Gazette Plus / ጋዜጣ ፕላስ/
25K subscribers
41K photos
338 videos
7 files
5.81K links
Ethiopian Press Agency, established in 1940 , is a public printing media enterprise operating in Ethiopia.
Download Telegram
"የበጋ የመስኖ ስንዴ ልማት እስካሁን ውጤታማ ሆኗል። ባገኘናቸው ውጤቶች ላይ፣ ፈጠራ የታከለባቸውን ጥረቶች በማከል ከውጪ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት ሕልማችንን እውን እናደርጋለን"

-የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ
“የኢትዮ -ሱዳን የድንበር ግጭት የአገሪቱን ልማትና ሰላም የማይፈልጉ ኃይሎች ሴራ ነው” ዶክተር ደመቀ አጭሶበአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የፖሊቲካል ሳይንስና የዓለም አቀፍ ግንኙነት ትምህርት ክፍል መምህር
****************************
(ኢ ፕ ድ)
ኢትዮጵያና ሱዳን ለዘመናት አብረው በሰላም የኖሩና ሰፊ ድንበር የሚጋሩ ጎረቤት አገራት ቢሆኑም በቅርብ ጊዜ በድንበር አካባቢ የተፈጠረው ግጭት ከድንበር በዘለለ የኢትዮጵያን ልማትና ሰላም የማይፈልጉ ሃይሎች አገሪቱን የማተራመስ ሴራ መሆኑ ተገለፀ::
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የፖሊቲካል ሳይንስና የዓለም አቀፍ ግንኙነት ትምህርት ክፍል መምህር ዶክተር ደመቀ አጭሶ የድንበር ግጭቱን አስመልክቶ በተለይ ለአዲስ ዘመን እንዳስታወቁት፤ የኢትዮጵያና ሱዳን ሰፊ ድንበር የሚጋሩ፣ ለዘመናት በሰላም አብረው የኖሩ ሕዝቦች ናቸው።
በአገራችን እየተካሄደ ያለውን የሕግ ማስከበር ሂደት ተከትሎ ሱዳን በድንበር አካባቢ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት መክፈቷ ያልተለመደ ክስተት መሆኑን የጠቆሙት ዶክተር ደመቀ፤ ከግጭቱ በስተጀርባ የአገራችንን ሰላም የማይፈልጉ ግብጾችና የኛው አኩራፊ ሃይሎች መኖራቸው ቅንጣት አያጠራጥርም ብለዋል::
ኢትዮጵያ ከግብጽ ይልቅ የሱዳን ታሪካዊ ወዳጅና አጋር መሆኗን ያመለከቱት ዶክተሩ፤ እ.ኤ.አ በ1973 እስከ 1983 በኮሎኔል ኒሜሪ ዘመን በታሪክ ተረጋግታ የማታውቀው ሀገር ሱዳን ለአስር ዓመታት ያህል በንጉሥ ኃይለ ሥላሴ እገዛ ሰላም ሰፍኖባት እንደነበር አስታውቀዋል:: በወቅቱ አንፃራዊ ሰላም የሰፈነው ኢትዮጵያ በአዲስ አበባ ኮርድ አማካይነት ለደቡብ ሱዳኖች እውቅና ሰጥታ ወደ ፌዴራል መንግሥት እንዲካተቱ በማገዟ እንደሆነም አመልክተዋል::
እ.ኤ.አ በ1989 በወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ሥልጣን በያዙት በኮሎኔል ኦማር አልበሽር ዘመንም በደቡብ ሱዳንና በሱዳን መካከል በተፈጠረው ግጭት፣ በተለይ በዳርፉር ግጭት አስከፊ ሰብዓዊ ቀውስ እንዳይፈጠር የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ሃይል ድርሻ ጉልህ መሆኑንም ጠቁመዋል::
https://www.press.et/Ama/?p=39077
ቦይንግ ስለ 737 ማክስ አውሮፕላኑ ዲዛይን ለተመሰረተበት የወንጀል ክስ 2.5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ለመክፈል ተስማማ
***********************
(ኢ ፕ ድ)
ቦይንግ ስለ 737 ማክስ አውሮፕላኑ ዲዛይን ከአሜሪካ የደኅንነት እና ጥንቃቄ ባለሙያዎች መረጃዎችን በመደበቅ ለተመሰረተበት የወንጀል ክስ 2.5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ለመክፈል ተስማማ።
የአሜሪካ ፍትህ ቢሮ እንዳለው ከሆነ ኩባንያው "ከግልጽነት ይልቅ ትርፍን" አስቀድሟል።
ቦይንግ 737 ማክስ አውሮፕላን በኢትዮጵያ እና በኢዶኔዢያ ተከስክሶ የ346 ሰዎች ህይወት አልፏል።
ቦይንግ ለመክፈል ከተስማማው ገንዘብ ውስጥ 500 ሚሊዮን ዶላሩ በአውሮፕላኑ አደጋ ቤተሰቦቻቸውን ላጡ የሚከፋፈል ይሆናል።
ቦይንግ እንዳለው ይህ ስምምነት ኩባንያው "ያለበት ጉድለት" ምን ያህል መሆኑን ያሳያል።
የቦይንግ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊ ዴቪድ ካልሁን እንዳሉት "ወደ እዚህ ስምምነት መግባታችን ትክክለኛው ነገር እንደሆነ በጽኑ አምናለሁ፤ ይህም ከእሴቶቻችን እና ከሚጠበቅብን ምን ያህል ወደ ኋላ መቅረታችንን ያሳያል።"
"ይህ ስምምነት ሁላችንንም የሚያስታውሰን ለግልጽነት የገባነው ግዴታ ምን ያህል ወሳኝ እንደሆነ፤ እንዲሁም አንዳችንም እንኳን እርሱን ሳናሟላ ብንቀር መዘዙ የከፋ መሆኑን ነው።"
የአሜሪካ ፍትህ ቢሮ እንዳለው ከሆነ የቦይንግ ባለስልጣናት በኢንዶኔዢያ እና በኢትዮጵያ ለአውሮፕላኑ መከስከስ ምክንያት ስለሆነው ኤምካስ የተባለው አውቶማቲክ የበረራ መቆጣጠሪያ ሥርዓት ላይ ስላለ ለውጥ መረጃ ደብቀዋል።
እንደ ቢቢሲ ዘገባ፤ ይህ ውሳኔ የሚያሳው የአውሮፕላን አብራሪው ስልጠና መመሪያ ስለሥርዓቱ በቂ መረጃ አለመያዙን፣ ይህም በተሳሳተ መረጃ የአውቶማቲክ ሥርዓቱ የአብራሪውን ውሳኔ እንደሚሽረውና፣ ይህም አውሮፕላኑ ከማኮብኮቢያው በተነሳ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ አፍንጫውን አዘቅዝቆ ቁልቁል እንዲምዘገዘግ እንደሚያደርገው ነው።
“የትግራይ ሕዝብ የገጠመውን ፈተና ከፌደራል መንግሥት ጎን በመቆም ሊሻገረው ይገባል” ዶክተር ሙሉ ነጋ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈፃሚ
************************
(ኢ ፕ ድ)
የትግራይ ህዝብ የገጠመውን ፈተና ከፌደራል መንግሥት ጎን በመቆም ሊሻገረው እንደሚገባ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ሙሉ ነጋ ጥሪ አቀረቡ ::
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ሙሉ ነጋ በዓሉን አስመልክተው በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፤ በክልሉ የሕግ ማስከበር ከተጀመረ ጀምሮ በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው:: በተለይም ሰላምና መረጋጋትን ከማምጣት አንፃር ጥሩ እንቅስቃሴ አለ፡፡
በዓሉን ለማክበር መሰረታዊው ነገር ሰላም ነው:: በዚህ ጉዳይ ላይ ውጤታማ ሥራዎች በመሥራት ላይ ናቸው ያሉት ዶክተር ሙሉ፣ በዓሉን ተመርኩዞ ዋና አስፈላጊ የሆኑት አስቸኳይ ዕርዳታ የሚፈልጉ አካላትን ማገዝ ነው:: ይህም በከፍተኛ ሁኔታ እየተከናወነ ነው ብለዋል ::
ብዙ የትግራይ አካባቢዎችም ከመብራትና ስልክ ጀምሮ ችግር የገጠማቸው በመሆናቸው ይህንንም ለማስተካከል ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን አመልክተው፣ በክልሉ ባንኮች እንዲከፈቱ መደረጉም የዚህ ትኩረት አካል እንደሆነ ጠቁመዋል::
መብራትና ስልክ እንዲሁም ውሃ ያላገኙ አካባቢዎች በዓሉን በጭለማ እንዳያሳልፉ እየተሠራ መሆኑን የሚጠቁሙት ዶክተር ሙሉ፤ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ በመሰረተ ልማት ችግር ምክንያት በተለይም በመንገድ ችግር የዕለት ደራሽ ዕርዳታውን ለማድረስ ችግር ገጥሟል:: ችግሩን በተቻለው ሁሉ በመፍታት ህዝቡ በዓልን በተረጋጋ መንፈስ እንዲያከብር እየተሞከረ ነው ብለዋል::
https://www.press.et/Ama/?p=39072
የጥፋት ስትራቴጂስቱና ዋነኛው የጁንታ መሪ ስብሃት ነጋ በቁጥጥር ስር ዋለ
*******************
(ኢ ፕ ድ)
የጥፋት ስትራቴጂስቱና ዋነኛው የጁንታ መሪ ስብሃት ነጋን ጨምሮ ሌሎች የጥፋት ቡድኑ አመራሮች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የሀገር መከላከያ ሰራዊት አስታወቀ።
በአኢትዮጵያ ላለፉት 27 አመታት የማተራመስ ስትራቴጂ የነደፈ ያስተባበረና ያደራጀ በመጨረሻም ጦርነት እንዲቀሰቀስ በማድረግ በሀገራችን ሰራዊት ላይ እጅግ ዘግናኝ ጦርነት በመክፈት ሰራዊቱን ያስጨፈጨፈው የጁንታው ቁንጮ ስብሃት ነጋ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የመከላከያ ሰራዊት ኃይል ስምሪት መምሪያ ኃላፊ ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ አያሌው ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት አስታውቀዋል።
ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ አያሌው ዛሬ እንደገለፁት፤ የጁንታው ቁንጮ አመራር ስብሃት ነጋ ከተደበቀበት ለሰው ልጅ እጅግ አስቸጋሪ የሆነ ሰርጥ ውስጥ በቁጥጥር ስር ውሏል።
የጁንታውን ቁንጮ ስብሀት፣ የጥፋት ቡድኑ አባላት በሰርጡ ውስጥ ተሸክመው በማስገባት ደብቀውት እንደነበር ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ ገልፀው፤ ጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊትና ሌሎች የፌዴራል የፀጥታ አካላት በጋራ ባደረጉት ፍተሻና አሰሳ ከተደበቀበት በማውጣት በቁጥጥር ስር አውለውታል።
በተጨማሪም ከመከላከያ የከዱ ሌሎች ከሃዲ የጁንታው ቡድን አመራሮች ከጁንታው መሪ ስብሃት ነጋ ጋር አብረው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ገልጸዋል።
እነዚሁ ከመከላከያ የከዱ የጁንታው ቡድን አመራሮች የጁንታውን ታጣቂ ሀይል በማዋጋትና በማሰልጠን እኩይ ዓላማቸውን ለማስፈፀም ሲሰሩ መቆየታቸውን ጠቁመው፣ በመጨረሻም የጁንታውን አመራር ዙሪያ ጥበቃ ሲያስተባብሩ ቆይተው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ገልፀዋል።
እነዚህኑ የጁንታው አመራሮች ለመከላከል በአካባቢው ጥበቃ ላይ የነበረ የጁንታው ታጣቂ ሀይልም መደምሰሱን ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ ተናግረዋል።
በዚሁ መሰረት በቁጥጥር ስር የዋሉት
1. የጁንታው ቁንጮ አመራርና የጥፋት ስትራቴጂስት ስብሃት ነጋ
2. ሌተናል ኮሎኔል ፀአዱ ሪች- የስብሃት ነጋ ባለቤትና ቀደም ሲል በጦር
ሃይሎች ሆስፒታል ሃኪም የነበረች፣ በኋላም በጡረታ የተገለለች፤
3. ኮሎኔል ክንፈ ታደሰ- ከመከላከያ የከዳ
4. ኮሎኔል የማነ ካህሳይ- ከመለካከያ የከዳ
5. አስገደ ገ/ ክርስቶስ- ከመሃል ሀገር ተጉዞ ቡድኑን የተቀላቀለና ለጊዜው
ሃላፊነቱ ያልታወቀ ግለሰብ
6. አምደማርያም ተሰማ ተወልደ፣ የክልሉ የቅሬታ ሰሚ ፅ/ቤት ኃላፊ
የነበረ
7. ኮማንደር በርሄ ግርማ፣ የክልሉ ልዩ ሀይል ሎጀስቲክ ሀላፊ የነበረ
በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን
8. የሜጀር ጀነራል ሃየሎም አርአያ ባለቤት የነበረችና ኑሮዋን በአሜሪካ አድርጋ የቆየች በኋላም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ወደ ጁንታው ተቀላቅላ የነበረች፣ ወይዘሮ አልጋነሽ መለስ ጁንታውን በመያዝ ኦፕሬሽን ሂደት ውስጥ ለማምለጥ ስትሞክር ገደል በመግባት ህይወቷ ማለፉን ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ አያሌው ገልፀዋል።
ሌሎች የጁንታው አመራሮችንም የማደኑ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ብርጋዴል ጀነራል ተስፋዬ አስታወቀዋል።
የጁንታው ቃል አቀባይ የነበረው ሴኩቱሬ ጌታቸው፣ የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ስራ አስኪያጅና የብሮድካስት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር የነበረው ዘርአይ አስገዶም፣ የድምጸ ወያኔ ሃላፊ የነበረው
አበበ አስገዶም እና የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ የነበረው ዳንኤል አሰፋ ከሹፌሮቻቸውና ከጥበቃዎቻቸው ጋር መደምሰሳቸው መገለጹ ይታወሳል።
በተመሳሳይ ወይዘሮ ቅዱሳን ነጋን ጨምሮ 9 የጁንታው ቁልፍ አባላት በቁጥጥር ስር መዋላቸው ትናንት ተገልጿል።
የገዳ ስርአት ለአለም ቅርስነት የተመዘገበበትን 4ኛ አመት የመታሰቢያ በአል ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ የገዳ ፓናል ውይይት በቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ እየተካሄደ ነው
*****************
(ኢ.ፕ.ድ)
መርሃግብሩ የተጀመረው በገዳ አባቶች ምርቃት ሲሆን፣ በመርህግብሩ የተገኝኙት የፌዴራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሀብታሙ ሲሳይ፣ የምእራብ ጉጂ ዞን ዋና አስተዳዳሪ እንዲሁም የቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ጫላ ዋታን ጨምሮ አባ ገዳዎች ፣ ሀደ ስንቄዎች እና የተለያዩ እንግዶች ናቸው።
በዝግጅቱ ላይ የገዳ ስርአትን የተመለከቱ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ይካሄድባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል።
መርሃግብሩን ያዘጋጀው የኦሮሚያ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ከቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ እና ከምእራብ ጉጂ ዞን ጋር በጋራ በመሆን ነው።
ውይይቱ ዛሬን ጨምሮ ነገም የሚቀጥል መሆኑ ታውቋል።
‹‹ለሱዳን ትንኮሳ ቸኩለን ምላሽ መስጠት አይገባንም››
-ዶ/ር ኢንጅነር ጥላሁን ኤርዱኖ
በአዳማ ዩኒቨርሲቲ የካርታ ምህንድስና መምህር
**************************
(ኢ ፕ ድ)
ሱዳን በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ላደረገችው የመሬት ወረራ ትንኮሳ ፈጥኖ የኃይል ምላሽ መሥጠት እንደማይገባ የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዶክተር ኢንጅነር ጥላሁን ኤርዱኖ አስታወቁ፡፡
ዶ/ር ኢንጅነር ጥላሁን ኤርዱኖ ለአዲስ ዘመን እንዳስታወቁት፤ የሱዳን ጦር በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ለፈፀመው የመሬት ወረራ ቸኩሎ የኃይል ምላሽ መሥጠት ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል። በተለይም ውስጣዊውን ችግር በተሟላ ሁኔታ መፍታት ባልተቻለበት በዚህ ወቅት ወደ ኃይል ምላሹ መግባት አገሪቱን ያላሰበችው አደጋ ውስጥ ሊጥላት ይችላል፡፡
እንደእርሳቸው ገለፃ፤ ሱዳንም ሆነች ግብፅ በኢትዮጵያ ላይ እያደረጉት ያሉት ትንኮሳ ዋነኛ አላማ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ለማስተጓጎል ነው፡፡ በተለይም ሱዳን የቅኝ ግዛት ውልን በማጣቀስ ያደረገችው ትንኮሳ ግድቡ የሚገነባበትን አካባቢ ሰላም በማወክ ውሃውን ከግብፅ ጋር ብቻ የመጠቀም ፍላጎታቸውን ለማስቀጠል ከመሻት ነው፡፡ ከትንኮሳ በስተጀርባም የግብፅ ወታደራዊ መንግሥት እጅ ያለበትና ከፍተኛ ድጋፍ የሚደረግለት ነው፡፡
‹‹የሱዳን ዋነኛ ፍላጎት ቸኩለን እንድንገጥማት ነው›› ያሉት ዶክተር ጥላሁን ይህንን ማድረጉ ደግሞ አገሪቱ ካለችበት ፖለቲካዊ ችግር ጋር ተዳምሮ ከፍተኛ ዋጋ ሊያስከፍል እንደሚችል ሥጋታቸውን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የትንኮሳውን ዋነኛ አላማ በመረዳት ትክክለኛውን ጊዜ መጠበቅ እንደሚገባው አመልክተዋል፡፡
መላው ኢትዮጵያውያንም እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ ለአገራቸው ሰላም በህብረት መቆም እንደሚገባቸው የተናገሩት ዶክተር ጥላሁን ለዚህ ደግሞ በብሔርና በጎሳ ለመለያየት የሚደረገውን የጠላት ኃይሎች ጥረት እንዳይሰምር በጋራ ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
https://www.press.et/Ama/?p=39157
ኢዜማ የምርጫ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አስታወቀ
******************
(ኢ ፕ ድ)
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሲያካሂድ የነበረውን የምርጫ ዝግጅት ማጠናቀቁን አስታወቀ።
ፓርቲው ለዝግጅት ክፍሉ ትናንት በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ምርጫ ቦርድ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ይፋ መደረጉን ተከትሎ ምርጫው ላይ በንቃት ለመሳተፍ እና ምርጫው ሰላማዊ፣ ነፃ እና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሲያደርግ የነበራቸውን ዝግጅቶች አጠናቆ ወደትግበራ እየገባ ነው።
ለምርጫው ሲያደርግባቸው ከቆየባቸው ዝግጅ ቶች መካከል አባላት እና ደጋፊዎች በምርጫ እንቅስቃሴ ወቅት ሊመሩበት የሚገባ የምርጫ ሥነ-ምግባር መመሪያ ይፋ መሆኑን አመልክቷል።
ይህ መመሪያ ቀጣዩ ምርጫ ለሀገራችን ሰላም እና መረጋጋት እንዲሁም ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ያለውን ፋይዳ ከግምት በማስገባት የተዘጋጀ መሆኑን ያመለከተው መግለጫው፣ መመሪያው ለአባላት እና ደጋፊዎች ታትሞ እንደሚሰራጭ አስታውቋል፡፡ በመመሪያው ዙሪያ ሥልጠናም እንደሚሰጥ ጠቁሟል።
https://www.press.et/Ama/?p=39158
የጁንታው ከፍተኛ አመራሮች በጅግናው የሀገር መከላከያና የጸጥታ ሃይሎች ትብብር መያዛቸው ትላንት መገለጹ ይታወቃል። ከእነዚህ መካከል ስብሀት ነጋ፣ ቅዱሳን ነጋና ሌሎች የጁንታው አመራሮች ከላይ በምስሉ የሚታዩት ናቸው።
ስብሃት ነጋን ጨምሮ በቁጥጥር ስር የዋሉ ዘጠኝ የጁንታው አመራሮች አዲስ አበባ ገቡ
*********************
(ኢ.ፕ.ድ)

የጥፋት ስትራቴጂስቱና ዋነኛው የጁንታ መሪ ስብሃት ነጋን ጨምሮ በቁጥጥር ስር የዋሉ ዘጠኝ የጁንታው አመራሮች አዲስ አበባ ገብተዋል።

የሀገር መከላከያ ሰራዊት የጥፋት ስትራቴጂስቱና ዋነኛው የጁንታ መሪ ስብሃት ነጋን ጨምሮ ሌሎች የጥፋት ቡድኑ አመራሮች በቁጥጥር ስር ማዋሉን መግለጹ ይታወሳል።

የጁንታው አመራሮች የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የፌደራል ፖሊስና ሌሎች የፌደራል ጸጥታ ተቋማት ባደረጉት ፍተሻና አሰሳ ከተደበቁበት ለሰው ልጅ እጅግ አስቸጋሪ የሆነ ሰርጥ ውስጥ ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት።

የጥፋት ቡድኑ አመራሮችን ለመከላከል በአካባቢው ጥበቃ ላይ የነበረ የጁንታው ታጣቂ ሀይል መደምሰሱም በወቅቱ ተገልጿል።



በዚሁ መሰረት


1.የጁንታው ቁንጮ አመራርና የጥፋት ስትራቴጂስት፣ ስብሃት ነጋ

2.ቅዱሳን ነጋ -የትግራይ ክልል አፈ ጉባኤ የነበረች

3. ቴዎድሮስ ሀጎስ-የመለስ አመራር አካዳሚ ፕሬዚዳንትና የኢፈርት ቦርድ ሃላፊ የነበረ፣

4. አባዲ ዘሙ-በሱዳን የኢትዮጵያ የቀድሞ አምባሳደር የነበረና የጁንታውን ፖለቲካ ክንፍ የተቀላቀለ፣

5. ዶክተር ሰለሞን ኪዳኔ -የቀድሞ የትግራይ ክልል ከተማ ልማት ቢሮ ሃላፊና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊ የነበረ፣

6. ገብረመድህን ተወልደ-የክልሉ ንግድ ቢሮ ሃላፊ የነበረ፣

7. ወልደጊዮርጊስ ደስታ-የክልሉ መንገድ ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊ የነበረ፣

8. ተክለወይኒ አሰፋ-የማረት ስራ አስፈጻሚ የነበረ፤

9. ወይዘሮ ምህረት ተክላይ - የክልሉ ምክር ቤት ህግ አማካሪ የነበረች፤ ሁሉም በዛሬው እለት አዲስ አበባ ገብተዋል።

የምዕራብ እዝ ዋና አዛዥ ሜጀር ጀኔራል መሰለ መሰረት ለኢዜአ እንዳሉት፤ ጀግናው የመከላከያ ሰራዊት በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ የጁንታውን ሃይል ድል አድርጎ አሁን ደግሞ የቡድኑን አመራሮች በቁጥጥር ስር እያወለ መሆኑን ተናግረዋል።

ሰራዊቱ በህግ ማስከበርና ህልውና ዘመቻ አንፀባራቂ ድሎችን ያስመዘገበ መሆኑን ጠቅሰው፤ የሀገር መከላከያ ሰራዊት የጥፋት ስትራቴጂስቱና ዋነኛው የጁንታ መሪ ስብሃት ነጋን ጨምሮ ሌሎች የጥፋት ቡድኑ አመራሮች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ነው የተናገሩት።

እንደ ኢዜአ ዘገባ፤ የ24ኛ ክፍለጦር አዛዥ ኮሎኔል አማረ በዓታ በበኩላቸው፣ ሰራዊቱ ሌት ተቀን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ቀሪ የጁንታው ቡድን አመራሮች ከያሉበት እያደነ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከል
እየተመረቀ ነው
***************************
(ኢ ፕ ድ)
የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከል የሚገኘው በጥንታዊቷና ታሪካዊቷ ከተማ በአንኮበር ነው፡፡
በ333 ዓ.ም የተመሠረተችው አንኮበር ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የበርካታ ነገሥታት መቀመጫ እንደነበረችና ሌሎች ነገሥታትም ከሌላ አካባቢ ወደ አንኮበር መጥተው ንግሥናቸዉን ሲቀበሉ እንደነበረ የአንኮበር ወረዳ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት አስታውቋል፡፡
አንኮበር ከተቆረቆረች ጊዜ ጀምሮ ለበርካታ የሸዋ ነገሥታት መቀመጫ በመሆን አገልግላለች። 38 ነገሥታትም ነግሰውባታል። ከ15ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህም አምሀየሱስ፣ አስፋው ወሰን፣ ወሰን ሰገድ፣ ሳኅለስላሴ፣ ኀይለመለኮትና ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ነግሰውባታል። መቀመጫቸው አድርገዋትም ሀገር አስተዳድረዋል።
ይህች የጥንታዊ ነገሥታት መቀመጫ የበርካታ ባሕላዊ ትውፊቶችና ታሪካዊ እንዲሁም ሃይማኖታዊ ቅርሶች መገኛ ናት።
የወረዳው ባሕልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ኀላፊ ፈለቀ ምሕረት ለአብመድ እንደተናገሩት ጥንታዊ የብራና መጻሕፍት፣ የወርቅ ጽናጽል፣ የብር ከበሮ እና መቋሚያን ጨምሮ በወቅቱ የነገሥታቱ መገልገያ የነበሩ በርካታ ታሪካዊ ቅርሶች መገኛ ናት።
እነዚህን ቅርሶች በተደራጀ ቦታ ለማስቀመጥና ለጉብኝት ክፍት አልነበሩም፣ ይልቁንም የተቀመጡት በወረዳው በሚገኙ 97 ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት ተበታትነው ነበር። በዚህም ምክንያት ቅርሶችን ከነታሪካቸው በሚፈለገው ደረጃ ለትውልድ ማስተዋወቅ አልተቻለም ብለዋል።
ወረዳውም በቱሪዝም ተጠቃሚ መሆን አልቻለም ነው ያሉት። አሁን አንኮበር ታሪኳን የምታስተዋውቅበትና ቅርሶቿንም የምታድስበት ዘመናዊ ቤተመዘክር እንደተገነባላት አስረድተዋል።
እንደ ኀላፊው ገለጻ ወረዳው ለቤተ መዘክሩ ግንባታ ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጎበታል። ቤተ መዘክሩ የደኀንነት ካሜራዎች ተገጥመውለታል። የክልሉ መንግሥትም ቅርሶች ከሰው ንክኪ ነፃ ሆነው እንዲጎበኙ የሚያስችል መስተዋት አሠርቷል።
ይህም ቅርሶች ለጉብኝት ክፍት እንዲሆኑ ከማስቻል ጀምሮ ደኀንነታቸው በአስተማማኝ መልኩ እንዲጠበቅ ያደርጋል ብለዋል። የወረዳውን የቱሪዝም እንቅስቃሴም በከፍተኛ ደረጃ ያነቃቃል ተብሎ ታምኖበታል።
ወረዳውም ቱሪዝሙን ይበልጥ ለማነቃቃት በቤተ መዘክሩ አጠገብ ደረጃውን የጠበቀ የእንግዶች ማረፊያ ለመገንባት እንቅስቃሴ ጀምሯል።
የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከልም በዛሬው ቀን እየተመረቀ መሆኑን አብመድ ዘግቧል።
የ2013 ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በሰላም መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ
***************************
(ኢ ፕ ድ)
ዛሬ መነሻውን መስቀል አደባባይ መዳርሻውን አክሱም ህንፃ አካባቢ ያደረገው ታላቁ ሩጫ ያለምንም የፀጥታ ችግር በሰላም መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ለ20ኛ ጊዜ በተደረገው የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር የውጭ ሀገር ዜጎችን ጨምሮ በርካታ የከተማችን ነዋሪዎች ተሳትፈውበታል፡፡
ለውድድሩ በሰላም መጠናቀቅ የከተማዋ ነዋሪዎች፣ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፣ የፌዴራል ፖሊስና ሌሎች የፀጥታ አካላት፤ እንዲሁም የፕሮግራሙ አዘጋጆች እና የተሳታፊዎች ቀና ትብብር ለስነስርዓቱ በስኬት መጠናቀቅ አስተዋፅዖ የላቀ በመሆኑ ለሁሉም አካላት ኮሚሽኑ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡
የ20ኛው የ2013 ዓ.ም የታላቁ ሩጫ የወንዶች አሸናፊዎች
1ኛ. አቤ ጋሻሁን - ከአማራ ማረሚያ
2ኛ. ታደሰ ወርቁ - ደቡብ ፓሊስ
3ኛ. ሚልኬሳ መንገሻ - ከሰበታ ክለብ
የ20ኛው የ2013 ዓ.ም የታላቁ ሩጫ የሴቶች አሸናፊዎች
1ኛ. ፅጌ ገ/ሰላማ - ከኢትዮ አትሌትክስ
2ኛ. መድን ገ/ስላሴ - ከንግድ ባንክ
3ኛ. ገበያነሽ አያሌው - ከመከላከያ
አቶ ተፈራ ዋልዋ ከሁለት አመት በፊት ስለ ለውጡና ስለ ጁንታው እንዲህ ብለው ነበር
👉 አብይ እና አብይን የመሳሰሉ ጭንቅላቶች ለሀገራችን የዘመኑ ጭንቅላቶች ናቸው፤
👉 ፈጥኖ መሄድ የሚችል ጭንቅላቶች ለውጥ ፈላጊ ጭንቅላቶች ናቸው፤ ለውጡ ደግሞ ዝም ብሎ ተነካኪ ለውጥ አይደለም፤ ተሻግሮ የሚሄዱ ለውጦችን ማምጣት የሚፈልጉ ጭንቅላቶች ናቸው፤
👉 ታዲያ ይሄ ኢትዮጵያን ማሸጋገር አይችልም ብሎ ማሳብ እንዴት ይቻላል፤
👉 ይሄ ኢትዮጵያን ያበላሻል ብለው የሚያስቡ እዛው ድሮ የነበረ ቦታ ላይ ቆሞ የቀረ አስትሳሰብ የያዘ ሰው ብቻ ነው፤ ወይም ደግሞ እኛ ያለፍንበትን ረስተዋል ማለት ነው፤
👉 እኛ ስንታገል በትልልቅ ሰዎች “ተማሪ ጠግቦ፤ አይ የልጅ ነገር” ይባል ነበር፤ ግን እድላቸውን የሚወስን ጉዞ ውስጥ ነበር የምንጓዘው፤ አሁንም የሆነው ይሄው ነው፤
👉 የዝምባብዌው ሙጋቤ በ90 አመታቸው አገር ለመምራት እኔ ነኝ ብለው ነበር፤ የእኔው ባልደረቦች እኛ በምናስበው መንገድ ነው ሁሉ ነገር መሄድ ያለበት ብለው ሲያስቡ የኢትዮጵያ ሙጋቤዎች ነው ያልኳቸው፤
👉 አሁን እነ አብይ የሚራመዱትን ጉዞ የዘመኑ ጉዞ ነው፤ የዘመኑ ሀይል ነው፤ ተገቢ ነው ይሄ ነው የበለጠ ይሄን አገር የሚያራምደው ብሎ ማሰብ ከተሳነን እኛ ራሳችን ያለፍንበትን መርሳት ነው፤
በመከላከያ ሠራዊት ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ያደረጉ ዋነኛ የጁንታው አመራሮች በቁጥጥር ስር ዋሉ
**************
(ኢ.ፕ.ድ)
አገርን ለመበታተን አቅደው በመከላከያ ሠራዊት ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ያደረጉ አሸባሪዎችና ዋነኛ የጁንታው አመራሮች በቁጥጥር ስር ዋሉ።
ከአገር መከላከያ ሠራዊቱን በማስከዳት ተግባር ላይ ተሰማርተው የነበሩና በጦርነቱ ከሠራዊቱ ከድተው ጁንታውን የተቀላቀሉ ጄኔራል መኮንኖች፣ ከፍተኛ መኮንኖች፣ መስመራዊ መኮንኖችና የግል ጥበቃዎቻቸው ላይ እርምጃ መወሰዱንም የመከላከያ ሠራዊት ሃይል ስምሪት መምሪያ ሃላፊ ብርጋዴል ጄኔራል ተስፋዬ አያሌው ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ገልጸዋል።
በዚሁ መሰረት እርምጃ የተወሰደባቸው
1ኛ- ሜጀር ጄኔራል ኢብራሂም አብዱልጀሊል፡- ቀደም ሲል የመከላከያ ሎጂስቲክ ሃላፊ የነበረና አሁን የጁንታው ሎጂስቲክ ሃላፊ የነበረ
2ኛ- ብርጋዴል ጄኔራል ገብረኪዳን ገብረማርያም፡- የመከላከያ ኢንዶክትሪኔሽን ሃላፊ የነበረና በጡረታ ከተሰናበተ በኋላ ጁንታውን የተቀላቀለ
3ኛ- አስር ከፍተኛ መኮንኖች
4ኛ - ሁለት መስመራዊ መኮንኖች
5ኛ- አንድ የክልሉ ረዳት ኮሚሽነር የነበረና ከፖሊስ ከድቶ ወደ ጁንታው የተቀላቀለ ናቸው።
በተጨማሪም የክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩ የጁንታው አመራሮች በቁጥጥር ስር ውለዋል
እነዚህም
1ኛ- አቶ አባይ ወልዱ፡- የቀድሞ የክልሉ ፕሬዚዳንት የነበረ
2ኛ- ዶክተር አብርሃም ተከስተ- የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት የነበረ
3ኛ- ዶክተር ረዳኢ በርሄ፡- የክልሉ ኦዲተር ሃላፊ የነበረ
4ኛ ዶክተር ሙሉጌታ ይርጋ፡- የክልሉ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ ሃላፊ የነበረ
5ኛ- አቶ ዕቁባይ በርሄ- የሃይማኖት ጉዳይ ክትትል ሃላፊ የነበረ
6ኛ- አቶ ጌታቸው ተፈሪ፡- የክልሉ ፕሬዚዳንት ፅህፈት ቤትና የሠላምና ደህንነት ሃላፊ የነበረ
7ኛ- ወይዘሮ ኪሮስ ሃጎስ፡- የክልሉ ማህበራዊ ጉዳይ ሃላፊ የነበረች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ገልፀዋል።
በተጨማሪም ሁለት ከመከላከያ ከድተው ጁንታውን የተቀላቀሉ ከፍተኛ መኮንኖች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን እነሱም ኮሎኔል ገብረእግዚአብሄር አምባዬና ኮሎኔል ትርፏ አሰፋ መሆናቸውን ብርጋዴል ጄኔራሉ ገልፀዋል።
በእጸገነት አክሊሉ
ኢፋ ሊበን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተመረቀ
*************************
(ኢ ፕ ድ)
በቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን ሊበን ጭቋላ ወረዳ በ20 ሚሊዩን ብር ወጪ የተገነባው ኢፋ ሊበን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተመረቀ፡፡
በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ለተማሪዎቹ ዩኒፎርም ፣ቦርሳና የሙቀት መለኪያ መሳሪያዎች ለትምህርት ቤቱ በስጦታ ተበርክተዋል፡፡
ትምህርት ቤቱ በዉስጡ የአስተዳደር ህንጻ፤የመማሪያ ክፍሎች ፤ላብራቶሪ፤ ቤተ መጽሀፍት፣ የኮምፕዩተር ላብራቶሪና የመጸዳጃ ህንጻዎችን ያካተተ ነው፡፡
ጽ/ቤቱ ካሰራቸዉ 20 ትምህርት ቤቶች ዉስጥ በዛሬዉ እለት ያስመረቀዉ የኢፋ ሊበን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታቸዉ ተጠናቆ ከተመረቁት አምስተኛዉ ሲሆን ቀሪዎቹን ትምህርት ቤቶችን በቅርቡ በሁሉም ክልሎች ያስመርቃል፡፡
ትምህርት ቤቱ በሙሉ አቅሙ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር በአንድ ፈረቃ 1300 ተማሪዎችን የመቀበል አቅም አለዉ፡፡ የቀዳማዊት እመቤት ጽ/ቤት በትምህርት ቤት እርቀትና እጥረት ምክንያት ልጆቻቸዉን ወደ ትምህርት ገበታ ላልላኩ የሊበን ጭቋላ፣ አዱላላ፣ቆቃ እና የአካባቢዉ ነዋሪዎች ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤቱ በመላክ እድሉን እንዲጠቀሙ ጥሪ ማስተላለፉን ከቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡