ስንክሳር ወግጻዌ ዘተዋሕዶ
858 subscribers
3.46K photos
103 videos
194 files
1.2K links
የየዕለቱ ስንክሳር እና ግጻዌ የሚቀርብበት ቻናል ነው፡፡

ለማንኛውም አስተያየት እና እርማት
@zetaodokos ላይ ይላኩልን።

👇👇የYoutube Channel ይቀላቀሉ👇👇
https://youtube.com/channel/UCupqpIYe_mMpSM7jMT3Njhw
Download Telegram
ከዚህም በኋላ የከበረ አባ መቃርስ ተመልሶ ከእርሱ አስቀድሞ በዚያ በረሀ ውስጥ ሰው እንዳለ ያይ ዘንድ ወደ በረሀው ውስጥ ዘልቆ ገባ። ዕራቁታቸውን የሆኑ ሁለት ሰዎችን አይቶ ፈራ የሰይጣን ምትሐት መስሎታልና እልቦት ቦሪቦን ብሎ ጸለየ ይህም አቡነ ዘበሰማያት ማለት ነው እነርሱም በስሙ ጠርተው መቃሪ ሆይ አትፍራ አሉት እርሱም በበረሀ የሚኖሩ ቅዱሳን እንደሆኑ አውቆ ወደ እርሳቸው ቀርቦ እጅ ነሣቸው። እነሱም በዓለም ስላሉ ሰዎች ስለ ሥራቸውም ጠየቁት እርሱም በቸርነቱ እግዚአብሔር በሁሉም ላይ አለ ብሎ መለሰላቸው።

እርሱም ደግሞ የክረምት ቅዝቃዜ ይቀዘቅዛቸው እንደሆነ የበጋውም ትኩሳት ያልባቸው እንደሆነ ጠየቃቸው። እነርሱም በዚህ በረሀ እግዚአብሔር አርባ ዓመት ጠብቆናል የክረምት ቅዝቃዜ ሳይቀዘቅዘን የበጋ ትኩሳት ሳያልበን ኖርን ብለው መለሱለት ደግሞ እንደናንተ መሆን እንዴት እችላለሁ አላቸው።

እነርሱም ወደ በዓትህ ተመልሰህ ስለ ኃጢአትህ አልቅስ አንተም እንደእኛ ትሆናለህ አሉት ከእነርሱም በረከትን ተቀብሎ ወደቦታው ተመለሰ።

በእርሱ ዘንድ መነኰሳት በበዙ ጊዜ ጕድጓድ ቆፍረው መታጠቢያ ሠሩለት ሊታጠብ በወረደ ጊዜ ሊገድሉት ሰይጣናት በላዩ አፈረሱት መነኰሳትም መጥተው አወጡት።

እግዚአብሔርም ከዚህ አለም መከራ ሊያሳርፈው በወደደ ጊዜ ሁልጊዜ የሚጐበኘውን ኪሩብን ወደርሱ ላከ። እርሱም እኔ ወደ አንተ መጥቼ እወስድሃለሁና ተዘጋጅ አለው ከዚያ በኋላ አባ እንጦንስንና የቅዱሳንን አንድነት ማኅበር ሰማያውያን የሆኑ የመላእክትንም ሠራዊት በእግዚአብሔር እጅ ነፍሱን እስከ ሰጠ ድረስ ያይ ነበር።

መላ የዕድሜው ዘመን ዘጠና ሰባት ሆነ። የቅዱስ መቃርስ ነፍስ ወደ ሰማይ ስታርግ እንዳየ በዚህ ነገር ደቀ መዝሙሩ አባ በብኑዳ ምስክር ሆነ ሰይጣናትን እንደሰማቸው እየተከተሉ መቃሪ ሆይ አሸነፍከን አሸነፍከን እያሉ ሲጮኹ እስከ ዛሬ ገና ነኝ አላቸው ወደ ገነትም ሲገባ መቃሪ ሆይ አሸነፍከን ብለው በታላቅ ድምፅ ጮኹ የክብር ባለቤት ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ይመስገን ስሙም ይባረክ ከእጃችሁ ያዳነኝ አላቸው ብሎ መስክሮአል።

የሥጋው ፍልሰትም እንዲህ ሆነ እርሱ በሕይወት ሳለ ሥጋውን እንዳይሠውሩ ልጆቹን አዞአቸው ነበር የሀገሩ የሳሱይርም ሰዎች መጥተው ለደቀ መዝሙሩ ለዮሐንስ ገንዘብ ሰጡ።

ይህንንም ስለ ገንዘቡ ፍቅር ይመክረውና ይገሥጸው የነበረ ገንዘብ ከመውደድ ተጠበቅ የሚለው ነው። እርሱም መርቶ የቅዱስ አባ መቃርስን ሥጋ አሳያቸው ወደሀገራቸው ሳሱይር ወሰዱት እስከ ዓረብ መንግሥት መቶ ስልሳ ዘመን በዚያ ኖረ ደቀ መዝሙሩ ዮሐንስ ግን ገንዘብ ስለመውደዱ ዝልጉስ ሆነ።

ከዚህም በኋላ ልጆቹ መነኰሳት ወደ ሀገሩ ወደ ሳሱይር ሔዱ የከበረ አባት የአባ መቃርስን ሥጋ ሊወስዱ ፈለጉ የአገር ሰዎችም ከመኰንኑ ጋር ተነሥተው ከለከሉአቸው በዚያቺም ሌሊት የከበረ አባ መቃሪ ለመኰንኑ ተገልጦ ተወኝ ከልጆቼ ጋራ ልሒድ አለው። መኰንኑም መነኰሳቱን ጠርቶ የአባታቸውን ሥጋ ተሸክመው ይወስዱ ዘንድ ፈቀደላቸው።

በዚያን ጊዜም ተሸከመው አክብረው ወሰዱት በብዙ ምስጋና በመዘመርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከእርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ማለድ ብለው ሲደርሱ አርፋ አገኟት፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ንጉሥ_ሰማዕት_ገላውዴዎስ

በዚህችም ቀን የኢትዮጵያ ንጉሥ ሰማዕት ገላውዲዎስ አንገቱን የተቆረጠበት ቀን ነው። ይህ ቅዱስም በተግሣጽ በምክር በፈሪሀ እግዚአብሔር አደገ አባቱ ንጉሥ ልብነ ድንግል ሃይማኖቱ የቀና ነበርና በዘመኑም የእስላም ወገን የሆነ ስሙ ግራኝ የሚባል ተነሥቶ አብያተ ክርስቲያናትን አጠፋ።

ከንጉሥ ልብነ ድንግል ጋር ጦርነት ገጠመ ንጉሡም ወግቶ መመለስ ቢሳነው አርበኞች ሠራዊትን እስከሚሰበስብ ከእርሱ ሸሸ በስደትም እያለ በድንገት ታሞ ሞተ።

ይህም አመፀኛ የኢትዮጵያን ሀገሮች እያጠፋ ዐሥራ አምስት ዓመት ያህል ኖረ። ከኢትዮጵያም ሕዝቦች የሚበዙትን ማርኮ ከቀናች ሃይማኖት አውጥቶ የእርሱ ሃይማኖት ተከታዮች አደረጋቸው በመመካትም እንዲህ አለ። ሀገሮችን ሁሉ ግዛቶቼ ስለ አደረግኋቸው ከእንግዲህ የሚቃወመኝ የለም።

ከዙህ በኋላ እግዚአበሔር ይህን ቅዱስ ገላውዴዎስን አስነሣ ከግራኝ ታላላቅ መኳንቶቹ ጋር ጦርነት ገጠማቸው ድልም አድርጎ አሳደዳቸው።

ግራኝም በሰማ ጊዜ ተቆጣ ከቱርክ አርበኞች ጋርና ከአእላፍ ፈረሰኞች ጋር መጥቶ ንጉሡን ገጠመው ጌታችንም ግራኝን በንጉሥ ገላውዴዎስ እጅ ጣለው ገደለውም። ግራኝን በመፍራት የተበተኑ ሁሉ ከተማረኩበትም ሁሉ ተመለሱ የፈረሱ አብያተ ክርስቲያናትም ተመልሰው ታነፁ የክብር ባለቤት የሆነ የክርስቶስ ሃይማኖት ተቃናች።

ከዚህም በኋላ ከእስላሞች ወገን አንዱ ከብዙ አርበኞች ሠራዊት ጋር መጣ በመድኃኒታችን የስቅለት በዓል ከጥቂት ሰዎች ጋራ ተቀምጦ ሳለ በድንገት ንጉሡን ተገናኘው ሰዎቹም የጦር መኰንኖች እስቲሰበሰቡ ፈቀቅ እንበል አሉት።

እርሱ ግን የክርስቲያኖችን መማረክና የአብየተ ክርስቲያናትን መፍረስ አላይም ብሎ እምቢ አለ እንዲህም እያለ ወደ ውጊያው መካከል ገብቶ በርትቶ ሲዋጋ የኋላ ኋላ እስላሞች ሁሉም ከበቡት።

ተረባረቡበትም በጐራዴም ጨፈጨፉት በብዙ ጦሮችም ወጉት ከፈረሱም ጣሉት የከበረች አንገቱንም ቆረጡት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ከገድላት_አንደበት)