Wazema Media / Radio
48.7K subscribers
189 photos
36 videos
7 files
931 links
Wazema Radio other contents are available either in our website/social media or FM radio stations in Ethiopia. www.wazemaradio.com
Download Telegram
Media is too big
VIEW IN TELEGRAM
በኢትዮጵያ የሕዝብ እና ቤት ቆጠራ በአስር አመት እንዲደረግ በሕገመንግስቱ ተቀምጧል።በ2009 ዓ.ም መደረግ የነበረበት ቆጠራ እስካሁን አልተደረግም።የሕዝብ ቆጠራ አለመደረጉ በፖለቲካ፣ማሕበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ያመጣል ሲሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና የምጣኔ ሀብት ተመራማሪዎች ይገልጻሉ። ዝርዝሩን ይዘናል። ያዳምጡን።
ለቸኮለ! ረቡዕ'ለት ሰኔ 6/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ በአማራ ክልል ባለፈው ዕሁድ በምዕራብ ጎጃም ዞን ደምበጫ ከተማ በተፈጠረ ግጭት ሁለት የመከላከያ ሠራዊት አባላትና ሦስት ሰላማዊ ሰዎች እንደተገደሉ የደምበጫ ወረዳ ፖሊስ መናገሩን ዶይቸቨለ ዘግቧል። አንድ የከተማዋ ሆስፒታል ሐኪም፣ በግጭቱ 18 ሰዎች መቁሰላቸውንና አራት ሰዎች ለከፍተኛ ሕክምና ወደ ባሕርዳር መላካቸውን መግለጣቸውን ዘገባው ጠቅሷል። ግጭቱ የተቀሰቀሰው፣ መከላከያ ሠራዊት ወደ ከተማዋ በድንገት መግባቱን ተከትሎ ወጣቶች መንገዶችን በመዝጋት ተቃውሟቸውን ሲገልጡ እንደኾነ የዓይን ምስክሮች እንደነገሩት ዘገባው አመልክቷል። በተመሳሳይ ግጭቱ ወደ ፍኖተ ሰላም ከተማ ተዛምቶ፣ ፖሊስ አንድ ተቃዋሚ ሰልፈኛን በጥይት እንደገደለና ከ10 በላይ ሰዎችን እንዳቆሰለ ነዋሪዎች ተናግረዋል ተብሏል። የዞኑ ኮምንኬሽን ቢሮ በበኩሉ፣ በጠቅላላው በግጭቱ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከሦስት አይበልጥም ማለቱ ተዘግቧል።

2፤ በትግራይ ክልል በተራዘመ የምግብ እጥረት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩን ሪፖርተር አስነብቧል። ከመቀሌ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሳምረ በተባለች ወረዳ ባለፉት አራት ወራት ብቻ 25 ሰዎች እንደሞቱ መረዳቱን የጠቀሰው ዘገባው፣ 670 ሕጻናት ደሞ በአስጊ ሁኔታ ላይ መኾናቸውን ዘገባው አመልክቷል። የወረዳው ጤና ጽሕፈት ቤት፣ በተለይ የምግብ ዕርዳታ ከተቋረጠ ከጥር ወር ወዲህ ችግሩ መባባሱን ገልጧል ተብሏል። 50 ሺህ ተፈናቃዮች በሚኖሩባት ተንቤን ከተማ፣ ችግሩ ከሳምረ ወረዳ የባሰ መኾኑንና 10 ሺህ ተፈናቃዮች በተጠለሉበት አንድ ትምህርት ቤት ብቻ 19 ሰዎች በቅርብ ጊዜያት ውስጥ በርሃብ እንደሞቱ ዘገባው አመልክቷል።

3፤ ትምህርት ሚንስቴር በትግራይ ክልል በሰሜኑ ጦርነት የመማር ማስተማር ሥራቸውን ያቋረጡት መቀሌ፣ አዲግራትና ራያ ዩኒቨርስቲዎች በሐምሌ ወር ተማሪዎችን መቀበል እንደሚጀምሩ መናገሩን የመንግሥት ዜና ወኪሎች ዘግበዋል። ሦስቱም ዩኒቨርስቲዎች በቀጣዩ ዓመት መስከረም መደበኛ መማር ማስተማር አገልግሎታቸውን እንደሚጀምሩ ሚንስቴሩ መግለጡን ዘገባዎቹ አመልክተዋል። ራያ ዩኒቨርስቲ ከአሁኑ ተማሪ መቀበል እንደጀመረ የገለጠው ሚንስቴሩ፣ በጦርነቱ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበት አክሱም ዩኒቨርስቲ ግን ላልተወሰነ ጊዜ ተዘግቶ ይቆያል ብሏል። ዩኒቨርሲቲዎቹ የሚቀበሉት፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በሌሎች ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ያልተመደቡ 20 ሺህ ተማሪዎቻቸውን እንደኾነ ሚንስቴሩ ጨምሮ አስታውቋል።

4፤ ብሄራዊ የተሃድሶ ኮሚሽን የቀድሞ ተዋጊዎችን ወደ መደበኛ ሕይወት ለመመለስ የየሚያስፈልገው ገንዘብ ከፍተኛ መኾኑ ትልቅ እንቅፋት እንደኾነበት የፌደራልና ክልል መንግሥርት ሰኞ'ለት በመልሶ ማቋቋሚያ መርሃ ግብር ላይ በአዲስ አበባ ባካሄዱት ውይይት ላይ መናገሩን "ኢትዮጵያ ኢንሳይደር" ዘግቧል። የተሃድሶ ኮሚሽኑ ኮሚሽነር ተሾመ ቶጋ በመድረሄኩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ለሂደቱ የሚያስፈልገውን ከፍተኛ የገንዘብ ወጪ ኮሚሽኑ መለየቱን ከመግለጽ ውጭ ትክክለኛውን መጠን እንዳልጠቀሱ ዘገባው አመልክቷል። ኾኖም በስምንት ክልሎች በመልሶ ማቋቋም መርሃ ግብሩ ለሚታቀፉ 250 ሺህ የቀድሞ ተዋጊዎች 550 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ ከኮሚሽኑ ምንጮች መስማቱን ዜና ምንጩ ጠቅሷል።

5፤ የሱዳን ጦር ሠራዊት ዋና አዛዥና የአገሪቱ መሪ ጀኔራል ቡርሃን ከባላንጣቸው የፈጥኖ ደራሹ ሠራዊት ዋና አዛዥ ጀኔራል ሞሐመድ ደጋሎ ጋር ፊት ለፊት የመገናኘት ፍላጎት እንደሌላቸው አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የአገሪቱ ባለሥልጣን መናገራቸውን የፈረንሳይ ዜና ወኪል ዘግቧል። ባለሥልጣኑ ይህን የተናገሩት፣ ኢጋድ ሁለቱ ባላንጣዎች ፊት ለፊት እንዲነጋገሩ ጥረት እንደሚያደርግ መግለጡን ተከትሎ ነው። ኢጋድ ለግጭቱ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲያፈላልጉ፣ የኬንያ፣ ኢትዮጵያ፣ ሱማሊያ እና ደቡብ ሱዳን መሪዎችን ወክሏል። በተያያዘ፣ አሜሪካ እስካኹን ያልተሳካው የሱዳን ኃይሎችን የማሸማገል ጥረት ምን አቅጣጫ መያዝ እንዳለበት በቀጣይ ቀናት እወስናለኹ ብላለች።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ4416 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ5304 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 65 ብር ከ4628 ሳንቲምና መሸጫው 66 ብር ከ7721 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ58 ከ8187 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ59 ብር ከ9951 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ ማለዳ! ሐሙስ ሰኔ 8/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የፌደራሉ ዓቃቤ ሕግ በ53 ተጠርጣሪዎች ላይ በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የሽብር ክስ መመስረቱን ፍትህ ሚንስቴር አስታውቋል። ተከሳሾቹ የተከከሰሱት፣ "ፖለቲካዊና ርዕዮተ ዓለማዊ ግባቸውን በኃይል ርምጃ ለመጫን"፣ "የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ለማስገደል"፣ አመጽ በማስነሳት ባጠቃላይ 217 ሰዎች እንዲገደሉ በማድረግና ተያያዥ ወንጀሎች እንደኾነ ተገልጧል። ተከሳሾቹ፣ "የአማራ ክልል ገዥ ፓርቲር በማስወገድ የአገሪቱን ማዕከላዊ ሥልጣን ለመቆጣጠር" አስበው እንደነበርም ሚንስትቴሩ ጠቅሷል። ከተከሳሾቹ መካከል፣ ዶ/ር ወንደወሰን አሠፋ፣ ዶ/ር መሠረት ቀለመወርቅ፣ መስከረም አበራ፣ ጋዜጠኛ ገነት አስማማውና ጋዜጠኛ ጎበዜ ሲሳይ እንደሚገኙበት ተገልጧል። ፍርድ ቤቱ ክሱን ለመስማት ለሰኔ 9 ቀጠሮ ይዟል ተብሏል።

2፤ ኢሰመጉ የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል በአዲስ አበባ ሰላምና ጸጥታ አሰፍናለኹ በማለት ሥልጣኑን ያላግባብ በመጠቀም ላይ ይገኛል ሲል አዲስ ባወጣው መግለጫ ከሷል። ግብረ ኃይሉ፣ በከተማዋ በዜጎች ላይ "ድንገተኛ የመንገድ ላይ ፍተሻ፣ እስር፣ ማዋከብና እንግልት" እየፈጸመ መኾኑን የጠቀሰው ኢሰመጉ፣ ድርጊቶቹ የሕግ ስነ ሥርዓቶችን ያልተከተሉና ሰብዓዊ መብቶችን የሚጥሱ እንደኾኑ ገልጧል። ኢሰመጉ፣ ሥልጣናቸውን ያላግባብ በሚጠቀሙ የግብረ ግብረ ኃይሉ አካላት ላይ የቁጥጥር ሥርዓት እንዲዘረጋ አሳስቧል። የጸጥታና ደኅንነት ግብረ ኃይል ባለፈው ሳምንት ባወጣው መግለጫ በአዲስ አበባ ተከታታይ ኦፕሬሽኖች እንደሚያካሂድ መግለጡ ይታወሳል።

3፤ ዓለማቀፉ የፍልሰት ድርጅት 17 ኢትዮጵያዊያን ፍልሰተኞችንና ስደተኞችን ሰኞ'ለት ከሊቢያ ወደ ሩዋንዳ ማጓጓዙን አስታውቋል። ድርጅቱ ከኢትዮጵያዊያኑ በተጨማሪ 117 የሌሎች አፍሪካ አገራት ዜጎች የኾኑ ፍልሰተኞችንና ስደተኞችን በዕለቱ ወደ ሩዋንዳ መላኩን ገልጧል። ድርጅቱ ፍልሰተኞቹን ወደ ሩዋንዳ ያጓጓዘው፣ ሊቢያ ውስጥ በአስቸጋሪ ኹኔታ ውስጥ የሚገኙ እፍሪካዊያን ፍልሰተኞችን ለመቀበል ከአራት ዓመታት በፊት ከተመድና አፍሪካ ኅብረት ጋር በደረሰችበት ስምምነት መሠረት ነው። ኢትዮጵያዊያን ፍልሰተኞች ሊቢያ ውስጥ በሕገወጥ ሰው አዘዋዋሪዎች ለባርነት መሸጥን ጨምሮ ለከፋ ስቃይ እንደሚዳረጉ ድርጅቱ በተደጋጋሚ ሲገልጥ ቆይቷል።

4፤ አሜሪካ አብዱላሂ ኦስማን ሞሐመድ የተባለውን የአልሸባብ አባል አድራሻ ለጠቆማት የአምስት ሚሊዮን ዶላር ጉርሻ እንደምትሰጥ ቃል ገብታለች። አሜሪካ በጥብቅ የምትፈልገው አብዱላሂ ሞሐመድ ወይም በቅጽል ስሙ "ኢንጂነር እስማኤል"፣ የአልሸባብ ከፍተኛ የፈንጂ ባለሙያ እንደኾነ ገልጣለች። ሞሐመድ፣ ለአልሸባብ መሪ አሕመድ ዲንዬ ወይም አቡ ኡቤይዳ ልዩ አማካሪ እንደኾነ አሜሪካ ጨምራ አስታውቃለች።

5፤ አራት ተጽዕኖ ፈጣሪ የአሜሪካ ሕግ አውጭ ምክር ቤቶች አባላት ደቡብ አፍሪካ የአሜሪካ የቀረጥ ነጻ ንግድ ዕድል (አጎዋ) ተጠቃሚ ኾና በመቀጠሏ ላይ ጥያቄ ማንሳታቸውን የአሜሪካ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። የምክር ቤቱ አባላት በደቡብ አፍሪካ ላይ ጥያቄ ያነሱት፣ ደቡብ አፍሪካ ሩሲያ በዩክሬን ላይ በፈጸመችው ወረራ ዙሪያ ድጋፏን ለሩሲያ ሰጥታለች በማለት እንደኾነ ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። ደቡብ አፍሪካ የጦርነቱ ላይ በምትከተለው ፖሊሲ የአሜሪካን ሕግ ሳትጥስ እንዳልቀረች ከገለጡት የሕግ አውጭ ምክር ቤቱ አባላት መካከል፣ የተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ ሃላፊ ማይክ ማክኮልና ሴናተር ክሪስ ኩንስ ይገኙበታል። [ዋዜማ]
Media is too big
VIEW IN TELEGRAM
በመንግስት ወደ አረብ ሃገራት የሚላኩ ሰራተኞች ...
ዝርዝሩን ይዘናል። ያዳምጡን።
#Ethiopia #wazemaradio #labor #skills
ለቸኮለ! ሐሙስ ሰኔ 8/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የገንዘብ እጥረት የገጠማቸው የግል ባንኮች የቁጠባ መጠናቸውን ለመጨመር በተወሰነ የጊዜ ገደብ ለከፍተኛ ገንዘብ አስቀማጭ ደንበኞች ከፍተኛ ወለድ እያቀረቡ መኾኑን ዋዜማ ተረድታለች። ባንኮች ለከፍተኛ ገንዘብ አስቀማጮች ከ12 እስከ 14 በመቶ ወለድ ይከፍሉ የነበረ ሲኾን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ከ16 እስከ 18 ነጥብ 5 በመቶ ወለድ መክፈል ጀምረዋል። አምስት ባንኮች በዚህ መልክ የተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰብ ላይ መጠመዳቸው ታውቋል። የገንዘብ እጥረቱ፣ ከአንድ ባንክ ወደ ሌላ ባንክ ገንዘብ ማዘዋወርን አስቸጋሪ አድርጎታል። ብዙ የግል ባንኮች በመጋቢት ወር የፈቀዷቸውን ብድሮች በገንዘብ እጥረት ሳቢያ እስካኹን እንዳለቀቁ የባንክ ሃላፊዎችና ተበዳሪ ባለሃብቶች ለዋዜማ ተናግረዋል።

2፤ የኢተ ንግድ ባንኮች ከአንድ ወይም ሁለት የግል ባንኮች በስተቀር የጥሬ ገንዘብ እጥረት የለባቸውም ሲሉ የብሄራዊ ባንክ ምክትል ገዥ ሰለሞን ደስታ ዛሬ በአዲስ አበባ በተካሄደ የምሥራቅ አፍሪካ የፋይናንስ ስብሰባ ላይ መናገራቸውን ሪፖርተር ዘግቧል። የባንኩ ምክትል ገዥ፣ አንድ በስም ያልጠቀሱት ባንክ የገንዘብ እጥረት እንደገጠመው መናገራቸውን የጠቀሰው ዘገባው፣ ባንኩ ችግሩን ለመፍታት የማኔጅመንት ማስተካከያ ማድረግ ያስፈልገዋል ማለታቸውን አመልክቷል። ኾኖም ምክትል ገዥው፣ በአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፉ አቅርቦትና ፍላጎት ተመጣጣኝ አለመኾኑ ከፍተኛ የገንዘብ ፍላጎት እንደፈጠረ መጠቆማቸውን ዜና ምንጩ ጠቅሷል።

3፤ የትግራይ ክልል የምግብ ዕርዳታ ዝርፊያን እንዲመረምር ያቋቋመው ኮሚቴ ሰብሳቢ ጀኔራል ፍስሃ ኪዳኑ በድርጊቱ ፌደራል መንግሥት፣ የክልሉ ባለሥልጣናትና የኤርትራ ሠራዊት እንደተሳተፉ በምርመራ መረጋገጡን ለክልሉ ቴሌቪዥን ተናግረዋል። ሰብሳቢው፣ የተፈናቃይ ካምፖች አስተባባሪዎችና የረድኤት ሠራተኞችም በድርጊቱ መሳተፋቸውን ገልጸዋል። መርማሪ ቡድኑ ከለያቸው 186 የወንጀሉ ተጠርጣሪዎች፣ ሰባቱ በቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል። ሰብሳቢው፣ ፌደራል መንግሥቱ፣ የትግራይ ባለሥልጣናትና የኤርትራ ኃይሎች በምርመራ በተረጋገጠው መሠረት በየፊናቸው ዘርፈውታል ያሉትን ስንዴ፣ የምግብ ዘይትና አተር ብዛት በአሃዝ አስደግፈው ዘርዝረዋል።

4፤ ሕወሃት የኢትዮጵያ መንግሥትና ዓለማቀፍ የረድኤት ድርጅቶች በትግራይ ክልል ለተቋረጠው የምግብ ዕርዳታ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጠይቋል። የሕወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ ትናንት ባካሄደው ስብሰባ ማጠቃለያ ላይ ባወጣው በዚኹ መግለጫ፣ በክልሉ የምግብ ዕርዳታ መቋረጡ በዕርዳታ ፈላጊው ሕዝብ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል ሲል አስጠንቅቋል። የዓለም ምግብ ፕሮግራምና የአሜሪካ ዓለማቀፍ ተራድዖ ድርጅት ለክልሉ ተረጅዎች የታሰበው የምግብ ዕርዳታ ላይ ዝርፊያ ተፈጽሟል በማለት የዕርዳታ ሥርጭት ካቆሙ አንድ ወር አልፏቸዋል።

5፤ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ መለስ ዓለም የሱዳን ተፋላሚ ወገኖች ተወካዮች በኢጋድ አሸማጋይነት አዲስ አበባ እንዲገናኙ እንቅስቃሴ እንደተጀመረ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ መናገራቸውን መግለጫውን የተከታተለው ዶይቸቨለ ዘግቧል። የኢጋድ አደራዳሪዎች፣ በ10 ቀናት ውስጥ ኹለቱን ወገኖች አዲስ አበባ ውስጥ የማገናኘት ዕቅድ መያዛቸውን መለስ መግለጣቸውን ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። ኢጋድ ለሱዳን ግጭት ሰላማዊ መፍትሄ እንዲያፈላልጉ የኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሱማሊያና ደቡብ ሱዳን መሪዎች የተካተቱበት አሸማጋይ ቡድን የሰየመ ሲኾን፣ ቡድኑን የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ እንዲመሩት መርጧል።

6፤ የሱዳኑ ግጭት ከተቀሰቀሰ ዛሬ ሦስተኛ ወሩን ይዟል። ትናንት የምዕራብ ዳርፉር አስተዳዳሪ ካሚስ አብዱላህ አባካር ለጊዜው ማንነታቸው ባልታወቁ ኃይሎች ተገድለዋል። የሱዳን ጦር ሠራዊት ዋና አዛዥና ጀኔራል ቡርሃን፣ ለግድያው ባላንጣቸው ጀኔራል ደጋሎ የሚመሩትን ፈጥኖ ደራሽ ሠራዊት ተጠያቂ ያደረገ ሲኾን፣ ፈጥኖ ደራሽ ሠራዊቱ ግን በግድያው እጁ እንደሌለበት ገልጦ ግድያውን አውግዟል። በግጭቱ እስካኹን 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሕዝብ የተፈናቀለ ሲኾን፣ 528 ሺህ ሕዝብ ወደ ጎረቤት አገራት እንደተሰደደ የዓለማቀፉ ፍልሰት ድርጅት መረጃ ያመለክታል።

7፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ4302 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ5188 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 65 ብር ከ2932 ሳንቲምና መሸጫው 66 ብር ከ5991 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ58 ከ5723 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ59 ብር ከ7437 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ ማለዳ! ዓርብ ሰኔ 9/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚንስቴር ቻይና ውስጥ የተገጣጠሙ የኤሌክትሪክ ቮልስዋገን ተሽከርካሪዎች ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ ለጊዜው እገዳ መጣሉን ሪፖርተር አስነብቧል። ሚንስቴሩ ጊዜያዊውን እገዳ የጣለው፣ የጀርመኑ ቮልስዋገን አምራች ኩባንያ ቻይና ለተገጣጠሙ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሕጋዊ ማረጋገጫ አለማስጠቱን በጀርመን ኢምባሲ በኩል ለሚንስቴሩ ማሳወቁን ተከትሎ እንደኾነ ዘገባው ጠቅሷል። መንግሥት ከውጭ በሚገቡ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ በቅርቡ ቀረጥ ማንሳቱ ይታወሳል።

2፤ ከአማራ ክልል የዋግኽምራ ዞን አስተዳደር በሰሜኑ ጦርነት ወቅት ከ18 ቀበሌዎች የተፈናቀሉ ተፈናቃዮችን እስካኹን ወደቀያቸው መመለስ እንዳልቻለ መናገሩን ቪኦኤ ዘግቧል። የአበርገሌና ጻግብጅ ወረዳዎች ተፈናቃዮች ወደቀያቸው መመለስ ያልቻሉት፣ የአገው ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ ታጣቂዎች በቀበሌዎቹ በመንቀሳቀስ ላይ በመኾናቸው እንደኾኑ ዘገባው ጠቅሷል። የአገው ሕዝቡ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ በበኩሉ፣ ታጣቂዎቹ ከአካባቢው እንደማይወጡ ገልጦ፣ የመንግሥትን ተፈናቃዮችን መልሶ የማቋቋም እንቅስቃሴ ግን አላስተጓጉልም ማለቱን ዜና ምንጩ ተአመልክቷል።

3፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እየተጠናቀቀ ባለው በጀት ዓመት የ20 በመቶ ገቢ ጭማሪ ማግኘቱን ትናንት ማስታወቁን የአገር ውስጥ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። አየር መንገዱ ዘንድሮ ያገኘው ገቢ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ሲኾን፣ ባለፈው ዓመት ገቢው ግን 5 ቢሊዮን ዶላር እንደነበር ተገልጧል። የአየር መንገዱ ሥራ አስፈጻሚ ኩባንያው ካቀደው ትርፍ የበለጠ ሊያገኝ እንደሚችል ጠቁመዋል ተብሏል። አየር መንገዱ፣ በተያዘው በጀት ዓመት 13 ነጥብ 7 ሚሊዮን መንገደኞችንና 723 ሺህ ቶን ካርጎ ማጓጓዙን እንደገለጠ ዘገባዎቹ አመልክተዋል። አየር መንገዱ ከኮሮና ወረርሽኝ በፊት ወደነበረበት አቅሙ መመለሱን ስራ አስፈፃሚው ከቀናት በፊት መግለጣቸው ይታወሳል።

4፤ ሱዳን የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ የኢጋድ አሸማጋይ ቡድን መሪ ኾነው መሰየማቸውን እንደማትቀበለው በውጭ ጉዳይ ሚንስቴሯ በኩል ባወጣችው መግለጫ አስታውቃለች። ሱዳን የፕሬዝዳንት ሩቶን ሚና እንደማትቀበል ያስታወቀችው፣ ኢጋድ የኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሱማሊያና ደቡብ ሱዳን መሪዎች የተካተቱበትን የሱዳን ግጭት አሸማጋይ የኢጋድ ቡድን እንዲመሩ በሰየማቸው ማግስት ነው። ሱዳን የኢጋድን ቡድን፣ እንደ ቀድሞው ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር መምራት እንዲቀጥሉ ለኢጋድ የወቅቱ ሊቀመንበር ለጅቡቲው ፕሬዝዳንት ኦማር ጌሌ አቋሟን ማሳወቋን ገልጣለች። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ዓርብ ሰኔ 9/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተቀሰቀሰው የኮሌራ ወረርሽኝ የ153 ሰዎች ሕይወት መቅጠፉን የተመድ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ አስታውቋል። ቢሮው፣ በኦሮሚያ፣ ደቡብ፣ ሱማሌና ሲዳማ ክልሎች በ85 ወረዳዎች ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች በወረርሽኙ እንደተጠቁ ገልጧል። የአኹኑ የኮሌራ ወረርሽኝ ለረጅም ጊዜ በመቆየት በአገሪቱ ታሪክ ከቀዳሚዎቹ ተርታ እንደሚመደብም ቢሮው ጨምሮ አመልክቷል። የአኹኑ የኮሌራ ወረርሽኝ የመጀመሪያ ታማሚ የተመዘገበው ባለፈው ዓመት ነሐሴ ላይ ነበር። የአቅም ማነስ፣ የገንዘብ እጥረት፣ የኮሌራ ክትባት ዓለማቀፍ ሥርጭት ሰንሰለት መናጋቱ ችግሩን እንዳባባሱት ተገልጧል።

2፤ መንግሥት በትግራይ ክልል በምግብ ዕርዳታ ላይ ለተፈጸመው ዘረፋ "ይቅርታ እንዲጠይቅ" ኢዜማ ዛሬ ባወጣው መግለጫ ጠይቋል። ፓርቲው፣ የዕርዳታ ምግብ ዝርፊያ ፈጻሚዎችን ተጠያቂ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ላይ "ገለልተኛ አካል" እንዲካተትበትና ሂደቱ በየጊዜው ለሕዝብ ይፋ እንዲደረግ አሳስቧል። ኢዜማ አያይዞም፣ "የዕርዳታ እህል መዝረፍና እንደ መከላከያ ያሉ ተቋማትን ስም በሚያጠለሽ ኹኔታ እንዲነሳ ማድረግ የመንግሥትን የሞራል ዝቅጠት ያሳያል" ብሏል። ሕወሃት የምግብ ዕርዳታን "ለታጣቂዎቹ አሳልፎ በመስጠት ፖለቲካዊ ጥቅሙን እንዲያስጠብቅ" ለማድረጉም ተጠያቂው ፌደራል መንግሥቱ እንደኾነ ኢዜማ ገልጧል።

3፤ ኢትዮጵያ ኢጋድ ለሱዳን ግጭት ሰላማዊ መፍትሄ እንዲያፈላልጉ በሰየማቸው አራት መሪዎች ቡድን ውስጥ መካተቷን ሱዳን ተቃውማ እንደነበር ለጉዳዩ ቅርብ ከኾኑ ዲፕሎማቶች ሰምቻለኹ ሲል ዘ ኢስት አፍሪካን ዘግቧል። የመሪዎቹ ጉባኤ ቀደም ሲል ካቋቋመው የመሪዎች ቡድን፣ ጅቡቲን አስወጥቶ ኢትዮጵያንና ሱማሊያን አካትቶ ነበር። ኾኖም ዘግየት ብሎ የወጣው የመሪዎቹ ጉባኤ የአቋም መግለጫ፣ ሱማሊያን በመተው ጅቡቲ በቡድኑ አባልነቷ እንደቀጥለች ጠቅሷል። ሱዳን ኢጋድ ከመግለጫው "ሽምግልና" የሚለውን ቃል እንዲያስወጣና የቡድኑ ሊቀመንበር አድርጎ በሰየማቸው የኬንያው ፕሬዝዳንት ምትክ የደቡብ ሱዳኑን ፕሬዝዳንት እንዲተካ ጠይቃለች። ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ፣ ኢጋድ በሱዳን ጥያቄዎች ዙሪያ የውሳኔ ለውጥ አላደረገም።

4፤ ደቡብ ሱዳን የነዳጅ ማምረቻ ግብዓቶችንና ቁሳቁሶችን በበኢትዮጵያ በኩል በጅቡቲና በሞምባሳ ወደቦች በኩል ለማስገባት መወሰኗን ሱዳን ትሪቡን ዘግቧል። ደቡብ ሱዳን ኬሚካሎችን ጨምሮ ቁልፍ የነዳጅ ምርት ግብዓቶችን የምታስገባው በፖርት ሱዳን በኩል ሲኾን፣ አኹን ግን የሱዳኑ ግጭት በግብዓት አቅርቦቷ ላይ መስተጓጎል እንደፈጠረባት ገልጣለች። አገሪቱ በቀን የምታመርተውን 170 ሺህ የሚጠጋ ድፍድፍ ነዳጅ ለዓለም ገበያ የምታቀርበው፣ ወደ ፖርት ሱዳን በተዘረጋ የነዳጅ ቧንቧ በኩል ነው።

5፤ ሰባት የአፍሪካ አገራት መሪዎች ለዩክሬንና ሩሲያ ጦርነት ሰላማዊ መፍትሄ ለማፈላለግ ዛሬ ዩክሬን ገብተዋል። ዛሬ ዩክሬን የገቡት፣ የደቡብ አፍሪካ፣ ኮንጎ፣ ግብጽ፣ ዛምቢያ፣ ኡጋንዳ፣ ሴኔጋልና ኬሞሮስ መሪዎች ናቸው። ቡድኑን የመሩት፣ የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎዛ ናቸው። መሪዎቹ የሰላም ሃሳባቸውን ለዩክሬን ባለሥልጣናት ካቀረቡና ከተወያዩ በኋላ፣ ወደ ሩሲያ ያቀናሉ ተብሏል።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ4863 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ5577 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 65 ብር ከ9787 ሳንቲምና መሸጫው 67 ብር ከ2983 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ59 ከ2724 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ60 ብር ከ4578 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ ማለዳ! ቅዳሜ ሰኔ 10/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ዞን ኪራሙ ወረዳ ታጣቂዎች ስምንት አርሶ አደሮችን መግደላቸውን ዶይቸቨለ ዘግቧል። ታጣቂዎቹ በርካታ የቁም እንስሳትን እንደዘረፉ የዓይን ምስክሮች መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። የወረዳው ኮምንኬሽን ጽሕፈት ቤት፣ በጥቃቱ ሌሎች 13 ሰዎች እንደቆሰሉ ገልጧል። የምሥራቅ ወለጋ ዞን በበኩሉ፣ የጥቃቱ ፈጻሚዎች "ጽንፈኛ ታጣቂዎች" መሆናቸውን መናገሩን ዘገባው አመልክቷል።

2፤ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ኢሰመኮ የሽብር ተከሳሾች ያቀረቡትን የሰብዓዊ መብት ጥሰት መርምሮ ውጤቱን በ15 ቀናት ውስጥ እንዲያቀርብ ትናንት ማዘዙን የአገር ውስጥ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ችሎቱ ተከሳሾቹ ዓቃቤ ሕግ በፍላሽ አያይዞ ያቀረበባቸውን ማስረጃ መመልከት እንዲችሉ ሁኔታዎች እንዲመቻቹላቸው አዟል ተብሏል። ሁለት ተከሳሾች ለኢሰመኮ ቃላቸውን ሲሰጡ ፖሊስ አብሮ መገኘቱ ጫና እንደፈጠረባቸው ለችሎቱ እንዳስረዱና ችሎቱም ድርጊቱ ስህተት መኾኑን እንደገለጠ ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። 51ዱ ተከሳሾቹ ከተከሰሱባቸው ወንጀሎች መካከል፣ የአማራ ክልልንና የፌደራል መንግሥቱን ሥልጣን በኃይል የመቆጣጠር ዓላማ ነበራቸው የሚል ይገኝበታል።

3፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የተወሰኑ የምክር ቤቱ አባላት ሌላ የጋራ ምክር ቤት እናቋቁማለን በማለት መዛታቸውን አጣጥሎታል። ምክር ቤቱ ባለፈው ሳምንት ያወጣውን መግለጫ የተቃወሙ ፓርቲዎች ብዛታቸው 32 እንደኾኑ ቢገልጡም፣ የምክር ቤቱ ዋና ጸሃፊ ራሄል ባፌ ግን ከ10 አይበልጡም በማለት ለዋዜማ ተናግረዋል። ፓርቲዎቹ ተቃውሞ ያሰሙት፣ ምክር ቤቱ በአገሪቱ ወቅታዊ ኹኔታ ዙሪያ ስላደረገው ስብሰባ ባወጣው መግለጫ ያካተታቸው አንዳንድ ነጥቦች አይወክሉንም በማለት ነው። ምክር ቤቱ፣ መግለጫው የአባል ፓርቲዎች አብላጫ ድምጽ ውጤት መኾኑን ለዋዜማ ገልጧል።

4፤ በምሥራቅ አፍሪካ ስደት ላይ ያተኮረ የኢጋድና የምሥራቅ አፍሪካ ኢኮኖሚ ማኅበረሰብ አባል አገራት ከፍተኛ የሚንስትሮች ስብሰባ ካምፓላ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ መካሄዱን ኢጋድ አስታውቋል። በስብሰባው ላይ ኢትዮጵያ በሰላም ሚንስትር ብናልፍ አንዷለም እንደተወከለች ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ገልጧል። ሚንስትር ብናልፍ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ለስደተኞች ዘላቂ መፍትሄ ለማስገኘት እያደረጋቸው ያሉትን እንቅስቃሴዎች ለስብሰባው አብራርተዋል ተብሏል። ለአራት ቀናት የተካሄደው ስብሰባ ዓላማ ለስደተኝነት ችግር ዘላቂ መፍትሄ ማስገኘት የሚይስችል ነው ያለውን የውሳኔ ሰነድ አጽድቋል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ቅዳሜ ሰኔ 10/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ለኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን በጻፈው ደብዳቤ በጦርነቱ ለተጎዱ የክልሉ ኢንቨስትመንቶች የካሳ ክፍያ፣ የዕዳና የታክስ ስረዛ እንዲደረግላቸው መጠየቁን ሪፖርተር ዘግቧል። ኮሚሽኑ የጥያቄዎቹን አፈጻጸም የሚገመግም የጋራ ኮሚቴ እንዲቋቋም ጭምር ጠይቋል ተብሏል። ኮሚሽኑ የውጭ ኢንቨስትመንት ኩባንያዎች በክልሉ ሙዓለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ፌደራል መንግሥቱ እንዲጋብዝ መጠየቁንም ዜና ምንጩ አመልክቷል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው፣ የክልሉ ኢንቨስትመንት ኩባንያዎች ብድር እንዲሰረዝላቸው ወይም የዕዳ መክፈያ ጊዜ እንዲራዘምላቸው ብሄራዊ ባንክን መጠየቃቸውን በዘገባው ተመልክቷል።

2፤ ምርጫ ቦርድ በቀጣዩ ሰኞ በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን በድጋሚ የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ያካሂዳል። በዞኑ የሚንቀሳቀሱት ተቃዋሚዎቹ የዎላይታ ብሄራዊ ንቅናቄ እና የዎላይታ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ግንባር ግን ቦርዱ ለሚያካሂደው የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ እውቅና አንሰጥም ማለታቸውን ዶይቸቨለ ዘግቧል። ሁለቱ ፓርቲዎች ሕዝበ ውሳኔውን የተቃወሙት፣ ሕዝበ ውሳኔው የዎላይታን ሕዝብ ራሱን የቻለ ክልል የመመስረት መብት የነፈገና ሕገ መንግሥታዊ ጥሰት ያለበት ሂደት ነው በማለት እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። ሁለቱ ፓርቲዎች ፌደሬሽን ምክር ቤት የዞኑን ሕዝብ ሕጋመንግሥታዊ መብት ጥሷል በማለት ቀደም ሲል በፍርድ ቤት ክስ መስርተዋል። የሰኞው ሕዝበ ውሳኔ፣ ጥር ላይ ወላይታን ጨምሮ ስድስት ዞኖችና አምስት ልዩ ወረዳዎች ያካሄዱት ሕዝበ ውሳኔ አካል ነው። ቦርዱ በወቅቱ የወላይታ ዞን ሕዝበ ውሳኔ ላይ የሕግ ጥሰት አግኝቼበታለኹ በማለት በድጋሚ እንዲካሄድ መወሰኑ ይታወሳል።

3፤ የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ የተመድ ጸጥታው ምክር ቤት በአገራቸው ላይ የጣለውን የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ሙሉ በሙሉ እንዲያነሳ በአካል እንዲጠይቁ በተያዘው ወር የምክር ቤቱ ሰብሳቢ የኾነችው ወዳጃቸው የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ጋብዛቸዋለች። ፕሬዝዳንቱ የጦር መሳሪያ ማዕቀቡ እንዲነሳ ለጸጥታው ምክር ቤት በሚያደርጉት ንግግር የሚጠይቁት፣ ምክር ቤት በሱማሊያ ወቅታዊ ጸጥታ ላይ በተያዘው ወር በሚያዘጋጀው ልዩ ስብሰባ ላይ እንደኾነ የሱማሊያ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ጸጥታው ምክር ቤት በአገሪቱ ላይ የጦር መሳሪያ ማዕቀብ የጣለው ከ30 ዓመት በፊት ቢኾንም፣ በተለያዩ ጊዜያት ማዕቀቡን በከፊል አንስቷል።

4፤ የአሜሪካው ፔንታጎን ትናንት ሌሊት በአንድ የአልሸባብ አመራሮች ስብሰባ ላይ በፈጸመው የድሮን ጥቃት በርካቶች መገደላቸውን የሱማሊያ መንግሥታዊ ዜና አውታሮች ዘግበዋል። የድሮን ጥቃቱ የተፈጸመው፣ ከኪሲማዩ ወደብ ወጣ ብሎ በጁባላንድ ራስ ገዝ በታችኛው ጁባ ግዛት እንደኾነ ዘገባዎቹ ገልጠዋል። አልሸባብ የፔንታጎን የድሮን ጥቃት ዒላማ የኾነው፣ በአፍሪካ የአሜሪካ ወታደራዊ ዕዝ (አፍሪኮም) ዋና አዛዥ ከሞቃዲሾና ከጁባላንድ ራስ ገዝ ባለሥልጣናት ጋር በአካል ተወያይተው በተመለሱና የሱማሊያ ጦር ከኢትዮጵያ፣ ኬንያና ጅቡቲ ጦር ጋር ጁባላንድ በሚንቀሳቀሰው አልሸባብ ላይ የተቀናጀ ዘመቻ ለማድረግ በዝግጅት ላይ ባሉበት ወቅት ላይ ነው።

5፤ አንድ የሱዳን ጦር ሠራዊት ከፍተኛ አዛዥ የባርቱም ነዋሪዎች የፈጥኖ ደራሹ ኃይሎች ከመሸጉባቸው ሠፈሮች እንዲወጡ መጠየቃቸውን ሱዳን ትሪቡን ዘግቧል። የጦሩ ከፍተኛ አዛዥና የሱዳን ሉዓላዊ ምክር ቤት ኣባል የኾኑት ጀኔራሉ ይህን ትዕዛዝ ያስተላለፉት፣ ጦር ሠራዊቱ በየሠፈሩና መኖሪያ ቤቶች የመሸጉትን የፈጥኖ ደራሽ ሠራዊት ኃይሎች በምድር ውጊያ ሊገጥም በመኾኑ እንደኾነ መግለጣቸውን ዘገባው ጠቅሷል። ጦር ሠራዊቱ እስካሁን ካርቱም ላይ ሲዋጋ የቆየው፣ በዋናነት በአውሮፕላና ድብደባና በከባድ መሳሪያ ነው። ጀኔራሉ፣ ውጊያው በአኹኑ ወቅት ከወታደሮች አልፎ ሲቪሉን ሕዝብና የፖለቲካ ኃይሎችን ጭምር ያካተተ ኾኗል ማለታቸውን ዘገባው ጠቅሷል።

6፤ የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ሴሪል ራማፎዛ የመሩት ለሩሲያና ዩክሬን ግጭት ሰላማዊ መፍትሄ አፈላላጊ የአፍሪካ መሪዎች ልዑካን ቡድን ዛሬ በሩሲያዋ ፒተርስበርግ ከተማ ገብቷል። ልዐካን ቡድኑ ወደ ሩሲያ ያቀናው፣ ከዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ዘለንስኪ ጋር ከተወያየ በኋላ ነው። የአፍሪካዊያኑ የመሪዎች ልዐካን ቡድን በሩሲያ ቆይታው፣ ግጭቱን በንግግር መፍታት በሚቻልበት ኹኔታ ዙሪያ ከሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ይወያያል። ልዑካን ቡድኑ፣ የሴኔጋል፣ የዲሞክራሲያዊት ኮንጎ፣ የኮሞሮስ፣ የዛምቢያና የግብጽ መሪዎችን ያካተተ ነው። [ዋዜማ[
ለቸኮለ ማለዳ! ሰኔ 12/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ ምርጫ ቦርድ ዛሬ በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን በድጋሚ የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ያካሂዳል። ቦርዱ ሕዝበ ውሳኔውን ዛሬ በድጋሚ የሚያካሂደው፣ ቦርዱ ባለፈው ጥር 29 በስድስት ዞኖችና አምስት ልዩ ወረዳዎች የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ማካሄዱ ይታወሳል። ኾኖም ቦርዱ የወላይታ ዞን ሕዝበ ውሳኔ ሂደት የሕግ ጥሰት ተገኝቶበታል በማለት ውጤቱን ሙሉ በሙሉ በመሰረዙ ነው ሕዝበ ውሳኔው በድጋሚ የሚካሄደው። ቦርዱ በዞኑ ለሚካሄደው ሕዝበ ውሳኔው 1 ሺህ 812 ድምጽ መስጫ ጣቢያዎች ማዘጋጀቱን ገልጧል።

2፤ የኢትዮጵያ የስደተኞች ጉዳዮች ቢሮ የዓለም ምግብ ፕሮግራምና የአሜሪካ ተራድዖ ድርጅት የምግብ ዕርዳታ በማቋረጣቸው በአገሪቱ የተጠለሉ ስደተኞች ከፍተኛ ችግር ላይ መውደቃቸውን መናገሩን ሪፖርተር ዘግቧል። በተለያዩ የስደተኛ መጠለያ ካምፖች የተጠለሉ 1 ሚሊዮን ስደተኞች የምግብ እርዳታ እንደተቋረጠባቸው የቢሮው ዋና ዳይሬክተር ተስፋሁን ጎበዛይ መግለጣቸውን ዘገባው ጠቅሷል። ከሱማላላንዱ ግጭት የተሰደዱ ከ91 ሺህ በላይ ስደተኞች በሱማሌ ክልል የተጠለሉ ሲኾን፣ ከሱዳን ግጭት የሸሹ ከ10 ሺህ በላይ ሱዳናዊያንና ኤርትራዊያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ ውስጥ እንደገቡ የተመድ መረጃዎች ያመለክታሉ።

3፤ የሱማሊያ መንግሥት በተያዘው ወር አፍሪካ ኅብረት ከአገሪቱ በከፊል የሚያስወጣቸውን ሰላም አስከባሪ ወታደሮች ለመተካት 20 ሺህ ወታደሮችን ማዘጋጀቱን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። አፍሪካ ኅብረት ከተያዘው ወር ጀምሮ በጥቂት ወራት ውስጥ ኹለት ሺህ ወታደሮችን ከሱማሊያ ለማስወጣት አቅዷል። ሱማሊያ የኅብረቱ ወታደሮች ሲወጡ የጸጥታ ክፍተቱን የሚሞሉት 20 ሺህ ወታደሮች፣ ኤርትራ፣ ኢትዮጵያ እና ኡጋንዳ ያሰለጠኗቸው እንደኾኑ ጠቅላይ ሚንስትር ሐምዛ ባሬ መናገራቸውን ዘገባዎች ጠቅሰዋል። ኅብረቱ በአውሮፓዊያን አቆጣጠር በ2024 ዓ፣ም ኹሉንም ሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ከአገሪቱ የማስወጣት እቅድ አለው።

4፤ ኹለቱ የሱዳን ተፋላሚ ወገኖች ሌላ የ72 ተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ደርሰዋል። አዲሱ የተኩስ አቁም ስምምነት ከዛሬ ንጋት 12 ሰዓት ጀምሮ ተግባራዊ ይኾናል። እንደካኹን ቀደሙ ኹሉ ተፋላሚዎቹ ወገኖች ከአኹኑ ተኩስ አቁም ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ያስቻሉት፣ የሳዑዲ ዓረቢያና አሜሪካ አደራዳሪዎች ናቸው። [ዋዜማ]
Media is too big
VIEW IN TELEGRAM
የቀጣዩ ዓመት በጀት ለምን አከራካሪ ሆነ?
ዝርዝሩን ይዘናል። ያዳምጡን።
#wazemaradio #federalbudget #2016 #Ethiopia
ለቸኮለ! ሰኔ 12/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ ምርጫ ቦርድ ዛሬ በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን በድጋሚ ሲያካሂድ የዋለውን የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ድምጽ አሰጣጥ የሰዓት ገደብ ከምሽቱ 12 ሰዓት ወደ 1 ሰዓት ማራዘሙን አስታውቋል። የዞኑ ድምጽ ሰጭዎች ድምጽ ሲሰጡ የዋሉት፣ ወላይታ ዞን ባለፈው ጥር 29 ቀን ሕዝበ ውሳኔ ካካሄዱት ሌሎች አምስት ዞኖችና አምስት ልዩ ወረዳዎች ጋር በጋራ አንድ ራሱን ያቻለ ክልል እንዲያቋቁም "እደግፋለኹ" ወይም "አልደግፍም" በሚሉ አማራጮች ላይ ነው። ቦርዱ ዛሬ በዞኑ በድጋሚ ሕዝበ ውሳኔ ያካሄደው፣ ጥር 29 በዞኑ የተካሄደው ሕዝበ ውሳኔ "መጠነ ሰፊ የሕግ ጥሰት" ታይቶበታል በማለት ውጤቱን በመሰረዙ ነው። ሌሎች አምስት ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ግን ከደቡብ ክልል ተነጥለው ራሱን የቻለ አዲስ ክልል ለማቋቋም በአብላጫ ድምጽ መወሰናቸው ይታወሳል።

2፤ ምርጫ ቦርድ ዛሬ በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን በድጋሚ ሲያካሂድ በዋለው የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ዙሪያ ምሽት 2:00 ሰዓት ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ አስታውቋል። ቦርዱ ከአዲስ አበባ 5 ሺህ 215 እንዲኹም ከወላይታ ዞን 3 ሺህ 845 የምርጫ አስፈጻሚዎችን ለሕዝበ ውሳኔው ማሠማራቱንና በዞኑ በጠቅላላው በ1 ሺህ 812 ጣቢያዎች ድምጽ ሰጪዎች ድምጽ ሲሰጡ እንደዋሉ በሌላ መግለጫው ገልጧል። ሦስት የአገር ውስጥ ሲቪክ ተቋማት 214 ታዛቢዎችን በዞኑ ማሠማራታቸውንም ቦርዱ ጠቅሷል። በርካታ ድምጽ ሰጪዎች ስድስት ወር ያልሞላው መታወቂያ ይዘው መገኘታቸውን የጠቀሰው ቦርዱ፣ መራጮቹ ሦስት የሰው ምስክሮችን አቅርበው ድምጽ እንዲሰጡ ተደርጓል ብሏል።

3፤ በአማራ ክልል ስር ራሱን "የወልቃይት ጠገዴ ዞን" በማለት ያዋቀረው አስተዳደር ምክትል ሊቀመንበር ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ከግጭት ማቆም ስምምነቱ በኋላ አስተዳደሩ ከወልቃይት ጠገዴ አካባቢ የትግራይ ተወላጆችን አላፈናቀለም በማለት ማስተባበላቸውን ቢቢሲ አማርኛ ዘግቧል። ከአካባቢው ለቀው የሚሄዱ የትግራይ ተወላጆች "በራሳቸው ፍቃድ ብቻ" ለቀው የሚሄዱ መኾናቸውን ደመቀ ጠቅሰው፣ በአካባቢው በርካታ የትግራይ ተወላጆች አኹንም እየኖሩ መኾኑን ማንም አካል በአካል መጥቶ ማረጋገጥ ይችላል ማለታቸውን ዘገባው አመልክቷል። ሂውማን ራይትስ ዎችና አምነስቲ ኢንተርናሽናል ኮሎኔል ደመቀ አኹንም የትግራይ ተወላጆችን ከአካባቢው በግዳጅ ያፈናቅላሉ በማለት በቅርቡ ላቀረቡባቸው ውንጀላ፣ ድርጅቶቹ በወልቃይት ጉዳይ ላይ "የሕወሃት ቃል አቀባይ እንጂ የመብት ተሟጋቾች" አልኾኑም በማለት መክሰሳቸውን ዘገባው ጨምሮ ጠቅሷል። የወልቃይት ጥያቄ ከሕዝበ ውሳኔ ይልቅ፣ ታሪክንና ሕግን መሠረት ያደረገ ሕጋዊ ምላሽ እንዲሰጠው እንደሚፈልጉ ደመቀ ተናግረዋል ተብሏል።

4፤ በኢትዮጵያ ለዘንድሮው የምርት ዘመን ከፍተኛ የአፈር ማዳበሪያ እጥረት በመከሰቱ በተለይ በአማራ ክልል አርሶ አደሮች የማዳበሪያ ጥያቄያቸውን በሰላማዊ ሰልፍ እስከማቅረብ ደርሰዋል። በአገሪቱ የአፈር ማዳበሪያ እጥረት መከሰቱን ያመነው ግብርና ሚንስቴር፣ ሰሞኑን ጅቡቲ ወደብ የደረሰ 7 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ እየተጓጓዘ መኾኑን መናገሩን መንግሥታዊ ዜና አውታሮች ዘግበዋል። ሰሞኑን ጅቡቲ የገባው የአፈር ማዳበሪያ፣ መንግሥት ዘንድሮው የምርት ዘመን ከውጭ ገበያ የገዛው 12 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ማዳበሪያ አካል እንደኾነ ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል።

5፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ4852 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ5749 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 66 ብር ከ6651 ሳንቲምና መሸጫው 67 ብር ከ9984 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ59 ከ6449 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ60 ብር ከ8378 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ማክሰኞ ሰኔ 13/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን ያካሄደው የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ትናንት ምሽት 1:00 ሰዓት ላይ ተጠናቋል። ቦርዱ፣ የድምጽ መስጫ ወረቀቶች በድምጽ መስጫ ጣቢያዎች ደረጃ ከምሽቱ ጀምሮ እየተቆጠሩ መኾኑን ገልጦ፣ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች ከዛሬ ጀምሮ በየጣቢያው እንደሚለጠፉ አስታውቋል። በዞን ደረጃ የሚገለጸውና ቦርዱ የሚያጸድቀው የሕዝበ ውሳኔ ውጤት የመጨረሻው ይኾናል።

2፤ የጠለምት፣ ማይጠብሪ እና ዲማ አካባቢ ነዋሪዎች ዕሁድ'ለት የአደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረጋቸውን ዶይቸቨለ ዘግቧል። ሰልፈኞቹ በሰልፉ ላይ ካንጸባረቋቸው ጥያቄዎች መካከል፣ "ማንነታችን ይከበር"፣ "ማንነታችን አማራ ነው" እና "መንግሥት ለመሠረትነው የአካባቢ አስተዳደር በጀት ይመድብልን" የሚሉ ጥያቄዎች እንደሚገኙበት ዘገባው አመልክቷል። ጠለምት፣ ማይጠብሪ እና ዲማ በትግራይና አማራ ክልሎች አዋሳኝ የሚገኙ ሲኾኑ፣ ከሰሜኑ ጦርነት በፊት በትግራይ ክልል ስር የነበሩና የማንነት ጥያቄ ሲያነሱ የቆዩ ሕዝቦች የሚኖሩባቸው ናቸው።

3፤ በኢትዮጵያ ብቸኛው የመኖሪያ ቤት ብድር አበዳሪ "ጎኽ ቤቶች" ባንክ መንግሥት የመኖሪያ ቤት ፈንድ እንዲያቋቋም ለብሄራዊ ባንክ ሃሳብ ማቅረቡን ካፒታል ጋዜጣ ዘግቧል። የፈንዱ ዓላማ፣ ለመኖሪያ ቤቶች ልማት የሚውል ገንዘብ ከተለያዩ ምንጮች ማሰባሰብ፣ ለአነስተኛ የፋይናንስ ተቋማት ወይም የቤት አልሚዎች ገንዘብ ማበደር እንደሚኾን የባንኩ ኃላፊዎች መናገራቸውን ዘገባው ጠቅሷል። ፈንዱ ልክ እንደ ጡረታ ፈንድ መንግሥት የሚያስተዳድረው ኾኖ መቋቋም እንደሚችልም ኃላፊዎቹ ገልጠዋል ተብሏል። ብሄራዊ ባንክ በዘርፉ ድጋፍ ማድረግ ለሚፈልጉ ባንኮች መመሪያ እንዲያወጣ ባንኩ ካኹን ቀደም ጠይቆ፣ ረቂቅ መመሪያው እየተዘጋጀ መኾኑን ዘገባው ጠቅሷል።

4፤ የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ የአገሪቱን ጦር ሠራዊት ዋና አዛዥ ጀኔራል የሱፍ ራጌን ከሃላፊነት ማንሳታቸውን የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። በተሰናባቹ የጦር ሠራዊቱ አዛዥ ምትክ፣ በመጀመሪያው የፕሬዝዳንቱ የሥልጣን ዘመን ወቅት የፕሬዝዳንታዊ ጥበቃ ጓድ አዛዥ የነበሩት ጀኔራል ኢብራሂም መሂያዲን እንደተሾሙ ዘገባዎቹ ጠቁመዋል። ፕሬዝዳንቱ የጦር ሠራዊቱን አዛዥ ያነሷቸው፣ ጦር ሠራዊቱ በአልሸባብ ላይ ለማካሄድ ያቀደው ኹለተኛው ዙር የማጥቃት ዘመቻ የሚጀመርበት ቀን መዘግየቱን ተከትሎ ነው። በኹለተኛው ዙር የማጥቃት ዘመቻ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያና ጅቡቲ ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ማክሰኞ ሰኔ 13/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ ትናንት በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን የተካሄደው የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ ጊዜያዊ ውጤት በድምጽ መስጫ ጣቢያዎች ደረጃ ሲገለጥ መዋሉን ምርጫ ቦርድ አስታውቋል። የቦርዱ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ፣ በሕዝበ ውሳኔው ድምጽ አሰጣጥ የተወሰኑ አነስተኛ ችግሮች ከማጋጠማቸው በስተቀር ሂደቱ በስኬት መጠናቀቁን ትናንት ምሽት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል። ሕዝበ ውሳኔው፣ ወላይታ ዞን ከጌዲዖ፣ ኮንሶ፣ ደቡብ ኦሞ፣ ጋሞና ጎፋ ዞኖች እና ከቡርጂ፣ አሌ፣ ባስኬቶ፣ ደራሼ እና አማሮ ልዩ ወረዳዎች ጋር በጋራ አንድ ክልል ያቋቁም እንደኾነ የሚወስን ይኾናል።

2፤ የዓለም ምግብ ድርጅት ተረጂዎች የሚመረጡበት የቁጥጥር ሥርዓት ባግባቡ ከተዘረጋ የምግብ ዕርዳታ ሥርጭቱን በሐምሌ ኹለተኛ አጋማሽ በትግራይና በስደተኛ ጣቢያዎች እንደገና ሊቀጥል እንደሚችል መናገሩን ሮይተርስ ዘግቧል። የድርጅቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቫለሪ ጓርኔሪ፣ በምግብ ዕርዳታ ተረጅዎች ምልመላ ላይ የአካባቢና የክልል ባለሥልጣናትን ተጽዕኖ መቀነስ እንደሚፈልግ መግለጣቸውን ዘገባው ጠቅሷል። ድርጅቱ በተለይ በትግራይ ክልል በዕርዳታ የቁጥጥር ሥርዓቱ ላይ ችግር እንደነበረበት የድርጅቱ መርማሪዎች ማረጋገጣቸውን ሃላፊዋ መጥቀሳቸውን የገለጠው ዘገባው፣ ድርጅቱ ለተጠቀሱት ተረጂዎች ዕርዳታውን ለመቀጠል ከባለሥልጣናት ዋስትና ማግኘቱንና በሌሎች አካባቢዎችም በፍጥነት ዕርዳታ የመጀመር ተስፋ እንዳለው ሃላፊዋ ተናግረዋል ተብሏል።

3፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቤት አከራዮች እስከ ሰኔ 30 ድረስ የቤት ኪራይ እንዳይጨምሩ ወይም ተከራዮችን በግዳጅ እንዳያስለቅቁ አሳስቧል። አስተዳደሩ ይህን ማሳሰቡያ ያወጣው፣ ከቤት ባለቤቶች ላይ የተጣለውን የጣሪያና ግድግዳ ግብር ሰበብ በማድረግ አከራዮች በተከራዮች ላይ የኪራይ ጭማሪ ማድረጋቸውን ስለደረሰበት መኾኑን ገልጧል።

4፤ የአፍሪካ ኅብረት የሰላም፣ ጸጥታና ፖለቲካ ጉዳዮች ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ ከኢትዮጵያ ጦር ሠራዊት ዋና ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ጋር በአካል ተገናኝተው መወያየታቸውን በትዊተር ገጻቸው አስታውቀዋል። ውይይቱ በኢትዮጵያ መንግሥት እና ሕወሃት መካከል በተደረሰው የፕሪቶሪያው የግጭት ማቆም ስምምነት ዙሪያ እንደነበር አምባሳደር ባንኮሌ ገልጸዋል። ባንኮሌ፣ በተለይ በትግራይ ክልል ግልጽ የኾነ የትጥቅ ማስፈታት፣ ተዋጊዎችን የመበተንና መልሶ የማዋሃድ መርሃ ግብር ለአፍሪካ ቀንድ የጋራ ደኅንነት ባለው አስፈላጊነት ላይ ከፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጋር መነጋገራቸውን ጨምረው ጠቅሰዋል።

5፤ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ በጋና አክራ ላይ በሚካሄደው የአፍሪካ የኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ ሳይገኙ ቀርተዋል። ዐቢይ፣ በስብሰባው ላይ ንግግር እንዲያደርጉ ከተጋበዙ የአሕጉሪቱ መሪዎች መካከል እንደኾኑ ሪፖርተር ዘግቧል። ዐቢይ የዚምባብዌና ሳዖቶሜ ፕሬዝዳንቶችና የቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዝዳንት በተካተቱበትና "ጠንካራ አሕጉራዊ የፋይናንስ ተቋማት ባላቸው ጠቀሜታ" ላይ በሚወያይ ቡድን ተመድበው እንደነበርም ዘገባው ጠቅሷል። ዐቢይ በጉባዔው ላይ ለምን እንዳልተገኙ የታወቀ ነገር የለም። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ምክትል ገዥ ፍቃዱ ደግፌና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት ግን፣ በግላቸው በጉባዔው ላይ መገኘታቸውን ዜና ምንጩ አመልክቷል። አሕጉራዊው ባንክ፣ ለአፍሪካ አገራት የወጪና ገቢ ንግድና ኢንቨስትመንት ብድር የሚሰጥ ሲኾን፣ ኢትዮጵያም የባንኩ ባለድርሻ ናት።

6፤ የአፍሪካ ኅብረት የሰላም ተልዕኮ ዛሬ ከሱማሊያ በመጀመሪያው ዙር ሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ማስወጣት መጀመሩን አስታውቋል። ዛሬ ሂርሸበሌ ግዛት የሚገኘውን ወታደራዊ ጦር ሠፈራቸውን ለአገሪቱ ጦር ሠራዊት ያስረከቡት፣ የቡሩንዲ ወታደሮች ናቸው። የዛሬው የቦታ ርክክብ፣ ኅብረቱ ከተያዘው ወር ጀምሮ ባጭር ጊዜ ውስጥ 2 ሺህ ወታደሮችን የመቀነስ ዕቅድ እክል ነው። የኅብረቱ ጦር እስከ በአውሮፓዊያኑ ታኅሳስ 2024 ዓ፣ም ሙሉ በሙሉ ከአገሪቱ የመውጣት ዕቅድ ይዟል። የቡሩንዲ ወታደሮች የሚወጡት፣ አልሸባብ በኅብረቱ ወታደሮች ላይ ድንገተኛ ጥቃቶቹን ባጠናከረበት ወቅት ላይ ነው።

7፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ4956 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ5855 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 66 ብር ከ6414 ሳንቲምና መሸጫው 67 ብር ከ9742 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ59 ከ5201 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ60 ብር ከ7105 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ረቡዕ ሰኔ 14/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ለሌሎች አገራት አየር መንገዶች ያልከፈለውን 95 ሚሊዮን ዶላር የተከማቸ ዕዳ እንዲከፍል ዓለማቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር በአዲስ አበባ እያካሄደው ባለው ስብሰባ ላይ ማሳሰቡን ሪፖርተር ዘግቧል። በመንግሥት ላይ የተከማቸው ዕዳ፣ ሌሎች አየር መንገዶች አዲስ አበባ ውስጥ በትኬት ሽያጭና ሌሎች አገልግሎቶች ያገኙት ብሄራዊ ባንክ በዓለማቀፍ ሕግ መሠረት ወደ ዶላር ቀይሮ ያልሰጣቸው ገቢያቸው ነው። መንግሥት ዕዳውን ለአየር መንገዶቹ ካልከፈለ፣ የአገሪቱ ዓለማቀፍ የአየር በረራ ግንኙነቶች ላይ ችግር ሊፈጥር እንደሚችል ማኅበሩ ማስጠንቀቁን ዘገባው ጠቅሷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበኩሉ፣ ኤርትራና ናይጀሪያን ጨምሮ የተወሰኑ አገራት ከትኬት ሽያጭና ሌሎች አገልግሎት ያገኘውን 180 ሚሊዮን ዶላር እንዳልለቀቁለት ገልጧል ተብሏል።

2፤ መንግሥት ለቀጣዩ በጀት ዓመት በራያና አካካቢው ለሚገኙ ሦስት ወረዳዎችና አንድ የከተማ አስተዳደር የመደበውን የፌደራል ድጎማ በጀት ለትግራይ ክልል እንዳይለቅ የሚጠይቅ የ145 ሺህ ሕዝብ ፊርማ ሰኞ'ለት ለፌደሬሽን ምክር ቤት መቅረቡን "ኢትዮጵያ ኢንሳይደር" ዘግቧል። ከአካባቢው ሕዝብ ፊርማውን አሰባስቦ ያቀረበው፣ የወሎ ራያ አማራ ማንነትና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ እንደኾነ ዘገባው አመልክቷል። ከሰሜኑ ጦርነት በፊት በሦስቱ ወረዳዎችና አንድ የከተማ አስተዳደር የሚኖረው ሕዝብ የማንነት ጥያቄ ሲያነሳ መቆየቱና ከጦርነቱ መቀስቀስ ጀምሮ ግን ሕዝቡ ራሱን በራሱ እያስተዳደረ መኾኑ በአቤቱታው ላይ ተገልጧል ተብሏል። ፌደሬሽን ምክር ቤትም አቤተታውን እመረምራለኹ ማለቱን ዘገባው ጠቅሷል።

3፤ ከፍትህ ሚንስቴር እና ፌደራል ፖሊስ የተውጣጣ ልዑካን ቡድን ኢትዮጵያዊያን ፍልሰተኞች በሕገወጥ ሰው አዘዋዋሪዎች አማካኝነት ወደ ጅቡቲ የሚገቡባቸውን መተላለፊያዎች ተዘዋውሮ መመልከቱን በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ብርሃኑ ጸጋዬ በትዊተር ገጻቸው ገልጸዋል። ልዑካን ቡድኑ፣ የጎበኛቸው የሕገወጥ ፍልሰተኞች መተላለፊያዎች፣ "ኦቦክ" እና በቀይ ባሕር በኩል ወደ መካከለኛው ምሥራቅ በጅልባ መውጫ የኾነው "ፋንታሂሮ" የተባለ ቦታ እንደኾኑ አምባሳደሩ ጠቅሰዋል። ልዑካን ቡድኑ፣ ከአካባቢው የጅቡቲ አስተዳዳሪዎችና ከዓለማቀፉ የፍልሰት ድርጅት ሃላፊዎች ጋር በኢትዮጵያዊያን ሕገወጥ ፍልሰት ዙሪያ መወያየቱም ተገልጧል።

4፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው አየር መንገዱቸው በኪሳራ የተነሳ ለበርካታ ዓመታት በረራ ያቋረጠውን የናይጀሪያ አየር መንገድ በቀጣዩ ዓመት ጥቅምት እንደገና ወደ በረራ ለመመለስ ብርቱ ጥረት እያደረገ መኾኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። አየር መንገዱ ባለፈው ወር የናይጀሪያ አየር መንገድን በረራ ለማስጀመር፣ አንድ የራሱን ቦይንግ አውሮፕላን ወደ ናይጀሪያ ልኮ ነበር። ኾኖም የናይጀሪያ ሲቪል አቬሽን በአዲስ መልክ ለተዋቀረው አየር መንገድ የበረራ ፍቃድ ባለመስጠቱና የናይጀሪያ የግል አየር መንገዶች የመሠረቱበት ክስ ባለመቋጨቱ፣ በረራው ሳይጀመር መቅረቱ ይታወሳል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ እንደገና በተዋቀረው የናይጀሪያ አየር መንገድ ውስጥ 49 በመቶ ድርሻ የያዘ ሲኾን፣ የናይጀሪያ መንግሥት 5 በመቶ እንዲኹም ናይጀሪያዊያን ባለሃብቶች ቀሪውን ድርሻ ይዘዋል።

5፤ የኢትዮጵያ ወታደሮች አልሸባብ ዛሬ በኢትዮጵያና ሱማሊያ የጋራ ወታደራዊ ጦር ሠፈር ላይ ባደረሰው የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት 5 ወታደሮች እንተገደሉና በርካቶች እንደቆሰሉ የሱማሊያ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። የቡድኑ አጥፍቶ ጠፊዎች በወታደራዊ ጦር ሠፈሩ ላይ ጥቃት የፈጸሙት፣ ከጦር ሠፈሩ 100 ሜትር ርቀት ላይ ፈንጂዎችን በማፈንዳት እንደነበር ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል። የፈንጂ ፍንዳታውን ተከትሎ በተደረገ የተኩስ ልውውጥ የቡድኑ ታጣቂዎች ተገድለዋል ተብሏል። አልሸባብ በድንበር አካባቢ ከሳምንት በፊት በኢትዮጵያ ወታደራዊ ጦር ሠፈር ላይ ተመሳሳይ ጥቃት ለማድረስ ሞክሮ ሳይሳካለት እንደቀረ ይታወሳል።

6፤ ዛሬ ጧት ዋሽንግተን የገቡት የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ ዛሬ ከአሜሪካ መከላከያ ሚንስትር ኦስቲን ሎይድ ጋር በኹለትዮሽ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚወያዩ ፔንታጎን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ከዚያም ወደ ኒውዮርክ በማቅናት፣ የተመድ ጸጥታው ምክር ቤት በሱማሊያ ወቅታዊ ጸጥታ ላይ በሚያካሂደው ልዩ ስብሰባ ላይ ንግግር እንደሚያደርጉና ጸጥታው ምክር ቤት በሱማሊያ ላይ የጣለውን የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ሙሉ በሙሉ እንዲያነሳ እንድንጠይቁ ይጠበቃል። ጸጥታው ምክር ቤት፣ በሱማሊያ ላይ ልዩ ስብሰባ እንዲቀመጥና ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ንግግር እንዲያደርጉ የጋበዘቻቸው የጸጽታው ምክር ቤት የወቅቱ ሊቀመንበር የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ናት።

7፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ5114 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ6016 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 66 ብር ከ4317 ሳንቲምና መሸጫው 67 ብር ከ7603 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ59 ከ5592 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ60 ብር ከ7504 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ ማለዳ! ሐሙስ ሰኔ 15/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የካርጎ ሎጅስቲክስ ክፍል "ወደ ሌላ አገር በሽያጭ ሊተላለፍ" ወይም "ለብድር መያዣነት ሊውል" እንደኾነ ተደርጎ በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች የሚሰራጨው መረጃ "ከእውነት የራቀ" እና "መሠረተ ቢስ" መኾኑን አስታውቋል። "ይህ ከእውነት የራቀ ወሬ የብሔራዊ አየር መንገዳችን ስም እና ገጽታ" ይጎዳል ያለው አየር መንገዱ፣ ወሬውን የሚያሰራጩ አካላት ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጠይቋል።

2፤ ኦብነግ አንድ የመከላከያ ሠራዊት አባል ማክሰኞ'ለት ቀብሪደሃር ከተማ ውስጥ በከፈተው ድንገተኛ ተኩስ ከተገደሉት ግለሰቦች መካከል ሦስቱ አባላቱ እንደኾኑ አስታውቋል። የሠራዊቱ አባል በተኩሱ አንድ የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ አመራር አባልን ጨምሮ አራት ሰዎችን ገድሎ ሌሎች ሁለት ሰዎችን ማቁሰሉን ግንባሩ ገልጧል። የሱማሌ ክልልና ፌደራል መንግሥታት ድርጊቱን አጣርተው ርምጃ እንዲወስዱ የጠየቀው ኦብነግ፣ በክልሉ በተደጋጋሚ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶች "አጠቃላይ አመጽ" ሊቀሰቅሱ ይችላሉ በማለት አስጠንቅቋል።

3፤ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ኩባንያ ሥራ አስፈጻሚ አንዋር ሶሳ በቀጣዩ ወር ከሃላፊነት እንደሚለቁ የኬንያው ሳፋሪኮም ኩባንያ አስታውቋል። አንዋር ሶሳ፣ ከሃላፊነታቸው የሚሰናበቱት በኢትዮጵያ የተመደቡበትን ሥራ በማጠናቀቃቸው እንደኾነ ኩባንያው ገልጧል። አንዋር ሶሳ ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ኩባንያ በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት መሠረቱን ከጣለ ጀምሮ በዋና ሥራ አስፈጻሚነት በማገልገል ላይ ናቸው።

4፤ የኤርትራ መንግሥት በኤርትራ የተመድ ልዩ ራፖርተር ያወጣውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሪፖርት አጣጥሏል። ኤርትራ፣ የልዩ ራፖርተሩ ሪፖርት መሠረታዊ ችግር ያለበት፣ የኤርትራ ጠላት ከኾኑ አገራት መረጃ የሰበሰበና ብሄራዊ የውትድርና አገልግሎት የግዳጅ ሥራ እንደኾነ አድርጎ በሃሰት የሚያጠለሽ ነው በማለት ከሳለች። የተመድ ሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት "ተቀባይነት የሌለውን" ሪፖርት ውድቅ እንዲያደርግና በሰብዓዊ መብቶች አጠባበቅ ዙሪያ መነጋገርን እንዲመርጥ ኤርትራ ጥሪ አድርጋለች። ልዩ ራፖርተሩ፣ ሰሞኑን ስብሰባ ላይ ላለው የተመድ ሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ሪፖርቱን አቅርቧል። [ዋዜማ]
ለቸኮለ! ሐሙስ ሰኔ 16/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች

1፤ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ደመቀ ኢትዮጵያ ዘንድሮ ሕዳሴ ግድብን ለአራተኛ ጊዜ በውሃ ለመሙላት ዝግጅት ላይ መኾኗን ዛሬ በድንበር ዘለል ወንዞች አጠቃቀም ዙሪያ ዛሬ በአዲስ አበባ በመከረው የቀጠናው ከፍተኛ የሚንስትሮች ስብሰባ ላይ መናገራቸውን ቪኦኤ ዘግቧል። ደመቀ፣ “ሕዳሴ ግድብ የአገራት የጋራ ሃብት የኾነውን ወንዝ ለብቻቸው መጠቀም የሚፈልጉ ኃይሎችን አሉታዊ ትርክት በመቋቋም፣ ወደ መጠናቀቂያው ምዕራፍ እየተቃረበ" መኾኑን ገልጸዋል ተብሏል። ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር በበኩሉ፣ ደመቀ "ሕዳሴ ግድብ የፍትሃዊና ምክንያታዊ ውሃ አጠቃቀም ተምሳሌት ነው" በማለት መናገራቸውን በትዊተር ገጹ ገልጧል። በስብሰባው ከኢትዮጵያ በተጨማሪ፣ ኡጋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ታንዛኒያ እና ዲሞክራሲያዊት ኮንጎ ተገኝተዋል።

2፤ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ ፈረንሳይ ባዘጋጀችው አዲስ ዓለማቀፍ የፋይናንስ ጉባዔ ላይ በመሳተፍ ላይ እንደኾኑ ጽሕፈት ቤታቸው አስታውቋል። ዐቢይ "የ21ኛው ክፍለ ዘመን ተግዳሮቶችን ለመቅረፍ የባለብዙ ወገን ልማት ባንኮችን ሞዴል ማሻሻል" በሚል ርዕስ በተዘጋጀ ውይይት ላይ መሳተፋቸው ተገልጧል። የጉባዔው ዓላማ፣ ዓለማቀፉን የፋይናንስ መዋቅር ማስተካከልና በታዳጊ አገራት የዕዳ አከፋፈል ላይ ስምምነት ላይ መድረስ ነው።

3፤ በኦሮሚያ ክልል ደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን የሰደን ሶዶ ወረዳ አስተዳዳሪ በቀለ ቃቻ ማክሰኞ'ለት ማንነታቸው ባልታወቀ ታጣቂዎች ተገድለው መገኘታቸውን ቢቢሲ አፋን ኦሮሞ ሬዲዮን በመጥቀስ የአገር ውስጥ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። አስተዳዳሪው ተገድለው የተገኙት፣ ቅዳሜ'ለት ከመኖሪያ ቤታቸው ታፍነው ከተወሰዱ በኋላ እንደኾነ ተገልጧል። የዞኑ አስተዳደር ለግድያው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊትን ተጠያቂ አድርጓል ተብሏል። ታጣቂዎቹ አስተዳዳሪውን ለመልቀቅ፣ 10 ሚሊዮን ብር ጠይቀው እንደነበር መስማቱን ዘገባው ጨምሮ ጠቅሷል።

4፤ የተመድ ጸጥታው ምክር ቤት ዛሬ በሱማሊያ ወቅታዊ ጸጥታ ዙሪያ በልዩ ስብሰባ ያደርጋል። ፕሬዝዳንት ሐሰን ሞሐመድ በምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ ንግግር ለማድረግ ኒውዮርክ ገብተዋል። ፕሬዝዳንት በንግግራቸው፣ አልሸባብ በአገራቸው ደኅንነት ላይ ስለደቀነው አደጋ ማብራሪያ እንደሚሰጡና ጸጥታው ምክር ቤት በሱማሊያ ላይ የጣለውን የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ሙሉ በሙሉ እንዲያነሳ እንደሚጠይቁ ይጠበቃል። የምክር ቤቱ ልዩ ስብሰባ እንዲጠራ ያደረገችው፣ የምክር ቤቱ የወቅቱ ሰብሳቢ የኾነችው የፕሬዝዳንቱ ወዳጅ አገር የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ናት። ፕሬዝዳንት ሞሐመድ፣ ትናንት ከአሜሪካ መከላከያ ሚንስትር ኦስቲን ሎይድ ጋር በሱማሊያና አሜሪካ የጸረ-አልሸባብ ትብብር ዙሪያ መክረዋል።

5፤ አሜሪካ በደቡብ ሱዳን ግጭት ወቅት የጾታዊ ጥቃት ወንጀሎችን አስፈጽመዋል ባለቻቸው ኹለት ግለሰቦች ላይ ማዕቀብ ጥላለች። ማዕቀቡ ኹለቱ ግለሰቦቹና ከግለሰቦቹ ጋር ግንኙነት ያላቸው አካላት በአሜሪካ ያላቸውን ንብረትና ገንዘብ ማንቀሳቀስ እንዳይችሉ የሚያግድ ነው። የአሜሪካ ግምጃ ቤት ማዕቀብ የጣለባቸው፣ ከደቡብ ሱዳን ጦር ሠራዊት ሜጀር ጀኔራል ጄምስ ናንዶ እና የተቃዋሚው የሬክ ማቻር አጋር የኾኑት የምዕራብ ኢኳቶሪያ ግዛት ገዥ አልፈርድ ፉቱዮ ናቸው። ኹለቱ ግለሰቦች ማዕቀብ የተጣለባቸው፣ በምዕራብ ኢኳቶሪያ ግዛት ሲቪሎችን በማሳፈንና በሴቶች ሏይ የአስገድዶ መድፈርና ሌሎች ከባድ ወንጀሎች እንዲፈጸሙ በማድረጋቸው እንደኾነ ግምጃ ቤቱ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። አሜሪካ፣ ጾታዊ ጥቃትን ብቻ በተናጥል ወስዳ በግለሰቦች ላይ ማዕቀብ ስትጥል በታሪኳ የአኹኑ የመጀመሪያዋ ነው።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 54 ብር ከ5223 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 55 ብር ከ6127 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ በድረገጹ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 66 ብር ከ2367 ሳንቲምና መሸጫው 67 ብር ከ5614 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ59 ከ5329 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ60 ብር ከ7236 ሳንቲም ሲሸጥ መዋሉን ባንኩ ገልጧል። [ዋዜማ]