Gazette Plus / ጋዜጣ ፕላስ/
25.2K subscribers
40.8K photos
333 videos
7 files
5.8K links
Ethiopian Press Agency, established in 1940 , is a public printing media enterprise operating in Ethiopia.
Download Telegram
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለዒድ አል ፈጥር በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አሰተላለፉ
+++++++++++++++
#ጋዜጣ_ፕላስ- በሕዝበ ሙስሊሙ ዘንድ ዒድ አል ፈጥር የበረከት በዓል ተደርጎ ይታመናል። ሮመዳንም የአላህ (ሱወ) ደግነት የሚገለጥበት፣ ውድ ስጦታዎችን ለሰው ልጆች የሰጠበት ወር ነው። ቁርአን ወደ ምድር የወረደበት፣ ጀሃነም ተዘግቶ የጀነት በሮች የሚከፈቱበት፣ ሁሉም እንደ እምነቱ ጽናትና እንደ አላህ (ሱወ) እዝነት ምናዳዎችን የሚያገኝበት ወቅት በመሆኑ ሕዝበ ሙስሊሙ ዘወትር የሮመዳንና ዒድ አል ፈጥርን መምጣትን በጉጉት ይጠብቃል።
በዒድ አል ፈጥር ከፈጣሪ በረከት የሚቸራቸው የሮመዳንን ወር በፆምና በዱዓ ያሳለፉት ናቸው፤ በበዓሉ መምጣት የሚያደሰቱትም ሮመዳንን በመልካም ተግባር ለማሳለፍ የበረቱ ናቸው። በተቀደሰው ወር ከክፋት የተቆጠቡ፤ ለድኾችና አቅመ-ደካሞች ዘካት የሰጡ፤ የበደሏቸውን ይቅር ለማለት የደፈሩ በሐሴትና በመንሳዊ ኃይል ተሞልተው ለዒዱ ይደርሳሉ። በተቃራኒው ለዱዓ የሰነፉና ለመስጠት የሰሰቱ ከፈጣሪ በረከት አያገኙም።
ከፊታችን ግንቦት ላይ የሚካሄደው ምርጫ ሀገራችንን የዴሞክራሲን ድል የምትቀዳጅበት፣ ወደ ቀጣይ ብሩህ ዘመንዋ የምትሸጋገርበት በር ነው። እንደ ሀገር ለዓመታት ዴሞክራሲን ስንናፍቅ ኖረናል። ጉዞአችን አልጋ በአልጋ አልነበረም። ነገር ግን ከፈተና በሁዋላ በረከት፣ ከብርታት በኋላ ሐሴት እንዳለ ከሮመዳን ጾምና ከዒድ አል ፈጥር በዓል እንማራለን።
መልካም የዘራ ሰው መልካም ምርት እንደሚያጭድ ሁሉ፤ እሾክ የዘራውም አሜኬላ ያጭዳል። ስለተመኘን ብቻ አሜኬላው በመልካም ሰብል አይለወጥም። በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊ ጉዳዮች ውስጥ ዘርና ምርት የተቆራኙ ናቸው። ስለዴሞክራሲም ስናስብ ይሄንን ሐቅ መዘንጋት የለብንም። የምንገነባው ሕጋዊና ሕዝባዊ መንግሥት የሚወሰነው በቅድመ ምርጫ ተሳትፎአችን ልክ ነው።
ተሳትፎአችን ከጠየመ ዴሞክራሲያችንም ይጠይማል። ደካማ ተሳትፎ አድርገን ጠንካራ ዴሞክራሲ ለማዋለድ መመኘትም ሞኝነት ነው። ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በባዶ መሬት አይበቅልም፤ በግጭትና ሥርዓት አልበኝነትም አይገነባም። ይልቁንም ስክነትን፣ ለትብብርና ቅንጅት ልብን ክፍት ማድረግን፣ በጨዋታው ሕግ መመራትን ይጠይቃል።
ሮመዳን ቤተሰብ የሚገናኝበት፣ ኅሊና የሚሰበሰብበት፣ ሰውነት የሚገራበት እና መንፈስ የሚቀናበት ወር ነው። ዒድ አል ፈጥር ደግሞ የሰውን ልጅ ጤናማ ግንኙነቶች የሚያመለክት በዓል ነው። የሰው ልጅ ከፈጣሪው ጋር፣ ከራሱ ጋር እና ከወገኑ ጋር የሚኖረው ግንኙነት ጤናማ ካልሆነ ጠቅላላ ሕይወቱ ጤናማ አይሆንም። በሮመዳን ወቅት ጾሙ ሰዎችን ከራሳቸው ጋር ያገናኛቸዋል፤ ሰላትና ዱአ ከፈጣሪያቸው ጋር ያገናኛቸዋል፤ አፍጣርና ዘካት ደግሞ ከማኅበረሰቡ ጋር ያገናኛቸዋል። ኢትዮጵያውያን ጤናማ ሕይወትን መምራት እንድንችል እነዚህን ሦስቱን ጤናማ ማድረግ አለብን።
ሰው ከፈጣሪው እና ከራሱ ጋር ያለው ግንኙነት ጤናማ ካልሆነ ለማኅበረሰብም ለሀገርም ጠንቅ ነው። ሰው ከራሱ ጋር እየተጋጨ ከኖረ ከሁሉም ጋር ይጋጫል።
ዛሬ ጦርነትን ባህል፣ ዝርፊያን ልማድ፣ ጥፋትን ዕሴት፣ ውድመትን ክብር አድርገው የሚኖሩት ሰዎች የመጀመሪያው ችግራቸው ከፈጣሪያቸውና ከራሳቸው ጋር አለመስማማት ነው። ውስጣዊ ባሕርያቱ ያልተስማሙለት ሰው ከማንም ጋር አይስማማም። ዕርቅ፣ ሰላም፣ ፍቅር፣ መግባባት እና መስማማት የሚባሉት ነገሮች አይገቡትም።
ሰው ከፈጣሪውና ከራሱ ጋር ከተስማማ፣ ከማንም ጋር መስማማት ይችላል። ከእንስሳትም ጋር ሳይቀር። “ለድንቢጥ እንኳን ቢሆን የራራ ሰው፤ በፍርድ ቀን (ቂያማህ) አላህ ይራራለታል” ሲሉ ነቢዩ መሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ያስተማሩት ለዚህ ነው። የእስልምና ዋናው መሠረቱ ሰላም የሆነው ለዚህ ነው። ሰላም ማለት ከራስና ከአካባቢ ጋር በጤናማ ግንኙነት ለመኖር መቻል ነውና።
የዘንድሮውን የዒድ በዓል ስናከብር በዓለማችን ስለ ሰላም የሚነገረውን ያህል የዓለም ሕዝቦች በሰላም መኖር ለምን አልቻሉም ብለን እንጠይቅ? የግጭትና የጦርነት ድንጋይ እየደጋገመ ለምን ይመታናል? ከአዛኝ ይልቅ ገዳይን እንደ ጀግና የሚያየው ልምምዳችን ለምን ገናና ሆነ? የሰው ልጅ ከግጭትና ከጦርነት ያተረፈው ድህነትና ኋላ ቀርነት መሆኑን እያየን ለምን አልተማረንም? ሠልጥኗል በምንለው ዓለም የሚኖሩ ወገኖቻችን እንዴት ግጭትንና ጦርነትን የሚያበረታቱ ሆኑ? ይህ ትውልድ እነዚህን ጥያቄዎች በሚገባ አጢኖ ምላሽ ሊያገኝላቸው ይገባል።
ከራሳቸው ጋር ሰላም ያጡ አካላት የማኅበረሰቡን ሰላም እንዲረብሹ ልንፈቅድላቸው አይገባም። ከሮመዳን ዕሴቶች ጋር የተጣሉ ሰዎች ዘመኖቻችንን እንዲረብሹ ልንፈቅድላቸው አይገባም። በዐሥራ ሁለተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደ ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን መኖር ቀድሞ መገኘት ነው። በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን እንደ ዐሥራ ሁለተኛው ክፍለ ዘመን መኖር ግን መረገም ነው።
መግደል፣ ማገት፣ የገበሬውን እርሻ ማቃጠል፣ ሴቶችን መድፈር፣ ማኅበራዊ ተቋማትን መመዝበር፣ ቅርስና ታሪክን ማበላሸት፣ ጠመንጃን የሁሉም ነገር መድኃኒት አድርጎ መውሰድ፣ እነዚህ ሁሉ ከ800 ዓመታት በፊት ያለፉ የሰው ልጅ ጠባያት ናቸው።
ከሦስት አካላት ጋር የታረቁ ሰዎች ብርቱዎች ናቸው ይባላል፤ ከራሳቸው፣ ከማህበረሰባቸው እና ከፈጣሪያቸው ጋር። እንደ ኢትዮጵያዊ እኛም ራሳችንን የገዛን፣ ፈጣሪን የምንፈራ እና ለማህበረሰብ ሰላምና እድገት የምንጨነቅ መሆን አለብን። ኢትዮጵያ የምታድግና የምትበለጽገው በዜጎችዋ እንጂ በሌላ አይደለም።
ዜጎችዋ ሲገነቡ ትገነባለች፤ ዜጎችዋ ሰላም ሲሆኑ ሰላም ትሆናለች፤ ዜጎችዋ ሲስማሙ የብልጽግና ጉዞዋ ይሰምራል። የኢትዮጵያም መበልጸግ የሌላ ሳይሆን የእኛ መበልጸግ ነው። ስለሆነም ኢትዮጵያ እንድትበለጽግ የሚፈለግብንን መሥዋዕትነት ሁሉ የመክፈል ኃላፊነት የእኛ ነው።
የእኛ ልፋት ከዛሬ አልፎ ለትውልድ ይተርፋል። ሀገር መውደዳችን የሚታወቀው እና መልካም ዜግነታችን የሚገለጠው በሥራችን ነው። ነቢዩ መሐመድ (ሰ.ዐ.ወ.) “ምርጥ ሰዎች ማለት ሌሎችን ለመጥቀም የበረቱ ሰዎች ናቸው” ብለው ያስተማሩትም ለዚህ ነው።
ይሄን የዒድ አል ፈጥር በዓል እነዚህን መልካም ዕሴቶች እያሰብን፣ ሦስቱን ጤናማ መሥመሮችንም እያጸናን እንድናከብረው አደራ እላለሁ።
በድጋሚ መልካም የዒድ አል ፈጥር በዓል ይሁን!
ዒድ ሙባረክ!
ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!!
ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
መጋቢት ፣ 2018 ዓ.ም
5
“በኢትዮጵያ የሚከበረው ዒድ አል-ፈጥር ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ የሚታደምበት በዓል ነው”

- ፕሮፌሰር አደም ካሚል
+++++++++++++++++++

#ጋዜጣ_ፕላስ | በኢትዮጵያ የሚከበረው ዒድ አል-ፈጥር እንደ መካና መዲና በዓለም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ በጋራ የሚታደምበት ታላቅ በዓል መሆኑን የታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር አደም ካሚል ገለጹ።

ፕሮፌሰር አደም ከጋዜጣ ፕላስ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳብራሩት፤ የረመዳን ጾም ሕዝበ ሙስሊሙ ለ30 ቀናት በመጾም ከፈጣሪው ምሕረት የሚጠይቅበት ታላቅ ወቅት ነው።

ጾሙን ያጠናቀቀው ምእመን የዒድ አል-ፈጥርን በዓል ከትንሽ እስከ ትልቅ፣ ሴት ወንድ ሳይል በአደባባይ በአንድነት የሚያከብረው ልዩ በዓል መሆኑን ተናግረዋል።

ከበዓሉ አንድ ቀን አስቀድሞም አቅም ለሌላቸው ወገኖች ዘካ በመስጠት የተግባራዊ መረዳዳት ሥርዓት የሚከናወንበት መሆኑንም አውስተዋል።

ዓለም አሁን እያስተናገደች ያለውን የሰላም እጦትና የኢኮኖሚ ቀውስ ተከትሎ፣ ወቅቱ ከምንጊዜውም በላይ ጸሎት የሚደረግበት መሆኑን ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል።

በኢትዮጵያም ፍጹም ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ያላቸውን ከፍተኛ ምኞት አክለዋል።

የዒድ አል-ፈጥር በዓል ብሔር፣ ቋንቋና ቀለም ሳይለይ ሕዝበ ሙስሊሙ በአንድነት ፈጣሪን የሚያመሰግንበት በመሆኑ፤ ማኅበረሰቡ በዓሉን እርስ በርስ በመረዳዳት፣ በመጠያየቅና በመተሳሰብ እንዲያከብር ፕሮፌሰር አደም ጥሪ አቅርበዋል።

በሰለሞን ወልዴ
#ዒድ_አል_ፈጥር #ረመዳን #ኢትዮጵያ
1
#የዒድ_አልፈጥር_በዓል

1 ሺህ 447ኛው የዒድ አልፈጥር በዓል በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
7👍1
🔥 ተመሳሳይ ያረጁ ዜናዎችን ማንበብ ይብቃዎ! አልጎሪዝምዎን ይቀይሩ።

🇪🇹 🌍 ከኢትዮጵያ፣ ከአፍሪካ እና ከአለም አቀፍ ዙሪያ የተሰሙ አዳዲስ ክስተቶችን በተለየ ምልከታ በስፑትኒክ ኢትዮጵያ ይከታተሉ እንዲሁም ያልተጋሩ ፎቶዎችንና ቪዲዮዎችን በየእለቱ በስፑትኒክ ኢትዮጵያ ብቻ ያገኛሉ።

ከሌሎች መገናኛ ብዙኃን የማያገኟቸውን ትኩስ ትኩስ መረጃዎችን ስፑትኒክ ኢትዮጵያ ለእርስኦ ያቀርብልዎታል።

📌አዳዲስ መረጃዎችን በየእለቱ ለመከታተል አሁኑኑ ቻናላችንን በመቀላቀል ያልተሰሙ መረጃዎችን ይከታተሉ::
👇🏾👇🏾👇🏾
https://t.me/+eM_pls45dPAyZjZi
👍6
የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን አዲስ የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋቱን አስታወቀ
+++++++++++++++++++

#ጋዜጣ_ፕላስ | በሀገሪቱ እየታየ ያለውን የነዳጅ እጥረትና ሕገወጥ ንግድ ለመፍታት በቴክኖሎጂ የታገዘ አዲስ የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋቱን የኢትዮጵያ ነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን አስታወቀ።

የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ደስታው መኳንንት (ዶ/ር) ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ በየዓመቱ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ በነዳጅ ስርቆት ወይም "መቀሸብ" ምክንያት በሕገወጥ መንገድ ይባክናል።

ችግሩ ከጅቡቲ ጀምሮ እስከ ማደያዎች ድረስ ባለው ሰንሰለት ውስጥ የሚፈጸም መሆኑን የጠቆሙት ዋና ዳይሬክተሩ፤ አንድ የነዳጅ ቦቴ መንገድ ላይ በመቆም ብቻ በርካታ ሊትር ነዳጅ እንደሚሰረቅና በማደያዎችም "አየር በመሸጥ" እስከ 10 በመቶ የሚደርስ ስርቆት እንደሚፈጸም ተናግረዋል።

ይህንን ሕገወጥ ዝውውር ለመግታት መንግሥት የ40/20/40 የነዳጅ ሥርጭት ቀመር አዘጋጅቶ እየተገበረ ይገኛል።

ይህ አዲስ አሠራር የኩባንያዎችን የማደያ ብዛት፣ ነዳጅ የማከማቸት አቅምንና ሕዝቡን በቀጥታ የሚያገለግሉ የዲስፔንሰር ወይም የመቅጃ መሣሪያዎችን ቁጥር መሠረት በማድረግ ፍትሐዊና ቁጥጥር የሚደረግበት የነዳጅ ሥርጭት እንዲኖር ታስቦ የተቀረጸ መሆኑን አስረድተዋል።

በተጨማሪም በመንገድ ላይ የሚቀሸበውን ነዳጅ ለመቆጣጠር አላርም የሚያደርግ “ሴንሰር” በቦቴዎች ላይ እየተገጠመ መሆኑን ደስታው (ዶ/ር) ገልጸዋል።

ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሊትር ነዳጅ በሕገወጥ መንገድ ሲንቀሳቀስ መያዙን ያነሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በ352 ማደያዎችና በ256 ቦቴዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን አስታውቀዋል።

በዮሐንስ መልካሙ
2
አነስተኛ ወርቅ አምራቾችን ወደ ኢንዱስትሪ መሪነት የማሸጋገር ሥራ እየተከናወነ ነው
+++++++++++++++++++

#ጋዜጣ_ፕላስ | በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አነስተኛ የወርቅ አምራቾችን ወደ ዘመናዊ የኢንዱስትሪ ባለቤትነት የሚያሸጋግር አሠራር በመዘርጋትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ ወደ ኢንዱስትሪ መሪነት የማሸጋገር ሥራ እየተሠራ መሆኑን የክልሉ ማዕድን ልማት ቢሮ አስታወቀ።

የምክትል ቢሮ ኃላፊው አቶ ናስር መሀመድ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፤ በማዕድን ልማት ዘርፉ ለአካባቢው ነዋሪዎች ሰፊ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ አነስተኛ አምራቾችን ወደ ዘመናዊ የኢንዱስትሪ ባለቤትነት የሚያሸጋግር ሥርዓት ተዘርግቷል።

አነስተኛ አምራቾችን በአምስት ሄክታር መሬት ላይ በማደራጀት ወደ ሥራ እንዲገቡ በተደረገው ጥረት እስካሁን ከ50 ሺህ በላይ ዜጎች ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን የገለጹት አቶ ናስር፤ ይህ አደረጃጀት የአካባቢው ነዋሪዎች ያላቸውን የቆየ ልምድና እውቀት ከሕጋዊ አሠራር ጋር በማቀናጀት ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል።

አምራቾቹን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ወደ ተሻለ የኢንዱስትሪ ደረጃ የማሸጋገር ሥራ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን፤ ባለሀብቶች ከአነስተኛ አምራቾች ጋር በጋራ እንዲሠሩ ወይም ከ5 እስከ 50 ሄክታር መሬት ወስደው በኩባንያ ደረጃ እንዲሰማሩ የማድረግ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል።

ከወርቅ በተጨማሪ እንደ የድንጋይ ከሰል፣ እምነበረድ እና ብረት ያሉ 17 ዓይነት ማዕድናት ለክልሉ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ለውጥ እንደ ሞተር እንዲያገለግሉ ጥናት እየተደረገባቸው እንደሚገኝም ምክትል ቢሮ ኃላፊው ጠቁመዋል።

በሳሙኤል ወንደሰን
#ጋዜጣ_ፕላስ #አነስተኛ_አምራቾች #ኢንዱስትሪ#ቤኒሻንጉል_ጉሙዝ #ማዕድን #ወርቅ #ኢትዮጵያ
1
ሐዋሳ እና ብስክሌተኞቿ
++++++++++++++

#ጋዜጣ_ፕላስ | በኢትዮጵያ ከተሞች ብስክሌትን አዘውትረው የመጠቀም ባህል ካዳበሩ ነዋሪዎች መካከል የሐዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ይጠቀሳሉ። በከተማዋ የተሰራው የኮሪደር ልማት ሥራ ዘመናዊነትን እንድትጎናጸፍ ፣ እንድትዋብና ምቹ እንድትሆን ያደረጋት ሲሆን፤ ጎዳናዎቿ ብስክሌት የሚጋልቡ አብዮተኞች እንዲበራከቱ አስችሏታል፡፡ በብስክሌት እየተጓዙ ጤናቸውን የሚጠብቁ እየተዝናኑ ነዳጅን የሚቆጥቡ የከተማዋ ነዋሪዎችም እየበዙ መጥተዋል፡፡ እርዎስ? እርስዎ የሚኖሩበት ከተማስ?
1
This media is not supported in your browser
VIEW IN TELEGRAM
ከሉሲ እስከ ኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ ፤ የአፋር ስጦታ!

‎ዛሬ በአፋር ክልል የ'’ገበታ ለትውልድ’' ፕሮጀክታችን አካል የሆነውንና የሰው ልጅ ታሪክ ከጀመረበት ጥንታዊ ምድር የተገነባውን ኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ ለመመረቅ ተገኝተናል።

የከባቢው ጸጋ የተገለጠበት ይኽ ስራ የቱሪዝም ልህቀትና የግብርና ዘርፍ መነቃቃትን አዲስ ምዕራፍ በማብሰር፣ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ መድረክ ላይ ይበልጥ ጎልታ እንድትታይ የማድረግ ከፍተኛ ዐቅም አለው!

-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
‎‘ኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ’ ሁሉን አቀፍ ምድራዊ ገነት!

‎በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የ’ገበታ ለትውልድ’ ውጥን አካል የሆነው ‘ኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ’፤ ማህበረሰብን ለማበልጸግና ሀገራዊ ዕድገትን ለማረጋገጥ የባለራዕይ መሪ የአመራር ጥበብና ቁርጠኝነትን የሚያሳይ ምስክር ነው።

‎ ሎጅው በተለያዩ የፍራፍሬ እና የደን ዛፎች በለመለመ 78,000 ካሬ ሜትር ስፋት ባለው መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን፤ ተፈጥሯዊ የ"ሰማያዊ ዓይን" ፍልውሃ መዋኛ፣ ሁለት ግዙፍ ሰው ሰራሽ ሐይቆችና 3.2 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የእግር ጉዞ (ሀይኪንግ) ምቹ መንገድ አካቷል።

‎የማረፊያ ክፍሎቹንም በተመለከተ፦ የግል መዋኛ ገንዳ ያላቸው ሁለት ፕሬዝዳንታዊ ቪላዎች፣ አስራ ሁለት እርስ በእርስ የተያያዙ የመኝታ ክፍሎች እና አስራ ስድስት ባለ አንድ መኝታ ቤቶችን ይዟል። በተጨማሪም ዘመናዊ የምግብ አዳራሾች፣ የእንግዳ መቀበያ ህንፃ፣ የስብሰባ አዳራሽ፣ የቢሮ ክፍሎች፣ የተሽከርካሪ ማቆሚያ እና ሁለት ሄሊኮፕተሮችን በአንድ ጊዜ ማሳረፍ የሚችል ስፍራ (ሄሊፓድ) ያካተቱ መሰረተ ልማቶች ተሟልተውለታል።

‎ኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ ከቱሪስት መዳረሻነቱ ባለፈ፣ ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰትን በመሳብ ታላላቅ ጉባዔዎችን ለማስተናገድ ተደማሪ ዐቅም ነው። ‎በመስተንግዶ እና በአገልግሎት ዘርፎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ለአካባቢው ኢኮኖሚ ትልቅ መነቃቃትን የሚፈጥር ሲሆን ፕሮጀክቱ በጠንካራ አመራር ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ መዳረሻን የማቅረብ የገበታ ለትውልድ መርሃ-ግብር ርዕይን ሰንቆ ቀጣይነት ላለው ቀጣናዊ ዕድገት እንደ ወሳኝ ሞተር ሆኖ ያገለግላል።

#PMOEthiopia #VisitEthiopia #EthiopiaDelivers