መዝገበ ቅዱሳን
22.8K subscribers
1.93K photos
9 videos
6 files
27 links
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው! መ/ሳ 1÷7
Bewust mesimer lemanegager
@Yesadkusitota
የሰማነውን እንናገራለን
ያየነውን እንመሰክራለን
Download Telegram
✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

✞ እንኩዋን #ለብርሃነ_መስቀሉ እና #ለቅዱሳኑ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞

#ቅዱስ_ዕፀ_መስቀል

=>ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና ቸር አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ከሰማያዊ ክብሩ ወደ ምድር ወርዶ: በማሕጸነ #ማርያም_እግዝእት በኪነ ጥበቡ ተጸንሶ: በኅቱም ድንግልና ተወልዶ: በፈቃዱ መከራ መስቀልን ተቀብሎ:
¤ከግራ ቁመት:
¤ከገሃነመ እሳት:
¤ከሰይጣን ባርነት:
¤ከኃጢአት ቁራኝነትም አድኖናል::

=>+"+ እምእቶነ እሳት ዘይነድድ አንገፈነ +"+ እንዳለ ሊቁ::

+ምንም መስቀል በብሉይ የወንጀለኞች መቅጫ ሆኖ ቢቆይም እግዚአብሔር ለዓለም መዳኛነት የመረጠው ነውና ሕብረ ትንቢቶች ሲነገሩለት: በብዙ ሕብረ አምሳልም ሲመሰል ኑሯል:: ከተፈጥሯችን ጀምሮ ዓለም ራሷ አርአያ #ትዕምርተ_መስቀል ናት::

+እግዚአብሔር ለቃየን እንዳይገድሉት ከሰጠው ምልክት (ዘፍ. 4:15) ጀምሮ
¤#ይስሐቅ ሊሰዋ የተሸከመው እንጨት (ዘፍ. 22:6):
¤#ቅዱስ_ያዕቆብ ያያት የወርቅ መሰላል (ዘፍ. 28:12):
¤ያዕቆብ የዮሴፍን ልጆች የባረከበት መንገድ (ዘፍ. 48:14):
¤ባሕረ ኤርትራን የከፈለችው #የሙሴ_በትር (ዘጸ. 14:15):
¤#የናሱ_ዕባብ የተሰቀለበት እንጨት (ዘኁ. 21:8) ጨምሮ በርካታ ምሳሌዎች ለቅዱስ መስቀሉ መኖራቸውን መተርጉማን ተናግረዋል::

+#ቅዱስ_ዳዊትን የመሰሉ ነቢያት ደግሞ "ለሚፈሩሕ ከቀስት ያመልጡ ዘንድ ምልክትን ሰጠሃቸው" እያሉ መስቀሉን ከርቀት ተመልክተዋል:: (መዝ. 59:4)

+በሐዲስ ኪዳን ግን ምሳሌው ገሃድ ሆኖ: ጌታ በዕፀ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ሥጋውን ቆረሰበት: ደሙን አፈሰሰበት: ዓለምንም አዳነበት:: ስለዚህም "#መስቀል_ብርሃን_ለኩሉ_ዓለም: #መሠረተ_ቤተ_ክርስቲያን" ተብሎ የሚመሰገን ሆኗል::

+#ቅዱስ_ያሬድ ሊቁ አክሎ "መስቀል መልዕልተ ኩሉ ነገር: ያድኅነነ እምጸር" ብሎ ጠላትን ማሳፈሪያ መሆኑን ይነግረናል:: #ብርሃነ_ዓለም #ቅዱስ_ዻውሎስም ስለ መስቀሉ አምልቶ አጉልቶ አስተምሯል:: መመኪያችን ነውና:: (1ቆሮ. 1:18, ገላ. 6:14)

+አንዳንዶቹ እኛን 'የተሰቀለውን ትታቹሃል' ይሉናል:: የተሰቀለውማ የጌቶች ጌታ: የነገሥታት ንጉሥ: የአማልክት አምላክ: ሁሉ በእጁ የተያዘ: #ኢየሱስ_ክርስቶስ ነውና ከኦርቶዶክስ በላይ የሚያመልክ በወዴት አለና::

+ነገር ግን መስቀሉን ንቆ የተሰቀለውን ማክበር አይቻልምና እኛ ለመስቀሉ የጸጋ ስግደትን እንሰግዳለን: እናመሰግነዋለን: እናከብረዋለን: ቤዛ: ጽንዕ: መድኃኒት: ኃይል እያልንም እንጠራዋለን:: አባቶቻችን በመስቀሉ ምርኩዝነት ማዕበለ ኃጢአትን: ባሕረ እሳትን ተሻግረዋል::

+በመስቀሉ ቢመኩ አጋንንትን ድል ነስተዋል:: ጠላትንም አሳፍረዋል:: እኛም በመስቀሉ አምነን ከብረን: ገነን እንኖራለን:: ተጠቅመንበታልና ከራሳችን ሕይወት በላይ ምስክርን አንፈልግም::

+"+ #በዓለ_መስቀል +"+

=>#መድኃኔ_ዓለም ክርስቶስ ካረገ ከዓመታት በሁዋላ አይሁድ በአንድ ነገር ተቸገሩ:: የክርስቶስን ሐዋርያት እያሳደዱ ቢገድሉም ከመስቀሉና ሥጋ ክርስቶስ አርፎበት ከነበረው ጐልጐታ ላይ የሚደረገውን ተአምር ግን መግታት አልተቻላቸውም::

+መቼም ለተንኮል አያርፉምና ቅዱስ መስቀሉን ሽፍቶቹ ከተሰቀሉባቸው ጋር ደርበው አርቀው ቀበሩት:: አካባቢው የጉድፍ መጣያ እንዲሆንም አዋጅ ነገሩ:: ለክፋት ሲሆን ተባባሪው ብዙ ነውና ለ270 ዓመታት ያህል ቆሻሻ ቢጥሉበት ተራራ ሆነ::

+ከዚህ ሁሉ ነገር በሁዋላ እናታችን ቅድስት #እሌኒ (ሔለና) በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነት: በቅዱስ #ኪራኮስ መሪነት: በቅዱስ #ሚካኤል ረዳትነት ደመራ አስደምራ: እጣን አጢሳ መካነ መስቀሉን አገኘች::

+መስከረም 17 ቀን የተጀመረው ቁፋሮ መጋቢት 10 ቀን ተጠናቆ: ንጹሕ መስቀሉ ወጥቶ ብርሃን በርቷል: ሙታን ተነስተዋል:: ከ10 ዓመት በሁዋላም የመስቀሉ ቤተ መቅደስ ታንጾ መስከረም 17 ቀን ተቀድሷል::

+ይህ ቅዱስ ዕፀ መስቀልም በደጉ #አፄ_ዳዊት ዘመን ወደ ሃገራችን መጥቶ: በጻድቁ #አፄ_ዘርዓ_ያዕቆብ አማካኝነት በደብረ ከርቤ (#ግሸን_ማርያም) ተለብጦ ተቀምጧል::

+"+ #ቅዱስ_አውዶኪስ_ቀሲስ +"+

=>ይህ ቅዱስ ሰው ለቅዱስ መስቀሉ ከነበረው ፍቅር የተነሳ በብዙ ድካም ወደ #ኢየሩሳሌም በእግሩ ተጉዞ ነበር:: ከብዙ መንገደኞች ጋር በጐዳና ላይ ሳሉ ታዲያ አንድ አይሁዳዊ (ሰማርያዊ) ተቀላቀላቸው:: በወሬ በወሬ የት እንደሚሔዱ ሲጠይቃቸው "መካነ መስቀሉን ለመሳለም ወደ #ጐልጐታ ነን" አሉት::

+እሱ ግን ከት ብሎ ስቆ "እንዴት እንጨት ትሳለማላችሁ" በሚል አፌዘባቸው:: የፀሐዩ ሐሩር እጅግ ጠንቶ ነበርና ቅዱስ አውዶኪስ ኃይለ መስቀሉን ሊያሳይ ወደደ:: በመንገድም መርዝነት ያለው ውሃ ነበርና ቅዱሱ ቀርቦ ጸልዮ በመስቀሉ ባረከውና ፈጥኖ ወደ ጣፋጭነት ተቀየረ::

+ምዕመናኑ ደስ ብሏቸው ሲጠጡ ያ አይሁዳዊ 'እጠጣለሁ' ብሎ ቢቀርብ ወደ ነበረው ተመለሰበት:: 'በኮዳ የያዝኩትን እማልጠጣ' ብሎ ቢከፍተው ደግሞ ተልቶ አገኘው:: እጅግ ደንግጦ አለቀሰ:: በጣም ጠማው: ግን ምኑን ይጠጣ!

+አማራጭ ሲያጣ ወደ ቅዱስ አውዶኪስ ሒዶ እግሩ ላይ ወድቆ አለቀሰ:: በመስቀሉ ቢማጸን መራራው ጣፈጠለት:: በዚህ ምክንያትም ወደ ክርስትና ተመልሷል:: ቅዱሱ በመልካም ሽምግልና ሲያርፍ ውሃው የተቀየረበት ቦታ ላይ ቤተ መቅደስ ታንጾ በዚህ ቀን ተቀድሷል::

+"+ #ቅድስት_ታኦግንስጣ +"+

=>በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረችው ሮማዊቷ እናት መንገድ ላይ ቁማ #ወንጌል ስታነብ በንጉሥ ወታደሮች ተማርካ ወደ #ሕንድ ተወስዳለች:: በዚያም በመስቀል አማትባ ሙት በማስነሳቷ የሃገሩ ሰው ወደ ክርስትና ከነ ንጉሡ ተመልሰዋል:: እርሷም ገዳም አንጻ: ደናግሉን ሰብስባ በንጽሕና ኑራለች:: በዚህ ቀን ዐርፋ ሲቀብሯት የብርሃን መስቀል መቃብሯ ላይ ተተክሏል::

=>አምላከ ቅዱሳን በኃይለ መስቀሉ: በሞገሰ መስቀሉ ይጠብቀን:: ከበረከቱ አሳትፎ በዓሉን የሰላም ያድርግልን::

=>መስከረም 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ዕፀ መስቀል
2.ቅድስት እሌኒ ንግስት
3.ቅዱስ ኪራኮስ አረጋዊ
4.ቅዱስ መቃርስ ሊቀ ዻዻስ
5.ቅዱስ አውዶኪስ ቀሲስ
6.ብጽዕት ታኦግንስጣ ሮማዊት
7.ቅዱስ ዲዮናስዮስ ሊቀ ዻዻሳት

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ቀዳሜ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ)
3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ
4.አባ ገሪማ ዘመደራ
5.አባ ዸላሞን ፈላሢ
6.አባ ለትጹን የዋህ
7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ (ዘደሴተ ቆዽሮስ)

=>+"+ የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና . . . መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ:: የግሪክ ሰዎችም ጥበብን ይሻሉ:: እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን:: +"+ (1ቆሮ. 1:18-23)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
@petroswepawulos
#መስከረም_17

መስከረም ዐሥራ ሰባት በዚህች ቀን #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የተሰቀለበት የከበረ #መስቀል በዓሉ ነው፣ #የቅድስት_ድንግል_ታኦግንስጣ እና የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ_ዲዮናስዮስ እረፍታቸው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#በዓለ_መስቀል

መስከረም ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ለከበረ መስቀል በዓሉ ነው። ይህም የጻድቁ ንጉሥ የቈስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒ ከተሠወረበት የገለጠችው ነው።

የጎልጎታን ኮረብታ በአስጠረገች ጊዜ የከበረ መስቀልን አገኘችው ታላቅ ኮረብታም የሆነበት ምክንያት እንዲህ ነው። ብዙዎች ድንቆች ተአምራት ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመቃብሩና ከመስቀሉ የሚገለጡ ሁነው ሙታን ይነሡ ነበርና የጎበጡና በሽተኞች ሁሉ ይፈወሱ ነበር።

ስለዚህም አይሁድ ተቆጡ እንዲህም ሥርዓትን ሠርተው አዘዙ በይሁዳ አገር ሁሉና በኢየሩሳሌም ቤቱን የሚጠርግ ሁሉ ወይም አፈር ወይም ጉድፍ የሚጠርግ በናዝሬቱ ኢየሱስ መቃብር ላይ ይጥል ዘንድ እንዲህም እያደረጉ ዕሌኒ ንግሥት እስከ መጣች ድረስ ከሦስት መቶ ዓመት በላይ ኖሩ።

እርሷም በመጣች ጊዜ ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብርን እስከ አሳዩዋት ድረስ አይሁድን ይዛ አሠቃየቻቸው ያንን ኮረብታም እስከ ጠረጉ ድረስ አስገደደቻቸው የከበረ መስቀሉም ከተቀበረበት ተገልጦ ወጣ።

ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንም ተሠራች በዚች ቀንም አከበሩዋት ለመስቀሉም በዓልን መስከረም ዐሥራ ሰባት ቀን አከበሩለት። የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም ከሀገሮቻቸው በመምጣት ክብር ይግባውና ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤውን በዓል እንደሚያከብሩ ለመስቀልም ታላቅ በዓልን የሚያክብሩ ሆኑ።

ክርስቲያኖችም በጎዳና እየተጓዙ ሳሉ ስሙ ይስሐቅ የሚባል አንድ ሳምራዊ ሰው ከእርሳቸው ጋር ነበር ከእርሱም ጋር ብዙዎች ሳምራውያን ነበሩ ይህ ይስሐቅም የክርስቲያን ወገኖችን ለምን በከንቱ ትደክማላችሁ ለዕንጨትስ ልትሰግዱ እንዴት ትሔዳላችሁ እያለ ይሣለቅባቸው ነበር። ከክርስቲያን ወገኖችም ስሙ አውዶኪስ የሚባል አንድ ቄስ አለ ሕዝቡም በጎዳና ሲጓዙ የሚጠጡት ውኃ አላገኙም ነበርና ተጠሙ።

ወደ አንድ ጉድጓድም ሔዱ በውስጡም መሪር የሆነና የገማ ውኃ አገኙ እጅግም በውኃ ጥማት ተሠቃዩ። ይስሐቅም እጅግ ይሣለቅባቸው ጀመረ የቀናች ሃይማኖት ካለቻችሁ ይህ የገማና የመረረ ውኃ ተለውጦ እስቲ ጣፋጭ ይሁን ይላቸው ነበር።

ቀሲስ አውዶኪስም በሰማ ጊዜ መንፈሳዊ ቅናትን ቀንቶ ከዚያ ሳምራዊ ይስሐቅ ጋር ተከራከረ ያ ሳምራዊም በመስቀል ስም የተአምራት ኃይልን ከአየሁ እኔ በክርስቶስ አምናለሁ አለ። ያን ጊዜም ቀሲስ አውዶኪስ በዚያ በገማ ውኃ ላይ ጸለየ ውኃውም ወዲያውኑ ጣፋጭ ሆነ ከእርሱም ሕዝቡ ሁሉ እንስሶቻቸውም ጠጡ።

ሳምራዊ ይስሐቅ ግን በተጠማ ጊዜ በረዋት ከያዘው ውኃ ሊጠጣ ፈለገ ግን ገምቶ ተልቶ አገኘውና መሪር ለቅሶን አለቀሰ። ወደ ከበረ ቄስ አውዶኪስም መጥቶ ከእግሩ በታች ሰገደ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመነ በከበረ ቄስ በአውዶኪስ ጸሎት ጣፋጭ ከሆነው ከዚያ ውኃም ጠጣ።

በዚያም ውኃ ውስጥ ታላቅ ኃይል የሚሠራ ሆነ እርሱ ለአማንያን የሚጣፍጥ ሲሆን ለከሀዲያንና ለአረማውያን የሚመር ሆነ በውስጡም የብርሃን መስቀል ታየ በአጠገቡም ውብ የሆነች ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩ።

ሳምራዊ ይስሐቅም ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ በደረሰ ጊዜ ወደ ኤጴስቆጶሱ ሒዶ ከቤተሰቡ ጋር የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። የከበረ መስቀልም ዳግመኛ የተገለጠበት መጋቢት ዐሥር ቀን ነው ዜናውንም በዚሁ ቀን ጽፈናል።

ምእመናንም በታላቁ ጾም መካከል በዓሉን ማክበር ስለአልተቻላቸው በዓሉን ቤተ ክርስቲያኑ በከበረችበት ቀን አደረጉ ይህም መስከረም ዐሥራ ሰባት ቀን ነው በዚህም ቀን አስቀድሞ ከከበረ መቃብር በንግሥት ዕሌኒ እጅ የተገለጠበት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ታኦግንስጣ

በዚችም ቀን የከበረች ሮማዊት ታኦግንስጣ አረፈች ። ይቺም ቅድስት በደጋጎች ነገሥታት በአኖሬዎስና በአርቃዴዎስ ዘመን የነበረች ናት። በዚያም ወራት የህንድ ንጉሥ መልእክተኞች እጅ መንሻ ይዘው ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ መጡ በሚመለሱም ጊዜ ይችን ድንግል ታኦግንስጣን አገኟት የምታነበውም መጽሐፍ በእጅዋ ውስጥ ነበር ወደ አገራቸውም ነጥቀው ወሰዷት ለህንድ ንጉሥም ሚስቶቹንና ቤተሰቦቹን የምትጠብቅ ሆነች።

በአንዲት ዕለትም የንጉሡ ልጅ አስጨናቂ በሆነ ደዌ ታመመ የከበረች ታኦግንስጣም ወስዳ በብብቷ ታቅፋ በመስቀል ምልክት አማተበችበት በዚያንም ጊዜ ዳነ ከእርሷም ስለ ተደረገው ተአምር የዚች የከበረች ድንግል ታኦግንስጣ ዜናዋ በሀገሩ ሁሉ ተሰማ ከዚያችም ቀን ወዲህ በእነርሱ ዘንድ እንደ እመቤት እንጂ እንደ አገልጋይ አልሆነችም።

ከዚህም በኋላ የህንድ ንጉሥ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ ጉም ጭጋግ ዐውሎ ነፋስና ጨለማ በላዩ መጣ ንጉሡ ግን የከበረች ታኦግንስጣ ስታማትብ ስለአየ በመስቀል ምልክት ማማተብን ያውቅ ነበርና ያን ጊዜ በጭጋጉ በጉሙ በጨለማውና በጥቅሉ ነፋስ ላይ በመስቀል ምልክት አማተበ። ወዲያውኑ ፀሐይ ወጣ ታላቅ ጸጥታም ሆነ ጠላቶቹንም በዚሁ የመስቀል ምልክት ድል አደረጋቸው እጅግም ደስ አለው።

ንጉሡም ከጦርነት በተመለሰ ጊዜ ለከበረች ታኦግንስጣ። ከእግርዋ በታች ሰገደ እርሱንና ቤተሰቦቹን ሁሉ የሀገሩንም ሰዎች የከበረች የክርስትና ጥምቀትን ታጠምቀው ዘንድ ለመናት ቅድስት ታኦግንስጣም እንዲህ አለችው ይህን አደርግ ዘንድ ለእኔ አይገባኝም የሚያጠምቃችሁን ካህን ይልክላችሁ ዘንድ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ ላኩ።

ያን ጊዜም ከወገኖቹ ጋር የሚያጠምቀውን ካህን እንዲልክለት የህንድ ንጉሥ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ መልእክተኞችን ላከ ንጉሥ አኖሬዎስም ልመናውን ተቀብሎ የሚያጠምቃቸውን ቄስ ላከ ቄሱም አጠመቃቸው መሥዋዕትንም ቀድሶ ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው እግዚአብሔርንም የምትወድ የከበረች ድንግል ታኦግንስጣ እጅግ ደስ አላት ያንንም ቄስ መንፈሳዊ ሰላምታ ሰጠችውና ከእርሱ ቡራኬ ተቀበለች እርሱም ከእርሷ በረከትን ተቀበለ።

ከዚህም በኋላ ለራስዋ ገዳም ሠራች ብዙዎች ደናግልም ተሰበሰቡ የምንኩስና ልብስንም በመልበስ እንደርሷ መሆንን ወደዱ እርሷም እመ ምኔት ሆነች። ያም ባሕታዊ ቄስ የክርስትና ጥምቀትን ከአጠመቃቸው በኋላ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ ተመልሶ የህንድን ሰዎች እንዳጠመቃቸውና ክብር ይግባውና ወደ ክርስቶስ ሃይማኖት እንደገቡ ነገረው። ንጉሥ አኖሬዎስም እጅግ ደስ አለው የሮሜ አገር ሊቀ ጳጳሳትንም ይህን ባሕታዊ ኤጲስቆጶስ አድርጎ እንዲሾምላቸው አዘዘው እርሱም ኤጲስቆጶስነት ሹሞ ከህንድ ሰዎች ላከላቸው እጅግም ደስ አላቸው።

ከዚህም በኋላ ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሊሠሩ ጀመሩ ምሰሶዎችንም በፈለጉ ጊዜ አላገኙም በዚያም አከባቢ ታላቅ የጣዖት ቤት ነበረ በውስጡም ያማሩ ምሰሶዎች አሉ። ድንግሊቱ ታኦግንስጣም ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ብዙ በማልቀስ ለመነች ያን ጊዜም እሊያ ምሰሶዎች ከጣዖት ቤት ፈልሰው ሐናፂዎች ከሚሹት ቦታ በቤተ ክርስቲያን መካከል ተተከሉ አማንያን ሁሉ ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን አመሰገኑት ጣዖትን ሲያመልኩ የነበሩም ጣዖቶቻቸውን ሰብረው ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ተመልሰው ገቡ በዚያችም አገር ታላቅ ደስታ ሆነ።