Daily Wisdom ደይሊ ዊዝደም
350 subscribers
83 photos
6 videos
2 files
93 links
በጊዜውም አለጊዜውም ቃሉን ስበክ።
#ትምህርት
#ስብከት
#ታሪክ
#መፅሐፍት
#ይከታተሉን
አጋር @ws_youth
Download Telegram
#የህይወት_ማዕዶት
🍕🍕🍕🍕🍕
ሚያዚያ 16/2012 ዓ.ም

Lockdown
#ኳረንታይን!!

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ ባላችሁበት ፀጋና ሰላም ይብዛላችሁ።

👆የተወደዳችሁ ይህ መልዕክት በውስጥ መስመር ከተወደዱ አንድ የቤተክርስቲያናችን አባል በእንግሊዘኛ የተላከልኝን መልዕክት በጣም ጠቃሚ መልዕክት ስለሆነ እንድለቀው አስፈቀጄ በሚከተለው መልኩ አብላልቼ እንድታነቡት አቅርቤዋለሁ። ወንድማችንን ጌታ ይባርካቸው።👇

የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍል :- 1ኛ ቆሮ 15:1-11

መግቢያ :- መዘጋት / ኳረንታይን የሚለው ሐሳብ መንቀሳቀስ መከልከልን ለማሳየት እና በየቤታችን ከበራችን ቁልፍ መልስ መቀመጣችንን ለማሳየት ነው።
ሁሉም ነገሮች ባይዘጉም እንኳን በእኛ አውድ ግን ቤተክርስቲያን መዘጋቷ እና እቤታችን መሆናችን ይታወቃል። በእንደዚያ አየነት ከቁልፍ መልስ መንቀሳቀስ ሳይችል የኖረን ድንቅ ሰው ህይወት ለትምህርታችን የምንካፈልበት ሐሳብ ነው።

ሐዋሪያው ጳውሎስ ከሌሎች ሐዋሪያት ሁሉ ከኢየሱስ ጋር ከነበሩት ጋር ሁሉ ሳይቀር አንፀባራቂ የአገልግሎትን ገድል የፈፀመ ሁሌም የምናነሳው ሞዴል አገልጋይ ነው። እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ ብሎ ለመናገር ብርቱ ድፍረት ያለው በማያሳፍር ህይወትና አገልግሎት ያገለገለ ሰው ነው።

ሐዋሪያው ራሱ ስለራሱ ሲመሰክር እንደዚህ አለ “ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ የሆንሁ እኔ ነኝ፤ ለእኔም የተሰጠኝ ጸጋው ከንቱ አልነበረም ከሁላቸው ይልቅ ግን ደከምሁ፥ ዳሩ ግን ከእኔ ጋር ያለው የእግዚአብሔር ጸጋ ነው እንጂ እኔ አይደለሁም።”
  — 1ኛ ቆሮንቶስ 15፥10
#ከሁሉ ይልቅ መድከሙን አጉልቶ ያወራናል። ለትምክህት ያነሳው ሐሳብ መስሎን ልንስት ስንል የለም በእኔ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፀጋ ነው ብሎ ለፀጋው ክብርን ያስገባል።

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ :- ጳውሎስ ከማንም በበለጠ መጠነ ሰፊ የወንጌል ጉዞዎችን ያደረገ ፣ ውጤታማ ስብከቶችን የሰበከ እና በመጀመሪያዋ የቤተክርስቲያን ታሪክ ከየትኛውም ሐዋሪያ እና ሚሽነሪ በላይ ወንጌልን ያደረሰ/ያዳረሰ ሰው ነው። ለዚህም ማስረጃነት ማንሳት ካስፈለገን የሐዋሪያት ስራን ከ13 -28 ምዕራፍ በሐዋሪያው አገልግሎት ላይ ያተኮረ መሆኑ ትልቅ ትምህርት ይሰጠናል። እንደምታስታውሱ ሦስቱ የወንጌል ጉዞዎች ድንቅ ምስክር ናቸው።

ሐዋሪያው በአዲስ ኪዳን ካሉት 27 መፅሐፍ የእርሱ አበርክቶት ከፍተኛ ነው። 14 መፅሐፍትን አበርክቶልናል።
ታዲያ ይሄን ሁሉ ስራ የሰራው ጳውሎስ በጣም ድንቅ መልዕክቶችን ያበረከተልን ተገልሎ ወይም በእስርቤት (በኳረንታይን) ውስጥ ሆኖ በነበረበት ጊዜ ነው።
እርሱ እንደውም እርሱን ማሰር እንጂ በውስጡ ያለውን ማሰር ፣ ወንጌልን ማሰር ፣ ቃሉን ማሰር እንደማይችሉም ተናግሯል። ፊሊጲሲዮስ በጣም የአዲስ ኪዳኑ ድንቁ የደስታ መፅሐፍ ላይ ከእስር ቤት ሆኖ በፃፈልን መልዕክት እንደዚህ ብሏል

 “ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ።”
  — ፊልጵስዩስ 4፥13

ታላላቅ እውነቶችን ባወራበት በኤፌሶን መፅሐፍ ላይ ደግሞ ከዚያው እስርቤት ሆኖ

"“እንግዲህ በእኛ እንደሚሠራው ኃይል መጠን ከምንለምነው ወይም ከምናስበው ሁሉ ይልቅ እጅግ አብልጦ ሊያደርግ ለሚቻለው፥”
  — ኤፌሶን 3፥20

አስቡት እስርቤት ነው ያለው ግን እርሱ ግን እንደታሰረ ሰው አይደለም የሚያወራው። ይልቁንም ለእኛ እንደዚህ ይለናል :-

“ስለዚህ በክፉው ቀን ለመቃወም፥ ሁሉንም ፈጽማችሁ ለመቆም እንድትችሉ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ አንሡ።”
  — ኤፌሶን 6፥13
ጳውሎስ ታስሯል ካላችሁ አካሉ እንጂ በእውነታው እንደተፈታ ሰው ነው የሚናገረው።

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ :- አንዳንዶች የምታስታውሱ ትኖራላችሁ የገፈቱም ቀማሽ የነበራችሁ ሰዎችም አትጠፋም ከቅርብ ጊዜ በፊት ቤተክርስቲያናት በሀገራችን ተዘግተው ነበር። በስልጣን ላይ የነበሩትም እግዚአብሔር የለም ብለው በመሳለቅ በየአደባባዩ ያውጅ ነበር። ነገር ግን የቤተክርስቲያን ታሪክ እንደሚያወሳን በዚያ ጊዜ ቤተክርስቲያናት እጅግ ያበችበት ወይም የተቀጣጠለችበት ጊዜ ነበር። ቤት ለቤት በነበረው አገልግሎት በጣም አመርቂ ውጤትን ያስመዘገቡበትም ጊዜ ነበር።

ሁሉ ነገር በተዘጋበት የእግዚአብሔርን መንግስት በተሻለ አስፋፍተው ነበር።

በተመሳሳይ አሁን ቤተክርስቲያን እንደ ስደቱ ጊዜ በመንግስት አስገዳጅነት ሳይሆን ያው በዚህ አስከፊ በሽታ ምክንያት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምክንያት ተዘግታ አለች። ይሄን ጊዜ ግን ልናባክነው አይገባም እጅጉን አስደናቂ ነገር ልንሰራበት ይገባል።

እኛ በብዙ አቅጣጫ በጣም ነፃ ሰዎች ነን።

በህይወታችን ላይ ትልቁ ዋጋ ያለው ነገር ቢኖር ጊዜ ነው። በጊዜያችን ማንኛውንም ነገር ልንሰራበት እንችላለን።  ወዳጆቼ ልክ እንደ ሐዋሪያው ጳውሎስ ጊዜአችንን በሚገባ በመጠቀም የተሻለ ነገር ልናበረከትበት በምንችልበት ሁኔታ ውስጥ ማሳለፍ የሚገባን ሰዓት ቢኖር አሁን ነው።
.
.
ትላልቅ መፅሐፍትን እና መልዕክቶችን ሐዋሪያው የፃፈልን ከእስር ቤት ሆኖ ነው። ዛሬም በዚህ ጊዜ እኛ ውስጥ ያሉትን ለትውልድ የሚጠቅሙትን ትልልቅ ሐሳቦች እና ራዕዮች የምንወልድበት ጊዜ ቢኖር አሁን ነው።

በዋጋ የማይተመነውን ጊዜ ዋጋ ላለው እና ዋጋ ለሚኖረው ነገር መስዋዕት እናድርገው። አጋጣሚውን ለመልካም መጠቀም የምንችል የክርስቶስ አዕምሮና ልብ ያለን ሰዎች ነን እና በዚያው አቅማችን መገለጥ ይሁንልን።

እግዚአብሔር በመንፈሱ ፀጋውን ያብዛልን❤️

🙏አብዝተን እንፀልይ ፣ መፅሐፍቅዱሳችንን እናንብብ🙏

ቡሩካን ናችሁ!

እወዳችኋለሁ!

አዘጋጅቼ ያቀረብኩላችሁ ፦

አገልጋያችሁ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችሁ ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
#የህይወት_ማዕዶት!
🍞🍞🍝🍝🍝🍝🍞🍞🍉🍍🍍
ሚያዚያ 17/2012
**************
#ለመልካም_ነው#ለበጎ_ነው!

“እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን።”
  — ሮሜ 8፥28

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
👇👆👇👆👇👆👇👆👇
የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ :- እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ያለእግዚአብሔር ፈቃድ የሆነ ወይም እርሱ ሳያውቀው የተከወነ አይደለም። እንዚአብሔርን ለሚወዱ እንደሐሳቡ ለተጠሩ ነገር ሁሉ ተያይዞ ለበጎ ይደረግላቸዋል ማለት እንልመድ።

ውዶቼ :- አሁን ላይ ቤተክርስቲያን ዘግተን ቤታችን ማምለካችን ፣ በሚዲያዎች አምልኮ እና ቃል መካፈላችን እንቅስቃሴያችን ተገድቦ ስታየው መዓት መጣብን አትበል እኛ እግዚአብሔርን ለምንወደው ለበጎ ነው በል።

የማይሳሳት እግዚአብሔር ስላለህ በተሳሳተ አለምና የተሳሳተ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎችም መሃል ብትሆን ለበጎ ነገር መቀየር የሚችል አምላክ መኖር አትርሳ።
አንድ ምሳሌ አነበብኩልህ እግዚአብሔር_አይሳሳትም በሚል የቀረበ ነው።

👍በአንድ ወቅት አንድ ንጉስ አንድ የወንድ አገልጋይ ነበረው ይህ አገልጋይ ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ለንጉሱ እንደዚህ ይላል! ንጉስ ሆይ ተስፋ አትቁረጥ እግዚአብሔር አይሳሳትም የሚያደርገው ሁሉ ትክክል ነው ይለዋል።

👍 አንድ ቀን ወደ ደን ወጡ ከዛ የጫካ እንስሳ ንጉሱን አጠቃው አገልጋዩም እንስሳውን ገደለው ሆኖም ግን የንጉሱን አንድ ጣት ከመበላት አላዳነም: ንጉሱም እንደዚ አሉ እግዚአብሔር መልካም ቢሆን ኖሮ በአውሬ ባልተጠቃው ጣቴንም ባላጣው ነበር አሉ፡

👍አገልጋዩም መለሰ ንቀት አይሁን አሁንም ቢሆን የምለው አንድ ነገር ነው እግዚአብሔር መልካም ነው በስራውም አይሳሳትም፡

👍 ንጉሱም በመልሱ ተቆጣና አገልጋዩን ወደ እስር ቤት እንዲወሰድ አዘዘ፡ ወደ እስርም እየወሰዱት በድጋሚ ንጉሱን አለው እግዚአብሔር መልካም ትክክልም ነው:

👍በሌላም ቀን ንጉሱ ብቻውን ወደ አደን ወጣ ሰውን ለመስዋት የሚያቀርብ አንድ የዱር ሰውም አገኘው ሰውየውም ንጉሱን በመሰዊያው አቅርቦት አንድ ጣት እንደሌለው ለአማልክቶቹም ለመሰዋት ሙሉ እንዳልሆነ ባወቀ ጊዜ ፈታው፡

👍ንጉሱም ወደ መንግስቱ ሲመለስ አገልጋዩን እንዲፈቱት አዘዘ ንጉሱም ገጓደኛዬ በእውነት እግዚአብሔር ዛሬ ለኔ መልካም ሆነልኝ ልገደል ነበር ግን በዛች ባጣዋት አንድ ጣት ምክንያት በነፃ ተለቀኩኝ ግን ጥያቄ አለኝ እግዚአብሔር

👍መልካም ከሆነ አንተን ወደ እስር እንድከትህ ለምን ፈቀደ አለው አገልጋዩም እንዲህ ሲል መለሰ ጌታዬ ሆይ እኔን እስር ቤት ባትከተኝ ኖሮ ከ አንተ ጋር መሄዴ አይቀርም ከዛ ለመስዋህት እቀርብ ነበር ምክንያቱም እኔ አካሌ ሙሉ ነው፡

👍እግዚአብሔር የሚሰራው ሁሉ ትክክል ነው ተሳስቶም አያውቅም ሁልጊዜ በህይወታችን ጥሩ ያልሆነ ነገር ይገጥመናል ግን ሁሉም በምክንያት ለበጎ ነው።
መቀመጣችን ለበጎ ነው። ይሄ ቫይረስ የመጣውም ለበጎ ነው።(ይሄን ስታነብ ትንሽ ጎምዘዝ ብሎሃል አይደል ግን ለበጎ ነው።) እየሆነ ያለውና የሚሆነው ሁሉ ለበጎ ነው።
ዮሴፍ እነርሱ ክፋ አስበው አደረጉት እግዚአብሔር ግን ለመልካም አደረገው እንዳለ። ከምታልፍባቸው የህይወት ጎዳናዎች መልካም ነገር ማውጣት የሚችል መልካም አምላክ እንዳለ አትርሳ። ነገሮች ለመልካም እየተሰሩ እንጂ እየተበላሹ አይደሉም።

በጣም የምወዳችሁ ቤተሰቦቼ እግዚአብሔር አይሳሳትም ብላችሁ ለራሳችሁ ለሁኔታው ፣ ለሰው ሁሉ ተናገሩ። እግዚአብሔር ብቻ ነው ከሞተ ነገር ማር ማውጣት የሚችለው ፣ ከወደቀ ሰው ህይወትን ማምጣት የሚችለው ፣ እግዚአብሔር ብቻ ነው በእሳት ውስጥ እና በአስቸጋሪ ውሃ ውስጥ መንገድ የሚያበጀው። እናም እግዚአብሔር ነገሩን ለመልካም ፣ ለበጎ ይሰራዋል እርሱም አይሳሳትም። አሜን !!
@WorkofGrace
መልካም ቀን ይሁንላችሁ!
💟💖💖💖💖💖
እወዳችኋለሁ

ቡሩካን ናችሁ!!

የእናንተው አገልጋይ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችሁ
                    ──•◈•──
        @WorkofGrace
#የህይወት_ማዕዶት!

ሚያዚያ 19/2012 ዓ.ም ጠዋት 2:00

ርዕሱ :- በአንበሳ እንዳትበላ!

በቢኒያም ኃይሉ መጋቢ!

የመልዕክቱ ክፍል 1ኛ ነገ 13:1-24!

***//****************
መግቢያ!

ማንም ሰው በተሳሳተ ውሳኔ ላይ ሆኖ ወይም የእግዚአብሔር ቃል ጥሶ ፣ ባለመታዘዝ መበላት አይፈልግም። ዳንኤል ከአንበሳ አፍ የተረፈ የእግዚአብሔር ሰው ነው። ዛሬ የማካፍላችሁ ቃል  ደግሞ በአንበሳ ስለተበላ ነብይ የሚያወራ ነው።

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ ይሄን ሐሳብ በማንኛው የዕለት ተዐለት እንቅስቃሴዎቻችን እግዚአብሔር ምን ብሏል ? እግዚአብሔርስ ምን ይላል ? የሚለውን ሐሳብ የሚያስተጋባ ሆኖ ታገኙታላችሁ።

የተበላው ነብይ ለምን ተበላ ?
ነብዩ በጣም የሚገርማችሁ የእግዚአብሔርን ሐሳብ የሚያገለግል ሰው ነው። እግዚአብሔር ያለውን የሚያስፈፅም ፣ እግዚአብሔር ያለውን ከማድረግ የማይመለስ ሰው እና ቆራጥ ሰው ነው። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ትዕዛዝ የሚያስወጡ በእግዚአብሔር ስም እየማሉ ፣ እየተነበዩ የሚናገሩ ሰዎች ተገኙ! ከሰማው የእግዚአብሔር ቃል ይልቅ የሐሰተኞችን ድምፅ ሰማ! ክፍሉን አንብቡት አገልግሎቱ ጥሩ አጨራረሱ ግን በአንበሳ መበላት ሆነ። ታዲያ እኛ ምን እንማራለን ፦
#በተሳሳተ መንገድ እና ውሳኔ ላለመሄድ !

1. እግዚአብሔር በቃሉ የነገረህ ፈቃዱ ላይ ብቻ ተጣበቅ።
የእግዚአብሔር ፈቃድ ማለት እግዚአብሔር አንተ/ቺ ፣ እርሶ ፣ እኛ እንድንሆንለት የሚፈልገው ነገር ነው። ሞኝ መሆን የለብህም ምክንያቱም ሞኝ የራሱን ፈቃድ በመከተል ይጎድላል። በውጤቱም ኪሳራን ይከናነባል።
“አላዋቂዎችን ከጥበብ መራቅ ይገድላቸዋልና፥ ሰነፎችንም ቸልተኛ መሆን ያጠፋቸዋልና።”
  — ምሳሌ 1፥32
በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ እግዚአብሔር ምን ይላል ? የእግዚአብሔርስ ፈቃድ ምንድን ነው ? ምንስ ብሏል? በል!
ያወቅከውን የእግዚአብሔር ፈቃድ በፀሎት ልታስቀይረው አትችልም። ይልቁን መፀለይ ያለብህ ፈቃዱን እንድንፈፅም ፀጋ ይብዛልኝ ብለህ ነው።

2.በህይወታችን ትልቅ ልዩነት የሚያመጣው መታዘዝ እንያዝ!

መታዘዝ አራት ፊደል ነች ግን ብዙ ሰው የሚከብደው ይሄንን መፈፀም ነው። አትብላ በመጣህበት መኔገድ አትመለስ የሚለውን ትዕዛዝ መፈፀም የህይወት ጎዳናው ነበር። ነገር ግን ያንን መጣስ ደግሞ የሞት መንገድ ነው። ያለአግባብ ህይወታችሁን ለምን ትገብራላችሁ ? ለምንስ ያልተገባ ዋጋ ትከፍላላችሁ? ሰው በመታዘዝ ጥቂት ነገር ከመክፈል ይልቅ ባለመታዘዝ ትልቅ ዋጋ የሚከፍልበት ጎዳና ላይ ለምን መግባት እንደሚመርጥ አላውቅም። ይሄ ትልቅ ድንዛዜ ነው። እግዚአብሔር ይንቀልልን።

ውዶቼ :- እኔ እንደ አንድ እንደ እግዚአብሔር ሰው የምመክራችሁ እናንተ ከምትፈልጉት ይልቅ እሱ ያዘዛችሁ ይበልጥ የተሻለ ነገር አለውና ያንን ብቻ አስቡ! ያንን ብቻ አስቀጥሉ! ታተርፋላችሁ። አሁን ባለንበት ሁኔታ እንኳን የጤና ባለሞያዎችን መስማት እና መታዘዝ ይጠቅመናል እንጂ አይጎዳንም። የሰማዩ እና የቃሉ ትዕዛዝ ደግሞ እንዴት አትራፊ አያደርገን።

3. ከውሸተኞች እና ከውሸት ወሬ ራስህን ጠብቅ!

ብዙ ሰውን ዛሬ ላይ ገደል የከተተው እና ከመስመር ያወጣው ምንድን ነው ካላችሁ በእግዚአብሔር ስም የሚምሉ ውሸተኞች በመንገድህ ይገጥሙሃል። እግዚአብሔርን ምስካሪ እየጠሩ በተሳሳተ መረጃ እና በተሳሳተ ወሬ በአንበሳ ሊያስበሉህ ይፈልጋሉ። 
 
ሀገራችን በሚገርማችሁ መልክ ሀሰተኛ መረጃን ለመከላከል በሚል በወንጀለኝነት የሚያስጠይቅ ህግ ማውጣቱን ታውቃለህ። ባለፋት ጥቂት ወራት ሀገሪቷ የታመሰችው ሰዎች የተፈናቀሉት ፣ የተገደሉት ሌሎች እኩይ ተግባራት የተከናወኑት በእውነተኛ መረጃ ሳይሆን "በበሬ ወለደ" ውሸቶች መሆኑን አትርሳ።

ህይወትህን እና ውሳኔህን ከሚያዛባ "በሬ ወለደ" ውሸቶች ራስህን ጠብቅ።
“እውነትን ግዛ አትሽጣትም፥ ጥበብን ተግሣጽን ማስተዋልንም።” ምሳሌ 23፥23

ማናችንም ራሳችንን ከውሸት ካልጠበቅን በስተቀር የራሳችንን ህይወት አደጋ ውስጥ እንከታለን። የራሳችሁ ህይወት ጠባቂዎች ራሳችሁ ናችሁ።

ሀሰት ከሀሰት አባት የሚመነጭ ነገር ነውና ማንኛውንም ነገር ስትሰሙ ምንም አይነት ነገር ከመነገራችሁ እና የትኛውንም ውሳኔ ከመወሰናችሁ በፊት መረጃው እውነት መሆኑን ለማወቅ በራሳችሁ መንገድ ሞክሩ። ሰይጣን ለሄዋን ውሸቱን ነገራት የሞተችው ግን እርሷ ናት። ውሸት የማንንም ህይወት ከመጉዳቱ በፊት የሚጎዳው የእኛን ህይወት ነው።

ነብዩ ከሰማው ከእግዚአብሔር ቃል ይልቅ ፣ ከተረዳው ከእግዚአብሔር ፈቃድ ይልቅ በእግዚአብሔር ስም እየተማለ የተነገረውን ውሸት ሰምቶና አምኖ ያንን በማድረጉ ህይወቱን አጣ ! በአንበሳም ተበላ! አድነን!

መደምደሚያ!

 አድነን ማለት አያድነንም የሚያድነን ትክክለኛ ውሳኔዎችን ለመወሰን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማወቅ ፣ ባወቅነው የእግዚአብሔር ፈቃድ ላይ መታዘዝን ማሳየት ፣ እግዚአብሔርን ለምስክርነት እየጠሩ ከሚመጡ ውሸቶች ራስን መጠበቅ ፣ በእነዚያ ውሸቶችም ላይ ተነሳስቶ እርምጃ አለመውሰድ! በአንበሳ ከመበላት ያተርፈናል። የዘንድሮ አንበሳ ምናልባት ራሱ አንበሳው ላይሆን ይችላል ግን ህይወታችንን ሊያሳጣ የሚችል ፣ ህይወታችንን ሊያመሰቃቅል የሚችል መንገዳችን ላይ ያደባ ክፋ መኖሩን አንርሳ!

ፀሎት

እግዚአብሔር ሁላችንን ይጠብቀን! ደግሞም ይራራልን ! በፈቃዱ መንገድ ራሳችንን ከሀሰት ጠብቀን የምንሄድበትን ፀጋ ያብዛልን! አሜን! ከዚህ ክፋ ወረርሽኝ ምድራችንን ይታደጋት ፣ እኛ እና ቤታችንን በደሙ ይሸፍነን! አሜን!
ሁልጊዜም ፈቃዱን ብቻ እውነቱን ብቻ የምንከተልበትን ማስታዋል ያድለን። አሜን!

#በአንበሳ እንዳትበላ!

🙏ፀሎት እናብዛ🙏

ቡሩካን ናችሁ!

እወዳችኋለሁ

የእናንተው አገልጋይ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችህ ነኝ!
#የህይወት_ማዕዶት!
🍞🍝🍞🍝🍞
ማለዳ 2:00 መልካም ንባብ እና ውሎ!
*//***********
#ፍፃሚያችሁ የምርጫችሁ ውጤት ነው።

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

“አብራምም እግዚአብሔር እንደ ነገረው ሄደ፤ ሎጥም ከእርሱ ጋር ሄደ፤ አብራምም ከካራን በወጣ ጊዜ የሰባ አምስት ዓመት ሰው ነበረ።”
  — ዘፍጥረት 12፥4

ፍፃሜ መዳረሻ ላይ በሚደረግ ውሳኔ የሚገኝ ሳይሆን መነሻችሁ ላይ የምትወስኑት ውሳኔ ውጤት ነው።
👆👇👇👆
#እሺ ወይም እንቢ !

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ
አብርሃም ያለበት ዕድሜ የህይወቱን ፍፃሜ የሚጠብቅበት እንጂ ህይወትን እንደ አዲስ የሚጀምርበት አልነበረም። ሆኖም ግን እንደ አንድ ወጣት ልጅ እግዚአብሔርን በአዲስ ጉልበት ለመታዘዝ ወሰነ። አዲስ ጉልበት ያለው ዕድሜ ላይ ሳይሆን ልብ ላይ ነው። ሰባ አምስት አመቱ ላይ እምቢ የሚልባቸው ተፈጥሯዊም ፣ አካላዊ ገደቦች እያሉበት እርሱ ግን እሺን መረጠ።

የህይወታችሁን ፍፃሜ የሚያሳምርላችሁ ዛሬ ላይ የምታሳልፏት ለእግዚአብሔር ትዕዛዝ ያላችሁ "እሺታ" ነች።

እምቢ ለማለት ከሚያስችሏችሁ ገደቦች ይልቅ እሺ እንድትሉ የሚያስችላችሁን የእግዚአብሔርን አቅም ተመልከቱ።

ውዶቼ :- እግዚአብሔር እንዲህ እና እንዲያ አደርጋለሁ ብሎ የሚናገረው የእናንተን የኢኮኖሚ ፣ የእድሜ ፣ የትምህርት ዝግጅት ፣ ዕውቀታችሁን ፣ ያላችሁን ጡንቻ ወዘተ ታምኖ ሳይሆን ራሱን ታምኖ ነው። እናስ ካላችሁ እናማ እሱ ለሚለን ነገር ያላችሁበትን የትኛውንም ሁኔታ ሳታዩ "እሺ" በሉት። ሊያውም ያለምንም ቅድመ ሁኔታዎችም ጭምር።

ብዙዎቻችን ከእግዚአብሔር ዘላለማዊ አጀንዳ የጎደልነው እምቢን መርጠን ነው። በእምቢታችን ውስጥ እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ ቢሆንም ሊሰራ አይችልም።
 
እምቢ ማለት ለእግዚአብሔር ትዕዛዝ የነገን መልካም ፍፃሜ ማጣት ማለት ነው።

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ :- ሁላችንም ምርጫ አለን።

አብርሃም እግዚአብሔር ተው ያለውን ለመተው የሚከፈለውን ዋጋ ከፍሎ ሲጓዝ እግዚአብሔር ደግሞ ለአብርሃም ከተወው ጋር የማይነፃፀር ሰማያዊ አቅርቦትን ለቀቀለት።

መታዘዝ በመተውና በመከተል መካከል ያለ ውስጣዊ ግብግብን የሚያመጣ ነው። የእናንተም አሸናፊነት በዚያ ግብግብ ውስጥ ለእግዚአብሔር እሺ ማለትን በመምረጥ እና ያንኑ እሺታ በመኖር ላይ ይመሰረታል።

🙏ፀሎት🙏

አባት ሆይ አንተን በመውደድ እና በማፍቀር ህይወታችንን መምራት እንድንችል የበለጠ ፀጋ ይብዛልን።
አባት ሆይ አንተን በመታዘዝ አንተን እሺ በማለት ፍፃሚያችንን ውብ ማድረግ የምንችልበትን መንፈስ አብዝተህ ጨምርልን እኛም ዋጋውን ከፍለን ለመጓዝ የፈቀድን እንድንሆን ፀጋ ይብዛልን።

 🙏አብዝተን እንፀልይ🙏

ቡሩካን ናችሁ!

😍እወዳችኋለሁ😍

የእናንተው አገልጋይ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችሁ።
👍👍👍👍👍👍👍
ምሽት ከ1:00 -2:00 ጌታን በምናመልክበት እና ቃል የምንሰማበት ሰዓት ላይ እንገናኝ
❤️❤️❤️❤️❤️❤️❤️
#የህይወት_ማዕዶት
🍔🍔🍔🍔
#ትልቁ_ሀብታችን!

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

ሚያዚያ 21/2012 ዕረቡ ማለዳ

“እኔ ግን በቸርነትህ ታመንሁ፥ ልቤም በመድኃኒትህ ደስ ይለዋል።”
  — መዝሙር 13፥5

ሀብት ስንል ሊመነዘር የሚችል የተከማቸ ጠቃሚ ነገር ማለት ነው። የእግዚአብሔር ቃል በጣም ውድ ከምንም ነገር በላይ የከበረው ሐብታችን ነው። ዕድሜ ልክ በእያንዳንዱ ህይወታችን ብንመዝረው የማያልቅ ፣ የማይጎድል ሐብት ነው።
ዳዊት በመዝሙሮች እጅግ እልፍ የበለፀጉ ቃሎችን በመግለፅ እና በመዘመር የሚያክለው የለም። እየዘመረ የእግዚአብሔርን ባህሪ ያወራናል። ስራውን እያደነቀ እግዚአብሔርን ያስተዋውቀናል።
ዳዊት ከላይ ያነበብኩላችሁን ቃል ምዕራፋ ሲጀምር ምሬትን የሀዘን እንጉርጉሮን እያሰማ ነው የሚጀምረው። ለምን ረሳህኝ በሚል በጭንቀት ተራራ ላይ ተቀምጦ ነው ፣ በአሰቸጋሪ የህይወት ሁኔታ ውስጥ ሆኖ እያለቃቀሰ ነው። ታዲያ ፀሎቱን እንደዚህ የጀመረ ሰው እንዴት እግዚአብሔርን እያከበረ እና  ምስጋናዋን እያቀረበ ፣ እንዴት ስለቸርነቱ እና ስለመልካምነቱ ዘመረ የሚለውን ሐሳብ ስታነቡ ከመደነቅ ውጪ ምንም አማራጭ የላችሁም።
ዳዊት የሚያለቅስበት ምዕራፍ ውስጥ ነው ያለው ፣ ህመም ውስጥ ነው ነገር ግን በአንተ ቸርነት እታመናለሁ ፣ ልቤም በአንተ መድሃኒትነት ደስተኛ ነኝ አለ።

ዝማሬዬን አላቋርጥም  ምክንያቱም በቸርነቱ ባለፀጋ የሆነ ደግሞም በለጋሽነቱም ባለፀጋ የሆነ አምላክ አለኝ የሚል ነው የዳዊት ዝማሬ።

- ዳዊት ጥያቄ ስለሌለው ሳይሆን የሚያመሰግነው ፣ ጥያቄውን አልፎ ነው የሚያመሰግነው። በህይወቱ የነበሩ ጥያቄዎች ፦
* “አቤቱ፥ እስከ መቼ ፈጽመህ ትረሳኛለህ?
* እስከ መቼስ ፊትህን ከእኔ ትሰውራለህ?”
 *እስከ መቼ በነፍሴ እመካከራለሁ?
*ትካዜስ እስከ መቼ ሁልጊዜ ይሆናል?
*እስከ መቼ ጠላቴ በላዬ ይጓደዳል?”
 *አቤቱ አምላኬ፥ እየኝ ስማኝም፤
*ጠላቴ፦ አሸነፍሁት እንዳይል፥”
  *የሚያስጨንቁኝም እኔ ብናወጥ ደስ እንዳይላቸው፥
* ለሞትም እንዳልተኛ ዓይኖቼን አብራ።”
ዳዊት በጌታ እንደተተወ እያሰበ ነበር። ነገር ግን ሲጨርስ እግዚአብሔር የማይጥል የማይረሳ መሆኑን በቃሉ ያንፀባርቀዋል።
እርሱ ከእኛ ጋር ለመሆን እስከመጨረሻው እንደማይተወን ቃል ገብቶልናል።
ኢየሱስ እኔ እስከዓለም ፍፃሜ ድረስ ከእናንተ ጋር ነኝ ብሎ በቃሉ ዛሬም ያበረታናል። በአለም ላይ ብዙ መከራን ሊገጥመን ይችላል እኛ ግን አለምን በክርስቶስ ማሸነፋችንን እንዳንረሳ እርሱ በመስቀል ላይ ለእኛ ሲል ተሸንፎ አሸንፎልናል። የእርሱ ትንሳኤ ደግሞ ለእኛ አዲስ ህይወትን ሰጥቶናል። እኛ ደግሞ የእርሱ አካል ነን።
 
ዳዊት በጥያቄው አልቀጠለም ነገር ግን ከእርሱ የጥያቄ ግዝፈት ይልቅ ግዙፍ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቸርነት አጉልቶ ሲያወራው እናያለን።

ዳዊት በመጨረሻ በቸርነቱ እና በመሃሪነቱ እየተደሰትን እንሂድ። እርሱን እናግዝፈው ብሎ ሲያወራን እናየዋለን።

እኔም እላችኋለሁ ከችግሩ ይልቅ ቸርነቱን እንዘምር። ከታመመነው ይልቅ መድሀኒትነቱን እንስበክ።

የማያልቅው የሚመነዘረውን ትልቁን ሀብት ቸርነቱን አውጁ! ቸርነቱን አውሩ!  መድሃኒቱን አውጁ!

ማንኛውንም ነገር በልመና እና በፀሎት ከምስጋና ጋር ጥያቄያችንን እናቀርባለን እንጂ በአንዳች አንጨነቅም። ቸርነቱን እና ምህረቱን እንዘምራለን እናወራለን።
ልክ እንደ ዳዊት እግዚአብሔር እንደማይረሳ ከዚህ በፊት በክፋ ቀን የደረሰልን አምላካችን እግዚአብሔርን እናስታውስ።
በመድሃኒትነቱ እንደሰት!

ፀሎታችንን በለቅሶ ብንጀምርም ስንጨርስ ግን በምስጋና መደምደም አለብን። ስንጀምር ለምን ? ብለን ብንጀምር እንኳን ስንጨርስ ቸር ነህ ብለን መዝጋት አለብን።

የማያልቀው ፍቅሩን ይዘን እንቀጥል።የእግዚአብሔር የቸርነት እና የምህረት ብልፅግና የማያልቅ የተትረፈረፈ ነው።አሜን!
#ትልቁ ሀብታችን ቸርነቱ እና መድሐኒትነቱ ነው።

🙏አብዝተን እንፀልይ🙏

ቡሩካን ናችሁ!

እወዳችኋለሁ

የእናንተው አገልጋይ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችሁ ነኝ።

መልካም ቀን!!
#የህይወት_ማዕዶት
🍞🍕🍕🍕🍕
#ምህረቱ

በቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

ሚያዚያ 22/2012
ሐሙስ ማለዳ

“እነሆ ባሪያህ በፊትህ ሞገስን አግኝቶአል፥ ነፍሴን ለማዳን ያደረግህልኝን ምሕረትህንም አብዝተሃል፤ ክፉ እንዳያገኘኝና እንዳልሞት ወደ ተራራ ሸሽቼ አመልጥ ዘንድ አልችልም፤”
— ዘፍጥረት 19፥19

ሎጥ እሳት ሊዘንብ ባደመነበት ሰማይ ስር ሆኖ ክፋ እንዳያገኘው ስለበዛለት ምህረት እያወራ ፣ ደካማነቱን ባልረሳ መልኩ ደግሞ ማምለጥ እንደማይችል በመናዘዝ ሌላ ምህረትን ጠየቀ።

ምህረት ከክፋ እንዳመልጥ ካላሮጠኝ ከሰማይ ከሚዘንበው እሳት አይደለም ከሚያሳድደኝ ተራ ነገር እንኳን ማምለጥ የማልችል ደካማ ነኝ ነው ንግግሩ።

የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ የእግዚአብሔር ምህረት ካልበዛልን በስተቀር ፣ በጣም ደካማ ፍጥረት ነን። ነገር ግን የእግዚአብሔር ምህረት ዕድሜ መቀጠል ብቻ ሳይሆን ከለላ ይሆናል።

ይህች ሌሊት ለእኔ ልትነጋልኝ አይገባም ወይም መንጋት አልነበረባትም የምንልበት ጊዜ አለብን። አንድም ከምናልፍበት ከባድ ሁኔታ የተነሳ ሁለተኛ ከድካማችንን እና ሰርተነዋል ብለን ካሰብነው ኃጢያት የተነሳ። እንደምታውቁት የኖርነው ስራችን እየተቆጠረልን ቢሆን ኖሮ ማንም የመኖር መብት አልነበረውም ግን የኖርነው በምህረቱ እየደገፈን ነው።

ለዚህም ነው ሰቆቃው ኤርሚያስ
“ሔት። ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው፤ ርኅራኄው አያልቅምና።” ሰቆ. 3፥22

ያለበትን እውነት ስታስቡ ፣ እውነትም ብላችሁ ስለምህረቱ የምታመሰግኑበት ዕልፍ ምክንያቶች አሏችሁ።

የእግዚአብሔር ምህረት አይደለም ከታሰበብን ከተወረወረብንም ቀስትና ፍላፃ እየጠበቀን ነው እዚህ ያደረሰን። ፍላፆዋቹ ልባችን ውስጥ ሊገቡ እየተምዘገዘጉ ሳሉ ጋሻችን የሆነው የእግዚአብሔር ምህረት ቀስቱን ወደመጣበት እየመለሰው ዛሬ ላይ ደርሰናል።
“ለባሪያህ ከሠራኸው ከምሕረትህና ከእውነትህም ሁሉ ትንሽ ስንኳ የማይገባኝ ነኝ፤ በትሬን ብቻ ይዤ ይህን ዮርዳኖስን ተሻግሬ ነበርና፥ አሁን ግን የሁለት ክፍል ሠራዊት ሆንሁ።”
— ዘፍጥረት 32፥

ያዕቆብ ይሄን ያለው የተደረገለት ገብቶት ነው። ካልተደረገላችሁ ይልቅ የተደረገላችሁ ይበልጣል የምለው ያላችሁን ነገር ቆጥሬ ሳይሆን የማይቆጠረውን የበዛውን ምህረት አስቤ ነው። ምህረቱ ለእኛ ትልቁ ሀብታችን ነው። ትንሹ እንኳን የማይገባን ነበርን ነገር ግን የእግዚአብሔር ምህረት እንዲህና እንዲያ አደረገን አደረገልን።

ይሄ የእናንተ ቀን ነው። የሚያስቆዝም ነገር ቢኖርም እንዳትቆዝሙ ምክንያቱም የማያልፍ ቀን የለም። በማያኖር ሁኔታ ውስጥ እንድትኖሩ ምህረቱን አብዝቶ ዕድል ከሰጣችሁ እያከበራችሁት ደስተኛ ሆናችሁ ዋሉ።
ተንገዳግዳችኋል ማለት ትወድቃላችሁ ማለት አይደለም። ወድቃችኋል ማለት በዚያው ትቀራላችሁ ማለት አይደለም።
ምክንያቱም የወደቀም ይነሳል ፣ የሳተም ይመለሳል። እና ጊዜው ከባድ ነው አትበል በጊዜው ከባድነት ውስጥ የተሸከመ ምህረት ነው ከባድ። አንተ ፈፅሞ ተስፋ አትቁረጥ የእግዚአብሔር ምህረት ድላችን ነው።
መልካም ቀን
ቡርካን ናችሁ።
ከምታልፋበት ጎዳና ይልቅ የተያዛችሁበት የምህረት ክንዱ ይበልጣል።
❤️❤️❤️እወዳችኋለሁ❤️❤️
ቡሩካን ናችሁ!
የእናንተው አገልጋይ እና የጌታ ባሪያ ወንድማችሁ ነኝ።
#የህይወት_ማዕዶት!

ቀን ግንቦት 8/2012

ቅዳሜ

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

#የህይወት_ብርሃን!

ብርሃን ህይወት ነው። ብርሃን ጤንነት ነው። ብርሃን ራሱ ኢየሱስ ነው።

ኢየሱስን ለማየት(የእስራኤልን መፅናናት) ሲጠብቅ የነበረው ፃድቅና ትጉህ ሰው ፣ መንፈስ ቅዱስ በላዩ ላይ የነበረ ሰው ሲናገር እንደዚህ አለ “ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው።” ሉቃስ 2፥32
ኢየሱስ መገለጥን የሚሰጥ ብርሃን ጨለማን ያሸነፈ የማይጠፋ የዘላለም ፀኃይ ነው።

ኢየሱስ ራሱ ደግሞ እንደዚህ አለ ፦
“ደግሞም ኢየሱስ፦ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም ብሎ ተናገራቸው።” ዮሐ. 8፥12

ተስፋ ቢስነት ያለው ጨለማ ውስጥ ነው። በብርሃን የምትኖር ከሆነ አንተ ተስፋ ቢስ ህልም አልባ ፣ ህይወት አልባ አይደለም።

የእኛ ህይወት እና የህይወታችን ብርሃን እኮ ራሱ ኢየሱስ ነው።
ይህቺ አለም ላይ የሚኖር ማንም ሰው ያለተፈጥሮዊው ብርሃን መኖር አይችልም። ያለብርሃን ምንም ነን። በዚች ምድር ላይ የሚታይ ለውጥን የሚሰጠን እና የሚያመጣልን ብርሃን ነው። ያለብርሃን ዋጋም የለንም። ብርሃን ዋጋው ሊተመን የማይችል ውድ ነገር ነው።

የምንበላው ምግብ እንኳን ብርሃን ወደ ምግብነት ተቀይሮ መሆኑን አስተውለነው ይሆን። ቫይታሚን ዲን አምርቶ የሚሰጠን ራሱ ብርሃን ነው። ዝም ብለህ ሁሉንም ነገር ስታስበው በብርሃን ነው የሚንቀሳቀሰው እኛን ጨምሮ።

ዘላለማዊው ዘላለምህን የሚወስነውን ብርሃን ህይወት የሆነውን ኢየሱስን እንዴት ይዘህው ይሆን ?

በዚህ የዘመን ዕላቂ እና ሞት እንደቀላል ነገር በሚወራበት ይሄን ያህል ሺ ሰው ሞተ ብለው የሚዘግቡት ጋዜጠኞች ላይ እንኳን ምንም አይነት የሀዘን ፊት አታይም ድምፃቸው ውስጥ ድል የተገኘበት ሰበር ዜና የሚያወሩ እንጂ ስለሰው መርገፍ እየተናገሩ አይመስሉም።
በዚህ ሰዓት ብርሃን የሆነውን ፣ ህይወት የሆነውን ኢየሱስን ይዘሃል ወይ ?

“ለኃጢአተኛ የፍጻሜ ተስፋ የለውምና፥ የኀጥኣንም መብራት ይጠፋልና።” ምሳሌ 24፥20

ፍፃሜ የሚያምረው እና ዘላለምህ የሚቀየረው ክርስቶስን በማመን ፃድቅ ስትሆን ነው። መፅደቅ በስራ ሳይሆን መስቀል ላይ የተሰራውን በማመን ነው።

በዚህ ምድር ላይ ያለው የኃጣን መብራት እውነተኛው አይደለም ፌኩ ነው። መፅሐፍ ቅዱስ እንደዚህ

“በክፉዎች ላይ አትቅና፥ ዓመፃንም በሚያደርጉ ላይ አትቅና፤ እንደ ሣር ፈጥነው ይደርቃሉና፥ እንደ ለመለመ ቅጠልም ይረግፋሉና።” መዝ 37፥1-2

“ኃጥአን ከፍ ከፍ ብሎ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ለምልሞ አየሁት። ብመለስ ግን አጣሁት፤ ፈለግሁት ቦታውንም አላገኘሁም።” መዝ 37፥35 -36

ፃድቅ ግን
“ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል፥ እንደ ሊባኖስ ዝግባም ያድጋል።
በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተተክለዋል፥ በአምላካችንም አደባባይ ውስጥ ይበቅላሉ።” መዝ 92፥12 -13

ፃድቅ የሆንነው የህይወታችን ብርሃን የሆነውን ኢየሱስን ብርሃናችን እና ህይወታችን አድርገን ተቀብለነው ነው።

ምንም ጨለማው ቢበረታ ፣ ምንም አስጨናቂ ዘመን ላይ ብንሆን እኛ ተስፋቸው እንደሚጠፋና በጨለማ እንደተቀመጡ አይደለንም።

ኢየሱስ የህይወታችን ብርሃን ነው። ተስፋችንም ህያው ነው።

ከፀሎት መሰዊያችን አንራቅ ፣ መፅሐፍ ቅዱሳችንን ሁልጊዜ እናጥና ፣ ይሄም ጊዜ ያልፋል ፣ ኢየሱስ ተመልሶ ይመጣል።

ቡሩካን ናችሁ!
ኢየሱስ ይወዳችኋል።

❤️እወዳችኋለሁ❤️

join @workofgrace
@workofgrace
#የህይወት_ማዕዶት!

ግንቦት 9/2012

ዕሁድ!

#የተመለከተው_ብድራት!

ብድራት...ነገን የሚገኝን ክብር ፣ ነገን የሚመጣን ሽልማት እና ያልታየ ደስታ ማለት ነው።
ላለየህው ብድራት መከራ ልትቀበልለት አትችልም።
በክርስቶስ ኢየሱስ ላገኛችሁት ህይወት ብድራታችሁን አይታችሁታል ወይ ?

#ብድራቱን ያየው ሙሴ :-

“ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና።” ዕብ 11፥25-26

1.የግብፅን ገንዘብ ናቀ።

ይሄ በየቤተክርስቲያነችን እንዳለ እወጃና ፋከራ ቀላል አይደለም። ገንዘበ ባሪያዬ እንጂ ጌታ አይደለም። መጠቀሚያዬ እንጂ መጠቀሚያው አይደለሁም። በለው በይው ተባባሉ እንደማለት ቀላል አይደለም።
አሁን ሙሴ ያለው የገንዘቦች መንቀሳቀሻ የሆነው ቤተመንግስት ውስጥ ነው። የግብፅ ቤተመንግስት እንደ አንዳንድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንደሆኑ "ቸርቾች" ኦዲት አይደረግም። አስበው ቀጣይ ደግሞ አልጋ ወራሽ ነህ ።ያሻህን እየበላህ ፣ ያሻህን እየነዳህ ፣ ያሻህ ጋር እየሄድክ ፣ በኢኮኖሚ ክላስ በረራ ፈለሰስ እያልክ ፣ እረ ተወው የግል አውሮብላን ይዘህ እየተንቀባረርክ ልትኖርበት የምትችልበት የገንዘብ ክምችት ውስጥ ዋኝ ስትባል ያንን የመካድ አቅም የሚኖርህ ብድራትህን ካየህ ነው። ለዚያ ነው እጅህ ላይ ያለውን ጉባኤ መሃል ክጄዋለሁ ማለት እና በገንዘብ ገንዳ ውስጥ ሆነህ መካድ ይለያያል። የገንዘብ ጠቃሚነትን ሳይሆን የካደው ለገንዘብ ብሎ ክርስቶስን መካድ ነው ያልፈለገው። ገንዘብ የሚለው ነገር እንደፊደሉ ቀላል አይደለም የመግዛትና የመሰልጠን አቅም አለው። ጌታ ሆኖ የእግዚአብሔር ቦታ የመንጠቅ አቅም አለው። ሙሴ ገንዘብ ውስጥ ሆኖ ሲክደው ሲንቀው እኛን ብዙዎቻችንን እኮ ያመረቀንና ያሰከረን ምኞቱና ፍላጎቱ ነው። ገንዘብ ስጠን ብለን የምንፀልየው ራሱ ገንዘብ ከሰጠን በኋላ ራሱ ገንዘብ የሰጠንን ገልብጠን የተቀበልነውን ገንዘብ ጌታ ለማድረግ ነው። ሙሴ በገንዘብ ከመንደላቀቅ ይልቅ ስለክርስቶስ መነቀፍን ሙሴ በገንዘብ ፍቅር ከመጠፈር ይልቅ ስለክርስቶስ በመካራ መቀፍደድን መረጠ።

ወንጌል የድህነት እኮ አይደለም? ስትለኝ ሰማሁ ልበል የብልጥግናም ግን አይደለም። በነገራችን ላይ ብልጥግና ፓርቲ እንጂ ወንጌል አለመሆኑን ካልሰማህ የሚቀጥለው ምርጫ ላይ ትሰማለህ😂😂

በነገራችን ላይ መፅሐፍ ቅዱሳችን ገንዘብን ተቃውሞ ፅፎ አያውቅም ግን ለእርሱ መገዛትን እና ማስበለጥን እርሱን መውደድን ነው ተቃውሞ የሚፅፈው። ምክንያቱም የእጆችህን ስራ እባርካለሁ ካለ ያው ምንም ስያሜ ስጠው በገንዘብ ማለቱ ነው። ገበሬ የሚያመርተው ሊበላ ብቻ ሳይሆን ገንዘብ ሊያገኝበት ነው።
ሙሴ እኮ ድንቅ ሰው ነው። የሚገርምህ ነገር ከግብፅ ቤተመንግስት ካለው የገንዘብ ካዝና ይልቅ ለክርስቶስ በሚመጣ መነቀፍ ውስጥ ያለ ብልጥግና የበለጠ ነው።

ቶፕ 10 ባለጠጋዎች ውስጥ ስም ዝርዝርህ ባይወጣም። ቶፕ የእግዚአብሔር አገልጋዮችና የመንግስቱ ሰዎች ውስጥ ስምህ በእምነት መናቅን ካስተማሩት ጋር መነሳቱ አይቀርም። ዕብራዊያን 11 እኮ ቶብ የገንዘብ ባለፀጎችን ሳይሆን የዕምነት ባለፀጎችን ነው የሚያነሳው። #ኪሳቸው ውስጥ ገንዘብ ባታገኝም ደሆች ሆነው እንዳይመስል ብዙዎችን ባለጠጎች የሚያደርግ እምነት ያላቸው ሰዎች ናቸው።

ዘንድሮ ተምታቷል አገልጋዩን የገንዘብ ባለፀጋ የሚያደርግ ምዕመኑን ደህ የሚያደርግ እምነት ምን አይነት እምነት ነው።

#ሙሴ ምራቁን ጢቅ ብሎ የተፋበትን የግብፅ ገንዘብ እኛ ስናሳድደው እንዳንገኝ ጌታ ይርዳን። ሙሴ ምራቅ ጢቅ እየተባለበት ሊኖር ስለክርስቶስ መከራ ሊቀበል መረጠ።

2.ለጊዜው የሚገኝ የኃጢአት ደስታን ናቀ።

ይህቺ ግብፅ ዘማዊነት ህጋዊነት ያገኘበት ሀገርና ከተማ ነች። ኃጢያት ጊዜያዊና ደስታ አለው እርሱም ጊዜያዊና ዘላለምን የሚያሳጣ ደስታ ነው። በክርስቶስ የሚገኘውን እና መከራውን በመካፈል ውስጥ ያለውን ደስታ አላነፃፅረውም አለ።በኃጢአት ከሆነ ደስታ ለክርስቶስ መከራ መቀበል ዘላለማዊ ፌሽታ ነው ሙሴ ለምን አለ ካላችሁ ብድራቱን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ነው።ብድራታችሁን እዩ ፣ ብድራታችሁን ላይ ትኩረት አድርጉ። ጴጥሮስ ሁሉን ትተን ተከተልነህ ምን እናገኛለን ሲለው እንደዚህ አለው
“ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ እውነት እላችኋለሁ፥ ስለ እኔና ስለ ወንጌል ቤትን ወይም ወንድሞችን ወይም እኅቶችን ወይም አባትን ወይም እናትን ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን ወይም እርሻን የተወ፥“አሁን በዚህ ዘመን ከስደት ጋር ቤቶችን ወንድሞችንና እኅቶችንም እናቶችንም ልጆችንም እርሻንም መቶ እጥፍ፥ በሚመጣውም ዓለም የዘላለም ሕይወት የማይቀበል ማንም የለም።”
— ማርቆስ 10፥29-30

በቃ ብድራትህን ፣ ብድራትሽን ተመልከቺ!!

ቡሩካን ናችሁ!

ኢየሱስ ይወዳችኋል!!

@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

@workofgrace
@workofgrace
#የህይወት_ማዕዶት!

ግንቦት 10/2012

ሰኞ

#መስቀሉ_እና_ሰላሙ!

"ድንቅ ነው ለእኔ ጌታ ድንቅ ነው የእኔ ኢየሱስ...!
ይሄን መዝሙር ስትሰማ 12 ዓመት ደም ሲፈሰኝ ኖሬ 38 ዓመት እግሮቼን ታስሬ....ብለህ እንደምትቀጥል አውቃለሁ።

ዘማሪው "እኔን" በወከለ አይነት ስሜት እንደዘመረው እና ፈዋሽነቱን ለማሳየትም እንደሆነ አውቃለሁ። ግን እውነታው ከዚያ ያልፋል።
ኢየሱስ መስቀል ላይ የወጣው የፊልም ተዋናይ ሆኖ አይደለም። ኢየሱስ መስቀል ላይ የወጣው የሆነ ድራማ ለመስራት አይደለም። ከአዳም ጀምሮ የተበላሸውን ወደ ላይ ከእግዚአብሔር ጋር ወደ ጎን ከሰው ጋር ያለውን ሰላማዊ ህብረት ለማስተካከል ነው። ሰላምን ለመስጠት ሰላም ሊሆን ነው።

ደም ፈሶህም ሞትክ ፣ ደም ሳይፈስህም ሞትክ ፣ ሞት ሞት ነው ግን በኢየሱስ የተሰራውን የሰላም ስራ በማመን ከአብ ጋር ካልታረቅክ ሞትህ ድርብ ነው የሚሆነው። ብዙ ሰው ለፈውሱ አምኖት ለዘላለም ህይወቱ ግን ባለማመኑ ምክንያት ሁለት ሞትን ሞቷል እየሞተም አለ። ሐዋሪያው ጳውሎስ እንደዚህ አለ :- “....በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ሁሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና።”
— ቆላ 1፥19-20

የመስቀሉ ስራ ደሙን በማፍሰስ ሰላምን ማምጣት ነው። ሰውን ከተጣላው ከእግዚአብሔር ጋር ማስታረቅ ነው።
ስለዚህ የዚህ ሰላም ዋጋው ምንያህል ነው ?
#የሰላም ዋጋው ኢየሱስን ያህል ነው።

በኢየሱሰ ስራ የተገኘን ሰላም እንደቀላል መቁጠር ደግሞም እንደቀላል መተው ፈፅሞ የተሰራውን ስራ አለማወቅ ነው።
ልጁን ያስከፈለውን ይሄን ሰላም ልንጠብቀው ልንከባከበው ይገባል። ይሄ ሰላም ውድ ነው። ሰላም በማጣት እየተሰቃዩ ያሉ ሰዎችን ስታይ በእጅህ የገባው ሰላም በምንም ሊተካ አይችልም።
ኢየሱስ ራሱ "ሰላሜን እተውላችኋለሁ.." ብሏል ይሄም ማለት

#ይሄ ሰላም መለኮታዊ እና ዘላለማዊ የሰላም አለቃ የሆነው የኢየሱስ ባህሪ ተካፋይ የሆንበት ምስጢር ነው።

በብሉይ ኪዳን የነበረው ሊቀ ካህን ሲባርክ እንደዚህ ብሎ ነው :- “እግዚአብሔር ፊቱን ወደ አንተ ያንሣ፥ ሰላምንም ይስጥህ።” ዘኍልቁ 6፥26
አሜን ብለው ይሄዳሉ። የአዲስ ኪዳኑ የማይተካው ዘላለማዊ የሆነው ሊቀካህናችን ግን ራሱ እግዚአብሔር ነውና የራሱን ሰላም ሰጥቶን ሄደ። የቡሉይው ሊቀካህን ሲባርክ የአዲስ ኪዳኑ ግን ራሱን ሰጥቶ ፣ የእርሱን ሰላም በውስጣችን አድርጎት ነው የሄሄደው።

ደግሞም "በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ..." ይሄ የሚያሳየው ኢየሱስ ማንነቱን ነው የሰጠን። ራሱን ነው የሰጠን ። ይሄን ደግሞ ያለው "በአለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ..." ባለበት ምዕራፍ ነው...ይሄ ደግሞ የመከራ መጥፎ ባህሪው ስጋን ማጎሳቆሉ ብቻ ሳይሆን ውስጣዊ ሁከትን መፍጠሩ ፣ ሰላምን በመንሳት መንፈሳዊነታችን ላይ መረጋጋት እንዳይኖር ማድረግ። ውጪውን ሁከት ማድረጉ ውስጣዊ አለመረጋጋትን እና ሁከትን ለመፍጠር ነው። ታዲያ ኢየሱስ ቀጥሎ እንደዚህ አለ " ነገር ግን አይዟችሁ እኔ አለምን አሸንፌዋለሁ..." ኦ ክብር ለእርሱ ይሁን!!

ህይወታችን በሰላሙ ባለቤት እጅ መሆኑ ብቻ የትኛውንም መከራ ስቀን እንድናልፈው ይረዳናል።
ህይወትህ እንኳን በሰው እጅ ፣ በመንግስታት እጅ አልሆነ አሁን በዚህ ሰዓት ምን ትሆን ? ምንስ እንሆን ነበረ ?

ነገር ግንን በደንብ አስምሮበት ላነበበ አሁን ያለውን መከራ በሁለት ምክንያት ያሸንፈዋል
1. በእርሱ(በኢየሱስ) በመኖሩ ምክንያት
2. ኢየሱስ ያላሸነፈው መከራ እንደሌለ በመረዳት!
በዚህ ምክንያት ሰላም ይስጥህ ከሚል ምርቃት ባለፈ ሰላም የሆነውን ኢየሱስን በመያዝ ውስጣዊና መንፈሳዊ አለማችን ፍፁም መረጋጋት ውስጥ ይገባል።

ሰላማችን ዋጋው ኢየሱስ! ምንጩ ኢየሱስ! ቆይታውም ዘላለማዊ ነው።
ሰላማችሁን ከሚነጥቁ ነገሮች ራሳችሁን ጠብቁ።
ጳውሎስ ሰውን ሁሉ በሚሞግትበት ምዕራፋ በሮሜ መጀመሪያዎቹ ላይ እንደዚህ ይላል

“የሰላምንም መንገድ አያውቁም። በዓይኖቻቸው ፊት እግዚአብሔርን መፍራት የለም።”
— ሮሜ 3፥17-18

የሰላምን መንገድ አለማወቅ የኃጢያተኝነት ክርስቶስን ያለመረዳት እና እውነት መንገድ ህይወት የሆነውን እርሱን አለመከተልን ያሳያል።
የሰላም መንገድ ክርስቶስን የማወቅ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር የመፍራት መንገድ ነው።

“የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።”
— ሮሜ 14፥17

የእግዚአብሔር መንግስት ውስጥ ከሆናችሁ በመስቀሉ ስራ በደሙ ሰላም ነን። ሰላም ህይወታችን ነው።

ይሄን ሰላም ያላገኛችሁ ኑ ወደዚህ ሰላም ይሄን ሰላም የያዛችሁ ደግሞ ጠብቁት።
የሚሰማኝ ሰላም ብቻ ፣ ደህንነት ብቻ ያለው ዘማሪ ጌታ ይባርከው።
ምክንያቱም “እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፤”
ሮሜ 5፥1
እግዚአብሔር የሰላም አምላክ ነው። እኔም ልጁ የሰላም ልጅ ነኝ።
ሰላሜንም አልጥልም ደግሞም አላስነካም።
#ኢየሱስ ሰላም ነው።

ከገበያ የገዛሁት ሰላም የለኝም በመስቀላይ ከፈሰሰው ደሙ በእምነት የሸመትኩት የማያልቅ ዘላለማዊ ሰላም አለኝ።

ቡሩክን ናችሁ!

ኢየሱስ ይወዳችኋል።

@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

👉share it ሼር ይደረግ👈

💁‍♂💁‍♀ Work of Grace🙏
👉👉 @workofgrace
👉👉 @workofgrace
👉👉 @workofgrace
👆👆👆👆👆
🀄️🀄️ሉን JOIN US
Forwarded from LikeBot
#የህይወት_ማዕዶት!
(ዘውትር ማክሰኞና ሐሙስ ብቻ የሚቀርብ)

ግንቦት 11/2012
ማክሰኞ
ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

#ቃለ_እግዚአብሔር

ደስታዬ ያለው ፣ ህይወቴ ያለው ቃሉ ላይ ነው። ቃሉን አለማንበብና ከቃሉ መንፈስ ጋር አለመገናኘት ማለት የህይወትን መንገድ መሳት ፣ ከህይወት አለም መራቅ ነው። ቃሉ ህይወት ነው። ምግባችን ነው። ጥንካሪያችን ነው። ኃይላችን ነው።

“ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ፥ የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ።” ኤርምያስ 15፥16

የእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የራሱ የእግዚአብሔር ስልጣን ፣ ኃይል ፣ ተግባር እና ሰራዊት እንዳለ እናውቃለን።
ቃሉ ታዲያ ከእግዚአብሔር ሲወጣ ደግሞ የሚሰራውም ያው የራሱን የእግዚአብሔርን ያህል ነው። ቃሉ ማንነቱ ነው።
ቃሉ ያገኛቸው ሙሴ ከገዳይነት ወደ አዳኝነት ፣ ጳውሎስ ከአሳዳጆነት ወደ ሰባኪነት እንዲሁም ወደተሳዳጅነት ፣

ቃሉ ህይወት ቀያሪ ነው። ጨለማው ላይ ብርሃን ይብራ አለ እንጂ እንደቶማስ ኤዲሰን አምፖል ለማምረት አልሞከረም። እርሱ ቃል ውስጥ በቀን እና በጨለማ የሚሰለጥኑ ትላልቅ ብርሃናትና ከዋክብቶች አሉ።

ምድር ውስጥ ያሉትን ይገለጡ አለ እንጂ እንደ ገበሬ አላረሰም አልኮተኮተም አልዘራም። እርሱ ቃል ውስጥ ዘሩም ፣ ኩትኳቶውም ፣ የማብቀልና የማፍራቱም የመከታተሉም ነገር አለ።

ውሃ ውስጥ ያሉትን አዘዛቸው ተርመሰመሱ ያሌለ አይነት ዝርያ የለም ሁሉም ዝርያ የመጣው ከምንድን ነው ? ከቃሉ ውስጥ ነው።

ቃሉ ከአፋ ከወጣ መስራት ያለበትን መፈፀም ያለበትን ነገር እና አስፈፃሚ ሰራዊቶቹን ሁሉ ይዞ ነው የሚወጣው። እርሱ አለምን የሚያስተዳድራት ከአፋ በሚወጣው ቃሉ እና ቃሉ በሆነው ስብዕና ባለው በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ነው። አለቀ!

ቃለ እግዚአብሔርን ስትሰማ እንደተረት እና ተራ ነገር አትስማው ህይወት ሁሉ ያለበት ቃል መሆኑን እየተረዳህ ስማው።

ኢየሱስ እንዲህ አለ "እኔ የነገርኳችሁ ቃል መንፈስ ነው ህይወትም ነው።" ዮሐ 6:36

ህይወታችን ቃሉ ነው። ዳግመኛ የተወለድነው ከማይጠፋው ከእግዚአብሔር ቃል ነው። ያ ዘር የማይጠፋ ዘር ነው።

እግዚአብሔር ሰማያቱን ያፀናው ሰራዊታቸውን ሁሉ ያቆመው በቃሉ ነው ። ሰማይ ያለምሶሶ ቆሟል ብለሃል ልክ ነው ግን በማይታየው አለም ቃል የተባለ ምሶሶ አለ እርሱም ከመለኮት የወጣው ቃል ነው።

ፀኃይ ትወድቃለች ብለን ዘንግተን አናውቅም ነገር ግን በሰማያት ላይ እንደቤታችን አንፖል ጠፍሮ የያዛት ጠንካራ ገመድ የለም ግን ቃሉ ወጥሮ ይዟታል። ዙረቷን ሳታዛባ የቀጠለችው እግዚአብሔር ባወጣው ቃል ነው።

ስንቱን ልጥራልህ ስንቱንስ ልዘርዝርልህ ለእግዚአብሔር ቃል ክብር እንዲኖርህ ፣ ባለህ ላይ ደግሞ የበለጠ ለማከል ነው።

ቃሉን አክብረው ፣ ተቀበለው እንደሚልህ ሁንለት ቃል ውስጥ ያለ በጀትና ኃይል ማንኛውንም ነገር ለመፈፀምና ለማስፈፀም የሚችል ኃይል ነው።

"የእግዚአብሔር ቃል አያረጅም ፣ የኢየሱስ ቃል አያረጅም ዘላለም ይኖራል.." እያበራ፣ እየገዛ ፣ እየሸነፈ ፣ እያኖረ ፣ እያበረታ ይኖራል።

ቃሌ ከሚያልፍ ሰማይና ምድር ይለፍ ማለቱን ስታስብ ይሄን ያህል የተናገረውን ለማድረግ የሚተጋ በጣም ታማኝ አምላክ እንዳለህ ሊሰማ ይገባል።

እግዚአብሔር ታማኝ ነው ፣ በቃሉም ታማኝ ነው።

ቃለ- እግዚአብሔር የቀየረው ብቻ ጌታውን ያመስግን ቃሉንም ያክብር።

ቡሩካን ናችሁ!

❤️ኢየሱስ ይወዳችኋል

@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
ለጥያቄዎ @BiniservantofGod

👉share it ሼር ይደረግ👈

💁‍♂💁‍♀ @workofgrace🙏
👉👉 @workofgrace
👉👉 @workofgrace
👉👉 @workofgrace
👆👆👆👆👆
🀄️🀄️ሉን JOIN US
#የህይወት_ማዕዶት

ግንቦት 20/2012

ሐሙስ!

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

#የሚያስፈልገውን_አንገብጋቢውን_ማወቅ!

ህይወት በጣም በብዙ አስፈላጊ ነገር የተሞላች ነች። ግን የትኛው ከየትኛው ቀድሞ መገኘት እንዳለበት ማወቅ ያስፈልገናል።
#አስቸኳይ እና አስፈላጊ- ይሄንን በተቻለ ፍጥነት ልናደርገው የሚገባ ነገር ነው። አሁን አድርገው የሚባልለት!
#አስፈላጊ ግን አስቸኳይ ያልሆነ ነገር - ይሄን ደግሞ በፕሮግራም ልትሰራው የምትችለው ነው።
#አስቸኳይ ግን አስፈላጊ ያልሆነ - ሌላ ሰው ሊሰራው እንዲችል አድርገህ የምትሰጠው ነው።
#አስቸኳይ ደግሞም አስፈላጊ ያልሆነ ከህይወትህ ላይ አውጥተህ የምትጥለው ነገር ነው። አጥፋው!

የስነ-ህይወት ስንሳኔው ከላይ በላው ነገር የሚወሰን እንደሆነ ይታመናል። ታዲያ አንድ ቀን ኢየሱስ ማርታ እና ማሪያም ቤት ተገኘ። ዛሬ እኛ ቤት እንደተገኘው !! አዎ አለ አላስተዋልነወሰ ይሆናል እንጂ ! ሁለቱ አንድ ጣራ ያሉ እህቶች የማይገናኙ ገፅታዎች። ሁላችን የመረዳታችን ያህል ነን። አይደለም ከቤታችን ውጪ በቤታችን ካሉት ሰው ጋር እንኳን መንፈሳዊ ገፅታችን ለየቅል ነው። ግን ጥያቄው ማን ነው ልክ እያደረገ ያለው የሚለው ነው ። ሁለቱም ኢየሱስ ይወደዋል ያሉትን በየግላቸው እያደረጉ ነው ግን የትኛው ከየትኛው መቅደም ፣ የትኛውስ መብለጥ አለበት።
#የማርታ አካሄድ! የማርታዎች አካሄድ!

#1.ግምታዊ አካሄድ!

በህይወት ውስጥ ትልቅ አደጋ ላይ የሚጥለን እግዚአብሔር የሚፈልገውን በሚመስል መልኩ ፣ እግዚአብሔር የማይፈልገውን ስንሰራ መገኘታችን ነው። በመሰለኝ እና በገባኝ ፣ የልቡን እና የነፍሱን ፍላጎት እያገለገልን እየመሰለን ለልባችን ጩኸትና ለነፍሳችን ፍላጎት በመኖር ራሳችንን ደስ በማሰኘት መንገድ እንሄዳለን።

ዳዊት አስተውሎ ያደርግ ነበር ! ማለትም ምንም ከማድረጉ በፊት የአምላኩን ፈቃድ እንጂ የስሜቱን ፈቃድ አይከተልም ነበር። ጌታ ምን ይላልን እና ምን ይፈልጋልን ካላስቀደምን ህይወታችንን እንደልባችን ነው የምንመራው።
#በግምታችን እና በእንደዚህ ይሆናል ፣ በመሰለኝ ነገሮች የምናደርግ ሆነን እንድናገለግለውም አይፈልግም።

#2.ለማገልገል መነሳት!

ለማገልገል መነሳት ውስጥ ምን ሰሰህተት አለ አንበል። ስህተት ባይኖረውም ምን ማስቀደም እንዳለብን መረዳት ያስፈልጋል።
ማገልገል ውስጥ እግዚአብሔርን ብቻ ማክበር ነው ያለው ብለን እናስብ ይሆን ? አዎ ብዙ ጊዜ የሚታሰበው እንደዚያ ነው ግን ህይወት ይቀድማል። ቅድሚያ ልንሰጠው የተገባውን ነገር መለየት መቻል ያስፈልጋል። የማርታ ለማገልገል መነሳቷ ሳይሆን ችግሯ ለመቀመጥ ቅድሚያ አለመስጠቷ ነው። መቀመጥን ማስቀደም ከአገልግሎት የሚበልጥ ቀዳሚ ተግባር ነው።
ሳኦል የሳተው ሳሙኤልን ከመጠበቅ ይልቅ መስዋዕቱን ለማሳረግ መቸኮሉ ነው። የህይወቱን ወይም የቅባቱን መንገድ ሳተው ፣ መልካም ሰራው ብሎ አምላኩን በደለው ፣ ሊፀናለት የነበረውን ነገር አጣው ፣ ስህተቱ መሰዋዕቱ ብቻ ሳይሆን ትልቁ ስህተት ፀንቶ መጠበቅ አለመቻሉ ነው። እግዚአብሔር በብዙ ጎንበስ ቀናችን ከመክበሩ በፊት ትዕዛዙን በመጠበቃችን መክበር ይፈልጋል። በጣም አስፈላጊውን እና ልናደርገው የተገባውን ነገር ቀዳሚ ስፍራ እንስጠው።
#የሚያሰፈልገው አንድና ብቸኛ ነገር!

እግዚአብሔር በአክቲቪቲያችን(ተፍተፍ በማለታችን) ከሚደነቀው ይልቅ እግዚአብሔር እርሱ በሚፈልገው ነገር ላይ መቆማችንን ይፈልገዋል ያስደንቀዋል ።

ማርታ ከኢየሱስ የአድናቆት ጭብጨባን የፈለገች ትመስላለች። እንድታግዘኝ ንገራት እንጂ ብላ በሌላ አንጋገር አሞግሰኝ እንጂ እኔ የማደርገው እኮ አይነት ነው። አይ ማርታ ! አይ ማርታዎች ! በሞራል መቀጠል ይፈልጋሉ እነርሱ የሚያደርጉት ለእግዚአብሔር በጣም የተሻለ ነገር ይመስላቸዋል። የእነርሱ ሐሳብ ምርጥ ነው ብለው ስለሚያስቡ እግዚአብሔር ስለእነርሱ እንዲነሳላቸው ይፈልጋሉ ግን ማሪያም ያለችበት ልብ ድንቅ ነው። አትከስም ዝም ! ንገራት እንጂ እየተባለችም ዝም።

#ማርታ ሐሳብ ውስጥ ኃጢያትም ተንኮልም አታዩም ግን አለማወቅን ፣ ቅድሚያ መሰጠት ያለበትን ነገር አለመረዳትን ያሳያል።

ችግሩ ያልተረዳችው ነገር እያለ ሌሎችን ለመውቀስ መነሳቷ ነው። ከኢየሱስ የድጋፍ ድምፅ መፈለጓ ነው። መስመሩን አልፋዋለች ፍላጎቱን አጥታዋለች። የእርሱን ነጥብ አላገኘችውም።
#የኢየሱስ_ምክር!

1.መቀመጥ ይቀድማልም ይበልጣልም።

ለመስማት መቀመጥ ከሰነፎች መስዋዕት እጅግ የተሻለ ነው። ሳኦል የሳተው መስማትን እንደተራ ነገር ስለቆጠረ ነው። ድርጊቱም ግማሽ መታዘዝ የተሞላበት ነው። መስማት እና መታዘዝ አብረው ይሄዳሉ። የሚፈልገውን እንጂ የምንፈልገውን በማድረግ ልናስደስተው አንችልም።

ጊዜውን ቃሉን ለመስማት ቃሉን ለማንበብ እንጠቀምበት። ቃሉ አስፈላጊያችን ነው። ቃሉ የህይወታችን መሰረት ነው። ከቃሉ ጋር እናሳልፍ! ከቃሉ ጋር እንጣበቅ!

2.ህብረት ማድረግ በህልውና ውስጥ መኖር!

መገኘቱን አግኝታ ለመገኘቱ መገኘት አልቻለችም ትልቅ ኪሰራ። እርሱ ጋራ ከማሳለፍ ይልቅ ወደጓዳ ገባች በዚህ ሰዓት ጌታ ምንድን ነው የሚፈልገው ብላ አለማወቋ። ጌታ በመገኘቱ ውስጥ ተገኝተን ከዚያ በወጣ ማንነት እንጂ በፈቃዳችን እንድናገለግለው አይፈልግም።
የተቀመጠ ሐሳብም ሞገስም አለው። መገኘቱን ብቻህን ሆነህ አግኘው። አሁን በጉባኤ ከማግኘት በግል እንድናገኘው ፈልጓል። ጉድ ጉዳችሁ በዝቶብኝ እኔን ረስታችሁኝ ነበር አሁን እስቲ ከእኔ ጋር ሁኑ ብሎ ጊዜ ሰጥቶናል እናተርፍበት ይሆን ወይስ እንከስርበት ይሆን ?

ከምንም በላይ ለጌታ መገኘት ይበልጣል። ለጌታ መገኘት ያስፈልጋል። ጊዜያችንንም ራሳችንንም ለጌታ በመስጠት ይባርከን።
#ባከነች
#ተጨነቀች
#ግን ምንም አላተረፈችም ሙሉ በሙሉ አጎደለች።
ይሄን ያላት ሰው ቢሆን ቀንቶባት ነው እንል ነበር ግን ይሄን ያላት ራሱ ኢየሱስ ነው።

ኢየሱሰ ስለእኔ ምን ይል ይሆን ? ጎሽ ወይስ ተቀመጥ ?
ጠንክር ወይስ ባከንክ ? ቀጥል ወይስ አቁም ?

ይሄን ጥያቄ ለሁሉም ሰው ትቼዋለሁ። ይሄን የኳረንታይን ጊዜ ፣ በቤት የመሆን ጊዜን ድምፁን ለመስማት በመቀጥ እና እርሱን በመፈለግ ከህልውናው ጋር በማሳለፍ ይባርከን ብያለሁ።

ቡሩካን ናችሁ!

እወዳችኋለሁ

መልካም ቀን !!

Share it ሼር ይደረግ
👌👌 @workofgrace
👌👌 @workofgrace
👌👌 @workofgrace
ተቀላቀሉን
#የህይወት_ማዕዶት!

📝እግዚአብሄር አሁንም ይዞሃል📝

ግንቦት 22/2012

ቅዳሜ

@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

🖊እንደ ኢዮብ ሆነንም ደርሶብንም አያውቅም ! ግን ከኢዮብ በላይ የመረሳትና የመተው ስሜት የሚሰማን ነገር በጣም ግራ ይገባኛል።
ኢዮብ
- ተፈጥሮ ከድቶታል
- ሞት ቤቱ ላይ ተደራርቦበታል
- ጤንነት ከድቶታል
- ሚስቱ አፅናኝ ከመሆን አምላኩን እንዲረግም ጎትጓች ሆናለች። (ለእርሷ አምላክ የሙላት ጊዜ ተመላኪ የችግር ጊዜ ተረጋሚ አድርጋው አስባለች።)
- ወዳጅ ተብዬዎች ቁስሉ ላይ እንጨት ለመስደድ የማይፈሩ ደፋሮች ነበሩ።

🖊ቆይ አንተ/ቺ ይሄ ሁሉ ደርሶብሽ ይሆን ? አንዱ ወይ ሁለቱ ደርሶብህ በቃ አለቀልኝ ፣ እግዚአብሔር ረሳኝ ተወኝ የሚል መዝሙር ግጥምና ዜማ ሰርተህ ለምን እንደምትዘምር አላውቅም።
ጌታ አሁን በዚህ መልዕክት እየተናገረህ ነው። መቼም አልተውህም እያለህ ነው።

📖የእምነትህ ደረጃ የሚያሳድጉ አስቸጋሪ ሆኔታዎች አሉ። "ከፊታችን የተሰለፉ ረጅም ተራራዎች፣ የሚዳሰሱ ጨለማዎች፣ ሁሉ ገሸሽ ብሎ ብቻችንን የሆንን ሲሰማን ፣ ያለን በዜሮ ሲባዛ፣ ህይወት ምስቅልቅል ስትልና እግዚአብሄርን ፍፁም ልናገኘው እማንችልበት በሚመስለን ጊዜ እምነታችን ይፈተናል።"

🧑‍💻በሰላም በደስታ እና በምቾት ቀን ማን ይክዳል?
ኢዮብ የደርሰበትን ነገር ደግሜ ላስታውስህ ቤተሰቡን፣ ስራውን፣ ጤናውን፣ ልጆቹን ያለውን ነገር ሁሉ በአንድ ቀን ውስጥ አጣ። አንተ በአንድ ቀን ምን አጣህ ? ምንስ ተሰወረብህ ?

🧑‍💻እንደዚህ እንደመፃፍ እና እንደመስበክ ቀላል መሰለህ ? አይደለም። ከሙላት ከድሎት ፣ ደስ ከሚል ቤተሰብነት ፣ ከከበረ ብልፅግና ፣ ከነበረበት ከፍታ የነጋው ቀን እስኪመሽ ወደቀ ፣ ተከሰከሰ ፣ ተፈረካከሰ ፣ መኖርን ሳይሆንን ሞት አሁን ካለሁበት ይሻላል የሚልበት ሁኔታ ውስጥ ገባ።

🤦ይሄ ሲደንቀን 37 ምዕራፍ እና ለማይቆጠሩ ቀናት እግዚአብሄር ዝም አለው። ተናጋሪዎች በዝተው መካሪነን ባይ አቁሳዮች ፣ ያልሰራውን ኃጢያት ሰርቺያለሁ እንዲል እያስገደዱት ነው ፣ ኃጢያትህ ነው እንዲ አይነት መዓት ያዘነበብህ ብለው ሰማይ ስለ እርሱ የሚያወራውን የማያውቁ የሁኔታው ተንታኞች ፣ ኮሜንታተሮች የኢዮብን ስቃይ ሲያበዙት አሁንም ሰማይ ዝም ብሏል። ያማል ፣ በጣም ያስለቅሳል ፣ ልብን ይሰብራል

- ያልገባው ሁኔታ በህይወትህ እየሆነ ?
- ሰዎች ስለ እርሱ ብዙ እያሉ ሰማይ ዝም ብሎት ኢዮብዬ ያመሰግናል።

🧏‍♂ኢዮብን እንምሰለው ?
#1. ባለማጉረምረም ይልቅ በማመስገን!
" ኢዮብም ተነሣ .... የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን። " ኢዮብ 1፥20፦21

🧎ችግሩ በተከሰተበት በዚያው ቀን ፀጉሩን ቢላጭ አመድ ላይ ለሐዘኑ ቢቀመጥም።
በከንፈሩ ግን ማጉረምረምን ሳይሆን ምስጋናን ሞላው። በከንፈርህ አትበድል። በልቡ የማይበድል በከንፈሩ ሊበድል አይችልም። ሐዘን ላይ ነን ማለት አናመሰግንም ማለት አይደለም። አመስግን።

#2.የሚሰማህን ለሚሰማህ ለእግዚአብሔር ንገረው።
ኢዮብዬ! በውስጡ ያለውን ትኩሳት ለእግዚአብሔር መናገር ይችልበታል።

"ሰውን የምትጠብቅ ሆይ፥ በድዬስ እንደ ሆነ ምን ላድርግልህ? ስለ ምን እኔን ለአንተ ዓላማ አደረግኸኝ? ስለ ምን እኔ ሸክም ሆንሁብህ?" ኢዮብ 7:20

🧎ኢዮብ ለእርሱ አላማ እንዳደረገው የገባው ያለ ነገር ይመስላል። ሰባተኛው ምዕራፍ በልቡ ውስጥ ያለውን ትኩሳት ፣ የውስጡን ግልብጥብጦሽ የመንፈሱን ጭንቀት ለሚገባው ፣ ሳይናገር ለሚያደምጠው ፣ ከእስትንፋሱ ቅርብ ለሆነው ነገረው። ንገረው ፣ ንገሪው !!

#3.ትላንትና ያደረገለትን የማይረሳ ሰው ነው።

በፈተና ጊዜ ሊረዳው የማይችል አምላክ እንዳለው አያስብም። ሁኔታዎች እግዚአብሔር ከአንተ ርቋል ብለው ቢሰብኩትም እርሱ ግን ቅርቡ እንደሆነ ያውቃል።

“መንገዳቸውን መረጥሁ፤እንደ አለቃ ሆኜ ተቀመጥሁ ፤ ንጉሥ በሠራዊቱ መካከል እንደሚኖር ፥ ኅዘነተኞችን እንደሚያጽናና ኖርሁ።” ኢዮ 29፥25

📕ኢዮብ 29 አሁን ብታነበው ኢዮብ የነበረበትን ከፍታ ነው የምታየው። ያንን ያደረገው እግዚአብሔር እንደሆነ ፈፅሞ አይረሳም።
- “ለዕውር ዓይን፥ ለአንካሳ እግር ነበርሁ።”
- “ለድሀው አባት ነበርሁ፤ የማላውቀውንም ሰው ሙግት መረመርሁ።”
- “የሚጮኸውን ችግረኛ፥ ድሀ አደጉንና ረጂ የሌለውን አድኜ ነበርሁና።”

👌የትላንትናው ኢዮብ ሁኔታ እና የዛሬው ኢዮብ ሁኔታ ቢቀያየርም እግዚአብሔር ግን አይቀያየርም። የእኛ ሁኔታና እኛ እንጂ እግዚአብሔር አይቀየርም። አለ በዙፋኑ። አላማውን እየፈፀመ ነው። እየተሰራን እንጂ እየፈረስን አይደለንም። አሜን !!

እንዲህ ብለህ አውጅ :-

💛እግዚአብሄር መልካም ነው
💚እግዚአብሔር ያፈቅረኛል
💚እግዚአብሔር አይተወኝም።
💚እግዚአብሔር ብርሃኔና መድሃኒቴ ነው
💙እግዚአብሔር ለእኔ ያለው ዕቅድ መልካም እና የሰላም ሐሳብ ነው።

👌ይሄንን ለራስህም ለሁኔታውም በደንብ ንገረው። የኖርከው በአንተ መልካምነት ሳይሆን በእርሱ መልካምነት ነው።

👉አንድ የእግዚአብሔር ሰው እንዲህ ብሎ አስፍሯል :- "እግዚአብሄር በብርሀን የነገረህን ነገር በጨለማ አትጠራጠረው ። የተቆለለውን ተራራ ሳይሆን ከተራራው ከጀርባ ያለውን ሜዳ ታያለህ፣ የሚዳሰሰውን ጨለማ ሳይሆን ወገግ ብሎ የወጣውን ብርሃን ትመለከታለህ፣ ብቻህን ያስቀሩህን ሰዎች ሳይሆን ብቻውን ጎልቶ የሚታይህን እግዚአብሄርን ታያለህ ይህ ሁሉ የሚሆነው ከፍ ወዳለ ደረጃ እያደረሰህ ስለሆነ ነው። ስለዚህ በችግርህ አትቸገር ሁኔታዎች የእግዚአብሄርን ባህሪ አይቀይሩትም። የእግዚአሄር ፀጋ አሁንም በሙሉ ብርታቱ አለ።" እኔም አሜን ብያለሁ !!

✉️ቡሩካን ናችሁ!!✉️

❤️እወዳችኋለሁ❤️

ይቀላቀሉንን 👇👇👇
👉👉👉 @workofgrace
👉👉👉 @workofgrace
👉👉👉 @workofgrace
Share and join
#የህይወት_ማዕዶት!

ዕሮብ

ግንቦት 26/2012

#አትሂጅብን!
#አትሂድብን!
💖💖

በሰው ዘንድ የምትሰራቸው መልካም ነገሮች ሁሉ ሰዎች አንተን እንዲፈልጉህ ከማድረጉ በላይ እንድትሄድባቸው አይፈቅዱልህም።
መፅሐፍ ቅዱሴን ሳጠና በጣም ካስገረሙኝ ሰዎች መካከል ጣቢታ የተባለችው ሴት ነች። ወይም ዶርቃ !
ይህቺ ሴት መልካም ነገር የሞላባት ፣ መፅዋች ፣ ለመበለቶች የሚሆን ልብስ ሰርታ በነፃ የምታከፋፍል ሴት ነች።
ይህቺ ሴት መቁረስን ብቻ ሳይሆን መቆረስን ጭምር የምታውቅ ለሰዎች ህይወት መትረፍን የለመደች ሴት ነች። መልካምነቷ ጉንጯ ላይ ብቻ ያልቀረ ይልቁንም በተግባር ሰው ሁሉ የሚመሰክረው ነበረ።

ድንገት ታማ ሞተች ይለናል መፅሐፍ ቅዱስ። ሰዎቹ ግን ተስፋ አልቆረጡባትም ። ተስፋ በሚቆረጥበት ሞት ውስጥ ሆና ሳለች ...! እነርሱ ግን ሬሳ ሳጥን ከመግዛት ይልቅ እንደተኛ ሰው አጥበው ሰገነት ላይ አኖሯት።

ስማኝ በሰዎች ዘንድ አትሂድብን የምትባል አይነት ሰው ስትሆን ሞተህ እንኳን ተስፋ አይቆረጥብህም።
ዶርቃ ለቀብር መሰናዳት ሲኖርባት እንድትሄድ አንፈቅድላትም ብለው መበለቶቹ በሙሉ ጴጥሮስን አስጠሩት።

ያለመሰሰት ሰጠች ! ያለመሰሰት ኖረች። ያለመሰሰት አካፈለች። ያለመሰሰት ...!

ምሰጠው የለኝም አትበል ብዙ የምትሰጠው ነገር አለህ። ዕውቀትህን ፣ ጉልበትህን ፣ ታለንትህን ፣ ገንዘብህን ወዘተ መስጠት ትችላለህ።
በዚህ ህይወት ሰው ንፋግ የሚሆነው የሚሰጠው ስለሌለው ሳይሆን መስጠት ገንዘብ ብቻ እንደሆነ ስለሚያስብ ነው።

ዶርቃዎች የትናችሁ ? 👐👐
ጴጥሮስም መጥቶ ከእንቅልፍ እንደሚቀሰቅስ ሰው አስነሳት።
አትሂድብን
አትሂጂብኝ
እንባላለን ወይስ እረ እንኳን እርሷ ሄደችልን እንኳን እርሱ ሄደልን ተብሎ ይነገርብን ይሆን።
እኔ ግን ልባርካችሁ ምድር ሁሉ አትሂድብን ብሎ የሚናፍቃችሁ አይነት ሰው ያድርጋችሁ።
ተናፋቂ ሰው እንጂ ምነው እርሱን/ እርሷን የሚገላግለን በመጣ አይባልባችሁ።
#አትሂድብን
#አትሂጅብን
ሐዋ 9:37-42
ኖራም መልካምነት የሞላባት ነች ከሞት ስትነሳ ደግሞ ብዙዎች ወደ ጌታ እንዲመጡ ምክንያት ናት!
ኑሮችሁ ብቻ ሳይሆን ሞታችሁ ጌታችሁን ያክብርላችሁ።
በሰው ዘንድ የምትፈለጉ የምትናፈቁ ሰዎች ያድርጋችሁ።
አሜን
ብሩካን ናችሁ!

@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
#አትሂጅብን!
የዛሬ አመት አከባቢ ፌስቡክ ገፄ ላይ ለጥፌው ከነበረ የተወሰደ።

Share and Join
👉👉 @workofgrace
👉👉 @workofgrace
👉👉👉 @workofgrace
❤️❤️❤️❤️❤️❤️❤️❤️
#የህይወት_ማዕዶት
26/9/2012
ሐሙስ
#መልካም ማድረጋችሁን ቀጥሉ
አስተማሪ ታሪክ
#አንድ_ምሽት_ላይ ልክ ባለሱቁ ሱቁን ከመዝጋቱ በፊት አንድ ውሻ ወደ ሱቁ ይገባል።
ውሻው በአፉ ዘምቢል ይዟል። ዘምቢሉ ውስጥ የሚገዙ እቃዎች ዝርዝር እና ገንዘብ ተቀምጧል።
#ባለሱቁ_ገንዘቡን_ወስዶ እቃዎቹን በዘምቢሉ ውስጥ ያኖረዋል።
ወዲያውኑ ውሻው ዘምቢሉን ይዞ ይሄዳል።
#ባለሱቁ_ስለገረመው የውሻው ባለቤት ማን እንደሆነ ለማወቅ ውሻውን ይከተለዋል።ውሻው አውቶብስ ፌርሜታ ቆሞ ይጠብቃል።
ከትንሽ ጊዜ በኋላ አንድ አውቶብስ ሲመጣ ውሻው አውቶብሱ ውስጥ ይገባል።
#ትኬት_ቆራጩ እንደመጣ ወደፊት ጠጋ አለ የአንገት ቀበቶው ላይ ያለውን ገንዘብና አድራሻ ለማሳየት።
ትኬት ቆራጩም ገንዘቡን ወስዶ ትኬቱን በአንገት ቀበቶው ውስጥ ያኖርለታል። የሚወርድበት ቦታ ሲደርስ ወደፊት ቀረብ ብሎ ጭራውን ያወዛውዛል መውረድ እንደሚፈልግ ለማመልከት መሆኑ ነው።
#አውቶብሱ እንደቆመለትም ይወርዳል። ባለሱቁ አስከአሁን እየተከተለው ነበር። ውሻው ከአንድ ቤት ደርሶ በሩን በእግሮቹ ያንኳኳል።
#ባለቤቱ_ከውስጥ ወጥቶ ውሻውን በዱላ ይመታዋል። በዚህ ጊዜ ባለሱቁ ተናዶ " ውሻውን ለምንድነው የምትመታው?" ብሎ ይጠይቀዋል። ባለቤቱም እንዲህ ብሎ ይመልስለታል። "ከእንልፌ ቀስቅሶኛል።
ቁልፉን ይዞ መሄድ ነበረበት።"
#ይህ_የህይወት_እውነት_ነው! ሰዎች ለአንተ የሚሰጡት ግምት ማብቂያ የለውም።
ከዚህ በፊት የሰራሃቸው ጥሩ ነገሮች ሁሉ ይረሳሉ። ትንሿ ስህተትህ ጎልታ ትወጣለች። ይህ የዚህ ቁሳዊ ዓለም ተፈጥሯዊ ገጽታ ነው! በዚህ ምድር ቆይታችን የከፈልነውን ዋጋ ማንም ባይረዳን እንኳን ከማንም ምንም አይነት ምላሽ ሳንጠብቅ ለመልካም ነገር መትጋታችንን እንቀጥል!

አጋራዋችሁ!
ቡሩካን ናችሁ
#pest
ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ
@workofgrace
#የህይወት ማዕዶት

ሰኔ 4/2012

ሐሙስ!
#ንባብ ውስጥ የቀሰምኩት የዛሬው ምርጥ ነገር።
💖💖

#አባታችን_ሆይ_እንዴት_ትላለህ?
🙇‍♀🙇‍♀🙇🙇🙇‍♀🙇‍♀🙇🙇

🤦‍♀ እንደ ልጅ ካልኖርህ እንዴት "አባት" ትለዋለህ?

🤦‍♂ሌላውን ጠልተህ ራስ ወዳድ ከሆንክ እንዴት አባት "አችን" ብለህ በአንድነት ትጠራዋለህ?

🤦‍♀ ምድራዊ ነገር ብቻ እያሰብህ እንዴት "በሰማያት የምትኖር" ትለዋለህ?

🤦‍♂ልብህ ከእርሱ ርቆ በአንደበትህ ብቻ እየጠራኸው "ስምህ ይቀደስ" እንዴት ትለዋለህ?

🤦‍♀ ሥጋዊና መንፈሳዊውን እየቀላቀልህ "መንግሥትህ ትምጣ" ለምን ትለዋለህ?

🤦‍♂መከራን በጸጋ የማትቀበል ከሆነ "ፈቃድህ ይሁን" ለምን ትላለህ?

🤦‍♀ ለራስህ ሆድ እንጂ ለተራቡት ግድ የማይሰጥህ ከሆነ ለምን "እንጀራችንን ሥጠን" ትላለህ?

🤦‍♂ በወንድምህ ላይ ቂም ይዘህ "እኛም የበደሉልን ይቅር እንደምንል" እንዴት ትላለህ?

🤦‍♀የኃጢአትን አጋጣሚዎች ሳትሸሽ "ወደ ፈተና አታግባን" እንዴት ትላለህ?

🤦‍♂ክፉን ለመቃወም አንዳች ሳታደርግ "ከክፉ አድነን" እንዴት ትላለህ?

🤦‍♀ጸሎቱን ከልብህ ሳትሰማውስ እንዴት አሜን ትላለህ?

እኔ ጠቃሚ ነው ብዬ ሼር አድርጌዋለሁ ከጠቀመህ ሼር አድርገው።

ቤተሰብ ይሁኑ
@workofgrace
@workofgrace

መልካም ቀን !!
💖💕💖
#የህይወት_ማዕዶት!
#💖💖💖
@workofgrace

#አታማርር

#ሰኔ 9/2012 ዓ.ም.

ማክሰኞ

ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)

#እግዚአብሔር በስራ ላይ ነው።

“ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል።” 1ኛ ቆሮ 10፥13

አንዳንድ ጊዜ ያዙኝ ልቀቁኝ የምንልበት የፈተና ምዕራፍ ብዙ ነው። እኛ ብቻ የተለየን ፣ በእኛ ላይ ብቻ የተለየ መዓት እንደ ደረሰብን አድርገን እንቆጥራለን። እናም እግዚአብሔር ደግሞ የረሳን እኛንም የማያስበን ይመስለናል። በመከራ ላይ መከራም ይጨምርብናል ብለን እናማዋለን። የማይወደን ይመስለናል። ግን በእርሱ እስትንፋስ በህይወት እንዳለን እንረሳዋለን። ከማመስገን ይልቅ ፣ ይሄም አልፎ ታሪክ ይሆናል ይረሳል ከማለት ይልቅ ሰማይን ማኩረፍ አይጠበቅብንም። ከተማርንበት እያንዳንዷ የህይወት ምዕራፍ ትምህርት ቤታችን ነች። በምድር ላይ ምሩቅ ፈተና የማይነካው ከእግዚአብሔር ማሰልጠኛ የወጣ ሰው የለም። ስለዚህ አታማር !!

ይሄ ታሪክ የሚነግረን ነገር አለ ፦

አንድ ሰው ነበር በባህር ብቻውን በመርከብ እየተጓዘ በድንገት
በመዓበል ተመታና መርከብ ተሰባብሮ በባህሩ ውሰጥ ሰመጠች ሰውዬው እንደምንም እራሱን አድኖ አንድ ደሴት ላይ ያርፍና ጎጆ ነገር ሰርቶ ለቀናት ለብቻው እዛች ደሴት ላይ ይኖራል ,,,,,,,,
.....ምግብን ... ዓሳ እያጠመደ እየተመገበ ብዙ ቆየ።
አንድ ቀን ዓሳ ሊያጠምድ ወደ ባህሩ እየሄደ በመሀል እዛች ባህር ላይ ጭስ ይሸተዋል ዞር ብሎ ሲመለከት
ያቺ ጎጆው እየነደደች ነው ,,,,,,,እየሮጠ ቢመለስም ጎጆዎን ሊያድናት አልቻለም ለካ ዓሳ ለማብሰል ያቀጣጠለው እሳት ተያይዞ ጎጆውን አንድዷታል አለቀሰ ፈጣሪወን ወቀሰ እንዴት እዚህ ባህር ላይ ለብቻዬ ጥለከኝ ከቤተሰቦቼ ነጥለክኝ ስታበቃ በስንት ልፋት የሰራዋትን ጎጆ ታቃጥልብኛለክ ብሎ አለቀሰ
አማረረ,,,,,,,, ከደቂቃዎች በዋላ አንድ ድምፅ ሰማ ወደ ድምፁ ፊቱን ሲያዞር አንድ ትልቅ መርከብ አየ ተደሰተ ,,,,,, የመርከብ ሰዎችም መጥተው ጭነው ወሰዱት ከዚያም ለመርከብ ሰዎች ጠየቃቸው !
እንዴት አገኛችሁኝ እዚህ አካባቢ እዚህ ባህር ላይ ማንም አይመጣም እኮ እናንተ እንዴት መጣችሁ ? አላቸው ,,,,, መርከበኞቹም እኛም በዛኛው በኩል ዞረን
እየሄድን ነበር ከዚያ በኩል ጭሰ አየንና እዚህ ሰው ይኖራል ብለን መጣን አንተ አገኘን አሉት።

አቤት ጌታዬ ለካ ከዚህ ከስቃይ ልታወጣኝ ፈልገህ ነው ትንሻ ጎጆዬን ያፈርሰከው ወደ ትልቁ ቤቴ ልትወሰደኝ ነው ። አለ አንዳንዴ የሆነ ነገር ስናጣ ሲበላሽብን ፈጣሪንም ሰውንም ስናማርር እንኖራለን ግን ካጣነው ነገር ከጎደለብን ነገር ጀርባ ብዙ ጥሩ ነገር ልናገኝ እንደምንችል እንዘነጋለን በችግራችን ጊዜ መጠጋት ያለብንን እግዚአብሔርን እንረሳለን ከዚያም አልፈን የሁሉ ነገር ፈጣሪውን እንኮንነዋለን ። ያጣነውን የሰጠን እግዚአብሔር አዕምሮችን ከሚያስበው በላይ ሊሰጠን እንደሚችል ማመን አለብን !

በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ ሁን እግዚአብሔር አለ። አሜን አሜን!

ፈተናው ውስጥ ስትሆን መውጫውን የሚያዘጋጀውን እግዚአብሔርን አመስግን።

ቡሩካን ናችሁ!

እወዳችኋለሁ
💖💖💖

Join💯Share💯
@workofgrace
@workofgrace
#የህይወት_ማዕዶት!
ሐምሌ 18/2012
#አርብ
@workofgrace
#ዛየራዊያኑ_አለማወቃቸው ስኬታቸውን አሳጣቸው።

#አለማወቅ የተባለው በሽታን በፀሎት ልታባርረው አትችልም። አለማወቅን ማባረር የምትችለው ለማወቅ በምታደርገው ጥረትና በማወቅ ብቻ ነው።
ህዝቤ ዕውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቷል ይላል የእግዚአብሔር ቃል ። ይሄም ማለት ሰይጣን ከሚያጠፋው ይልቅ አለማወቅ የሚያጠፋው ይበልጣል። ብዙ ሰው ወደ ስህተት የሚሄደው በምንድን ነው ከተባለ ባለማወቅ ነው። ለማወቅ ደግሞ የማወቅን ጉጉት ማሳደርና ማወቅን መናፈቅ ያስፈልጋል።
*//***********
ዛሬ ወደ ዛየር ሆነ ተብሎ ስለሚወራው ነገር ላካፍላችሁ :-
በአንድ ወቅት በዛይር ምድር እንዲ ሆነ በዛይር የሚኖሩ የዛይር ህዝቦች በሀገራቸው አንድ ተአምረኛ ድንጋይ ያገኛሉ።
ይህ ድንጋይ በጣም በጣም ትልቅ እና ጠፍጣፋ ድንጋይ ነው ጠዋት ለጥቂት ሰዓታት የፀሀይ ብርሃን ከሰበሰበ በኋላ ቀኑን ሙሉ በጣም ግሎ ነው የሚያሳልፈው ስለዚህ የዛይር ህዝቦች አንድ ነገር አሰቡ ይህን ድንጋይ ለምግብ ማብሰያነት ለሁሉም የሀገሪቱ ህዝቦች ይውል ዘንድ ተነጋገሩ እናም ህዝቡም ከማገዶ ተጠቃሚነት ወደዚህ ትልቅ አብሳይ ድንጋይን በመጠቀም ምግባቸውን ለማብሰል ጠዋት ለጥቂት ሰዓታት ፀሀይ ከሞቀ በኋላ ቀኑን ሙሉ ምግብ ሲበስልበት ይውላል በዚህም የሀገሪቱ ህዝቦች ደስተኛ ነበሩ።
ከአመታት በኋላ ግን አንድ ትልቅ ምሁርና ባለሀብት ሰው ለስራ ወደ ዛይር ይመጣና ይህን ተአምረኛ ድንጋይና ጥቅሙን ይመለከታል በጣም በመገረምና በመደነቅ ካየው በኋላ እንደዚህ አላቸው :- "ለሁላችሁም የሚሆን የምግብ ማብሰያ እገዛልሃችኋለሁ ይሄንን
ድንጋይ ግን እወስደዋለሁ።" አለ ህዝቡ ሁሉ በደስታ ሆኖ ውሰደው ማብሰያውን ብቻ ስጠን አሉት። ህዝቡም ምግብ ለማብሰል የሚሰለፈው ሰልፍ ሰልችቶት ስለነበረ የየራሱን የምግብ ማብሰያ ለማግኘት ሲል ተስማማ።

ባለሀብቱ እንደ ቃሉ የምግብ ማብሰያን ገዝቶ ሰጣቸው በልዋጩም ያንን ትልቅ ተአምረኛ ድንጋይ ወደ ሀገሩ ይዞት ገባ የዛይር ህዝቦች ያላወቁት ነገር ለአመታት ምግብ ሲያበስሉ የነበረበት ድንጋይ ድንጋይ ሳይሆን ዳይመንድ(አልማዝ) ነበር ምሁር የተባለው ሰው ግን አልማዝነቱን አውቆ በዋጋው ሳይሆን እነሱ ለአልማዙ በሰጡት ዋጋ ለውጦ ላይመልስ ወሰደው።

#አለማወቅ ክፋ በሽታ ነው ግን የማይፈወስ በሽታ አይደለም። ሰይጣን የሚጠቀመው ባለማወቃችን ነው ብዙ ውድ የሆኑ እሴቶቻችንን በርካሽ ነገር ይዘርፈናል።

ታስታውሳላችሁ ኢየሱስ ጋር መጥቶ ምን አለው ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይሄን ሁሉ(አለምን ማለቱ ነው) እሰጥሃለሁ አለው። ኢየሱስ ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክህ ብቻ ስገድ ተብሎ ተፅፏል አለው።

እግዚአብሔርን ማምለክ በምንም ልንቀይረው የማይገባ እውነታ ነው። አለም ሁሉ ተሰጥታን እግዚአብሔርን ከመካድ አለም ሁሉ ቀርታብን እግዚአብሔር ማምለክ ውድ እንደሆነ ስንቶች እናውቅ ይሆን ?

#በሰይጣን ከተዘረፍነው ይልቅ በአለማወቅ የተዘረፍነው ይበልጣል።

የተወደዳችሁ ውዱን በርካሽ ላለመቀየር ዛሬም እናውቅ ዘንድ እንዘርጋ።

#ይሁዳ አለምንና ሞላዋን የፈጠረውን ኢየሱስን ቢያውቀው ኖሮ ለሰላሳ ብር ሲል አይሸጠውም ነበር።

#ይሁዳ የሚተነፍሰው እስትንፋስ ከኢየሱስ የተሰጠው እንደሆነ ቢያውቅ ኖሮ በሰላሳ ብር ኢየሱስ እንዲሞት አሳልፎ እየሰጠ ስኬትን አያልምም ነበር።

#ኢየሱስን ማወቅ ፣ ቃሉን ማወቅ በርካሽ ነገሮች ላለመሸነፍ ትልቅ በር ከፋች መንገድ ነው።

ዛሬስ እንደዛየሮቹ ባለማወቅ ላለመሸነፍ ውድ ነገር ላለማጣት ምንያህል ለማወቅ ዋጋ እየሰጠን ይሆን።

ያጣናቸውን ነገሮች ሁሉ ያጣነው በሰይጣን ብቻ ነው ብሎ ከማሳበብ ወጥተን ባለማወቃችንም ጭምር እንደሆነ አምነን ተቀብለን ለማወቅ እንነሳ መልዕክቴ ነው።

#የዛየር መንፈስ ወጋው ብሎ በመቃወም ይሄ አይሄድም። እና በማወቅ እንዋጋው እንውጋውም።
@workofgrace
ቡሩካን ናችሁ !!
እወዳችኋለሁ
@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
@workofgrace
💖💖💕💕💕
#የህይወት_ማዕዶት!

ሐምሌ 19/2012

#ቅዳሜ

#እንኳን ለሊት ቀንም ጭምር እንጮኋለን"
@workofgrace
“ወደ እኔ ጩኽ፥ እኔም እመልስልሃለሁ፤ አንተም የማታውቀውን ታላቅና ኃይለኛ ነገርን አሳይሃለሁ።”
ኤር 33፥3

አንድ ባለፀጋ በጎቹን🐏🐏 የሚጠብቁለት ሁለት ዉሾች🐕🐕 ነበሩት። እነዚያም ዉሾች🐕 ጌታቸዉ 👨‍የዕለት ምግባቸዉን🍲 ሳያጓድልባቸዉ በምቾት ያኖራቸዉ ነበር። እነርሱም እየጮኹ በጎቹን 🐏ይጠብቁለታል ፧አንድ ቀንም ዉሾቹ 🐕🐕እንዲህ ሲሉ ተማከሩ ፧ከዚህ በኋላ ለዚህ ባለፀጋ 👨‍አንጮኽም ሰለቸን ብለዉ አምፀዉ አንዱ ዉሻ🐕 ወደ በረሃ ሄደ አንዱ ደግሞ ከበጎቹ 🐕መሀል ተኛ ።
በመሸም ጊዜ ሌባ🏃‍♂ ወደ በረቱ ገብቶ ዛሬማ ተለቅ ያለዉን በግ ነዉ መያዚ ያለብኝ ብሎ አሰበ ፧ከበጎቹ 🐏🐏🐏 መካከል ሲፈልግ ውሻዉ በግ መስሎት ተለቅ ያለ በግ አገኘዉ ብሎ ተሸክሞ ወደ ጫካ ይገባል ሊያርደውም ቢላዋ ይዞ ሲመጣ ዉሻዉ ሲጮኽ ሌባዉ በግ አለመሆኑን አይቶ ተናዶ ገርፎ ደብድቦ ይለቀዋል፧ ወደ በረሃ የሄደዉም ረሃብና ጥም አንገላቶት አደረ።
ጠዋት ሲነጋም መንገድ ላይ ተገናኝተዉ እንዴት እንደነበር አዳራቸዉን ማዉጋቶ ጀመሩ። ባለመጮኸቸው እጅግ እንደበደሉ ያም ሳያንስ ከጌታቸው ጋር ቅራኔ በመግባታቸውና የራሳቸውን መንገድ መከተላቸው ትክክል አሀመሆኑ ገባቸው።
በዚህን ጊዜ ምን እናድርግ ብለዉ ተማከሩ ጌታቸዉንም ይቅርታ መጠየቅ እንዳለባቸዉ ተማመኑ፧ ሄደዉም የጌታቸዉ እግር ስር ወደቁ ይቅር በለን ለካስ መጮኻችን ለኛዉ ጥቅም ነበር ፡ከዚህ በኋላ እንኳን ለሊት ቀንም ጭምር እንጮኻለን ብለዉ ቃል ገቡ።

#እግዚአብሔር ጩኹ ያለን ለእኛ ጥቅም እንጂ ለእርሱ ጥቅም አይደለም። ኤርሚያስ ነብይ ነው። ነብይ መሆኑ ከመጮኸ እንዲቆጠብ ሊያደርገው አይገባም። መጮኸ አለበት። እኛም እሳት ሲነሳ ብቻ ሳይሆን ሁልጊዜ ወደ እርሱ መጮኸ አለብን።

መቼም መጮኸ ስል መፀለይ ማለቴ እንደሆነ ግልፅ ነው። መፀለይ አለመቻል በደል መሆኑን እናውቅ ይሆን ? አለመፀለይ ከመዋሸት ፣ ከመስረቅ እና ሌሎችም ኃጢያት ናቸው ከምንላቸው እኩል ኃጢያት ነው።

ውሾቹ እንዲህ አሉ :-

"መጮኽ ከጌታችን ይልቅ ለኛ ይጠቅመናል ስንጮኽ ጠላት አይቀርበንም ስንጮኽ ሳንራብ ጠግበን እናድራለን ስንጮኽ እንፈራለን(ጠብቆ) ስንጮኽ እንድናለን....."
@workofgrace
እና የተወደዳችሁ የጌታ ቤተሰቦች :-

ወደ እግዚአብሔር ስንጮኸ ማምለጥ ይሆንልናል። ዲያቢሎስን ድል እንነሳዋለን በጩኸታችን የምናተርፈው ሰውና ትውልድ አለ።
@workofgrace
#ስንጮኸ ባህሩና ማዕበሉን ፀጥ የሚያደርገው ጌታ ይነሳል። ፀሎታችን ዋጋ አለው። ለምኑ ፣ ጠይቁ ፣ ፈልጉ ካለ ከእኛ የሚጠበቀው ድርሻ ልንወጣ ስለሚፈልግ ነው። የእረሱን ድርሻ ለእርሱ ትተን የእኛን ድርሻ እኛ እንወጣ ባናውቀው ነው እንጂ መጮኸችን ጥቅሙ ለእኛ እና በእኛ ዙሪያ ላሉት ብቻ ነው።

#ተግቶ መፀለይ መጮኸ መልስ ያመጣል። ከእግዚአብሔር ዘንድም አክሊል አለው ብዬ አምናለሁ።

#መቼም ቢሆን ፀሎት ርካሽ ሆኖ አያውቅም። ውዱን እንቁዎቻችንን አንጣል። ፀሎት ያቆመ ሰው ማለት በከባድ መንፈሳዊ ራህብና ጉስቅልና ውስጥ ለማሳለፍ እንዲሁም በጠላት ጥቃት ለመንገላታት ፈቃዱን የሰጠ ሰው ማለት ነው።

#ፀሎት ርካሽ ተግባር ሆኖ አያውቅም።

#እንኳን በችግር ጊዜ በሰላሙም ጊዜ እንጮኸለን ማለት ይሁንልን።

#መልካም የመጮህ ቀን እና ጊዜ ይሁንላችሁ። ይሁንልን።
@workofgrace
#ሳታቋርጡ ፀልዩ!
#ሳታቋርጡ ጩኹ!

ቡሩካን ናችሁ
እወዳችኋለሁ
@ቢኒያም ኃይሉ(መጋቢ)
@workofgrace
@workofgrace
💖💕💕💕
#የህይወት_ማዕዶት
@workofgrace
#የማለዳው አጭር መልዕክት
@workofgrace
#እግዚአብሔር_በከባድ_በአስቸጋሪው_ነገር_ግን_በተሻለው_መንገድ_ይመራናል

“እንዲህም ሆነ ፈርዖን ሕዝቡን በለቀቀ ጊዜ፥ ምንም ቅርብ ቢሆን እግዚአብሔር በፍልስጥኤማውያን ምድር መንገድ አልመራቸውም፤ እግዚአብሔር፦ ሕዝቡ ሰልፉን ባየ ጊዜ እንዳይጸጽተው ወደ ግብፅም እንዳይመለስ ብሎአልና።”
ዘጸ 13፥17

ህይወት ምስቅልቅሎሽ የሞላባት ብዙ ጎዳናዎች አሏት። ጎዳናዎቹን ግን መምረጥም ማወቅም አስቸጋሪ ነው። ወደ ቤትህ እና ወደ ስራ ቦታ ፣ ወደማምለኪያ ስፍራ የምትሄድበትን መንገድ መምረጥ ትችል ይሆናል ነገር ግን በህይወትህ የሚገጥምህን ፈተናና መንገድ ግን ፈፅሞ መምረጥ አትችልም።

#የህይወት መንገድ ፣ ወደ አብ መድረሻ ስለሆነው ስለማያየምታታው ብቸኛ እና አዳኝ ስለሆነው መንገድ ስለኢየሱስ አይደለም እያወራሁት ያለሁት።

እያወራው ያለሁት ስለምታልፍበት መንገድ ነው። እስራኤላዊያን ከግብፅ በአስደናቂ የእግዚአብሔር ክንድ ቢወጡም እግዚአብሔር ግን በቀላሉ መንገድ ሳይሆን በተሻለው መንገድ ሲመራቸው ታያላችሁ። ያም የተሻለ የሚባለው መንገድ ከባድና አስቸጋሪ መንገድ ነው ግን የተዓምራት መንገድ ነው።

#የተዓምራት መንገድ የተሻለ እንጂ ቀላል መንገድ ሆኖ አያውቅም። አስደናቂ እንጂ በ15 ቀን ከሚገቡበት ቀላሉ መንገድ ይልቅ ብዙ የእግዚአብሔር እጅ አይተው የሚገቡበትን ፣ ተዓምራቱንና ምህረቱን ተለማምደው የሚገቡበትን ቀይ ባህር ሲከፈል አይተው የሚጓዙበትን የ40 ቀንን መንገድ መረጠላቸው።

ቀላሉን መንገድ ሳይሆን አስቸጋሪ ከባድ ግን የተሻለውን መንገድ መረጠላቸው።


አታጉረምርም። ቀላል መንገድ እያለ አትበል። የህይወትህ ዲዛይነርና ማስተር እርሱ ህይወትህን በቀና መንገድ ብቻ ሳይሆን በተሻለ መንገድ ይመራሃል።

#ቀላሉን ሳይሆን ከብዙ ቻሌንጅ ጋር ከባዱን ግን የተሻለውን መረጠላቸው።

እነሱ ቀላል ባሉት ቢሄዱም ቻሌንጁ አይቀርም ነበር ግን እግዚአብሔር ባለመስማታቸው እና ባለመታዘዛቸው ብዙ ዋጋ ይከፍላሉ።

የእነርሱ ቀላል ያለእግዚአብሔር ከባድ ከሚሉት በላይ ነው። የእግዚአብሔር ከባድ ግን እነርሱ ቀላል ከሚሉት የተሻለ ነው።

አሁን የምናልፍበትን አይቶ ከመበሳጨት እግዚአብሔርን ማመስገን በጣም አስፈላጊ ነው።

#እርሱ ለእኛ የተሻለውን ያውቃል።
@workofgrace
መልካም ቀን!
እወዳችኋለሁ
ቡሩካን ናችሁ
#12/12/12
#በመቶ አመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚመጣ ግጥምጥሞሽ ላይ ጠቃሚ መልዕክት !

#የህይወት ማዕዶት
@workofgrace
#አትጨነቁ

ማቴ 6:25
“ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?”

ኢየሱስ ይሄንን ትምህርት ሲያስተምር አስተያየት እየሰጠ አይደለም ባትጨነቁ ጥሩ ነው እያለም አይደለም። ነገር ግን ትዕዛዝ እየሰጠ ነው።

መጨነቅ ኃጢያት ነው። መጨነቅ ማለት ማሰብ ከሚገባ በላይ ማሰብ ማለት ነው። ከቁመት ፣ ከአቅምና ከራሳችን ሁኔታ በላይ ማሰብ ማለት ነው። የፀጉር ቀለምን በተፈጥሮ ለመቀየር መፍጨርጨር ማለት ነው። ነጩን ወደ ጥቁር ለመቀየር በጭንቀት ማዕበል መናጥ ማለት ነው።

#ጥናቶች ያመላከቱትን ነገሮች በማንሳት ትምህርቴን ላጠናክርላችሁ። ራሳችሁንም ፈትሻችሁ ንሰሃ ግቡ።

"እንደ እውነቱ ከሆነ ግን አብዛኛዎቹ የምንጨነቅባቸው ነገሮች ቀድሞውኑ መሰረት የሌላቸው ናቸው፡፡ ለምሳሌነት የጥናቱን ውጤቶች እንመልከት፡፡ የምንጨነቅባቸው ነገሮች . . .

#40% በፍጹም ለማይደርስብን ነገር ...
#30% ምንም ልንለውጠው ስለማንችለው ስላለፈው ነገር ...
#12% ሰዎች ስለእኛ ስለሚናገሩብን ፍርድ፣ ወሬና ሃሜት ...
#10% ስለጤንነታችን (ስለተጨነቅን የሚብስ) ...
#8% ስለእውነተኛ ልናስብበት ስለሚገባ ሁኔታ ...

በፍጹም ለማይደርስብን ነገር …
ያለን አማራጭ ምክንያታዊነትን ማዳበር ነው፡፡ ሁኔታው ሊደርስብንና ላይደርስብን የሚችልበትን የእድል መጠን አመዛዝነን ያለመድረሱ ሁኔታ ካመዘነ፣ መጨናነቅን የማቆምን ሂደት መጀመርና እየተዉ መሄድ የግድ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ግን እንዲሁ ምክንያት ፈልገው የመጨነቅ “ሱስ” አለባቸው፡፡ ይህ ዝንባሌ የሚመጣው ለረጅም ጊዜ በአጣብቂኝ ሁኔታ ከማሳለፍና ስሜታችን የጭንቀት ሰለባ ሆኖ ከመክረሙም የተነሳ ሊሆን ይችላል፡፡ ያም ሆነ ይህ ፍጹም የማይደርስ ነገር ተለይቶ ሊታወቅና ከስሜታችን የደም ዝውውር ውስጥ ሊወገድ ይገባዋል፡፡

ምንም ልንለውጠው ስለማንችለው ስላለፈው ነገር …

ያለን አማራጭ ፈጽሞ አንዴ የሆነ ነገር መሆኑንና ምንም ብናደርግ ልንለውጠው እንደማንችል በመቀበል አእምሮን በአዳዲ ነገሮች መሙላት ነው፡፡ "

#የተወደዳችሁ ትላንት መመለስ አትችልም። ትላንትናን በማሰብ መብሰልሰል ለማረር ካልሆነ ምንም የምናመጣው ለውጥ የለም። ይልቁን የምንማርበት ነገር ካለ እንማርበትና በጥበብ እንለፈው።

#ሰዎች ስለእኛ ስለሚናገሩብን ፍርድ፣ ወሬና ሃሜት …

"ያለን አማራጭ መቆጣጠር የማንችለውን የሰውን ባህሪይ ለመቆጣጠር ከመጦዝ ይልቅ መቆጣጠር የምንችለውን የራሳችንን በሆነ ባልሆነው የመጨነቅ ዝንባሌ ለመቆጣጠር መስራቱ ይመረጣል፡፡ ሰዎች ስለአንተና በአንተ ላይ የሚሉት ነገር አንተ ካልፈቀድክለት በስተቀር ምንም ሊያደርግህም እንደማይችል አትዘንጋ፡፡ ብትችል ወሬው አንተ ጋር የማይደርስበትን መንገድ ፍጠር፡፡ ካልቻልክ ደግሞ ወሬው ወደ ስሜትህ የማይደርስበትን ጥንካሬ አዳብር፡፡"

#የተወደዳችሁ ይሄ ሁሉንም ሰው ያሳከረ ጉዳይና ብዙዎችን ለበሽታ ያጋለጠ እውነት ነው። በጣም ከምደነቅባቸው ሰዎች መካከል የአሁኑን ጠቅላይ ሚኒስተር ዶክተር አብይን ነው። በዚህ ዘመን በእርሳቸው ልክ የሚሰደብ ፣ የሚተች ፣ የሚብጠለጠል ሰው አላየውም። በጣም የሚደንቀኝ ንቀው ማለፍ መቻላቸው ፣ ጭንቀት ሲነበብባቸው ማየት አለመቻሌን ሳስበው ይደንቀኛል።

ወዳጄ አንድ ነገር ልንገርህ ለተወራብህ ሁሉ መልስ መስጠት አትችልም። መጨነቅም የለብህም። ይልቁን ስራህን መቀጠል ነው ያለብህ። ሰዎች ስለአንተ የሚያስቡትንም የሚያወሩትንም መቆጣጠር አትችልም ግን አለመጨነቅና ራስህን በፀሎትና በመልካም ስራ ማጎልበት ግን የሚከለክልህ የለም። ብዙዎች አለስተዋዮች ያለዕድሜያቸው ያረጁትም ፣ የሞቱትም እንዴት እንዲህ እባላለሁ ብለው በጭንቀት ሲብሰለሰሉ ነው። ሰው የሚለውን አያጣም ብለህ መልካም ማድረግህን ቀጥል ጭንቀትን ግን ጠልዘህ አባረው....

#ስለጤንነታችን (ስለተጨነቅን የሚብስ)

ያለን አማራጭ ስለጤነታችን የሚያሳስበን ሁኔታ ካለ ያንን ለማስቀረት ወይም ለመቀልበስ የምንችለውን ያህል መሞከር ነው፡፡ የህክምና ክትትል ማድረግ መፀለይ

#ጭንቀታችን ግን “ምናልባት እታመም ይሆን” የሚል ከሆነ፣ ይህ የራስ በራስ ትንበያ እንደሚፈጸም አትጠራጠር፡፡

ጭንቀት በሽታን የመሳብ ባህሪይ አለውና፡፡

#የተወደዳችሁ በአለም ላይ አሁን ላይ ጥናት ቢሰራ ከኮሮናም በላይ ገዳይ በሽታ ጭንቀት መሆኑ ምንም ጥርጥር የለም።

#ስለእውነተኛ ልናስብበት ስለሚገባ ሁኔታ

ያለን አማራጭ በቅድሚያ፣ ሁኔታው በትክክልም የሚያሳስብና በቅጡ ካልያዝነውም የሚስጨንቅ ጉዳይ ስለሆነ ማሰባችንና በመጠኑም ቢሆን ትክክለኛው መሆኑን አምኖ መቀበል አስፈላጊ ነው፡፡

ሲቀጥል ያሳሰበንን ሁኔታ በምን መልኩ ብንጋፈጠው ልናሸንፈው እንደምንችል በሚገባ ማሰብን ይጠይቃል፡፡
አእምሮን በጭንቀት ከመሙላት ይልቅ ትክክለኛውን ምላሽ በማሰብ መሙላት በብዙ እጥፍ ይመረጣል፡፡ በጉዳዩም ላይ ሰውን ማማከሩም አንዱ መንገድ ነው፡፡

#የተወደዳችሁ ቤተሰቦቼ #አትጨነቁ ማለት ትዕዛዝ ነው። ትዕዛዙን መተላለፍ ደግሞ ኃጢያት ነው።

በጭንቀት ውስጥ ያላችሁ ሰዎች መጀመሪያ ንሰሃ ግቡ ከዚያም ደግሞ በፀሎትና በምክር ሊያግዟችሁ የሚችሉ መንፈሳዊ አገልጋዮችን አግኙ።

#የማቴዎስ 6 ሐሳብ ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ።

እወዳችኋለሁ

ቡሩካን ናችሁ
12/1212
በመጋቢ ቢኒያም ኃይሉ

@workofgrace
@workofgrace