ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ
15.5K subscribers
335 photos
80 videos
146 files
208 links
This channel is not operated by Deacon Yaregal Abegaz

https://youtube.com/@yaregalabegaz?si=1f5NHTaQ2l2LbxWQ

“ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው።”
— 2ኛ ቆሮ 11፥28
Download Telegram
ቅዱስ ሚካኤል - መልአከ ምክሩ
***
በቅዱሳት መጻሕፍት እግዚአብሔር ከቅዱሳን ጋር ስለሚያደርገው የምክር ጉባኤ ተጽፏል። ይህ መለኮታዊ ምክር ( the devine council) እግዚአብሔር ስለሚያደርገው እና ስለፍርዱ ከተመረጡ ቅዱሳን ጋር የሚያደርገው ነው። ይህን የሚያደርገውም ከቅዱሳንም መርጦ ላከበራቸው ያለውን ክብር ያሳይ ዘንድ ከሥልጣኑ በጸጋ እያሳተፋቸው እንጂ ከእግዚአብሔር ፍርድ እና ምክር የሚጎድል ኖሮ እነርሱ ሊሞሉለት አይደለም።
የመጀመሪያው ይህን የተመረጡ ቅዱሳን ምክር የሚያሳይ ጥቅስ መዝ. 81/82 ነው፦ “እግዚአብሔር በአማልክት ማኅበር ቆመ፥ በአማልክትም መካከል ይፈርዳል።"
ሌላኛው ደግሞ "እግዚአብሔርን በሰማይ የሚተካከለው ማን ነው? ከአማልክትስ ልጆች እግዚአብሔርን ማን ይመስለዋል? በቅዱሳን ምክር እግዚአብሔር ክቡር ነው፤ በዙሪያው ባሉት ሁሉ ላይ ታላቅና ግሩም ነው፤" የሚለው ነው። (መዝ. 89፥6-7)
***
ቅዱስ ሚካኤል መልአከ ምክሩ የሚባል የመላእክት አለቃ ሆኖ የዚህ መለኮታዊ ምክር አካል ስለሆነ ነው። 'ተሾመ' የሚለው ቃል ይህን መመረጥ ይገልጣል። ከሌሎች መላእክት በተለየ በዙፋን ላይ ተቀምጦ መሳሉም ለዚሁ ነው። ድንግል ማርያምም የዚህ ማኅበር አካል ነች። ቀድሞ የክርስቶስ ምሳሌ የሆነው ሰሎሞን ለእናቱ ያለውን ክብር ይገልጥ በጎኑ ዙፋን አስቀምጦ ያማክራት ነበር። (1ኛ ነገ. 2፥19) ዳዊትም "ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች" ብሎ ተናግሮላታል። (መዝ. 44/45፥9)
ሐዋርያትም እንዲሁ ናቸው፤ ጌታ በ12ቱ የእሥራኤል ነገዶች ላይ ሲፈርዱ በዙፋን እንደሚቀመጡ መናገሩ የመለኮታዊው ምክር አካላት እንዳደረጋቸው ያሳያልና። (ማቴ. 19፥28)
ይህንም ነቢዩ ዳንኤል ቀድሞ ተናግሮታል፦ “ዙፋኖችም እስኪዘረጉ ድረስ አየሁ፥ በዘመናት የሸመገለውም ተቀመጠ፤ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ፥ የራሱም ጠጕር እንደ ጥሩ ጥጥ ነበረ፤ ዙፋኑም የእሳት ነበልባል ነበረ፥ መንኰራኵሮቹም የሚነድድ እሳት ነበሩ።” (ዳን. 7፥9) ነቢዩ 'ዙፋኖች' ያለው እግዚአብሔር ብዙ ዙፋኖች ኑረውት ሳይሆን የተመረጡ ቅዱሳን የሚሳተፉበትን ከእግዚአብሔር ፍርድ ሲወጣ ቀድመው የሚያውቁ እና በባለሟልነት የሚማልዱ የቅዱሳን ጉባኤ ክብራቸውን ለማመልከት ነው።
***
በዚህ ሁሉ ታላቁ መልአክ ሚካኤል አለ! ኦ ሚካኤል ኦ ሚካኤል! ከእግዚአብሔር የተሰጠህ ክብር ታላቅ ነው። ለጎስቋሎች ባሮችህ ለምንልን። አሜን።
#ሳታቋርጡ_ጸልዩ

"ሥራ የሚሠራ ሰው ቀኑን ሙሉ በጸሎት ተጠምዶ መዋል አይችልም" አትበለኝ፤ ይችላል። በጸሎት የሚያስፈልገው ድምፅ ሳይሆን ሀሳብ ነው ፤ እጅ ሳይሆን እደ ልቦናን ማንሣት  ነው፤   አፍአዊ ሳይሆን ውስጣዊ አኳኋን ነው ።ይህን ለማድረግ ደግሞ ቦታም ጊዜም አይገድብህም። በጉልበትህ ባትንበረከክ፤ ደረትህንም ባትደቃ እንኳ መንፈስህ ትጉ ከሆነ ጸሎትህ ሥልጡን ነው ።

    #ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
"ይፈኑ ለክሙ ጰራቅሊጦስሃ፤ አጽናኝ መንፈስ ይልክላችኋል" (ዮሐ.፲፬፥፲፮)

እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሳችሁ!

የቤዛነት ሥራውን ከፈጸመ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ሲያርግ ለሐዋርያት የሰጣቸው ተስፋ አጽናኝና የእውነት መንፈስ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን አብ እንደሚልክላቸው፣ እርሱም አጽናኝ የሆነ ጰራቅሊጦስ እንደሆነ ለዘለዓለሙም ከእነርሱ ጋር እንደሚሆን ነግሯቸው ነበር፡፡ ጌታችን እንደተናገረውም በሰጣቸው ተስፋ መሠረት ባረገ በዐሥረኛው ቀን በተነሣ ደግሞ በሃምሳኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡ ‹‹ወአነ እስእሎ ለአብ ይፈኑ ለክሙ ጰራቅሊጦስሃ፤ ካልአ ዘይሄሉ ምስሌክሙ ለዓለም፤ እኔም አብን እለምነዋለሁ፤ እርሱም ለዘለዓለም ከእናንተ ጋር ይኖር ዘንድ ሌላ አጽናኝ መንፈስ ይልክላችኋል›› እንዲል፡፡ (ዮሐ.፲፬፥፲፮)

ይህንንም መንፈስ ቅዱስ የወረደበትን ቀን በዓለ ጰራቅሊጦስ እያልን እናከብረዋለን፤ ከጌታ ዐበይት በዓላትም አንዱ ነው፡፡ጰራቅሊጦስ ማለት መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ወይም ለመንፈስ ቅዱስ የሚሰጥ ሌላኛው ስሙ እንደሆነ ከርእሳችን እንረዳለን፡፡‹‹ጰራቅሊጦስ መንፈሰ አብ ወወልድ ስቡሕ፤ ጰራቅሊጦስ የተመሰገነ የአብና የወልድ መንፈስ ነው›› በማለት አምላክነቱን በአንድነት በሦስትነት ጸንቶ የሚኖር እውነተኛ አምላክ፣ ከአብ የሠረጸ የእውነት መንፈስ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ (ሰይፈ ሥላሴ ዘሐሙስ)

ጰራቅሊጦስ ማለት ‹‹መንፈስ ቅዱስ፣ አጽናኝ፣ አስታራቂ፣ አሳምሮ የሚያናግር ማለት ነው›› ይላል፡፡ (ሕያው ልሳን) አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ‹‹ጰራቅሊጦስ›› ማለት ‹‹ናዛዚ፣ መጽንዒ፣ መስተፍስሒ፣ መንፈስ ቅዱስ፣ በዓለ ሃምሳ፣ የትንሣኤ ሃምሳኛ፣ የዕርገት ዐሥረኛ፣ እሑድ ቀን የሚውል ወዘተ…›› እያሉ ይተረጉሙታል፡፡ (ገጽ ፱፻፯)

በጥቅሉ ጰራቅሊጦስ ማለት መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ያዘኑትን የሚያጽናና፣ የራቁትን የሚያቀርብ፣ የተሰወረውን የሚገልጥ፣ የረቀቀውን የሚያጎላ፣ የተከፉትን የሚያስደስት፣ ለመምህራን አንደበት የሆነ መጽንዒ፣ የሚያጸና፣ መንጽሒ የሚያነጻ ኃጢአትን ይቅር የሚል የሚደመስስ የእውነት መንፈስ፣ የእውነት አምላክ ነው፡፡ ጌታችን እርሱን እስኪልክላቸው ኃይልን ብርታትን እስኪላበሱ አላዋቂዎችን አዋቂ የሚያደርግ ከሣቴ ምሥጢር፣ ፈሪዎችን ደፋር (ጥቡዓን) የሚያድርጋቸው፣ በአሕዛብ በዓላውያን ፊት ያለ ኀፍረት፣ ያለ ፍርሃት እንዲመሰክሩ፣ በእሳቱ፣ በስለቱ እንዳይሸማቀቁ የሚያደርጋቸውን የእውነት መንፈስ እንደሚልክላቸውና እርሱም ለዘለዓለሙ አብሯቸው እንደሚኖር ተስፋ ሰጥቷቸው ነበር፡፡

እንዲህም ብሏቸዋልና፤ ‹‹ዘኢይክል ዓለም ነሢኦቶ፤ ዓለም እኔን ለሕማም ለሞት አሳልፎ እንዲሰጠኝ ለሕማም ለሞት አሳልፎ ሊሰጠው የማይቻለው፤ እስመ ኢይሬእዮ ወኢየአምሮ፤ አያየውም፤ አያውቀውምና፤ ወአንትሙሰ ተአምርዎ፤ እናንተ ግን ታውቁታላችሁ፤ አድሮባችሁ ይኖራልና በውስጣችሁም ይኖራልና፡፡›› አድሮባቸው የሚኖረውን፣ ሕማመ ሥጋ፣ ድካመ ሥጋን የሚያርቅላቸውን፣ የምሥራቹን ለዓለም ሁሉ የሚያደርሱበትን ኃይል ጸወን የሚሆናቸውን እውነተኛ የሆነ የራሱንና የአባቱን መንፈስ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በሃምሳኛው ቀን፣ ባረገ በዐሥረኛው ቀን በዕለተ እሑድ ጰራቅሊጦስ የተባለውን የእውነት መንፈስ ላከላቸው፡፡ እርሱ የእውነት መንፈስ ነው አለ፤ የሐሰት መንፈስ አለና ሲለይ ነው፡፡

መንፈስ ቅዱስ በ፻፳ው ቤተ ሰብ ላይ እንደወረደ፡- ‹‹እንዘ ሀለዉ ኩሎሙ ኅቡረ አሀተኔ መጽአ ግብተ እምሰማይ ድምፅ ከመ ድምፀ ነፋሰ ዓውሎ፤በአንድነት ተሰብስበው ሳሉ ከወደ ሰማይ እንደ ዓውሎ ነፋስ ድምፅ ያለ ድምፅ ነጉዶ ተሰማ …›› (የሐዋ.ሥራ ፪፥፪) ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት፣ ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስትና ሰባ ሁለቱ አርድእት መቶ ሃያው ቤተ ሰብ በኅብረት በኢየሩሳሌም ይኖሩ ነበር፡፡

ምክንያቱም ከላይ እንዳየነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹አንትሙሰ ንበሩ ሀገረ ኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እምአርያም፤ እናንተ ግን ከሰማይ ኃይል እስክትለብሱ ማለትም ሰማያዊ ሀብትን፣ ሰማያዊ ዕውቀትን፣ ሰማያዊ ኃይልን እስክትለብሱ በኢየሩሳሌም ቆዩ›› ብሏቸው ነበርና በኅብረት ይኖሩና፣ በኅብረት ይጸልዩ፣ የተስፋውንም ቃል ይጠብቁ ነበርና ድንገት በተሰበሰቡበት እንደ ዓውሎ ነፋስ ያለ ታላቅ ድምፅ አሰምቶ የተቀመጡበትን ቤት ሞላው፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፪)

ላንቃ ላንቃ ያለው እሳት መስሎም ታያቸው፤ በሁላቸውም ላይ መንፈስ ቅዱስ አደረባቸው፡፡ በዚህም ኃይል የሚሆናቸውን፣ ሀብት የሚሆናቸው ዕውቀትን ገንዘብ አደረጉ፡፡ ሁሉም በየራስ በየራሳቸው ሰባ ሁለት ቋንቋ መናገር ጀመሩ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያትና በሌሎቹ ላይ እንደ ነፋሰ ዓውሎ ሆኖ ነው የወረደው፡፡ ምክንያቱም ነፋስ ረቂቅ ነው፤ መንፈስ ቅዱስም ረቂቂ ነውና፤ ነፋስ ኃያል ነው፤ ፍሬውን ከገለባው ይለያል፤ መንፈስ ቅዱስም ጻድቃንን ከኃጥአን ይለያልና፡፡ ነፋስ በምልዓት ሳለ አይታይም፤ አይታወቅም፤ ነገር ግን የሚታወቀው ባሕር ሲያናውጥ፣ ዛፍ ሰያወዛወዝ፣ ቅጠሉን ሲያረግፈው፣ አቧራውን ሲያስነሣው በሥራው ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስም በምልአት ሳለ አይታወቅም፤ ነገር ግን ቋንቋ ሲያናግር፣ ምሥጢር ሲያስተረጉም ይታያልና፡፡ ነፋስ መዓዛ ያመጣል፤ መንፈስ ቅዱስም መዓዛ ጸጋን ያመጣልና በነፋስ ተመስሎ ወርዷል፡፡

ሰባ ሁለት ቋንቋ ሲናገሩም ከልዩ ልዩ ቦታ የተሰበሰቡና ልዩ ልዩ ቋንቋ የሚናገሩ አይሁድ በዚያ (በኢየሩሳሌም) ነበሩና አደነቁ፤አንዳንዶቹ እንዲያውም ግራ ተጋብተው ‹‹እነዚህ ሰዎች ሁላቸውም የገሊላ ሰዎች አይደሉምን? በየሀገራችን ቋንቋ ሲናገሩ እንደምን እንሰማቸዋለን›› እያሉ ያደንቁ ነበር፤ አንዳንዶቹ ግን ይስቁባቸው ነበር፡፡ምክንያቱም ከከተማ የመጡ እኩያን አይሁድ ሰቃልያነ አምላክ ናቸውና የመንፈስ ቅዱስን ሥራ ላለማድነቅ በሐዋርያት ላይ ሳቁባቸው፤ ‹‹እሊህ ያልፈላ ጉሽ ጠጅ ጠጥተው የሆነ ያልሆነውን ይቀባጥራሉ›› ብለው ተሳለቁ፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፭-፲፫)

እንደ እውነቱ ከሆነ ያልፈላ ጉሽ የወይን ጠጅ የጠጣ፣ ጠጥቶም የሰከረ ሰው፣ እንኳን የማያውቀውን ቋንቋ ሊናገር ቀርቶ የሚያውቀውንም በተናገረው አይናገረም፤ ስካር አንደበትን ያስራል፤ ትንፋሽን ያሳጥራል እንጂ አዲስ ቋንቋ፣ ሁላቸውም የሚሰሙት የሀገራቸውን ቋንቋ ሊናገሩ አይችሉም ነበር፡፡ አይሁድ ግን ክፉዎች ነበሩና እውነቱን መቀበል አይሹም፡፡ የዘመናችን መናፍቃንም ወንጌል ተከድኖባቸው፣ እውነቱ ተሸፍኖባቸው፣ በዕውቀት የተራቀቁትን፣ መንፈስ ቅዱስ ተመልተው ምሥጢር የሚያመሠጥሩትን፣ ክብሩን የሚገልጡትን በመንፈስ ቅዱስ የሚመሩ መምህራንን፣ ሊቃውንትን እንደሚያቃልሉትና እንደሚያሾፉ ዓይነት ማለት ነው፡፡

ግን ጊዜው የስካር አይደለም፤ ምክንያቱ ገና ንጋት (ነግህ) ነውና፤ ነቢዩ ኢዩኤል የተናገረው ቢፈጸም ነው እንጂ፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ መንፈሴን አሳድርበታለሁ›› ያለው ጌታ አስቀድሞ በነቢዩ የተናገረው ትንቢት መፈጸሙ የእግዚአብሔር መንፈስ በእነርሱ ላይ ስለ መውረዱ አዲስ ዕውቀትን እንደገለጠላቸው ነገራቸው፤ ገሠጻቸው፤ ስለ ጌታችን ወደዚህ ዓለም መምጣት፣ አይሁድ ግን በክፋት እንደሰቀሉት፣ እርሱ ግን በሥጋ ሞቶ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ስለ መነሣቱና ስለማረጉ ለዚህም ምስክሮቹ መሆናቸውን ጭምር ሰበከ፡፡
በዚህ ስብከት ልባቸው ተነካ፤ ጴጥሮስንና ሌሎእንም ‹‹ምን እናድርግ›› አሏቸው፡፡ ጴጥሮስም ‹‹ንስሐ ግቡ፤ ኃጢአታችሁም ይሰረይላችሁ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ›› አላቸው፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፭-፴፰) ቋንቋ የሚያናግረውን፣ በጥበብና በዕውቀት የሚሞላውን፣ በሀብቱ ስቦ በረድኤት አቅርቦ ሀብተ መንፈስ ቅዱስን የሚያሰጥ የኃጢአት ስርየትም የሚገኝበትን በክርስቶስ አምኖ በመጠመቅ የሚገኘውን የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ እንዲቀበሉ መከራቸው፡፡ ቃሉንም የሰሙ፣ ሰምተውም ያመኑ ብዙ ነፍሳት ተጠመቁ፤ ቁጥራቸውም ሦስት ሺህ ያህል ነበሩ፡፡

እናም በዓለ ጰራቅሊጦስ እያልን ከዕርገት በዐሥረኛው ቀን፣ ከትንሣኤው በሃምሳኛው ቀን የምናከብረው ታላቅ በዓል መሠረቱ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ከሰማያት የወረደበት፣ ለጌታ ቤተ ሰቦች የተገለጠበትና በእያንዳንዳቸው ላይ ያደረበት፣ በዚህም ሕይወት የሚሰጠውን አምላካዊ ዕውቀት ያገኙበት፣ ዓለምን ተዘዋውረው ያስተምሩበትና ተአምራት መንክራት ያድርጉ ዘንድ ሕዝቡንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚጠሩበትን የዓለም ቋንቋ የገለጠበት፣ በዚህም የመንፈስ ቅዱስን ድንቅ ሥራ የተመለከቱ፣ በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት ልባቸው የተነካ ብዙዎች በክርስቶስ ኢየሱስ አምነው የተጠመቁበትና ወደ በረቱ የተሰበሰቡበት ድንቅ የተአምራትና የምሥጢር ቀን በመሆኑ እንድናከብረው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡

መጽሐፈ ፍትሐ ነገሥት ‹‹በበዓለ ሃምሳ ሥራ አትሥሩ፤ ነገረ ክርስቶስን ባመኑ ምእመናን ላይ የወረደ መንፈስ ቅዱስ ተገልጦበታልና›› ይላል፡፡ (ፍት.ነገ.አን.፲፱፥፯፻፵) እናም እኛ ክርስቲያኖች ይህንን ታላቅ የበረከት በዓል፣ ይህንን የተቀደሰ ቀን ስናከብረው እንዴት ይሆን? በወይን ጠጅ ሰክረን ወይስ ኃጢአታችን ይሰረይልን ዘንድ ንስሓ ገብተን ወይስ በሌላ ሁኔታ? ጰራቅሊጦስ ነፍስና ሥጋን የሚያጸና፣ ለንጹሐን የክብር አክሊልና ሞገስ ነው፤ ይህን የእውነት መንፈስ በእኛ ላይ ያድር ዘንድ፣ ስብራታችን እንዲጠገን፣ ጎደሏችን እንዲሞላ፣ ድንቁርናችንን እንዲያስወግድ፣ ከኀዘናችን እንዲያጽናናን፣ እንለምነዋለን ወይስ በምግበ ሥጋ ተጠምደን ጨለማውን የማያርቀውን ዕውቀት የማይገልጸውን፣ ኀዘንና ትካዜ የሚጨምረውን የበዓል አከባበር እናከብራለን?

ራሳችንን እንድናይ፣ ንስሐን የሚቀበል፣ ኃጢአትንም ይቅር የሚል፣ የሚያነጻ መንፈስ (ጰራቅሊጦስ) በእውነት ይርዳን! ተቀድቶ የማያልቅ የዕውቀት መጠጥ ነው፤ ምሥጢር ገላጭ በመሁኑ ምሥጢሩን እንዲገልጽልን በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደ መንፈስ ቅዱስ በእኛም ላይ ያድር ዘንድ አእምሮውን፣ ማስተዋሉን እንዲሰጠን መልካም ፈቃዱ ይሁን፤ አሜን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
‹‹በዚያን ጊዜ ይጾማሉ›› (ማቴ.፱፥፲፮)

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና መሠረት በዓለ ጰራቅሊጦስ በዋለ ማግስት ጀምሮ የሚጾመው ጾም ጾመ ሐዋርያት ተብሎ ይጠራል። የዚህ ጾም የመግቢያው ቀን በየዓመቱ የሚለያይ ሲሆን “ቢፈጥን ከግንቦት ፲፮ አይቀድምም፤ ቢዘገይ ደግሞ ከሰኔ ፳ አያልፍም” ብለው ሊቃውንት አባቶቻችን ያስተምራሉ። ይህ ጾም የሚፈታበት ቀን ግን እንደ መግቢያው የማይቀያየር ሲሆን ሁልጊዜ ሐምሌ አምስት በቅዱሳን ጴጥሮስ እና ቅዱስ ጳውሎስ የሰማዕትነት መታሰቢያ በዓል ቀን ጾሙ ይጠናቀቃል።

በዚህ ጾም የሐዋርያት ክብራቸው፣ ቅድስናቸው እንዲሁም አገልግሎታቸው ይታሰባል፡፡ ሁሉን ትተው ጌታን መከተላቸው፣ ዓለምን ዞረው ማስተማራቸውና ስለ ቅዱስ ስሙ በጽናትና በጥብዐት መከራ መቀበላቸው ይታወሳል፡፡ ስለ ተሰጣቸው የወንጌል አደራ እስከ ሞት ድረስ መታመናቸው ይሰበካል።

ቅዱሳን ሐዋርያት ይህን ጾም ሁለት ነገሮችን መሠረት በማድረግ ጾመውታል። የመጀመሪያው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወላቸውን ጾምን የአገልግሎት መጀመሪያ የማድረግ አርአያነት ነው። ይኸውም ክብር ይግባውና አምላካችን ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ አብ በሰማይ ተናግሮ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ ክብሩ፣ አምላክነቱ የባሕርይ ልጅነቱ የተገለጠ ሲሆን ከተጠመቀ በኋላ አገልግሎቱን ከመጀመሩ በፊት ሳይውል ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ በመሄድ ፵ ቀን እና ፵ ሌሊት ጾሟል። (ማቴ.፫ እና ፬) ቅዱሳን ሐዋርያትም ይህን ጌታችን ያደረገውን ተግባር አርአያ በማድረግ በበዓለ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ወርዶ፣ ኃይልን ተቀብለው የጸጋ ልጅነታቸው ሲገለጥ ለአገልግሎት ከኢየሩሳሌም ከመውጣታቸው በፊት ጾምን የአገልግሎታቸው መጀመሪያ በማድረግ ጾመዋል። ይህም አርአያነት ቀጥሎ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እና በርናባስ ለስብከት አገልግሎት በተለዩ/በተመረጡ ጊዜም ጾመዋል። (ሐዋ.፲፫፥፪-፫) ስለዚህ ጾምን የአገልግሎት መጀመሪያ ማድረግ የመጀመሪያው መሠረት ነው።

ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀራጭ በነበረው በማቴዎስ ቤት ተቀምጦ ሳለ የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ‹‹እኛና ፈሪሳውያን ብዙ ጊዜ የምንጦመው ደቀ መዛሙርትህ ግን የማይጦሙት ስለ ምንድን ነው?›› ብለው ለጠየቁት ጥያቄ የሰጠው ምላሽ ነው። ይኽውም ‹‹ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉን? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወስድበት ወራት ይመጣል፤ በዚያን ጊዜም ይጾማሉ›› ብሎ የመለሰው መልስ በሐዋርያት በተግባር መፈጸሙን እንድረዳ ነው። ይህም ቃል ይፈጸም ዘንድ ሚዜዎች የተባሉ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙሽራው ክርስቶስ ከእነርሱ በተለየ/ባረገ ጊዜ መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ጾመውታል።(ማቴ.፱፥፲፴-፲፮)

ዛሬ ደግሞ እኛ ክርስቲያኖች ከቅዱሳን ሐዋርያት በረከት እንሳተፍ ዘንድ ይህን ቅዱስ ጾም እንጾማለን። እነርሱ ጾመው በጀመሩት አገልግሎት ዓለምን በስብከተ ወንጌል ጨው ሆነው እንዳጣፈጡ በክህነት የሚያገልግሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችም እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክላቸው፣ ይቀበልላቸው፣ ያሳካላቸው ዘንድ በትጋት ሆነው ይጾሙታል። ይህ ሲባል ግን ምንም እንኳን ይህን ትልቅ በረከት የሚያሰጥ ጾም ‹‹የቄስ ጾም›› እያሉ ራሳቸውን የሚያስቱ ቢኖሩም ቤተ ክርስቲያናችን ግን በቀኖና ወስና የዐዋጅ ጾም ብላዋለችና ሁላችንም ክርስቲያኖች ከሰባት ዓመት ጀምሮ ልንጾመው ይገባል። (ፍት.ነገ.፲፭፣ገጽ.፭፻፷፮)

በዚህ ጾም ቅዱሳን ሐዋርያት ራሳቸውን ለአገልግሎት እንዳዘጋጁ፣ እንደጸለዩ እና አገልግሎታቸውንም እንደፈጸሙ እኛም በቀጣይ ልንጀምረው ያሰብነው በልቦናችን ያለው መልካም አሳብ ይፈጸም ዘንድ እግዚአብሔርን እየለመንን እንጾመዋለን። የእነርሱን አገልግሎት የባረከ አምላክ የእኛንም አገልግሎታችንን፣ ሥራችንን፣ ትምህርታችንን፣ ትዳራችንን በአጠቃላይ ሕይወታችንን እንዲባርክልን እየተማጸንን እንጾመዋለን።

የቅዱሳን ሐዋርያት ረድኤት፣ በረከት፣ ድል የምትነሣ፣ ጥርጥር ነቅዕ የሌለባት ሃይማኖታቸው ከሁላችን ጋር ትሁን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

Mahebere kidusan
ወላዲተ_አምላክ_በዲያቆን_ያረጋል_አበጋዝ.pdf
352.7 KB
ወላዲተ አምላክ

*እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም "ወላዲተ አምላክ" ትባላለችን? ለምን?

* "ወላዲተ አምላክ" የቃሉ ትርጉም

* የቃሉ ነገረ መለኮታዊ ፋይዳ

* የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክነት በመጽሀፍ ቅዱስ ትምህርት

* የእመቤታችን ወላዲተ አምላክነት-በቀደምት አበው ትምህርት

+++++++++~~~+++++++

ቅዱስ ቄርሎስ ንስጥሮስ “ወላዲተ አምላክ” የሚለውን መቃወሙ በነገረ ክርስቶስና በነገረ ድኅነት ላይ የሚያስከትለው ነገር መሠረታዊ የሆነ ኑፋቄ መሆኑን በሚገባ አስረድቷል፡፡ እነዚህን ነገሮችም እንደሚከተለው በሚገባ ለይቶ አውጥቷቸዋል፡-

ከድንግል ማርያም የተወለደው አካላዊ ቃል የእኛን ባሕርይ ነሥቶ (ተዋሕዶ) ሥግው ቃል ካልሆነና ሰው ብቻ (ዕሩቅ ብእሲ) ከሆነ መዳናችን አደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስ የተቀበላቸው ሕማማትና መከራዎች የሥግው ቃል (ሥጋን የተዋሐደውና የእኛን ባሕርይ ባሕርዩ አድርጎ ሰው ሆኖ በሥጋ የተገለጠው አካላዊ የእግዚአብሔር ቃል) ሕማማትና መከራዎች ሳይሆኑ የዕሩቅ ብእሲ (የስው ብቻ) ይሆናሉና፡፡ ፍጡር በሆነ በሰው ብቻ መዳን አይቻልምና ስለዚህ ድነናል ማለት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ወላዲተ አምላክ የሚለውን ቃል መካድ የአምላክን ሰው የመሆን ምሥጢር (ምሥጢረ ሥጋዌን) እና የሰውን መዳን መካድ ነው፡፡

እንደዚሁም አካላዊ ቃል አዲሱን ሰው ዳግማዊ አዳምን ለመፍጠር አካላዊ ቃል ከእኛ ባሕርይ ጋር ሊያደርግ የሚያስፈልገው ተዋሕዶ፡ ንስጥሮስ እንዳለው ዓይነት አፍኣዊና የጉርብትና ዓይነት ዝምድና ሳይሆን፣ ውሳጣዊና ባሕርያዊ የሆነ ጥብቅ እና አማናዊ የሆነ ተዋሕዶ ያስፈልገው ነበር፡፡ ይህ አይደለም ከተባለ የባሕርያችን መታደስ፡ በሐዲስ ተፈጥሮ የመዳናችን ነገር ሁሉ ከንቱ ይሆናል፡፡

#መድሎተ_ጽድቅ

#ዲያቆን_ያረጋል_አበጋዝ
“If your marriage is like this, your perfection will rival the holiest of monks.” ✝️ St John Chrysostom

St John’s advice to husbands :

+ Never speak to your wife in a mundane way but with compliments, with respect and with much love.
+ Tell her that you love her more than your own life, because this present life is nothing, and that your only hope is that the two of you pass through this life in such a way that in the world to come, you will be united in perfect love.
+ Say to her, ‘Our time here is brief and fleeting, but if we are pleasing to God, we can exchange this life for the Kingdom to come. Then we will be perfectly one both with Christ and with each other, and our pleasure will know no bounds. I value your love above all things, and nothing would be so bitter or painful to me as our being at odds with each other. Even if I lose everything, any affliction is tolerable if you will be true to me.’
+ Show her that you value her company, and prefer being at home to being out at the marketplace
+ Esteem her in the presence of your friends and children
+ Praise and show admiration for her good acts; and if she ever does anything foolish, advise her patiently.
+ Pray together at home and go to Church; when you come back home, let each ask the other the meaning of the readings and the prayers.
«ወንድምህን አትናቀው»

ወዳጄ ሆይ! ክርስቲያን ነህን? እንኪያስ በፍጹም ወንድምህን አትናቀው። እህትህን አትናቃት። ምንም ይሁን ምን ሰው አትናቅ። ይህ የምትንቀው ወንድም በተለይ ክርስቲያን ከሆነ ክርስቶስን እየሰደብከዉ እንደሆን አስተውል። "እንዴት?"  ያልከኝ እንደሆንም ይህ የምትንቀው ወንድምህ የክርስቶስ ሕዋስ (ብልት) ኾኗል። የክርስቶስ ሕዋስ ከኾነ ደግሞ እሱን ናቅኸው ማለት ክርቶስን ናቅኸው ማለት ነው። ወንድምህን የምትንቅ ከሆነም በጲላጦስ አደባባይ ጌታን ከገረፉት፣ እራቁቱን ከሰቀሉት፣ ሐሞትንና ከርቤን ቀላቅለው ከሰጡት፣ በፊቱ ላይም ከተፉበት ሰዎች በምንም አትተናነስም። ስለዘህ ወንድምህን ከመናቅ ተጠንቀቅ።

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
ቅዱስ ጳውሎስን በትክክል ስለመረዳት
***
ሐዋርያው በገላትያ እና ሮሜ መልእክቶቹ ስለ 'ኦሪት ሕግ' የተናገራቸው ጉዳዮች አሉ። አነዚህን ነገሮች በትክክል ለመረዳት ሐዋርያው ከማን ጋር እየተነጋገረ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል። ጉዳዩ ከአይሁድ ዘመም ክርስቲያኖች ጋር ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ሕጉ የተሰጠበትን ዓላማ በሚገባ አና በጥልቀት ካልተረዱ ሰዎች ጋር ነው ጉዳዩ። የመጀመሪያው ያልተረዱት ጉዳይ ሕግ እስራኤልን ከሌሎች አሕዛብ ለመለየት የተሰጠው ተግባር ማብቃቱን እና አሕዛብም በአብርሃም በኩል የተገባላቸው ኪዳን መድረሱን ባለመረዳት በክርስቶስ አንድ ሆነው ሲያበቁ ከአይሁድ የመጡት ከአሕዛብ ከመጡት ለመለየት ሕጉን መጠቀም መፈለጋቸው ነው። ያ ተፈጽሞአል። ክርስቶስ እስራኤልን ከአሕዛብ የሚለየው ሕግ ፍጻሜ ነው፤ ለሁሉም መጥቶአልና። ሁለተኛው ደግሞ ሕግ ያለ ክርስቶስ ማዳን እና ጸጋ ብቻውን ሊያድን እንደማይችል በመዘንጋታቸው እና ከክርስቶስ ማዳን ጋር ማፎካከራቸው ነው። ሕግ ኃጢኣትን በመግለጥ እና መርገምን በማምጣት ለሞት አሳልፎ ይሰጣል። ይህ የሆነው ሕጉ መጥፎ ሆኖ ሳይሆን የሰው ልጅ የነበረበት የድካም ሁኔታ ያደረገው ነው። በክርስቶስ ማዳን መንፈሳዊ ጸጋ ሲሰጥ ግን ሕጉ የባርነት መሆኑ ቀርቶ 'የሕይወት እና የእምነት ሕግ' ሆነ። በቀድሞ ሁኔታው 'የሞት ሕግ' ያለውን በአዲሱ ሁኔታ 'የክርስቶስ ሕግ' እያለ መጥራት ጀመረ። በመሆኑም ሕጉ በክርስቶስ አዲስ ኃይል እና ተግባር እንዳገኘ ተናገረ። ሕጉ አሁንም እንደሚጠቅም ግን ደጋግሞ ተናግሮአል። "ኃጢኣት በሕግ ይታወቃልና" በማለት ሰዎች ኃጢኣት የሆነውን ለይተን እናውቅ ዘንድ ሕጉ የግድ እንደሚያስፈልገን ተናግሮአል። (ሮሜ. 3፥20) በመሆኑም የቅዱስ ጳውሎስ ችግር 'ቅዱስ፣ ጻድቅ እና በጎ' ብሎ ከጠራ ከሕግ ጋር ሳይሆን ሕጉን በተሳሳተ እና ግልብ በሆነ መንገድ ከተረዱ ሐሰተኛ ወንድሞች ጋር ነበር። (ሮሜ. 7፥12)
የሚያሳዘው ግን የ15ኛው መ/ክ/ዘመን የተሐድሶ አራማጆችም በዚሁ መሰናክል መውደቃቸው ነው። ቅዱስ ጳውሎስን ከትክክለኛው መልእክታቱን በጻፈበት ዘመን ከነበረው ነባራዊ ዓውድ አንጻር ሳይሆን በመካከለኛቹ ዘመናት በሮም ቤተ ክርስቲያን የነበረው ቀውስ በፈጠረው ሌላ ዓውድ ለመረዳት የመሞከር ስህተት ፈጽመዋልና።
Dn. Bereket Azmeraw
እጅህ ላይ ባለው ነገር ከታመንህ እግዚአብሔር አምላክ በእጁ ውስጥ ያለውን ነገር ይሰጥሃል።

በውስጥህ ያለውን አቅም መጠቅም ከቻልህ እግዚአብሔር የአንተ ያልሆነ ተጨማሪ አቅም ይሰጥሃል።

ከእግረኞች ጋር ሳትደክም እኩል መራመድና መቅደም ከቻልህ እግዚአብሔር ፈረስን ለውድድር ይሰጥሃል። ኤር. 12፥5

የሚታዩ ኃጢአቶችን ለመዋጋት ታምነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር የተሸሸጉና የማይታዩ ኃጢአቶችን ድል እንድትነሣ ይሾምሃል።

በሕፃንነትህ በልጅነትህ ለእግዚአብሔር የታመንህ ሆነህ ከተገኘህ እርሱ በወጣትነትህ በምታደርገው ውጊያ ውስጥ ታማኝነትን ያድልሃል።

በሲና ምድረ በዳ ለመቀመጥ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር አምላክ የተስፋይቱን ምድር ከንዓንን ያወርስሃል።

በዚህ በተወሰነና አጭር ሕይወት ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር መጨረሻ የሌለውን ዘላለማዊ ሕይወት ያድልሃል።

ትልቁ ቁም ነገር በእጅህ ውስጥ የገባው ነገር ትንሽም ይሁን ጥቂት በእርሱ መታመን መቻልህ ነው። ስለሆነም ባለህ አንድ መክሊት ታምነህ ስትገኝ እግዚአብሔር አምስት መክሊቶችን በአደራ ይሰጥሃል።

አንተ በሚታዩት ነገሮች ላይ ታማኝ ሆነህ ስትገኝ እርሱ በማይታዩት ነገሮች ላይ ይሾምሃል።በመሆኑም ዓይን ያላየችውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልብ ያልታሰበውን መንግሥቱን ያወርስሃል። 1ኛ ቆሮ 2፥9

(#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ)
“ተጋድሏችን ለእውነት እንጂ ለቃላት አይደለም!”
ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ

ሰው ሐሳቡን የሚገልጸው በቃላት አማካኝነት መሆኑ የታወቀ ነው። ሆኖም ሰው የሚረዳውን ሁሉ አከናውኖ ለመግለጽ ግን ቃላት ብቻቸውን ብቁዎች አለመሆናቸው ግልጽ ነው። አዳዲስ ቃላትን በመፍጠርና ዐረፍተ ነገሮችን በመደርደር ለማስረዳት የሚደክመው ከዚህ የተነሣ ነው። ሰው በሰውነቱ የሚያስባቸውን ሐሳቦች ለመግለጽ እንኳ ቀላል ካልሆነ፣ አምላካዊ የሆኑ ነገሮችን ለመግለጽማ የሰው ልጅ ቋንቋና ገለጻ ምን ያህል ደካማ ይሆን? ነገረ ሃይማኖት ከቃላትና አገላለጾች በእጅጉ ያለፈ ነውና።
ኦርቶዶክሳዊ የነገረ ሃይማኖት አረዳድ ከቃላዊነትና ሐተታዊነት ይልቅ ወደ ተመስጧዊነትና አንክሮታዊነት የሚያደላውም ለዚህ ነው። ይህም አሉታዊ አረዳድ (Apophatism - አፖፋቲዝም) የሚባለው ነው። አንድ ሰው ነገረ እግዚአብሔርን የሚማረው ለድኅነት የሚጠቅመውን ያህል እንዲያውቅ፣ ብሎም አላዋቂነቱን ለማወቅ እንዲረዳው እንጂ እግዚአብሔርንና አሠራሩን በተመለከተ ሁሉን አውቃለሁ እንዲልና በዚህ ዐለም እንዳሉ የእውቀት ዘርፎች ዓይነት ራሱን እንደ ባለሞያ እንዲቆጥር አይደለም።

ቃላትን የምንፈጥራቸው እኛው ሰዎች ነን። አንድን ሐሳብ ለመግለጽ ወይም ለመወከል ስንል ወይ አዳዲስ ቃላትን እንፈጥራለን፣ አለዚያ ደግሞ የነበረን ቃል አዲስ ወይም የዳበረ ሐሳብ እንዲወክል እናደርገዋለን። በነገረ-ሃይማኖትም አምላካዊ ትምህርቶችን ለመግለጽ የተሄደበት መንገድ እንደዚሁ ያለ ነው። ጥልቅ የሆኑ አምላካዊ ጸጋዎችንና እውነቶችን ለመግለጽ ያስችላቸው ዘንድ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ወይ ነባር ቃላትን አዳዲስ ጽንሰ-ሐሳብ እንዲወክሉ ያደርጓቸዋል፣ አለዚያ ደግሞ እነዚያን ሐሳቦች የሚሸከሙ ቃላትን ለመፈለግና ለመፍጠር ጥረት ያደርጋሉ።

በዚህ ሂደት ውስጥ ታሳቢ ሊደረግ የሚገባው አንዱ መሠረታዊ ጉዳይ፣ ቃላት የሚወክሉት ሐሳብ እንደየ አረዳዱ የተለያየ ሊሆን የሚችል የመሆኑ ነገር ነው። በሆነ ወቅት ላይ ጤናማ ያልሆነ አስተምህሮን ለመግለጽ ጥቅም ላይ ውለው የነበሩ ቃላት በሌላ ወቅት ደግሞ ጤናማ የሆነ አስተምህሮን ለመግለጽ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ። ለዚህ ጉዳይ ሁነኛ ማሳያ የሚሆነው “homoousion - ሆሞዑሲዮን - ዋሕደ-ባሕርይ ምስለ አብ” የሚለው ቃል ነው።
Homos - አንድ ዓይነት ፤ ousia - ባሕርይ ማለት ነው። ይህ ቃል በ325 ዓ.ም. በኒቂያ በተካሄደው የመጀመሪያው ዐለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ላይ አባቶቻችን የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነትና ከአብ ጋር በባሕርይ አንድ መሆኑን ለመግለጽ የተጠቀሙበት ቁልፍ ቃል ነው። ሆኖም ከኒቂያ ጉባኤ ግማሽ ምዕት ዓመት ያህል ቀደም ብሎ በተካሄደው በአንጾኪያ ጉባኤ (264-272) ላይ ጳውሎስ ሳምሳጢ የተባለው መ*ና*ፍ*ቅ# የተወገዘው ይኸን ቃል በመጠቀሙ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ ጳውሎስ ሳምሳጢ ይህን ቃል (homoousion - ሆሞዑሲዮን) የተጠቀመው የአብን የወልድንና የመንፈስ ቅዱስን አካላዊ ህላዌ የሚክደውን የሰብአልዮስን ክህደት በሚወክል መልኩ ስለነበረ ነው። ቀደም ሲል ጳውሎስ ሳምሳጢ የተሳሳተ አስተምህሮን ለመግለጽ የተጠቀመበትና በአንጾኪያ ጉባኤ የተ#ወገዘበ*ት ይህ ቃል፣ በ325 ዓ.ም. በኒቂያ በተካሄደው ጉባኤ ላይ ግን የኢየሱስ ክርስቶስን ከአብ ጋር በባሕርይ አንድ መሆንና የባሕርይ አምላክነት በሚገልጽ መንገድ ጥቅም ላይ በመዋሉ የኦርቶዶክሳዊነት መለያ ቁልፍ ቃል ሆነ። ከዚያ ወዲህ “homoousion - ሆሞዑሲዮን” የሚለው ቃል የኦርቶዶክሳዊነት አጥርና ቅጥር ሆነ።

ሌላው ልብ ሊባል የሚገባው ጉዳይ ደግሞ ሰዎች የሚያምኑት አስተምህሮ አንድ ዓይነት ሆኖ ሳለ አገላለጻቸው የተለያየ ሊሆን የሚችልበት ዕድል ሊኖር የመቻሉ ነገር ነው። ይህ በአንድ በኩል የቋንቋና የቃላት ውስንነት ውጤት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ አጽንኦት አሰጣጣቸውና አገላለጻቸው ሊለያይ ስለሚችል ነው።

የቋንቋና የቃላት አጠቃቀም፣ አንድ አስተምህሮ (ሃይማኖት) ያላቸውን ወገኖች የተለያየ ነገር የሚያምኑ ሊያስመስል የሚችልበት ሁኔታ አለ። በዐራተኛው መቶ ዓመት ይህ ሁኔታ ተስተውሏል። በግሪኮችና በላቲኖች መካከል ሃይማኖታቸው አንድ ሆኖ ሳለ የግሪክ ነገረ-ሃይማኖታዊ ቃላትን ወደ ላቲን ቋንቋ ሲተረጉሙ ተመጣጣኝ የሆኑ አቻ ቃላትን ካለማግኘታቸው የተነሣ የተጠቀሟቸው የላቲን ቃላት ሃይማኖታቸው ችግር ያለበት መስሎ እንዲታይ ከሚያደርግበት ደረጃ ደርሶ ነበር። ይህን ሁኔታ የፈታው ታላቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ነበር። ቅዱስ ጎርርዮስ ነባቤ መለኮት፣ ስለ ቅዱስ አትናቴዎስ በጻፈው የውዳሴ ድርሰቱ ላይ ይህን ጉዳይና ቅዱስ አትናቴዎስ የፈታበትን መንገድ እንዲህ ገልጾታል፡-

“. . . እስካሁን በተናገርኩት ላይ ይህን ለእኔ በተለየ ሁኔታ አስደናቂ ሆኖ የሚታየኝን ተግባሩን [የቅዱስ አትናቴዎስን] ሳልጠቅስ ባልፍ፣ በተለይም ሰዎች ለመለያየትና ላለመግባባት ዝግጁዎችና ምቹዎች በሆኑበት በእኛ ዘመን፣ ከቅጣት ነጻ የሚያደርገኝ አይመስለኝም። ይህን እርሱ ያደረገውን ነገር ልብ ብለን ካስተዋልነው፣ ለዚህ ዘመን ሰዎችም ጠቃሚ ትምህርት ይሰጣልና። . . . መለያየት ያለው በእኛና በስህተት ውስጥ ባሉት ሰዎች መካከል ብቻ ሳይሆን፣ እጅግ አማኞች በሆኑት ዘንድም ነውና፣ ይኸውም ደግሞ የሚያስከትሉት ነገር በጣም ኢምንት በሆኑ ጥቃቅን አስተምህሯዊ ጉዳዮች (in regard to such doctrines as are of small consequence) እንዲሁም ደግሞ አንድ ዓይነት ትርጉም እንዲኖራቸው ታስበው በሚነገሩ አገላለጾች የተነሣም ነው እንጂ።

“አንድ ባሕርይ እና ሦስት አካላት (one Essence and three Hypostases) ማለትን ኦርቶዶክሳዊ በሆነ መንፈስ እንጠቀማለን፣ ባሕርይ (Essence) የሚለውን የባሕርይ አምላክነትን ለማለት፣ አካላት (Hypostases) የሚለውን ደግሞ የሦስቱን ህልውነትና የየራሳቸውን ገንዘብ ለማመልከት እንጠቀማለን። ሆኖም ጣሊያናውያን ይህንኑ ማለታቸው ቢሆንም ቅሉ፣ ከመዝገበ ቃላታቸው ስስነትና ከቃላት ድህነት የተነሣ፣ በኢሰንስ (Essence) እና በሃይፖስታስስ (Hypostases) መካከል ልዩነት ለማድረግ አልቻሉም። ከዚህ የተነሣም፣ ሰዎች በስህተት ሦስት ባሕርያት (Essences) ብለው የሚያምኑ እንዳይመስላቸው ለማድረግ በሚል ’ፐርሰንስ’ (Persons) የሚል ቃልን ተጠቀሙ። የዚህ ውጤት ግን አሳዛኝም አስቂኝም በሆነ ነበር። ይህ ትንሽ የቃላትና የአገላለጽ ልዩነት የሃይማኖት (አስተምህሮ) ልዩነትን እንደሚያመለክት ተደርጎ ከመወሰድ ደረጃ ላይ ደረሰ።

“ከዚያም ‘ሦስት ፐርሰንስ’ (Three Persons) በሚለው አስተምህሮ በውስጡ ሰብአ*ልዮሳዊነት እንዳለው አስጠረጠረ፣ ‘ሦስት ሃይፖስታስስ’ (Three Hypostases) በሚለው አስተምህሮ ውስጥ ደግሞ አር#ዮሳዊ*ነት*ነት እንዳለበት ይጠረጠር ጀመር፤ ሁለቱም በተረጋጋ መንፈስ አንዱ ሌላውን ለመረዳት ጥረት ከሚያደርግ መንፈስ ሳይሆን ከተከራካሪነትና ራስን ብቻ እውነተኛና ተቆርቋሪ ከማድረግ መንፈስ የተወለዱ ናቸውና። ከዚያም ቀስ በቀስ የሆነ ግን የማያቋርጥ የመነቃቀፍና የቁጣ መንፈስ በመካከላቸው እያደገ በመሄዱ፣ ከቃላትና አገላለጽ ልዩነቶች በተጀመረ አለመግባባት፣ መላው ዐለም በሃይማኖት ወደ መለያየት ሊያመራ ከሚችልበት አደጋ ላይ ደርሶ ነበር።
“ይህን እያየና እየሰማ፣ እውነተኛ የእግዚአብሔር ሰውና ታላቅ የነፍሳት እረኛ እንደ መሆኑ፣ በቃላት ስንጠቃና በአገላለጽ ልዩነት የመጣውን ይህን የመሰለውን አስነዋሪ የመለያየት አደጋ ዝም ብሎ መተው ከተግባሩ አንጻር ተገቢ ሆኖ አላገኘውም። ስለዚህም ለዚህ ደዌ ተገቢ የሆነውን መድኃኒት አደረገለት። በምን ሁኔታ? ቅንና ርኅሩኅ በሆነው መንገዱ ከሁለቱም ወገኖች ጋር ጉዳዩን ተወያየ፣ የሁለቱንም ወገኖች የአገላለጾቻቸውን ይዘትና ትርጉም በጥንቃቄ ከመዘነ በኋላ፣ እና የሁለቱም አገላለጾች አንድ ዓይነት ሐሳብ (መንፈስ) ያላቸው መሆናቸውን ተረዳ፣ በአስተምህሮ ረገድ በምንም ሁኔታ የተለያዩ እንዳልሆኑ ተረዳ። ስለሆነም ሁለቱም ወገኖች ሃይማኖታቸው አንድ በመሆኑ የየራሳቸውን ቃላትና አገላለጾች እንዲጠቀሙ በመፍቀድ፣ በቃላትና በአገላለጾች ልዩነት ብቻ ሊለያዩ የነበሩትን ወገኖች አንድ አድርጎ ጠበቃቸው። ይህ ድርጊቱ ከብዙ ትጋቶቹና ተጋድሎዎቹ፣ ይህ ታላቅ የሃይማኖት ጀግናችን ከተቀበላቸው ብዙ ስደቶቹና መከራዎቹ ሁሉ የበለጠ ዋጋ ያለው ነው፤ . . .” (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት፣ በእንተ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ቁ. 35-36)

ቅዱስ አትናቴዎስ ይህን ያደረገው፣ በ362 ዓ.ም. በእስክንድርያ በእርሱ ሰብሳቢነት በተካሄደ ጉባኤ ነበር።

እንግዲህ ሰዎች ሃይማኖታቸው አንድ ሆኖ ሳለ፣ ግን ጥልቅ የሆነው ነገረ ሃይማኖታዊ ሐሳብ ከቋንቋ ወደ ቋንቋ ሲተረጎም በሚፈጠሩ የቃላትና የአገላለጾች አጥጋቢ አለመሆን የተነሣ ሃይማኖታቸው የተለያየ ሊመስላቸው ይችላል ማለት ነው። በዚህ ላይ ደግሞ በፍቅርና በቅንነት አንዱ ሌላውን ለመረዳት ጥረት በማድረግ ፋንታ ሁሉም የራሱን አረዳድና አገላለጽ ብቻ ኦርቶዶክሳዊ የሌላኛውን ግን ኑ*ፋ*ቄ#ያዊ አድርጎ ለመፈረጅ ከቸኮለ፣ ከዚያ በኋላ መደማመጥና መግባባት ይቀርና መወጋገዝ ብሎም መለያየት ይከተላል። ቃላትና አገላለጾች ላይ ብቻ የተንጠለጠለ ጥራዝ ነጠቅ አካሄድ ቤተ ክርስቲያንን ከባድ ዋጋ ሲያሰከፍላት ኖሯል። ስለሆነም በትክክል የአስተምህሮ ልዩነት (ኑ*ፋ*ቄ#) የሆነውን የቃላትና የአገላለጽ ልዩነት ከሆነው ለይቶ ለመረዳት መረጋጋት፣ ፍቅር፣ ቅንነትና ትሕትና ይፈልጋል።

በዚያውም ላይ ደግሞ የምንጠቅሳቸው ምንጮች ከሌላ ቋንቋ የተተረጎሙ ከሆኑ፣ ጸሐፊዎቹ አባቶች በጻፉበት የመጀመሪያው ቋንቋ ያ ሐሳብ በምን ሁኔታ እንደ ተገለጸ ከምንጩ ወደ ማጣራት መሄድም ሌላው አስፈላጊ ነገር ነው። መተርጉማን የሚተረጉሙት በዚያን ዘመን በነበረው የቋንቋ አረዳድ እንዲሁም ሰው እንደ መሆናቸው በመረዳታቸው ልክ ነውና። ከላይ ለማውሳት እንደ ተሞከረው በሆነ ዘመን ያስወገዘ ቃል በሌላ ጊዜ ደግሞ የኦርቶዶክሳዊነት ቁልፍ ቃል ሊሆን ይችላል። ስለዚህ የሆነን ቃል “አለ/የለም”፣ “ይባላል/አይባልም” ከሚለው ባሻገር፣ ያ ቃል መቼና በማን እንዲሁም ምን ለማለት ጥቅም ላይ እንደ ዋለ መረዳት እጅግ አስፈላጊ ነው። “ነገረ አበው” (ፓትሮሎጂ) የሚባለው ትምህርት ጥቅሙ እዚህ ላይ ነው። የአባቶችን ትምህርት በዝርዝር ወደ መማር ከመግባት በፊት የነገረ-አበውን ትምህርት በአግባቡ መማር ቢቻል ብዙ ችግሮችን ለመፍታት ሰፊ ዕድል ሊሰጥ ይችላል።

በዚህም ላይ የሚጠቀሱትን ዘሮች ከተለያዩ ቅጂዎች ጋር ማመሳከርም አስፈላጊ ነው። እንደዚሁም እነዚያ አባቶች ብለዋቸዋል እየተባሉ የሚጠቀሱትን ነገሮች ከጥንት ምንጫቸው ማጣራት በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። እነ እገሌ ብለዋቸዋል እየተባሉ በታላላቅ አባቶች ስም ለዘመናት ሲጠቀሱና ሲያወዛግቡ የኖሩ ሆኖም ከምንጫቸው ሲፈለጉ ግን ያልተገኙ አገላለጾችና ሐሳቦች አይታጡምና።

ስለሆነም የሆኑ ቃላትን ብቻ በመውሰድ “እንደዚህ የሚል ቃል አለ/የለም”፣ “እንደዚህ ይባላል/አይባልም” ከሚል ባለፈ፣ ያን ቃል የሚሉት/የማይሉት ወገኖች ለምን እንደዚያ እንደሚሉ/እንደማይሉ ሐሳባቸውን ለመረዳት የተወሰኑ እርምጃዎችን መሄድ አስፈላጊ ነው። የኦርቶዶክሳዊነት ምሰሶ የነበረው ታላቁ አባት ቅዱስ አትናቴዎስ “ተጋድሏችን ለእውነት እንጂ ለቃላት አይደለም!” ያለው ለዚህ ነው።

ከቃላትና ከአገላለጾች ባሻገር የሆኑ፣ ከጥቅሶችና ገጸ-ንባቦች ባሻገር አስተምህሮን ማዕከል ያደረጉ፣ ከጥቃቅኑ ነገር አልፈው ትልቁን ሥዕል የሚመመለከቱ እንደ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ያሉ አባቶችን አይንሣን! እኛንም እንደዚህ ያሉ አባቶችን ለመስማትና ለመታዘዝ ያብቃን! አሜን!

በዚህች ደካማ ተምኔታዊ ጽሑፍ ላይ የቃላትና የአገላለጽ ችግር ካለም ይቅርታ በመጠየቅ ነው!

Dn Yaregal Abegaz
Please forgive me for my belated reply to your letter which is dear to me. I am not feeling well, and the thoughts about death do not leave me alone. I feel that if I live up to see 1963, I will not pass it through. For me personally,death is desirable. I know that there is future life, that there is God’s mercy for us and there is hope for us believing in the Lord Jesus Christ to enter intothe blissful eternity, rather than an everlasting torturous future.
Religious perceptions, though different from the spiritual meaning ofthe world, are also as real as the perceptions of the physical world. The earthly life is not for pleasures but for getting knowledge of oneself and of God.
During their earthly life people must make a resolute and irrevocable choice– to strive for good or for evil; for God or for devil. Those seeking God and His truth will find God and the rudiments of a new life here, on earth, and in itsfullness – after death. An egoist looking exclusively for earthly pleasures will find the devil and after death, as of one in spirit with the devil will go to the Devil’s kingdom, Hell, to join the community of downright egoists and evil-doers. Our future destiny is in our hands… Forgive me, if I am writing not quite what I should. I am sorry not to have come to see you this summer.
I wish to be farther from this life and from the spirit of this world. This spirit has taken possession of the whole mankind. Only from the outside it is possible to see and to feel the loathsome vileness and ugliness of this spirit.
There are very few people in the world today, who are capable of escaping the influence of this evil spirit on them. This is horrible! They say, that a frogmeeting with the eyes of a snake cannot cast its glance away, it starts to cry,but is unable to run away and instead is moving closer and closer to the snake until it fnally gets into its mouth.
There are words in one of the evening prayers, pleading: “Lord, take me away from the mouth of the abhorrent serpent, desiring to devour me alive and to throw into the hell.” These words come from human experience. Those possessed by this spirit do not understand them and do not believe those who have freed themselves from it.
May the Lord bless you and protect you from evil and lead you to eternal blissfulness after death. God willing, we might see each other in the outer world.
Choose God; keep away from the devil in spirit and in deed, so that the Lord’s words: “Who is coming to Me I will not cast out” may be also said about you.

#Abbot_Nikon_Vorobiev
#Spiritual_letters
ቅዱስ ጳውሎስ እና ሕግ
***
"መገረዝ ቢሆን አለመገረዝም ቢሆን ከንቱ ነው፥ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጠበቅ ነው እንጂ።" (1ኛ ቆሮ. 7፥19)
ታላቁ ሐዋርያ ጳውሎስ ሆይ! መገረዝ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ስለመሆኑ ለአንተ እንዴት ይነገራል? ለአብርሃም እና ለዘሩ መገረዝን ያዘዘ ራሱ እግዚአብሔር አይደለምን? መገረዝን ከትእዛዛት ለምን አወጣኸው? ብለን እንጠይቅ። እርሱም እንዲህ ይመልሳል።
የብሉይ ሕግ ልዩ ልዩ ገጽታ አለው። አንደኛው ገጽታው እስራኤል ከአሕዛብ ርኩሰት ይጠበቁ ዘንድ ከአሕዛብ ለመለያነት የተሰጡ ሕጋት ናቸው። እነዚህም የግዝረት፣ የመባልዕት፣ የበዓላት እና የቀናት ሕጋት ናቸው። እስራኤል በሃይማኖት እስኪጎለምሱ ድረስ በመንፈስ ሕጻናት በነበሩበት ዘመን እንደ ሞግዚት ሆነው ይጠብቋቸው ዘንድ በጊዜያዊነት የተሰጡ ሕጋት ናቸው። እነዚህን ሐዋርያው በገላትያ እና በሮሜ መልእክታቱ 'የሕግ ሥራ' እያለ የሚጠራቸው ናቸው። (ገላ. 2፥16፣ 3፥2፣ 3፥5፤ ሮሜ. 3፥20፣ 3፥27 ወ.ዘ.ተ. . . ) በክርስቶስ መምጣት አሕዛብ ሁሉ የአብርሃምን ተስፋ በእምነት የሚካፈሉበት ዘመን ሲደርስ እነዚህ እስራኤልን አጥር ቅጥር ሆነው ከአሕዛብ የሚለዩ ሕጋት ተፈጽመዋል፤ ክርስቶስ የእነዚህ ሕጋት ፍጻሜ ነውና። (ሮሜ. 13፥10)
አሁን በእነዚህ የአይሁድ ሕጋት ሥር ለመሆን መፈለግ ከአዋቂነት ወደ ሕጻንነት፣ ከነጻነት ወደ ባርነት መመለስ ስለሆነ ሐዋርያው ይህን አምርሮ ይቃወማል። በዚህ መንገድ ሆነው አሕዛብ ወደ ወንጌል ለመምጣት የግድ እነዚህን የአይሁድ ሕጋት ፈጽመው 'አይሁድ' መሆን አለባቸው ብለው እዳ የሚጭኑትን አይሁድ-ዘመም መምህራን "ከክርስቶስ ተለይተው ከጸጋው የወደቁ፣ ስለክርስቶስ መስቀል እንዳይሳደዱ የሚሸሹ፣ የመስቀሉን እንቅፋት ለማስወገድ የሚሰሩ" በማለት ይወቅሳል፤ ከክርስትና ወንጌል በተቃርኖ ያቆማቸዋል። (ገላ. 5፥3፣ 11፤ 6፥12)
ሌላኛው የሕግ ገጽታ ደግሞ አይሁድን ከአሕዛብ ያለመለየት ለሁሉም የሰው ልጆች የሚሆነው እና ሕግ ያልተሰጣቸው አሕዛብ ሳይቀር በልቡናቸው የሚያውቁት፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ ከኃጢአት ተለይቶ የሚታወቅበት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ "መገረዝም ቢሆን አለመገረዝም ቢሆን ከንቱ ነው፤" ካለ በዋላ በተጻራሪ የሚጠቅመው "የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጠበቅ ነው እንጂ፤" ብሎ የገለጸው ይህን ሰፊውን እና ጥልቁን የሕግ ገጽታ ነው።
በርግጥ ከክርስቶስ መምጣት በፊት ባሕርያችን ደክሞ ኃጢኣት ሰልጥኖ ስለነበር ሰው በሕግ ኃጢኣትን ቢያውቅም በጽድቅ መጽናት አልቻለም ነበር፤ ይልቁንም በገነት ውስጥ እንደሆነው ሕጉ ሲከለክለው እየጎመጀ ኃጢኣትን ይሠራ ነበር። የጉስቁልና ዘመን ነበርና። በዚህም የተነሣ ቅዱሱን ሕግ ራሱ ለመጥፎ መጠቀሚያ ያደርግ የነበረውን ክፉ ውድቀት ለመናገር ሐዋርያው በዚህ በሰፊ ገጽታውም ጭምር ሕጉን "የኃጢኣት ሕግ"፣ "የባርነት ሕግ"፣ "የእርግማን ሕግ"፣ "የሞት ሕግ" እያለ ጠንከር ባሉ አገላለጾች ጠርቶታል። (ሮሜ. 5፥20፣ 8፥2፣ ገላ. )
ነገር ግን ከዚህ ተነሥተው ሰዎች ወደተሳሳተ ድምዳሜ እንዳይሄዱ ደግሞ ፈጥኖ ስለ ሕጉ በጎነት እና ጽድቅ ጥብቅና ይቆማል። (ሮሜ. 7)
ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መጥቶ የሕግን እውነተኛ ገጽታ (እግዚአብሔርን እና ባልንጀራን መውደድ) በፊደሉ ሳይሆን በጥልቅ ትርጉሙ አስተምህሮ እንዲሁም በተግባር ፈጽሞ ካሳየ በኋላ፣ በሞቱ እና በትንሣኤው ባሕርያችን አድሶ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ካጠነከረን በኋላ ግን ሕጉ አዲስ ኃይል እንዳገኘ ያስረዳን ዘንድ ሐዋርያው በብዙ መልኩ ይጥራል። በአንድ ቦታ "ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና፥ እርሱም፦ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚል ነው፤" በማለት ሕጉ በክርስቶስ የፍቅር ትእዛዛት እንደጸና ይናገራል። (ገላ. 5፥14) ይህንኑ ሲያመለክትም "የክርስቶስ ሕግ" እያለ ይናገራል። (ገላ. 6፥2) ቀድሞ ለኃጢኣት ኃይል መጠቀሚያ ሆኖ የነበረው በመንፈስ ቅዱስ ሃይል ለጽድቅ መሆን መጀመሩን ሲናገርም "የመንፈስ ሕግ" ይለዋል። (ሮሜ. 8፥2)
***
ጠቅለል ሲደረግ የቅዱስ ጳውሎስ የሕግ አስተምህሮ ሰፊ እና መልከ ብዙ (differentiated) ነው። በአግባቡ ለመረዳት ሰፊውን ታሪካዊ እና ነገረ-ሃይማኖታዊ ዓውድ ማጤን ይገባል። ዋናው ነገር ግን ታላቁ ሐዋርያ ሕግ የሚባል ነገር አያስፈልግም፤ ተሽሮአል ብሎ አላስተማረም። የሕጉን መንፈስ እና ዓላማ እያሳየ የተፈጸመውን እና የጸናውን በየፈርጁ አስረዳ እንጂ። ሕጉን በተሳሳተ መልኩ የሚረዱትንም አወገዘ እንጂ። በተጨማሪም ሕግ ከሚፈጸምበት ጸጋ እና ሃይል ተለይቶ "ከክርስቶስ እምነት" በተጻራሪ ሊቆም እንደማይገባ በሃይለ ቃል አስተማረ እንጂ። (ገላ. 2፥16)
ቅዱስ ጳውሎስ ሕግን እንደተቃወመ አድርጎ የሚተረጎመው አካሄድ የ15ኛው መ/ክ/ዘመን የሉተር እና የሌሎች ተሐድሶዎች የተሳሳተ መረዳት (distortion) ውጤት ነው። ሉተር ጉዳዩን ይረዳው የነበረው ከቅዱስ ጳውሎስ ዓውድ አንጻር ሳይሆን ከራሱ የግል የሕይወት ቀውስ እና ከሮም ቤተ ክርስቲያን ዘመንኛ ችግር አንጻር ነበር። ይህም ትልቅ ምስቅልቅል አምጥቷል።
Bereket Azmeraw