ማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማዕከል ሕዝብ ግንኙነት
422 subscribers
1.08K photos
17 videos
1 file
84 links
Download Telegram
ጸሎተ ሐሙስ!

ጸሎተ ሐሙስ ጌታችን ምሥጢረ ቊርባንን ከምሥጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡

በወንጌልም እንደተጻፈው ፋሲካውን የሚያከብሩበት ቀን ሲደርስ ጌታ ኢየሱስም ጴጥሮስንና ዮሐንስን ሒዳችሁ ፋሲካን እንበላ ዘንድ አዘጋጁልን አላቸው፤ እነርሱም በየት እንድናዘጋጅልህ ትወዳለህ አሉት? ወደ ከተማ ገብታችሁ የውኃ ማድጋ የሚሸከም ስምዖን የተባለ ሰው ታገኛላችሁ፤ ወደ ገባበት ቤት እርሱን ተከተሉት፤ መምህር ከደቀ መዛሙርቶቼ ጋር ፋሲካ የሚያደርግበት አዳራሽ ወዴት ነው ይልሃል? በሉት እርሱ የተነጠፈውንና ታላቁን አዳራሽ ያሳያችኋል፤ በዚያም ፋሲካን አዘጋጁልን አላቸው፤ እነርሱም ወደ ተላኩበት ከተማ ገብተው አልዓዛርን የውኃ ማድጋ ተሸክሞ አገኙት፡፡ ጴጥሮስና ዮሐንስም ለስምዖን ጌታ በቤቱ ፋሲካን ሊያዘጋጅ መሻቱ እንደሆነ ነገሩት፤ እርሱም የፍጥረታት ጌታ በቤቱ ሊመጣ እንዳለ አስቦ ተደሰተ፤ ወደ ሚስቱ አክሮሲናም ሔዶ ይህ አልዓዛርን ከሞት ያስነሳ እኔንም በኃጢአቴ ይቅር ይለኛል፤ ያነጻኝ ዘንድ ከሐዋርያት ጋር በቤታችን ይመጣል አላት፤ አክሮሲናም እጅግ ተደሰተች፡፡
ጌታችንም ጊዜው ሲደርስ ከሐዋርያት ጋር በአንድነት መጣ፤ ስምዖንም ከቤቱ ወጥቶ ሮጦ ከጌታ እግር ሥር ሰገደ፤ ወደ ቤቱም ከሐዋርያት ጋር አስገባቸው፡፡ ይሁዳ ግን ይህን ሰዓት አልነበረም፤ ውጪ ከሻጭና ለዋጭ ጋር ገንዘብ ሲደራደር ነበር፤ ስምዖንም ለሚስቱ አክሮሲና ጌታና ሐዋርያት የሚገቡበት በእግራቸው የሚረግጡት ምንጣፍ እንድታነጥፍ አዘዛት፡፡ አክሮሲና ግን የጌታን መልክ አታውቀውም ነበር፤ ያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ጸሎት ሲጸልዩ አይታ ‹‹ከእናንተ ውስጥ መምህሩ ማነው›› አለቻቸው፤እነርሱም ዝም አሉ፤ መልከ መልካም ወደ ሆነውና የጌታ ወዳጅ ወደሆነው ዮሐንስ ተመልክታ እርሱ ይሆን አለች፤ ጴጥሮስ ግን ቀበል አድርጎ ‹‹ጌታ ኢየሱስ ከውስጠኛው ክፍል ቆሞ ይጸልያል፤ ጌታ እርሱ ነው›› አላት፡፡ እርሷም ገብታ ሰገደችለት፤ ይሁዳም በመጨረሻ ሳጥን ተሸክሞ መጣ፤ ጠባቂውንም እኔ የጌታ ደቀ መዝሙር ነኝ አለው፡፡ በር ጠባቂውም እለእስክንድሮስም የተነጠፈውን እስካጥፍ ጠብቅ ብሎ ዘለፈው፤ ልብሱንም አንስቶ አስገባው፤ /ግብረ ሕማማት ፭፻፹፫-፫፻፹፭/፡፡

በአንደኛው ሰዓት ሌሊት (ሐሙስ ለአርብ ምሽት)፤

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ልብሱን አኖረ፤ማበሻ ጨርቅም አንስቶ ወገቡን ታጠቀ፤ ይህችውም ሥራ የምታሠራና የምታስጌጥ ናት፤ ለዛሬው የመነኮሳት መታጠቂያ አብነት ናት፡፡ ለምሳሌ፡- ኢዮአብ ወደ ሰልፍ ሲገባ እየለበሳት ይገባ እንደነበረችው ያለ ዓይነት ነው፤ ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጥብ ዘንድ በጴጥሮስ ጀመረ፤ ጴጥሮስ ግን እኔ ባንተ ልታጠብ አይገባኝም አለ፤ ጌታችንም መልሶ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ እኔ እግርህን ካላጠብኩህ ከእኔ ጋር ዕድል ፈንታ የለህም›› (ዮሐ.፲፫፥፰)፡፡ ሌሎቹንም ሐዋርያት አጠባቸው፤ አሳልፎ የሚሰጠው ይሁዳንም እግሩን አጠበው፡፡ ጌታ አሳልፎ እንደሚሰጠው ሳያውቅ ቀርቶ አልነበረም፤ ፍቅርን ሲያስተምረውና ለንስሐ ጊዜ ሲሰጠው ነው እንጂ፤ እኛንም ለሚወደን ብቻ ሳይሆን ለሚጠላን እንኳን በጎ ማድረግ እንደሚገባ ሲያስተምረን ነው፡፡

ጌታችን ጾመና ጹሙ አለን፤ተጠመቀና ተጠመቁ አለን፤ ጸለየና ጸልዩ፤ ሰገደናም ስገዱ አለን፤ የሐዋርያትንም እግር አጥቦ እናንተም እንዲህ አድርጉ ብሎ መምህረ ትሕትናነቱን ገለጠልን፡፡ ዛሬም ከፓትርያርኩ ጀምሮ ሊቃነ ጳጳሳት፤ካህናት በየመአርጋቸው የምእመናኑን እግር በማጠብ የጌታን የትሕትና ሥራ ያስቡታል፡፡

ለሐዋርያት ትሕትናን ሲያስተምራቸው ጌታችን እግራቸውን እንደ አጠባቸው ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡ ከዚያም ዝ ውእቱ ሥጋየ ዝ ውእቱ ደምየ ብሎ ሥጋውንና ደሙን ሰጣቸው፤ ዛሬም የልጅነት ጥምቀት የሚቀበሉ ምእመናን በዚያኑ ዕለት ከክርስትና ቤት ወደ ቤተ መቅደስ ሔደው የጌታን ክቡር ሥጋና ደም ይቀበላሉ፤ መሠረቱም ጌታችን ለሐዋርያት ያደረገውን ተመርኩዞ ነው፡፡ ከፍ ከፍ ሊል የሚወድ ራሱን ዝቅ ያድርግ ብሎም አስተምሯቸዋል፤ አባ ጊዮርጊስ በመጽሐፈ ምሥጢር ጌታ ለጴጥሮስ ‹‹እኔ እግርህን ካላጠብኩህ ከእኔ ጋር ዕድል ፈንታ የለህም›› ያለውን ሲተረጉሙ ‹‹እኔ በአገልጋይ አምሳል እግርህ ካላጠብኩህ አንተም ከበታችህ ላሉት ራስህን ዝቅ ለማድረግ አትችልም፤ ራስህን ዝቅ ዝቅ ካላደረግህ አለቃ ልትሆን አትችልም›› ለማለት ነው ብለው ተርጉመውታል፡፡ ጌታችን ደግሞ አምላክ ፈጣሪ መምህር ሳለ ዝቅ ብሎ እንዳጠባቸው እነርሱም ክህነታቸውንና መምህርነታቸውን በትሕትና እንዲጀምሩ ሲያስተምራቸው ነው፡፡

በሁለተኛው ሰዓተ ሌሊት ምሽት፤

ጌታችን ሕብስቱን ባርኮ ለዐሥራ ሦስት ፈትቶ ሰጣቸው፤ ዐሥራ ሦስተኛውን እርሱ የሚቀበለው ነውና ነገር ግን የሚረባውና የሚጠቅመው አይደለም፤ ‹‹ዝ ውእቱ ሥጋየ ዝ ውእቱ ደምየ›› ብሎ ሕብስቱን ባርኮ ‹‹ይህ ሥጋዬ ነው እንካችሁ ብሉ ›› ወይኑንም ባርኮ ‹‹ይህ ደሜ ነው እንካችሁ ጠጡ›› ብሎ ሰጣቸው፡፡አስራ ሦስት አድርጎ መፈተቱ ሐዋርያትን እንዳይገርማቸው (እንዳያስፈራቸው) ነው፤ እራሱም ጥዒሞ አጥዐሞሙ/ቀምሶ አቀመሳቸው/ እንዲል አብነት ለመሆን፤ አንድም ነገ በመልዕተ መስቀል አስራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል እቀበላለሁ ሲል ነው፤ ጌታ ይህን ባያደርግ ኖሮ ዛሬ ካህኑ የጌታን ሥጋና ደም ሳይቀበል አቀብሎ ብቻ በሄደ ነበርና ለእነርሱ ለማስተማር ነው፡፡

ማዕዱንም እየበሉ ጌታችንም ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ! ከእናንተ መካከል አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል›› አላቸው፤ (ዮሐ.፲፫፥፳፩)፡፡ ሐዋርያት ሁሉ ደነገጡ! እርስ በርሳቸው ተያዩ፤‹‹እኔ እሆን? እኔ እሆን?›› ተባባሉ፤ ጴጥሮስም ዮሐንስን ጠጋ ብሎ ‹‹ማነው አሳልፎ የሚሰጠህ ብለህ ጌታን ጠይቀው›› አለው፤ወንጌላዊው ዮሐንስም ጌታን ጠጋ ብሎ ጠየቀው ጌታችንም ‹‹ከእኔ ጋር እጁን ከወጪቱ የሚያገባ እርሱ አሳልፎ ይሰጠኛል›› አለ፤ (ማቴ.፳፮፥፳፫/ሉቃ.፳፪፥፳፩)፡፡ ሐዋርያትም ‹‹ሁላችን ከወጪቱ የምንጠቅስ አይደለምን?›› ሲሉ ጌታችን ‹‹እኔ ከወጡ አጥቅሼ የምሰጠው ነው›› አላቸው፤ ያንጊዜ አጥቅሶ ለአስቆሮቱ ይሁዳ ሰጠው፤ ስለዚህ ወንጌላውያኑ ይህን ታሪክ ይዘው አንድ ሳለ በተለያየ አገላለጥ ገለጡልን፡፡

ይሁዳም እንደቸኮለ ሰው ይቅበዘበዝ ነበር፤እርሱም ጌታን እንዴት አሳልፎ እንደሚሰጠው በልቡ እያሰበ ነበር፡፡ ጌታም ወደ ይሁዳ ጠጋ ብሎ ‹‹ወዳጄ ይሁዳ ሆይ! ልትሠራው የምትሻው ሥራ ካለ ሒድ›› አለው፤ (ዮሐ.፲፫፥፳፯)፤ ይሁዳም ፈጥኖ ወጥቶ ወደ አይሁዳውያን ጌታን አሳልፎ ሊሰጥ ዋጋ ሊነጋገር ሔደ፡፡

ከሦስተኛው ሰዓተ ሌሊት እስከ አምስተኛይቱ ሰዓተ ሌሊት ድረስ

ለደቀ መዛሙርቱ ሲመክራቸው የመንፈስ ቅዱስንም መምጣት አብዝቶ ሲነግራቸው፤ ዓይኖቹን ወደ ሰማይ አቀና፤ እርሱ ከአባቱ ጋር አንድ እንደሆነም ነገራቸው፤ ለብቻው ፈቀቅ ብሎ ወዙ እንደ ደም እስኪፈስ እየሰገደ ጸለየ፤ወደ ደቀ መዛሙርቱ ተመለሰ፤ ተኝተው አገኛቸው፤ ቀሰቀሳቸው፤ ጴጥሮስንም አንድ ሰዓት ያህል እንኳን ከእኔ ጋር መትጋት አቃታችሁን? ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ አለው! (ሉቃ.፳፪፥፲፬-፵፮)፡፡

የጌታችን በአይሁድ መያዝ (ስድስተኛው ሰዓተ ሌሊት)

ጌታችንም ከአብ ጋር ስላለው አንድነትና ክብር ለሐዋርያት ካስተማራቸው በኋላ ‹‹ኢየሱስም ይህን ተናግሮ አትክልት ወደ አለበት ስፍራ ወደ ቄድሮስ ወንዝ ማዶ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወጣ፤ በዚያም ገባ›› (ዮሐ.፲፰፥፩)፡፡ወንዙን ተሻግሮ ያለውን ዛፍ አልፎ ወዳለው ዱር ገባ፡፡ ይሁዳም ይህችን ስፍራ ቀድሞ ጌታ ይመጣባት ስለነበር ያውቃት ነበርና ጭፍሮችንና የካህናት አለቆችን ፈሪሳውያን ሌሎች ፋና ጋሻ ጦርም የያዙትን አስከትሎ መጣ፡፡ ጌታችንም ‹‹ተነሡ እንሂድ! እነሆ አሳልፎ የሚሰጠኝ ቀርቧል›› አላቸው ወደ እነርሱ መጥቶ ቀረበ፤ ይሁዳም ወደርሱ ቀርቦ፤ ‹‹መምህር ሆይ ቸር ውለሃል፤ ሰላም ላንተ ይሁን›› ብሎ ሳመው፤ ይህ መሳም ለአይሁድ ጥቆማ ወይም ምልክት ነበር፡፡ ምክንያቱም የጌታ መልክና የወንጌላዊው የዮሐንስ መልክ ይመሳሰልባቸው ነበርና ሲለይላቸው ነው፤ ጌታችንም ‹‹በስኢምኑ ታገብኦ ለወልደ ዕጓለ እመሕያው፤ የሰውን ልጅ በመሳም አሳልፈህ ትሰጠዋለህን?›› አለው (ሉቃ.፳፪፥፵፰)፡፡
ይሁዳም ከጭፍሮቹ ጋር መጣ፤ ጌታ ኢየሱስንም ከበውት ወደ ሽማግሌዎችና የካህናት አለቃ ቀያፋ ወዳለበት ወሰዱት፤ ጴጥሮስ ግን ከሩቅ ሆኖ ይከተለው ነበር፤ የነገሩንም ፍጻሜ ያይ ዘንድ ከአንደኛው ቅጥር ግቢ ገብቶ ተቀመጠ፡፡ አይሁድም በክርስቶስ ላይ ሁለት የሐሰት ምስክሮችን አመጡ ‹‹ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስተኛው ቀን እሰራዋለሁ›› ብሏል ብለው ከሰሱት፤ ሊቀ ካህናቱም ተነስቶ ‹‹እንዲህ ሲያጣሉህ አትሰማምን›› አለው፡፡ ጌታችን ግን ምንም አልመለሰለትም፤ሊቀ ካህናቱም ‹‹ክርስቶስ ተብሎ የተነገረልህ የእግዚብሔር ልጅ አንተ እንደሆንክ ንገረኝ›› አለው፡፡ ጌታችንም ‹‹አንተ አልክ›› አለው፤ ያን ጌዜ ሊቀ ካህናቱ ተናዶ ልብሱን ቀደደው፤ራሱንም በብረት ዘንግ መቱት፤ የስቃዩ ጅማሬ ይህን ጊዜ ነበር፡፡
በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደረጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም እና የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ መምህር ዋሲሁን በላይ ዛሬ ሚያዚያ 24/2016 ዓ.ም ከመኖሪያ ቤታቸው በጸጥታ አካላት መወሰዳቸው ታውቋል።

የሁለቱ አገልጋዮች መኖሪያ ቤት መፈተሹም ተገልጿል።

በአሁኑ ሰዓት ሜክሲኮ ፌዴራል ፓሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ የሚገኙ ሲሆን የተያዙበት ምክንያት አልታወቀም።

ዝርዝር እንደደረሰን እናቀርባለን።
ዓርብ ስቅለት (የድኅነት ቀን)

እንኳን አደረሰን!

ዓርብ ስቅለት የዕዳ ደብዳቤያችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለመጨረሻ ጊዜ የተደመሰሰበት፤ ከአጋንንት አገዛዝ ነጻ የወጣንበት ዕለት ስለኾነ ‹የድኅነት ቀን› ይባላል፡፡ ጌታችን ከተያዘባት ሰዓት አንሥቶ አይሁድ ከቀያፋ ወደ ሐና፣ ከሐና ወደ ቀያፋ ሲያመላልሱት አደሩ፡፡ ሲነጋ ከቀያፋ ወደ ጲላጦስ አደባባይ አስረው ወሰዱት (ማቴ. ፳፯፥፩-፶፯)፡፡ አይሁድ ይህን አጥፍቶአል የሚሉት ነጥብ ሳይኖራቸው ነውና ጌታችንን ለፍርድ ያቀረቡት ጲላጦሰ እነርሱ ወደ ተሰባሰቡበት ቦታ ወጥቶ ‹‹ይህን ሰው ወደ እኔ ያመጣችሁበት በደል ምንድን ነው?›› ሲል በጠየቃቸው ጊዜ በቂ ምላሽ አላቀረቡም፡፡

‹‹ክፉ የሠራ ባይኾንስ ወደ አንተ ባላመጣነውም ነበር›› በሚል የሸፍጥ ቃል ሲያጕረመርሙ ጲላጦስ መልሶ ‹‹እኔ ምንም ጥፋት አላገኘሁበትም፤ እናንተወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት፤›› አላቸው፡፡ አይሁድም ኦሪት ‹‹ኢትቅትል ብእሴ ጻድቀ ወኀጥአ ኢታኅዩ፤ ጻድቅን ሰው አትግደል፤ ኀጥኡንም ከፍርድአታድን፤›› ትላለችና ‹‹እኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም፤›› ብለዋል (ዮሐ. ፲፰፥፳፰-፴፩)፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስ ‹‹በሕጋችን ጻድቀ ባሕርይክርስቶስን መግደል አይገባንም ሙሉ በሙሉ ጥፋተኞች ነን፤›› ሲያሰኛቸው ነው፡፡ በኋላም እርሱ ሞቶ ዓለም ይድን ዘንድ ወደ ምድር መጥቷልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ጥፋቱ ሞት ተፈረደበት፡፡ ስለዚህም ገርፈው ሰቀሉት፡፡

ጌታችን ሲሰቅልም የሚከተሉት ሰባት ተአምራት ተፈጽመዋል፤

፩. ፀሐይ ጨለመ፤

፪. ጨረቃ ደም ኾነ፤

፫. ከዋክብት ረገፉ፤

፬. የቤተ መቅደስ መጋረጃ ተቀደደ፤

፭. አለቶች ተፈረካከሱ፤

፮. መቃብራት ተከፈቱ፤
፯. ሙታን ተነሡ (ማቴ. ፳፯፥፶፩-፶፬)፡፡

ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ የሚከተሉትን ሰባት ዐበይት ቃላት አሰምቶ ተናግሯል፤

፩. ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ (አምላኪየ አምላኪየ ለምን ተውኸኝ?)››፤

፪. ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ››፤

፫. ‹‹አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው››፤

፬. እመቤታችንን ‹‹ሴትዮ ሆይ፣ እነሆ ልጅሽ››፤ ደቀ መዝሙሩንም ‹‹እናትህ እነኋት›› በማለት የቃል ኪዳን እናትነትና ልጅነት ማከናወኑ፤

፭. ‹‹አባት ሆይ በአንተ እጅ ነፍሴን አደራ እሰጣለሁ››

፮. ‹‹ተጠማሁ››፤

፯. ‹‹ዅሉ ተፈጸመ›› (ማቴ. ፳፯፥፵፭-፵፮፤ ሉቃ. ፳፫፥፵፫-፵፮፤ ዮሐ. ፲፱፥፲-፴)፡፡

ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ጨለማ ኾኖ ከቈየ በኋላ ከዘጠኝ እስከ ማታ እንደ ተለመደው ብርሃን ኾኖአል፡፡ ‹‹ወፍና ሠርክ ይበርህ ብርሃነ ፀሐይ›› እንዲል (ዘካ. ፲፬፥፯)፡፡ በዚህ ዕለት ሰባት መስተፃርራን (ጠበኞች) ታረቁ፤ ተስማሙ፡፡ እነዚህም፡- ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሕዝብና አሕዛብ፣ ነፍስና ሥጋ ናቸው (ኤፌ. ፪፥፲፤ ቈላ. ፩፥፳)፡፡ ጌታችን ጠዋት በሦስት ሰዓት ተገረፈ፤ በስድስት ሰዓት ተሰቀለ (ማቴ. ፳፯፥፩-፴፯፤ ሉቃ. ፳፫፥፩-፵፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፩)፡፡

በዘጠኝ ሰዓት ጌታችን በውኃው ተጠምቀን፣ ደሙን ተቀብለን የእግዚአብሔር ልጆች እንኾን ዘንድ ከቀኝ ጎድኑ ጥሩ ውኃ፣ ትኩስ ደም አፈሰሰልን (ዮሐ. ፲፱፥፴፬)፡፡ በዐሥራ አንድ ሰዓት ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል አውርደው ሽቶ እየረበረቡ በድርብ በፍታ ገንዘው ቀበሩት (ሉቃ. ፳፫፥፶-፶፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፴፰-፵፪)፡፡ ቅድስት ነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዳ ነፍሳትን ነጻ አወጣች (፩ኛ ጴጥ. ፫፥፲፱)፡፡ በዚህ ጊዜ በርሃነ መለኮቱ በሲኦል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር›› እየተባለ ይዘመራል፡፡ ከሆሣዕና አንሥቶ ተከልክሎ የነበረው ኑዛዜ ይናዘዛል፤ ጸሎተ ፍትሐት ይደረጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም እና የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ መ/ር ዋሲሁን በላይ በትናንትናው ዕለት ሚያዚያ 24 ቀን 2016 ዓ.ም በመንግሥት የጸጥታ አካላት ከመኖሪያ ቤታቸው ተወስደው ሜክሲኮ በሚገኘው የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ እንደሚገኙ አሳውቀን ነበር።


በዛሬው ዕለት ሚያዚያ 25 ቀን 2016 ዓ.ም ወደ ቤታቸው መመለሳቸውን እየገለጽን፣ በሂደቱ ጉዳዩን በመረዳት አፋጣኝ ምላሽ የሰጡንን የመንግሥት የጸጥታ አካላት እናመሰግናለን።

በተጨማሪም በትዕግሥት ስትከታተሉና በጸሎት ስታስቡ ለነበራችሁ አባቶች፣ ምእመናን እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት እያመሰገንን፣ በዓሉ የሰላምና የበረከት እንዲሆንላችሁ እንመኛለን።

ማኅበረ ቅዱሳን!
ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ

ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ ባሉት ዕለታት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ሳምንቱ እሑድ ድረስ የሚገኙት ዕለታትም ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ ይጠራሉ፤ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ዕለተ ሰኞ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች፡፡ ይህቺውም ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ናት (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

ማክሰኞ

ይህቺ ዕለት፣ ለሐዋርያው ቶማስ መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቶማስ› ተብላ ትጠራለች፡፡ የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በመጣ ጊዜ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ እርሱ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

ረቡዕ

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀናት በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ናት፡፡ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡
ኀሙስ

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡

ዐርብ

የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ተብላ ትጠራለች፡፡ በቤተ ክርስቲያን ደግሞ ጌታችን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጕልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ጊዜ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችንን ከዅሉ ቀድሞ ለማየት ለበቁት ሴቶች መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

እሑድ ሰንበት

በዋናው ትንሣኤ ሳምንት የምትመጣዋ ዕለተ እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብላ ትዘከራለች፡፡ ከላይ እንደ ተጠቀሰው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት ‹‹በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግን ‹ሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም›› አለ፡፡

ስለዚህም የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው የወዳጆቹን የልብ ዐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡ ቶማስንም ‹‹ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤›› ብሎ አሳየው፡፡

እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ ‹‹ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ›› የክርስቶስን ትንሣኤ አመነ፡፡ የሳምንቷ ዕለተ ሰንበት፣ የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡