ቅዱሳን ኅሩያን የዲ°ን ዮርዳኖስ ትምህርቶች
4.78K subscribers
773 photos
5 videos
17 files
239 links
የዲ.ን ሄኖክ ሀይሌን ስብከት በድምጽ እንለቃለን
ለአስተያየት @EMNE_TSYON @unitte_bot
በቴሌግራም ከፈለጉን @henokhailee
በfacebook ከፈለጉን https://www.facebook.com/tewahidosewhone/
በyoutube ከፈለጉን https://youtube.com/channel/UCq2ueVG6O3ZuKHJ485y7hfg
Download Telegram
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ ከአኵሱም ወደ ማይኪራህ አምርቶ እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን በአካለ ነፍስ ከሶርያ አባ ሕርያቆስ ከብሕንሳ አምጥታ ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን ንባቡን እየነገሩት በዜማ እንዲደርስላት አድርጋለች። ከዚህም አያይዞ ለሥጋ ወደሙ ጸሎት የሚያገለግሉትን ንባቡ የሌሎች ሊቃውንት ድርሰት የሆኑትን ዐሥራ አራቱን ቅዳሴዎች በዜማ አዘጋጀ።

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ጸለምት ሔዶ ምዕራፍ የተባለውን ድርሰቱን ደረሰ። ከዚህ በኋላ አገው፣ ፎገራ እና ወደ ሌሎችም ቦታዎች እየዞረ አስተማረ።

ቅዱስ ያሬድ በቅድስት አኵሰም ወንበር ዘርግቶ፣ ጉባኤ አስፍቶ ደቀ መዛሙርቱን እያስተማረ ሲኖር በጾመ፵ ሱባኤ ላይ ሳለ አንድ ቀን በምኵራብ ሰሞን ስለምናኔው እያስታወሰ በተመስጦ ሲዘምር የዜማው ጣዕም እንኳን ሌላውን ራሱን እጅግ ይመሥጠው ነበር። በጣዕመ ዝማሬው ተመሥጦ ሲያዳምጥ የነበረው ኢትዮጵያዊው ንጉሥ የዐፄ ገብረ መስቀል ዐይን ዐይኑን እየተመለከተ ሳይታወቀው በመስቀል ስላጢኑ (በበትረ መንግሥቱ ዘንግ) ጫፍ የቅዱስ ያሬድን እግር ወጋው። ቅዱስ ያሬድ ግንቀጠለ፤ ከሰማያት የተገኘች ቃለ ማሕሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ከቆመበት ሳይንቀሳቀስ ሕመሙ ሳይታወቀው ደሙም ያለማቋረጥ ፈሰሰ።

ቅዱስ ያሬድ የጀመረውን በፈጸመ ጊዜ ንጉሡ ደንግጦ በትሩን ከቅዱስ ያሬድ እግያሬድን ቢነቅለው ደሙ በኃይል ይፈስ ጀመር። ያን ጊዜ ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀል የቅዱስ ያሬድን ትዕግሥት ባለ ጊዜ በመደነቅ፣ በመገረምና በመደንገጥ ዝም በማለት አፉን ይዞ ቆመና ምድራዊ ዋጋ የሚፈልግ መስሎት "ካህን ያሬድ ሆይ የምትፈልገውን ዋጋ ጠይቀኝ" አለው። ቅዱስ ያሬድ መልሶ "የፈለግኹትን እንዳትከለክለኝ ቃል ኪዳን ግባልኝ" አለው። ንጉሡም የጸና ቃል ኪዳን ለቅዱስ ያሬድ ገባለት። ቅዱስ ያሬድም " ከዚህ ሐላፊ ዓለም ክብር ተለይቼ መናኝ ሆኜ እንድኖር ተወኝ ያሬድ አሰናብተኝ" ብሎ አሳብን ገለጸለት። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ካህን የጠየቀውን እንዳይከለክለው ከአፉ የወጣውን መሐላ አስቦ በምናኔ አሰናበተው እንጂ ሊከለክለው አልቻለም።

ቅዱስ ያሬድ ካህንም የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ወዳለችበት ጽዮን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ሁለት እጆቹን በታቦተ ጽዮን ላይ አኑሮ "ቅድስት ወብፅዕት፣ ስብሕት ወቡርክት፣ክብር ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዓርገ ሕይወት" ብሎ በደረሰው አንቀጸ ብርሃን ጸሎት እመቤታችንን አመሰገነ። በዚህ ጊዜ እጁ በታቦተ ጽዮን ላይ ረቦ በመንፈስ ቅዱስ እየተቃኘ ስለነበር ከመሬት አንድ ክንድ ከፍ ከፍ ብሎ ይታይ ነበር። እስከመጨረሻው በከፍተኛ ቃል በዕዝል ዜማ እየዘመረ እግዚአብሔር እና እመቤታችንን ከአመሰገነ በኋላ እመቤታችን በጸሎት መንገድ እንድትመራውና እስከ ፍጻሜ ገድሉ ትረዳው ዘንድ በጸሎት ለመናት። እመቤታችንም መልሳ "ሰማያዊት ጽዮን ያደረግኻት መቅደሴን፣ በመዝሙር በማሕሌት ምስጋና የኪሩቤልና የሱራፌል ወገን ሰማያውያን ያደረግኻቸው ልጆቼ ካህናትን እንዴትድረስ ትተህ ትሔዳለህ" ብላ ቃል በቃል አነጋገረችው። የመንገዱን ስንብት እስክትፈቅድለት በለቅሶና በእንባ ዳግመኛ ለመናት እርሷም እንዲሔድ ፈቀደችለት።

የቅዱስ ያሬድ ምናኔ፦ ወደ ገዳም ሊሄድ ተዘጋጀ በዚህ ጊዜ የሚወዱት ካህናት፣ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ተከትለውት እስከ ተከዜ ወንዝ ድረስ ሸኙት። ከእርሱ በሚለዩበትም ጊዜ "ሰላመ ነሳእነ ወሰላም ኃደግነ ለክሙ ወሰላመ እግዚአብሔር የሀሉ ምስለ ኩልክሙ፤ ሰላምን ከእናንተ ተቀበልን ለእናንተም ሰላምን ተውንላችሁ የእግዚአብሔር ሰላምም ከሁላችሁ ጋራ ይኹን" ብሎ በዜማ ተሰናበታቸው። ዳግመኛ "ወሰላም እግዚአብሔር እንተ ኵሉ ባቲ ተሀሉ ወትረ ምስለ ኵልክሙ፤ ፍቅርና ስምምነት ሁሉ ያለበት የእግዚአብሔር ሰላምታ ሁል ጊዜ ከሁላችሁ ጋራ ትኑር" ብሎ በጣዕ ዜማው መረቃቸው። ካህናቱም ይህን ሰምተው አለቀሱ። እርሱም ከእርሱ ጋራ አለቀሰ። በዚሁ ጣዕመ ዜማው የመጨረሻ ቡራኬውን ሰጣቸውና እርስ በእርሳቸው ተሳስመው ተነሰነባብተው ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑና እየተከዙ ወደ አገራቸው አኵሱም ተመለሱ። እርሱ ግን የተከዜን ወንዝ ተሻገረ። የወንዙ ፏፏቴና ጎርፍ እንሚጮህ አንበሳ ሲጮህ በሰማ ጊዜ "አኅለፍኮሙ በእግር እንተ የብስ ማእከለ ባሕር ተከዜ...፤ በተከዜ ባሕር መካከል በእግር እንደሚሻገር በደረቅ አሻገርካቸው..." እያለ በረቀቀ ምስጢር እግዚአብሔርን በማመስገን እየዘመረ ሲሒድ አንዲት ሴት ውሃ ቀድታ ወደ ቤቶ ስትመለስ ድምፁን ሰምታ ወይ ቃል! ወይ ቃል! እንዴት አንጀት ይበላል! ምንኛስ ያሳዝናል! ብላ ደጋግማ በማድነቅ ስለ ተናገረች ቅዱስ ያሬድ ቆሞ የዘመረባት ቦታ "ወይ ቃል" ተብላ ተጠራች። ዛሬ ይህች ቦታ ጎንደር ክፍለ አገር ደባርቅ አካባቢ "ወይ ቃል" ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ተብላ ትጠራለች።

ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ሔዶ  ጸለምት ወጥቶ ብርድ በጸናበት በረዶ በተከማቸበት ሳኔር ተብሎ በሚጠራ በሐዊ ዐምባ ጽመና ይዞ ተቀመጠ። በዚያም በብዙ ትጋት በጾምና በጸሎት ይልቁንም በስብሐት እግዚአብሔር ብቻ ተወስኖ ጉባኤ ዘርግቶ፣ ትምህርት አስፍቶ ከሱራፌል መላእክት እንደተማረው አድርጎ ከጸለምት፣ ከስሜን፣ ከአገውና ከሌላ አገር ወደ እርሱ የሚመጡትን ሰዎች ሁሉ ማሕሌተ እግዚአብሔር እያስተማረ ኖረ።

ቅዱስ ያሬድ ከትውልድ አገሩ አኵሱም መንኖ ከወጣ በኋላ ትዕግሥቱን እያዘወተረ ወደ እርሱ የመጡትን ሁሉ በማስተማር በገዳመ ስሜን ኖረ። ቅዱስ ቍርባን ለመቀበልና ቅዱሳት ገዳማትን ለመሳለም በፈለገ ጊዜ በሠረገላ ብርሃን ተጭኖ አኵሱም ደርሶ ቅዱስ ቍርባን ተቀብሎ ሌሎች ገዳማትንም ይሳለም ነበር።

በመጨረሻ ቅዱስ ያሬድ ካህን ዘመኑን ሁሉ በመላእክት ማኅሌት እግዚአብሔርን በማገልገልና ይህን ማኅሌት ለሚከተሉት ደቀ መዛሙርት በማስተማር ዘመኑን ፈጽሞ ለሃያ ሁለት ዓመታት በላይ በምናኔ ታግሦ በገድሉና በጣዕመ ዜማው ፀላኤ ሠናያትን ድል አድርጎ ከዚህ ዓለም ድካምና መከራ የሚያርፍበት፣ የሚሰወርበት ቀንና ሰዓት መድረሱን በጸጋ በዐወቀ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን ሰብስቦ "ይቤ ጳውሎስ ኃላፊ ንብረቱ ለዝንቱ ዓለም አኃውየ አስተፋጥኑ ገቢረ ሠናየ አነሰ በድረየኒ ፈጸምኩ ወሃይማኖትየኒ ሠለጥኩ እንከሰ ጽኑሕ ሊተ አክሊል ዘየዓሥየኒ መኰንነ ጽድቅ"  2ጢሞ4፥7-8 እያለ በሚያራራ ቃል ምክሩን ሰጥቶ ተሰናበታቸው። እነርሱም ምክሩን ተቀብለው "አባ አቡነ፣ አባ መምህርነ አይቴ ተሐውር ወለመኑ ተኀድገነ፤ አባታችን መምህራችን ወደ የት ትሔዳለኽ? ለማንስ ትተወናለኽ? እያሉ ሲያዝኑ ሲያለቅሱ በአንድ ዋሻ ውስጥ ገብቶ ግንቦት11 ቀን በ571ዓ.ም ተሰወረ። (ምንጭ፦ የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ቅዱስ ያሬድና የቅዱስ ያሬድ ታሪክ ከሚሉት መጻሕፍት።)

ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

#ሚያዝያ_5_ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፣
፩, #እግዚአብሔር ሰንበትን ቀደሰ
፪, ቅዱስ ሕዝቅኤል ነብይ
፫, ቅዱስ ዲዮስቆሮስ (ክፉ ላለመናገር ድንጋይ ጎርሶ የኖረ አባት)
፬, ቅድስት ታኦድራ
፭, ቅዱስ አርሳኒ
፮, ቅዱስ ያሬድ ካህን ልደቱ

#ወርኃዊ_በዓላት
፩, ቅዱስ ጴጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
፪, ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ
፫, አቡነ #ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ ጻድቅ (አባ ገብረ ሕይወት)
፬, ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮጵያዊ
፭, ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ