Gazette Plus / ጋዜጣ ፕላስ/
25.1K subscribers
41K photos
338 videos
7 files
5.81K links
Ethiopian Press Agency, established in 1940 , is a public printing media enterprise operating in Ethiopia.
Download Telegram
በአዲስ አበባ የገጽ ለገጽ ትምህርት ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ በየደረጃው እንደሚጀመር ተገለጸ
********************
(ኢ ፕ ድ)
በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የገጽ ለገጽ ትምህርት ከፊታችን ሰኞ (ህዳር 21 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በየደረጃው እንደሚጀመር ትምህርት ቢሮ አስታወቀ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ሀላፊ አቶ አዲሱ ሻንቆእንዳስታወቁት፤ በግል ትምህርት ቤቶቸ ከ1ኛ ክፍል ጀምሮ ህዳር 21 ቀን 2013 ዓ.ም ትምህርት ይጀመራል።
በመንግስት ትምህርት ቤቶች ከ5ኛ ክፍል ጀምሮ ህዳር 28 ቀን 2013 ዓ.ም እንደሚጀመር አቶ አዲሱ ተናግረዋል።
ከአንደኛ እስከ አራተኛ ክፍል ያሉ የመንግስት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የመማሪያ ክፍል ግንባታ እስኪጠናቀቅ በቤት እንደሚቆዩ የገለጹት አቶ አዲሱ፤ ወላጆች ለልጆቻቸው ድጋፍ እንዲያደርጉላቸው ጠይቀዋል።
በመንግስትም በግልም ትምህርት ቤት ያሉ የቅድመ ትምህርት (ኬጂ) የገጽ ለገጽ ትምህርቱ ለተወሰነ ጊዜ እንደማይጀመርም አስታውቀዋል።
በእነጀዋር መሀመድ የክስ መዝገብ ተከሳሾች ባቀረቡት ቅሬታ ላይ አቃቤ ህግ የፅሁፍ መቃወሚያውን አቀረበ
**********************
(ኢ ፕ ድ)
የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት የዐቃቤ ህግን መቃወሚያ ለመስማት ለህዳር 18 ቀን 2013 ዓ.ም በሰጠው ቀጠሮ መሰረት ዐቃቤ ህግ መቃወሚያውን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል፡፡
በዚህ ችሎት ላይ ተከሳሾች አቶ ጀዋር መሀመድ እና አቶ በቀለ ገርባ ወደ ችሎቱ ያልቀረቡ ሲሆን ለዚህም፤ በሀገሪቱ ውስጥ ካለው ወቅታዊ ሁኔታ አንፃር እንዲሁም ባለን ፖለቲካዊ ተሳትፎ የተነሳ እንዲሁም በማረሚያ ቤቱ እና በፍርድ ቤት መሀከል ያለው እርቀት ሰፊ በመሆኑ ሁኔታው የፀጥታ ስጋት ፈጥሮብናል፤ በዚህ ምክንያትም መቅረብ አልቻልንም በመሆኑም በቀጣይ ለሚኖረው የፍርድ ሂደት በአቅራቢያችን ጊዜያዊ ችሎት ይቋቋምልን የሚል አቤቱታቸውን በጠበቆቻቸው በኩል በፅሁፍ አቅርበዋል፡፡
ከዚህም ሌላ ዐቃቤ ህግ 11ኛ ተከሳሽ አቶ ደጀኔ ጉተማ፣ 14ኛ ተከሳሽ አቶ ብ/መስቀል አበበ እና 15ኛ ተከሳሽ አቶ ፀጋዬ ረጋሰ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ለማድረግ በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው ሊቀርቡ ስላልቻሉ በሌሉበት ክሳቸው እንዲታይ ትዕዛዝ እንዲሰጥበት ጠይቆ፤ ተከሳሾች በተቋሙ ላይ ላቀረቡት ቅሬታ በፅሁፍ ምላሽ መስጠቱን ገልጾ ነገር ግን ጠቅላይ ዐቃቤ ህጉ እንዲቀርቡ የተፃፈ ትዕዛዝ ባለመኖሩ ሊቀርቡ አለመቻላቸውን አስረድቷል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው የፌዴራል 1ኛ የፀረ ሽብርና ህገ-መንግስት ጉዳዮች ችሎት፡-
1. በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው ያልተገኙ ተከሳሾችን በሚመለከት ክሳቸው በሌሉበት እንዲታይ ወስኗል፤
2. በሌላም በኩል እነ አቶ ጀዋር መሀመድ ያቀረቡትን ጊዚያዊ ችሎት ይቋቋምልን ጥያቄ ለፍርድ ቤቱ አስተዳደር አቅርቦ ምላሽ እንዲሰጥበት እንደሚደረግ፤
3. ጠቅላይ ዐቃቤ ህጉ በግለሰብ ደረጃ ቀርበው ምላሽ ይስጡበት ለሚለው የተከሳሾች ቅሬታ ላይ ለትዕዛዝ ለመስጠት በሚድያ ቀረበ የተባለው አስተያየት በእንግሊዘኛ እና አማርኛ ኮፒ ተደርጎ በሲዲ ከቀረበ በኋላ ትዕዛዝ የሚሰጥበት መሆኑን በመግለፅ ቀጣዩን ቀጠሮ ለታህሳስ 08 ቀን 2013 ዓ.ም በማድረግ የእለቱ ችሎት ተፈፅሟል፡፡
ጁንታው ተስፋ በመቁረጥ ድልድዮችንና መንገዶችን ቢያፈርስም የሰራዊቱን እንቅስቃሴ መግታት እንዳልቻለ ተገለጸ
*****************
(ኢ ፕ ድ)
ራያ ግንባር፡- ጁንታው ህግን ለማስከበር በራያ ግንባር የተሰማራውን መከላከያ ሰራዊት እንቅስቃሴ ለመግታት ድልድዮችንና መንገዶችን ቢያፈርስም ሰራዊቱ መሰናክሎቹን እያለፈ ወደፊት መገስገሱን ከፍተኛ የጦር መኮንኖች ገልጸዋል፡፡
የ21ኛ ጉና ክፍለ ጦር ምክትል አዛዥና የሎጂስቲክ ክፍል ሃላፊ ኮሎኔል የሱፍ አደም እንደገለጹት፤ ጀግናው መከላከያ ሰራዊት በራያ ግንባር ህግን የማስከበር ርምጃ መውሰድ ከጀመረ ወዲህ ጁንታው የሚመካባቸውን ምሽጎችና ከባድ መሳሪያዎች በመደምሰስ ወደፊት እየገሰገሰ ነው።
የተሰጡትን ተደጋጋሚ የሰም አማራጮች አልቀበልም በማለት ጦርነትን የመረጠው ይህ ስግብግብና ከሀዲ የህወሓት ቡድን የመረጠው መንገድ እንደማያዋጣው ሲያውቅና አቅሙ ሲዳከም መሰረተ ልማቶችን እያወደመ መሸሽ ጀምሯል ብለዋል፡፡
የጁንታው ታጣቂዎች ‹‹ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል›› በሚል በከፍተኛ ወጪ የተገነቡ ኮንክሪት የአስፋልት መንገዶችን፣ ድልድዮችን እና ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ መስመሮችን በዶዘር በመቆፈር እና ቆርጦ በመጣልና መንገድ በመዝጋት የሰራዊቱን እንቅስቃሴ ለመግታት ሞክሯል ያሉት ሃለፊው፤ ቡድኑ ድልድዮችን አፍርሷል፤ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊ ገመዶችን በጣጥሷል፤ ትምህርት ቤቶችን፣ የመንግስት መገልገያ ተቋማትንና ቤተ እምነቶችን ማረፊያና ምሽግ አድርጓቸዋል ነው ያሉት፡፡
መከላከያ ሰራዊቱ በአንድ በኩል እየተዋጋ በሌላ በኩል የጥፋት ቡድኑ የሚያፈርሳቸውን መንገዶችና ድልድዮችን እየሰራ ተሸከርካሪዎችን በማሳለፍ የጁንታውን እጅ ለመያዝ የሚያደርገውን ጉዞ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡
ሰራዊቱ ወደ ግዳጅ ሲገባ አስፈላጊ ናቸው የተባሉ ሎጂስቲኮችን በሙሉ ማሟላቱን የገለጹት ኮለኔሉ፤ ከዚህ በተጨማሪ ከጁንታው ነጻ በወጡ ከተሞች ያለው ህዝብ ሳይቀር የሚያደርግለት ድጋፍም ሌላ አቅም ፈጥሮለታል ነው ያሉት፡፡
ተፈጥሯዊም ሆነ ሰው ሰራሽ መሰናክሎችን እያለፈ ለመሄድ የሚያስችል የተሟላ የሎጂስቲክ አቅም ስላለው ምንም አይነት እንቅፋት ቢገጥመው ወደፊት ከመሄድ የሚከለክለው አንዳችም ነገር የለም ብለዋል፡፡
ጁንታው አስራ አንደኛው ሰዓት ላይ ሆኖም እንኳ የጥፋት እጆቹን መሰብሰብ አልቻለም ያሉት ኮለኔሉ፤ በወንጀል ላይ ሌላ ወንጀል እየሰራ መሆኑን በመግለጽ፤ በቅርቡም ከሀዲና ወንጀለኛዎቹን የህወሓት አባላት ለህግ እንደሚያቀርቡ ያላቸውን እምነት ገልጸውልናል።
በኢያሱ መሰለ
በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ስም የታተሙ ህገ ወጥ መታወቂያዎች ተገኝተዋል
**************
(ኢ.ፕ.ድ)

በራያ አላማጣ ከተማ ከአንድ የመንግስት ቢሮ ውስጥ በርካታ በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ስም የታተሙ ህገ ወጥ መታወቂያዎች ተገኝተዋል።

በስፍራው አግኝተን ያነጋገርናቸው ምክትል ኮማንደር ጥላሁን ታደሰ እንደገለፁት ይህን መታወቂያ የሚጠቀሙት ግለሰቦች በአማራ ህዝብ ስም ወንጀልና የሽብር ጥፋት ለማድረስ ነው ብለዋል።

ይህ የትህነግ ድርጊት በተለያዩ አካባቢዎች በአማራ ህዝብ ስም ወንጀል በመፈፀም የአማራን ህዝብ ከሌሎች ብሄረሰቦች ጋር ለማጋጨት ያሴሩት ሴራ ነው ሲሉ ምክትል ኮማንደሩ ጨምረው ገልፀዋል።

ሁሉም የሀገራችን ህዝብ እና የፀጥታ አካላት መታወቂያ በሚያዩበት ጊዜ በደንብ ማስተዋል ይገባል።አጠራጣሪ ሁኔታ ሲያጋጥም ደግሞ ከሚመለከታቸው አካላት ማረጋገጥ ይገባል ሲሉ ምክትል ኮማንደር ጥላሁን ታደሰ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ምንጭ- የአማራ ክልል ፓሊስ ኮሚሽን
የሀገር መከላከያ ሰራዊቱን በሙያቸው ለማገዝ ሁለተኛ ዙር የአዲስ አበባ የህክምና ባለሙያዎች ልዑካን ወደ ስፍራው አቀኑ
*************
(ኢ.ፕ.ድ)

ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከተለያዩ ሆስፒታሎች የተውጣጡ ከ60 በላይ የጤና ባለሙያዎችን እና ሁለት ድጋፍ ሰጪ አምቡላንሶች ለመከላከያ ሰራዊት ሙያዊ ድጋፍ ለመሰጠት ወደ ስፍራው አቅንተዋል ።

የአዲስ አበባ ከተማ ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዮሐንስ ጫላን ጨምሮ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ለህክምና ባለሙያዎች አሸኛኘት አድርገዋል ።

የሀገር ጥሪን በመቀበል ሰራዊቱን በሙያቸው ለማገዝ ዝግጁ መሆናቸውን የገለጹት የጤና ባለሙያዎቹ በዚህም ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል ፡፡

በመጀመሪያው ዙር 48 የህክምና ባለሙያዎች የሀገር መከላከያ ሰራዊቱን በማገልገል ላይ እንደሚገኙ ከአዲስ አበባ ፕሬስ ሴክረተሪያት ያገኘነው መረጃ ያሳያል።
በአንድ ሳምንት ከ42 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የተለያዩ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ተያዙ
*****************
(ኢ.ፕ.ድ)

ከህዳር 11 ጀምሮ ባለው የአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ግምታዊ ዋጋቸው ከ42 ሚሊዮን 749 ሺህ በላይ የሚያወጡ የኮንትሮባምድ ዕቃዎች መያዙ ተገለጸ።

የተያዙት እቃዎች የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች ጥይት፣ አደንዛዥ ዕጽ፣ ቡና፣ ግመሎች እና የተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች መሆናቸውና በተለያዩ የጉምሩክ መቆጣጠሪያ ጣቢያዎች መያዛቸውን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታውቋል።

ኮንትሮባንድ ዕቃዎቹ በአዲስ አበባ ኤርፖርት፣ በሐዋሳ፣ በጅግጅጋ፣ በድሬዳዋ፣ በሞያሌ፣ በባህርዳር፣ ጅማ፣ በአዳማ፣ በኮቦልቻ እና በአሶሳ ጉምሩክ ቅ/ጽ/ቤቶች የተያዙ መሆኑ ተገልጿል።

ዕቃዎቹ ሊያዙ የቻሉት በጉምሩክ ሠራተኞች፣ በአካባቢው ኅብረተሰብ ጥቆማ፣ በክልል ፖሊስ፣ በፌደራል ፖሊስ፣ በአድማ በታኝ እና በመከላከያ አባላት የጋራ ጥረት መሆኑም ለማወቅ ተችሏል።

ከኮንትሮባንድ ዕቃዎች ማስተላለፍ ጋር ተያይዞ የተለያዩ አካላት እና አሸከርካሪዎች በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው እየተጣራ ይገኛል ሲል የገቢዎች ሚኒስቴር አስታውቋል።
የትግራይ ሕዝብ ከስግብግቡ ጁንታ ጋር እንዳልሆነ በተግባር አስመስክሯል
- ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ

የመከላከያ ሠራዊት በድል በገሠገሠባቸው የትግራይ አካባቢዎች ሁሉ የትግራይ ሕዝብ ለሀገሩ ያለውን ፍቅርና ለመከላከያ ሠራዊቱ ያለውን ክብር አሳይቷል። ጁንታው ካስታsጠቃቸው ጥቂት የክፋት ኃይሎች ውጭ ያለው የትግራይ ሕዝብ መቀሌ እስኪገባ ድረስ ለመከላከያ ሠራዊቱ የሚጠበቅበትን ድጋፍ ሁሉ አድርጓል። ይህም የሠራዊቱን ድልና የጁንታውን ሽንፈት አፋጥኖታል።

ስግብግቡ ጁንታ በየትኛውም መመዘኛ ለትግራይ ሕዝብ አይመጥነውም። የትግራይ ሕዝብ ከእውነት ጋር በመቆምና የጁንታውን እኩይ ዓላማ በመፃረር ከቀበሌ ቀበሌ፣ ከዞን ዞን መቀሌ እስኪገባ ድረስ ተመሳሳይ ድጋፍ ለሠራዊቱ ሰጥቷል። ለዚህም ከፍ ያለ ምስጋናዬን አቀርባለሁ። ጁንታው በሸሸበት ከተማና አካባቢ ሁሉ የጤና ተቋማትን፣ ተ/ቤቶችን፣ ድልድዮችን፣ መንገዶችን፣ መሥሪያ ቤቶችን እያወደመ ሄዷል። በዚህም የገዛ ወገኑ ጠላት መሆኑን አሳይቷል። ጁንታው እኔ ከሞትኩ ብሎ ያፈረሳቸውን መሠረተ ልማቶች በፍጥነት በመገንባት የትግራይ ሕዝብ ወደ ሰላማዊ ኑሮው እንዲመለስ ለማድረግ የቻልነውን ሁሉ እንደምናደርግ ቃል እገባለሁ።

በዚህ ዘመቻችን ንጹሐን ዜጎች ዒላማ ሳይሆኑ፣ ከተሞቻችንና ቅርሶቻችን ሳይጎዱ መቀሌ ለመግባት ተችሏል።
ክብር ለሀገር መከላከያ ሰራዊታችን!!!
በህወሓት ጁንታ በክህደት ከጀርባው የተወጋው የሀገር መከላከያ ሰራዊታችን መላውን ትግራይ በከፍተኛ ጀግንነት ከጁንታው ጨቋኝ አገዛዝ ነጻ አውጥቷል::
የመከላከያ ኤታማዦር ሹም ጀነራል ብርሃኑ ጁላ ሰራዊቱ መቀሌን መቆጣጠሩን ከገለጹ በኃላ ኢትዮጵያውያን በተለያዩ ከተሞች ደስታቸውን ገልጸዋል፤ የሀገር መከላከያ ሰራዊትን አመስግነዋል፤ አውድሰዋል።:
ክብር ለመከላከያ ሰራዊታችን!!!
ክብር ዘላቂ ሰላምና የሕግ የበላይነት ለማረጋገጥ ለታገላችሁ!!!!
ክብር ለኢትዮጵያ!!!!!!
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ነገ በወቅታዊ
አገራዊ ጉዳዮች ላይ ለምክር ቤት አባላት ማብራሪያ ይሰጣሉ
******************************
(ኢ ፕ ድ)
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ነገ በወቅታዊ
አገራዊ ጉዳዮች ላይ ከምክር ቤት አባላት ለሚቀርቡላቸው ጥያቄዎች ማብራሪያ እንደሚሰጡ ተገለጸ።
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 5ኛው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት 6ኛ ዓመት የስራ ዘመን 2ኛ ልዩ ስብሰባ ህዳር 21 ቀን 2013 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በሚገኘው መሰብሰቢያ አደራሽ ከጠዋቱ 3:00 ጀምሮ ማካሄድ ይጀምራል፡፡
አጀንዳዎቹም
1. የም/ቤቱን 6ኛ አመት የስራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ስብሰባ ቃለ ጉባኤ
መርምሮ ማጽደቅ፣
2. የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር አብይ አህመድ በወቅታዊ
አገራዊ ጉዳዮች ላይ ከምክር ቤት አባላት ለሚቀርቡላቸው ጥያቄዎች
የሚሰጡትን መልስ ማዳመጥ እንደሆነ ምክር ቤቱ አስታውቋል።
ሁለት ሻንጣ ሙሉ ብር ይዘው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ግለሰቦች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋሉ
*******************
(ኢ ፕ ድ)
በሁመራ ከተማ ሁለት ሻንጣ ሙሉ ብር ይዘው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ግለሰቦች በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገለፀ።
ዋና ሳጅን ታከለ እሸቴ ይባላል ፤የምዕራብ ጎንደር ዞን ፖሊስ መምሪያ ባልደረባ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ደግሞ በሁመራ ከተማ ሰላም እያስከበረ ይገኛል።
ህዳር 19 ቀን 2013 ዓ.ም ሰላም እያስከበረ በሚገኝበት ሁመራ ከተማ ላይ በአንድ በባለ ሶስት እግር ተሽከርካሪ(ባጃጅ) ላይ ሁለት ግለሰቦች ሁለት ሻንጣ ይዘው በመጓዝ ላይ ሳሉ ካለው ወቅታዊ ሁኔታ አኳያ ፍተሻ በሚያደርግበት ጊዜ ሁለቱም ሻንጣ ሙሉ ብር ሆኖ ተገኝቷል።
በወቅቱ ግለሰቦቹ "አንዱን ሻንጣ ሙሉ ብር እንስጥህና ልቀቀን"ቢሉትም ቃል የገባለትን ህዝብ እና ሙያውን በማስበለጥ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር እንዳዋላቸው የአማራ ፖሊስ ኮሚሽን መረጃ ያመለክታል።
በአሁኑ ሰዓት በሁለቱም ተጠርጣሪዎች ላይ ምርመራ እየተደረገ መሆኑም ተመልክቷል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያለፉባቸው ፈተናዎች
***************
(ኢ ፕ ድ)
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት መንበር ሲመጡ የነበሩበትን የሳንዱች አካሄድ (አስቸጋሪ ሁኔታ) ለምክር ቤቱ ተናገሩ።
👉 የሀይል ትንተና እና የሁኔታ ትንተናን በደንብ መስራት ካልተቻለ
የሚፈለገውን ነገር ማድረግ ህልም ይሆናል፤ በዚህ እውነታ
የሚያምን ሰው በጁንታው ላይ የተወሰደው እርምጃ ለምን ዘገየ
አይልም፤ ምክንያቱም የነበርንበት ሁኔታ ፍጹም አስቸጋሪ ነበር፤
👉 ጠቅላይ ሚኒስትር በሆንኩ እለት የግል ጠባቂዎችን እንኳን ይዤ መግባት እንደማልችል በደህንነት ሹሙ ተነግሮኛል፤ የግል ጠባቂዎቼን እንኳን ማዘዝ አልችልም ነበር፤ እንኳንስ አገር ልመራ፤
👉 የቤቴ እና የቢሮዬ ቁልፍ እንኳን በደህንነት ሰዎች እጅ ነበር፤
እንኳንስ የአገርን ደህንነት ልጠብቅ ይቅርና የልጆቼን ደህንነት እንኳን ማረጋገጥ በማልችልበት ሁኔታ ውስጥ ነበርኩ፤
👉 የቢሮዬን ግቢ እንኳን ለማየት ስጠይቅ አትችልም ተብዬ ተከልክዬ ነበር፤ በወቅቱ በአጭሩ ዘመናዊ እስር ቤት ውስጥ የነበረ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆኔን ተረዳሁ፤
👉 ይሄንን ሁኔታ ለመቀየር በተለይ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ስራዎችን ሰርተናል፤
👉በወቅቱ የመጀመሪያ ጉዞዬ የነበረው ወደሶማሌ ክልል ነበረና ለመሄድ ፈልጌ አትሄድም ተብዬ ተከልክዬ ነበር፤
👉ቀጣዩ ጉዞዬ መቀሌ ነበረና ወደዛ ሄድኩ ተወያይቼ ስመለስ ጁንታው ከፍተኛ መደናገጥ ውስጥ ገባ፤ ስለሆነም ከህዝቡ መለየት አለብን የሚል ምክር አደረጉ፤
👉ቀጣዩ ጉዞዬ ወደ አንቦ ለመሄድ ስነሳ አትሄድም ተብዬ ተከለከልኩ፤ ተጨማሪ ጥበቃ አድርጌ ሄድኩ፤
“ባለፉት ሁለት አመታት በኢትዮጵያ ውስጥ ዋና ዋናዎቹን ብቻ ብናይ 113 ግጭቶች ነበሩ”
- ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ
******************
(ኢ ፕ ድ)
👉 መንግስት ስራ እንዳይሰራ በተቀናጀ መልኩ በየቦታው ሽብር ይፈጠርለት ነበር፤
ባለፉት ሁለት አመታት ተኩል ውስጥ
👉 በኦሮሚያ ውስጥ ብቻ 37 ግጭቶች ነበሩ፤
👉 በአማራ ክልል 23 ግጭቶች ነበሩ፤
👉በቤባሻንጉል ጉሙዝ 15 ግጭቶች ነበሩ፤
👉 በአዲስ አባበ 14 ግጭቶች ነበሩ፤
👉በደቡብ፣ በጋምቤላ እና በተቀሩት የአገሪቷ ክልሎች ግጭቶች ነበሩ
👉 በሁሉም ክልልች ችግሮች አሉ፤ ትግራይ ብቻ ነው ሰላም የነበረው፤
👉 እነሱም አያፍሩም እኛ ብቻ ነን ስላም ይሉ ነበር፤ ዋናው የችግሩ
ባለቤቶች እነሱም ነበሮች፤
👉 አሰራራቸው ተራ አልነበረም፤ ገንዘብ፣ ስልጠና ስምሪት ሚዲያም
ነበራቸው፤
በመከላከያ ውስጥ የነበረውን የትግራይ ተወላጆች የበላይነት በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ተዘርዝሮ ተነግሯል
👉 መከላከያ ውስጥ የሙሉ ጀነራል ማዕረግ 60 በመቶ
በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነበር፤ የሌሎች ብሄሮች ድርሻ 40 በመቶ
ብቻ ነበር፤
👉 ሌተናል ጄነራል የትግራይ ተወላጆች 50 በመቶ ድርሻ ነበራቸው፤
👉 ሜጀር ጀነራል የትግራይ ተወላጆች 45 በመቶ ድርሻ ነበራቸው፤
በብርጋዴር ጀነራል ማዕረግ የትግራይ ተወላጆች 40 በመቶ ድርሻ
ነበራቸው፤
👉 በኮሎኔል ደረጃ 58 በመቶ የትግራይ ተወላጆች ድርሻ ነበራቸው፤
👉 በሌተናል ኮሎኔል ደረጃ 66 በመቶ በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነበር፤
👉 በሻለቃ ማዕረግ 53 በመቶ በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነበር፤
👉 እዞች ውስጥ አዛዥ መቶ በመቶ በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነው፤
👉 ምክትል አዛዥ መቶ በመቶ በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነበር፤
በሁሉም የሰሜን እዝ ላይ አዛዥ እና ምክትል አዛዥ ሎጂስቲክ እና
አስተዳደር በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነው፤
👉 ክፍለ ጦሮች ውስጥ የኢትዮጵያ ሜካናይዝድ ክፍለ ጦሮች መቶ
👉 በመቶ አዛዦቹ በትግራይ ተወላጆች የተያዙ ናቸው፤
👉 እግረኛ ክፍለ ጦሮች 80 በመቶ በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነው፤
👉 በመከላከያ ዋና መምሪያ ውስጥ 80 በመቶ በትግራይ ተወላጅ የተያዘ
ነበር፤
👉 ሜካናይዝድ ብርጌዶች 85 በመቶ እግረኛ ብርጌድ 80 በመቶ
በትግራይ ተወላጆች የተያዘ ነበር፤
👉 በመከላከያ ስልጠና ተቋማት ውስጥ 85 በመቶ በትግራይ ልጆች ነው
የሚመራ ነበር፤
አንደኛውን ጁንታ አባረን ሌላ ጁንታ እንዳንሆን ጥንቃቄ ያስፈልጋል ሲሉ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ አሳሰቡ
**********************
(ኢ.ፕ.ድ)
አንደኛውን ጁንታ አባረን ሌላ ጁንታ እንዳንሆን ጥንቃቄ ያሻል ሲሉ የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ አሳሰቡ፡፡
ጠቅላይ ሚንስትሩ ዛሬ 5ኛው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት 6ኛ ዓመት የስራ ዘመን 2ኛ ልዩ ስብሰባውን ባካሄደበት ወቅት በሰጡት ማብራሪያ እንደተናገሩት፤ “ከጁንታው ጋር በግል ጥላቻ የለኝም፤ እናንተም እንዳይኖራችሁ፡፡ የምንታገለውና ጠባችን ከአስተሳሰቡ ጋር ነው፡፡
በመሆኑም አንደኛውን ጁንታ ነቅለን ሌላ ጁንታ እንዳንሆን›› ብለዋል።
አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ እያለ በዘር እየከፋፈለ ያባላን ይሄ ጁንታ ነው፤ ስለዚህ በዘር የምንጣላ ከሆንን እኛም ጁንታዎች ነን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በትግራይ ክልል ውስጥ ያሉም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ያሉ የትግራይ ተወላጆች ከጁንታው ጋር ትስስር የሌላቸው ከሆኑ ኢትዮጵያዊ መሆናቸውን አምነን ማክበርና መጠበቅ አለብን ሲሉም አሳስበዋል።
ያለፈው አይነት በዘር የመከፋፈል አካሄድ እንዳይደገም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርበታል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በመከላከያም፣ በፖሊስም ሆነ በየትኛውም ሲቪል ስራዎች የትግራይ ተወላጆችን በሚመለከት አስፈላጊው ጥንቃቄ እና ጥበቃ መደረግ አለበት ሲሉም ተናግረዋል።
እንደ ጠቅላይ ሚንስትሩ ገለጻ፤ ባለፉት ጊዜያት የተወሰኑ የትግራት ተወላጆች ከስራ እንዲያርፉ ተደርጓል፡፡ ይህ የተደረገው በሁለት ምክንያቶች ነው። የመጀመሪያው በሰሜን ዕዝ እና በማይካድራ ላይ የፈጸመው ጭፍጨፋ እንዳይደገም ለማድረግ ሲሆን፤ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ እዚህም ብዙ ለጥቅም የተገዛና ለጥፋት የተሰለፈ ሃይል ስለነበረ ነው፡፡ በተጨባጭም ቤቱ ውስጥ ቦንብና ፈንጂ ያስቀመጠ ለእልቂት የተዘጋጁ ተገኝተዋል።
በመሀመድ ሁሴን
ከሀዲው የህወሓት ቡድን በውስጣቸው በፈጠረባቸው ከፋፋይነት የተነሳ ኢትዮጵያ በጎረቤት ሀገራት የምትጠላ ሆና እንደቆየች ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አስታወቁ
******************
(ኢ ፕ ድ)
ከሀዲው የህወሓት ቡድን በአገራቱ ውስጥ በፈጠረው ከፋፋይነት የተነሳ ኢትዮጵያ በጎረቤት ሀገራት የምትጠላ ሆና እንደቆየች የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ አስታወቁ።
5ኛው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት 6ኛ ዓመት የስራ ዘመን 2ኛ ልዩ ስብሰባውን ዛሬ ባካሄደበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ማብራሪያ፤ ከሀዲው የህውሓት ቡድን ኢትዮጵያን በክልልና በዘር ከመከፋፈል አልፎ ጎረቤት ሀገራትን ጭምር በጎሳና በዘር ሲያባላ እንደነበር ተናግረዋል።
“ሶማሊያ ስንሄድ እኛ እኮ እናንተን አናምናችሁም፤ በክልልና በጎሳ ከፋፍላችሁ የምታባሉን እናንተ ናችሁ፤ የእናንተ መንግስት ነው ይህን የሚያደርገን፤ በጣም ነው የምንጠላችሁ” በማለት ሳይደብቁ ኢትዮጵያን ይወቅሱ ነበር ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
“በተመሳሳይ ደቡቡ ሱዳን ስንሄድም አሁን ላይ በሀገራችን እየተባላንበት ያለው ጉዳይ የእናንተው ውጤት ነው” በማለት ኢትዮጵያን እንደሚወቅሱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለምክር ቤቱ አብራርተዋል።
“በኢጋድ ውስጥ ስዩም መስፍን የሚባለውን ሰውዬ መድባችሁ ከፋፍሎን አባልቶን ሄዷ” በሚልም በግልጽ የጁንታው አባላት በጎረቤት አገራት ላይ የሰሩትን የከፋፋይነት ሴራ ለመንግስት እንደሚናገሩ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያስታወቁት።
“ኢትዮጵያ ጎረቤት ሀገራት በሙሉ የሚጠላት ሀገር ነበረች፤ የተከበረው ምክር ቤት ይህን ማወቅ አለበት” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከለውጡ ወዲህ በተከታታይ በተሰራው ዲፕሎማሲ ምክንያት ከጥላቻ ወጥተው በጁንታው ላይ የተካሄደውን የህግ ማስከበር ዘመቻ ደግፈው ተባባሪ ሊሆኑ መቻላቸውን ነው የተናገሩት።
የምክር ቤቱ አባላትም የጎረቤት አገራት በጁንታው ላይ በተወሰደው ህግን የማስከበር እርምጃ ላሳዩት ተባባሪነት ምስጋናቸውን በጭብጨባ ገልጸዋል።
በወንድማገኝ አሸብር
በሁመራ ከተማ በአንድ ሆቴል በተደረገ ፍተሻ ለ2ኛ ጊዜ 37 ኩንታል አደንዛዥ እፅ ተገኘ
********
(ኢ.ፕ.ድ)

በሁመራ ከተማ በአንድ ሆቴል በተደረገ ፍተሻ ለ2ኛ ጊዜ 37 ኩንታል አደንዛዥ እፅ ተገኘ።

በከተማዋ ህግን የማስከበር ግዳጅ እየተወጡ የሚገኙ የአማራ ክልል ፖሊስ አባላት ህገወጥ ድርጊቶችን ለማስወገድ እና የህዝብን ሠላም ለማስጠበቅ እየሠሩ መሆኑን የከተማዋ ፖሊስ መምሪያ ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮማንደር ሙላት ማሞ ገልፀዋል።

ከአደንዛዥ እፁ በተጨማሪ በአንድ ሰው ስም የተመዘገቡ 11 የቤት ካርታዎች እና በዚሁ ግለሠብ ስም ከፍተኛ ገንዘብ የተዘዋወረበት ቼክ ተገኝቷል።

ተጨማሪ ገጀራዎች፣ መጥረቢያዎች እና የወንድ ማንኮላሻም መገኘቱን አብመድ ዘግቧል።
የቀድሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ኬሪያ ኢብራሂም እጃቸውን ሰጡ
***************
(ኢ.ፕ.ድ)
የቀድሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ኬሪያ ኢብራሂም እጃቸውን መስጠታቸውን የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ምንጮች አረጋገጡ።
ወሮ ኬርያ የሕወሐት ከፍተኛ አመራርና በመንግሥት ከፍተኛ ኃላፊነት የበበራቸው ቢሆንም የከሀዲው የህወሓት ቡድን ይሻለኛል ብለው ወደ መቀሌ መሄዳቸው ይታወሣል።
“የማይካድራ ጭፍጨፋ ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ሰብዓዊ እና ስነልቦናዊ ቀውስ እንዲሁም ጥልቅ ሀዘን ያስከተለ ነው” - ዶክተር ዳንኤል በቀለ ኢሰመኮ ኮሚሽነር
*******************
(ኢ ፕ ድ)
በህወሓት ጁንታ ቡድን ላይ ህግ የማስከበር ዘመቻ መጀመርን ተከትሎ በማይካድራ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የተፈጸመው እልቂት በነዋሪዎች እና በተመልካች ላይ አስከፊ የስነ ልቦና ቀወስ ሊያስከትል እንደሚችል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር (ኢሰመኮ) ዶክተር ዳንኤል በቀለ አስታወቀዋል።
ዶክተር ዳንኤል የማይካድራ ጭፍጨፋ አስመልክቶ በተለይ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንዳስታወቁት፣ በማይካድራ የተፈጸሙ ግፍ በቁጥር ከሚገለጸው ሪፖርት ባሻገር በነዋሪዎች ላይ ሰብዓዊ እና ስነልቦናዊ ቀውስ እንዲሁም ጥልቅ ሀዘን አስከትሏል፡፡
በማይካድራ አማራ እና በወልቃይት ተወላጆች ላይ ያነጣጠረውን ጥቃት ተከትሎ ቤተሰቦች መበታተናቸውንና ሕፃናት ለስነልቦና ቀውስ መዳረጋቸውን የተናገሩት ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል፤ የጭፍጨፋው ሰለባ ቤተሰቦች ህይወታቸውን እንደቀድሞ ለማስቀጠል አዳጋች እንደሚሆንባቸው ተናግረዋል። በመሆኑም ኢኮኖሚያቸው እዲያንሰራራ እና ስነ ልቦናዊ ቀውስን መቋቋም እንዲችሉ ብዙ ሊሰራ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
ተጎጂዎቹ አስቸኳይ ድጋፍና እንክብካቤ የሚፈልጉ መሆናቸውን የጠቆሙት ኮሚሽነሩ፣ መንግሥት እና ዓለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅት በአካባቢው የሚገኙ ተጎጂዎችን መልሶ ለማቋቋም በሚደረገው ጥረት እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል
የማይካድራ ጥቃት ቀላል የወንጀል ድርጊት አይደለም ፣ አስቀድሞ የታቀደ እና በጥንቃቄ የተቀናጀ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ነው ያሉት ዶክተር ዳንኤል፤ የአካባቢው የፀጥታ መዋቅር ለጥቃቱ ተጠያቂ ከሆነው ሳምሪ ከሚባለው ቡድን ጋር ተባብሮ ንጹሃንን ከጉዳት ከመጠበቅ ይልቅ ጥቃቱን መደገፉንና በጥቃቱ መሳተፉን አስረድተዋል፡፡
ወንጀሉ በአካባቢው በነበረው ሚሊሻዎችና ፖሊሶች ድጋፍና ተሳትፎ የተፈጸመ ነው ያሉት ዶክተር ዳንኤል፤ ለወንጀለኞች ድጋፍ ያደረጉ እና የተሳተፉ የአካባቢው የፖሊስ እና ሚሊሻ አባላት በሕግ ፊት ተጠያቂ መሆን አለባቸው ብለዋል ፡፡
ኮሚሽነሩ አክለውም፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ከዚህ ቀደም ተፈጽሞ የማይታወቅ አይነት ጭካኔ የተሞላበት የወንጀል ድርጊት እንዴት እንደተፈጸመና እንደተቀነባበረ ተጨማሪ ምርመራዎችን ማካሄድ እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።
የቅድሚያ ሪፖርቱ በቁጥር እና በጉዳት መጠን ላይ ትኩረት ተደርጎ የተዘጋጀ መሆኑን ያብራሩት ዶክተር ዳንኤል፤ ጭፍጨፋው ያስከተለው የስነልቦና-ማህበራዊ ተፅእኖው እንዲሁም ወንድም ወንድም ላይ እንዴት እንዲህ አይነት ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ሊፈጽም እንደቻለ የዘርፉን ባለሙያዎች ትንታኔ እና አካታች ጥናት እንደሚፈልግ ጠቁመዋል፡፡
በምርጫ 2013 ላይ የተኮረ ውይይት ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት የፖለቲካ ፓርቲዎች እየተወያዩ ነው
******************
(ኢ ፕ ድ)
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ በተገኘበት ቀጣዩን ምርጫ አስመልክቶ ከፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና ከሲቪክ ማኅበረሰብ ተወካዮች ጋር ውይይት እያካሄዱ ነው።
ውይይቱ ዐበይት ባለ ድርሻ አካላት ያላቸውን ሚና እና ኃላፊነት እንዲሁም የምርጫ ስርዓትን በሚያስቃኝ ገለጻ ተጀምሯል።
በጉጉት የሚጠበቀው እና ዐበይት ዴሞክራሲያዊ ተቋማት መሠረታዊ ለውጥ ማካሄዳቸውን ተከትሎ የሚከናወነው ታሪካዊ ምርጫ፣ ከ2010 አንስቶ ኢትዮጵያ በዴሞክራሲ ጎዳና የምታደርገው ጉዞ ዓይነተኛ ማሳያ ይሆናል ሲል የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።
ዛሬ ጠዋት አዲስ አበባ ውስጥ የፈነዳው ቦምብ ምንም ጉዳት አለማድረሱን ፖሊስ አስታወቀ
****************************
(ኢ ፕ ድ)
ዛሬ (ህዳር 23 ቀን 2013 ዓ/ም) ከጠዋቱ 1፡30 ሰዓት ላይ በቦሌ ክ/ከተማ ልዩ ቦታው ጎርጎርዮስ አደባባይ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በሚገኝ አንድ የቆሻሻ መጣያ ገንዳ ውስጥ ተጥሎ የተገኘ ቦምብ ከአካባቢው ሰዎች በደረሰው ጥቆማ የፈንጅ አምካኝ ባለሙያዎች ወደ ቦታው በማቅናት ለማምከን ባደረገው ሙከራ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ሊፈነዳ ችሏል።
በዚህም አንድ ግለሰብ የቦንቡ ፍንጣሪ በቅርብ ርቀት ከሚሰራበት ጋራዥ ቅጥር ግቢ በስራ ላይ ሳለ በፍንጣሪው ቀላል ጉዳት የደረሰበት ሲሆን፤ ተጎጂው የህክምና ርዳታ በማግኘት ወደ ቤቱ መመለሱን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ገልጿል።
ፖሊስ ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት ባላቸው ግለሰቦችና አጠቃላይ የምርመራውን ውጤት እንደደረሰው እንደሚያሳውቅ ገልጿል።
በተመሳሳይ በዚሁ ክ/ከተማ ወረዳ 6 ልዩ ቦታው ጉርድ ሾላ ቅዱስ ያሬድ ሆስፒታል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ለፖሊስ በደረሰ መረጃ መሰረት ባለሙያዎች ቦታው ድረስ በመገኘት ቦንቡን የማምከን ስራ ሰርተዋል፡፡
በነብስ ውጪ ግቢ ጣር ላይ የሚገኘው የጁንታው ተላላኪዎች በአዲስ አበባ በንፁሃን ላይ ከባድ ጉዳት ለማድረስ የሚደርጉትን መንፈራገጥ ለማምከን የሚቻለው ህብረተሰቡ ከፖሊስ ጋር የሚኖረውን የመረጃ ልውውጥ በማጠናከርና አካባቢውን በንቃት በመጠበቅ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጥሪ አቅርቧል።