ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ
20.4K subscribers
362 photos
94 videos
160 files
268 links
This channel is not operated by Deacon Yaregal Abegaz

https://youtube.com/@yaregalabegaz?si=1f5NHTaQ2l2LbxWQ

“ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው።”
— 2ኛ ቆሮ 11፥28
Download Telegram
እጅህ ላይ ባለው ነገር ከታመንህ እግዚአብሔር አምላክ በእጁ ውስጥ ያለውን ነገር ይሰጥሃል።

በውስጥህ ያለውን አቅም መጠቅም ከቻልህ እግዚአብሔር የአንተ ያልሆነ ተጨማሪ አቅም ይሰጥሃል።

ከእግረኞች ጋር ሳትደክም እኩል መራመድና መቅደም ከቻልህ እግዚአብሔር ፈረስን ለውድድር ይሰጥሃል። ኤር. 12፥5

የሚታዩ ኃጢአቶችን ለመዋጋት ታምነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር የተሸሸጉና የማይታዩ ኃጢአቶችን ድል እንድትነሣ ይሾምሃል።

በሕፃንነትህ በልጅነትህ ለእግዚአብሔር የታመንህ ሆነህ ከተገኘህ እርሱ በወጣትነትህ በምታደርገው ውጊያ ውስጥ ታማኝነትን ያድልሃል።

በሲና ምድረ በዳ ለመቀመጥ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር አምላክ የተስፋይቱን ምድር ከንዓንን ያወርስሃል።

በዚህ በተወሰነና አጭር ሕይወት ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር መጨረሻ የሌለውን ዘላለማዊ ሕይወት ያድልሃል።

ትልቁ ቁም ነገር በእጅህ ውስጥ የገባው ነገር ትንሽም ይሁን ጥቂት በእርሱ መታመን መቻልህ ነው። ስለሆነም ባለህ አንድ መክሊት ታምነህ ስትገኝ እግዚአብሔር አምስት መክሊቶችን በአደራ ይሰጥሃል።

አንተ በሚታዩት ነገሮች ላይ ታማኝ ሆነህ ስትገኝ እርሱ በማይታዩት ነገሮች ላይ ይሾምሃል።በመሆኑም ዓይን ያላየችውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልብ ያልታሰበውን መንግሥቱን ያወርስሃል። 1ኛ ቆሮ 2፥9

(#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ)
“ተጋድሏችን ለእውነት እንጂ ለቃላት አይደለም!”
ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ

ሰው ሐሳቡን የሚገልጸው በቃላት አማካኝነት መሆኑ የታወቀ ነው። ሆኖም ሰው የሚረዳውን ሁሉ አከናውኖ ለመግለጽ ግን ቃላት ብቻቸውን ብቁዎች አለመሆናቸው ግልጽ ነው። አዳዲስ ቃላትን በመፍጠርና ዐረፍተ ነገሮችን በመደርደር ለማስረዳት የሚደክመው ከዚህ የተነሣ ነው። ሰው በሰውነቱ የሚያስባቸውን ሐሳቦች ለመግለጽ እንኳ ቀላል ካልሆነ፣ አምላካዊ የሆኑ ነገሮችን ለመግለጽማ የሰው ልጅ ቋንቋና ገለጻ ምን ያህል ደካማ ይሆን? ነገረ ሃይማኖት ከቃላትና አገላለጾች በእጅጉ ያለፈ ነውና።
ኦርቶዶክሳዊ የነገረ ሃይማኖት አረዳድ ከቃላዊነትና ሐተታዊነት ይልቅ ወደ ተመስጧዊነትና አንክሮታዊነት የሚያደላውም ለዚህ ነው። ይህም አሉታዊ አረዳድ (Apophatism - አፖፋቲዝም) የሚባለው ነው። አንድ ሰው ነገረ እግዚአብሔርን የሚማረው ለድኅነት የሚጠቅመውን ያህል እንዲያውቅ፣ ብሎም አላዋቂነቱን ለማወቅ እንዲረዳው እንጂ እግዚአብሔርንና አሠራሩን በተመለከተ ሁሉን አውቃለሁ እንዲልና በዚህ ዐለም እንዳሉ የእውቀት ዘርፎች ዓይነት ራሱን እንደ ባለሞያ እንዲቆጥር አይደለም።

ቃላትን የምንፈጥራቸው እኛው ሰዎች ነን። አንድን ሐሳብ ለመግለጽ ወይም ለመወከል ስንል ወይ አዳዲስ ቃላትን እንፈጥራለን፣ አለዚያ ደግሞ የነበረን ቃል አዲስ ወይም የዳበረ ሐሳብ እንዲወክል እናደርገዋለን። በነገረ-ሃይማኖትም አምላካዊ ትምህርቶችን ለመግለጽ የተሄደበት መንገድ እንደዚሁ ያለ ነው። ጥልቅ የሆኑ አምላካዊ ጸጋዎችንና እውነቶችን ለመግለጽ ያስችላቸው ዘንድ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ወይ ነባር ቃላትን አዳዲስ ጽንሰ-ሐሳብ እንዲወክሉ ያደርጓቸዋል፣ አለዚያ ደግሞ እነዚያን ሐሳቦች የሚሸከሙ ቃላትን ለመፈለግና ለመፍጠር ጥረት ያደርጋሉ።

በዚህ ሂደት ውስጥ ታሳቢ ሊደረግ የሚገባው አንዱ መሠረታዊ ጉዳይ፣ ቃላት የሚወክሉት ሐሳብ እንደየ አረዳዱ የተለያየ ሊሆን የሚችል የመሆኑ ነገር ነው። በሆነ ወቅት ላይ ጤናማ ያልሆነ አስተምህሮን ለመግለጽ ጥቅም ላይ ውለው የነበሩ ቃላት በሌላ ወቅት ደግሞ ጤናማ የሆነ አስተምህሮን ለመግለጽ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ። ለዚህ ጉዳይ ሁነኛ ማሳያ የሚሆነው “homoousion - ሆሞዑሲዮን - ዋሕደ-ባሕርይ ምስለ አብ” የሚለው ቃል ነው።
Homos - አንድ ዓይነት ፤ ousia - ባሕርይ ማለት ነው። ይህ ቃል በ325 ዓ.ም. በኒቂያ በተካሄደው የመጀመሪያው ዐለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ላይ አባቶቻችን የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነትና ከአብ ጋር በባሕርይ አንድ መሆኑን ለመግለጽ የተጠቀሙበት ቁልፍ ቃል ነው። ሆኖም ከኒቂያ ጉባኤ ግማሽ ምዕት ዓመት ያህል ቀደም ብሎ በተካሄደው በአንጾኪያ ጉባኤ (264-272) ላይ ጳውሎስ ሳምሳጢ የተባለው መ*ና*ፍ*ቅ# የተወገዘው ይኸን ቃል በመጠቀሙ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ ጳውሎስ ሳምሳጢ ይህን ቃል (homoousion - ሆሞዑሲዮን) የተጠቀመው የአብን የወልድንና የመንፈስ ቅዱስን አካላዊ ህላዌ የሚክደውን የሰብአልዮስን ክህደት በሚወክል መልኩ ስለነበረ ነው። ቀደም ሲል ጳውሎስ ሳምሳጢ የተሳሳተ አስተምህሮን ለመግለጽ የተጠቀመበትና በአንጾኪያ ጉባኤ የተ#ወገዘበ*ት ይህ ቃል፣ በ325 ዓ.ም. በኒቂያ በተካሄደው ጉባኤ ላይ ግን የኢየሱስ ክርስቶስን ከአብ ጋር በባሕርይ አንድ መሆንና የባሕርይ አምላክነት በሚገልጽ መንገድ ጥቅም ላይ በመዋሉ የኦርቶዶክሳዊነት መለያ ቁልፍ ቃል ሆነ። ከዚያ ወዲህ “homoousion - ሆሞዑሲዮን” የሚለው ቃል የኦርቶዶክሳዊነት አጥርና ቅጥር ሆነ።

ሌላው ልብ ሊባል የሚገባው ጉዳይ ደግሞ ሰዎች የሚያምኑት አስተምህሮ አንድ ዓይነት ሆኖ ሳለ አገላለጻቸው የተለያየ ሊሆን የሚችልበት ዕድል ሊኖር የመቻሉ ነገር ነው። ይህ በአንድ በኩል የቋንቋና የቃላት ውስንነት ውጤት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ አጽንኦት አሰጣጣቸውና አገላለጻቸው ሊለያይ ስለሚችል ነው።

የቋንቋና የቃላት አጠቃቀም፣ አንድ አስተምህሮ (ሃይማኖት) ያላቸውን ወገኖች የተለያየ ነገር የሚያምኑ ሊያስመስል የሚችልበት ሁኔታ አለ። በዐራተኛው መቶ ዓመት ይህ ሁኔታ ተስተውሏል። በግሪኮችና በላቲኖች መካከል ሃይማኖታቸው አንድ ሆኖ ሳለ የግሪክ ነገረ-ሃይማኖታዊ ቃላትን ወደ ላቲን ቋንቋ ሲተረጉሙ ተመጣጣኝ የሆኑ አቻ ቃላትን ካለማግኘታቸው የተነሣ የተጠቀሟቸው የላቲን ቃላት ሃይማኖታቸው ችግር ያለበት መስሎ እንዲታይ ከሚያደርግበት ደረጃ ደርሶ ነበር። ይህን ሁኔታ የፈታው ታላቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ነበር። ቅዱስ ጎርርዮስ ነባቤ መለኮት፣ ስለ ቅዱስ አትናቴዎስ በጻፈው የውዳሴ ድርሰቱ ላይ ይህን ጉዳይና ቅዱስ አትናቴዎስ የፈታበትን መንገድ እንዲህ ገልጾታል፡-

“. . . እስካሁን በተናገርኩት ላይ ይህን ለእኔ በተለየ ሁኔታ አስደናቂ ሆኖ የሚታየኝን ተግባሩን [የቅዱስ አትናቴዎስን] ሳልጠቅስ ባልፍ፣ በተለይም ሰዎች ለመለያየትና ላለመግባባት ዝግጁዎችና ምቹዎች በሆኑበት በእኛ ዘመን፣ ከቅጣት ነጻ የሚያደርገኝ አይመስለኝም። ይህን እርሱ ያደረገውን ነገር ልብ ብለን ካስተዋልነው፣ ለዚህ ዘመን ሰዎችም ጠቃሚ ትምህርት ይሰጣልና። . . . መለያየት ያለው በእኛና በስህተት ውስጥ ባሉት ሰዎች መካከል ብቻ ሳይሆን፣ እጅግ አማኞች በሆኑት ዘንድም ነውና፣ ይኸውም ደግሞ የሚያስከትሉት ነገር በጣም ኢምንት በሆኑ ጥቃቅን አስተምህሯዊ ጉዳዮች (in regard to such doctrines as are of small consequence) እንዲሁም ደግሞ አንድ ዓይነት ትርጉም እንዲኖራቸው ታስበው በሚነገሩ አገላለጾች የተነሣም ነው እንጂ።

“አንድ ባሕርይ እና ሦስት አካላት (one Essence and three Hypostases) ማለትን ኦርቶዶክሳዊ በሆነ መንፈስ እንጠቀማለን፣ ባሕርይ (Essence) የሚለውን የባሕርይ አምላክነትን ለማለት፣ አካላት (Hypostases) የሚለውን ደግሞ የሦስቱን ህልውነትና የየራሳቸውን ገንዘብ ለማመልከት እንጠቀማለን። ሆኖም ጣሊያናውያን ይህንኑ ማለታቸው ቢሆንም ቅሉ፣ ከመዝገበ ቃላታቸው ስስነትና ከቃላት ድህነት የተነሣ፣ በኢሰንስ (Essence) እና በሃይፖስታስስ (Hypostases) መካከል ልዩነት ለማድረግ አልቻሉም። ከዚህ የተነሣም፣ ሰዎች በስህተት ሦስት ባሕርያት (Essences) ብለው የሚያምኑ እንዳይመስላቸው ለማድረግ በሚል ’ፐርሰንስ’ (Persons) የሚል ቃልን ተጠቀሙ። የዚህ ውጤት ግን አሳዛኝም አስቂኝም በሆነ ነበር። ይህ ትንሽ የቃላትና የአገላለጽ ልዩነት የሃይማኖት (አስተምህሮ) ልዩነትን እንደሚያመለክት ተደርጎ ከመወሰድ ደረጃ ላይ ደረሰ።

“ከዚያም ‘ሦስት ፐርሰንስ’ (Three Persons) በሚለው አስተምህሮ በውስጡ ሰብአ*ልዮሳዊነት እንዳለው አስጠረጠረ፣ ‘ሦስት ሃይፖስታስስ’ (Three Hypostases) በሚለው አስተምህሮ ውስጥ ደግሞ አር#ዮሳዊ*ነት*ነት እንዳለበት ይጠረጠር ጀመር፤ ሁለቱም በተረጋጋ መንፈስ አንዱ ሌላውን ለመረዳት ጥረት ከሚያደርግ መንፈስ ሳይሆን ከተከራካሪነትና ራስን ብቻ እውነተኛና ተቆርቋሪ ከማድረግ መንፈስ የተወለዱ ናቸውና። ከዚያም ቀስ በቀስ የሆነ ግን የማያቋርጥ የመነቃቀፍና የቁጣ መንፈስ በመካከላቸው እያደገ በመሄዱ፣ ከቃላትና አገላለጽ ልዩነቶች በተጀመረ አለመግባባት፣ መላው ዐለም በሃይማኖት ወደ መለያየት ሊያመራ ከሚችልበት አደጋ ላይ ደርሶ ነበር።
“ይህን እያየና እየሰማ፣ እውነተኛ የእግዚአብሔር ሰውና ታላቅ የነፍሳት እረኛ እንደ መሆኑ፣ በቃላት ስንጠቃና በአገላለጽ ልዩነት የመጣውን ይህን የመሰለውን አስነዋሪ የመለያየት አደጋ ዝም ብሎ መተው ከተግባሩ አንጻር ተገቢ ሆኖ አላገኘውም። ስለዚህም ለዚህ ደዌ ተገቢ የሆነውን መድኃኒት አደረገለት። በምን ሁኔታ? ቅንና ርኅሩኅ በሆነው መንገዱ ከሁለቱም ወገኖች ጋር ጉዳዩን ተወያየ፣ የሁለቱንም ወገኖች የአገላለጾቻቸውን ይዘትና ትርጉም በጥንቃቄ ከመዘነ በኋላ፣ እና የሁለቱም አገላለጾች አንድ ዓይነት ሐሳብ (መንፈስ) ያላቸው መሆናቸውን ተረዳ፣ በአስተምህሮ ረገድ በምንም ሁኔታ የተለያዩ እንዳልሆኑ ተረዳ። ስለሆነም ሁለቱም ወገኖች ሃይማኖታቸው አንድ በመሆኑ የየራሳቸውን ቃላትና አገላለጾች እንዲጠቀሙ በመፍቀድ፣ በቃላትና በአገላለጾች ልዩነት ብቻ ሊለያዩ የነበሩትን ወገኖች አንድ አድርጎ ጠበቃቸው። ይህ ድርጊቱ ከብዙ ትጋቶቹና ተጋድሎዎቹ፣ ይህ ታላቅ የሃይማኖት ጀግናችን ከተቀበላቸው ብዙ ስደቶቹና መከራዎቹ ሁሉ የበለጠ ዋጋ ያለው ነው፤ . . .” (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት፣ በእንተ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ቁ. 35-36)

ቅዱስ አትናቴዎስ ይህን ያደረገው፣ በ362 ዓ.ም. በእስክንድርያ በእርሱ ሰብሳቢነት በተካሄደ ጉባኤ ነበር።

እንግዲህ ሰዎች ሃይማኖታቸው አንድ ሆኖ ሳለ፣ ግን ጥልቅ የሆነው ነገረ ሃይማኖታዊ ሐሳብ ከቋንቋ ወደ ቋንቋ ሲተረጎም በሚፈጠሩ የቃላትና የአገላለጾች አጥጋቢ አለመሆን የተነሣ ሃይማኖታቸው የተለያየ ሊመስላቸው ይችላል ማለት ነው። በዚህ ላይ ደግሞ በፍቅርና በቅንነት አንዱ ሌላውን ለመረዳት ጥረት በማድረግ ፋንታ ሁሉም የራሱን አረዳድና አገላለጽ ብቻ ኦርቶዶክሳዊ የሌላኛውን ግን ኑ*ፋ*ቄ#ያዊ አድርጎ ለመፈረጅ ከቸኮለ፣ ከዚያ በኋላ መደማመጥና መግባባት ይቀርና መወጋገዝ ብሎም መለያየት ይከተላል። ቃላትና አገላለጾች ላይ ብቻ የተንጠለጠለ ጥራዝ ነጠቅ አካሄድ ቤተ ክርስቲያንን ከባድ ዋጋ ሲያሰከፍላት ኖሯል። ስለሆነም በትክክል የአስተምህሮ ልዩነት (ኑ*ፋ*ቄ#) የሆነውን የቃላትና የአገላለጽ ልዩነት ከሆነው ለይቶ ለመረዳት መረጋጋት፣ ፍቅር፣ ቅንነትና ትሕትና ይፈልጋል።

በዚያውም ላይ ደግሞ የምንጠቅሳቸው ምንጮች ከሌላ ቋንቋ የተተረጎሙ ከሆኑ፣ ጸሐፊዎቹ አባቶች በጻፉበት የመጀመሪያው ቋንቋ ያ ሐሳብ በምን ሁኔታ እንደ ተገለጸ ከምንጩ ወደ ማጣራት መሄድም ሌላው አስፈላጊ ነገር ነው። መተርጉማን የሚተረጉሙት በዚያን ዘመን በነበረው የቋንቋ አረዳድ እንዲሁም ሰው እንደ መሆናቸው በመረዳታቸው ልክ ነውና። ከላይ ለማውሳት እንደ ተሞከረው በሆነ ዘመን ያስወገዘ ቃል በሌላ ጊዜ ደግሞ የኦርቶዶክሳዊነት ቁልፍ ቃል ሊሆን ይችላል። ስለዚህ የሆነን ቃል “አለ/የለም”፣ “ይባላል/አይባልም” ከሚለው ባሻገር፣ ያ ቃል መቼና በማን እንዲሁም ምን ለማለት ጥቅም ላይ እንደ ዋለ መረዳት እጅግ አስፈላጊ ነው። “ነገረ አበው” (ፓትሮሎጂ) የሚባለው ትምህርት ጥቅሙ እዚህ ላይ ነው። የአባቶችን ትምህርት በዝርዝር ወደ መማር ከመግባት በፊት የነገረ-አበውን ትምህርት በአግባቡ መማር ቢቻል ብዙ ችግሮችን ለመፍታት ሰፊ ዕድል ሊሰጥ ይችላል።

በዚህም ላይ የሚጠቀሱትን ዘሮች ከተለያዩ ቅጂዎች ጋር ማመሳከርም አስፈላጊ ነው። እንደዚሁም እነዚያ አባቶች ብለዋቸዋል እየተባሉ የሚጠቀሱትን ነገሮች ከጥንት ምንጫቸው ማጣራት በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። እነ እገሌ ብለዋቸዋል እየተባሉ በታላላቅ አባቶች ስም ለዘመናት ሲጠቀሱና ሲያወዛግቡ የኖሩ ሆኖም ከምንጫቸው ሲፈለጉ ግን ያልተገኙ አገላለጾችና ሐሳቦች አይታጡምና።

ስለሆነም የሆኑ ቃላትን ብቻ በመውሰድ “እንደዚህ የሚል ቃል አለ/የለም”፣ “እንደዚህ ይባላል/አይባልም” ከሚል ባለፈ፣ ያን ቃል የሚሉት/የማይሉት ወገኖች ለምን እንደዚያ እንደሚሉ/እንደማይሉ ሐሳባቸውን ለመረዳት የተወሰኑ እርምጃዎችን መሄድ አስፈላጊ ነው። የኦርቶዶክሳዊነት ምሰሶ የነበረው ታላቁ አባት ቅዱስ አትናቴዎስ “ተጋድሏችን ለእውነት እንጂ ለቃላት አይደለም!” ያለው ለዚህ ነው።

ከቃላትና ከአገላለጾች ባሻገር የሆኑ፣ ከጥቅሶችና ገጸ-ንባቦች ባሻገር አስተምህሮን ማዕከል ያደረጉ፣ ከጥቃቅኑ ነገር አልፈው ትልቁን ሥዕል የሚመመለከቱ እንደ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ያሉ አባቶችን አይንሣን! እኛንም እንደዚህ ያሉ አባቶችን ለመስማትና ለመታዘዝ ያብቃን! አሜን!

በዚህች ደካማ ተምኔታዊ ጽሑፍ ላይ የቃላትና የአገላለጽ ችግር ካለም ይቅርታ በመጠየቅ ነው!

Dn Yaregal Abegaz
Please forgive me for my belated reply to your letter which is dear to me. I am not feeling well, and the thoughts about death do not leave me alone. I feel that if I live up to see 1963, I will not pass it through. For me personally,death is desirable. I know that there is future life, that there is God’s mercy for us and there is hope for us believing in the Lord Jesus Christ to enter intothe blissful eternity, rather than an everlasting torturous future.
Religious perceptions, though different from the spiritual meaning ofthe world, are also as real as the perceptions of the physical world. The earthly life is not for pleasures but for getting knowledge of oneself and of God.
During their earthly life people must make a resolute and irrevocable choice– to strive for good or for evil; for God or for devil. Those seeking God and His truth will find God and the rudiments of a new life here, on earth, and in itsfullness – after death. An egoist looking exclusively for earthly pleasures will find the devil and after death, as of one in spirit with the devil will go to the Devil’s kingdom, Hell, to join the community of downright egoists and evil-doers. Our future destiny is in our hands… Forgive me, if I am writing not quite what I should. I am sorry not to have come to see you this summer.
I wish to be farther from this life and from the spirit of this world. This spirit has taken possession of the whole mankind. Only from the outside it is possible to see and to feel the loathsome vileness and ugliness of this spirit.
There are very few people in the world today, who are capable of escaping the influence of this evil spirit on them. This is horrible! They say, that a frogmeeting with the eyes of a snake cannot cast its glance away, it starts to cry,but is unable to run away and instead is moving closer and closer to the snake until it fnally gets into its mouth.
There are words in one of the evening prayers, pleading: “Lord, take me away from the mouth of the abhorrent serpent, desiring to devour me alive and to throw into the hell.” These words come from human experience. Those possessed by this spirit do not understand them and do not believe those who have freed themselves from it.
May the Lord bless you and protect you from evil and lead you to eternal blissfulness after death. God willing, we might see each other in the outer world.
Choose God; keep away from the devil in spirit and in deed, so that the Lord’s words: “Who is coming to Me I will not cast out” may be also said about you.

#Abbot_Nikon_Vorobiev
#Spiritual_letters
ቅዱስ ጳውሎስ እና ሕግ
***
"መገረዝ ቢሆን አለመገረዝም ቢሆን ከንቱ ነው፥ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጠበቅ ነው እንጂ።" (1ኛ ቆሮ. 7፥19)
ታላቁ ሐዋርያ ጳውሎስ ሆይ! መገረዝ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ስለመሆኑ ለአንተ እንዴት ይነገራል? ለአብርሃም እና ለዘሩ መገረዝን ያዘዘ ራሱ እግዚአብሔር አይደለምን? መገረዝን ከትእዛዛት ለምን አወጣኸው? ብለን እንጠይቅ። እርሱም እንዲህ ይመልሳል።
የብሉይ ሕግ ልዩ ልዩ ገጽታ አለው። አንደኛው ገጽታው እስራኤል ከአሕዛብ ርኩሰት ይጠበቁ ዘንድ ከአሕዛብ ለመለያነት የተሰጡ ሕጋት ናቸው። እነዚህም የግዝረት፣ የመባልዕት፣ የበዓላት እና የቀናት ሕጋት ናቸው። እስራኤል በሃይማኖት እስኪጎለምሱ ድረስ በመንፈስ ሕጻናት በነበሩበት ዘመን እንደ ሞግዚት ሆነው ይጠብቋቸው ዘንድ በጊዜያዊነት የተሰጡ ሕጋት ናቸው። እነዚህን ሐዋርያው በገላትያ እና በሮሜ መልእክታቱ 'የሕግ ሥራ' እያለ የሚጠራቸው ናቸው። (ገላ. 2፥16፣ 3፥2፣ 3፥5፤ ሮሜ. 3፥20፣ 3፥27 ወ.ዘ.ተ. . . ) በክርስቶስ መምጣት አሕዛብ ሁሉ የአብርሃምን ተስፋ በእምነት የሚካፈሉበት ዘመን ሲደርስ እነዚህ እስራኤልን አጥር ቅጥር ሆነው ከአሕዛብ የሚለዩ ሕጋት ተፈጽመዋል፤ ክርስቶስ የእነዚህ ሕጋት ፍጻሜ ነውና። (ሮሜ. 13፥10)
አሁን በእነዚህ የአይሁድ ሕጋት ሥር ለመሆን መፈለግ ከአዋቂነት ወደ ሕጻንነት፣ ከነጻነት ወደ ባርነት መመለስ ስለሆነ ሐዋርያው ይህን አምርሮ ይቃወማል። በዚህ መንገድ ሆነው አሕዛብ ወደ ወንጌል ለመምጣት የግድ እነዚህን የአይሁድ ሕጋት ፈጽመው 'አይሁድ' መሆን አለባቸው ብለው እዳ የሚጭኑትን አይሁድ-ዘመም መምህራን "ከክርስቶስ ተለይተው ከጸጋው የወደቁ፣ ስለክርስቶስ መስቀል እንዳይሳደዱ የሚሸሹ፣ የመስቀሉን እንቅፋት ለማስወገድ የሚሰሩ" በማለት ይወቅሳል፤ ከክርስትና ወንጌል በተቃርኖ ያቆማቸዋል። (ገላ. 5፥3፣ 11፤ 6፥12)
ሌላኛው የሕግ ገጽታ ደግሞ አይሁድን ከአሕዛብ ያለመለየት ለሁሉም የሰው ልጆች የሚሆነው እና ሕግ ያልተሰጣቸው አሕዛብ ሳይቀር በልቡናቸው የሚያውቁት፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ ከኃጢአት ተለይቶ የሚታወቅበት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ "መገረዝም ቢሆን አለመገረዝም ቢሆን ከንቱ ነው፤" ካለ በዋላ በተጻራሪ የሚጠቅመው "የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጠበቅ ነው እንጂ፤" ብሎ የገለጸው ይህን ሰፊውን እና ጥልቁን የሕግ ገጽታ ነው።
በርግጥ ከክርስቶስ መምጣት በፊት ባሕርያችን ደክሞ ኃጢኣት ሰልጥኖ ስለነበር ሰው በሕግ ኃጢኣትን ቢያውቅም በጽድቅ መጽናት አልቻለም ነበር፤ ይልቁንም በገነት ውስጥ እንደሆነው ሕጉ ሲከለክለው እየጎመጀ ኃጢኣትን ይሠራ ነበር። የጉስቁልና ዘመን ነበርና። በዚህም የተነሣ ቅዱሱን ሕግ ራሱ ለመጥፎ መጠቀሚያ ያደርግ የነበረውን ክፉ ውድቀት ለመናገር ሐዋርያው በዚህ በሰፊ ገጽታውም ጭምር ሕጉን "የኃጢኣት ሕግ"፣ "የባርነት ሕግ"፣ "የእርግማን ሕግ"፣ "የሞት ሕግ" እያለ ጠንከር ባሉ አገላለጾች ጠርቶታል። (ሮሜ. 5፥20፣ 8፥2፣ ገላ. )
ነገር ግን ከዚህ ተነሥተው ሰዎች ወደተሳሳተ ድምዳሜ እንዳይሄዱ ደግሞ ፈጥኖ ስለ ሕጉ በጎነት እና ጽድቅ ጥብቅና ይቆማል። (ሮሜ. 7)
ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መጥቶ የሕግን እውነተኛ ገጽታ (እግዚአብሔርን እና ባልንጀራን መውደድ) በፊደሉ ሳይሆን በጥልቅ ትርጉሙ አስተምህሮ እንዲሁም በተግባር ፈጽሞ ካሳየ በኋላ፣ በሞቱ እና በትንሣኤው ባሕርያችን አድሶ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ካጠነከረን በኋላ ግን ሕጉ አዲስ ኃይል እንዳገኘ ያስረዳን ዘንድ ሐዋርያው በብዙ መልኩ ይጥራል። በአንድ ቦታ "ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና፥ እርሱም፦ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚል ነው፤" በማለት ሕጉ በክርስቶስ የፍቅር ትእዛዛት እንደጸና ይናገራል። (ገላ. 5፥14) ይህንኑ ሲያመለክትም "የክርስቶስ ሕግ" እያለ ይናገራል። (ገላ. 6፥2) ቀድሞ ለኃጢኣት ኃይል መጠቀሚያ ሆኖ የነበረው በመንፈስ ቅዱስ ሃይል ለጽድቅ መሆን መጀመሩን ሲናገርም "የመንፈስ ሕግ" ይለዋል። (ሮሜ. 8፥2)
***
ጠቅለል ሲደረግ የቅዱስ ጳውሎስ የሕግ አስተምህሮ ሰፊ እና መልከ ብዙ (differentiated) ነው። በአግባቡ ለመረዳት ሰፊውን ታሪካዊ እና ነገረ-ሃይማኖታዊ ዓውድ ማጤን ይገባል። ዋናው ነገር ግን ታላቁ ሐዋርያ ሕግ የሚባል ነገር አያስፈልግም፤ ተሽሮአል ብሎ አላስተማረም። የሕጉን መንፈስ እና ዓላማ እያሳየ የተፈጸመውን እና የጸናውን በየፈርጁ አስረዳ እንጂ። ሕጉን በተሳሳተ መልኩ የሚረዱትንም አወገዘ እንጂ። በተጨማሪም ሕግ ከሚፈጸምበት ጸጋ እና ሃይል ተለይቶ "ከክርስቶስ እምነት" በተጻራሪ ሊቆም እንደማይገባ በሃይለ ቃል አስተማረ እንጂ። (ገላ. 2፥16)
ቅዱስ ጳውሎስ ሕግን እንደተቃወመ አድርጎ የሚተረጎመው አካሄድ የ15ኛው መ/ክ/ዘመን የሉተር እና የሌሎች ተሐድሶዎች የተሳሳተ መረዳት (distortion) ውጤት ነው። ሉተር ጉዳዩን ይረዳው የነበረው ከቅዱስ ጳውሎስ ዓውድ አንጻር ሳይሆን ከራሱ የግል የሕይወት ቀውስ እና ከሮም ቤተ ክርስቲያን ዘመንኛ ችግር አንጻር ነበር። ይህም ትልቅ ምስቅልቅል አምጥቷል።
Bereket Azmeraw
ብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አባቶቻችን ሐዋርያትን ሰማዕትነት በተቀበሉበት ቀናት በዓላት ሰይማ ታከብራቸዋለች፡፡ እንዲሁም በስማቸው የተሰየመውን ጾም በመጾም አሠረ ፍኖታቸውን ይከተሉ ዘንድ ምእመናንን ታሳስባለች፡፡ በሐምሌ ፭ ቀን ደግሞ የደጋጎቹን ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስን በዓል ታደርጋለች፡፡ የእነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን በዓል መደረጉ በአንድ ቀን ሰማዕትነት በመቀበላቸው ነው፡፡

ሁለቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አመራረጣቸው በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ የጥሪው መንገድ ግን ይለያይ ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ለሐዋርያነት የተመረጠው ጌታችን በገሊላ ባሕር አጠገብ ሲመላለስ ከወንድሙ እንድርያስ ጋር ሆኖ ዓሣ ለማጥመድ መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ወደ እነርሱም ቀርቦ “በኋላዬ ኑና ሰዎችን አጥማጆች እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ ወዲያውም መረባቸውን ትተው ተከተሉት፡፡ (ማቴ.፬፥፲፰‐፳)

በአንጻሩ የቅዱስ ጳውሎስ አመራረጥ ደግሞ በተአምር ነው፤ ይኸውም እንዲህ ነው፡፡ በቀደመ ስሙ ሳውል ተብሎ የሚታወቀው ይህ ሐዋርያ የቤተ ክርስቲያን አሳዳጅ ነበር፡፡ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ በአይሁድ እጅ ሲወገር የተስማማ የገዳዮቹንም ልብስ ጠባቂ ነበር፡፡ (የሐዋ. ፯፥፶፰-፷)

ቅዱስ መጽሐፍ “ሳውል ግን ቤተ ክርስቲያንን ያፈርስ ነበር ወደ ሁሉም ቤት እየገባ ወንዶችንም ሴቶችንም እየጐተተ ወደ ወህኒ አሳልፎ ይሰጥ ነበር፡፡ . . . ሳውል ግን የጌታን ደቀ መዛሙርት እንዲገድላቸው እየዛተ . . .” እንዲል፡፡ (የሐዋ.፰፥፫፤፱፥፩) በክርስቶስ አምነው የተጠመቁ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ከሊቁ ካህናቱ ዘንድ የፈቃድ ደብዳቤ ጠየቀ፡፡ ይህን ዓላማውን ለማስፈጸም ወደ ደማስቆ ሲጓዝ በርሱ ዙሪያ ከሰማይ መብረቅ ወረደ፤ ዐይኖቹም ታወሩ፤ ወደ ምድርም ወደቀ፡፡

በዚያም ሳለ “ሳውል ሳውል፥ ስለምን ታሳድደኛለህ” የሚለውን ድምፅ ሰማ፡፡ ያነጋገረው ሳውል የሚያሳድደው ጌታ ነበር፡፡ “አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ፤ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብኻል” አለው፡፡ ከዚያም በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ተነሥቶ ወደ ከተማው ገባ፡፡ ሦስት ቀንም ሳይበላ ሳይጠጣ ተቀመጠ፡፡ ሐናንያ የተባለው ከደቀ መዛሙርት ወገን የሆነ ወደ እርሱ ዘንድ ቀርቦ ጸለየለት፤ ዐይኖቹም ተፈወሱ፤ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ (የሐዋ.፱፥፩‐፲፰)

ቅዱስ ጳውሎስ በወቅቱ ስለሆነው ነገር ለቆሮንቶስ ምእመናን ሲተረክላቸው “ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ፡፡ እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝና፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ” እንዲል፡፡ (፩ኛቆሮ.፰፥፱)

የቤተ ሰብ ሕይወታቸው
ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ቤተ ሰቦቹ ደግሞ በቅፍርናሆም ይኖሩ ነበር፡፡ የኦሪት መጻሕፍትን ያልተማረ ከዝቅተኛው የማኅበረሰብ ክፍል የተገኘ ሰው ነበር፡፡ (የሐዋ. ፬፥፲፫) ጳውሎስ ደግሞ በኪልቅያ በምትገኘው በጠርሴስ ተወለደ፡፡ ከአይሁድ ወገን ከብንያም ወገን ነበር፡፡ (ፊል.፫፥፭) በጠርሴስም ሳለ በገማልያል እግር ሥር የኦሪት ትምህርቱን ተማረ፤ በትምህርቱም የተመሰከረለት ነበር፤ (የሐዋ.፳፪፥፫፤፳፮፥፳፬) ይህ የሚያሳየው የእግዚአብሔር መንግሥት ለተማሩትም ላልተማሩትም፣ ለባለጸጎችም ለድሆችም የተዘጋጀ መሆኑን ነው፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ባለ ትዳር ነበር፡፡ አማቱም ታማ በነበር ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤቷ ገብቶ እንደፈወሳት በወንጌል ተጽፏል፡፡ (ማቴ.፰፥፲፬‐፲፭) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ድንግል ነበር፡፡ “ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና ነገር ግን፥ እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፥ አንዱ እንደዚህ ሁለተኛውም እንደዚያ፡፡ ላላገቡና ለመበለቶች ግን እላለሁ፡- እንደ እኔ ቢኖሩ ለእነርሱ መልካም ነው፤ ነገር ግን፥ በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና፥ ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ” በማለት ለቆሮንቶስ ምእመናን ጽፏል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፯፥፯‐፱) ቤተ ክርስቲያን እንደ ጴጥሮስ ያገቡ እንደ ጳውሎስ ያሉ ደናግላንን ይዛ የምትገኘው ጌታችን ሁሉንም ወደ እርሱ ስለጠራ ነው፡፡

የስማቸው መለወጥ
ቅዱስ ጴጥሮስ የዮና ልጅ ስምዖን ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፭) ነገር ግን ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን “እናንተስ ማን ትሉታላችሁ” ብሎ ሲጠይቃቸው ሐዋርያው ተነሣና፡- “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ጌታችን “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ፡፡ እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም አለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም” በማለት ጴጥሮስ ብሎ ሰየመው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፲፯—፲፰)

ጳውሎስን ደግሞ ጌታችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጠራው በመጀመሪያ ስሙ ሳውል ብሎ ጠራው፤ በምስክርነቱ ጊዜ ደግሞ “ጳውሎስ ሆይ፥ በኢየሩሳሌም ስለ እኔ እንደ መሰከርህ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሃልና፥ አይዞህ አለው፡፡” (የሐዋ.፳፫፥፲፩)

አገልግሎታቸው
የቅዱስ ጴጥሮስ አገልግሎቱ በአብዛኛው ሕግ ለተጻፈላቸው፣ ነቢያት ለተላኩላቸው፣ መሥዋዕት ለሚያቀርቡ፣ ግርዛት ለተሰጣቸው ለአይሁድ ነበር፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስ አገልግሎት የነበረው በአሕዛብ መካከል ነበር፡፡ ይህንንም ሲመሰክር “ለተገረዙት ሐዋርያ እንዲሆን ለጴጥሮስ የሠራለት፥ ለእኔ ደግሞ ለአሕዛብ ሐዋርያ እንድሆን ሠርቷልና፡፡” ብሏል፡፡ (ገላ.፪፥፯‐፰) እንዲያውም በአንድ ወቅት ጳውሎስና በርናባስን አይሁድ ትምህርታቸውን በተቃወሟቸው ጊዜ “እነሆ ወደ አሕዛብ ዘወር እንላለን እንዲሁ ጌታ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ለማዳን ትሆን ዘንድ ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌሃለሁ ብሎ አዞናልና” ብለው ነበር፡፡ (የሐዋ. ፲፫፥፵፮—፵፯)

በበዓለ ኀምሳ ቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከተቀበሉ በኋላ ጴጥሮስና ዮሐንስ በትምህርታቸው በኢየሩሳሌም ለነበሩ ነፍሳት ደረሱ፡፡ በአንድ ቀን ብቻ ሦስት ሺህ ነፍሳት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተጨመሩ፡፡ (የሐዋ.፪) ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ “ከሁላችሁ ይልቅ በልሳኖች እናገራለሁና እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” በማለት ስለተሰጠው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ መስክሯል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፲፬፥፲፰) ሁለቱም ሐዋርያት በምእመናን ላይ እጃቸውን በመጫን ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ያሳድሩ ነበር፡፡ (የሐዋ.፰፥፲፬፤፲፱፥፭‐፮)

በአገልግሎታቸው ድንቅ ተአምራትን ፈጽመዋል፡፡ ለምሳሌ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፡፡ “እግዚአብሔርም በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት ያደርግ ነበር፤ ስለዚህም ከአካሉ ጨርቅ ወይም ልብስ ወደ ድውዮች ይወስዱ ነበር፥ ደዌያቸውም ይለቃቸው ነበር ክፉዎች መናፍስትም ይወጡ ነበር፡፡” (የሐዋ.፲፱፥፲፩—፲፪) በኢዮጴም ጣቢታ የምትባል አገልጋይን ከሞተች፤ አጥበውም በሰገነት ከአኖሯት በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ካለበት ተጠርቶ ከጸለየ በኋላ ጣቢታ ሆይ ተነሽ ሲላት ዐይኖቿን እንደከፈተች ተጽፏል፡፡ (የሐዋ.፱፥፴፮—፵፪) በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ አውጤኪስ የሚባል ከሦስተኛ ደርብ ወደ ታች ወድቆ የሞተን ጎልማሳ እንዲነሣ አድርጓል፡፡ (የሐዋ.፳፥፯—፲፪)
መልእክታት
ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት መልእክታትን ለምእመናን ጽፏል፤ ቅዱስ ጳውሎስ በአካል ተገኝቶ ለሰበካቸውና ላጠመቃቸው የሮሜ፣ የቆሮንቶስ፣ የገላትያ፣ የኤፌሶን፣ የፊልጵስዩስ እና የቆላስይስ፣ የተሰሎንቈ፣ ለዕብራውያን ምእመናን መልእክታትን የጻፈ ሲሆን ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቹ ለጢሞቴዎስ፣ ለቲቶ እና ለፊልሞና መልእክታትን ሰዶላቸዋል፤ በአጠቃላይ ዐሥራ አራት መልእክታትን ጽፏል፡፡

ሰማዕትነታቸው
ሁለቱም ቅዱሳን ሐዋርያት በሮማው ቄሳር ኔሮን ዘመን ፷፯ ዓ.ም. ሰማዕትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ ሰማዕትነት የተቀበለ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ አንገቱን ተቀልቶ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡
በረከታቸው ይደርብን፤ አሜን!

Mahebere kidusan
እያንዳንዱ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ /1ኛ ቆሮ 3 ፤ 10/

እንኳን ለበዓለ ጴጥሮስ ወጳውሎስ አደረሰን አደረሳችሁ።

በቅዳሴያችን ወቅት ገባሬ ሠናይ ዲያቆኑ ከጳውሎስ መልእክት ካነበበ በኋላ በዜማ የምንለው መርግፍ እንዲህ ይላል። “ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ ሠናየ መልእክት ፈዋሴ ዱያን ዘነሣእከ አክሊለ ሰአል ወጸሊ በእንቲአነ ያድኅን ነፍሳተነ በብዝኀ ሣህሉ ወምሕረቱ በእንተ ስሙ ቅዱስ” – ‘አክሊልን የተቀዳጀህ፣ ድውያንን የምትፈውስ፣ መልእክትህ ያማረ፣ ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ ሆይ በይቅርታውና በቸርነቱ ብዛት ስለ ቅዱስ ስሙም ብሎ ነፍሳችንን ያድን ዘንድ [ወደ ጌታ] ስለእኛ ለምንልን፣ ጸልይልንም’ ማለት ነው።

በዚህች አጭር ጸሎት እንዲያደርግልን በምታሳስብ አጭር ልመና ውስጥ የቅዱስ ጳውሎስን ማንነት በአጭሩ የሚገልጹ ሦስት ነገሮች ተቀምጠዋል። ድዋያንን የሚፈውስ፣ መልዕክቱ ያማረ መሆኑና በዚህም አክሊል የተቀዳጀ መሆኑን የሚያሳዩ ወሳኝ መግለጫዎች ናቸው።

ቅዱስ ጳውሎስ በሁለንተናው ፈዋሴ ዱያን ነውና ዛሬም ቤተ ክህነታችን ከተያዘበት፣ የዘረኝነት፣ የጠባብነት፣ የሌብነት፣ የአላዋቂነት፣የፖለቲከኝነት እና ለሹመት የማበድ በሽታ ይፈውስልን።

መልእክቱም በእውነት በእጅጉ ያማረ ነው። በቆሮንቶስ መልእክቱ ላይ “የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ ተሰጠኝ መጠን እንደ ብልሃተኛ የአናጺ አለቃ መሠረትን መሠረትሁ፥ ሌላውም በላዩ ያንጻል። እያንዳንዱ ግን በእርሱ ላይ እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ። ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልምና፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ማንም ግን በዚህ መሠረት ላይ በወርቅ ቢሆን በብርም በከበረ ድንጋይም በእንጨትም በሣርም ወይም በአገዳ ቢያንጽ፥ የእያንዳንዱ ሥራ ይገለጣል፤ በእሳት ስለሚገለጥ ያ ቀን ያሳያልና፥ የእያንዳንዱም ሥራ እንዴት መሆኑን እሳቱ ይፈትነዋል። ማንም በእርሱ ላይ ያነጸው ሥራ ቢጸናለት ደመወዙን ይቀበላል፤ የማንም ሥራ የተቃጠለበት ቢሆን ይጎዳበታል” /1ኛ ቆሮ 3 ፤ 10 -15/ ሲል የገለጸውን እና እኛ ካለንበት ሁኔታ አንጻር ላለው የሚጠቅም የሚመስለኝን እንኳ ብናየው መልእክቱ ምንኛ ያማረ ነው። 

ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ሐዋርያት የሠሩት የቤተ ክርስቲያን መሠረት የማይለወጥ ማንም ፈላስፋም ሆነ ፖለቲከኛ፣ ጎልበተኛም ሆነ ሴረኛ ሊለውጠው የማይችል ንጹሕ ሐዋርያዊ መሠረት ነው ያለን። ከእነርሱ በኋላ የመጡት ግን ሐዋርያው እንዳለ በወርቅ በብር እና በከበረ ድንጋይ ያነጹ ቢኖሩም አንዳንዶቹ ደግሞ በገለባ፣ አንዳንዶቹም በሣር ሌሎቹም ደግሞ በእንጨት በጭራሮ የሚያንጹ ነበሩ። እኛ ሀገር በዚህ ወቅት የምናየው የዘር ቤተ ክህነት እና የጎሳ ጵጵስና ጉዳይ በሣር እና በአገዳ ያንጻሉ ያላቸውን የሚያስታውስ ነው። እንዲህ በእንጨት፣ በሣር፣ በአገዳ የሚያንጹት ቢኖሩም ቤተ ክርስቲያን ግን ጸንታ ትኖራለች ። በእግዚአብሔር የፍርድ እሳት ሲመረመር የእነርሱ ይቃጠላል፣ የባለ ብሮቹ እና የባለወርቆቹ የተባለው የንጹሐኑ ሥራ እና ተጋድሎ እና የመሳሰሉት ግን የበለጠ ይጠራል፣ ያበራል፣ ይከብራል። 

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በየዘመኑ ስለሚኖር እና አሁንም ስላለነው ሲናገርም “በትልቅም ቤት የእንጨትና የሸክላ ዕቃ ደግሞ አለ እንጂ የወርቅና የብር ዕቃ ብቻ አይደለም፥ እኵሌቶቹም ለክብር፥ እኵሌቶቹም ለውርደት ይሆናሉ” /2ኛ ጢሞ 2 ፡ 20/ ሲል የገለጸውም ምንኛ ያምራል። እውነት ለመናገር በትልቋ ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የክብር ዕቃ ዓይነት የከበሩ ሰዎች ቢኖሩም ግን ደግሞ መናኛ እና የውርደት ዕቃዎች በተባሉት የምንመሰል ሥራችን ሁሉ ተዋርዶ ማዋረድ የሆንንም እንኖራለን። ዘንድሮ እያየን ያለውም ይህን ይመስለኛል። ተዋርደው የሚያዋርዱ መንደርተኛ ሿሚዎች እና ተሿሚዎች፣ ደጋፊ አሽቃባጭ የጥፋት ቲፎዞዎች እና አጨብጫቢዎች ። ቅዱስ ጳውሎስ የሚለን በተልቅ ቤት ውስጥ ይህ ሁሉ ሊኖር የግድ ነው ነው የሚለን። ይህ ነገር ሁልጊዜም የነበረ እና ያለ ቢሆንም ዘንድሮ የምናየው ግን በትልቁ ቤት በእግዚአብሔር ቤት በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ዕቃው ሁሉ እጅ ሲነካው ቅድድ የሚል፣ ትንሽ ሙቀት የሚያቀልጠው የያዘውን ነገር እንኳ በወጉ የማያደርስ፣ የሽክል ዕቃ ያህል እንኳ ስባሪው የማይገኝ የእኛኑ ዘመን ስስ ፌስታል የሆንን ይመስለኛል። እውነቱን ለመናገር በየቤታችን ያለውን የኬንያን የፕላሲክ ዕቃ ያህል እንኳ ወግ መዓርግ ማጣታችን በእጅጉ ያሳዝናል። እንኳን የወርቅ እና የብር ዕቃ መሆን የሸክላ ዕቃ መሆንን እንዳቃተን ሳስብ እንኳ እገረማለሁ። ነገር ግን መልእክቱ ያማረው ያ ምርጥ ሐዋርያ እንዳለው በትልቁ ቤት በእግዚአብሔር ቤት ግን ይህ ሁሉ ይኖራል ተብሏልና ቢያንስ መደነቅ የለብንም።

ቅዱሱ ሐዋርያ ባዛሬው ዕለት ለእውነት ፣ እውነት ለተባለው ለክርስቶስ ተሰውቶ አክሊል ተቀዳጅቷል። አሁን የእርሱን ሥልጣን የሚፈልጉት ደግሞ የየጎሣ ዘውድ ለመቀዳጀት ይጣደፋሉ፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጥሶ ለመሾም ይሯሯጣሉ፣ ይፎክራሉ፣ ይሸልላሉ። ከሁሉ የሚገርመኝ ደግሞ ይህን በማድረጋቸው ያሸንፉ፣ ያጎዱን፣ በንዴት ያቃጠሉን መስሏቸው ሲደስቱ እና ሲደልቁ ስመለከት  እውነተኛው ዕብደት ምን እንደሚያደርግ እየገባኝ እገረማለሁ። በርግጥ በእብደት ውስጥ ያለ እብደቱ ገብቶት አያውቅም። እንኳን ያበደ፣ ለጊዜው እእምሮውን የሳተም ምን እንደሆነ የሚጠይቀው ከተሻለው በኋላ ነው። እውነቱን ለመናገር አሁን በትግራይ የሚታሰብውን ሳስብ ደም ያሰክራል የሚለው ነው ወደ አእምሮየ የሚመጣው። በተለይ አንዳንዶች ይልቁንም የዚሀ ጉዳይ አቀንቃኞች በርግጥም ተጎድተዋል፣ ደም አስክሯቸዋል። ፈዋሴ ዱያን የተባለው ቅዱስ ጳውሎስ ይፈውሳችሁ ከማለት በቀር ሌላ ምን ይባላል። ሰው ከእግዚአብሔር ቃል እና ሕግ ይልቅ እንዴት ለፖለቲከኞች ጭልጥ ብሎ ያታዘዛል? የእነርሱን ለብቻው የምጽፍበት ስለሚሆን አሁን አልነካካም። ለሁሉም ግን አእምሮው ጨርሶ ያልጠፋበት ካለ ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ማንም ቢሆን እንዴት እንዲያንጽ ይጠንቀቅ።
Dn. Birhanu Admas
Everyday Saints and Other Stories(1).pdf
15.8 MB
In Communist Russia in 1984, five youths from non-religious backgrounds joined a monastery. This is the story of what they experienced and some of the "everyday saints" they met. The author says, "In this book I want to tell you about this beautiful new world of mine, where we live by laws completely different from those in 'normal' worldly life—a world of light and love, full of wondrous discoveries, hope, happiness, trials and triumphs, where even our defeats acquire profound significance: a world in which, above all, we can always sense powerful manifestations of divine strength and comfort."
በዓለ ቅድስት ሥላሴ

እንኳን ለቅድስት ሥላሴ ዓመታዊ ክብረ በዓል አደረሳችሁ!

ውድ አንባብያን! እንደምን ሰነበታችሁ? አሜን! የአምላካችን የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን! የሐምሌ ሰባት በዓለ ቅድስት ሥላሴን በተመለከተ አጭር ጽሑፍ አቅርበንላችኋል፤ ተከታተሉን!

በዚህችም ቀን ልዩ የሆኑ ሦስቱ አካላት ቅድስት ሥላሴ በኦሪት መጽሐፍ እንደ ተጻፈ ወደ አብርሃም ቤት ገቡ ያቀረበላቸውንም ተመገቡ። የይስሐቅንም ልደት አበሠሩት ባረኩት፤ አከበሩትም። (መጽሐፈ ስንክሳር ዘሐምሌ ሰባት)

አብርሃም አባታችን በተመሳቀለ ጎዳና አራት በር ያላት ግንብ ሠርቶ ያለፈውን ያገደመውን የወጣውን የወረደውን ሲቀበል ይኖር ነበር:: ሰይጣን በዚህ ቀንቶበት ግንባሩን ገምሶ፣ ልብሱን፣ ገፎ፣ አጥንቱን ከስክሶ፣ ልብሱን በደም ለውሶ ሄዶ፡፡ ወደ አብርሃም ቤት መሄጃ መንገድ ላይ ተቀምጦ ወደ አብርሃም ቤት እንግዳ ሲመጣ “ወዳጄ ወዴት ትሄዳለህ?” ይለዋል፤ “ወደ አብርሃም ቤት” ይለዋል:: “አይ አብርሃም የቀድሞው አብርሃም መሰለህ? እኔ ያጎርሰኛል፤ ያለብሰኛል ብዬ ብሄድ ይኼው እንደምታየኝ ግንባሬን ገምሶ፣ ደሜን አፍሶ ሰደደኝ፤ እኔን ያገኘ መከራ እንዳያገኝህ ይቅርብህ፤ ባትሄድ ይሻልሃል” እያለ እንግዳ መለሰበት::

ከዚህ በኋላ አብርሃም “ማዕደ እግዚአብሔር ያለ ምስክር እንዴት ይቀርባል?” ብሎ ሦስት ቀን ጾሙን አደረ። ቅድስት ሥላሴ ርኅሩኃን ናቸውና በእንግዳ ልማድ ሄደው ከደጁ ከመምሬ ዛፍ ተቀምጠው አያቸው፤ እርሱም ሊቀበላቸውም እየሮጠ ወጣ፤ በቀረበም ጊዜ ወደ ምድር ሰገደ፤ “አቤቱ በፊትህ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ ባርያህን አትለፈኝ ብዬ በእውነት እለምንሃለሁ፤ ከቤቴ ገብታችሁ ዕረፉ” አላቸው:: “በፊትህ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ ባርያህን አትለፈኝ” ብሎ መናገሩ አንድነቱን፣ ጥቂት ውኃ ይምጣላቸሁ እግራችሁን ታጠቡ ብሎ መናገሩ ሦስትነታቸውን ለመግለጽ ነው:: ይህ ምሳሌ ነው፤ ዛፏ የእመቤታችን ምሳሌ ናት፤ ሥላሴ በዛፏ ሥር ተቀምጠው እንደ ታዩ አብ ለአጽንዖ፣ መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ፣ ወልድ ለተዋሕዶ በእመቤታችን የማደራቸው ምሳሌ ነው:: ይህቺ ዛፍ በአብርሃም ደጃፍ ተተክላ፣ ቅርንጫፎቿን አንሰራፍታ ቅድስት ሥላሴን ለመቀበል እንደበቃች፣ እመቤታችንም ከአብርሃም ዘር ተወልዳ፣ ጸጋዋ ተንሰራፍቶ፣ ክብሯ፣ ልዕልናዋ ሰፍቶ የሥላሴ ማደሪያ ለመሆን በቅታለችና፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ “አንቲ ውእቱ ዕፀ ድርስ ዘለአብርሃም በርስአኒሁ ዘብኪ አጽለለ እግዚአብሔር በሥላሴሁ፤ለአብርሃም በእርጅናው ወቅት እግዚአብሔርን በሦስትነት ያስጠለለብሽ የወይራ ዛፍ አንቺ ነሽ” በማለት ገልጾታል:: (እንዚራ ስብሐት)

ቅድስት ሥላሴም “አዝለህ አግባን” አሉት ጽንዐ ፍቅሩን ለማጠየቅ ነው፡፡ አብርሃምም አንዱን አዝሎ ሲገባ ሁለቱን ገብተው አግኝቷቸዋል! አብርሃም ሣራን “ሦስት መስፈሪያ ዱቄት አምጥተሸ በአንድ አድርገሽ ጋግሪ” አላት፤ እርሷም እንዳዘዛት አደረገች፤ “ወአቅረበ ሎሙ መዓረ ወዕቋነ ወእጓለ ላህም ስቡሓ፤ ድፎ ዳቦ አቅርቦላቸዋል፤ ላህም ሠውቶላቸዋል” ባርከው አስነሥተውለታል! ሕያዋን እንደሆኑ ለማጠየቅ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ልጅ እንደሚወልድ ነግረውት ሲሄዱ ከሦስቱ አንዱ “የዛሬ ዓመት በእውነት ወደ አንተ እመጣለሁ፤ ሚስትህ ሣራም ልጅ ትወልዳለች” ብሎ ተስፋውን ነግሮት ሄደዋል:: (ዘፍ.፲፰፥፲)

ቅድስት ሥላሴ በእንግዳ አምሳል የገቡት በቤተ አብርሃም መስተናገዳቸውን ቅዱስ ያሬድ ሲናገር “አብርሃም ርእየ ሠለስተ እደወ በዛቲ ዕለት ምሥጢረ ሥላሴ ዜነወ እትነሣእ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ውእቱ ኀይልየ አምላኪየ ረዳእየ ወመድኀንየ፤ አብርሃም ሦስት አረጋውያንን ተመለከተ፤ በዚያች ዕለት የሥላሴን ምሥጢር ተናገረ፤ አብና ወልድ መንፈስ ቅዱስ ኀይሌ፣ አምላኬና መድኀኒቴ ነው ብዬ እነሣለሁ” በማለት የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት ተገልጦለት እንደተናገረ ሊቁ በዜማው መስክሯል:: (ድጓ ዘሥላሴ ኆኅተ ሰብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቅጽ ፪ ገጽ ፭፻፰፯)

ይስሐቅን ሳይወልድ አብራም ይባል ነበር፣ አበ ውሁዳን ማለት ነው፡፡ ይስሐቅን ከወለደ በኋላ ግን አብርሃም ተብሏል አበ ብዙኃን ማለት ነው፡፡ (ዘፍ.፲፯፥፮ አንድምታ ትርጓሜ)

አባታችን አብርሃም ይስሐቅን ሳይወልድ “አብራም” ይባል ነበር፤ “አበ ውሁዳን” ማለት ነው፡፡ ይስሐቅን ከወለደ በኋላ ግን “አብርሃም” ተብሏል፤ “አበ ብዙኃን” ማለት ነው፡፡ ባሕረ ጥበባት ቅዱስ ያሬድ እግዚአብሔር ለአብርሃም ምሥጢር እንደገለጠለት ሲናገር “አብርሃምን መረጠው ወዳጄም አለው፤ የተሰወሩ ምሥጢራትን ሁሉ ገለጠለት፤ አብርሃም እንደ ፀሐይና እንደ ንጋት ኮከብ ብሩህ እንደሆነ በመንፈስ ቅዱስ ሁሉንም ነገር ነገረው” ሲል ዘምሯል፡፡ (ድጓ ዘሥላሴ፣ ኆኅተ ሰብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቀጽ ፪ ገጽ ፭፻፰፯)

ስለዚህ በአብርሃም በኩል ምሥጢሩን ለገለጡለት ለቅድስት ሥላሴ ምስጋና እንደሚገባ ሲናገር “ንግሩ ምሕረቶ ለሥላሴ ወዜንዉ ሠናይቶ ለሥላሴ መሃይምናን ንግሩ ምሕረቶ ለሥላሴ፤ የሥላሴን ምሕረቱን ንገሩ፤ የሥላሴ በጎነቱን መስክሩ! እናንተ ምእመናን የሥላሴ ምሕረቱን ተናገሩ” በማለት ያሳስባል።

አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በስም በአካል በግብር ሦስትነት በባሕርይ በሕልውናና በፈቃድ አንድነት የጸኑ ናቸው። በዚህ ጊዜ ተገኙ፤ በዚህ ጊዜ ያልፋሉ አይባሉም፤ መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸው። እንግዲህ ሥላሴ ስንል፦

*ሥላሴ ዋሕድ* በአንድ እግዚአብሔር ከሚገኝ ከሦስቱ አካላት ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ በቀር፥ ቅድመ ዓለም ቢሆን ፣ ድኅረ ዓለማት ቢሆን ፈጽሞ ሌላ መንቲያ ወይም ተመሳሳይ የሌለውና ብቻውን የሚኖር ልዩ ሦስት "ሦስትነት" መሆኑን የሚያረጋግጥ አብነት ነው።

ሃሌ ሉያ ለአብ ፥ሃሌ ሉያ ለወልድ፥ሃሌ ሉያ ወለመንፈስ ቅዱስ ሥላሴ ዋሕድ።

*ሥላሴ ዘለዓለም (ዘለዓለም ሥላሴ)* ይህ ሲባል የሥላሴ መጠሪያ ስም ከጊዜ በኋላ የተገኘ ሳይሆን ከዘለዓለም በሥላሴነቱ የነበረ ያለ የሚኖር መሆኑን የሚታወቅበት ገለጻ ነው። እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም ሀሎ እግዚአብሔር በትሥልስቱ፤ እግዚአብሔር ከዓለም በፊት እስከዘለዓምም ድረስ እግዚአብሔር በሦስትነቱ አለ፡፡ (ቅዳሴ ዘዲዮስቆሮስ)

*ሥሉስ ቅዱስና ልዩ ሦስትነት* ይህ ሦስትነት አንድነት ያለው በመሆኑ ሥሉስ ቅዱስ ይሰኛል ማለት ሦስት አካላትን የያዘ ቅዱስ የተለየ ባሕርይ ያለው እግዚአብሔር ወይም መለኮት ማለት ነው።

*ልዩ ሦስትነት* የእግዚአብሔር ልዩ ሦስት ሲባል በሦስትነት በአንድነት የሚገኙ ልዩ ምሳሌዎች አሉና ከዚያ ለይቶ ለማስገንዘብ ነው። ከእነዚህም አንዱ የአካል ሦስትነት ቢኖራቸውም የባሕርይና የህልውና አንድነት የላቸውም። ለምሳሌ “አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ” ብለን የምንጠራቸው ሦስት ስሞች ናቸው።

እንደዚሁም ደግሞ በአንድ የአካል ስም ሲጠሩ በኩነታት ሦስትነት ያላቸው አሉ። እነርሱም ፀሐይ፣ እሳት፣ ቀላይ፣ ባሕር፣ ተክልና ንፋስ ናቸው። የሰው ነፍስ ብትሆንም እንኳን የኩነት፣ የግብር ሦስትነት አላት እንጂ የአካል ሦስትነት የህልውና አንድነት የላትም።
ሥላሴ ግን የአካል፣ የግብር፣ የኩነት ሦስትነት፥የመለኮት የባሕርይ የህልውና አንድነት አላቸው። ልዩ ሦስት "ቅድስት ሥላሴ" ይባላሉ።

ዳግመኛም ሥላሴ፡-
ወላድያነ ዓለም “ቅዱስ” ሥላሴ ማለት ትተን “ቅድስት” ሥላሴ ብለን በሴት አንቀጽ እንጠራቸዋለን፤ የምንጠራበት ምክንያት ምንድን ነው? ስንል ስለ ብዙ ምሥጢር ነው፤ እንደ ሊቃውንቱ ትንታኔ ሴት ርኀርኅተ ልብ ናት፤ ሥላሴም ለፍጥረታቸው ርኅሩኃን ናቸውና፡፡ አንድም ሴት ከባሕርይዋ ልጅ ትወልዳለች! ሥላሴም ወላድያነ ዓለም ናቸው፤ ይህን ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር ካለመታየት ወደ መታየት አምጥተው የፈጠሩ ፈጥረውም የሚያስተዳድሩ ቅድስት ሥላሴ ናቸውና:: አንድም ጽኑዕ፤ ንጹሕ፣ ክቡር፣ ልዩ ሲል ነው፡፡ ሰውን ጽኑዕ ቢሉት እስከ ጊዜው ነው፤ እንጂ ኋላ በሕማም በሞት ይለወጣል:: ቅድስት ሥላሴ ግን መቼም መች ሕልፈት ውላጤ ድካም ሕማም የለባቸውም፡፡

አምልኮት መሠረት

ቅድስት ሥላሴ የአምልኮታችን መሠረት ነው፤ ይህ ማለት ምስጋናም ሆነ አምልኮት የሚጀመረው በቅድስት ሥላሴ ነው፤ የማንኛውም አገልግሎት መክፈቻም ሆነ መዝጊያ የቅድስት የሥላሴ ስም ነው! ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን “በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ” ብላ ጀምራ “ስብሐት ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ” ብላ ትዘጋለች::

ባሕረ ጥበባት ቅዱስ ያሬድ ሲናገር “ሃሌ ሃሌ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሃሌ ሉያ አአትብ ወእትነሣእ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ሠለስተ አስማተ ነሚእየ እትመረጐዝ እመኒ ወደቁ እትነሣእ ወእመኒ ሖርኩ ውስተ ጽልመት እግዚአብሔር ያበርህ ሊተ በእግዚአብሔር ተወከልኩ፤ ቅድመ ዓለም የነበረ ዛሬም ያለ ወደ ፊትም ዓለም አሳልፎ የሚኖር በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተነሥቼ አማትባለሁ፤ እነዚህን ሦስት ስሞች ይዤ እመረኮዛለሁ፤ ብወድቅ እነሣለሁ፤ ወደ ጨለማ ብሔድ እግዚአብሔር ያበራልኛል፤ በእግዚአብሔር ታመንኩ” ሲል የሃይማኖታችን መነሻና መድረሻ ቅድስት ሥላሴ መሆኑን መስክሯል:: (ድጓ ዘሥላሴ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቅጽ ፪ ገጽ ፭፻፹፰)

ዳግመኛም ቅድስት ሥላሴ የአምልኮታችን መሠረት የእምነታችን ምንጭ እንድሆነ ሊቁ ግልጥ አድርጎ ሲነግረን “ነአምን ወናመልክ በአሐዱ እግዚአብሔር ዘእምቅድመ ዓለም ሀሎ ወነአምን በካልዑ እግዚአብሔር ዘበምልክናሁ ለአብ ይመስሎ ወነአምን በሣልሱ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ዘይመልዕ፤ ቅድመ ዓለም በነበረ በአንዱ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን እናመልካለን፤ አብን በጌትነት በሚመስለው በሚተካከለው በእግዚአብሔር ወልድ እናምናለን እናመልካለን፣ በዓለም ምሉዕ በሆነው በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እናምናለን እናመልካለን” ሲል ቅድስት ሥላሴ የአምልኮታችን ማዕከል መሆናቸውን ተናግሯል፡፡ (ድጓ ዘሥላሴ)
የሚሠዋው መሥዋዕት፤ የሚጸለየው ጸሎት፣ የሚታጠነው ዕጣን የሚቀርበው ቁርባን ሁሉ የሚያርገው ወደ ቅድስት ሥላሴ ነው:: ሊቁ እንዲህ እንዳለ “አንትሙሰ ከመ ዕብነ ሕይወት ተሐነጹ ቤቶ ለመንፈስ ቅዱስ ወለክህነቱ ቅዱስ ከመ ታዕርጉ መሥዋዕተ ወትንግሩ ሠናይቶ፤ ለቅዱስ አገልግሎት ሕያው መሥዋዕትን ታሣርጉ ዘንድ በጎነቱን ትነግሩ ዘንድ፣ እናንተ እንደ ሕይወት ድንጋይ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ሆናችሁ ታነጹ” በማለት ዘምሯል፡፡ (ድጓ ዘሥላሴ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቅጽ ፪ ገጽ ፭፻፹፰)

ሙሴ የያዛቸው ሦስት ስሞች

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ወደ ከነአን ሲጓዝ ለጉዞው መሳካት የእግዚአብሔርን ረድኤት የሚጠይቅበትና ሕዝቡ ሲበድሉ የእግዚአብሔርን ምሕረት የሚማፀንበት ሦስት ስሞች ነበሩ፡፡ እነዚህን የያዛቸው ሦስት ስሞች ደጋግሞ መጥራት የፈጣሪውን ምሕረትና ረድኤት አግኝቷል፤ እነዚሀ ሙሴ የያዛቸው ስሞች ምንድን ናቸው? ሙሴ በአብርሃም፣ በይስሐቅ፣ በያዕቆብ ስም ፈጣሪውን ይማጸን እንደነበር ተናግሯል፡፡ እነዚህ ሦስት ስሞች የሥላሴ ምሳሌ ናቸው፤ እነዚህ ስሞች የቃል ኪዳን ማስታወሻ ናቸው፤ እግዚአብሔር ለጊዜው ምድራዊቷ ርስት ከነአንን እንደሚያወርስ፣ ለፍጻሜው ደግሞ ሰማያዊቷን ርስት ወደ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚያወርስ ከሕዝቡ በረድኤት እንደማይለይ ቃል ኪዳን ይገባ የነበረው በእነዚህ ስሞች ነበር፤ ሕዝቡም ለአብርሃም ለይስሐቅ ለያዕቆብ የገባውን ቃል ኪዳን አስቦ የእግዚአብሔር ልብ እንዲራራላቸው ያደርጉ ነበር።

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ይገልጠዋል “መፍቀሬ ሰብእ ክርስቶስ ፈኑ ሣህለከ ወምሕረተከ ዘአንተ ታርኁ ክረምተ በጸጋከ ወትሴሲ እመዝገብከ ስብሐት ለከ ወዐቢይ ኀይልከ ዘሠራዕከ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ ዘሠርዐ ለአብርሃም ወመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ንስእለከ ወናስተበቊዐከ እስመ ኵሉ ዘሥጋ ያንቃዓዱ ኀቤከ፤ ሰው ወዳጅ ክርስቶስ ሆይ ይቅርታህንና ምሕረትህን ላክ፤ አንተ ክረምትን የምትከፍት፣ ከመዝገብህ በጸጋህ ትመግባለህ፤ ምስጋና ለአንተ ይገባል፤ ኀይልህ ታላቅ ነውና፤ ለዕረፍት ሰንበትን የሠራህ፤ ለአብርሃም ለይስሐቅ የማልክ፤ ለያዕቆብ ምስክርነትን ያቆምክ” ሲል ዘምሯል፡፡ እነዚህ ሦስት ስሞች (አብርሃም ይስሐቅና ያዕቆብ) የእግዚአብሐር ሕዝብ የመሆን ምልክት ነበሩ፤ ሥላሴም የሃይማኖት ምልክት ናቸውና፡፡ (ድጓ ዘሥላሴ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቅጽ ፪ ገጽ ፭፻፹፱)

ቅዱስ ያሬድ ሲናገር “ነሡእየ ማዕተበ ዘወልደ እግዚአብሔር አአትብ በሥላሴ እመኒ ወደቁ አቲብየ እትነሣእ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኀይለ መስቀሉ እትመረጐዝ፤ የወልደ እግዚአብሔርን የኢየሱስ ክርስቶስ ምልክት የኾነውን ቅዱስ መስቀል ይዤ በሥላሴ ስም አማትባለሁ፤ ብወድቅ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አማትቤ እነሣለሁ፤ በመስቀሉም እመረኮዛለሁ” ሲል ዘምሯል:: (ድጓ ዘሥላሴ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ ቅጽ ፪ ገጽ ፭፻፹፱ )

በአጠቃላይ ምሥጢረ ሥላሴን በሚገባ መርምሮ መረዳት ለማንም ቢሆን አይቻለውም። እርሱ ባወቀ ግን በብዙ አይነት በብሉይ ኪዳንም ይልቁንም በሐዲስ ኪዳን ምሥጢረ ሥላሴን እራሱ ባለቤቱ በጥምቁቱ ገልጦልናል፡፡ ይህንንም በዓል ሰናከብር እግዚአብሔር (ሥላሴ) በአብርሃም ቤት ተገኝተው፣ የአብርሃምን ቤት በርከው ሊመጣ ያለውን የሐዲስ ኪዳን ነገረ ድኅነት በግልጥ ነገሮናል። እኛም በዓሉን ሰናከብር እምነታችን በቅድስት ሥላሴ ላይ በማድረግ በቀናች ሃይማኖት ልንጸና ይገባናል!

እንደ አብርሃም ንጹሕ ልብ ይዘን፣ ከኀጢአት ርቀን እንግዶችን እንድንቀበል አምላካችን እግዚአብሔር ይርዳን፤ አሜን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
ምንጭ፦ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ በሊቀ ጉባኤ ጌታሁን ደምፀ
አምስቱ አዕማደ ምሥጢር በምኑን በኀበ ሰብእ
ሃይማኖተ አበው ተስፋ ገብረ ሥላሴ
ምሥጢረ ምሥጢራት በገብረ መድኅን እንየው እና መዝገበ ቃል ገ/ሕይወት

Mahebere kidusan
Media is too big
VIEW IN TELEGRAM
እግዚአብሔርን የኢትዮጵያ ብቻ አምላክ ማድረግ አደገኛ ነው

#ዲያቆን_ያረጋል_አበጋዝ
ነገረ ሃይማኖት 101
***
በአመክንዮአዊነት የታጠረ፣ በተወሰኑ ፎርሙላዎች ላይ የቆመ፣ ወጥ በሆነ መንገድ በቀላሉ ማብራራት የሚቻል (coherently explainable) ነገረ-ሃይማኖታዊ ሐተታ ስታይ የሆነ የጎደለ ነገር እንዳለ ተረዳ። የክርስትና ነገረ-ሃይማኖት ከአመክንዮ ጋር የሚቃረን ባይሆንም ከሰው መረዳት የሚያልፍ እና በጥቂት አመክንዮአዊ ሐተታዎችና ፎርሙላዎች የማይጠቃለል ምሥጢር አለው። መለኮታዊ ስለሆነ!
በመሆኑም ሰዎች በአመክንዮአቸው ልክ ቀንሰው የሰፉት (reductionist) ትምህርት የሚቀረው ብዙ ነገር አለ፤ ስህተትን ያስከትላል።
የምዕራቡ ዓለም ክርስትና በመካከለኛው ዘመን ክርስትናን በአርስቶትላዊ አመክንዮ ውስጥ ለመቀመር ሞክሮ ብዙ ተጎድቷል። የእኛም ሊቃውንት በዚህ አልተፈተኑም ማለት ይከብዳል። በተለይ በአንዳንድ 'ሊቃውንት' ነገረ-ክርስቶስ የሚብራራበት የመገናዘብ ሐተታ (communication of idioms) የተለጠጠ እና አመክንዮአዊ ትምክህት የሚታይበት ነው። ይህ ወደ ችግር እንጂ ድኅነት የሚወስድ አይደለም። ነገረ-ክርስቶስ የመዳን ምሥጢር ነው። ክብር ይገባዋል።

Bereket Azmeraw