መዝገበ ቅዱሳን
20.7K subscribers
1.92K photos
9 videos
6 files
24 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
#አባ_ጋልዮን_መስተጋድል

በዚችም ቀን ዳግመኛ ተጋዳይ አባ ጋልዩን አረፈ። ይህም በቀንና በሌሊት ለጸሎት የማይታክት ተጋዳይ ሆነ ጐልማሳ ሁኖ ሳለ ከመነኰሰም ጀምሮ እስከ ሸመገለ ድረስ ከበአቱ ቅጽር ውጭ አልወጣም ከማኅበር ጸሎት ጊዜ በቀር ከመነኰሳቱ ማንም አያየውም።

ሰይጣናትም ተጋድሎውን በአዩ ጊዜ መነኰሳትን ተመስለው ወደርሱ በመንፈቀ ሌሊት ገብተው እንዲህ አሉት። እኛ ተሠውረን የምንኖር ገዳማውያን ነን ከእኛ አንዱ በሞት ስለተለየ ከእኛ ጋራ ልንወስድህ ወደን ወዳንተ መጣን ለእርሱም ቃላቸው እውነት መስሎት ልብስና ሲሳይ ወደማይገኝበት ጠፍ ወደ ሆነ ተራራ ላይ እስከ አደረሱት ድረስ አብሮአቸው ሔደ።

ሲጠቃቀሱበትም በአየ ጊዜ ሰይጣናት መሆናቸውን አውቆ በላያቸው በመስቀል ምልክት በአማተበ ጊዜ ተበተኑ። በሚመለስም ጊዜ በወዲያም በወዲህም መንገድ አጣ የክብር ባለቤት ወደሆነ ጌታችን ጸለየ ከዚህ በኋላ ከአንዱ ገዳም ወደ አንዱ ገዳም የሚዘዋወሩ ከአባ ሲኖዳ ገዳም የሆኑ መነኰሳት ተገለጹለት። እነርሱም የዳዊትን መዝሙር ያነቡ ነበር ስለ ሥራው ጠየቁት በእርሱ ላይ የደረሰውን ሁሉ በነገራቸው ጊዜ ከእርሳቸው ጋራ ወስደውት በፀሐይ የበሰለ ዓሣ እየተመገበ ከእሳቸው ጋራ አንዲት ዓመት ሙሉ ኖረ።

ያመነኰሰው መምህሩ አባ ይስሐቅም ወሬውን በአጣ ጊዜ ፊቱን ያሳየው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። አባ ጋልዮንም በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ወደ ርሱ መጣ አባ ይስሐቅም በአየው ጊዜ በእርሱ ደስ አለው ወዴት ነበርክ አለው እርሱም ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ነገረው።

ከዚህም በኃላ የሚያርፍበት ጊዜ ደርሶ በሰላም አረፈ መነኰሳቱም በክብር ቀበሩት።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ነሐሴ_19

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ በዚች ቀን የታላቁ #አባ_መቃርስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ የደግነት የምጽዋት የፍቅር አባት የሆነው #ደጉ_አብርሃም ጣዖት የሰበረበት፣ የአልዓዛር ልጅ #የቅዱስ_ፊንሐስ መታሰቢያው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ቅዱስ_መቃርስ

ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሳስዊር ከሚባል አገር ወደ አስቄጥስ ገዳም የታላቁ አባ መቃርስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ።

ከዕረፍቱ በኋላ ከሀገሩ ከሳስዊር ሰዎች መጥተው ሥጋውን ሰርቀው ወደ ሀገራቸው ወሰዱት ቤተ ክርስቲያንም ሠርተውለት ሥጋውን በዚያ አኖሩት እስላሞች እስከ ነገሡበት ዘመንም በዚያ ኖረ።

ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ ቦታ አፍልሰውት በዚያም ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት። ለአባ መቃርስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ አባ ዮሐንስ እስከ ተሾመበት ዘመን ኖረ።

ሊቀ ጳጳሳቱም የከበረች ጾመ አርብዓን ሊጾም ወደ አባ መቃርስ ገዳም በወጣ ጊዜ ፈጽሞ አለቀሰ እንዲህም ብሎ ጸለየ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የከበረ የአባ መቃርስ ሥጋ በዚህ ገዳም በመካከላችን ይሆን ዘንድ እንድትረዳኝ እመኛለሁ።

ከጥቂት ቀኖችም በኋላ አባ ሚካኤል ሔደ ከእርሱ ጋራም ስለ ገዳሙ አገልግሎት አረጋውያን መነኰሳት አሉ ልቦናቸውም በመንፈሳዊ ሁከት ተነሣሥቶ ያመጡት ዘንድ የአባ መቃርስ ሥጋ ወደ አለበት ቦታ ደረሱ።

የአገር ሰዎችም በአዩአቸው ጊዜ በትሮቻቸውንና ሰይፎቻቸውን በመያዝ ከመኰንናቸው ጋራ ተሰብስበው ከለከሏቸው። በዚያቺም ሌሊት በልባቸው ፈጽሞ እያዘኑ አደሩ። አባ መቃርስም በዚያች ሌሊት ለመኰንኑ በራእይ ተገለጠለትና ከልጆቼ ጋራ መሔድን ለምን ትከለክለኛለህ እንግዲህስ ተወኝ ከእሳቸው ጋራ ወደ ቦታዬ ልሒድ አለው።

ያ መኰንንም በጥዋት ተነሣ እየፈራና እየተንቀጠቀጠ የከበሩ አረጋውያን መነኰሳትን ጠርቶ የከበረ የአባ መቃርስን ሥጋ ሰጣቸው። እነርሱም ደስ ብሏቸው ተቀበሉት በመርከብም ተሳፍረው ተርኑጥ ወደሚባል አገር ደረሱ ከእርሳቸውም ጋራ የሚሸኙአቸው ከየአገሩ የመጡ ብዙ ሕዝቦች ነበሩ። በዚያችም ሌሊት በዚያ አደሩ ጸሎትንም አደረጉ ቀድሰውም ለሕዝቡ ሥጋውንና ደሙን አቀበሉ።

ከዚህም በኋላ ተሸክመው ወደ ገዳም ተጓዙ ሲጓዙም ከበረሀው እኵሌታ ደርሰው ከድካማቸው ጥቂት ሊአርፉ ወደዱ። አባ ሚካኤልም የከበረ የአባታችን የአባ መቃርስን ሥጋ የምናሳርፍበትን እግዚአብሔር እስከ ገለጠልን ድረስ እንደማናርፍ ሕያው እግዚአብሔርን ብሎ ማለ።

ከዚህም በኋላ የከበረ የአባ መቃርስን ሥጋ የተሸከመ ገመል ወደ አንድ ቦታ ደርሶ በዚያ በረክ አለ። የከበረ የአባ መቃርስ ሥጋ ያለበትንም ሣጥን ይጥል ዘንድ በራሱ ወዲያና ወዲህ ይዞር ጀመረ። አረጋውያን መነኰሳትም እግዚአብሔር የፈቀደው ያ ቦታ እንደሆነ አወቁ እጅግም አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ያም ቦታ እስከ ዛሬ የታወቀ ነው።

ወደ ገዳሙም በቀረቡ ጊዜ መነኰሳቱ ሁሉም ወጡ ወንጌልና መስቀሎችን ይዘው መብራቶችን እያበሩ እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን እስከ አስገቡት ድረስ በታላቅ ክብር በራሳቸው ተሸክመው ወሰዱት።

እግዚአብሔርም በዚያች ሌሊት ተአምራትን አደረገ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አበ_ብዙሃን_ቅዱስ_አብርሃም

በዚህችም ቀን የሃይማኖት የደግነት የምጽዋት የፍቅር አባት የሆነው ደጉ አብርሃም ጣዖት የሰበረበት እለት ይታሠባል።

በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የአብርሃም አባቱ ታራ ጣዖትን ይጠርብና ይሸጥ ነበር። ሽጦ ገንዘብ የሚያመጣለት ደግሞ ልጁ አብርሃም ነበር። በዚያ ወራት አብርሃም እውነተኛውን አምላክ ፍለጋ ገብቶ ነበር። አንድ ቀን ጣዖቱን ሊሸጥ ወደ ገበያ እየሔደ የተሸከመውን እንጨት ይመራመረው ገባ። "አሁን ይሔ ምኑ ነው አምላክ!" እያለም ያደንቅ ገባ። መንገድ ላይም ደክሞት ካረፈበት "ለምን አልጠይቀውም" በሚል አናገረው።

"እርቦኛል አብላኝ" አለው:: መልስ የለም:: "እሺ አጠጣኝ" አለው:: አሁንም ያው ነው:: "ባይሆን እሺ አጫውተኝ" አለው:: ጣዖቱ ተራ እንጨት ነውና መልሱ ዝምታ ነበር:: ከዚያ ተነስቶ ወደ ገበያው ሲደርስ "ዐይን እያለው የማያይ: ጀሮ እያለው የማይሰማ አምላክ የሚገዛ" እያለ ይጮህ ጀመር::

ይህን ሲሰሙ አንዳንዶቹ "የታራ ልጅ አብዶ" ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ "እሱ ያቀለለውን ማን ይገዛዋል" ብለውት ሔደዋል:: ከገበያ ሲመለስም ጣዖቱን ተመልክቶ አብርሃም እንዲህ አለ:: "አንተ ቀድሞውን በዕለተ ሠሉስ የተፈጠርክ ዕፅ ነህ" ብሎ ሰባበረው።

ወደ ቤቱ ሲመለስም ሁሉንም ጣዖታት ሠባበራቸው:: ይህ የተደረገው ከ2,000 ዓመታት በፊት በዚህች ቀን ነው። የመንግስተ ሰማያት አበጋዝ የእግዚአብሔር ወዳጅ አባታችን አብርሃም በመጨረሻው በውሃ፣ በነፋስ፣ በእሳትና በፀሐይ ተመራምሮ ፈጣሪውን አግኝቷል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ፊንሐስ_ካህን

በዚህች ቀን የአልዓዛር ልጅ የፊንሐስ መታሰቢያው ነው። ካህኑ ፊንሐስ የብሉይ ኪዳን ዘመን አገልጋይ: ከነገደ ሌዊ: የሊቀ ካህናቱ የአሮን የልጅ ልጅ ነው:: አባቱም ሊቀ ካህናቱ አልዓዛር ነው:: ፊንሐስ እሥራኤል ከግብጽ ሲወጡ ሕጻን የነበረ ሲሆን አድጐ በመጀመሪያ ካህን፤ አባቱ አልዓዛርና አያቱ አሮን ሲያርፉ ደግሞ ሊቀ ካህንነትን ተሹሟል::

አንድ ቀን በጠንቅዋዩ በበለዓም ክፉ ምክር እሥራኤላውያን ከሞዐብ ሴቶች ጋር በኃጢአት በመሳተፋቸው እግዚአብሔር ተቆጥቶ ነበር:: ያጠፋቸው ዘንድም መቅሰፍት ተጀምሮ ሳለ ፊንሐስ ወንድና ሴት: በደብተራ ኦሪቱ አንጻር የማይገባውን ሲሠሩ አያቸው::

ለፈጣሪው ቀንቶ በአንድ ጦር ሁለቱንም በአንድ ላይ ጥሏቸዋል:: ያን ጊዜ ጌታ "አስተንፈስካ ለነፍስየ" ብሎታል:: መቅሰፍቱም ተከልክሏል:: በዚህም ምክንያት ካህኑ ፊንሐስ የ300 ዓመት ዕድሜ ተጨምሮለት: እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: (ዘኁ. 25፥7, መዝ. 105፥30)

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ አባቶቻችን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ነሐሴ_20

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሃያ በዚች ቀን መጻሕፍትን የተረጐመ #አባ_ሰላማ አረፈ፣ በከሀዲው ንጉሥ ዳኬዎስ ዘመን የነበሩ ከኤፌሶን ሀገር #ቅዱሳን_ሰባቱ_ደቂቅ አረፉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ሰላማ_ካልዕ (#መተርጉም)

ነሐሴ ሃያ በዚች ቀን መጻሕፍትን የተረጐመ አባ ሰላማ አረፈ።

እኒህ ታላቅ ደግ ሰው የነበሩት በሃገራችን ኢትዮዽያ ከ1340 እስከ 1380 ዓ/ም ነው:: በትውልድ ግብጻዊ ቢሆኑም ለኢትዮዽያ ቤተ ክርስቲያን ብዙ ውለታን ውለዋል:: በዘመኑ ዻዻስ ሁነው ቢመጡም እንደ ሌሎቹ ዻዻሳት በቤተ መንግስት አካባቢ ሥራ ፈትተው መቀመጥን አልፈለጉም::

ወዲያው እንደ መጡ የግዕዝ ልሳንን ልቅም አድርገው ተማሩ:: ቀጥለው ኢትዮዽያውያን ሊቃውንትን ሰብስበው ቅዱሳት መጻሕፍትን ይተረጉሙ ገቡ:: አሥራው መጻሕፍትን (81ዱን) ጨምሮ ብዙ መሠረታዊ መጻሕፍትን መተርጐም ችለዋል::

ይህም ሥራ አድካሚ በመሆኑ ከ30 ዓመታት በላይ ጊዜን ወስዷል:: ከተረጐሟቸው መጻሕፍትም፦ #ስንክሳር#ግብረ_ሕማማት#ላሃ_ማርያም#ፊልክስዩስ(መጽሐፈ መነኮሳት)፣ #መጽሐፈ_ግንዘት፣ድርሳን ዘቅዱስ #ያዕቆብ_ዘሥሩግ. . . ይጠቀሳሉ::

አቡነ ሰላማ በስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸውና በገዳማዊ ሕይወታቸው ይታወቁ ነበር:: በተጨማሪም በየቦታው እየዞሩ ይናዝዙ: ያጠምቁም ነበር:: በወቅቱ ልክ እንደ ስማቸው ሰላም እንዲሰፍን ይተጉ ነበር:: መሣፍንቱን: ነገሥታቱን እያስታረቁ ለቤተ ክርስቲያን በአንድነት እንዲቆሙ አድርገዋል::

ጻድቁ አቡነ ፊልዾስን ጨምሮ ቅዱሳንን ገንዘውም ቀብረዋል:: በቀደመ ስማቸው #አባ_ፊቅጦር የሚባሉት ካልዕ (2ኛው) ሰላማ በ1380 ዓ/ም ከ40 ዓመታት ትጋት በኋላ ዐርፈዋል:: ሲጠሩም:- #መተርጉም (መጻሕፍትን የተረጐሙ)፣ #ብርሃነ_አዜብ(የኢትዮዽያ ብርሃን)፣ #መጋቤ_ሃይማኖት ተብለው ነው::

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳን_ሰባቱ_ደቂቅ

በዚህችም ቀን በከሀዲው ንጉሥ ዳኬዎስ ዘመን የነበሩ ከኤፌሶን ሀገር ሰባቱ ደቂቅ አረፉ። እሊህም ሰባቱ ደቂቅ ከንጉሥ ዳኬዎስ ጭፍሮች ውስጥ በመዛግብቱ ላይ የሾማቸው ነበሩ። አምልኮ ጣዖትንም በአወጀ ጊዜ ጣዖትን በማምለክ ሥራ አልተሳተፉም። እሊህንም ቅዱሳን በንጉሥ ዘንድ ወነጀሏቸው ይዞም አሠራቸው።

ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ ቦታ ለመሔድ በፈለገ ጊዜ እስከ ሚመለስ ድረስ ፈትቶ ለቀቃቸው ምናልባት ከምክራቸው ቢመለሱ ብሎ በልቡ አስቦ። ከዚህም በኋላ እሊህ ቅዱሳን ለረከሱ ጣዖታት እንዳይሰግዱ የጭፍራነት ሥራቸውን ትተው በተራራ ውስጥ ወደአለ ዋሻ ሒደው በዚያ ተሠወሩ።

የዋሻውን አፍ ዘጉ ከእሳቸውም ጋራ በንጉሥ ዳኬዎስ ስም የተቀረጸ ብር ነበር። ከእርሳቸውም አንዱም አንዱ በየተራቸው ወጥቶ ምግባቸውን ገዝቶ ወደእሳቸው ይመለስ ነበር። ዳኬዎስም ከሔደበት እንደተመለሰ በሰሙ ጊዜ የዋሻውን ደጃፍ ዘግተው ተኙ።

የእሊህንም ቦታቸውን የሚያውቅ አማኒ የሆነ ከጭፍሮች ውስጥ አንድ ሰው ነበረ ወደ ከተማ ሲወጡ ያገኛቸው ዘንድ ጠበቃቸው ባልመጡም ጊዜ ተነሥቶ ወደ ዋሻቸው ሔደ። ዋሻዋንም ከውስጥ እንደ ዘጓት ሁና አገኛት እነርሱም በረሀብ የሞቱ መሰለው ታላቅም የደንጊያ ሠሌዳ አምጥቶ ከእሳቸው የሆነውን ገድላቸውን ጽፎ በቀዳዳ ወደ ዋሻው ውስጥ አስገባው።እሊህም ቅዱሳን በእግዚአብሔር ትእዛዝ ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዘመናት አንቀላፉ ዳኬዎስም ሙቶ እስከ ቴዎዶስዮስ ብዙ ነገሥታት ነገሡ።

በዚህም ምእመን ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ዘመን ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉ ሰዎች ተነሥተው ብዙዎች ተከተሏቸው። በዚያንም ጊዜ እሊህን ቅዱሳን ሰባቱን ደቂቅ እግዚአብሔር አነቃቸው ትንሣኤ ሙታን መኖሩን ግልጽ ያደርግ ዘንድ።

ከዚህም በኋላ ከእርሳቸው አንዱ ምግባቸውን ሊገዛ የከሀዲ ዳኪዎስንም ወሬ ይሰማ ዘንድ ብር ይዞ ወጣ ወደ ከተማም በገባ ጊዜ የከተማዋ ሁኔታ ተለወጠበት። በከተማውም በር መስቀሎችን አየ በየቅጽሮቿም የክብር ባለቤት የሆነ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ስሙን ያለ መፍራት ሲጠሩ ሰማ አንዱንም ሰው ይች አገር ኤፌሶን አይደለችምን ብሎ ጠየቀ እርሱም አዎን ናት አለው።

ያንንም ብር አውጥቶ ለባለ ሱቁ ሰጠው ምግባቸውን ይሸጥለት ዘንድ ባለ ሱቁም ያን ብር ተመለከተው የንጉሥ ዳኬዎስም ስም ተቀርጾበት አገኘውና ያንን ሰው ይዞ በአንተ ዘንድ የተሸሸገ መዝገብ አለ ይህ ምልክት ከአንተ ተገኝቷልና አለው።

እንዲህም ሲጣሉ ወደእርሳቸው ብዙ ሰዎች ተሰበሰቡ እንዲህም ብለው ጠየቁት አንተ ከወዴት ነህ ከዚች አገር ነኝ አላቸው።ማንን ታውቃለህ አሉት እርሱም ዕገሌንና ዕገሌን አላቸው ከዘመን ብዛት የተነሣ የጠራቸውን ሰዎች የሚያውቃቸው የለም።ስለዚህም በእርሱ ላይ ተቆጥተው ወደ ዳኞችና ወደ ኤጲስቆጶስ አባ ቴዎድሮስ ወደ ንጉሥ ቴዎዶስዮስም አቀረቡት።

ንጉሡና ኤጲስቆጶሱም ከአንተ የሆነውን እውነቱን ንገረን ከወዴት አገር ነህ አሉት። እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው እኛ ሰባታችን የከሀዲ ንጉሥ ዳኬዎስ ጭፍሮች ነን እርሱም ወጥቶ ወደ ሌላ አገር በሔደ ጊዜ ከአንዷ ዋሻ ውስጥ ገብተን የዋሻዋን በር ዘግተን ተኛን። እነሆ ስንነቃ የምንመገበውን ምግብ እገዛ ዘንድ ላኩኝ።

ንጉሡና ኤጲስቆጶሱ በሰሙ ጊዜ ተነሥተው ወደዚያ ዋሻ ከእርሱ ጋራ ሔዱ ከእርሳቸውም ጋራ ብዙ ሕዝቦች አሉ ቅዱሳኑንም ተቀምጠው አገኙአቸው። የዘመኑም ቁጥር በውስጡ የተጻፈበትን በከሀዲው ንጉሥ በዳኬዎስ ዘመን የሆነውን ሠሌዳውን ወድቆ አገኙት ዘመኑም ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዓመት እንደሆነ ታወቀ።

ንጉሡና ኤጲስቆጶሱ ከሕዝቡ ሁሉ ጋር አደነቁ ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉትም ይህን ድንቅ ሥራ አይተው ትንሣኤ ሙታን እንዳለ አመኑ። እሊህ ሰባቱ ደቂቅንም በጠየቋቸው ጊዜ ከእርሳቸው የሆነውን ሁሉ ነገሩአቸው።

ከዚህም በኋላ ተመልሰው ተኙ። ነፍሳቸውንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ። ንጉሥም የወርቅ ሣጥን ሠራላቸው በሐር ልብሶችም ገንዘው በመልካም ቦታ አኖሩዋቸው። ከሥጋቸውም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ።

ስማቸውም:- መክሲማኖስ፣ ታሙኪሮስ፣ መርዳዲሞስ፣ ዮሐንስ፣ ቈስጠንጢኖስ፣ አዝሚና ዲዮናስዮ ነው።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የእሊህም ቅዱሳን በረከታቸው ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን!

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#መስከረም_24

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሃያ አራት ኢትዮጵያዊቷ #ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ ወደ ደብረ ሊባኖስ የገባችበት፣ ከላይኛው ግብጽ የሆነ ቅዱስ አባት #መነኰስ_ጎርጎርዮስ ያረፈበት እና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመረጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ #ሐዋርያ_አድሊጦስ የምስክርነቱ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ

መስከረም ሃያ አራት ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ወደ ደብረ ሊባኖስ የገባችበት ነው። ቅድስት እናት ክርስቶስ ሠምራ ቅንነቷ፣ ደግነቷና ቅድስናዋ እጅግ የበዛ ነው። አንድ ቀን ግን ገና በትዳር ውስጥ እያለች ከአገልጋዮቿ አንዷን ትጠራትና ታዛታለች። ያቺ አገልጋይ ግን የታዘዘችውን ጀሮ ዳባ ልበስ ብላ ሳትታዘዛት ትቀራለች።

ደጋግማ ብትነግራትም ልትሰማት አልቻለችም። ያን ጊዜ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ልትገስጻት ብላ ጠጠር ብትወረውርባት ያች አገልጋይ ወድቃ ሞተችባት። ቅድስቲቱ እጅግ ደንግጣ አለቀሰች። የምታደርገውንም አጣች።

ወዲያው ግን ፈጠን ብላ: ወገቧን ታጥቃ ትጸልይ ጀመረች። "ጌታየ ሆይ! ከሞት አስነሳልኝና ዓለምን ትቼ በቀሪ ዘመኔ አንተን አገልለግልሃለሁ" ብላ ፈጣሪን በብዙ እንባ ተማጸነችው:: ያን ጊዜም አገልጋዩዋ ከሞት ተነሳችላት።

ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ጊዜን አላጠፋችም። ልጆቿን በቤት ትታ ሃብትን ብረቷን ንቃ አንድ ልጇን አዝላ ቤቷን እንደ ተከፈተ ትታው ወደ ገዳም ወጣች። በዚህ ዕለትም (መስከረም 24 ቀን) ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገባች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ጎርጎርዮስ_ዘላዕላይ_ግብጽ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ከላይኛው ግብጽ የሆነ ቅዱስ አባት መነኰስ ጎርጎርዮስ አረፈ ። የዚህም የቅዱስና የተመሰገነ ጎርጎርዮስ ወላጆቹ ደጎች ናቸው በዚህ ዓለም ገንዘብም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህን ልጃቸውን ጎርጎርዮስንም በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት ። መንፈሳዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን ሁሉ ሥጋዊም የሆነ ጥበብንና ቋንቋን አስተማሩት ።

ከዚህም በኋላ የሀገራቸው ኤጲስቆጶስ ወደ ሆነ ወደ አባ ይስሐቅ ወሰዱት እርሱም እጁን በላዩ ጭኖ አናጒንስጢስነት ሾመው ።

ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ሊአጋቡት አሰቡ እርሱ ግን ይህን ሥራ አልወደደም ሁለተኛም ወደ ጳጳስ ወስደውት ፍጹም ዲቁናን ተሾመ ወደ አባ ጳኲሚስም አዘውትሮ በመሔድ ከእርሱ የእግዚአብሔርን ሕግ የሚማር ሆነ ከወላጆቹም ብዙ ገንዘብን ወስዶ ወደ አባ ጳኲሚስ አቅርቦ በገዳማቱ ለሚሠሩ ሕንፃዎች ሥራ ያደርግለት ዘንድ ብዙ ልመናን ለመነው እርሱም ተሳትፎ እንዲሆንለት ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያንና ለመነኰሳት ቤት መሥሪያ አደረገለት ።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዓለምን ትቶ ጥሪቱንና ገንዘቡን ሁሉ ንቆ በመተው ወደ ቅዱስ አባ ጳኲሚስም ሒዶ የምንኲስና ልብስን ለብሶ በጾም በጸሎት በመትጋት በመስገድ ከትሕትና፣ ከቅንነት፣ ከፍቅር ጋር ይጋደል ጀመረ አርአያነቱንና ምሳሌነቱን በአዩ ጊዜ ከእርሱ ፈሪሀ እግዚአብሔርን ተምረው አመንዝራዎች የከፋ ሥራቸውን እስከ ተውና ንስሐም ገብተው ንጹሐንም እስከ ሆኑ ድረስ ተጋደሉ ። ከአባ ጳኲሚስም ዘንድ ዐሥራ ሦስት ዓመት ኖረ ።

አባ መቃርስም ወደ አባ ጳኲሚስ በመጣ ጊዜ ሰውነቱን በማድከም ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚያም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊመለስ ወደደ አባ ጳኲሚስም ከአባ መቃርስ ጋር እንዲሔድ አባ ጎርጎርዮስን አዘዘው እርሱም አብሮ ሔደ በእርሱም ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖረ ።

ከዚህም በኋላ በዋሻ ብቻውን ይኖር ዘንድ እንዲአሰናብተው የከበረ አባ መቃርስን ለመነው እርሱም እንደ ወደድክ አድርግ አለው ። ያን ጊዜ ወደ ተራራ ሒዶ ታናሽ ዋሻ ቆርቁሮ በውስጧ ሰባት ዓመት ኖረ አባ መቃርስም በየዓመቱ ሁለት ጊዜ መጥቶ ይጎበኘዋል አንደኛ ለከበረ የልደት በዓል ሁለተኛ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተነሣባት በትንሣኤ በዓል ቀን ከርሱ ጋርም ሥጋውንና ደሙን ተቀብሎ ወደ ቦታው ይመለሳል ። አባ መቃርስም ስለ ሥራው ሁሉ ይጠይቀዋል እርሱም የሚያየውንና በእርሱ የሆነውን ሁሉ ይገልጽለታል አባ መቃርስም ሊሠራው የሚገባውን የምንኲስና ሥራን ይሠራ ዘንድ ያዘዋል ።

በተጋድሎም ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመታት ሲፈጽሙለት ከዚህ የድካም ዓለም ያሳርፈው ዘንድ እግዚአብሔር ፈቅዶ መልአኩን ላከለት እርሱም ከሦስት ቀን በኋላ ከዚህ ከኀላፊው ዓለም ወጥተህ ወደ ዘላለም ሕይወት ትገባለህ አለው ።

አባ ጎርጎርዮስም በአስቄጥስ ገዳም ያሉ አረጋውያንን አስጠራቸውና ተሳለማቸው በጸሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት ከሦስት ቀንም በኋላ አርፎ ወደ ዘላለም ሕይወት ገባ ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሐዋርያ_አድሊጦስ (ከሰባ ሁለቱ አርድእት)

በዚህችም ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመረጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ ሐዋርያ አድሊጦስ የምስክርነቱ መታሰቢያ ነው ። ይህም ሐዋርያ ትውልዱ ከአቴና አገር ከታላላቆቿና ከምሁራኖቿ ነው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ አገለገለውም ።

አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በሃምሳኛው ቀን ከተቀበለ በኋላ ወደ ብዙዎች አገሮች ሒዶ ሕይወት የሆነ ወንጌልን ሰበከ መግኒን ወደሚባልም አገር ደርሶ በውስጧ የከበረ ወንጌልን ሰበከ የብዙዎችንም ልቦና ብሩህ አድርጎላቸው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ። የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ሕይወት የሆኑ የወንጌልንም ትእዛዞች አስተምሮ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው ።

ከዚህም በኋላ ከእሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ አቴና አገር ተመለሰ በውስጧም የከበረ ወንጌልን አስተማረ በዚያን ጊዜም በደንጊያ ወገሩት ጽኑዕ የሆነ ሥቃይንም አሠቃዩት ። ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ወረወሩትና በዚያ ተጋድሎውንና ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መስከረምና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
አሁንም ስለ እግዚአብሔር ብለህ ስለ ቀናች ሃይማኖትም በድካም ከእኛ ጋር አንድ በመሆን ስለእኛ ወደ ግብጽ ሊቀ ጳጰሳት ወደ ቅዱስ ፊላታዎስ ጳጳስ ይልክልን ዘንድ ከራስህ ደብዳቤ እንድትጽፍለት እለምንሃለሁ የሚል ነበር ።

በዚያንም ጊዜ የኖባ ንጉሥ ጊዮርጊስ ለኢትዮጵያ አገር ጳጳስን ይሾምላቸው ዘንድ የልመና ደብዳቤ ወደ አባ ፊላታዎስ ጻፈ ይህ ቅዱስ ፊላታዎስም ልመናውን ተቀብሎ ከአስቄጥስ ገዳም ስሙ ዳንኤል የሚባል አንድ ጻድቅ መነኰስ አስመጣ እርሱን ጵጵስና ሹሞ ወደ ኢትዮጵያ አገር ላከው ወደ እነሱም በደረሰ ጊዜ የኢትዮጵያ ሰዎች በታላቅ ደስታ ተቀበሉት ። በዚህም አባት ፊላታዎስ ዘመን ብዙ ተአምራት ተገልጠዋል በሰላምም አረፈ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል እና በቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
በዚህችም ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት ቆዝሞስ አረፈ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ አራተኛ ነው። ይህም አባት ብዙ መከራና ኀዘን ደረሰበት በዘመኑም በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ላይ መከራና ችግር ደረሰባቸው በእነዚያም ወራት የክርስቲያን ወገኖችና አይሁዳውያን ልብሳቸውን በሰማያዊ ቀለም እንዲያቀልሙት እንጂ ነጭ ልብስ እንዳይለብሱ የእስላሞች ንጉሥ ጋዕፊር አዝዞ ነበርና።

በዚህም አባት ዘመን ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ በአስቄጥስ ገዳም በቅዱስ ሳዊሮስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ነበረች ጐኗም ተገልጦ ከእርሷ ብዙ ደም ፈሰሰ በግብጽ አገር ከአሉ ከሌሎች ሥዕሎችም ከዐይኖቻቸው ብዙ ዕንባ ፈሰሰ ይህም የሆነው በሊቀ ጳጳሳቱና በክርስቲያን ወገኖች ላይ ስለ ደረሰው መከራ እንደ ሆነ በመራቀቅ የሚያስተውሉ አወቁ።

ከዚህም በኋላ ስለእነዚያ የከፉ ወራቶች ፈንታ በጎ የሆኑ ወራቶችን እግዚአብሔር ሰጠው ሁል ጊዜም ምእመናንን የሚያስተምራቸውና የሚያጽናናቸው በቀናች ሃይማኖትም የሚያበረታታቸው ሆነ ። በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም ላይ ሰባት ዓመት ከአምስት ወር ከኖረ በኋላ በአምስት መቶ ሰባ አምስት ዓመተ ሰማዕታት ኅዳር ሃያ አንድ ቀን አረፈ ይንሶር በሚባል ዋሻውም ተቀበረ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘአስዩጥ

በዚችም ቀን ደግሞ የብርሌ የብርጭቆ ሠሪዎች ልጅ የሆነ ከአስዮጥ አገር ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ አረፈ ። ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ በበጎ ተግሣጽ አሳድገውታል የጥርብ ሥራንም አስተማሩት ከጥቂት ዘመናትም በኋላ አባቱና እናቱ አረፉ። ያን ጊዜ ወደ ቅዱስ አባ ኢስድሮስና ወደ አባ ባይሞን ዘንድ ሒዶ መነኰሰ በጾምና በጸሎት በገድል ሁሉ ተጠምዶ ተጋደለ ዜናውም በራቁ ገዳማት ሁሉ ተሰማ ።

ከዚህም በኋላ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጠለት ወደ ሀገሩ ሒዶ ወገኖቹን የጽድቅን ጎዳና ይመራቸው ዘንድ አዘዘው። ቅዱስ ቊርባንንም ሳይቀበል ከበዓቱ የማይወጣ ሆነ። በአንዲት ዕለትም ሁለት ቅዱሳን አረጋውያን አባ አብዢልና አባ ብሶይ ወደርሱ መጡ ገና ወደርሱ ሳይቀርቡ ከሩቅ ሳሉ ስማቸውን በመጥራት ሳያውቃቸው አባቶቼ ለመምጣታችሁ ሰላምታ ይገባል ብሎ ተናገረ እጅግም አደነቁት አባ ሲኖዳም ከግብጽ አገር እየመጣ ብዙ ጊዜ ይጎበኘው ነበር።

የከዳተኞችም ጠብ በግብጽ አገር ላይ በተነሣ ጊዜ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ የላከው የጦር መኰንን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጣ። በጸሎቱም ይራዳው ዘንድ ለመነው ቅዱስ ዮሐንስም መስቀሉን አንሥቶ መኰንኑን አይዞህ አትዘን አንተ ጠላቶችህን ድል ታደርጋለህና አለው እንደ ቃሉም ሆነ።

ዳግመኛም በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ላይ ጠላት በተነሣበት ጊዜ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ላከ እርሱም አትዘን አንተ ጠላትህን ታሸንፋለህ አለው ያን ጊዜም ጠላቶቹን አሸነፈ ።

ከዚህም በኋላ በእነዚያ ወራት ንጉሥ ቴዊዶስዮስ የርኲሰትን ሥራ ስለ ሠሩ የአስዮጥን ሰዎች እንዲገድሏቸው ሀገራቸውንም እንዲአጠፉ አዘዘ። ንጉሡም የላከው መኰንን ሳይደርስ የእግዚአብሔር መልአክ ይህን ነገር ለአባ ዮሐንስ አሳወቀው የሀገርም ሰዎች የንጉሡን ትእዛዝ በሰሙ ጊዜ ወደ አባ ዮሐንስ ገዳም ወጥተው ስለ መጥፋታቸው በፊቱ አለቀሱ አባ ዮሐንስም አትጨነቁ አይዟችሁ እግዚአብሔር ያድናችኋልና አላቸው።

መኰንኑም በመጣ ጊዜ ከእርሱ በረከትን ይቀበል ዘንድ ወደ አባ ዮሐንስ ደረሰ አባ ዮሐንስም ንጉሡ ያዘዘውን ሁሉ ነገረው መኰንኑም ሰምቶ ደነገጠ ለቅድስናውም ተገዢ ሆነ ለመኰንኑም ርኩስ መንፈስ ያደረበት የዐሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ነበረው ያድንለት ዘንድ ቅዱስ ዮሐንስን ለመነው በዚያንም ጊዜ ዘይትን ቀብቶ አዳነው።

ከዚህም በኋላ የአስዩጥ ሰዎችን መገደላቸውን እንዲተው ወደ ንጉሥ ይጽፍለት ዘንድ መኰንኑን አባ ዮሐንስ ለመነው መኰንኑም ጽፎ ለአባ ዮሐንስ ሰጠው አባ ዮሐንስም ተቀብሎ ወደ ዋሻው ገባ ወደ ጌታችንም ጸለየ ብርህት ደመናም መጣች ተሸክማም ወደ ንጉሡ አደረሰችው ያን ጊዜም ንጉሥ ከማዕድ ላይ ነበረ ያንንም ደብዳቤ ከወደላይ ጣለለት ንጉሡም አንሥቶ በአነበበው ጊዜ ከመኰንኑ የተጻፈ እንደሆነ በመካከላቸው በአለ ምልክት ተጽፎ አገኘው የተጻፈውም ቃል ስለ አባ ዮሐንስ ልመና ሀገሪቱን ማጥፋትን እንዲተው የሚል ነበር ቀና ባለ ጊዜም ደመና አየ ንጉሡም አደነቀ።

ከዚህም በኋላ ሀገሪቱን ማጥፋትን ስለ አባ ዮሐንስ ይተው ዘንድ መልሱን ለመኰንኑ ንጉሡ ጽፎ ደብዳቤዋን ወደ ደመናው ወረወራት የተሰበሰቡትም እያዩ እጅ ተቀበለችውና ወደ ደመናው ገባች ወዲያውኑ አባ ዮሐንስ በዚያች ደመና ወደበዓቱ ተመለሰና በማግሥቱ ያቺን ደብዳቤ ለመኰንኑ ሰጠው በላይዋም የንጉሡ ፊርማውና ማኅተሙ አለ በአያትና በአነበባት ጊዜ ደነገጠ አደነቀም ስለ ሀገሪቱ ድኅነትም እግዚአብሔርን እያመሰገነ ወደአገሩ ተመለሰ።

የንጉሥ ዘመድ የሆነች የከበረች ሴት ዜናውን በሰማች ጊዜ ከደዌዋ ይፈውሳት ዘንድ ወደርሱ መጣች በጸሎቱም ተፈወሰች። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ በሞተ ጊዜ መናፍቁ መርቅያን ነገሠ ። ቅዱስ አባ ዲዮስቆሮስንም አሠቃየው ። የቀናች ሃይማኖትን ስለመለወጡ አባ ዮሐንስ እየዘለፈና እየረገመው ወደ ርሱ ደብዳቤ ላከ ከጥቂት ወራትም በኋላ እግዚአብሔር ቀሠፈው።

ለእርሱም ዕድሜው መቶ ሃያ አምስት ዓመት ሲሆነው ዕረፍቱ እንደ ደረሰ አወቀ እየጸለየም ግምባሩን ምድር አስነክቶ ሰገደ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን በጸሎቷ የሚገኝ በረከቷም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ይኑር። በቅዱሳኑም ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ዳግመኛም ለጣዖታት መስገድን እሺ ይለው ዘንድ ቅዱስ ጢሞቴዎስን ማባበል ጀመረ እምቢ ባለውም ጊዜ የነዳጅ ድፍድፍ ሥጋውን ቀብተው ከእሳት ማንደጃ ውስጥ እንዲጨምሩት አዘዘ በጨመሩትም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ከዚህ ቃጠሎ አዳነው ።

ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ወደ ወህኒ ቤት መለሱት ተአምራትንም የሚያደርግ ሆነ በአንዲት ዕለትም በዚያ ሲጸልይ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ መጥቶ ቃል ኪዳንን ገባለት ሰላምታንም ሰጠው።

በማግሥቱም ከእሥር ቤት አውጥተው ወደ በንሑር ከተማ ወስደው ቅድስት ራሱን ቆረጡ ያን ጊዜ ንውጽውጽታ ሆነ አየርም መላእክትን ተመላች አማንያን ሰዎችም መጥተው ሥጋውን ወስደው በመልካም አገናነዝ ገንዘው ቀበሩት። የመከራውም ዘመን በአለፈ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት ሰኔ ሃያ ሰባት ቀንም አከበርዋት ሥጋውንም በውስጥዋ አኖሩ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር#ከገድላት_አንደበት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
በዳግመኛውም ዓመት ያቺ ባሕር ተገልጣ እንደ ልማዳቸው ገቡ ሕፃኑንም በሕይወት ሁኖ በቅዱስ ቀሌምንጦስ የሥጋ ሣጥን ዘንድ ቁሞ አገኙት በዚህ ባሕር ውስጥ አኗኗርህ እንዴት ነበር ምን ትበላ ነበር የባሕር አራዊትስ እንዴት አልበሉህም ብለው ጠየቁት። እርሱም ቅዱስ ቀሌምንጦስ ያበላኝ ነበር እግዚአብሔርም በባሕር ካሉ አራዊት ይጠብቀኝ ነበር ብሎ መለሰ ሰምተውም እጅግ አደነቁ በቅዱሳኑና ስለ ከበረ ስሙ ደማቸውን በአፈሰሱ ሰማዕታት የሚመሰገን ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
✞ ይህ ታላቅ መልአክ በ1ኛ ነገ. 19፥5-18 በምናገኘው ታሪክ ላይ ነብዩ ኤልያስን ከተኛበት እየቀሰቀሰ እንጎቻን ብላ ሲለው የነበረው መልአክ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ፋኑኤል ነው፡፡

✞ ሌላው የአዳም 7ኛ ትውልድ የሆነው ሞትን ሳያይ የተሰወረው ሄኖክ እንዲህ ሲል ጠቅሶታል "አራተኛውም የዘላለም ሕይወትን የሚወርሱ ሰዎች ተስፋ ሊሆን ንሰሐ በሚገቡ ሰዎች ላይ የተሾመው ፋኑኤል ነው" መ.ሄኖክ 10፥15

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ዜና_ማርቆስ_ጻድቅ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ ዕረፍታቸው ነው።

አባ ዜና ማርቆስ በሃገራችን በተለይ በደቡብ ምድረ ጉራጌ ስመ ጥር ሐዋርያዊ ጻድቅ ናቸው። ምድረ ሽዋ ደግሞ እርሳቸውን ጨምሮ የብዙ ቅዱሳን መፍለቂያ ናትና ክብር ይገባታል። ነቢየ ጽድቅ ዳዊት "ትውልደ ጻድቃን ይትባረኩ" "የጻድቃን (የቅኖች) ትውልድ ይባረካል" (መዝ.111) ያለው ነገር በምድረ ዞረሬ (ጽላልሽ) ተፈጽሟል።

ሦስት ወንድማማች የተባረኩ ካህናት በስፍራው ነበሩ። ስማቸው ጸጋ ዘአብ፣ እንድርያስና ዮሐንስ ይባላል። ከእነዚህ መካከልም ጸጋ ዘአብ እግዚእ ኃረያን አግብቶ ኮከበ ከዋክብት ተክለሃይማኖትን ሲወልድ፤ ካህኑ ዮሐንስ ደግሞ ዲቦራ የምትባል ደግ ሴት አግብቶ ዜና ማርቆስን ወልዷል።

የአቡነ ዜና ማርቆስ ጽንሰታቸው ሚያዝያ 30 በብሥራተ ማርቆስ ወንጌላዊ ሲሆን ልደታቸው ደግሞ ኅዳር 24 ቀን በበዓለ ሱራፌል ካህናተ ሰማይ ነው። ዘመኑም 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ነው።

ዜና ማርቆስ በተወለዱ በ40 ቀናቸው አጐታቸው ቀሲስ እንድርያስ (የ72 ዓመት ሽማግሌ ናቸው) ሊያጠምቁ ቀረቡ። ሕጻኑ ዜና ማርቆስ ግን ከእናታቸው እቅፍ ወርደው 3 ጊዜ "እሰግድ ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ" እያሉ ቢሰግዱ የመጠመቂያው ገንዳ ውኃ ፈላ። ይህንን የተመለከቱት ካህኑ ደንግጠው ወጥተው ሲሮጡ ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት ተገልጦ "አትፍራ! ይልቁኑ ከጠበሉ ራስህን ተቀባ" አላቸው። እንዳላቸው ቢያደርጉ ራሰ በራ ነበሩና ጸጉር በቀለላቸው።

ሕጻኑ ዜና ማርቆስ ግን 5 ዓመት ሲሞላቸው ወደ ጉባኤ ቤት ገብተው በአጭር ጊዜ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቁ። ዲቁናን ተቀብለው ወደ ቤታቸው ሲመለሱም ሽፍቶች አግኝተው በትራቸውን ቀምተው አንገላተው ሰደዋቸዋል። ወዲያው ግን ያቺ በትር እባብ ሁና ሽፍቶችን አጥፍታቸዋለች።

ጻድቁ ለቤተሰብ እየታዘዙ፣ ንጽሕናቸውንም እየጠበቁ ኑረው 30 ዓመት ሲሞላቸው ወላጆቻቸው ግድ ብለው ማርያም ክብራ ለምትባል ወጣት አጯቸው። እሳቸው ግን በሠርጉ ሌሊት ከጫጉላ ቤት ጠፍተው በርሃ ገቡ። ከዚያም በቅዱስ መልአክ መሪነት ሃገረ ምሑር ደረሱ። በቦታውም ጣዖትን ሰባብረው፣ ተአምራትንም አድርገው ሕዝቡን ወደ ክርስትና መለሱ።

መስፍኑ አውጊት ግን ተፈታተናቸው። አሠራቸው። አሥራባቸው(በረሀብ ቀጣቸው)። በጦር እወጋለሁ ሲል ግን መሬት ተከፍታ ከነ ተከታዮቹ ውጣዋለች። ከ5 ዓመታት በኋላ ግን ማልደው ከሰጠመበት አውጥተው አጥምቀውታል። ቀጥለውም ምድረ ጉራጌ ወርደው ሕዝቡን አሳምነው አጥምቀዋል።

የአዳልን ሕዝብና ንጉሡን አብደልማልን አስተምረው ያጠመቁም እርሳቸው ናቸው። ድል አሰግድ የሚባለውን መስፍንም ያሳምኑ ዘንድ ጠንቋዮቹን ድል አድርገው አጥፍተዋል።

ጻድቁ ዜና ማርቆስ ከዚህ ሐዋርያዊ ሥራቸው በተጨማሪ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ምንኩስናን ከተቀበሉባት ቀን ጀምረው በጾም፣ በጸሎትና በሰጊድ ኑረዋል። ፀሐይን በምድረ ጉራጌ እስከ ማቆም ደርሰውም ብዙ ተአምራትን ሠርተዋል።

አእላፍ ደቀ መዛሙርትን ሲያፈሩ 200 አንበሶች በቀኝ፣ 200 ነብሮች በግራ ይከተሏቸው ነበር። ደብረ ብሥራትን ጨምሮም ገዳማትን አንጸዋል። በመጨረሻም የምሕረት ቃል ኪዳንን ከፈጣሪ ዘንድ ተቀብለው ታኅሣሥ ሦስት ቀን በ140 ዓመታቸው ዐርፈዋል።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአማላጅነቷ ይማረን፤ በመልአኩ እና በቅዱሱ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን ።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታኅሣሥና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
የዚህም አባት ተአምራቶቹ ብዙ ናቸው ተነግሮ አያልቅም በአንዲትም ቀን በበረሀ ውስጥ ሲጓዝ ጅብ ልብሶቹን በጥርሶቻ ይዛ ሳበችውና በሠንጣቃ ገደል ውስጥ የወደቁ ልጆቿን አሳየችው በአወጣላትም ጊዜ ሰገደችለት እግሮቹንም ላሰች።

ከዚህም በኋላ ዕረፍቱ ሲቀርብ በታኅሣሥ ሦስት ቀን ወደ ሠርግ እንደሚጠራው ራእይን አየ ይኸውም የቅዱሳን አባቶች የአባ እንጦንስ፣ የአባ መቃርስ፣ የአባ ጳኪሚስ፣ የአባ ቴዎድሮስ፣ የአባ ሙሴ ጸሊም፣ የአባ ሲኖዳ የአንድነት ተድላ ደስታ ወዳለበት ነው። እነርሱም በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ከእኛ ጋር ትኖር ዘንድ ወደእኛ መምጣትህ መልካም ነው አሉት ብዙ አትክልቶችና ዙፋኖች ወዳሉት ታላቅ አዳራሽም ደጅ አደረሱት ማቴዎስ ይገባ ዘንድ የአዳራሹን ደጆች ክፈቱ የሚልንም ቃል ሰማ ከዚህም በኋላ በዚሁ ወር በሰባት አረፈ ሦስት አክሊላትንም ተቀበለ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን በጻድቅ በነቢያት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
በዚያንም ወራት የከሀዲው ልዮን ልጅ ቁስጠንጢኖስ ተነሥቶ በአምላክ ፈቃድ ስለተሣሉ ሥዕሎች ጸብ በማንሣት አብያተ ክርስቲያናትን አወከ ይህም አባ ዮሐንስ የቤተክርስቲያን ሹመት ሳይኖረው በቀናች ሃይማኖት እያጸናቸው በአምላክ ፈቃድ ለተሣሉ ሥዕሎችም ስግደት እንደሚገባ መስክር ከቅዱሳት መጽሕፍት እያመጣ የሚጽፍና ወደ ምእመናን ሁሉ የሚልክ ሆነ ።

ከሀዲው ቈስጠንጢኖስም በሰማ ጊዜ ጥርሱን አፋጨ በዮሐንስ ብርዕ አምሳል የሚጽፍ ጸሐፊንም ፈልጎ በዮሐንስ ብርዕ አምሳያ እንዲህ ብሎ አጻፈ ከአንተ ዘንድ ያለ ዮሐንስ ከአንተ ጋር ተዋግቼ አገርህን እማርክ ዘንድ ይህን ደብዳቤ ጽፎ ላከልኝ ብሎ በወንጀል ለደማስቆ ገዥ ላከለት በሰማ ጊዜም እውነት ስለ መሰለው የሚጽፍባት ቀኝ እጁን ቆረጠው ።

አባ ዮሐንስም የተቆረጠች እጁን ይዞ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ሒዶ በብዙ ዕንባ እንዲህ ብሎ ለመናት እመቤቴ ሆይ ለሥዕልሽ መስገድ ስለሚገባ በተጣለሁ ጊዜ አይደለምን ይህ መቆረጥ የደረሰብኝ አሁንም በቸርነትሽ ፈውሺኝ አንቺ በሥራው ላይ ሁሉ ችሎታ አለሽና ይህንንም ብሎ ጥቂት አንቀላፋ ። በእንቅልፉም ሳለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገለጸችለትና እጁን እንደ ቀድሞው መለሰችለት በነቃም ጊዜ ድና አገኛት እግዚአብሔርንም አመሰገነው ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምንም አመሰገናት ።

ከዚህም በኋላ ወደ ገዳም ሒዶ መነኰሰ አበ ምኔቱም የምንኩስናን ሥርዓት ያስተምረው ዘንድ ለአንድ ሽማግሌ መንፈሳዊ አባት ሰጠው ሽማግሌውም ልጄ ዮሐንስ ሆይ አፍአዊት ከሆነች ትምርትህ ምንም ምን አታድርግ ግን ዝምታን ተማር አለው ከትሕትናውም ብዛት የተነሣ ሰይጣንን ድል ነሣው ።

ከዕለታትም በአንዲቷ ከመነኰሳቱ አንዱ ሽማግሌ ሞተ መነኰሳቱም ስለ ወንድማቸው ሙሾ እንዲአወጣለት አባ ዮሐንስን ለመኑት አባ ዮሐንስም ከሽማግሌው መምህሬ ትእዛዝ የተነሣ እኔ እፈራለሁ አላቸው ለማንም አይገለጥም አሉት ምልጃንም በአበዙበት ጊዜ ለሚሰማት ሁሉ የምታሳዝን ሙሾ ደረሰ መምህሩም አውቆ በእርሱ ላይ ተቆጣ ከበዓቱም አባረረው እርሱም አባ ዮሐንስ ወደ አረጋውያን ሁሉ ተማጠነ ሽማግሌውንም ይቅርታ እንዲአደርግ ግድ በአሉት ጊዜ የመነኰሳቱን የመፀዳጃ ቤት የጠረገ እንደሆነ እምረዋለሁ አለ አባ ዮሐንስም ሰምቶ መንፈሳዊ መምህሩ እንዳዘዘው አደረገ እርሱም ቅንነቱንና ትሩፋቱን አይቶ በደስታ ተቀብሎ ወደ ማደሪያው አስገባው ።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም አረጋዊ መምህሩን ድርሳናትን መድረስን እንዳይከለክለው አዘዘችው ከዚህም በኋላ ብዙ ድርሳናት ደረሰ የኢየሩሳሌሙም ሊቀ ጳጳሳት ቅስና ሾመው በአምላክ ፈቃድ ስለ ተሣሉ ሥዕሎች ክብር ስለ ቀናች ሃይማኖትም ነገሥታቱንና መኳንንቱን ሲዘልፋቸው ኖረ ወደ ሽምግልናም በደረሰ ጊዜ ወደ ወደደው ክርስቶስ ሔደ ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ተክለ_አልፋ_ዘደብረ_ድማሕ

በዚህችም ቀን የደብረ ድማሕ ገዳም አበምኔት ቅዱስ አባት ተክለ አልፋ አረፈ። ዳግመኛም በክርስቶስ የሚታመን የገብረ ማርያም ዕረፍቱ ነው እርሱም የሰማዕታትንና የጻድቃንን በየዕረፍታቸው ቀን ለየአንዳንዱ ርኁባንን በማጥገብ የተራቆቱትን በማልበስ መታሰቢያቸውን የሚያደርግ ነው ።

እንዲህም ባለ ሥራ ላይ እያለ ያንጊዜ እስላሞች ወደ ሸዋ አገር መጡ እርሱም ያማሩ ልብሶችን ለብሶ ወደ ቤተክርስቲያን ሔዶ ገብቶ ጸሎትን ጸለየ ሲጸልይም እስላሞች ወደርሱ መጥተው ራሱን በሰይፍ ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ሁሉ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታኅሣሥ#ከገድላት_አንደበት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ታኅሣሥ_16

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ታኅሣሥ ዐስራ ስድስት በዚች ቀን የእስራኤል መሳፍንት አንዱ #ቅዱስ_ጌዴዎን_ኃያል ዐረፈ፣ #የሙሴ_እኅት_ማርያም መታሰቢያዋ ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ጌዴዎን_ኃያል

ታኅሣሥ ዐስራ ስድስት በዚች ቀን የእስራኤል መሳፍንት አንዱ ጌዴዎን ዐረፈ፡፡ ይህም ከነገደ ምናሴ የሆነ የአባቱ ስም ዮአስ ይባላል ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ ተገለጠለትና ለእስራኤል ሾመው። የጠዖታትንም መሠዊያ እነሰዲያፈርስ ዛፎችንም እንዲቆርጥ አዘዘው መሠዊያም ለእግዚአብሔር ሠርቶ በዚያ በሰበረው ዕንጨት እንዲሠዋ አዘዘው ሁሉንም እንዳዘዘው አደረገ። እግዚአብሔር የላከው መልአክም ተመለከተው "እስራኤልን ከምድያም እጅ ታድናቸዋለህና ከሠራዊትህ ጋር ሒድ እነሆ ላክሁህ" አለው።

ጌዴዎንም "አድናቸዋለሁ እንዳልክ እስራኤልን በእጄ ታድናቸው እንደሆነ እነሆ እኔ በአደባባይ የተባዘተ ፀምርን እዘረጋለሁ ጠል በምድር ላይ ሳይወርድ በፀምሩ ላይ ብቻ ቢወርድ አድናቸዋለሁ እንዳል እስራኤልን በእጄ እንድታድ ናቸው ያን ጊዜ አውቃለሁ" አለ እንዳለውም ሆነ። ጌዴዎንም በማግሥቱ ማልዶ ሒዶ ያንን ጨመቀው ከዚያ ፀምር አንድ መንቀል ሙሉ ውኃ ወጣ።

ጌዴዎን እግዚአብሔርን "በቊጣህ አትቆጣኝ ዳግመኛ አንድ ጊዜ ልናገር በፀምር ላይ ብቻ ሳይወርድ ጠል በምድር ሁሉ ላይ ይውረድ" አለው። እግዚአብሔርም በዚያች ሌሊት እንዳለው አደረገ። ፀምሩ ብቻ ደረቅ ሁኖ ጠል በምድር ሁሉ ላይ ወረደ። ጌዴዎንንም የእግዚአብሔር መንፈስ ረድኤት አጸናው ነጋሪትንም መታ አብያዜርም በኋላው ሁኖ ደነፋ ወደ ነገደ ምናሴር፣ ወደ ነገደ ዛብሎን፣ ወደ ነገደ ንፍታሌምም መልክተኞችን ላከ ወጥተውም ተቀበሏቸው። ጌዴዎንም ከርሱ ጋር ያሉ ወገኖቹም ሁሉ ሔዱ አሮኤድ በሚባል አገርም ሰፈሩ የመሰድያምና የአማሌቅ ሠራዊትም በእንበሬም ቆላ መሠዊያ ቀኝ ሰፈሩ።

እግዚአብሔርም ጌዴዎንን "እጃችን አዳነችን ብለው እንዳመኩብኝ የምድያምን ሰዎች በእጃቸው መጣል እንደማልችል ካንተ ጋር ያሉ ሕዝብ ብዙ ናቸው" እግዚአብሔር ጌዴዎንን እንዲህ አለው "ከእናንተ የሚፈራ የመመደነግጥ ሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይመለስ" ብለህ ለሕዝቡ ንገራቸው። ሕዝቡም ከገለዓድ ተመለሱ ከሕዝቡም ሁለት እልፍ ከሁለት ሽህ ተመልሰው እልፍ ሰዎች ቀሩ።

እግዚአብሔር ጌዴዎንን "ገና ብዙ ሕዝብ አሉ ወደ ውኃ አውርደህ በዚያ ፈትናቸው እኔ ይሒዱ የምልህ ሰዎች እነርሳቸው ካንተ ጋር ይሒዱ" አለው ሕዝቡንም ወደ ውኃ አወረዳቸው። እግዚአብሔር ጌዴዎንን "ውሻ በምላሱ ጠለፍ ጠለፍ አድርጎ እንዲጠጣ ከውኃው ጠለፍ ጠለፍ አድርጎ የሚጠጣውን ሁሉ ለብቻው አቁመው ውኃን ይጠጣ ዘንድ በጉልበቱ የተንበረከከውንም ሁሉ ለብቻው አቁመው" አለው። በምላሳቸው ጠለፍ ጠለፍ አድርገው የጠጡ ሰዎች ቊጥራቸው ሦስት መቶ ሆነ የቀሩት ሕዝብ ግን ውኃን ይጠጡ ዘንድ በጉልበታቸው ተንበረከኩ።

እግዚአብሔርም ጌዴዎንን "እንደዚህ በእጃቸው ውኃን በጠጡት በእነዚህ ሦስት መቶ ሰዎች አድናችኋለሁ የምድያምን ሰዎች ወደ ቤታቸው ይመለሱ" አለው። በዚያችም ሌሊት እሊህ ሦስት መቶ ሰዎች መለከትን ነፉ "ይህ የእግዚአብሔር ኃይልና የጌዴዎን ጦር ነው" ብለው ጮኹ። የምድያምም ሰዎች የመለከቱን ድምፅ በሰሙ ጊዜ እግዚአብሔር በልባቸው ፍርሀትን አሳድሮባቸው ደንግጠው ሸሹ እግዚአብሔርም ያንዱን ሰይፍ ወዳንዱ ወደ ጓደኛው መለሰ በሠራዊቶቻቸው ሁሉ እርስበርስ መተላለቅ ሆነ መኳንንቶቻቸውን ኄሬብንና ዜብን ነገሥቶቻቸው ዛብሄልንና ስልማናንም ገደሏቸው ከምድያምም ሠራዊት ፈረሰኞችና ጦረኞችን አንድ መቶ ሁለት ሽህ ገደሉ።

ከዚህም በኋላ የምድያም ሰዎች በእስራኤል ፊት ተዋረዱ ዳግመኛም ራሳቸውን ከፍ ከፍ አላደረጉም በጌዴዎንም ዘመን ምድር አርባ ዘመን ዐረፈች። ከዚህም በኋላ በዚች ቀን ታኅሣሥ16 በሰላም በፍቅር ዐረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ማርያም_እህተ_ሙሴ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የሙሴ እኅት ማርያም መታሰቢያዋ ነው፡፡ ይህች እናት የሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴና የሊቀ ካህናቱ ቅዱስ አሮን ትልቅ እህት ስትሆን ወላጆቿ እንበረምና ዮካብድ ይባላሉ:: እሥራኤል ከግብጽ ባርነት እንዲወጡ የእርሷን ያህል አስተዋጽኦ ያደረገች ሴት የለችም::

ከመነሻውም ቅዱስ ሙሴን የጠበቀች: በሕግ በሥርዓት እንዲያድግ ከእናቱ ጋር ያገናኘች: ወገኖቿ ከግብጽ ሲወጡም ሴቶችን የመራች እናት ናት:: ወንድሞቿን ሙሴንና አሮንንም ታገለገላቸው ነበር:: በተለይ እግዚአብሔር ባሕረ ኤርትራን የብስ ሲያደርጋት ከበሮን አንስታ "ንሴብሖ ለእግዚአብሔር" ብላ ፈጣሪዋን አመስግናለች:: (ዘጸ. 15:20)

አንድ ጊዜም "ኢትዮዽያዊቷን ሲፓራን ለምን አገባህ" በሚል ስለ ተናገረችው እግዚአብሔር ተቆጥቶ በለምጽ መቷታል:: (ዘኁ. 12:1) ቆይቶም በቅዱሱ ምልጃ ምሯታል:: ማርያም በመንገድ ሳሉ: ወደ ርስት ሳይደርሱ ዐርፋ ተቀብራለች:: (ዘኁ. 20:1)

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታኅሣሥ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ጥር_7

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ሰባት በዚች ቀን #በዓለ_ሥሉስ_ቅዱስ ሕንጻ ሰናዖርን ያፈረሱበትና ቅዳሴ ቤታቸው ነው፣ የከበረ አባት የሮሜ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ሶል_ጴጥሮስ አረፈ፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#በዓለ_ሥሉስ_ቅዱስ

ጥር ሰባት በዚች ቀን በዓለ ሥላሴ የሚከበረው ስለ ሁለት ምክንያቶች ነው:: ቀዳሚው ሕንጻ ሰናዖርን ማፍረሳቸው ሲሆን ሌላው ደግሞ ቅዳሴ ቤታቸው ነው::

#ሕንጻ_ሰናዖር
ሰናዖር ከሺዎች ዓመታት በፊት በአሁኗ ኢራቅ አካባቢ እንደ ነበረ የሚነገርለት ግዛት ሲሆን ስሙ ለሃገሪቱም: ለንጉሡም በተመሳሳይ ያገለግል ነበር:: ከናምሩድ ክፋት በሁዋላ ሰናዖርና ወገኖቹ ከሰይጣን ተወዳጁ::

ከጥፋት ውሃ (ከኖኅ ዕረፍት) በሁዋላ በሥፍራው በአንድነት ይኖሩ ነበርና እርስ በርሳቸው "ኑ ሳንበተን ስማችን የሚጠራበትን ሕንጻ እንሥራ:: በዚያውም አባቶቻችን በውሃ ያጠፋ እግዚአብሔርን እንውጋው" ተባባሉ::

ቀጥለውም ሰማይ ጠቀስ ፎቅን ገነቡ:: ከሕንጻው መርዘም የተነሳ በጸሐይ አብስለው በልተዋል ይባላል:: ቀጥለውም ጦር እያነሱ ፈጣሪን ሊወጉ ወርውረዋል::

መቼም የእነዚህን ሰዎች ክፋትና ቂልነት ስንሰማ ይገርመን ይሆናል:: ግንኮ ዛሬ ሰለጠንኩ በሚለው ዓለም እየተሠራ ያለው ከዚህ የከፋ ነው:: ቸርነቱ ቢጠብቀን እንጂ እንደ ክፋታችንስ ጠፊ ነበርን::

ርሕሩሐን ሥላሴ ግን የሰናዖር ሰዎች የሠሩትን አይተው ማጥፋት ሲችሉ አላደረጉትም:: የባሪያቸውን የኖኅን ቃል ኪዳን አስበዋልና:: ይልቁኑ "ንዑ ንረድ ወንክአው ነገሮሙ ለከለዳውያን-ቁዋንቁዋቸው እንደባልቀው" አሉ እንጂ::

ከለዳውያን ልሳናቸው ተደበላልቆ 71 ቁዋንቁዎች ተፈጠሩ:: እነርሱም ስምምነት አጥተው ተበተኑ:: ሥላሴም ያን ሕንጻ በነፋስ ትቢያ እንዲሆን በተኑት:: ስለዚህም እስከ ዛሬ ሥፍራው "ባቢሎን (ዝሩት)" ሲባል ይኖራል::

#ቅዳሴ_ቤት
ልክ የዛሬ 324 ዓመት አድያም ሰገድ ኢያሱ በኢትዮዽያ በነገሡ በ10ኛው ዓመት (በ1684 ዓ.ም) በጐንደር ከተማ ንግሥተ አድባራት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተሰርታ ተጠናቃለች::

ጥር 7 ቀንም ሊቁ ክፍለ ዮሐንስን ጨምሮ በርካታ ምዕመናን: ሠራዊት: መሣፍንትና ሊቃውንት ባሉበት ቅዳሴ ቤታቸው ተከብሯል:: በዕለቱም ታላቅ ሐሴት ተደርጉዋል:: ኢያሱ አድያም ሰገድ ኃያል: ደግ: ጥበበኛ: አስተዋይ: መናኝ ንጉሥ ነውና::

ቤተ ሥላሴን አስጊጿታልና ከዚህ ቀን ጀምሮ ጥር ሥላሴ በድምቀት የሚከበር ሆኗል:: ነገር ግን በተሠራች በ16 ዓመቷ ደጉ ኢያሱ ከተገደለ በሁዋላ ቤተ ክርስቲያኑ በአደጋ ፈርሷል:: ዛሬ የምናየው በ1708 ዓ.ም በልጁ በአፄ ዳዊት ሣልሳዊ የታነጸውን ነው::

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሶል_ዼጥሮስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የከበረ አባት የሮሜ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት ሶል ጴጥሮስ አረፈ። ይህንንም አባት ስለ ተጋድሎው ገናናነት ስለ አገልግሎቱም ስለ ትሩፋቱ ስለ አዋቂነቱና ስለ ደግነቱ ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ መልጥያኖስ ከአረፈ በኋላ መርጠው ሊቀ ጵጵስና በሮሜ ሀገር ላይ ሾሙት። በሐዋርያት አለቃ በጴጥሮስ ወንበር በተቀመጠ ጊዜ የዕሌኒ ልጅ የሆነ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስን የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው ከከሀድያን ጋር ስለሚያደርገው ጦርነት ምክንያት ገና አልተጠመቀም ነበርና የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሶ የእግዚአብሔርን አብያተ ክርስቲያናት ሠራቸው።

የዚህም አባት የሶል ጴጥሮስ ገድሉ እጅግ ብሩህ የሆነ ነው እርሱ ሁል ጊዜ ሕዝቡን ያስተምራቸዋልና ከልቡናቸውም ከሰይጣን የሆነ ጥርጥርንና ክፉ ሐሳብን ያርቃል። ከእነርሳቸው ሥውር የሆነውንም የመጻሕፍት ምሥጢር ተርጕሞ ያስገነዝባቸዋል። አይሁድንና ዮናናውያንን ሁል ጊዜ ይከራከራቸው ነበር ከእርሳቸውም ብዙዎችን መልሶ ወደ ቀናች ሃይማኖት አስገባቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ስሙም በምእመናን ዘንድ ፈጽሞ የሚያስፈራ ሆነ።

እግዚአብሔርን ስለ ማወቅና ስለ ወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ብዙ ድርሳናትን ደረሰ። በተሾመ በሰባተኛውም ዓመት ስለ አርዮስ በኒቅያ ከተማ ሃይማኖታቸው የቀና የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት የከበሩ አባቶች የአንድነት ስብሰባ ሆነ ይህም አባት ሶል ጴጥሮስ ከእርሳቸው አንዱ ነበር አርዮስንም ከተከታዮቹ ጋር ረገመው አውግዞም ለየው።

በሹመቱም ዐሥራ አንድ ዓመት ኖረ መልካም ተጋድሎውን ፈጽሞ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ከዚህም በኋላ ባኮስ እስከ ኑብያ ድረስ ሄዶ ወንጌልን ሰብኮ ብዙዎችን አሳምኖ አጥምቋል፡፡ በዚህም ጊዜ ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ በባኮስ እየተሰጠ የነበረውን የወንጌል ብርሃን የበለጠ እንዲበራ አድርጓል፡፡ ከጃንደረባውም ጋር ሆነው በብዙ ቦታዎች አብረው ወንጌልን ሰብከው አምልኮተ ጣዖትን አጥፍተዋል፡፡

ከዚህም በኋላ ባኮስ ወደ የመን በመሄድ በዚያም ክርስትናን በማስተማር ብዙዎችን አሳምኖ ካጠመቀ በኋላ ወደ ፐርሺያ ከዚያም ወደ ሕንድ፡ በመሄድ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሟል፡፡ በመጨረሻም ጥንት ታፕሮባና (taprobana)፡ ዛሬ ሲሎን በምትባለው ደሴት ወንጌልን በማስተማር ላይ እያለ በሰማዕትነት እንዳረፈ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ (lives of the most eminent fathers of the church, page 87) በሌላም በኩል ሐዋርያው ባኮስ (አቤላክ) ከመጠመቁ በፊት 35 ዓመት ከተጠመቀ በኋላ ደግሞ41 ዓመት ኖሮ በኢየሩሳሌምም 3ዓመት ተቀምጦ ወንጌልን ዞሮ ካስተማረ በኋላ በመጨረሻ በ79ዓመቱ ጥር 18 ቀን በሰሜን ተራራዎች ላይ ቅዱስ ያሬድ በተሰወረበት ቦታ እንደተሰወረ ሊቀ ብርሃናት መርቆሬዎስ አረጋ ጽፈዋል፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳት_ደናግል_ማርያ_ወማርታ (የአልዓዛር እህቶች)

በዚህችም ዕለት ከአራ ቀኖች በኋላ ጌታችን ከመቃብር ያስነሳው የአልዓዛር እህቶች የማርያ እና የማርታ መታቢያቸው ሆነ፡፡ በዘመነ ሐዋርያት በተመሳሳይ 'እንተ ዕፍረት-ባለ ሽቱ' ተብለው የሚጠሩ 2 እናቶች ነበሩ:: 2ቱም ስማቸው ማርያም ስለ ነበር ለመለየት እንዲያመች አንደኛዋን 'ማርያም ኃጥዕት ከኃጢአት የተመለሰች': 2ኛዋን ደግሞ 'ማርያም እኅተ አልዓዛር - በቢታንያ የነበረችው ብለው አበው ይጠሯቸዋል::

በሉቃስ ወንጌል ላይ የምትገኘው ከኃጢአት ሕይወት የተመለሰችው ስትሆን በዮሐንስ ወንጌል 12:1 ላይ ያለችው የአልዓዛር እህት (ድንግሊቱ) ናት:: ዛሬም የምናስባት ይህቺውን እናታችን ነው::

ቅድስት ማርያም መድኃኒታችን ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በሚያስተመርበት ዘመን በቢታንያ አካባቢ ትኖር የነበረች ድንግል ወጣት ናት:: ወላጆች ባልነበረበት ቤት ውስጥ ታላቆቿ አልዓዛርና ማርታ አሳድገዋታል::

በቤተሰብ ደረጃ እንግዳን ይቀበሉ ነበርና ጌታችን ወደዳቸው:: አልዓዛርን ከ72ቱ አርድእት: ማርያምና ማርታን ደግሞ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ቆጥሯቸዋል:: ወንድማቸው አልዓዛር በታመመ ጊዜ ወደ ጌታ ልከው ነበር::

ያለ ጊዜው የማይሠራ ጌታ ባይመጣ አልዓዛር ሞተ:: በ4ኛው ቀን አምላክ ሲመጣ ቅድስት ማርያም በጌታ ፊት ሰግዳ "እግዚእየ ሶበሰ ኀሎከ ዝየ እምኢሞተ እሑየ-አንተ በዚህ በኖርክስ ወንድሜ ባልሞተ ነበር" ብላ አለቀሰች:: (ዮሐ.11)

ጌታም ስታለቅስ ባያት ጊዜ አምላክነቱ አራርቶት አለቀሰ:: ወዲያውም በስልጣነ ቃሉ አዞ አልዓዛርን አስነሳው:: ከፋሲካ (ጌታ ከመሰቀሉ 6 ቀናት) በፊትም ቅዱሳኑ ለጌታ ግብር አገቡ:: እርሱም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ታደመላቸው:: (ዮሐ. 12:1)

በዚያም አልዓዛር ከጌታ ጐን ሲቀመጥ: ቅድስት ማርያም ከጌታ ሥር ተንበርክካ: ናርዶስ የሚሉትን የ300 ዲናር ሽቱ በጌታ ላይ አፈሰሰች:: መዓዛ መለኮቱና ሽቱው ሲገናኝ "መልዐ መዓዛሁ" እንዲል ምስጥ የሚያደርግ ሽታ ቤቱን ሞላው::

በወቅቱ ይሁዳ ቢቃወምም ጌታ ምላሹን ሰጥቶታል:: ቅድስት ማርያምንም "ማርያምሰ ኃርየት መክፈልተ ሠናየ ዘኢየኃይድዋ" ብሎ አመስግኗታል:: ያስመሰገናት ቁጭ ብላ በተመስጦ መማሯ ብቻ እንዳልሆነ አባ ሕርያቆስ መስከሯል::

ሲመክረንም "አርምሞንና ትዕግስትን እንደ ማርያም ገንዘብ እናድርግ" ብሎናል:: (ቅዳሴ ማርያም) ቅድስት ማርያም በጌታችን ክርስቶስ በኅማሙ ጊዜ: ሲቀብሩት ነበረች:: ትንሳኤውንም ዐይታለች::

ከጌታ እርገት በኋላም መንፈስ ቅዱስን ተከትላ ለወንጌል አገልግሎት ተግታለች:: ቅድስት እናታችን ማርያም እንተ ዕፍረት ዛሬ በዓሏ ከእህቷ ቅድስት ማርታ ጋር ይከበራል::

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ገድለ_ቅዱስ_ጊዮርጊስ#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር#መዝገበ_ቅዱሳን#ከገድላት_አንደበት#ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ቅዱሱም መልሶ ይህ አይገባም ትክክለኛውስ ለእግዚአብሔር እንድንሠዋ ለእርሱም እንድንሰግድ ይገባል እሊህ አማልክቶቻችሁ አፍ አላቸው አይናገሩም ዓይን አላቸው አያዩም ጆሮ አላቸው አይሰሙም አፍንጫ አላቸው አያሸቱም እጅ አላቸው አይዳስሱም እግር አላቸው አይሔዱም በአንደበታቸውም አይናገሩም በአፋቸው ውስጥ ትንፋሽ የለምና የሠሩአቸውም እንደነርሱ ይሁኑ እኔ ግን ሰማይና ምድርን በውስጣቸው ያለውን ሁሉ ከፈጠረ ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ለሌላ አልሰግድም አለው።

አርያኖስም ከቅዱስ ቢፋሞን አፍ ይህን ነገር ሰምቶ እጅግ ተቆጣ በየዓይነቱም ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው ዳግመኛም በፈረስ ጅራት አሥሮ መላ ከተማውን አስጎተተው እናቱና አገልጋዮቹም ሁሉ ወደርሱ መጡ እነርሱንም ከከበረ የወንጌል ቃል አስተማራቸው ገሠጻቸውም በዚያንም ጊዜ በግልጽ እኛ ክርስቲያን ነን ብለው ጮኹ የመኰንኑን ወንበር ገለበጡ መኰንኑም ጒድጓድ እንዲቆፍሩላቸውና እሳትንም አንድደው በውስጡ በሕይወት ሳሉ እንዲወረውሩአቸው አዘዘ እንዳዘዘውም አደረጉባቸው ቊጥራቸውም አምስት መቶ ነው።

ምስክርነታቸውንም እስኪፈጽሙ የከበረ ቢፋሞን ያጽናናቸውና ያስታግሣቸው ነበር እናቱም ልጅዋ ቢፋሞንን በላይዋ እንዲጸልይ ለመነችው እርሱም በመስቀል ምልክት በላይዋ አማተበና በሰላም ሒጂ አላት በዚያንም ጊዜ ሰውነቷን በእሳት ውስጥ ጣለች። ከእነሱ ጋርም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች።

የከበረ ቢፋሞንን ግን አርያኖስ ወደ ንጉሥ መክስምያኖስ ሰደደው ንጉሡም የነገሥታትን ትእዛዝ የምትተላለፍ ለአማልክት የማትሰግድ ሥራየኛው ቢፋሞን አንተ ነህን አለው። ቅዱሱም ሥራይን ግን አላውቅም ለረከሱ አማልክትም አልሰግድም አንተና አማልክቶችህ በአንድነት ወደ ገሀነም እሳት ትወርዳላችሁና አለው ንጉሡም ተቆጥቶ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው ከማሠቃየትም በሰለቸ ጊዜ ወደ ኄሬኔዎስ ሰደደው እርሱም ወደ አርያኖስ ሰደደው በእነዚያ ቀኖችም ምንም አልበላም።

አርያኖስም ወስዶ በብረት ችንካሮች ቸነከረውና ለአማልክት ካልሰገድክ አጠፋሃለሁ አለው ቅዱሱም እርሱንና አማልክቶቹን ዘለፈ ረገማቸውም ከዚህም በኋላ በከተማዪቱ ሁሉ መንገድ እንዲጎትቱትና ከእንዴናው ከተማ ውጭ በእሳት እንዲአቃጥሉት መኰንኑ አዘዘ ይህንንም ሁሉ አደረጉበት ጌታችንም ያለ ጥፋት በጤና ከእሳት ውስጥ አወጣው የከበረ ቢፋሞንም ከእሳት ውስጥ ቁሞ በነበረ ጊዜ ከእግሮቹ ብዙ ደም ፈሰሰ ከሕዝብ ጋር የቆመ አንድ ሰው ነበረ እርሱም ለምጻምና ዕውር ነበር ከደሙም ወስዶ ዓይኖቹን ቀባ ያን ጊዜ አየ ከለምጹም ነጻ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የምታመን ክርስቲያን ነኝ ብሎ ጮኸ ራሱንም እንዲቆርጡ መኰንኑ አዘዘና ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

የከበረ አባ ቢፋሞንንም ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አርያኖስ አዘዘ ቢፋሞንም አገልጋዩን ዲዮጋኖስን እንዲህ ሲል ሥጋውን በሥውር እንዲጠብቅ ደሙንም በበፍታ ልብስ እንዲቀበል ገድሉንም በአውሲም አገር ላሉ ምእመናን እንዲነግር አዘዘው የመከራው ወራት ያልፍ ዘንድ አለውና ከዚህም በኋላ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ብሎ በመስቀል ምልክት አማተበ ወደ ጭፍሮችም ቀርቦ የታዘዛችሁትን ፈጽሙ አላቸው እነርሱም ወደ ሌላ ቦታ ብቻውን ወስደው ራሱን በሰይፍ ቆረጡት ።

ከአንገቱም ብዙ ደም ፈሰሰ አገልጋዩ ዲዮጋኖስም ከእርሱ ዘንድ ያለውን በፍታ ዘርግቶ የቅዱስ ቢፋሞንን ደም ተቀበለበት። በዚያም ቦታ እጅግ ጣፋጭ የሆነ መዓዛ መላ ጭፍሮች እስኪያደንቁና እስኪደነግጡ ድረስ ታላቅ ፍርሀት ወረደባቸው ከዚያም ቦታ ሸሹ።

ከዚህም በኋላ ምእመናን መጥተው ሥጋውን ወሰዱ ብዙ ሽቱ አምጥተውም በመዘመር በክብር ገነዙት ከከተማም ውጭ ተሸክመው ወስደው ቀበሩት ከመቃብሩም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ አገልጋዩም ያቺን በፍታ ወስዶ ጠበቃት ወደ ሀገሩ ሊሔድ በፈለገ ጊዜ የሚፈራ ሆነ ምን እንደሚያደርግም አሰበ የከበረ ቢፋሞንም ተገለጠለትና ለወዳጁ ለቴዎድሮስና ለሀገሩ ሰዎች ዜናውን እንዲነግር አዘዘው እግዚአብሔርም ምእመናን ሰዎችን ላከለት እነርሱም ከእርሳቸው ጋር በመርከብ አሳፍረው ወሰዱት በመርከብም ውስጥ ሳለ የክብር ባለቤት ጌታችን ከዚያች በፍታ በከበረ ቢፋሞን ደም ከታለለችው ተአምራትን ገለጠ አገልጋዩ ዲዮጋኖስም ገድሉን ነገራቸው አደነቁ ጌታችንንም አመሰገኑት እርሱንም ወደ አገሩ ወደ አውሲም አደረሱት ዲዮጋኖስም ለወዳጁ ለቴዎድሮስና ለሀገሩ ሰዎች ሁሉ የገድሉን ዜና ነገራቸው ያቺንም በደም የታለለች በፍታ ሰጣቸው ይህችም የመከራው ወራት አልፎ ደጉ ቈስጠንጢኖስ ነግሦ በሀገሮች ሁሉ በክርስቲያን ወገኖችም ላይ ሰላምና ጸጥታ እስከሆኑ ድረስ በእነርሱ ዘንድ ተጠብቃ ኖረች።

እግዚአብሔርም የከበረ የቢፋሞንን ሥጋ ለምእመናን አለኝታና መጽናኛ ለበሽተኞችም የሚፈውስ ኃይል እንዲሆን ሊገልጠው ወደደና በእርሱም በላይኛው ግብጽ በጥማ አውራጃ በቃው ከተማ በጥር ሃያ ሰባት በዚች ቀን በሰማዕትነት የሞተ ነው።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ይህም አባት ቴዎድሮስ በገድል የተጠመደ ሆነ መልኩም የሚያምር ነው በሰውነቱም ላይ ከውስጥ ማቅ በመልበስ በላዩ የብረት ልብስ መንቈር ይለብስ ነበር በቅንነቱና በትሕትናው ፍጹም ሆነ። በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ተመርጦ በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ። የክርስቶስንም መንጋዎች በበጎ አጠባበቅ ጠበቀ ሁልጊዜ መጻሕፍትን በማንበብ ያስተምራቸው ነበር ይልቁንም በሰንበትና በበዓላት ቀን።

የሹመቱም ዘመን ጸጥታና ሰላም ነበረ ቤተ ክርስቲያንም በሰላም ኖረች በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም ላይ ዐሥራ አንድ ዓመት ተኩል ከኖረ በኋላ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_አብዱልማዎስ_ገዳማዊ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ገዳማዊው ጻድቁ አብዱልማዎስ አረፉ። ጻድቁ ግብጻዊ ሲሆኑ በበርሃ ሰው ሳያዩ ለ70 ዓመታት በቅድስና ኑረዋል:: በጊዜውም እግዚአብሔር አባ አብዱልማዎስን ወደ አባ ዕብሎይ ልኳቸው ነበር:: ሁለቱ ተገናኝተው አብረው ለ3 ቀናት ሲቆዩ ቅዱስ መልአክ እየተገለጸ አጽናንቷቸዋል:: ከሥውራን ማኅበርም ተቀላቅለው ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብለዋል::

አባ ዕብሎይ ሲያርፍ አንበሶች እያገዟቸው ቀብረዋቸዋል:: እርሳቸውም "እኔን የሚቀብረኝ ስጠኝ" ብለው ጸልየው ነበርና 3 ገዳማውያን መጥተውላቸዋል:: የካቲት 5 ቀን አባ ዕብሎይን ገንዘው ቀብረው በ3ኛው ቀን አርፈዋል::

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
"ልጆቼ ሆይ! ከብርሃን ጨለማን ከደግነት ክፋትን ከጽድቅ ይልቅ ኃጢአትን . . . ምነው መምረጣችሁ? እኔ ስለ እናንተ በየቀኑ እየለመንሁ እነሆ አለሁ:: ወደ ጨለማ ገሃነም እንዳትወርዱ እባካችሁ ንስሐ ግቡ!" ቅድስት ድንግል ማርያም ይህንን ለቅዱሱ ሰው ነግራው ቅዱስ ዳዊትን አስከትላ በግሩማን መላእክት ታጅባ ወደ ውሳጤ መንጦላዕት (የእሳት መጋረጃዎች ወደ ተተከሉበት ድንኳን) ገባች:: በዚያም ተመሰገነች::

ለዛም አይደል ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ:- "ይዌድስዋ መላእክት ለማርያም በውስተ ውሳጤ መንጦላዕት : ወይብልዋ : በሐኪ ማርያም ሐዳስዩ ጣዕዋ::" ሲል ያመሰገናት::

ቅዱስ ጐርጐርዮስም ከሰማይ ቆይታ መልስ ያየውን ሁሉ ጽፎ ለአበው ሰጥቷል:: ስለዚህም ረዓዬ ኅቡዓት (ምሥጢራትን ያየ) ይሰኛል:: ቅዱሱ ተረፈ ዘመኑን በተጋድሎ ፈጽሞ በዚህች ቀን አርፏል::

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ከዚህ በኋላ ይህ አባት እለእስክንድሮስ ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ በመንበረ ሢመቱ ላይ ተቀመጠ አርዮስንም ከወገኖቹ ጋራ አውግዞ አሳደደው። የሀገር ታላላቆችም ከሕዝቡ መጡ ከውግዙቱ እንዲፈረታውም ለመኑት። በውግዘት ላይ ውግዘትን እንዲጨምር እንጂ እንዳይፈታ አባ ጴጥሮስ እንዳዘዘው ነገራቸው።

ከዚህ በኋላ አርዮስ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሒዶ በግፍ አወገዘኝ ብሎ እለእስክንድሮስን ከሰሰው። ስለዚህም ንጉሡ ሦስት መቶ አሥራ ስምንት የከበሩ አባቶችን በኒቅያ ከተማ ሰበሰበ፡፡ ይህም አባት እለእስክንድሮስ ተመርጦ ለጉባኤው ሊቀ መንበር ሆነ አትናቴዎስም ጸሐፊ ነበር። አርዮስንም ተከራክረው ክህደቱን ግልጽ አደረጉ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከአባቱ ከአብ ጋራ ከሕይወቱ መንፈስ ቅዱስም ጋራ በመለኮቱ ትክክል እንደሆነ አስረዱት።

ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። በአንድ ቃልም ጸሎተ ሃይማኖትን ከአባቶች ጋራ ሠሩልን ደግሞ በእርሳቸው ቤተ ክርስቲያን ለዘላለም የምትመራባቸው ሃያ ቀኖናን ሠርተው ወሰኑ።

ከዚህ በኋላም ይህ አባት እለእስክንድሮስ ወደ መንበረ ሢመቱ ከድል ጋራ ተመለሰ። በበጎ አጠባበቅም መንጋውን ጠበቀ በወንጌላዊ ማርቆስ መንበርም አሥራ ሰባት ዓመት ኖሮ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ማርቆስ_ሐዲስ

በዚህችም ቀን የሐዲስ ማርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፡፡ እርሱም በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች አርባ ዘጠነኛ ነው ። ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ነው እርሱም በሥራው ሁሉ ቅድስናውን ጠብቆ ኖረ የተማረም ዐዋቂ ሆነ ለወንጌላዊ ማርቆስም በስም ሁለተኛ ነው ።

አባ ዮሐንስም ዲቁና ሾመው እጅግ መልካም ካህን ሆነ መጻሕፍትን በሚያነብ ጊዜ በአንደበቱ ቅልጥፍና በነገሩ ጣዕም የሚሰሙት ሁሉ ደስ የሚላቸው ሆኑ ። ከዚያም አባ ዮሐንስ ከእርሱ ጋራ አኖረው በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው ያለ እርሱም ምክር አባ ዮሐንስ ምንም ምን አይሠራም ።

ከዚህ በኋላ በአባ መቃርስ ገዳም የምንኲስና ልብስ አለበሰው በዚያች የምንኵስና ልብስ በለበሰባትም ቀን ከቅዱሳን አረጋውያን አንድ ጻድቅ ሰው መጥቶ በእርሱ ላይ እንዲህ ብሎ በሕዝብ ፊት ይህ ስሙ ማርቆስ የሚባል ዲያቆን በአባቱ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ሊቀመጥ አለው ብሎ ትንቢት ተናገረለት ።

የአባ ዮሐንስም የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ አባ ማርቆስን ሊቀ ጵጵስና እንዲሾሙት ኤጲስቆጶሳቱን አዘዛቸው በእርሱ መሾምም ደስ አላቸው ። ከአባ ዮሐንስ ዕረፍት በኋላም ያለ ፈቃዱ ሾሙት እርሱ ግን ከእርሳቸው ሸሽቶ ወደ አስቄጥስ ሔደ ሰዎችንም ልከው አሥረው ወደ መንበረ ሢመቱ አመጡት ።

ከዚህ በኋላም ጸጥ ብሎ ስለ አብያተ ክርስቲያን የሚያስብ ሆኖ የፈረሰውን አነፀ ጠገነ፡፡ በዘመኑም የመናፍቃንን ጠባይ ከሕዝቡ ውስጥ አስወገደ ይኸውም በግብጽ አገር የተገለጡ ለብቻቸውም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የሚኖሩ ናቸው እርሱም አስተምሮ መክሮ መልሶ ከመንጋዎቹ ጋራ አንድ አደረጋቸው። እግዚአብሔርም በዚህ አባት እጅ ድውያንን በመፈወስ አጋንንትን በማስወጣት ብዙ ድንቆች ምልክቶችን ገለጠላቸው።

ከእርሳቸውም አንዱን አስተውል አንተ ያለ ፍርሀት በድፍረት ሥጋውንና ደሙን የምትቀበል ባትሆን ይህ ባላገኘህም ነበር ከእንግዲህ ከክፉ ሥራና ከአንደበትህ ከሚወጣ ከከንቱ ነገርም ሰውነትህን ጠብቅ አለው።

በዘመኑም በምዕራብ ያሉ እስላሞች ይሸጡአቸው ዘንድ ብዙ ክርስቲያኖችን ከሮም ግዛት ውስጥ ማርከው ወደ እስክንድርያ አመጡአቸው ይህም አባት እጅግ አዘነ ከየገዳማቱና ከምእመናን ብዙ ገንዘብ ለምኖ ከእስላሞች እጅ በሠላሳ ሽህ የወርቅ ዲናር ዋጃቸው የነፃነትም ደብዳቤ ጽፎ ነፃ አወጣቸው ። እንዲህም አላቸው ወደ አገሩ መመለስ የሚሻ እኔ ስንቅ ሰጥቼ አሰናብተዋለሁ ከእኔ ጋራ መኖር የሚሻም ካለ እኔ እጠብቀዋለሁ አላቸው። የተመለሱ አሉ ስንቅ ሰጥቶም ያሰናበታቸው አሉ ከእርሱ ዘንድ የቀሩትንም ጠበቃቸው አጋባቸውም።

ከዚህ በኋላ ስለ መድኃኒታችን ቤተ ክርስቲያን አሰበ አደሳትም ሰይጣንም በሀገር ውስጥ ሁከት አስነሥቶ በእሳት አቃጠላት ይህም አባት መልሶ ዳግመኛ አደሳት። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ ጥቂት ታመመ በፋሲካ በዓል በእሑድ ቀንም ወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ተገለጠለት ለሚወዱት እግዚአብሔር ስለ አዘጋጀው ተድላ ደስታ ነገረውና ሥጋውንና ደሙን ከተቀበልክ በኋላ ታርፋለህ አለው። በነቃ ጊዜም እንዴት እንዳየ ከእርሱ ዘንድ ላሉ ኤጲስቆጶሳት ነገራቸው።

ከዚያም የቅዳሴውን ሥርዓት ጀምሮ ቀድሶ ሥጋውን ደሙን ተቀበለ በዚያን ጊዜም አረፈ የሹመቱም ዘመን ሃያ ዓመት ሆነ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ሚካኤል_ዘእስክንድርያ

በዚህችም ቀን የከበረ አባት አባ ሚካኤል የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ ሦስተኛ ነው ። ይህም ቅዱስ ጻድቅ መንኲሶ በአስቄጥስ በቅዱስ ዮሐንስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ ተሾመ ከዚያም ያለ ፈቃዱ ወስደው በግድ ሊቀ ጵጵስና በእስክንድርያ አገር ላይ ኅዳር ሃያ አራት ቀን ሾሙት ። በሊቀ ጵጵስናውም ሥራ ተጠምዶ የሚጋደል ሆነ እንደ ሐዋርያትም አጠባበቅ መንጋውን ጠበቀ ።

ታላቁ ጾምም በደረሰ ጊዜ ወደ አስቄጥስ በዚያ ሊጾም ወጣ ከመሾሙ በፊት በዚያ ገዳም ውስጥ በብሕትውና ሁኖ መጠመዱንና የቀድሞ መጋደሉን አሰበ ።

ወደ ጌታችንም እንዲህ ብሎ ለመነ አቤቱ እኔ በብቸኛነት መኖርን እንደምሻ አንተ ታውቃለህ ለዚች ለተሾምኩባትም ሹመት ችሎታ የለኝምና የምትገባኝም አይደለችምና በይቅርታህም ብዛት ነፍሴን ወስደህ ከዚህ ድካም ታሳርፈኝ ዘንድ እለምንሃለሁ ጌታም ልመናውን ተቀበለ ከፋሲካ በዓል በኋላም በፍቅር አንድነት አረፈ፡፡ የሹመቱም ዘመን ሁለት ዓመት ከአምስት ወር ነው።

ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሚያዝያ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
ከዚህም አስቀድሞ የከተማው ሰዎች የሚያመልኩትን ዘንዶ እርሱ እንደ ገደለው የአውኪስጦስ አገር ሰዎች ወደ ንጉሥ ከሰውት ነበርና ስለዚህ ንጉሥ ልኮ አስቀረበው።

ቅዱስ ቴዎድሮስም ወደ ንጉሡ በቀረበ ጊዜ ንጉሡን እንዲህ ብሎ ዘለፈው አንተ የክፉ ሥራ ሁሉ መገኛ የሆንክ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ የክብር ባለቤትን ትተህ የረከሱ ጣዖታትን ያመለክ የኃጢአት ልጅ ሆይ ወዮልህ እግዚአብሔርም ፈጥኖ መንግሥትህን ያጠፋታል።

በዚያን ጊዜም ንጉሡ ተቆጥቶ ከመሬት ላይ ጥለው ይገርፉት ዘንድ ወታደሮችን አዘዛቸው። ይህንንም አደረጉበት ደሙም እንደ ውኃ ፈሰሰ። እጆቹንና እግሮቹንም ከግንድ ጋር ቸነከሩት።

በሥቃይም ውስጥ ሳለ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ወደርሱ ወረደ እንዲህም አለው ጽና እነሆ የገድልህ ፍጻሜ ቀርቦአል ሥጋህ በውስጡ በሚኖርበትም ቦታ ድንቆችና ተአምራቶች ይገለጣሉ እነሆ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠህ መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ፣ ወይም በስምህ የተራበ ለሚያጠግብ፣ የተጠማውን ለሚያጠጣ፣ ወይም ለቤተክርስቲያንህ መባን መጻሕፍትንም ለሚሰጥ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስስለታለሁ። ገድልህንም የሚጽፈውን፣ ወይም የሚያነበውን፣ የሚሰማውን፣ ወይም የሚገዛውን እኔ ስሙን በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ።

ከዚህም በኋላ ብዙዎች ከንጉሥ ሠራዊትና ከሕዝቡ ተሰብስበው በንጉሡ ላይ እንዲህ ብለው ጮኹበት አንተ ከሀዲ እግዚአብሔር ያጥፋህ ከጠላቶቻችን ያዳነንን ኃያልና ጽኑዕ የሆነውን የከበረ ቴዎድሮስን ታሠቃየዋለህና ይህንንም ብለው በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ያን ጊዜም ንጉሥ ተቆጥቶ ሁሉንም አስገደላቸው ሰማዕትም ሆኑ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ።

ከዚህም በኋላ ንጉሡ አዘዘ የብረት ዐልጋም አምጥተው ቅዱሱን በላዩ አስተኙት ከበታቹም እሳትን አነደዱ ቅዱስ ቴዎድሮስም እንዲህ ብሎ ጸለየ አቤቱ ፈጣሪዬ ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ምድጃ እንደ አዳንካቸው አድነኝ። ወዲያውኑም ያ እሳት ጠፋ እንደ ንጋት ጊዜ ቊርም ሆነ።

ከሰማይም እንዲህ የሚል ቃል መጣ ክብር ይግባውና ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የተሰጠህ ሆይ ጽና በርታ ያን ጊዜም ቅዱሱ ተነሥቶ በንጉሡ ፊት ቆመ እንዲህም አለው ክብር ይግባውና ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አድኖኛልና አንተ ከሀዲ እፈር አለው። የንጉሡም የጭፍራ አለቃ ይህን በአየ ጊዜ ክቡር ቴዎድሮስ ከሚያመልከው ክብር ይግባውና ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም ብሎ ጮኸ ርሱንም ራሱን አስቆረጠውና በሰማዕትነት ሞተ።

ቅዱስ ቴዎድሮስንም ብዙ ከአሠቃየውና ማሠቃየቱ ከሰለቸው በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ሥጋውንም እንዲአቃጥሉ አዘዘ። በጌታችንም ፈቃድ ከእናቱ ደጅ ወስደው እራሱን ቆረጡ ከእርሱም ደም፣ ወተትም ፈሰሰ ታላቅ እሳትም አንድደው ሥጋውን በውስጡ ጨመሩ እሳቱም ከቶ አልነካውም። እናቱም ለወታደሮች ብዙ ወርቅ ሰጥታ ሥጋውን ወሰደች በአማሩ ልብሶችም ገነዘችው እስከ መከራው ፍጻሜም በቤቷ ውስጥ አኖረችው።

ከዚያ በኋላም አብያተ ክርስቲያናት ተሠሩለት ስብጥ በሚባል በአባቱ አገርም በተሠራች ገዳም ሥጋውን አኖሩ ከሥጋውም ድንቆችና ተአምራቶች ተደረጉ ታላቅ ፈውስም ሆነ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
#ጥቅምት_1

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት አንድ በዚህችም ቀን  #ቅድስት_አንስጣስያ በሰማዕትነት አረፈች፤ ዳግመኛም የማርታና የአልዓዛር እህት #የቅድስት_ማርያም_እንተ_ዕፍረት የእረፍቷ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_አንስጣስያ_ሰማዕት

በዚህችም ቀን በጥቅምት አንድ ቅድስት አንስጣስያ በሰማዕትነት አረፈች። ይችም ቅድስት መስተጋድልት ከሮሜ አገር ናት ወላጆቿም ክርስቲያኖች ናቸው ጠቃሚ የሆነ ትምህርትን በማስተማር ክብር ባለው በመልካም ሥርዓት አሳደጓት።

በአደገችም ጊዜ ወላጆቿ ሊያጋቧት ፈለጉ እርሷ ግን ይህን ሥራ አልፈለገችም የምንኲስናን ልብስ መልበስ ፈለገች እንጂ፤ ከታናሽነቷም መንፈሳዊ ገድልን መረጠች።

ስለዚህም በሥውር ሒዳ በሮሜ ካሉ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባች ታናሽ ስትሆንም የምንኲስና ልብስን በመልበስ በጾም በጸሎት በረኃብ በጽምዕ በመጠመድ የዚህን ዓለም ሐሳብ ሁሉ ከልቡናዋ ቆርጣ በመተው በመጋደል ሥጋዋን አደከመች።

በቀኑ ርዝመትም ሁሉ የምትጾም ሆነች በየሁለት ቀኖችም ታከፍላለች በጌታችን ጾም ግን ያለ ሰንበታት ቀን የምትመገበው የለም። በሰንበታትም የምትመገበው ከቀትር ጸሎት በኋላ ነው። በነዚያም በምንኲስናዋ ወራት በእሳት ያበሰሉትን ወጥ አልቀመሰችም።

በገዳሟ አቅራቢያም ሌላ የደናግል ገደም አለ የዚያ ደብር በዓልም በደረሰ ጊዜ እመ ምኔቷ በዓሉን ለማክበር ይቺን ቅድስት አንስጣስያን ከእኅቶቿ ደናግል ጋር አስክትላት በአንድነት ተጓዙ። ሲጓዙም የንጉሥ ዳኬዎስን ወታደሮች አየቻቸው። ከእርሳቸውም ጋር የታሠሩ ክርስቲያኖች አሉ ወታደሮቹም አሥረው በቁጣ ይጎትቷቸው ነበር። ልቧም በሃይማኖቷ ፍቅር ነደደና ያን ጊዜ እንዲህ ብላ ዘለፈቻቸው የእውነት ፈጣሪን የካዳችሁ ልባችሁ የደነዘዘ እግዚአብሔር በመልኩና በአምሳሉ በፈጠራቸውና ስለእነርሱም ነፍሱን ለሞት አሳልፎ በሰጠላቸው ላይ ለምን እንዲህ ትሠራላችሁ።

ይህንንም በአለቻቸው ጊዜ ወታደሮች ተቆጡ ይዘውም ወደ መኰንኑ አቀረቧት እርሱም እንዲህ ብሎ ጠየቃት በእውነት አንቺ የተሰቀለውን የምታመልኪው ክርስቲያን ነሽን? እርሷም ስለእኛ የተሰቀለውን ክብር ይግባውና እርሱን አመልከዋለሁ ብላ መለሰችለት።

በዚያን ጊዜም ጽኑ ሥቃይን አሠቃያት በሥጋዋም እሳትን ጨመረ ከዚህም በኋላ ዘቅዝቆ ሰቀላት ከበታቿም አጤሱባት ከሃይማኖቷም ባልተናወጸች ጊዜ ራሷን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። በዚህ በታላቅ ሥቃይም ውስጥ ሳለች ራሷን በሰይፍ ቆረጧት። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ማርያም_እንተ_ዕፍረት

ዳግመኛም በዚህች ዕለት የማርታና የአልዓዛር እህት ቅድስት ማርያም እንተ ዕፍረት የእረፍቷ መታሰቢያ ነው።

በዘመነ ሐዋርያት በተመሳሳይ 'እንተ ዕፍረት' (ባለ ሽቱ) ተብለው የሚጠሩ 2 እናቶች ነበሩ:: ሁለቱም ስማቸው ማርያም ስለ ነበር ለመለየት እንዲያመች አንደኛዋን 'ማርያም ኃጥዕት (ከኃጢአት የተመለሰች) ሁለተኛዋን ደግሞ 'ማርያም እኅተ አልዓዛር በቢታንያ የነበረችው ብለው አበው ይጠሯቸዋል።

በሉቃስ ወንጌል ላይ የምትገኘው ከኃጢአት ሕይወት የተመለሰችው ስትሆን በዮሐ. 12:1 ላይ ያለችው የአልዓዛር እህት (ድንግሊቱ) ናት። ዛሬም የምናስባት ይህቺውን እናታችን ነው።

ቅድስት ማርያም መድኃኒታችን ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በሚያስተመርበት ዘመን በቢታንያ አካባቢ ትኖር የነበረች ድንግል ወጣት ናት። ወላጆች ባልነበረበት ቤት ውስጥ ታላቆቿ አልዓዛርና ማርታ አሳድገዋታል።

በቤተሰብ ደረጃ እንግዳን ይቀበሉ ነበርና ጌታችን ወደዳቸው። አልዓዛርን ከ72ቱ አርድእት: ማርያምና ማርታን ደግሞ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ቆጥሯቸዋል። ወንድማቸው አልዓዛር በታመመ ጊዜ ወደ ጌታ ልከው ነበር።

ያለ ጊዜው የማይሠራ ጌታ ባይመጣ አልዓዛር ሞተ። በ4ኛው ቀን አምላክ ሲመጣ ቅድስት ማርያም በጌታ ፊት ሰግዳ "እግዚእየ ሶበሰ ኀሎከ ዝየ እምኢሞተ እኁየ" "አንተ በዚህ በኖርክስ ወንድሜ ባልሞተ ነበር" ብላ አለቀሰች። (ዮሐ.11)

ጌታም ስታለቅስ ባያት ጊዜ አምላክነቱ አራርቶት አለቀሰ። ወዲያውም በስልጣነ ቃሉ አዞ አልዓዛርን አስነሳው። ከፋሲካ (ጌታ ከመሰቀሉ 6 ቀናት) በፊትም ቅዱሳኑ ለጌታ ግብር አገቡ። እርሱም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ታደመላቸው። (ዮሐ.12፥1)

በዚያም አልዓዛር ከጌታ ጐን ሲቀመጥ ቅድስት ማርያም ከጌታ ሥር ተንበርክካ ናርዶስ የሚሉትን የ300 ዲናር ሽቱ በጌታ ላይ አፈሰሰች። መዓዛ መለኮቱና ሽቱው ሲገናኝ "መልዐ መዓዛሁ" እንዲል የሚመስጥ ሽታ ቤቱን ሞላው።

በወቅቱ ይሁዳ ቢቃወምም ጌታ ምላሹን ሰጥቶታል። ቅድስት ማርያምንም "ማርያምሰ ኃርየት መክፈልተ ሠናየ ዘኢየኃይድዋ" ብሎ አመስግኗታል። ያስመሰገናት ቁጭ ብላ በተመስጦ መማሯ ብቻ እንዳልሆነ አባ ሕርያቆስ መስከሯል።

ሲመክረንም "አርምሞንና ትዕግስትን እንደ ማርያም ገንዘብ እናድርግ" ብሎናል። (ቅዳሴ ማርያም) ቅድስት ማርያም በጌታችን ክርስቶስ በኅማሙ ጊዜ ሲቀብሩት ነበረች። ትንሳኤውንም ዐይታለች።

ከጌታ እርገት በኋላም መንፈስ ቅዱስን ተከትላ ለወንጌል አገልግሎት ተግታለች። ቅድስት እናታችን ማርያም እንተ ዕፍረት ዛሬ እንዳረፈች እናዘክራለን።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምትና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
@petroswepawulos
@petroswepawulos
@petroswepawulos