ፍሬ ሀይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት (mana dilbata firee amentaa)
188 subscribers
226 photos
8 videos
19 files
37 links
በዚህ መንፈሳዊ ቻናል የኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ሐይማኖታችንን እንድናውቅ የሚረዱ :-

፨ ከተለያዩ መንፈሳዊ ቻናሎች የምናገኛቸውን መረጃዎች አናጋራቹሃለን።

፨ ጥያቄ አና መልስ አንጠያየቃለን።


፨ መንፈሳዊ መፃህፍትን በ አማርኛ ፣ Afaan oromoo አና English language እናካፍላቹሃለን።

ሐሳብ አስተያየት ካላቹ @ye_gebriel ላይ አሳውቁን።
Download Telegram
"በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጣ" (ሽራፊ ሃሳብ 1 ከኒቆዲሞስ ምንባብ)  ኒቆዲሞስ በውድቅት ሌሊት ወደ ጌታችን መጣ። ሌሊት እንግዲህ በቂ ብርሃን የሌለበት ፣ እንቅፋት የሚበዛበት ፣ ጭልም የሚልበት ፣ ግራ ቀኝ ቢያዩ ሰው የሚታጣበት ፣ ማጅራት ከሚመቱ ወንበዴዎች በቀር በመንገድ ሌላ ሰው የማያጋጥምበት ፣ ብርድና ቆፈን ሰውነትን የሚያስጨንቅበት ሰዓት ነው። ይህ የአይሁድ መምህር በሌሊት የመጣበት ምክንያቱ ብዙ ሲሆን ለእምነት ማነስ ማሳያ የሚሆን ሰው ነው።  

ዛሬ ደግሞ ለአፍታ ኒቆዲሞስን "በሌሊት ወደ ኢየሱስ በመምጣቱ" በጥቂቱ እናመስግነው።  ብዙ እግሮች ወደ ኃጢአት በሚሮጡባት ሌሊት ወደ ክርስቶስ የሮጠውን ይህንን ሰው እስቲ እናድንቀው!  ይህንን የሌሊት ግርማ ሳይበግረው ወደ ኢየሱስ የተጓዘ የጨለማ ተጓዥ ፣ ይህንን ሰዓታት ቋሚ ፣ ይህንን ማሕሌት ቋሚ በጥቂቱ ብናመሰግነው ምን አለ? ከጌታ ፊት ቆሞ ቅኔ የተመራውን ፣ ስለ ልደት እየተናገረ ስለ ጥምቀት የሚያመሰጥረውን የፈጣሪን ቅኔ ተቀብሎ ሊያዜም ከጀመረ በኋላ መቀበል ሲያቅተው ጌታችን "አንተ የአይሁድ መምህር ስትሆን ይህንን አታውቅምን?" ብሎ የገሠፀውን ኒቆዲሞስን እስቲ ዛሬ በበጎነቱ አርኣያ እናድርገው።  

በሕይወታችን ውስጥ የተስፋ ብርሃን ጭልም ባለብን ጊዜ ፣ እንቅፋት በበዛብን ወቅት ፣ ግራ ቀኝ አይተን ሰው ባጣንበትና ብቸኝነት በዋጠን ሰዓት ፣ ክፉ ከማድረግ በማይመለሱ ጨካኞች በተከበብን ሰዓት እኛስ ወዴት እንሔዳለን?  

ሕይወቱ "ሌሊት" የሆነበት ሰው ሁሉ  ወደ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ቢሔድ እንደሚሻለው ከኒቆዲሞስ የተሻለ ምሳሌ የለም። ሕይወቱ የጨለመ ባይሆን እንኳን ልቡ የጨለመበት ፣ በኃጢአት ጠል የጠቆረ ፣ በበደል ብርድ ቆፈን እጅ እግሩ የታሰረ ከእኛ መካከል ስንት አለ?  

እመነኝ ፣ ተስፋ ቆርጠህ ቁጭ ብለህ እስከሚነጋልህ ብትጠብቅ አይነጋም። ይልቅ ተነሥና "በሌሊት ወደ ክርስቶስ ሒድ" እርሱ ተስፋ ለቆረጠው ማንነትህ ዳግመኛ መወለድ እንዳለም ይነግርልሃል። ኒቆዲሞስ ጌታችንን ሊያየው ሔዶ  ራሱ ታይቶ እንደመጣ አንተም ወደ እርሱ የቀረብህ እንደሆነ ራስህን ታያለህ።  

በ"ሌሊት" ውስጥ ለሚኖር ሰው ነግቶ ፀሐይ ትወጣልኛለች ብሎ ከሚጠባበቅ ይልቅ በሌሊት እንደ ኒቆዲሞስ ተነሥቶ ወደ ጽድቅ ፀሐይ ወደ ክርስቶስ ቢሔድ ይሻለዋል።  ወደ እርሱ ለሚሔድ ሰው ሌሊቱ ይነጋል ፣ ክርስቶስ ያለበት ሌሊት ከቀን ይልቅ ብሩሕ ነው ፣ እውነተኛው ብርሃን ያለበት ጨለማም ጨለማ አይደለም። ስለ እርሱ "ጨለማም በአንተ ዘንድ አይጨልምም" ተብሎ ተጽፎአልና። 

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መጋቢት 16 2010 
ኒቆዲሞስ
ናይሮቢ ፣ ኬንያ

#share
@diyakonhenokhaile
+ ለምን ሔዋን ላይ ብቻ ? +

ሔዋን ላይ ወቀሳው ይበረታል ብቻ እንጂ አዳምም ከደሙ ንጹሕ አልነበረም፡፡ ነገሩን አስተውለን ያየነው እንደሆን አዳምንም ከሔዋን በላይ የሚያስወቅስ ብዙ ነገር እናገኛለን፡፡ እግዚአብሔር አዳምን ‘አትብላ ካልኩህ ዛፍ በላህን?’ ብሎ ሲጠይቀው የሠጠው መልስ ‘ረዳት ትሁንህ ብለህ የሠጠኸኝ ሴት ከዛፉ ሠጠችኝና በላሁ’ ነበረ፡፡

ከጥበብና ማስተዋል ጋር የተፈጠረው ታላቁ ፍጥረት አዳም እንደ አላዋቂ ሕፃን ‘ሠጠችኝና በላሁ’ ሲል ተመልከቱ!

አዳም ሆይ የተሠጠህን ሁሉ እንዴት ትበላለህ? ርቦህ ነበረ እንዳንል ከውድቀት በፊት እንደማትራብ እናውቃለን፡፡ በዕድሜ ከአንተ የምታንስህ ፣ ከጎንህ በመገኘትዋ ልጅህ ከምትባለው ሔዋን የተሻለ ልታስተውል አይገባህም ነበርን? ‘አልቅሳ ስለለመነችኝ ፣ ስላባበለችኝ በላሁ’ እንኳን አላልህም፡፡ ‘ሠጠችኝና በላሁ’ ማለት ከአዋቂ የማይጠበቅ ተራ መልስ ነው፡፡

ቅዱስ ባስልዮስ ‘አዳም ክፋትን የሠራው በሚያስገድድ ፍላጎት ሳይሆን ካለማሰብ ነበረ’ (St. Basil the Great, On the Human Condition, Homily on Explaining that God is not the Cause of Evil, page 75)
እንዳለው አዳም ሔዋን እጁ ላይ ያስቀመጠችውን ፍሬ ወደ አፉ ለመስደድ ቆይ ጥቂት ላስብበት እንኳን
አላለም፡፡ ሔዋን ከእባብ እንደሰማችው ዓይነት ብዙ ማብራሪያም አልጠየቀም ፤ የሠጠችውን ተቀብሎ በላ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ፦
‘አዳም ለሔዋን በቀላሉ እጅ እንደሠጠበት መንገድ ከሆነ ያለ ሰይጣንም ቢሆን መበደሉ የማይቀር ይመስላል’ ይላል፡፡ (St. John Chrysostom, To Stageiron 1,5 page 47)

ቅዱስ ኤፍሬምም በዘፍጥረት ትርጓሜው ‘እባብ ባይመጣ ኖሮ አዳም ባልወደቀ ነበር የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ነገር ግን አዳም እባብ ባይመጣ ኖሮ በኤሊ ይሸነፍ ነበር’ ብሎ ችግሩ የአሳሳቾቹ ማንነት ሳይሆን የአዳምና ሔዋን ስኁታንነት መሆኑን ያስረዳል፡፡

የአዳም በደል ከሔዋን በደል የሚከፋበት ብዙ መንገድም አለ፡፡ እንደሚታወቀው የእግዚአብሔርን ከዛፉ ፍሬ አትብሉ የሚል ትእዛዝ ቀድሞ የሰማው አዳም ነበረ፡፡ አዳም ያንን ትእዛዝ በሰማበት ወቅት ሔዋን አልነበረችም፡፡ ስለ ትእዛዙ የሰማችው ከአዳም ነበር፡፡ ልብ አድርጉ ትእዛዙ አዳም በቀጥታ ከእግዚአብሔር የሰማው ሲሆን ሔዋን ግን በተዘዋዋሪ የሰማችው ነው፡፡ ስለዚህ ሔዋን ብትበድል በሰው ተሰብካ ነው ፤ አዳም ግን በቀጥታ የተነገረው ሲሆን ለሔዋን የሕግ መምህርዋም ነበረ፡፡

‘የጌታውን ፈቃድ አውቆ ያልተዘጋጀ እንደ ፈቃዱም ያላደረገ ያ ባሪያ እጅግ ይገረፋል ... ብዙ ከተሠጠው ብዙ ይሹበታል’ እንዲል ከሔዋን በላይ ከአዳም ብዙ ይጠበቅ ነበር፡፡ ሉቃ. ፲፪፥፵፯

የሚደንቀው በፈተና ጊዜም ሕጉን አስታውሳ የጠቀሰችው ሔዋን ብቻ ነበረች፡፡ ‘ሞትን እንዳትሞቱ አትብሉ አትንኩትም አለን’ ብላ እባብን ትንሽም ቢሆን ተከራክራለች፡፡ አዳም ግን ስለ ሕጉ እንደ ሔዋን አስታውሶ ‘ለምን ቀጠፍሽው? አትብሉ ተብለን የለም እንዴ?’ አላላትም፡፡ በራሱ አንደበት የሆነውን ሲናገር ‘ሠጠችኝና በላሁ’ ነው ያለው፡፡ ምንም እንኳን መጨረሻ ላይ ብትስትም በዚህስ ሔዋን ከአዳም ተሽላ ተገኝታለች፡፡

የአዳም ሌላ ጥፋት ከዛፉ ፍሬ ለምን እንደበላ ለመግለፅ ምክንያት ያቀረበበት አገላለጽ ነው፡፡ ‘ረዳት ትሁንህ ብለህ የሠጠኸኝ ሴት ከዛፉ ሠጠችኝና በላሁ’ አለ፡፡ ‘አጥንትሽ ከአጥንቴ ፣ ሥጋሽ ከሥጋዬ ፤ አንድ ሥጋዬ አካሌ’ ብሎ በፍቅር ቃል እንዳልተናገረላት አሁን ‘አጥንቴና ሥጋዬ አካሌ ሠጠችኝ’ አላለም፡፡ ከእርሱ እንዳልተገኘች ፣ እንዳያት እንዳልወደዳት ሁሉ አሁን ግን ባዕድ አድርጎ ‘የሠጠኸኝ ሴት’ ብሎ ለፈጣሪ መለሳት፡፡ የሰው ልጅ አመስግኖ የተቀበለውን ነገር አልሆን ሲለው ተሳድቦ እንደሚመልስ በዚህ ታወቀ፡፡
#share
@diyakonhenokhaile
ሔዋን ለእግዚአብሔር ‘እባብ አሳተኝና በላሁ’ አለች፡፡ ይህ ንግግርዋ ከአዳም ንግግር በብዙ እጥፍ የተሻለ ነው፡፡ ‘የሠጠኸኝ ሴት’ የሚለው የአዳም ንግግር እግዚአብሔርን ከተከሳሾች ቁጥር የሚጨምር ሲሆን ‘እባብ አሳተኝ’ የሚለው ቃል ግን ፈጣሪን ከመወንጀል የጸዳ ነው፡ ፡

‘ለሰው ልጆች ተገዢ ይሁን ብለህ የፈጠርከው እባብ አሳተኝና በላሁ’ ብትል ኖሮ አዳምን በመሰለች ነበር፡፡ እርስዋ ግን ከእባብ ጀመረች እንጂ ‘ያው አንተ የፈጠርከው እባብ’ አላለችም፡፡

‘አሳተኝና በላሁ’ የሚለው ንግግርዋም ከአዳም ‘ሰጠችኝና በላሁ’ የሚል ንግግር እጅግ በጣም የተሻለ ነው፡፡ ሰጠችኝና በላሁ ሲል ሙሉ በሙሉ ጥፋቱን ወደ ሔዋን የደፈደፈ አነጋገር ሲሆን ‘አሳተኝና በላሁ’ በሚለው ውስጥ ግን ‘እኔም ስቻለሁ ፣ ተታልያለሁ’ የሚል የራስን ጥፋት ማመን አለበት፡፡ ቅዱስ አምብሮስ ‘ሔዋን ከአዳም ይልቅ መታለልዋን ቀድማ አመነች’ ያለው ይህንን ነው፡፡ (St. Ambrose of Milan, On Paradse 32)

የብርሃን እናት ገጽ 84-85
#share
@diyakonhenokhaile
አዎን አቤቱ የሁሉ አምላክ ነህ፤
አዎን አቤቱ የሁሉ ንጉሥ ነህ፤
አዎን አቤቱ ሁሉን የያዝክ ነህ፤
አዎን አቤቱ ሁሉን የምትገዛ ነህ፤
አዎን አቤቱ ሁሉን የምታድን ነህ፤
አዎን አቤቱ በእውነት የሁሉ ገዢ ነህ፤
አዎን አቤቱ የሁሉ መድኀኒት ነህ፤
አዎን አቤቱ ሁሉን የምትጠብቅ ነህ፤
አዎን አቤቱ ሁሉን የምትመግብ ነህ።

የልጅህን ሥጋ ከእኛ ሥጋ ጋር አንድ እንዳደረግህ፤ የአንተን መሲሕ ደምም ከእኛ ደም ጋር አንድ እንዳደረግህ እንዲሁ አንተን መፍራትን በልቡናችን፤ በጎ አምልኮትንም በሕሊናችን ጨምር።

ሥጋውያን የምንሆን እኛ ግን የሥጋን ሕግ እናስባለን፤ የሥጋንም ሥራ እንሠራለን፤ በሥጋም መንገድም እንሄዳለን። አንተ ግን የመንፈስን ሥራ አስተምረን፤ የመንፈስንም ሕግ አስረዳን፤ የመንፈስንም መንገድ ምራን።

እኛን ኃጥአንን ብትምረን ያን ጊዜ መሐሪ ትባላለህና። ጻድቃንን ግን ከሥራቸው የተነሳ ትምራቸዋለህ፤ እንደ ጽድቃቸውም ትሰጣቸዋለህ።

የቀደመ በደላችንን አታስብብን፤ አቤቱ ይቅርታህ ፈጥኖ ይደረግልን። ወደ አንተ እንጮሃለን፤ ወደ አንተ እናለቅሳለን፤ ወደ አንተ እንማልላለን ለዘለዓለሙ አሜን።

✟ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ✟

ለሌሎችም እንዲደርስ በየግሩፑ #Share አደሩጉው !

@Orthodox_sibket

  @Orthodox_sibket

@Orthodox_sibket
የማይገባው ተሸላሚ

ቄሱ ሲናዝዙ "ኩኑ ፍቱሐነ ወንጹሐነ ይረስየኒ ወይሬሲክሙ ድልዋነ ለመንግሥተ ሰማያት" "የተፈታችሁ ንጹሐን ሁኑ እኔንም እናንተንም ለመንግሥተ ሰማያት የተገባን ያደርገን ዘንድ" ብለው ጣታችንን ዐሥራ ሁለት ጊዜ በእግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ ሲያስቆጥሩን ለወትሮ ያላሰብሁት ነገር ታሰበኝ::

"እኔንም እናንተንም ለመንግሥተ ሰማያት የተገባን ያደርገን ዘንድ" የሚለው ቃል!

መንግሥተ ሰማያትን መውረስ መቼም ከእኛ መካከል የማይፈልግ ሰው የለም:: ለመንግሥተ ሰማያት ግን የተገባን ነን ወይ?

እውነት አሁን ጌታ ቢመጣና ሁሉንም በደላችንን ትቶ ሁላችንንም በቀኙ

አቁሞ መንግሥቴን ውረሱ ቢለንና ወደ መንግሥቱ ብንገባስ? ለመንግሥተ ሰማያት የሚሆን ማንነት አለን ይሆን? ከእኛ መካከል ለመንግሥተ ሰማያት የተገባ ማን ነው?

ጌታ ሆይ እንኳን ለመንግሥትህ በምድር ላለችው ቤትህ የሚገባ ማንነት እንደሌለኝ ሳስብ "መንግሥትህ ትምጣ" ማለት አስፈራኝ::

"በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው" በተባለላት ቤትህ እንኩዋን እንደሚገባኝ መመላለስ ላልቻልሁት ለእኔ መንግሥትህን እንዴት ልመኝ? 1 ጢሞ. 3:15

" አቤቱ፥ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል? በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል?” ብሎ ዳዊት ቢጠይቅ የመለህለት ውስጥ ራሴን አጣሁት:: መዝ. 15:1 ስለዚህ ለመንግሥትህ የሚሆን ማንነት ማጣቴ አሳፈረኝ::

የሰርግ ልብስ ሳልለብስ ወደ ሰርግ ቤትህ የገባሁ ብሆንስ? በመላእክት ማኅበር መካከል ዕርቃኔን ብቆምስ? እውነት የኔን ጠባይ ወደ መንግሥትህ ይዤው ልገባ ይቻል ይሆን? በመንግሥትህ ለእኔ ዓይነቱ ሰው የሚሆን ቦታ አለህ ይሆን? እርግጥ ነው በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ ብለሃል:: ለእኔ ዓይነቱ ቁስለኛ የሚሆን ቤትስ ይኖርህ ይሆን? ግዴለም ከደጁም ቢሆን አስገባኝ::

ያስተማሩ የሐዋርያት ማኅበር ፣ ድል የነሡ ሰማዕታት ማኅበር ፣ ቡሩካን የሆኑ የጻድቃን ማኅበር በዚያ እንዳለ አውቃለሁ:: ወደ መንግሥትህ ብገባ የእኔ ምድብ ወዴት ይሆን? ይቅር የተባሉ ሰዎች ማኅበር የለህ ይሆን? ምሕረትህ የበዛላቸው ሰዎች ማኅበር ፣ እንደ ቸርነትህ ብዛት የተማሩ ፣ እንደ ይቅርታህ ብዛት መተላለፋቸው የተደመሰሰላቸው ሰዎች ማኅበር የለህ ይሆን? ክርስቲያን ተብዬ ልጠራ ያልተገባኝ እኔን በቸርነትህ ለመንግሥትህ ዜግነት የተገባሁ አድርገኝ::

#share

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሚያዝያ 2016 ዓ.ም.

@diyakonhenokhaile
የማይገባው ተሸላሚ

ቄሱ ሲናዝዙ "ኩኑ ፍቱሐነ ወንጹሐነ ይረስየኒ ወይሬሲክሙ ድልዋነ ለመንግሥተ ሰማያት" "የተፈታችሁ ንጹሐን ሁኑ እኔንም እናንተንም ለመንግሥተ ሰማያት የተገባን ያደርገን ዘንድ" ብለው ጣታችንን ዐሥራ ሁለት ጊዜ በእግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ ሲያስቆጥሩን ለወትሮ ያላሰብሁት ነገር ታሰበኝ::

"እኔንም እናንተንም ለመንግሥተ ሰማያት የተገባን ያደርገን ዘንድ" የሚለው ቃል!

መንግሥተ ሰማያትን መውረስ መቼም ከእኛ መካከል የማይፈልግ ሰው የለም:: ለመንግሥተ ሰማያት ግን የተገባን ነን ወይ?

እውነት አሁን ጌታ ቢመጣና ሁሉንም በደላችንን ትቶ ሁላችንንም በቀኙ

አቁሞ መንግሥቴን ውረሱ ቢለንና ወደ መንግሥቱ ብንገባስ? ለመንግሥተ ሰማያት የሚሆን ማንነት አለን ይሆን? ከእኛ መካከል ለመንግሥተ ሰማያት የተገባ ማን ነው?

ጌታ ሆይ እንኳን ለመንግሥትህ በምድር ላለችው ቤትህ የሚገባ ማንነት እንደሌለኝ ሳስብ "መንግሥትህ ትምጣ" ማለት አስፈራኝ::

"በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው" በተባለላት ቤትህ እንኩዋን እንደሚገባኝ መመላለስ ላልቻልሁት ለእኔ መንግሥትህን እንዴት ልመኝ? 1 ጢሞ. 3:15

" አቤቱ፥ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል? በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል?” ብሎ ዳዊት ቢጠይቅ የመለህለት ውስጥ ራሴን አጣሁት:: መዝ. 15:1 ስለዚህ ለመንግሥትህ የሚሆን ማንነት ማጣቴ አሳፈረኝ::

የሰርግ ልብስ ሳልለብስ ወደ ሰርግ ቤትህ የገባሁ ብሆንስ? በመላእክት ማኅበር መካከል ዕርቃኔን ብቆምስ? እውነት የኔን ጠባይ ወደ መንግሥትህ ይዤው ልገባ ይቻል ይሆን? በመንግሥትህ ለእኔ ዓይነቱ ሰው የሚሆን ቦታ አለህ ይሆን? እርግጥ ነው በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ ብለሃል:: ለእኔ ዓይነቱ ቁስለኛ የሚሆን ቤትስ ይኖርህ ይሆን? ግዴለም ከደጁም ቢሆን አስገባኝ::

ያስተማሩ የሐዋርያት ማኅበር ፣ ድል የነሡ ሰማዕታት ማኅበር ፣ ቡሩካን የሆኑ የጻድቃን ማኅበር በዚያ እንዳለ አውቃለሁ:: ወደ መንግሥትህ ብገባ የእኔ ምድብ ወዴት ይሆን? ይቅር የተባሉ ሰዎች ማኅበር የለህ ይሆን? ምሕረትህ የበዛላቸው ሰዎች ማኅበር ፣ እንደ ቸርነትህ ብዛት የተማሩ ፣ እንደ ይቅርታህ ብዛት መተላለፋቸው የተደመሰሰላቸው ሰዎች ማኅበር የለህ ይሆን? ክርስቲያን ተብዬ ልጠራ ያልተገባኝ እኔን በቸርነትህ ለመንግሥትህ ዜግነት የተገባሁ አድርገኝ::

#share

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሚያዝያ 2016 ዓ.ም.

@diyakonhenokhaile
This media is not supported in your browser
VIEW IN TELEGRAM
"እጅግም አዝነው እያንዳንዱ፦ “ጌታ ሆይ፥ እኔ እሆንን?” ይሉት ጀመር" ማቴ. 26:22

ስንት የአጥቢያ ኮከቦች ለአንተ
ዘምረውልህ ወደቁ
በሰማይ መቅደስህ አጥነው
በትዕቢት ረግፈው አለቁ
እፈራለሁ እኔም ለራሴ
መንገዴን ንገረኝ ጌታ
ጠዋት በዘመርሁበት አፍ
እንዳልሳደብ በማታ

#share
#share

▫️@diyakonhenokhaile
https://t.me/diyakonhenokhaile
+ የሚያምር እግር +

በጸሎተ ሐሙስ ልብን የሚሰውር አንድ ነገር ተፈጽሞ አለፈ፡፡ ይህም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር የማጠቡ ነገር ነው፡፡ የሰውን የቆሸሸ እግር እያሸ የሚያጥብ አምላክ ፣ የተማሪዎቹን እግር የሚያጥብ መምህር ፣ የባሪያዎቹን እግር የሚያጸዳ ጌታ ማየት እንዴት ያስጨንቃል?

እስቲ ለአንድ አፍታ ወደዚያ ቤት በሕሊናችን ተጉዘን እንግባና ጌታን እግር ሲያጥብ አብረን እንመልከተው፡፡

የአምስተኛው ክፍለ ዘመን ባለቅኔ የቅዱስ ኤፍሬም ተማሪ ሶርያዊው ቄርሎና በመንፈስ ሆኖ ያንን ቤት በዓይነ ሕሊናው እንዲህ ቃኝቶት ነበር ፦

'ጌታ ውኃ ቀዳና መታጠቢያውን ተሸከመ። የማበሻ ጨርቅ ያዘና ታጠቀ፡፡ የደቀ መዛሙርቱን እግር ሊያጥብ ጀመረ፡፡ ሕሊናዬን አንዳች ነገር ሲወጋው ተሰማኝ ዕንባዬም ፈሰሰ። በፍርሃት ፊቴን ሸፈንኩ ዓይኖቼንም በመሳቀቅ ዞር አደረግሁ፡፡ ሲያጥባቸው ለማየት አቅም የለኝምና ብወጣ ተመኘሁ' ይላል፡፡ (Hymns of Cyrillona, On The Washing of the feet, Gorgias Press pg 72)እውነትም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጎንብሶ ማጠብ ለማሰብ ይከብዳል፡፡
@diyakonhenokhaile

ጌታችን ሐሙስ ዕለት ያደረገውን ነገር መጥምቁ ዮሐንስ ቢያይ ኖሮ ምን ይል ይሆን? ጌታ ሊጠመቅ ወደ እርሱ በመጣ ጊዜ ዮሐንስ 'አንተ እንዴት ልትጠመቅ ወደ እኔ ትመጣለህ?' ብሎ አልነበር? መጥምቁ ዮሐንስ ሆይ ና ተመልከት! በአንተ በባሪያው እጅ ሊጠመቅ ሲመጣ ስለ ትሕትናው የተደነቅህበት ጌታ ዛሬ ደግሞ አጥምቁኝ ከማለት አልፎ የባሪያዎቹን እግር ሲያጥብ አጎንብሶ ታየ፡፡ አንተ 'የጫማውን ጠፍር ተጎንብሼ ልፈታ አይገባኝም' ያልክለት ጌታ አጎንብሶ የሐዋርያቱን ጫማ ሲፈታና እግራቸውን ሲያጥብ ብታይ ምን ትል ይሆን? በዮርዳኖስ ዳር 'አንተ እንዴት ልትጠመቅ ወደ እኔ ትመጣለህ?' ያልከውን ጌታ ቅዱስ ጴጥሮስ 'አንተ እንዴት የእኔን እግር ታጥባለህ?' ሲለው ተመልከት! በእርግጥ በዮርዳኖስ ወንዝ ከታየው ትሕትና የበለጠ ትሕትና በዚያች የመታጠቢያ ወኃ ውስጥ ታየ፡፡ ውኃ በተሞላ በአንድ ማስታጠቢያ ውስጥ የፍጡር እግርና የፈጣሪ እጅ አንድ ላይ ሆነው የታዩበትን ያን ቅጽበት እጅግ ታላቅ ትሕትና ተማርንበት፡፡ ፍጡር ፈጣሪውን ሲያጠምቀው ከማየት በላይ ፈጣሪ የፍጡርን እግር ሲያጥብ ማየት ድንጋይ ልባችንን የሚሰብር ቅጽበት ነው፡፡

ከመጥምቁ ዮሐንስ በፊት የነበሩት ነቢያትስ ይህንን ቢያዩ እንዴት ይደነቁ ይሆን? ኢሳይያስ ሆይ 'ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ሆኖ አየሁት' ያልክለት ጌታ ዝቅ ባለ መቀመጫ ላይ ቁጭ ብሎ የአሳ አጥማጆችን እግር ሲያጥብ ተመልከተው፡፡ ነቢዩ ዳዊት ሆይ 'እግሮቹ በሚቆሙበት ሥፍራ እንሰግዳለን' ብለህ የዘመርክለት ጌታ እግር እያጠበ ነው፡፡ የሚገርመው እግር ከማጠቡ በፊትም ውኃ አስቀረበ አይልም ምክንያቱም ውኃውን የቀዳውም እርሱ ራሱ ነበረ፡። አብርሃም ለእንግዶቹ እንዳለው 'ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ' ብሎ ውኃ አላስቀዳም፡፡ (ዘፍ. 18፡4) ራሱ ወኃወን ቀድቶ በመታጠቢያው ሞልቶ የባሪያዎቹን እግር አጠበ። ለነገሩ በትሕትና የተጠመቀበትን የዮርዳኖስን ወንዝስ ቢሆን በወኃ የሞላው እርሱ አልነበረምን? ...

ጴጥሮስ ተጨነቀ ፤ 'ጌታ ሆይ አንተ እንዴት የእኔን እግር ታጥባለህ?' አለና ተከላከለ፡፡ የጴጥሮስ ጭንቀት ብዙ ነገር ከማሰብ የመነጨ ነው፡፡ 'ኪሩቤል በፊትህ ግርማ እንዳይቃጠል ፈርተው በፊትህ ሲቆሙ በክንፎቻቸው እግራቸውን ይሸፍናሉ፡፡ ታዲያ እኔ እጠብልኝ ብዬ እንዴት ደፍሬ እግሬን እሠጥሃለሁ? ሱራፌል የልብስህን ጫፍ የማይነኩህ ጌታ የእኔን እግር እንዴት ታጥባለህ? በባሕር ላይ በአንተ ትእዛዝ የተራመድሁት አይበቃኝም? እንዴት እግርህን ልጠብህ ትለኛለህ? ይህንን ዕዳ እንዴ እሸከመዋለሁ?' የሚል ጽኑ ጭንቀት ያዘለ ጥያቄ ነበር፡፡ ጌታ ግን ዕውር ባበራባቸው እጆቹ እግር አጠበባቸው፡፡ ሸክላ ሠሪው አጎንብሶ የሸክላውን እግር አጠበ፡፡ ሰውን ከምድር አፈር የፈጠረው አምላክ ትቢያውን በክብር አስቀምጦ እግሩን አጠበው፡፡

ጌታችን ያጠበው ከሰዓታት በኋላ እግሬ አውጪኝ ብለው ጥለውት የሚሸሹትን የደቀ መዛሙርቱን እግሮች ነበረ፡፡ ለአንድ ሰዓት እንኳን አብረውት ሊተጉ የማይችሉትን ተማሪዎቹን እግር አጠበ፡፡ ጥለውት እንደሚሔዱ እያወቀ 'ንጹሐን ናችሁ' ብሎ አወደሳቸው፡፡ 'ወደ አብ እንደሚሔድ አውቆ የወደዳቸውን እስከ መጨረሻው ወደዳቸው' እንደሚል ምድር ላይ በቀረችው ጊዜ ያልከፈለው የፍቅር ዕዳ እንዲኖርበት አልፈለገምና ጊዜውን ለመውደድ ተጠቀመበት፡፡ የሚወዳቸውን ደቀ መዛሙርት እግራቸውን አጥቦ በፍቅር ተሰናበታቸው፡፡

ጌታ ሆይ የእኔንስ እግር የምታጥበው መቼ ነው? በእውነት በምድር ላይ ከእኔ እግር በላይ የቆሸሸ አለ? ያልረገጥሁት የኃጢአት ጭቃ ፣ ያልነካሁት የበደል ቆሻሻ እንደሌለ አታውቅምን? 'በክፉዎች ምክር የሔደ' እግሬን የማታጸዳው ለምንድን ነው? (መዝ. 1፡2) 'የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም' ብለህ የለምን? እውነት ነው ፤ እግሬን ከኃጢአት ከከለከልክልኝ ሌላውን አካሌን ማዳንህም አይደል? አጥብቀህ ከምትጠላቸው ነገሮች መካከል አንዱ የሆነውን 'ወደ ክፉ የሚሮጥ እግሬን' የማታጥብልኝ ለምንድን ነው? (ምሳ. 6፡18)እባክህን እጠበኝ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እሆናለሁ፡፡ በእርግጥ የሐዋርያትን የቆሸሸ እግር በውኃ እንዳጠብከው አስበን አደነቅን እንጂ በማግሥቱ ደግሞ የዓለምን ኃጢአት በደምህ አጥበሃል፡፡ ከዳንሁ በኋላ የቆሰልሁትን ፣ ከታጠብኩ በኋላ ያደፍሁትን እኔን በከበረ ሥጋና ደምህ ከኃጢአቴ እድፍ ታጥበኝ ዘንድ ነው ልመናዬ፡፡

በጌታ እጅ የታጠበው የሐዋርያት እግር እንዴት የታደለ ነው? በእሱ ስለታጠበ ዓለምን ዞሮ ወንጌል ለማዳረስ የቻለ እግር ሆነ፡፡ ጌታ ያላጠበው እግር ወንጌል ለዓለም አያደርስም፡፡ ባልታጠበ እግራችን ብንዞር እኛ እንጂ ወንጌል ዓለምን አይዞርም፡፡ ስለዚህ ሐዋርያ ሊሆን የሚሻ ሁሉ ጌታ ሆይ እግሬን እጠብልኝ ብሎ መለመን አለበት፡፡ ወንጌሉም 'የደቀ መዛሙርቱን እግር ሊያጥብ ጀመረ' ይላልና ክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ሊሆኑ ለሚወዱ ሁሉ እግራቸውን ማጠቡን አሁንም አያቋርጥም፡፡

ጌታ ያጠበው እግር ምን ይሆናል ካልከኝ 'የሚያምር እግር ይሆናል' እልሃለሁ፡፡ ሐዋርያት እግራቸው እጅግ ያምር ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ በእግሩ እብጠት የማይንቀሳቀሰው ቅዱስ ያዕቆብ ሳይቀር እግሩ ያማረ ነበር፡፡ ምክንያቱም 'መልካሙን የምሥራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው?' ተብሎ ተጽፎአል፡፡ ሮሜ 10፡15

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

ሚያዝያ 24 2016 ዓ.ም.

ኢየሩሳሌም ፤ ፳ኤል
#share
#share

▫️@diyakonhenokhaile
https://t.me/diyakonhenokhaile
ጰራቅሊጦስ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን ነው:: በትንሣኤው ተፀንሳ እስከ ዕርገቱ ድረስ ለዐርባ ቀናት ተሥዕሎተ መልክእ (Organ formation) የተፈጸመላት ቤተ ክርስቲያን ዛሬ የተወለደችበት ቀን ነው:: እግዚአብሔር በባቢሎን ሜዳ የበተነውን ቋንቋ የሰበሰበበትና እንዱ የሌላውን እንዳይሰማው እንደባልቀው ያሉ ሥሉስ ቅዱስ አንዱ የሌላውን እንዲሰማ ያደረጉበት ዕለት ዛሬ ነው:: ሰው ወደ ፈጣሪ ግንብ ሰርቶ በትዕቢት ለመውጣት ሲሞክር የወረደው መቅሠፍት ዛሬ በትሕትና ፈጣሪን ሲጠባበቁ ለነበሩ ሐዋርያት ፈጣሪ ራሱ ያለ ግንብ ወርዶ ራሱን የገለጠበት ዕለት ነው::

ዛሬ እስራኤል ከግብፅ በወጡ በሃምሳኛው ቀን በሲናን ተራራ የወረደው እሳትና በጽላት ላይ የተጻፈው ሕግ የተሠጠበት ቀን ነው:: ፋሲካችን ክርስቶስ በታረደ በሃምሳኛው ቀን በሐዲስ ኪዳንዋ ደብረ ሲና በጽርሐ ጽዮን በእሳት አምሳል መንፈስ ቅዱስ ወርዶ በሐዋርያት በልባቸው ጽላት ቃሉን የጻፈበት ቀን ነው:: በዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ በርግብ አምሳል በትሕትና የወረደው መንፈስ ቅዱስ ዛሬ በእሳትና በነፋስ አምሳል ወደ ሐዋርያቱ የወረደው ዛሬ ነው:: ርግብ ሆኖ የወረደው ሊመሰክርለት እንጂ ኃይል ሊሠጠው ስላልነበረ ነው:: ዛሬ ግን ለሐዋርያቱ ኃይል ሊሠጣቸው ፈልጎ በእሳትና በነፋስ ኃይሉን ገለጠ::

መንፈስ ቅዱስ ሲወርድ በዚያ መገኘት ከፈለጋችሁ በቅዳሴው መካከል ተገኙ:: ካህኑን "ይህች ቀን ምን የምታስፈራ ናት? ይህች ቀን ምን የምታስጨንቅ ናት? መንፈስ ቅዱስ ከመልዕልተ ሰማያት የሚወርድባት?" ሲል ታገኙታላችሁ:: ኢሳይያስ ያየውን ራእይ ማየት ከፈለጋችሁ ወደ ቅዳሴ ገስግሱ:: ሱራፊ በጉጠት ፍሕም ይዞ ኃጢአታችሁን የሚተኩስበትን ደሙን ለመቀበል ከፈለጋችሁ ወደ ቅዳሴው ገስግሱ:: "ፈኑ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ላዕሌነ" እያላችሁ የምታዜሙበት ዕለታዊው ጰራቅሊጦስ ቅዳሴው ላይ ተገኙ:: በአዲስ ቋንቋ ትናገራላችሁ:: የእናንተ ቋንቋ ሳይቀየር የሁሉም ቋንቋ ተናጋሪ ሰምቶ ይረዳችሁዋል::

ለሐዋርያት የተሠጠኸውን ሠጥተኸን ከሐዋርያት ያገኘኸውን ያላገኘህብን ሆይ ቅዱስ መንፈስህ ከእኛ አትውሰድብን:: የማዳንህን ደስታ ሥጠን:: በእሺታም መንፈስ ደግፈን::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሰኔ 16 2016 ዓ.ም.

#share

▫️@diyakonhenokhaile
https://t.me/diyakonhenokhaile