ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ
15.5K subscribers
335 photos
80 videos
146 files
208 links
This channel is not operated by Deacon Yaregal Abegaz

https://youtube.com/@yaregalabegaz?si=1f5NHTaQ2l2LbxWQ

“ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው።”
— 2ኛ ቆሮ 11፥28
Download Telegram
ብዙዎች በሰርጋቸው ቀን "የአገራችን ባሕል ነው" የዘፈን ድግስን ያዘጋጃሉ። ወይም ደግሞ "ቤተሰብ እሺ አይልም" በማለት እንደሚቸገሩ ይናገራሉ። ነገር ግን ይህን የቅዱስ ዮሀንስ አፈወርቅ ቃል ማስታወስ ይገባል

"ጋብቻ ዝሙትን የምናጠፋበት መድኃኒት ነው። ስለዚህ በዲያብሎስ ስራ (በዘፈን) ጋብቻን አናቃልል። ከዚህ ይልቅ አሁን የሚያገቡ ሰዎች በቃና ዘገሊላ እንደ ኾነው ያድርጉ። በመካከላቸው ጌታችን ክርስቶስ እንዲኖር ያድርጉ። "እንዴት ይህን ማድረግ ይችላሉ? ብሎ የሚጠይቅ ሰው ሊኖር ይችላል። ካህናትን በመጥራት! 'እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል' ይላልና (ማቴ 10:40)። ስለዚህ ዲያብሎስን አርቁት። የሴሰኝነት ዘፈኖችን፣ የርኵሰት ዜማዎችን፣ ሥርዓት የለሽ ጭፈራዎችን፣ የሚያሳፍሩ ቃሎችን፣ ዲያብሎሳዊ ትርኢቶችን፣ ሁከቶችን፣ቅጥ ያጡ ሳቆችን፣ ሌሎች እነዚህን የመሰሉ አግባብ ያይደሉ ነገሮችንም አስወግዱ። በእነዚህ ፈንታም የጌታችን ክርስቶስ ቅዱሳን አገልጋዮችን ጥሩ ፣ በእነርሱም በእውነት ያለ ሐሰት ከእናቱና ከወንድሞቹ ጋር በሰርጋችሁ ላይ ይገኛል። " በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ ሁሉ እርሱ ወንድሜ እኅቴም እናቴም ነው" ብሏልና (ማቴ 12:50)።
አንዳንድ ሰዎች እንደዚህ ያሉ ተግሣጻትን ስለምናገርና የጥንት ባሕሎችን ስለማስቀር አሰልቺና አስቸጋሪ እንደ ኾንኩ አድርገው እንደሚያስቡ ዐውቃለው። ነገር ግን እነርሱ ስለ ተቃወሙኝ በፍጹም አልጨነቅም። እኔ የምፈልገው በእናንተ ዘንድ ተቀባይነትን ማግኝት ሳይኾን የእናንተን ጥቅም ነውና። ከዚህ ጥበብ ጥቅምን እንድታገኙ እንጂ እንድታመሰግኑኝ አልፈልግምና። ስለዚህ "ይህ ባሕል ነው" ብሎ አንድ ሰውስ እንኳ አይንገረኝ። ኀጢአት በድፍረት የሚፈፀምበት እስከ ኾነ ድረስ ባሕሉን እርሱት። ክፉ ሣራ የሚሰራባቸው እስከ ኾኑ ድረስ ባህሎቹ የቱንም ያህል ጥንታውያን ቢሆኑ ከእናንተ አስወግዷቸው። ክፉ ስራ የማይሰራባቸው ከኾኑ ግን ያልተለመዱ እንኳን ቢሆኑ ተቀበሏቸው።
እስኪ ንገሩኝ! ከእናንተ መካከል ከመዝሙረ ዳዊት ውስጥ አንዲትዋን ምዕራፍ ወይም ከሌላው የቅዱሳት መጻህፍት ክፍል ውስጥ ጥቂት በቃልህ ድገም ቢባል ይህን ማድረግ የሚችል ማን ነው? አንድ ሰውስ እንኳ አይገኝም።
የሚያሳዝነው ነገር ግን ይኼ ብቻ አይደለም። ከመንፈሳዊ ነገሮች አንፃር እንደዚህ አእምሮ የጎደላችሁ ኾናችሁ ሳለ ዲያቢሎሳዊ በኾኑ ነገሮች ላይ ግን ከእሳት በላይ ኀያላን ናችሁ። እንዲህም በመኾናችሁ አንድ ሰው መጥቶ ዲያቢሎሳዊ ዘፈኖችንና የዝሙት ዜማዎችን ንገሩኝ ቢላችሁ ከእናንተ መካከል እነዚህን የሚያውቁና ደስ ተሰኝተው የሚደግሟቸው ብዙ ሰዎችን ያገኛል።

ነገር ግን"ለምንድን ነው እንደዚህ የምትኾኑት?" ተብላችሁ ስትጠየቁ የምትመልሱትስ መልስ ምን የሚል ነው? "እኔ ከመነኮሳት አንዱ አይደለሁም። ሚስት አለቺኝ፣ልጆችም አሉኝ፣የቤተሰብ መሪ ነኝ" የሚል ምክንያት ታቀርባላችሁ። ለምን እንደዚህ ትላላችሁ? ከመነኮሳቱ ይልቅ ይበልጥ ማንበብ ያለባችሁ እናንተ ኾናችሁ ሳለ ብዙዎች እንዲጠፉ ያደረገው "ቅዱሳት መፃህፍትን ማንበብ ለመነኮሳት ብቻ ነው" የሚለው አመለካከታችሁ ነው። ይበልጥ ብዙ መድኃኒት የሚያስፈልጋቸው በማእከለ ዓለም የሚኖሩትና ዕለት ዕለትም መንፈሳዊ ቁስል የሚያገኛቸው ሰዎች ናቸውና። ስለዚህም ከለማንበባችሁም በላይ" የእኛ ማንበብ ትረፍ ነገር ነው" ብላችሁ ማሰባችሁ በራሱ የዲያብሎስ አሳብ ነው። ወይስ ንዑድ ክቡር የሚኾን ጳውሎስ "ዝንቱ ኵሉ ተጽሕፈ ለተግሣጸ ዚአነ - ይህም ኹሉ እኛን ሊገስጸን ተፃፈ"(1ኛ ቆሮ 10:11) ያለውን አላዳመጣችሁምን?

ቅዱስ ዮሀንስ አፈወርቅ
#ግንቦት_11

#ቅዱስ_ያሬድ_ካህን_ወማኅሌታይ

ግንቦት ዐሥራ አንድ በዚህች ዕለት የሱራፌል አምሳላቸው የሆነ ኢትዮጵያዊው ማኅሌታይ ያሬድ የተሰወረበት ነው። ይህም ቅድስ ከአባ ጌዴዎን ዘመዶች ወገን ነው እርሱም በኢትዮጵያ አገር ከታነፁ አብያተ ክርስቲያን ለምትቀድም ከአክሱም ካህናት ውስጥ ነው እርሷም አስቀድሞ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት በውስጥዋ የተሰበከና አምላክን በወለደች በእመቤታችን በከበረች ድንግል ማርያም ስም የከበረች ናት።

ይህም አባ ጌዴዎን ትምህርትን ሊአስተምረው በጀመረ ጊዜ መቀበልም ማጥናትም እስከ ብዙ ዘመን ተሳነው። በአንዲት ዕለትም መምህሩ በእርሱ ላይ ተበሳጭቶ መትቶ አሳመመው። ያሬድም ሸሽቶ ከዱር ውስጥ ገባ ከኀዘኑም ብዛት የተነሣ ከዛፍ ሥር ተጠለለ። ወደ ዛፉ ላይም ትል ሲወጣ አየ ትሉም ከዛፉ እኩሌታ ደርሶ ይወድቅ ነበረ እንዲሁም ብዙ ጊዜ ከአደረገ በኋላ በጭንቅ ከዛፉ ላይ ወጣ።

ቅዱስ ያሬድም የትሉን ትጋት በአየ ጊዜ ወደ መንፈሳዊ መምህሩ ተመልሶ አባቴ ሆይ ይቅርታ አድርግልኝና እንደ ወደድክ አድርገኝ አለው መምህሩም ተቀበለው።

ከዚህ በኋላ በብዙ ልቅሶ ወደ እግዚአብሔር በለመነ ጊዜ ልቡናው ብሩህ ሆኖለት በአጭር ጊዜ የብሉይና የሐዲስ መጻሕፍትን ተምሮ ፈጸመ ዲቁናም ተሾመ።

በዚያም ወራት እንደ ዛሬ በከፍተኛ ቃል የመዝሙር ማኅሌት የለም ነበር በትሑት እንጂ። እግዚአብሔርም መታሰቢያ ሊአቆምለት በወደደ ጊዜ ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን ላከለት እነርሱም በሰው አንደበት ተናግረውት ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ከእሳቸው ጋራ አወጡት በዚያም ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ የሚያመሰግኑበትን ማኅሌታቸውን ተማረ።

ወደ አነዋወሩ ወደ ምድርም በተመለሰ ጊዜ በአክሱም ዳር ወደ ከበረች ቤተ ክርስቲያን በሦስት ሰዓት ገባ በታላቅም ቃል ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ የጽዮንም ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ። ዳግመኛም እንዴት እንደሚሠራት የድንኳንን አሠራር ለሙሴ አሳየው አስተማረው አለ።

ይቺንም ምስጋና አርያም ብሎ ጠራት። የቃሉንም ድምፅ በሰሙ ጊዜ ንጉሡም ንግሥቲቱም ጳጳሱም ከካህናቱ ሁሉ ጋራ የመንግሥት ታላቆችና ሕዝቡ ሁሉ ወደርሱ ሮጡ ሲሰሙትም ዋሉ።

ከዚያም በኋላ ከዓመት እስከ ዓመት በየክፈለ ዘመኑ በክረምትና በበጋ በመጸውና በጸደይ በአጽዋማትና በበዓላት በሰንበታትም እንዲሁም በመላእክት በዓል በነቢያትና በሐዋርያት በጻድቃንና በሰማዕታት በደናግልም በዓል የሚሆን አድርጎ በሦስቱ ዜማው ሠራ ይኸውም ግዕዝ ዕዝል አራራይ ነው።

የሰው ንግግር የአዕዋፍ የእንስሳትና የአራዊት ጩኸት ከዚህ ከሦስቱ ዜማው አይወጣም።
በአንዲት ዕለትም ቅዱስ ያሬድ ከንጉሥ ገብረ መስቀል እግር በታች ቁሞ ሲዘምር ንጉሡም የያሬድን ድምፅ እያዳመጠ ልቡ ተመሥጦ የብረት ዘንጉን በያሬድ እግር ላይ ተከለው ከእርሱም ደምና ውኃ ፈሰሰ። ያሬድም ማኅሌቱን እስከ ሚፈጽም አልተሰማውም።

ንጉሡም አይቶ ደነገጠ በትሩንም ከእግሩ ላይ ነቀለ ስለ ፈሰሰው የደምህ ዋጋ የፈለግኸውን ለምነኝ ብሎ ለያሬድ ተናገረው ያሬድም ላትከለክለኝ ማልልኝ አለው። ንጉሥም በማለለት ጊዜ ወደገዳም ሔጄ እመነኲስ ዘንድ አሰናብተኝ አለው ንጉሡም ሰምቶ ከመኳንንቱ ጋራ እጅግ አዘነ ተከዘም እንዳይከለክለውም መሐላውን ፈራ እያዘነም አሰናበተው።

ከዚህ በኋላም ቅዱስ ያሬድ ወደ ቤተክርስቲያን ገብቶ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ ፈጽሞ የከበረሽና የተመሰገንሽ ከፍ ከፍም ያልሽ የብርሃን መውጫ የሕይወት ማዕረግ የሆንሽ የሚለውን ምስጋና እስከ መጨረሻው በተናገረ ጊዜ ክንድ ያህል ከምድር ከፍ ከፍ አለ።

ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሒዶ በጾም በጸሎት ተወስኖ ሥጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያ ፈጸመ። እግዚአብሔር ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጥቶታል።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን ያሬድ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ግንቦት)
ከበረሐውያን አንደበት.pdf
16.4 MB
ከበረሐውያን ሕይወትና አንደበት

ጥበብ ወምክር ዘአበው ቀደምት

++++++~+++++

#ጸሎት_ከበረሓውያን_አበው


ሁሉም ነገር ለፈቃድህ የሚገዛልህና የሚታዘዝልህ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፣ ያደረግሁትን ነገር ሁሉ ይቅር በለኝ፣ ኃጢአተኛ
የሆንኩትን እኔን ከአሁን በኋላ እንዳልበድል አድርገኝ፡፡ ጌታ ሆይ፣ የማይገባኝ መሆኔን
ባውቅም ከኃጢአቴ ሁሉ ልታነጻኝ ትችላለህ። ጌታ ሆይ፣ ሰው ፊትን እንደሚያይ፣ አንተ ግን ልብን እንደምታይ አውቃለሁ፡፡ ቅዱስ መንፈስህን ወደ ውስጤ ጥልቅ ላክልኝ፣ ነፍሴንና ሥጋዬን ይኖርበትና ገንዘቡ ያደርገው ዘንድ፡፡ ያለ አንተ ልድን አልችልም፤ በምትጠብቀኝ በአንተ ግን ማዳንህን እናፍቃለሁ፡፡ እናም አሁን አንተን ማዳንህን እለምንሃለሁ፡፡ የአንተን ጥበብ እሻለሁ፣ የሚረዳኝንና የሚጠብቀኝን ታላቁን ደግነትህንና ቸርነትህን እማጸናለሁ፡፡ ሁሉን ቻይ ታላቅ አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፣ በቀንና በሌሊት የአንተን መኖር አስታውስና አንተን ሁል ጊዜ በፊቴ አደርግህ ዘንድ ልቤን ምራልኝ፡፡

+ አሜን +


#ዲያቆን_ያረጋል_አበጋዝ
Repentance can comprise joy. The Holy Fathers have such a concept that encompasses both antipodes – sorrow and joy. It is when we cry over our sins, but in no way become desperate and discouraged, and our sorrow is dissolved by happiness, as we know that God loves us, no matter what and there is always hope and an opportunity, even for us the way we are… Our Church is full of such opportunities for a person to change and become a friend of God.
#archpriestSergiyBaranov
"በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር እንደ ክብሩ ባለ ጠግነት መጠን ይስጣችሁ፤ የእናንተ ሥርና መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ…" (ኤፌ. 3፥16)
***
ወልደ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ እስከ መስቀል በደረሰ የማዳን ግብሩ የገለጠው የሥላሴ ሰማያዊ ፍቅር በልቡናችን እስካልታተመ እና በፈቃዳችን ራሳችን ለወደደን ለእርሱ ትእዛዛት ተገዥዎች አድርገን እስካላቀረብን ድረስ ጌታችን ደጋግሞ የሚያወድሰው፣ ሐዋርያው ጳውሎስ ከአንደበቱ የማይለየው 'እምነት' ርቱዕ በሆነ መልኩ አለን ማለት አንችልም። እምነት ከተስፋ እና ፍቅር ያልተለየ ሕያው እና የሚለውጥ ነገር እንጂ ተራ እውቀት አይደለም። ስለ ክርስትና ብዙ እውቀት ስላለን እምነት አለን ማለት አይደለም። (እንዲያውም እውቀት ከጸጋ እግዚአብሔር የተራቆተ ከሆነ ትዕቢትን በማምጣት የእምነትን ብርሃን ሊያጨልም ይችላል!)
እምነት ማለት ማንነትን የሚለውጥ ኃይል ነው። እምነት ጸሎተ-ሃይማኖትን መድገም ብቻ አይደለም፤ በእግዚአብሔር ፍቅር ውስጥ መኖር እና ለጌትነቱ ራስን ማስገዛትም ነው እንጂ። ዲያቆኑ በቅዳሴ ሰዓት ጸሎተ ሃይማኖትን እንድንደግም ሲያዘን "በጥበበ እግዚአብሔር" ይሁን የሚለን ለዚህ ነው። እምነት በፍቅር ለፈጠረን፣ ላዳነን እና ልጆቹ ላደረገን አምላክ በፍቅር መታመንም ነው! ዛሬ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን መታሰቢያ አያደረግን ነው። እርሱ ከቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ሊቃውንት አንዱ ነው። በዘመናት ሁሉ እንዲህ እንደ ጸሐይ እንዲያበራ ያደረገው ግን በዋናነት ሊቅነቱ ሳይሆን ቅድስናው ነው፤ ሊቅነቱ የቅድስና እንጂ የመራቀቅ ውጤት አይደለምና።

Bereket Azmeraw
ከሲኖዶስ የምጠብቀው እና የምጠይቀው

አቤቱ ጌታዬ እና መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሳላውቅ በድፍረት አውቄ በትዕቢት ከመናገር እንድትጠብቀኝ እለምንሃለሁ። ጌታዬ መድኃኒቴ ኢይሱስ ክርስቶስ ሆይ አንተ በደምህ ከመሠርትሃት በኪዳንህም ካቆምካት፣ አካልህ ከሆነች፣ ብልት አድርጋ ከምትሰበስበን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ከሚያወጣ ድፍረት፣ ምን አገባኝም ከሚል ፍርኅት እንድትጠብቀኝ እኔ ከሁሉ የማንሰው ኃጢአተኛ ልጅህ እለምንሃለሁ። ጌታዬ ሆይ ከእንግዲህስ ወዳጆቼ እንጂ ባሪያዎቼ አልላችሁም ብለህ ባከበርሃቸው፣ ምሥጢራትህንም ሁሉ በገለጽህላቸው ፍጹማን ወዳጆችህ፣ አንተ ታማኝ መልካም ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ ብለህ በምታከብራቸው ትጉኃን አገልጋዮችህ፣ ለባሕርይህ ለማይስማማ ሞት ራስህን አሳልፈህ በሰጠህላቸው ንጹሐን ምእመናን በጎችህ ብለህ እንኳን የአባቶቼን የየትኛውንም ሰው ኅሊና ሊጎዳ ከሚችል ክፉ ሐሳብም ሆነ ንግግር ትጠበቀኝ ዘንድ እለምንሃለሁ። ጌታ ሆይ ከግብዝነት፣ ከአድርባይነት እና ከሚታወቅም ከማይታወቅም ጥፋት እንድትጠብቀን በጎውን እና እውነተኛውን ነገር ብቻም ለመናገር ከአንተ ውጭ እንኳን እኛ የበቁትም ቢሆኑ አይቻላቸውምና ስለቅዱሳንህ ሁሉ ይልቁንም የባሕርያችን መመኪያ የደኅንነታችን ዘውድ ስለምትሆን ንጽሕት እናትህ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ብለህ በመልካሙ መንገድ ብቻ ምራን፣ እኔንም ከዚህ መንገድ አታውጣኝ አሜን። ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ፤ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፤ አሜን።

አንዳንድ ሰዎች ስለሲኖዶስ በጻፍናቸው ተነሥተው ጉዳዩን ለመጠምዘዝ ከተቻለም መለያየት እና ጸብ በመፍጠር የሚፈልጉትን ለማሳካት እንደሚጥሩ ስለተሰማኝ፣ በቅንነት ሆነው ጥያቄያችንም የመብት ጥያቄ የመሰላቸው እና እራሳቸውንም የሆነ አካባቢ ተወካይ አድርገው የመብት ጥያቄ ጠያቂ እና አስተባባሪ ሆነው ስላየሁ የእኔ እና እኔንም የሚመስሉ ወንድሞቼ ጥያቄ ምን ዓይነት ጥያቄ እንደሆነ ስለቅዱስ ሲኖዶስ ያለኝን እምነት በማስቀደም በመግለጽ ጥያቄዬን በድጋሜ አቀርባለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ ፦

ቅዱስ ሲኖዶስ የእግዚአብሔር መንግሥት አስፋፊዎች የመላእክት ወንድሞች የሰማያዊ ዜጎች አንድነት እንጂ የከርስቲያኖች የየአካባቢው ተወካዮች የሚሰበስቡበት ምክር ቤት እንዳለሆነ በደንብ አዋቃለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ ከብዙ ቋንቋ ተናጋሪዎች የመጡ አባቶች ቢገኙበትም የየቋንቋቸው ወኪሎች ስብስብ እንዳልሆነም በደንብ አውቃለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ ከየአካባቢው ተወልደው አድገው በመጡ አባቶች የተመላ ቢሆንም የየተገኙበትና የየመጡበት አካባቢ ተወካዮች እና የወንበር ምድብ ቆጣሪዎች ስብስብ እንዳልሆነና ሊሆንም እንደማይችል፣ እንደማይገባውም በደንብ አውቃለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ በሰማይ ያለች የእግዚአብሔርን መንግሥት በምድር ሆነው ያገለግሉ ዘንድ የሚላኩ የእግዚአብሔር አምባሳደሮች ስብስብ እና ለላካቸው ለእግዚአብሔር መንግሥት ፍላጎት ብቻ የሚሠሩ በተፈጥሮ ከሰው ወገን ቢሆኑም በክህነት ምክንያት ከመላእክት ወገን የሆኑ እና እንደ መላእክትም ለሁሉም እኩል ቅርብ የሆኑ ሊሆኑም የሚገባቸው አባቶች ስብስብ እንደሆነ አምናለሁ። ከዚህም የተነሣ ከመካከላቸው ከላከው ከእግዚአብሔር እና ከሾመችው ከአካሉ ከቤተ ክርስቲያን ፈቃድ ወጥቶ የራሱን ፈቃድ የሚከተል፣ የምድራዊ መንግሥታትን ፈቃድ ለመፈጸም እና ለማስፈጸም የሚሠራ አካል ቢገኝ ከማኅበረ መላእክት ወገን ሳለ የራሱን ሌላ መንግሥት ማቋቋም ከፈለገ ከዲያብሎስ እና እርሱን እሺ በጄ ካሉት ከሠራዊቱ የሚመደብ እንደሆነ አምናለሁ፤ አውቃለሁም።

በሐዋርያት መዓርግ ተሹሞና እና ተሰይሞ በጉባኤያቸውም ተገኝቶ እውጭ ላሉት ምሥጢር የሚሰጥ፣ ከእነርሱም ጋር የጥቅም ውል ያለው ቢኖር አልደነቅም። እንዲህ ያለው ከሐዋርያት ሲኖዶስ እያለ ከአይሁድ ጋር የጥቅም ውል የተዋዋለ እና ከጉባኤያቸውም የተሰናበተውን ይሁዳን እንደሚመስል እና በእርሱ ምክንያትም ሌሎች እንደማይተቹ በደንብ ተምሬያለሁና።
ረቂቅ ባሕርይ በነበረው በሳጥናኤል ምትክ ከመሬት አፈር የተፈጥረው አዳም እንደተተካ፤ በይሁዳም ምትክ ማትያስ በሐዋርያት እጩነት ቀርቦ በዕጣ እንደገባ ከአባቶቼ ተምሬያለሁ፣ አዋቃለሁምና የሚወጣ ቢኖር አልደነግጥም አልረበሽምም። እንዲህ ባላው ሰው ምክን ያት ቤተ ክርስቲያን ስሟ እንደማይጎድፍ ክብሯ እንደማይቀንስ ሁሉን የሚያውቅ ጌታ አስቀድሞ አለማስገባት እየተቻለው ለይሁዳ እድሉን በመስጠት አስተምሮናልና።

ቅዱስ ሲኖዶስ ለእጃችሁ በትር አትያዙ የተባሉ ሐዋርያት ወራሽ እንጂ ሰይፍ፣ ጎራዴና እና ዱላ ይዘው ክርስቶስን ለመያዝ የመጡ፣ ዳዊት በመዝሙሩ አገቱኒ ከለባት ያላቸው ለምድራዊ ገዥዎች ፍላጎት የሚጮሁ የዚያ ዘመን አይሁድ ወራሽ እንዳልሆነ አውቃለሁ፣ አምናለሁም።

ቅዱስ ሲኖዶስ በዐመጻው ምክንያት መልአከ እግዚአብሔር በሰይፍ እጁን የቀጣውን ታውፋንያን ንስሐውን ተቀብሎ በተአምራት እጁን መልሶ ዐመጸኛውንም ወደ ትሕትና እና መታዘዝ የሚመልሱ የቅዱስ ጴጥሮስ ልጆች ስብስብ እንጂ እንደ አውሳብዮስ እና ጓደኞቹ የመንግሥታትን ጉልበት ተጠቅሞ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍሉ ሰዎች ስብስብ እንዳለሆነ አውቃለሁ፣ እንዲህ ሆኖ እንዲኖርም እጠብቃለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት እንደ ጠቢቡ ሰሎሞን ረቂቅ ፍርድ ፈርዶ ሕዝቡን የእግዚአብሔርን መጋቢነት የሲኖዶስን መንፈስንቅዱሳዊነት ሊያሳይ እንደሚተጋ እንጂ እንደ ኢሳይያስ የንጉሥ ድምፅ ፈርቶ እኔ ምን አገባኝ ብሎ ቤተ ክርስቲያንን ለዖዝያን ፍላጎት አሳልፎ በመስጠት ለምጻም የሆኑ ሰዎች ስብስብ እንዳልሆነ ፣ እንደማይሆን፣ ሊሆንም እንደማይገባው አምናለሁ፤ እጠብቃለሁም።

ቅዱስ ሲኖዶስ የእግዚአብሔር መንግሥት ለሁሉም ይዳረስ ዘንድ ተጭንቆና ተጠብቦ እንደ ጳውሎስ እስከ ዕልዋሪቆን እንደ በረተሎሜዎስም በላእተ ሰብእ ያሉበት ድረስ ሔዶ ለመስተማር የሚያስቡ አባቶች ስብስብ እንጂ እንደ አካባቢ የልማት ድርጅቶች በየአካባቢው ሕንፃ ለመሥራት ግንብ ለማቆም የሚሯሯጡ ዉሉደ ባቤል ደቂቀ ናምሩድ ስብስብ እንዳልሆነ አምናለሁ፣ ተስፋም አደርጋለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ እቄሣር ግቢ ቢገባ እዚያ ያሉትን ለውጦ እንደ ጳውሎስ ከቄሳር ቤት የሆኑት ሰላምታ ያቀርቡላችኋል የሚሉ ጥቡዓን ስብስብ እንጂ እንደ ዴማስ በከተማ ውበት በቤተ መንግሥት ግርማ ተሰልቦ አላማውን ለውጦ የሚኖር ከተሜዎች ስብስብ እንዳለሆነ እረዳለሁ።

ቅዱስ ሲኖዶስ እንደ ዲዮስቆሮስ ጥርሱ እስኪረግፍ ቢደበደብ እንደ አትናቴዎስ አምስት ጊዜ ቢሰደድ በትዕግሥት መከራውን ተቀብለው ቤተ ክርስቲያንን የሚያሻግሩ ፣ ዐለም ትቷችኋል ቢባሉ ልክ እነደ አትናቴዎስ እኔም ዐለምን አልፈልገውም የሚሉ ልበ ሙሉዎች ስብስብ እንጂ በቤተ መንግሥት ማዕድ እና ሺንገላ ልባቸው የሚማልል አባቶች ስብስብ እንዳልሆነ አውቃለሁ፣ እጠብቃለሁም።

ቅዱስ ሲኖዶስ እንደ ሲሞን ገንዘባቸውን ይዘው እናንተ የያዛችሁትን መዓርግ ልያዝ፣ ጓደኞቼ ከደረሱበት ልድረስ ብለው በእኔ ጊዜ ነው ወይ መመሪያ የሚወጣው እያሉ ዘመድ አዝማድ ስጦታ አስይዘው በመላክ፣ ውለታ ቆጥረው በማስታወስ የሚወተውቱ ሲሞናዊያንን ገንዘብህ ይጥፋ፣ ሀሳብህም አይፈጸም እያለ እነርሱን ትቶ ማትያስን በይሁዳ ፈንታ በተካበት መንገድ ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሚሆኑትን የሚሾም ወራሴ ጰጥሮስ ወሐዋርያት እንደሆነ አውቃለሁ አምናለሁም።
ቅዱስ ሲኖዶስ ሠራኤ ሕግ ወፈጻሜ ሕግ የሆነውን ጌታቸውን የተከተሉ፣ ሙጽአ ሕግ የሆነችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተልእኮ በሕገ እግዚአብሔር በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የሚያስፈጽሙ አባቶች ስብስብ እንደሆነ አምናለሁ፣ አውቃለሁም።

ለዚህም ነው በዘወትር ጸሎታችን ያለውን እንደ ሁሉም ክርስቲያኖች ሁሉ ዕለት ዕለት “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት” ብለው ያስተማሩኝን የማምነው፣ የምመሰክረው፣ የምጸልየውም።

ቤተ ክርስቲያን ከጉባኤያት ፣ ከምክር ቤቶች፣ ከስብሰባዎች ሁሉ በላይ የሆነችውም በተፈጥሮዋም፣ በአሠራሯም፣ በሒደቷም ከሁሉም በላይ በሆነው በጌታዋ በቤዛዋ በመድኃኒቷ እንዲህ ጸንታ የምትኖር ስለሆነች እና መሆንም ስላለባት እንደሆነ አውቃለሁ፣ አምናለሁም።

አንዳንድ ሰዎች ዘመን ሰጠን፣ ጉልበት አገኘን ብለው ይህን አስትተው እንደ ጎሣ ምክር ቤት፣ እንደ ፌዴሪሽን ምክር ቤት፣ እንደ ወንድማማቾች እድር፣ እንደ ተወላጆች ማኅበር፣ እንደ መሳሰሉት ቅርጽ እና መልክ ይዛ እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ መሆኗ ቀርቶ እንተ ታሕተ ኩሉ መንግሥታት፣ ፓርቲያት ፣ ብሔር ወጎሣ ወመማክርት እንድትሆን የሚፈልጉትን ሁሉ ነፍሴ አጥብቃ ትጸየፋለች፣ በሚቻለኝም ሁሉ እንደ አባቶቼ ይህን እቃወመዋለሁ። እንዲህ እንዲሆን የሚመኝ የሚሠራ ካለም ክርስቶስን ረዳቴ እና ጌታየ አድርጌ ቅዱስ ጴጥሮስ ሲሞንን እንደረገመው እረግመዋለሁ፣ ከኅብረቱ እንደለየውም ቢያንስ ራሴን ከእንዲህ ያለው እለያለሁ።

የእኔ ጥያቄ ለሲኖዶስ፦

እኔ ቅዱስ ሲኖዶስን የምጠይቀው የመብት ጥያቄ የለኝም። ቅዱስ ሲኖዶስ የታዛዦች የአገልጋዮች ጉባኤ እንጂ የባላ ሥልጣናት ምክር ቤት አይደለምና።
እኔ ቅዱስ ሲኖዶስን የምጠይቀው የአካባቢ፣ የጎሳ፣ የቋንቋ፣ ... የመሳሰሉት የውክልና ጥያቄም የለኝም። የሰማያውያን የመላእክት ወንድሞች የሆኑ ይህን ዐለም የካዱ አባቶች ጉባኤ ነውና። ቅዱስ ሲኖዶስን የምጠይቀው የእገሌ ይሾም የእገሌ አይሾም ጥያቄም የለኝም። ጥያቂዬ የሕግ እና የሥርዓት እንጂ የመብት እና የፖለቲካ አይደለምና።

ቅዱስ ሲኖዶስ አማኞች እንደ ፓርቲ ያቋቋሙት በፈለጉ ጊዜ ሕጉን ቀይረው ዘመን የወለደውን ንጉሥ የወደደውን አስመስለው የሚሠሩት ተራ ተቋም እንዳልሆነ ስማር ኖሪያለሁ፣ በዐለም ባሉት ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያን ሁሉም እንዲህ እንዳልሆነ አውቃለሁ፣ አያለሁምና ምንም ዐይነት የመብት ጥያቄ የለኝም። የመብት ጥያቄ ያለው ክርስቲያን ሆኖ ሊኖር የሚችልም የለምና።

የእኔ ጥያቄ መዳኑ በቤተ ክርስቲያን ሊፈጸምለት እንደሚሻ አንድ ኃጢአተኛ እና ደካማ ሲኖዶሴ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኔም ቤተ ክርስቲያን ሆና ማየት ብቻ ነው። ቤተ ክርስቲያንን መገለጫዋን ቅዱስ ሲኖዶስን በሌላው እንዳደረጉት ኢትዮጵያን ይምሰል በሚል ሽፋን ምክር ቤት ይምስል፣ የጎሳ ውክልና ምጥጥን ስሌት ይጠቀም የሚሉትን የምቃወመው ቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን እንድትሆን የልጅነት ድምፄን፣ ክርስቲያናዊ ግዴታዬን ለመወጣት ብቻ ነው።

መብት በሚል አደገኛ የፖለቲካ ቃል በር አስከፍቶ ሲኖዶስን የጎሳ ምክር ቤት፣ ቤተ ክርስቲያንም የድኅነት ቤት የፍጥረት ሁሉ መጠጊያ ሐመረ ኖኅ መሆኗን አስጥሎ ጥቅመ ሰናዖር፣ ሐይመተ ፈርዖን ሆና እንድትቆጠር እና ራሷ ከሆነው ከጌታ ከክርስቶስ ከብልቶቿ ከንጹሐን ምእመናን ለመለየት የሚደረገውን ጥረት የምቃወመው ሊቀርብ የሚገባው ጥያቄ የሕግ እና የሥርዓት እንጂ የመብት እና የፖለቲካ አይደለም ብዬ ስለማምን ነው።

ባለፈው ጊዜ በሻሸመኔ እና በተለያዩ አካባቢዎች የተገደሉ፣ አካላቸው የጎደለ፣ የታሠሩ የተገርፉ እና አሁንም የሚታሠሩ፣ ቤተ ክርስቲያናቸው እስካሁን የተዘጋባቸው፣ በአዲስ አበባ እንኳ ከሥራቸው ተፈናቅለው በደስታ የተቀበሉት ጥያቄያቸው የድኅነት የሕግ የሥርዓት ይከበር ጥያቄ ስለሆነ እንጂ የመብትማ ቢሆን እንዲህ አይሆንም ነበር። እነዚህ ሁሉ ጥያቄያቸው ቤተ ክርስቲያናቸውን ከወንበዴዎች፣ በጎቹንም ከተኩላ ጠብቃችሁ አድኑን የሚል ትሑት እና የመጨረሻ አነሥተኛ ጥያቄ ነው። የእኔም ጥያቄ ድኅነት ፈለገው የመጡ ምእመናን የጌታን ደም በቁርባን ሰጥተው በማዳን ፈንታ የምእመናን ደም ላፈሰሱ፣ በልተው ላልጠገቡ ለተራቡ ተኩላዎች ሰጥታችሁ አታስበሉን፣ ይልቁንም ድኅነታቸውን ሽተው ለሚያድኑን እረኞች አብቁን የሚል ብቻ ነው።

ይህ ካልሆነ ሲኖዶሱ ሲኖዶስ አይደለም ያሰኝና ብዙዎችን ሊያስወጣ፣ ምእመናን ሊከፋፍል፣ ... ሌላም ሌላም ችግር ሊያስከትል ስለሚችል የእነዚያ ሰዎች የድኅነት ጥያቄ የእኔም ልባዊ ጥያቄ ነው።

አባቶቼ የምታመልኩት የምታገለግሉት፣ እኔም ኃጢአተኛው እና ደካማው የማመልከው ላገለግለውም የምመኘው ሕያው እግዚአብሔር በሚያውቀው ጥያቄዬ አንድ እና አንድ ብቻ ነው።

ሲመተ ኤጲስ ቆጶሳትም ሆነ ማንኛውም ነገር በሕግ እና በሥርዓት ፣ ቀኖናውን መሠረት ባደረገ ለማንም በማያዘነብል፣ ለምእመናን ድኅነት እና ለቤተ ክርስቲያን እድገት እንጂ ለፓርቲዎችና እና ለፖለቲከኞች መሣሪያ ባልሆነ ግልጽ እና ሁሉም ሊያውቀው በሚችል በሲኖዶስ በጸደቀ የምርጫ መመሪያ እና ባለማድላት በተመሰከረላቸው አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ሲፈጸም ሕግ ሥርዓት ሲተገበር የማየት የልጅነት ጥያቄ ብቻ ነው።

በእኛ ዘመን ለምን ሕግ ይወጣል? ቀኖናስ ለምን ይጠበቃል የሚል ድምጽ ለሚሰሙት እንዴት ይረብሻል በእውነት። ይህ ድምፅ ይሰማል የሚል እምነት ባይኖረኝም መረበሹን አለመናገር ግን ድምፃቸውን እንደ አማራጭ ማስቆጠር መስሎ ስለተሰማኝ ከፊል የተስማማሁ ስለመሰለኝ ነው ያነሣሁት እንጂ ይደረጋል ብዬ አላስብም።

ጥያቄዬ ቅዱስ ሲኖዶስ በዓላማው በክብሩ ጸንቶ እንዲኖር ቅዱስ ጳውሎስ የሚያውኳችሁ ይቆረጡ እንዳለው ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ለመጣል እና ቤተ ክርስቲያንን ለማወክ ያሰፈሰፉ ሁሉ በሕግ ተቆርጠው እንዲወድቁ ብቻ ነው።

ጥያቄዬ ቤተ ክርስቲያንን ተሳታፊዎች የሚዘውሯት ተራ ምድራዊ ተቋም ሳትሆን ሰማያዊ መልኳን ይዛ እንድትጸና ሕግ ሥርዓቷ ይከበር የሚል ብቻ ነው።

ጥያቄዬ አሳሳቾች በሚፈጽሙት ችግር ምእመናን እንዳይረበሹ ለድኅነታቸውም መሰናክል እንዳይበዛ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ይከበር የሚል የልጅነት ጥያቄ ብቻ ነው።

ይህን መጥየቅ ካልቻልኩማ ምኑን ልጇ ሆንኩት፣ ስማረው የኖሩክትስ ምን ይጠቅመኛል። ለድኅነት ካልሆነስ ምን ይረዳኛል። ቤተ ክርስቲያኔ ቤተ ክርስቲያን ካልሆነችስ ምን ይጠቅመኛል። ፓርቲማ መች ቸገረኝ፣ ሕግ ጥሰት እና ድፈረትማ በዓለም ሁሉ ሞልቶ የለ። ከዚህ ሁሉ የጥፋት ባሕር ቀዝፋ የምታሽግር መርከቤን ሽንቁረው ውኃውን አስገብትው አብረን እናስጥምህ ሲሉኝ ዝም ካልኩኝማ ምኑን ሰው ሆንኩ? የተርሴስ ተጓዦች የተጨነቁትን ያህል ካልተጨነቅሁ ምን እጠቅማለሁ? እነሱ እንዳደረጉት ለመርከቢቱ የከበደውን ነገር ባላውቀው እንኳ ሸክም ካልቀነስኩ ምን ረባሁ? የተኛውን ካልቀሰቀስኩ ወደ አምላክህ ጩህ ካላልኩ ከእነዚያ ተጓዦች የማንስ እጅግ ምስኪን አልሆንምን? ስለዚህ የእኔ ጥያቄ የድኅነት እንጂ የመብት ጥያቄ አይደለም። የመብት ጠያቂዎችንም መስማት አልፈልግም። እርሱ ለፖለቲካ ፣ ለድርጅት፣ ለዚህ ዓለም ሰው ሰራሽ ተቋም እንጂ እግዚአብሔር ለመሠረታት፣ ፍጽምት እና አለነውር እንድትሆን ላደረጋት ቤተ ክርስቲያን የመብት ጥያቄ የለኝም፣ ሊኖረኝም አይችልም። የእኔ ጥያቄ እንተ ላዕኩሉን እንተ ታሕተ ኩሉ ሊያደርጉ የመጡትን በሕግ በሥርዓት ቆርጣችሁ፣ መርከባችን ከሚያናውጥ ማዕበል ቀዝፋችሁ አድኑን የሚል የድኅነት የሕግ የሥርዓት