱ ያስኬዳል ብቻ ሳይሆን 'የት ያደርሳልን?' መጠየቅ ይገባል። ወደ ፈለግነው ዓላማ ልታደርሰን የምትችለውን ትክክለኛ አዳራሽ መለየት ያስፈልጋል ካልሆነና ትክክለኛ ያልሆኑ አዳራሾች ጋር ከሆንን እኛ ልንደርስበት ካሰብነው መልሰው ወደ ጥፋት ሊያደርሱን ይችላሉ። ክፉ ባለእንጀርነት መልካሙን አመል እንደሚያጠፋ ክፉ አዳራሽም ከመልካሙ መዳረሻ ያጠፋል።

መጨረሻ ላይ የት መድረስ እንደሚፈልግ የማያውቅ ሰው ባገኘውና በተመቸው መንገድ ይሄዳል የትም ያድርሱት የት(እመቅም ያድርሱት መቀመቃት)  ካገኘው አዳራሽ ሁሉ ጋር ይጓዛል። መንገድ የመሰለው ሁሉ ለእርሱ መሄጃ ነው። ሉጋም እንደተደረገበት ፈረስ ማንም ወደ ፈለገው ይወስደዋል። ፍጻሜውም አያምርም።

አባቶቻችን መዳረሻቸውን አውቀው ነው የተጓዙት።
አብርሃም ወደ ሞሪያ ተራራ፣ ሙሴ ወደ ሲና ተራራ፣ ሎጥ ወደ ዞአር፣ ኤልያስ ወደ ኮሬብ ተራራ... ተጓዙ።

[ዘፍ፳፪፤ ዘፀ፫፤ ፴፩ ዘፍ፲፱፤ ፩ኛ ነገ፲፱]

ዛሬ በአማናዊቷ ዕፀ ሳቤቅ የተያዘ አማናዊው በግ ያለባት የኛዋ ሞርያ፤ ዘወትር ሐመልማል ከነበልባል ተዋህዶ የሚገለጥባት ህገወንጌል የተሰራባት ሲናችን፤ እንደሎጥ ከዓለሙ ጥፋት ሸሽተን የምናመልጥባት ዞአራችን፤ እንደ አከአብና ኤልዛቤል ሠራዊት ሆነው ከሚያሳድዱን አጋንንት የምናመልጥባት ኮሬባችን... ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ናት!

ወደዚህች መንፈሳዊት አውድ እንክርዳድ የማይገኝባት የስንዴ መሰብሰቢያ ወደሆነች የክርስቶስ ቅዱስ ሥጋው ክቡር ደሙ ወደ ሚሰጥባት ቤተ ክርስቲያን የምታደርሰንን አዳራሻችንን ለይተን ይሆን?

ሙሴ የእስራኤል አዳራሻቸው ነበር። እስራኤል ዘሥጋ ግን ብዙ ጊዜ ሙሴ ላይ አጉረመረሙ። አንዳንዶቹ ከሙሴ ይልቅ ዳታን፣ አቤሮን፣ ቆሬ የመሳሰሉ እኛም አዳራሽ ነን ባዮችን በመምረጥ ከመዳረሻቸው ሲናጠቡ ተመልክተናል።
[ዘኁ፲፮፤ ይሁ፩፥፲፩ ]

እኛም ወደ ቤተ መቅደሱ የምታደርሰንን ትክክለኛዋን አዳራሽ እንወቅ። በልዩ ልዩ የተንኮለኞች ወሬ ተታለን ከአዳራሻችን አንለይ። ፊልጶስ ናትናኤልን እንዳደረሰ ወደ ቤተ መቅደስ ከፍታ የምታደርሰን አዳራሻችን ጽጌ ተዋህዶ ናት!

ሲደክመን እያበረታች፣ ስንዝል እየደገፈች፣ ስንወድቅ እያነሳች፣ ወደ ቤተ መቅደሱ የምታደርሰን እውነተኛዋ አዳራሻችን ናትና ከእርሷ ጋር እንጓዝ።  እርሷ[ጽጌ ተዋህዶ] በተግባር የተፈተነች በፍሬዋም የታወቀች እውነተኛ አዳራሽ ናት። ብዙዎችን ወደ መቅደሱ አድርሳ ከእግዚአብሔር ጋር እንዳገናኘች ከታላላቆቻችን እንደሰማን እንዲሁ እኛም አይተናልና የሰማነውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን!

"ቤተ ክርስቲያንን ባንረዳትም(ረ-ይላላል) እንረዳት(ረ-ይጠብቃ)" እንዲል መ/ር ጥጋቡ እንደሻው። ጽጌ ተዋህዶንም እንረዳት እርሷ አዳራሽ ናት እንጂ መኖሪያ እንዳልሆነች እናስተውል። ስለዚህ ከአዳራሿ ደርሰን የጨረስን መስሎን ከቅድስቱ ሳንደርስ ከመንገድ እንዳንቀር።

ወደ ቅድስቱ ልታቀርበን ትጓጓለችና እስከ መጨረሻው አብረናት ተጉዘን ወደ ቅድስቲቱ እንግባ።

ከአዳራሻችን ጽጌ ተዋህዶ ጋር መልካም ጉዞ ተመኘን!!!
የጊንር ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
<unknown> – _ኖላዊነ_ሔር____ዘማሪ_ቀሲስ_እስክንድር_ወልደ_ማርያም(256k)
ኖላዊነ ሄር መድኃኔዓለም
ለነፍስ ወለሥጋ ወለኩሉ ዓለም
ዕቀበነ (*፫) ለዓለመ ዓለም
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ድምጼን ይለዩታል በጎቼ በሙሉ
እንዳያስታችሁ መንገደኛ ሁሉ
በራሱ በአምላክ የተባለላችሁ
በጎች ተሰብሰቡ ወደ በረታችሁ
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ነቢይ ነኝ የሚል የሠፈር ዜናዊ
አድርጎ የሾመ ራሱን ወንጌላዊ
ነጣቂ ተኩላው ተበራክቷልና
መንጋህን ጠብቀው በእምነት እንዲፀና
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ከአምላክ የተላከ እውነተኛ እረኛ
ለመንጋው የሚያስብ ያይደለ ምንደኛ
ፊት የተማረ ነው ኋላም የተሾመ
በሐዋርያዊ ክህነት በእውነት የታተመ
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ከጌታ የመጣ ካልሆነ ክህነቱ
ከአበው የተለየ ከሆነ ትምህርቱ
በበሩ ያልገባ ሌባ ነው ስላለ
ምዕመናን አትስሙት አሳቹ ስላለ
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ጩኸታችን ሰምተህ ጭንቀታችን አይተህ
በየዘመናችን የሚታደግ ልከህ
ለእውነተኛው መምህር የበጎች እረኛ
አንተው አሰማራን ተመልከት ወደኛ
✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
ኖላዊነ ሄር መድኃኔዓለም
ለነፍስ ወለሥጋ ወለኩሉ ዓለም
ዕቀበነ (*፫) ለዓለመ ዓለም

[ለነፍስ ለሥጋ ለዓለም ሁሉ ቸር ጠባቂ መድኃኔዓለም  ለዘለዓለሙ ጠብቀን]

✥✥✥   ✥✥✥  ✥✥✥
የነፍሳችንን ቁስለ የምትፈውስ የሥጋ ፈቃዳችንን ዝም የምታሰኝልን ለወጣቶች ጽሙናን የምታስተምረን የጸሎት እናቷ የዝምታ እህት የመልካም ምግባራት ሁሉ ምንጭ #ጾም እነሆ ደረሰችልን። በመልካም እንቀበላት።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይለናል

"ሙሽሪቱን በሰርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች አስቀድመው ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይጠርጉታል፤ የቆሸሸ ልብስን የለበሰ ሰው ወደ ሰርጉ አዳራሽ እንዳይገባ ያደርጉታል፤ ወደ አዳራሹ መግባት የሚችለው የሰርግ ልብስ የለበሰ ሰው ብቻ ነው፤ እናንተም እንዲህ ልታደርጉ ይገባችኋል፡- ልቡናችሁን በማንጻት፣ አብዝቶ ከመብላትና ራስን ካለመግዛት በመራቅ የምግባር እናት፣ የማስተዋልና የሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ደጀ ልቡናችሁን በመክፈት ልትቀበሏት ይገባችኋል፤ ይህን ያደረጋችሁ እንደ ኾነ ታላቅ ሐሴት ታደርጋላችሁ፤ እርስዋም ቁስለ ነፍሳችሁን ትፈውስላችኋለች"


ጾመን ለመጠቀም ያብቃን።
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ጾም ቀዳማዊ ትዕዛዝ ናት [ዘፍ፪፥፲፮] ይህቺ ቀዳማዊት ትዕዛዝ ህይወታቸው ሙሉ የጾም ህይወት ከሆነ ከመላእክት ጋር የምታስተባብረን አንድ የምታደርገን ናት! በእርግጥ የክርስቲያኖች የመጨረሻ ሕይወትም  እንደመላእክት ያለ ነው። [ማቴ፳፪፥፴] 

ጾም፦ ሙሴ ህግን ተቀብሎባታል [ዘፀ፴፬፥፳፰ ] ፤ የነነዌ ሕዝቦች ታወጀባቸውን መቅሰፍት አስመልሰውባታል [ዮና፫፥፯-፲]፤ አይሁድ በሐማ ተንኮል ከተሴረባቸው የሞት ሴራ ተርፈውባታል [አስቴር ፬፥፲፮ ] ፤ ዳንኤልና ሠለስቱ ደቂቅ ሕይወታቸው አድርገዋት የጥበብ ባለቤቶች ሆነውባታል [ዳን ፩፥፰ ፤ ፲፥፫]፤... ያለ ጾም የኖረ ነቢይ የለም!

እስራኤል የጾም ወራታቸውን የደስታ በዓል አድርገው አክብረዋል [ዘካ፰፥፲፱ ]

✥ ጌታችን ሐዋርያት እንደሚጾሙ ነግሮናል[ማቴ፱፥፲፭]፤ ሲጾሙም አይተናል [ሐዋ፲፫፥፪ ]፤ የጾም ወራትም በሐዋርያት ዘንድ የታወቀ ነው [ሐዋ፳፯፥፱]

ጾም በነቢያትም በሐዋርያትም የተኖረች ሕይወት ናት!

✥ጌታችን በተራራው ስብከቱ ስለጾም ሲናገር "ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ብሎ እንዴት መጾም እንዳለብን ነገረን። [ማቴ ፮፥፲፮] ይኽም ጾም ያስፈልጋል አያስፈልግም ከሚል ጥያቄ ማለፍ እንዳለብን ያመለክተናል።

✥ እኛ ክርስቲያኖች ጾም ያስፈልጋል አያስፈልግም ከሚለው አልፈን ስንጾም እንዴት እንጹም የሚለው ላይ እናተኩራለን፦
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም ከምግብ እንከለከላለን

✥ በጾማችን ወራት ለተወሰኑ ሰዓታት ከሁሉም ምግብ እንከለከላለን፤ የጾሙ ወራት እስኪያልፍ ደግሞ ከጥሉላት መብሎች እንከለከላለን።

✥ የጾማችን ወራት እስኪያልፍ በምግብ ጊዜ ጾሙን የምናልፍበት ማለፊያ እንጀራን እንመገባለን። የበረቱት ግን ይህንንም በመተው ጾምን ጀምረው ይፈጽሟታል [ዳን፲፥፫ ]

✥✥✥   ✥✥✥   ✥✥✥   ✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም በሃይማኖት ሆነን እንጾማለን

"አሚንሰ መሠረት ይእቲ ወካልዓኒ ህንጻ ወንድቅ እሙንቱ" እንዲል ዮሐንስ አፈወርቅ የሁሉም ነገር መሠረት ሃይማኖት ነው።

✥ ሃይማኖት ያለው ምግባር ከሌለው ከንቱ እንደሆነ ምግባር ያለውም ሃይማኖት ከሌለው ከንቱ ነው። [ያዕ፪፥፲፬]

✥ የዓቢይ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት የሚያስረዳንም ይህንኑ ነው - #ዘወረደ!

✥ እነየንታ ቅዱስ ያሬድን አብነት አድርገው "ዘወረደ እም ላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ - ከላይ የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት" በማለት ነገረ ክርስቶስን ይሰብኩናል።

✥ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በቅዳሴ ላይ የምታነብልን ወንጌል " ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው።"ይላል [ዮሐ ፫፥፲፫]

✥ እኛ ታላቁን ጾማችንን የምንጀምረው ይኽንን እየመሠከርን ነው 'ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም'!

"ምነው እነ ሄኖክ እነ ኤልያስ ወደ ሰማይ ወጥተው የለምን?" የሚለን ካለ እነሱ መች ከሰማይ ወረዱ? እንለዋለን። ደግሞስ ወደ ብሔረ ሕያዋን ተወሰዱ እንጂ መች ወደ ዘባነ ኪሩብ ወጡ? ቢወጡ ቢወጡ ወደ ጸጋ አምላክነት እንጂ[ዘፀ፯፥፩ መዝ፹፩(፹፪)፥፮ ] መች ወደ ባሕርይ አምላክነት ወጡ?

እግዚአብሔር ወልድ ከአምላክነቱ ሳይለይ ከሰማይ ወረደ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ፍጹም ሰው ሆነ[ዮሐ፩፥፲፬] ሰው በሆነ ጊዜም ከአምላክነቱ ያልተለየ እርሱ እግዚአብሔር ነው

ከእመቤታችን የተወለደው እርሱ በእርሷ ማህጸን በድንግልና ሰው ሆኖ የተጸነሰው ነው[ማቴ፩፥፳፫ ]።

በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ያየነው በባሕርይ አባቱ የባሕርይ ልጅነቱ የተመሰከረለት እርሱ[ማቴ፫፥፲፯] ከእመቤታችን በድንግልና የተወለደው ነው።

በመስቀል ላይ አይሁድ የሰቀሉት እርሱ[ማር፲፭፥፳፬] በዮርዳኖስ የተጠመቀው ነው።

ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በገዛ ሥልጣኑ የለየው እርሱ[ሉቃ፳፫፥፵፮] አይሁድ በመስቀል ላይ የሰቀሉት ነው።

ዮሴፍ እና ኒቆዲሞስ ገንዘው የቀበሩት እርሱ[ማቴ፳፯፥፷] በመስቀል ላይ በፈቃዱ የሞተው ነው።

ከህቱም መቃብር የተነሳው እርሱ[ሉቃ፳፬፥፭] በአዲስ መቃብር የተቀበረው ነው።

ወደ ሰማይ ሲወጣ ያየነው እርሱ[ሐዋ፩፥፱] በራሱ ሥልጣን ከሙታን የተነሳው ቀድሞ ከሰማይ የወረደው ነው።

ስለዚህም ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም!

ከሰማይ የወረደው አማላጅ አይደለምና ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ክርስቶስ አማላጅ አይደለም

ከሰማይ የወረደው ነቢይ ስላይደለ ወደ ሰማይ የወጣው እርሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢይ አይደለም።

ከሰማይ የወረደው እግዚአብሔር ነውና ወደሰማይ የወጣው ኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት እግዚአብሔር ነው።

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ሐዋርያት አድርጋ የሾመችው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳስተማረን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር ስንለው አለን በዚሁ ጸንተን እንኖራለን [ማቴ፲፮፥፲፮  ሐዋ፰፥፴፯ ]

ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽማ በተሰጠች በዚህች ሃይማኖት ሆነን ቅድስናንን እንጠባበቃለን።

ለቅድስቱ ያብቃን.....።
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
🙏ጸሎተ ምህላ ዘጽጌ ተዋህዶ🙏
👉ጸሎተ ዘወትር
👉64- ጊዜ በእንተ እግዝእትነ ማርያም መሀረነ ክርስቶስ [ስለ እመቤታችን ማርያም ብለህ ክርስቶስ ሆይ ማረን] እያሉ መስገድ
👉ውዳሴ ማርያም
✞አቡነ ዘበሰማያት [አባታችን ሆይ]
👉ውዳሴ አምላክ
✞አቡነ ዘበሰማያት [አባታችን ሆይ]
👉41- ጊዜ እግዚኦ መሀረነ ክርስቶስ [አቤቱ ክርስቶስ ሆይ ማረን] እያሉ መስገድ
👉መዝሙረ ዳዊት [አምስት አምስት ምእራፍ አድርሰው መጨረሻ ላይ መዝ 135'ን በጋራ ማድረስ]
👉እግዚኦታ ይደርሳል[ይህ በካህን የሚመራ ነውና ወደሚቀጥለው ይሻገሩ]
✞አቡነ ዘበሰማያት [አባታችን ሆይ]
👉አቤቱ ማረን[ከስግደት ጋር ማድረስ]
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ ስምህ ብለህ-------- ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ እናትህ ብለህ--------ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ መላእክት ብለህ ----- ከጥፋት አድንን
ስለ ሚካኤል ብለህ ------ ከጥፋት አድነን
ስለ ገብርኤል ብለህ ----- ከጥፋት አድነን
ስለ ሩፋኤል ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ ዑራኤል ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ ራጉኤል ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ ፋኑኤል ብለህ -------- ከጥፋት አድነን
ስለ ሳቁኤል ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ ነቢያት ብለህ --------- ከጥፋት አድነን
ስለ ሐዋርያት ብለህ ----- ከጥፋት አድነን
ስለ ሰማዕታት ብለህ ----- ከጥፋት አድነን
ስለ ቅዱሳን ብለህ -------- ከጥፋት አድነን
ስለ ጻድቃን ብለህ -------- ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ ዳዊት ብለህ ---------- ከጥፋት አድነን
ስለ ዮሐንስ ብለህ --------- ከጥፋት አድነን
ስለ ጊዮርጊስ ብለህ ------ ከጥፋት አድነን
ስለ ተክለሃይማኖት ብለህ -- ከጥፋት አድነን
ስለ አቡዬ ብለህ ---------- ከጥፋት አድነን
ስለ ገብረክርስቶስ ብለህ -- ከጥፋት አድነን
ስለ ክርስቶስሠምራ ብለህ-- ከጥፋት አድነን
ስለ አርሴማ ብለህ ----- ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ እናትህ ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ ድንግል ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ ማርያም ብለህ ------- ከጥፋት አድነን
ስለ አዛኝቷ ብለህ -------- ከጥፋት አድነን
ስለ ኪዳነምህረት ብለህ-- ከጥፋት አድነን
#አቤቱ_ማረን---------ይቅር በለን (*2)
ስለ ስምህ ብለህ -------- ከጥፋት አድነን
ስለ ቃልህ ብለህ ---------- ከጥፋት አድነን
ስለ መስቀልህ ብለህ ---- ከጥፋት አድነን
👉እንደቸርነትህ
👉አባታችን ሆይ
ትምህርተ ወንጌል [በዚህ ፈንታ ቅዱሳት መጻህፍትን አንብቡ]
____✞✞_________✞✞________
👉ሁላችንም ከቤተ ሰቦቻችን ጋራ በየቤታችን እንዳናስታጉል ትላለች ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ከሳምንት የቀጠለ]➥
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም ጾማችንን በመቀደስ ነው

በዘወረደ "ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም" ብሎ ሃይማኖትን ሰብኮን ተቀነዩ ለእግዚአብሔር በፍርሃት - ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ[ምስባክ መዝ ፪፥፲፩] እያለ የሚመክረን ዓቢይ ጾም በሁለተኛው ሳምንት ስለ መቀደስ ይነግረናል- #ቅድስት!

❖ በዘወረደ ያልጀመረ ቅድስት፣ ቅድስት ያልተከተለው ዘወረደ እንደሌለ ሃይማኖት እንበለ ምግባር፣ ምግባር እንበለ ሃይማኖት ህልው አይሆንም ምውት ነው! አይጠቅምም [ያዕ ፪፥፲፬]

❖ የቅ/ዮሐንስ መጥምቅ ደቀ መዛሙርት የነበሩት ቅ/ዮሐንስ[ወንጌላዊ] እና ቅ/እንድርያስ ጌታችንን "አይቴ ተኃድር? - በየት ታድራለህ?" ብለው ጠየቁት። ጌታም "ንዑ ትርአዩ- ኑና እዩ" ማለት እመኑብኝ በሚያምንብኝ ሰውነት አድራለሁ አላቸው። "ወሖሩ ወርእዩ - ሄዱና አዩ" ማለት አመኑ። ከዚህ በኋላ "ወወአሉ ኀቤሁ እስከ ዓሥሩ ሰዓት" ይላል እስከ አሥረኛው መዓርገ ቅድስና ደረሱ ሲል [ዮሐ፩፥፴፰-፴፱ ትርጓሜ ተመልከት] በሃይማኖት የተከተለ በቅድስና ይውላል!

❖ ቸሩ እግዚአብሔር በባሕርይው ቅዱስ ሆኖ ሳለ እኛን ቅዱሳን ሁኑ ይለናል [ዘሌ፲፱፥፪]
❖ በምናችን ነው የምንቀደሰው የምንል ከሆነ ቅ/ጴጥሮስ እንዲህ ይለናል
" እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ #በኑሮአችሁ_ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ" ፩ኛ ጴጥ፩፥፲፭-፲፮

❖ የኛ የክርስቲያኖች ኑሮአችን ሁሉ ለእግዚአብሔር የተለየ [የተቀደሰ] ሊሆን ይገባዋል ይኸውም ሁል ጊዜ በሁሉም ቦታ በሀሳባችን፣ በንግግራችን፣ በተግባራችንም ነው

ለዚህ ደግሞ ዘወትር መታገል ሥጋንም መጎሰም ያስፈልጋል።

ከቅድስና ተለይተን እንዳንጣል ሥጋችንን እየጎሰምን ከምናስገዛበት መሣሪያዎች ዋነኛዋ ጾም ናት! [፩ኛ ቆሮ፱፥፳፯]

❖ ለጸሎት እናት ለአርምሞ እህት ለመልካም ሁሉ ምግባራት ምንጭ የሆነች ይህቺ ጾም ወደ ቅድስና እንድትመራን ልንቀድሳት ይገባናል
" በጽዮን መለከትን ንፉ፥ #ጾምንም_ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ" እንዲል ኢዮኤል ፪፥፲፭

❖ ጌታችን እንደነገረን ጾማችን ከግብዞች ጾም መለየት[መቀደስ] አለበት [ማቴ፮፥፲፮]

ብዙዎች መጾምን ይጾማሉ የጾማቸው ዓላማ ግን ይለያያል
● ለግብዝነት የሚጾሙ አሉ [ማቴ፮፥፲፮]
● ሰውን ለመግደል ብለው የሚጾሙ አሉ [ሐዋ ፳፫፥፲፬]
● በጤና ማጣት ምክንያት ተገደው የሚጾሙ አሉ
● ለሥጋዊ ውበታቸው ብለው የሚጾሙ እንዳሉም ግልጥ ነው

የእኛ ጾም ለግብዝነት ያይደለ ለትህትና፣ ለመግደል ያይደለ ለማዳን፣ ተገደን ያይደለ ወደን፣ ለሥጋዊ ያይደለ ለነፍሳዊ ውበታችን ሊሆን ይገባል

ደግሞም ሆዳችንን ከምግብ ማጾም ብቻ ሳይሆን ቅዱስ ያሬድ እንዳስተማረን በዓይናችን ክፉ ከማየት በጆሮአችን ክፉ ከመስማት፣ በአንደበታችንም ክፉ ከመናገር መጾም ይገባል

❖ ይህ ካልሆነ "እኔ የመረጥሁት ጾም ይኽ ነውን?" የሚል ተግሳጽ ይከተለናል

❖ ጾማችንን በሚገባ ቀድሰን የጾምነው እንደሆነ "ዘጾመ ወጸለየ ወሰአለ እሙነ ይነስዕ እሴቶ - የጾመ የጸለየ የለመነ በእውነት ዋጋውን ይቀበላል" እንዲል በጎ ዋጋችንን እንቀበላለን

❖ ያን ጊዜ ብርሃናችን እንደ ንጋት ያበራል...ያን ጊዜ እንጣራለን እግዚአብሔርም ይሰማናል... ጨለማችን እንደ ቀትር ይሆናል፤... እግዚአብሔር ሁል ጊዜ ይመራለናል፤... እንደሚጠጣ ገነት ውኃውም እንደማያቋርጥ ምንጭ እንሆናለን፤... ከድሮ ዘመን ጀምሮ የፈረሱት ሥራዎች ይሠራሉ፤.... እኛም ሰባራውን ጠጋኝ የመኖሪያ መንገድን አዳሽ እንባላለን [ኢሳ፶፰፥፭-፲፪]

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

በሃይማኖት መሠረትነት [ዘወረደ] ጸንተን በኑሮአችን ተቀድሰን [ቅድስት] ከተነኘን የጌታችንን ትምህርት እያደመጥን፣ ቤተ መቅደሱን ሲያጸዳ እየተመለከትን በአማናዊቷ ምኩራብ እንኖራለን - ለአማናዊቷ ሙክራብ የበቃን ያድርገን! ይቆየን!
ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት
አመራሮች ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር በወቅታዊ
የቤተክርስቲያን ጉዳይ ዙሪያ ተወያዩ
*
***

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ማደራጃ መምሪያ ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት አመራሮች በቤተክርስቲያናችን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከቋሚ ሲኖዶስ ጋር ውይይት አደረጉ።

በውይይቱ ወቅት የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነቱ አመራሮች የቤተክርስቲያናችንን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ጥቅል ጥናታዊ ሰነድ ከመፍትሔ አቅጣጫ ጭምር ያቀረቡ ሲሆን ያቀረቡት ሰነድ በዝርዝር ተዘጋጅቶ፣
በማስረጃና በመረጃ ዳብሮ ችግሮቹን ደረጃ በደረጃ መፍታት በሚያስችል አግባብ እንዲቀርብ ቋሚ ሲኖዶስ አቅጣጫ ሰጥቷል።

ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት አመራሮቹም ለቋሚ ሲኖዶስ ያቀረቡት ሰነድ ሁኔታዎችን ለማመላከት እንጂ ያለቀለት ሰነድ እንዳልሆነ ገልጸው ዝርዝር ጥናቱን፣የጥፋቱን መጠን፣ባለቤቱንና የመፍትሔ አቅጣጫዎቹን የሚያመለክት ዝርዝር ሰነድ በማዘጋጀት እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል።

በውይይቱ ወቅትም ከቋሚ ሲኖዶስ አባላት ጥያቄና አስተያየት ተሰጥቶ ከሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤት አንድነት አመራሮቹ ምላሽ ተሰጥቶበታል።

ምንጭ: የ/ኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ