Gazette Plus / ጋዜጣ ፕላስ/
25K subscribers
41K photos
338 videos
7 files
5.81K links
Ethiopian Press Agency, established in 1940 , is a public printing media enterprise operating in Ethiopia.
Download Telegram
ከሊባኖስ 165 ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ተመለሱ
*********************************
(ኢፕድ)
በሊባኖስ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 165 ኢትዮጵያውያን ዛሬ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡
ኢትዮጵያውያኑ ወደ አገራቸው የተመለሱት በግለሰቦች፣ ግብረ ሰናይ ድርጅቶችና ቡድኖች በተደረገላቸው የትራንስፖርት ወጪ ነው፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለተመላሾቹ የአውሮፕላን ቲኬት ቅናሽ በማድረጉም ተገልጿል፡፡
በቀጣይም በራሳቸው ሙሉ ወጪ 243 ኢትዮጵውያን ወደ አገራቸው ይመለሳሉ ተብሏል፡፡
ወደ አገራቸው ለመመለስ ከ650 በላይ ዜጎች መመዝገባቸውም ተመልክቷል ፡፡
መንግሥትም በሊባኖስ የሚስተዋሉትን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች ተከትሎ ዜጎችን ወደ አገራቸው ለመመለስ ጥረት እያደረገ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ተመላሾቹ ቦሌ አለም አቀፍ አየር መንገድ ሲደርሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የስራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡
መንግሥት ከጥቅምት 2012 ዓ.ም ጀምሮ 2ሺህ 300 ዜጎችን ከሊባኖስ ወደ አገራቸው መልሷል፡፡
ሊባኖስ በገጠማት የኢኮኖሚ ቀውስ፣የኮቪድ 19 ወረርሽኝና በቅርቡ ቤይሩት ወደብ ላይ የደረሰው ፍንዳታ ተዳምሮ ችግር ውስጥ መሆኗ ይታወቃል ሲል ኢዜአ ዘግቧል፡፡
“ህወሓት ኢትዮጵያዊ ያልሆነ፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የቆመ እጅግ መሰሪ የፖለቲካ ኃይል ነው” - አቶ አገዘው ህዳሩ፣የራያ ራዩማ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር፤
************************************
(ኢፕድ)
አዲስ አበባ:- ህወሓት እጅግ መሰሪ የሆነና ኢትዮጵያዊ ያልሆነ፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የቆመ የፖለቲካ ኃይል መሆኑን የራያ ራዩማ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ አገዘው ህዳሩ አስታወቁ። በወንጀል ሊጠየቅ፤ ከፖለቲካ ፓርቲነት ሊሰረዝ፤ በአሸባሪነት ሊፈረጅ እንደሚገባም አሳሰቡ፡አቶ አገዘው ህዳሩ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንዳመለከቱት፣ ህወሓትን እየዘወሩ ያሉ ሐይሎች ከአስተሳሰባቸው ጀምሮ ኢትዮጵያውያን አይደሉም። በኢትዮጵያ ስም መጠቀም እስከቻሉ ድረስ በኢትዮጵያዊነት አብረው መቆየት የሚፈልጉ ናቸው፤ እነሱ መጠቀም እና በስልጣን መቆየት ካልቻሉ ኢትዮጵያን ለእነሱ ስጋት በማትሆን መንገድ መስራትና አፈራርሶ መሄድ ይፈልጋሉ።

ለዚህም የራሳቸውን ኢኮኖሚ፣ ፖለቲካ፣ የሚሊተሪና የፀጥታ አቅም አዳብረው መጠቀም እስከቻሉ ድረስ አብረው ለመቆየት ችግር የለባቸውም ያሉት ሊቀመንበሩ፣ ራሳቸው መጠቀምና ሌላውን በሚፈልጉት መንገድ ማሽከርከር ካልቻሉ ኢትዮጵያን አፍርሰው መልሰው ለእነሱ ስጋት እንዳትሆን አድርገው መሄድ ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቁመዋል።

“ህወሓት ለህዝቡም አይጠቅምም፤ እጅግ መሰሪ የሆነና ኢትዮጵያዊ ያልሆነ፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የቆመ የፖለቲካ ኃይል ነው። ስለዚህ ከዚህ ጋር የሚተባበር ኢትዮጵያዊ መኖር የለበትም ብዬ አምናለሁ። ይሄን የምለውም እኛ ከስር መሰረታቸው ስለምናውቃቸው ነው። ምናልባት ሌላው ህዝብ ግፍና በደሉን ብቻ ነው የሚያየው፤ እኛ ግን አስተሳሰባቸውንም ጭምር እናውቃለን “ብለዋል ።

የትግራይን ህዝብ ጨምሮ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ላይ ሆኖ የነዚህን ሰዎች ህልውናቸውን ማሳጠር እንዳለበት ያመለከቱት አቶ አገዘው፣ ለመላው ህዝባችን የሚጠቅመው አንድነቱ፣ ኢትዮጵያዊነቱ እና የጋራ ተጠቃሚነቱ እንደሆነ አስታውቀዋል።

ከእኩልነትና ከኢትዮጵያ አንድነት የሚገኘው ትርፍ እጅጉን የገዘፈ እንደሆነ በአጽዕኖት የተናገሩት ሊቀመንበሩ፣ ከህወሓት የገንጣይና ነጣይ ባህሪ አንጻር /ምን አይነት ስነልቡና እንደሆነ ባላውቅም/ ኢትዮጵያዊ ሆኖ ከህወሓት የፖለቲካ ጥቅም አገኛለሁ ብሎ የሚዶልት፤ የሚያሴር የፖለቲካ ሃይል ተግባር በጣም አስገራሚ እንደሆነ አመልክተዋል።

“እነዚህ ሰዎች ባልጠበቁት ሁኔታ ያውም በማይታመን መልኩ በፈጣሪ እርዳታ ከመሃል የኢትዮጵያ ክፍል ተገልለው ወደ አንድ ዳር እንዲሰበሰቡ ሆኗል። እነዚህ ሰዎች ደግሞ መልሰው ስልጣን መያዝ አይችሉም። ከዚህ አንጻር ፍላጎታቸውን ለመፈጸም ብዙ ሞክረዋል። ዙሪያውን ሄደው ኢትዮጵያን ለማመስ ያላደረጉት ጥረት የለም።

ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፤በጋምቤላ፣ በሶማሌ ሁሉ ሞክረዋል፤ በደቡብ አሁንም እየሞከሩ ነው፤ በኦሮሚያም ሙከራ አለ። ››ሲሉ አብራርተዋል።
እነዚህ ሰዎች ተፈጥሮ ፍትህን፣ እኩልነትን፣ ነጻነትን፣ ኢትዮጵያዊነትን እና በኢትዮጵያ ማዕቀፍ የፈለገው የፖለቲካም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ችግር ቢኖር፤ በኢትዮጵያዊነት ማዕቀፍ ፍትሃዊ ያልሆነውን አሰራር እየታገልክ ኢትዮጵያዊነትን እንደ አንድ ምሰሶ ይዘህ ኢትዮጵያን ማቆየት የሚል ህልም እንደሌላቸውም አስታውቀዋል።

ለውጡና የለውጡ ሀይል የሚያቀነቅነው ከእነሱ አስተሳሰብ በተቃራኒው ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፣ ኢትዮጵያዊነትን እንደ አንድ ምሰሶ የያዘ መሆኑን ገልጸዋል። ይህ ሀይል የፈለገው አይነት የፖለቲካ ችግር ቢኖር በኢትዮጵያዊነት ማዕቀፍ መፈታት አለበት የሚል አቋም እንዳለው ጠቅሰው፣ እነሱ ግን በልዩነት ላይ የተመሰረተ፣ በብሄር ብሄረሰቦች መካከል ተቃርኖ እንዲኖር ማድረግ ነው። ሌላው ቀርቶ የእነሱ ህልውና የሚረጋገጥ የሚመስላቸው ራሳቸውን የበላይና ሁሉን ነገር አድራጊና ፈጣሪ አድርገው በመመልከት፣ በመሳልና በዛው ልክ በመግለጽ ነው ብለዋል። ይህንንም በአብነት ሲጠቅሱ ጎንደርና ጎጃም እንዲሁም ወሎና ጎንደር የጋራ ነገር የለውም ብለው እንደሚስቡም አመልክተዋል።

“ይልቁንም እኛ ነን አንድ ያደረግነው ብለው ነው የሚያስቡት። ኦሮሞን አንድ ያደረግነው እኛ ነን ብለው ነው የሚያስቡት። ከዚህ በመነሳትም ነው አሁን ላይ እነዚህን አካባቢዎች ለማፈራረስና እንደፈለገን ለመበታተን ምክንያቶች አሉን ብለው በማመን ይሄን ለማድረግ እንቅስቃሴ ጀምረዋል ብለዋል።

በዚህ ደረጃ ኦሮሞን አንድ አድርጋችሁ፤ አማራን አንድ አድርጋችሁ ነው ለስጋት የዳረጋችሁን ብለው የሚወቅሷቸው ኃይሎች እንዳሉም ሊቀመንበሩ ተናግረዋል። ስለዚህ ቀድሞ አስተሳሰባቸው የተመሰረተው በማህበረሰቦች መካከል ተቃርኖ በመፍጠር በሚፈጠር የፖለቲካ ልዩነት የእነርሱን እድሜ ማራዘም እንደሆነም አስታውቀዋል።

“ የትግራይ ህዝብ ገና ለውጡ ከመምጣቱ በፊት በየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ እነዚህ ሰዎች ሲሰሩት በነበረው ግፍና በደል ምክንያት ከእነሱ ጋራ በአቻ መንገድ እየታየን በየትኛውም ቦታ የመንቀሳቀስና ሄደን የመስራት ስጋት እየተፈጠረብን ነው የሚል ምሬት ነበረው።

ልጆቻችንንና አገራችንን አጥብበውብናል የሚል አስተሳሰብ በትላልቆቹ ሰዎች ዘንድ ነበረ። ››ያሉት ሊቀመንበሩ፣ አሁንም ቢሆን ህወሓት ለትግራይ ህዝብ እንደማይጠቅም አስታውቀዋል። ይልቁንም የህወሓት ህልውና እየጨመረ በሄደ ቁጥር የትግራይ ህዝብ በህወሓት ዓይን እየታየ የበለጠ ተጎጂ እየሆነ ነው የሚሄደው”ብለዋል።

የትግራይ ህዝብም ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር አንድነቱን አጥብቆ እነሱን መታገል አለበት፤ በእውነተኛ የፖለቲካ ፓርቲዎች በኩልም እያየን ያለነው ውጣ ውረድ ሊወገድ፤ አንዳንዶቹም ወደ ህወሓት በመጠጋት ህልውናቸውን ለማቆየት እየሂዱበት ያለው መንገድ ሊታረሙ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ከዚህ ባለፈ ህወሓት የተወሰኑ ወራት በቆየ ቁጥር የኢትዮጵያ ፖለቲካ በሽታ እያመረቀዘ እንዲሄድ ማድረግ ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፣ ህወሓት በምንም ሃይል በኢትዮጵያውያን አንድነት መጥፋት ያለበት ነቀርሳ መሆኑንም አስገንዝበዋል።

“ይሄ ብቻም ሳይሆን በወንጀልም ሊጠየቅ፤ ከፖለቲካ ፓርቲነትም መሰረዝ፤ በአሸባሪነትም መፈረጅ ያለበት የፖለቲካ ፓርቲ ነው። ለዚህ አስፈላጊ ከሆነ የመረጃ ማሰባሰብ ስራ ቢሰራ የፈጸሙት ተግባር ከእነዚህ ሰዎች ጋር እንኳን ዜግነት ሰውነት መጋራት ሁሉ እስኪቀፍህ ድረስ ህውሃት እጅግ በጣም የክፉዎች ስብስብ ነው። ››ሲሉም ተናግረዋል። የዚህ ስብስብ መጥፋት ለኢትዮጵያ ህዳሴ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያውያን አንድነትና አብሮነት አንድ ትልቅ ነቀርሳ እንደመንቀል ነው ብለዋል።
አዲስ ዘመን ነሐሴ 26/2012
ወንድወሰን ሽመልስ
“በሰለጠነ አገር ሆነው ያልሰለጠነ መልዕክትና ፀያፍ ነገሮችን ከማስተላለፍ ይልቅ ወደ ህሊናቸው ተመልሰው ሁኔታዎችን ዳግም ማየት አለባቸው” - አቶ ፍቃዱ ተሰማ፣የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ፤

• ለውጡ አብዮት ሳይሆን ሪፎርም ነው። ሪፎርሙ ውስጥ ደግሞ የተለያዩ አካላት አሉ። ሪፎርሙን ወደፊት ይዘው መሄድ የሚፈልጉ አሉ፤ ሪፎርሙን ወደኋላ የሚመልሱ አሉ። እነዚህ ወደኋላ መመለስ የሚፈልጉ አካላት የራሳቸውን የቡድን ፍላጎትና የግለሰብ ፍላጎት ማዕከል አድርገው ነው።

• ለውጡን ሊቀለብሱና ወደኋላ ሊመልሱ ከሚፈልጉት ውስጥ አንዱ እንደ ህወሓት አይነቱ በሴራ ፖለቲካ አካሄድ ስልጣን ላይ የነበረና ያንን ስልጣን ያጣ ነው።ከተቻለ ወደስልጣን ለመመለስ፣ ካልተቻለ ደግሞ ሀገር ለመበተን የሚደረግ ሩጫ ነው።

• ሌላው ደግሞ ከውጪ የመጣውና ለውጡን እኔ ነኝ ያመጣሁት ብሎ የሚያስበውና አክቲቪዝም በዓለም ላይ ጫፍ የረገጠበትን አጋጣሚ ተጠቅሞ በዚህ መስመር የመጣ አዲስ ተስፈኛ አካል የተፈጠረበትና ነው።

• ይህ ደግሞ ቀደም ሲል የዴሞክራሲ ምህዳር ችግር ስለነበረ በውጪ የነበሩት ለውጡን ተከትሎ በተፈጠረው ምህዳር ወደ አገር ውስጥ የገቡ፤ የሪፎርሙ ውጤት ተደርገው የሚታሰቡ ናቸው።

• ለውጡ በአብዮት መጥቶ ቢሆን ግን ሁሉንም ጠራርጎ ነው መልክ የሚያሲዘው እንጂ ይሄን አይነት እድል አይሰጥም ነበር። ሪፎርም ግን በዚህ ሁሉ ፈታኝ ሁኔታዎች ውስጥ በብልሃትና በትዕግስት መስዋዕትነትም ጭምር እየከፈልክ የምትሄደው ስለሆነ፤ ያ ትዕግስትና የተከፈተው የዴሞክራሲ በር ነገሮች የመሰሉትን እንዲመስሉ አድርጓል።

• ሁሉም ወደ አገር በሚገባበት ጊዜ በሰላም እታገላለሁ ብሎ ነው የገባው። ከገባ በኋላ ግን ሁለት ቦታ የመቆም ሁኔታ ነው የታየው። በተለይ ኦነግ ሸኔ በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢ በህቡዕ የሚንቀሳቀስበት ሁኔታ ነበረ።

• የተከፈተው የዴሞክራሲ በር ሰዎች እንደልባቸው እንዲፈነጩ፤ ግለሰቦች መንግስት መስለው እንዲታዩ ያደረገበት ሁኔታ ነበር፤ ይህም በየደረጃው ያለው አመራር አጣብቂኝ ውስጥ እንዲገባ አድርጓል።

• የህግ የበላይነቱን ሙሉ በሙሉ ለማስከበር የሚደረገው ጥረት በራሱ የዴሞክራሲ ምህዳሩ እንዳይጠብ የሚል ስጋት ነበር።

• የዴሞክራሲ ምህዳሩ ጠቦ ያለፉ ነገሮች ተመልሰው ዴሞክራሲው አጣብቂኝ ውስጥ እንዳይገባ በሚደረገው ጥረት ሰፊ ክፍተቶች ተፈጥረዋል። በዚህ መሀል የችግሩ ሰለባ የሆኑ ሰዎች የሉም ማለት አይቻልም። ነገር ግን በአብዛኛው አመራሩን ይገልጻል ማለት ግን አይደለም።

• በተለያየ ጊዜ የሚደረጉ የሁከትና ጥፋት ጥሪዎች የሚከሽፉበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ህብረተሰቡ ጥሪያቸውን አልሰማም ያለበት ዋናው ምክንያትም ህብረተሰቡ ውስጥ ያለው የጠነከረ አንድነት ነው፤

• የትኛውም አይነት ጽንፈኝነት በህዝብ ደረጃ ተቀባይነት የለውም። ሙስሊሙ ክርስቲያን ላይ ተነስ፤ ክርስቲያኑ ሙስሊሙ ላይ ተነስ፤ አንዱ ብሄር ሌላው ብሄር ላይ ተነስ በሚል የሚገለጽ በህብረተሰቡ ውስጥ የለም።

• ከወጣቶቹ ጋር ሰፋ ያሉ ውይይቶችን አድርገናል። ውጪ ተቀምጠው ወደዚህ የሚያስተላልፉት መልዕክት አይጠቅመንም የሚል ድምዳሜ ላይ እየደረሰ ነው።

• በየጊዜው የሚተላለፉ መልዕክቶች የሚከሽፉበት ዋናው ምክንያትም ይሄ በመሆኑ ነው። ይሄንን አጠናክሮ በመቀጠል ከውጪ የሚያዝ አካል ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት የሚያጣበት ሁኔታን ለመፍጠር እየተሰራ ነው።

• ህብረተሰቡ በተደራጀ አግባብ በየአካባቢው ለሰላሙ መረጋገጥ የጸጥታ ስራውን ሆነ የልማት ስራውንም እንዲሰራ፤ በዚህም የልማቱም የሰላሙም ባለቤት እንዲሆን ማስቻል ላይ ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል።

• ብልጽግና የክልላችንን ህዝብ ጥያቄ ለመመለስ የመጣ ፓርቲ ነው ብዬ ነው የማየው። በስፋቱ ልክ መወከል አለብኝ የሚል ጥያቄ ነበር። ይሄ የፍትሃዊነት ጥያቄ ነው።

• የህግ የበላይነትን ከማስከበር አኳያ አጠቃላይ ህብረተሰቡን አሳትፈን ችግሩን ለዘለቄታው የመፍታት ስራ ተሰርቷል። አሁን በጥባጩ አካል የሚቆጣጠረው ዞንና ወረዳ ቀርቶ የሚቆጣጠረው ቀበሌ የለም።

• ብልጽግና አንድ ነው። በክልሎች ደረጃ ጽህፈት ቤት ነው ያለው። በአገር አቀፍ ደረጃ ዋናው ጽህፈት ቤት ነው ያለው። አንድ ወጥ ስራ አስፈጻሚ እና አንድ ወጥ ማዕከላዊ ኮሚቴም ምክር ቤትም ነው ያለው።

• እዚህ ደግሞ በክልሉ ሁለት ነገሮችን አስታርቆ ነው ብልጽግና የሚሰራው። የመጀመሪያው አገራዊ አንድነትን ፣ ሁለተኛ ደግሞ የብሄር ማንነትን ማዕከል አድርጎ ፌዴራሊዝምን ማስቀጠል ነው። ስለሆነም በጋራ ነው ተልዕኮ የምንወስደው፤ በጋራም ነው የምንፈጽመው።

• ባለፈው በክልላችን ችግሮች በሚፈጠሩበት ጊዜ ችግሩን ከመከላከል አኳያ ከአማራ ብልጽግና ፓርቲ ጋር አብረን ስንሰራ ነበር።

• ጽንፈኛው ሃይል አጠቃላይ ኦሮሞ በአማራ ላይ እንደተዘመተ ተደርጎ ስለተቀሰቀሰ፤ በዛ በኩልም ይሄን ነገር ተረድቶ ይሄ ነገር እንዳልሆነና ጽንፈኛ ሃይል የቀሰቀሰው እንደሆነ፤ እና ኦሮሞ አማራ ላይ ሊነሳ እንደማይችል የማስገንዘቢያ ስራዎች ባይሰሩ እና በተቀሰቀሰው ልክ ግጭት ቢፈጠር ኖሮ ሊደርስ የሚችለው ጉዳት ትልቅ ነበር የሚሆነው።

• በተመሳሳይ ከሶማሌ ብልጽግና ፓርቲ ጋር፣ ከአፋር ብልጽግና ፓርቲ ጋር፣ ባጠቃላይ ከሁሉም ክልሎች ብልጽግና ፓርቲ ጋር በየጊዜው እየተገናኘን እንገመግማለን፤ የተሞክሮ ልውውጥም እናደርጋለን። ስለዚህ አንድ ላይ ነው የምንሰራው ማለት ይቻላል።

• በአንድ ግምገማና በአንድ ኮንፍረንስ ሁሉም ችግሮች በአንድ ጊዜ ጠርተው ይጠፋሉ ማለት አይቻለም። ነገር ግን በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው ከአሁን በኋላ ፈተናዎች እየቀነሱ ይሄዳሉ፤

• ህብረተሰቡ የሰላሙም የልማቱም ባለቤት እንዲሆን ካደረግነው በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው ችግሮችን ማቃለል ይቻላል፤ ችግሮች ቢፈጠሩ እንኳን መቋቋም ይቻላል።

• ከቀበሌና ወረዳ ጀምሮ በትልልቅ ከተሞች ላይ ነው ማጥራት ያደረግነው። እንደገናም ወደ 11 የሚሆኑ ዞኖች ላይ የማጥራትና መልሶ የማደራጀት ስራ ሰርተናል።

• ሰፋ ያለ ቁጥር ያለው አመራር ከታች እስከላይ የማጥራትና የማስተካከል ስራ ነው የተሰራው። ይህ ደግሞ አገር መቀጠል አለበት፤ ህዝብ መቀጠል አለበት፤ ፓርቲ መቀጠል አለበት በሚል የተከናወነ ነው።

• ብልጽግና ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝቦች በእኩልነት የሚሳተፉበት፤ በፍትሃዊነት የሚወከሉበትም ፓርቲ ነው። እንደገናም በአገራችን ፈተና እየገጠመው ዴሞክራሲ እንዲያብብ ለማድረግ ነው።

• ሀሳብ አለኝ የሚል አካል እዚህ መጥቶ ሀሳቡን ይዞ ሰላማዊ ትግል ማግረግ ይችላል ከዚህ ውጪ ከኦሮሞ ባህል፣ እሴትና ተፈጥሮ ውጪ ኦሮሞን መሳል የሚፈልጉ የኦሮሞ ጽንፈኞችን ህዝቡ በቃችሁ ሊላቸው ይገባል።

• ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ብሄር ብሄረሰቦችም ጋር አንድ ሆኖ ዋጋ የከፈለበትን ለውጥና በለውጡ የጀመረውን ጉዞ ማስቀጠል፤ አካባቢውንም ሰላም ማድረግ አለበት፤ የሚል መልዕክት አለኝ።

ምንጭ አዲስ ዘመን ነሐሴ 25/2012
የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም ወደ ባንክ አደገ
**********************
(ኢፕድ)
የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም (አብቁተ)ወደ ባንክ ማደጉ ተገለጸ።
የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም ዋና ሥራ አስፈፃሚ መኮንን የለውምወሰን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተቋሙ ወደ ባንክ መሸጋገሩን ተከትሎ ከ3 እስከ 6 ወር ባለ ጊዜ ውስጥ ሦራ ለመጀመር ሠራተኞችን በቂ ስልጠና የመስጠትና ቢሮዎችን በማደራጀት ሥራ እንደሚሠራ ተናግረዋል።
ከዚያም ባለፈ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ በብቃት ለመጠቀም በቂ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ዋና ሥራ አስፈጻሚው አብራርተዋል።

ተቋሙ የባንክ አገልግሎቱን በ8 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር መነሻ ካፒታል የሚጀምር ሲሆን በ53 ነባር የተቋሙ ቅርንጫፎች ተደራሽ እንደሚሆንም አስረድተዋል።

ከዚህ በፊት ብድር ለወሰዱ ደምበኞች ሁለት አማራጭ መቀመጡን የተናገሩት ኃላፊው የመጀመሪያው በውሉ መሠረት መጨረስ ሲሆን ሁለተኛው አማራጭ የወሰዱትን ብድር መልሰው በአዲስ ብድር መጠየቅ መሆኑንም ገልጸዋል።

የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም ከዚህ በፊት የሠራቸውን መልካም ሥራዎች በመቀመር አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው የሚስተዋሉ ችግሮችን በማረምና በማስተካከል የክልሉን ኢኮኖሚ ለማሳደግ እንደሚሠራም አመልክተዋል።

የክልሉ መንግሥት ድርሻ 98 በመቶ የነበረ ሲሆን አሁን ግን ወደ ባንክ ሲያድግ ከ70 በመቶ መብለጥ እንደሌለበት መመሪያው ሲለሚገድብ 30 በመቶው ለግል አክሲዮን እንደሚሸጥ መናገራቸውን ከአማራ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
በግል ትምህርት ቤቶች ምንም አይነት ተጨማሪ ክፍያ ማድረግ እንደማይቻል ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ
************
(ኢ ፕ ድ)

በግል ትምህርት ቤት በሚከናወነው የትምህርት ቤት ምዝገባም ሆነ የትምህርት ክፍያ ጭማሪ ማድረግ እንደማይቻል ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

የ 2013 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ምዝገባ ከ ነሃሴ 20/2012 ዓ.ም ጀምሮ እንዲከናወን ትምህርት ሚኒስቴር ማስታወቁን ተከትሎ ከተማሪዎች ምዝገባ እና ከትምህርት ክፍያ ጋር ተያይዞ ወላጆች ቅሬታን እያቀረቡ መሆኑ ተገልጿል፡፡

የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሁሪያ አሊ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ የትምህርት ሚኒስቴር ያወጣውን የትምህርት ቤት ምዝገባ ክፍያ መመሪያን ተላልፈው ምዝገባ እያከናወኑ ያሉ ትምህርት ቤቶች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ እና ከመመሪያ ውጪ የሰበሰቡትን ገንዘብ ለወላጆች ተመላሽ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡

ሚኒስተር ዴኤታዋ የ2013 የትምህርት ዘመን ምዝገባ ላይም ምንም አይነት የክፍያ ጭማሪ ማድረግ እንደማይቻል እና እንደሚያስጠይቅም ተናግረዋል፡፡

ትምህርት ቤቶችም ምዝገባ ሲያከናውኑ ከዚህ በፊት ይጠቀሙበት የነበረውን የክፍያ አቀባበል ዘዴ መቀየር የማይችሉ መሆኑን እና ከዚህ በፊት በነበረው የክፍያ ስርዓት መቀጠል እንዳለባቸውም ገልጸዋል።፡

በተጨማሪም ትምህርት ቤቶች ከመደበኛ የትምህርት ክፍያ እና ከመመዝገቢያ ክፍያ ውጪ ሌሎች ተጨማሪ ክፍያ ማስከፈል ማይቻል መሆኑ ተነግሯል፡፡

የቀጣይ አመት ትምህርት የሚጀመርበትን ቀን በተመለከተም ትምህርት ሚኒስቴር እስከሚያሳውቅ ድረስ ማንኛውም ትምህርት ቤት ትምህርት መጀመር እንደማይችል ሚኒስትር ዴኤታዋ አስታውቀዋል፡፡
የካንሰር፣ ከፍተኛ ደም ግፊት፣ የስኳር በሽታ፣ የልብ ህመም፣ አስምና ለረጅም ጊዜ የሚቆይ የመተንፈሻ አካል ህመም ያለባቸው ህመምተኖች በኮቪድ19 በሽታ እንዳይጠቁ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ ምክንያቱም በዚህ በሽታ ከተጠቁ በሽታው ከሌሎች ሰዎች በበለጠ ሊጠናባቸው ይችላል፡፡

በመሆኑም:-
1. ወደ ጤና ተቋም የሚያደርጉትን ምልልስ በመቀነስ የቀጠሮ ጊዜ በሶስት ወራት እንዲራዘም ተደርጓል።

2. መድሃኒታቸውን በትክክልና ሳያቋርጡ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል።

3. እራስን አለማጨናነቅ፣ በቤት ውስጥ ቀላል የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ

4. ለኮቪድ 19 መከላከያዎችን ማለትም መሸፈን መራራቅ መታጠብን በሚገባ መተግበር

5. ህመም ከተሰማ ወዲያውኑ ወደ አቅራቢያ ጤና ተቋም መሄድ እና ሪፖርት ማድረግ፡፡

6. ህክምና የምናገኝበትንና መድሃኒት የምንወስድበትን ጤና ተቋም እንዲሁም የባለሙያ ስልክ ቁጥር መያዝ፣ በስልክ የጤና ባለሙያዎችን ምክር መጠየቅ፣ ማማከር ተገቢ ነው።

ተጨማሪ መረጃ ወይም ምክር ከፈለጉ በ952 በነፃ ይደውሉ።
ፓርቲዎች ፌዴሬሽን ምክር ቤት የትግራይ ክልል ምርጫን በሚመለከት ጠንካራ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ጠየቁ
*************************
የፌዴሬሽን ምክር ቤት ዛሬ በሚያካሂደው አስቸኳይ ስብሰባ የትግራይ ክልል ምርጫን በሚመለከት ጠንካራ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ የተለያዩ ፓርቲዎች ጥሪ አቀረቡ፡፡

የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ፤ ህብር ኢትዮጵያና ኢዜማ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በትግራይ ክልል ለማካሄድ በታቀደው ክልላዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ በገዢው ፓርቲና በሕወሓት መካከል ያለው ውጥረት በዘለቄታዊ መንገድ መፍታት የሚያስችል ውሳኔ ማስተላለፍ ይጠበቅበታል።

የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ዲሞክራቲክ ፓርቲ ሊቀመንበር ዶክተር አረጋዊ በርሔ እንደተናገሩት፤ ህወሓት ለማካሄድ ያሰበው ምርጫ ህገመንግስቱን የጣሰና ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ያስተላለፈውን ውሳኔ ያፈነገጠ ነው።በተለይም መላው አለም በኮረና ወረርሽኝ በተናወጠበትና ምርጫ ባስተላለፈበት በዚህ ወቅት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫው እንዲራዘም ያስተላለፈውን ውሳኔ የጣሰ ተግባር ነው።ሕወሓት ምርጫውን ለማካሄድ ህገ መንግስታዊ የጊዜ ገደብ ምክንያት ቢያደርግም ዋና አላማውም ትግራይን ከሌላው ህዝብ ለመገንጠል ያለመ ነው።

«ይህ ምርጫ ላለፉት 27ዓመታት በመላው አገሪቱ ያደረሱትን ጥፋትና ጉዳት ተጠያቂነት ለማምለጥ የሚያደርጉት ሽሽት ነው» ያሉት ሊቀመንበሩ፤ የህውሓት አመራሮች ምርጫውን የሚያካሂዱት ለእውነተኛ ዲሞክራሲ መስፈን ከማሰብ ሳይሆን በተገነጠለች ትግራይ ተዝናንተው ለመኖር ያቀዱት ሴራ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ይህ ሁኔታ ትግራይን ብቻ ሳይሆን መላውን የኢትዮጵያ ክፍል የሚያናጋ ስራ መሆኑን ገልፀው፤ «የትግራይ ህዝብ ወንድም እህት ከሆነው ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሊያጋጩት ነው» ብለዋል።

የትግራይ ህዝብ እስካሁን ድረስ የደረሰበት ችግር አልበቃ ብሎ ተጨማሪ መከራ እንዲመጣበት የሕወሓት አመራሮች ሩጫ ላይ መሆናቸውን የጠቀሱት ዶክተር አረጋዊ ፤ ይህም ትልቅና ዘላቂ ችግር ያመጣል የሚል ስጋት እንዳላቸው አስረድተዋል። «ሕወሓት የሚከተለው አካሄድ አደገኛ በመሆኑ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምርጫውን የሚያስቆም ጠንከር ያለ ውሳኔ ማስተላለፍ ይገባዋል» ብለዋል።

ይሁንና ጦርነት ማወጅም ሆነ የትግራይ ህዝብ ለሞት የሚዳርግ ማንኛውም እርምጃ ፓርቲያቸው መኖር አለበት ብሎ እንደማያምን ጠቁመው፤ ይልቁንም የተለያዩ ኢኮኖሚያዊ እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባ ተናግረዋል።ይህም ማለት ፋይናንስ ከመከልከል ጀምሮ የኮምዩኒኬሽንና የትራንፖርት አማራጮችን በመዝጋት ህውሃትን ከጥፋት ጎዳናው መመለስ እንደሚገባ አስገንዝብዋል።ከዚህም ባለፈ ህዝቡን ለተጨማሪ የጦርነት ስጋትም ሆነ በምርጫ ሰበብ ለባከነው ገንዘብ የህውሃትን አመራሮች ተጠያቂ ማድረግ እንደሚገባም አሳስበዋል።

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ናትናኤል ፈለቀ በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ የትግራይ ክልልን የሚያስተዳድረው የሕወሓት መንግስት ምርጫን ለማካሄድ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ ህገመንግስቱንም ሆነ ፓርቲዎች የፈረሙትን የጋራ የቃልኪዳን ሰነድ የሚጣረስ ነው።የክልሉ መንግስት እስካሁንም ድረስ ምክር ቤቱ የሚያስተላልፋቸውን ውሳኔዎች ወደ ጎን በመተው የራሱን መንገድ መምረጡን አስታውሰው፤ አሁንም የምክር ቤቱን ውሳኔ ይቀበለዋል የሚል እምነት እንደሌላቸው አመልክተዋል።በመሆኑም የሕወሓትን አቋም ሊያስቀይር የሚችል ውሳኔ ማስተላለፍ ከምክር ቤቱ እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል፡፡

«በእኛ እምነት የፌዴራል መንግስቱን በሚያስተዳድረው ብልፅግና እና በህወሃት መካከል ያለው ልዩነት ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ነው መፈታት ያለበት» ያሉት አቶ ናትናኤል፤ የፌዴራል መንግስት ህገመንግስቱን የማስከበር ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ ይህንን ኃላፊነቱን በሰላማዊ መንገድ ሊወጣው እንደሚገባ አስገንዝበዋል። «ሕወሃትንም ጨምሮ 107 የፖለቲካ ፓርቲዎች የፈረሙበት የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ቃልኪዳን ሰነድ መሰረት ምርጫ ተደርጎ ህገመንግስቱ እስከሚቀየር ድረስ አሁን ያለውን ህገመንግስት የማክበር ግዴታ ሁሉም ሃይሎች ለመወጣት ቁርጠኝነታቸውን ማሳየት አለባቸው» ብለዋል።

በሌላ በኩል ሕወሓት የፌዴራል መንግስት ምርጫውን ለማስተጓጎል ጥረት ቢያደርግ በህግ እንደሚጠይቀው መግለፁን በሚመለከትም ተጠይቀው « በአንድ በኩል ህግን እየጣሱ በሌላ በኩልም ተጠያቂነትን አሰፍናለሁ የሚለው ነገር የሚያስኬድ አይመስለኝም» ብለዋል፡፡ የፌዴራል መንግስቱን ስልጣን የሚጋፉ ከሆነና የሚወስደውንም እርምጃዎች አንቀበልም የሚሉ ከሆነ እነሱም በህግ ማንንም ተጠያቂ ሊያደርጉ የማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ እንደሚገቡ ተናግረዋል።
የህብር ኢትዮጵያ ሊቀመንበር አቶ ግርማ በቀለም «የፌዴሬሽን ምክር ቤት አስቸኳይ ጉባኤው ከትግራይ ክልል ምርጫ ጋር በተያያዘ ጠንካራ ውሳኔ ያስተላልፋል ብለን እንጠብቃለን»ብለዋል።

በተለይም በሁለቱ ፓርቲዎች መካከል ያለውን የፖለቲካ ውጥረት የሚያረግብ ውሳኔ ማስተላለፍ እንደሚገባው አሳስበዋል። ሁሉንም አካላት ያማከለ የፖለቲካ ድርድር ማድረግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህም አንዱ ሌላውን ለማሸነፍ ከማሰብ ብቻ ሳይሆን በቅንነትና በቁርጠኝነት አገርን ከትርምስ የማዳን ኃላፊነቱን መወጣት እንደሚገባው አመልክተዋል።

«አሁንም ቢሆን በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ ችግሮች መስማትና ማድመጥ የማይፈልገውን ነገር ሁሉ መስማትና ማድመጥ የማይፈልገውን ነገር ሁሉ ሊያደምጥበት የሚገባ ነገር መፈጠር አለበት» ያሉት ሊቀመንበሩ ፣ መንግስት ወይም የፌደሬሽን ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ ቁርጠኛ መሆናቸውን ካሳወቁ ሁሉም ዜጋ ሊተባበር እንደሚችል አስረድተዋል።

በፓርቲዎች መካከል ያለው ግንኙነት ጤናማ እና ልዩነቶች ያለግጭት የሚስተናገዱበት ሁኔታ መፈጠር እንደሚገባው አመልክተው፣ በተለይም ሁሉም የፖለቲካ ሃይሎች የገባነውን ቃል መተግበር ይጠበቅብናል ብለዋል ። «ይህን ቃልኪዳን ለማክበር መንግስት ቁርጠኝነቱን ካሳየና ሕወሓት ለማክበር ካልፈለገ ጉዳዩ በሁለቱ ፓርቲዎች ብቻ ሳይሆን የመላው የኢትዮጵያ ህዝቦች ጉዳይ ነው» በማለት ገልፀዋል።

በተያያዘ ዜና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባል የሆኑ የትግራይ ክልል ተወላጆች ምክር ቤቱ ዛሬ የሚካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ አጀንዳ ያልተገለፀላቸው በመሆኑ በስብሰባው እንደማይሳተፉ በደብዳቤ ገልፀዋል።
አዲስ ዘመን ነሐሴ 30/2012
የፌዴሬሽን ምክር ቤት የትግራይ ክልል የምርጫ እንቅስቃሴን በተመለከተ እየመከረ ነው
---------------------------------
የህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ የትግራይ ክልላዊ መንግስት አካሂደዋለሁ ባለው ምርጫ ዙሪያ የተለያዩ የውሳኔ ሀሳቦችን ለፌደሬሽን ምክር ቤት ማቅረቡን አስታውቋል፡፡

በኮሮና ስጋት ምክንያት በአገር ደረጃ ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ የተወሰነውን ምርጫ በተለይም ክልሉ ለማካሄድ ወስኖ የምርጫ ቦርድ ማቋቋሙ ህገ መንግስትን የሚጥስ ጉዳይ መሆኑን አመላክቷል፡፡

በሌላ በኩል በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ማለትም እንደ ራያ ዴሞክራሲያው ፓርቲና የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ምርጫውን በሙሉ ዝግጅት ለመሳተፍ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታ ሳይኖር በዚህ ወቅት ምርጫ መደረጉ አግባብነት የለውም ብለው ያቀረቡት አቤቱታ ተቀባይነት ያለው መሆኑን ጉባኤው በውሳኔ ሀሳብነት አካቶታል፡፡

እንደ ወልቃይትና ራያ ባሉ አካባቢዎች ከማንነት ጉዳይ ጋር የተነሱ ቅሬታዎች ከምርጫው ጋር ተያይዞ በአካባቢዎቹ የሰብዊ መብት ጥሰት እየተፈፀመ ነው በሚል የቀረቡ አቤቱታዎችም ህገ መንግስታዊ መሰረት ያላቸው በመሆኑ ሊጤኑ እንደሚገባ ጉባኤው አመልክቷል፡፡

የሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ያቀረባቸውን የውሳኔ ሀሳቦችን ተከትሎ የፌደሬሽን ምክር ቤት ይበጃል ይበጃል ያለውን ውሳኔ እንዲያሳልፍ ጠይቋል፡፡

የኢቢሲ ዘገባ እንዳመለከተው የፌደሬሽን ምክር ቤትም ዛሬ በጠራው አስቸኳይ ስብሰባው የህገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ባቀረበለት የውሳኔ ሀሳቦች ዙሪያ በዝግ እየመከረ ይገኛል፤ ይህን ተከትሎም የምክር ውይይት ካደረገበት በኋላ ውሳኔም ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የሩሲያ የኮሮና ቫይረስ ክትባት የኮቪድ 19 በሽታን የመቋቋም ምልክት እያሳየ ነው
የሩሲያ የኮሮና ቫይረስ ክትባት የኮቪድ 19 በሽታን የመቋቋም ምልክት እያሳየ መሆኑን የአገሪቱ ሳይንቲስቶች
አስታወቁ።
ቢ ቢ ሲ እንደዘገበው የሩሲያ ሳይንቲስቶች የኮሮና ቫይረስ ክትባት ውጤት በተመለከተ የመጀመሪያውን ሪፖርት
ለህትመት አብቅተዋል።
በህክምና መጽሄት ላይ የወጣው ሪፖርት እንዳመለከተው ክትባቱ የተሰጣቸው እያንዳንዶቹ ሰዎች ቫይረሱን ለመዋጋት
የሚያስችላቸው የመከላከል አቅም (አንቲቦዲ) አጎልብተዋል።
ሩሲያ ክትባቱ በአገር ውስጥ ስራ ላይ እንዲውል በነሀሴ ወር ፍቃድ የሰጠች ብቸኛ አገር መሆኗም ተገልጿል።
ኤክስፐርቶች የክትባቱን ብቃትና ደህንነት ለማረጋገጥ የተደረገው ሙከራ በጣም አነሰተኛ ነው ማለታቸውም
ተጠቅሷል።
ሆኖም የተገኘው ውጤት የክትባቱ ውጤታማነት የሚያመላክት መሆኑ በአገሪቱ እየተገለጸ ነው።
የክትባቱ ሙከራ በሰኔና ሀምሌ ወራት ሁለት ጊዜ መካሄዱ በሪፖርቱ የተጠቀሰ ሲሆን፤ በእያንዳንዱ ሙከራ ለ38 ፈቃደኛ
ለሆኑ ጤነኛ ሰዎች ክትባቱ መሰጠቱ ተመልክቷል።
ከ18 እስከ 60 የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙት ሰዎች ላይ ለ42 ቀናት ክትትል መደረጉና በሶስት ሳምንታት ውስጥ
የመከላከል አቅም (አንቲቦዲ) ማጎልበታቸው ነው የተገለጸው።
በአብዛኛው የታየው የክትባቱ የጎንዮሽ ጉዳትም የእራስ ምታት ህመምና የመገጣጠሚያ ህመም መሆኑ ተጠቁሟል።
የኮቪድ 19 በሽታን ከመከላከል አንጻር የክትባቱን ደህንነትና ውጤታማነት የበለጠ ለማረጋገጥ የክትባቱን ሙከራ
በስፋትና ለረጅም ጊዜ በሚቆይ መልኩ ማካሄድና ተጨማሪ ክትትል እንደሚያስፈልግ በሪፖርቱ መጠቀሱ ተመልክቷል።
በክትባቱ የ3ኛ ዙር ሙከራ ከተለያዩ የዕድሜ ክልሎች የሆኑ 40 ሺህ ፈቃደኞች እንደሚሳተፉም ተጠቅሷል።
በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ ኪት ሊመረት ነው
**********************
(ኢ ፕ ድ)
በኢትዮጵያ የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ ኪት ከአንድ ወር በኋላ ማምረት እንደሚጀመር የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ ለኢዜአ እንደተናገሩት ኮሮናቫይረስን የመመርመር አቅምን ከፍ ለማድረግ በርካታ ሥራዎች እየተሰሩ ነው።
በአሁኑ ወቅትም ከአንድ ወር በኋላ ከቻይና መንግሥት ጋር በመተባበር የመመርመሪያ ኪት ለማምረት ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
ለእዚህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ድጋፉን ከምታደርገው የቻይና መንግሥት ጋር በጉዳዩ ላይ እየመከሩ መሆኑን ገልጸዋል።
“የመመርመሪያ ኪቱን በአገር ውስጥ ማምረት ሲጀመር ከውጭ የሚገባውን ኪት ሙሉ በሙሉ ያስቀራል” ያሉት ዶክተር ደረጀ፣ ምርቱ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት እንደሚዳረስም ተናግረዋል።
ከእዚህ በተጨማሪ በየጊዜው እያደገ የመጣውን የመመርመር አቅም በእጅጉ ከፍ እንደሚያደርገው ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት የኢንፌክሽን መከላከያ ግብዓቶች በኢትዮጵያ በስፋት መመረት መጀመራቸውን ጠቁመው፣ የኮሮናቫይረስ መከላከያ ቁሶችን ወደ ውጭ አገራት መላክ መጀመሩንም ገልጸዋል።
እንድ ኢዜአ ዘገባ፤ በሐዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ እነዚህን ቁሶች የሚያመርቱ ኩባንያዎች ቀዳሚ መሆናቸውን ሚኒስትር ዴኤታው አመልክተዋል።
በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት 52 የኮሮናቫይረስ መመርመሪያ ማዕከላት የሚገኙ ሲሆን በእነዚህም በቀን ከ20 ሺህ በላይ ናሙናዎችን መመርመር ተችሏል።
ለአማራ ክልል ሰላም መስፈን አስተዋጽዖ ላበረከቱ አካላት የምስጋና ዝግጅት እየተካሄደ ነው።
በመድረኩ ላይ የክልል ርዕሰ መስተዳድሮችን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና ሌሎች ጥሪ የደረገላቸው እንግድች ተገኝተዋል።
በህብረተሰቡ ውስጥ በሚከሰት ሞት የአስከሬን አያያዝ ላይ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ተጠየቀ
በሃገር አቀፍ ደረጃ የኮሮና ቫይረስ በሽታን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መሰረት በሁሉም የሃገሪቱ ክፍል የአስከሬን አያያዝ ላይ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲደረግ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና አደጋ ማስተባበሪያ ማእከል አሳሰበ፡፡
ይህም ወረርሺኙን ለመግታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ነው የተመለከተው፡፡
የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አስቻለው አባይነህ እንደገለጹት በቀብር ስነ-ስርዓት ወቅት በርካታ ሰዎች ከተለያዩ ቦታዎች ስለሚመጡ የኮሮና ቫይረስን በማስተላለፍ በኩል የተለያዩ አጋጣሚዎች ሊፈጠሩ ይችላሉ፤ይህ ደግሞ ችግር ላይ የሚወድቁ ሌሎች ሰዎችን መፍጠር ስለሚሆን የቀብር ስነ-ስርዓት ሲፈጸም ህብረተሰቡ በእስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ላይ የተቀመጡትን መመሪያዎች በሚገባ በመገንዘብ ፣ተገቢውን ጥንቃቄ በመውሰድ ተግባራዊ ሊያደርግ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
የአስከሬን የቅብር ስነ-ስርዓት ላይ በሚኖሩ የተለያዩ ንክኪዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሺኝ እንዳይስፋፋ በሃገር አቀፍ ደረጃ ማንኛውም የሞተ ሰው የቅብር ስነ-ስርዓት ከመካሄዱ አስቀድሞ የኮሮና ቫይስ የላቡራቶሪ ናሙና መወሰድ እንዳለበትም ገልጸዋል፡፡
ከዚህ በፊት የቀብር ስነ-ስርዓት ለማድረግ የኮቪድ 19 ምርመራ ውጤት እስኪመጣ ይጠበቅ የነበረው መመሪያ ተሻሽሎ ከሰኔ 11/2012 ዓ.ም ጀምሮ ያለውን የቅብር መዘግየት፣የማህብረሰቡን ቅሬታ ታሳቢ በማድረግ የአስከሬን ናሙና እንደተወሰደ የቀብር ስነ-ስርዓት እንዲፈጸም መደረጉንም አቶ አባይነህ ገልጸዋል፤
ከጤና ተቋማት ውጪ ሞት በሚከሰቱ ጊዜ ኮቪድ -19 ን ለመከላከል የሚደረጉ ጥንቃቄዎች ከጤና ተቋማት ውጪ ሞት በሚከሰት ወቅት የአስከሬን ግነዛ፣አስከሬን የማጓጓዝ ፣የመቅበር እና የሃዘን ስነ-ስርዓት ላይ የሚደረጉ የሟች ቤተሰቦችና አስከሬን የሚገንዙ ሰዎች ሊያደርጓቸው የሚገቡ ጥንቀቄዎች እና ግዴታዎች በአስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጅ መሰረት የኮቪድን -19 ወረርሽን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚከተሉትን ተግባራት ተፈፃሚ ሊሆኑ እንደሚገባ ኢንስቲትዩቲ አስታውቋል፡፡በዚህም
• ለጤና ተቋም ማሳወቅ አስከሬኑ የኮቪድ-19 ላቡራቶሪ ናሙና እንዲወሰድ ማድረግ
• አስከሬን የሚገንዙ ሰዎች የእጅ ጓንት፣የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል ወይም ከፕላስቲክ የተሰራ ጓንት እና መነጽር እንዲለብሱ ማድረግ
• ሀኪሞች በሌሉባቸው አስከሬን ለማጓጓዝ ተገቢውን ጥንቃቄ ለማድረግ በሚችሉ ሰዎች ብቻ እንዲከናዎን ማድረግ
• ኮቪድ 19 ምልክት የሚታይባቸው ሰዎች አስከሬን ከሚያጓጉዙ ሰዎች ጋር እንዳይሳተፉ ማድረግ
• በቀብር ስነ-ስርዓቱ ላይ የሚገኙ ሰዎች ሁሉ ሁለት የአዋቂ እርምጃ በመራራቅ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ እንዲሁም አስከሬኑንም ሆነ አስከሬኑ ያለበትን ሳጥን ያለመነካካትና ያለመሳም
• አስከሬን ከተጫነ በኋላ የሰውነት መከላከያ አልባሳት በመልበስ አስከሬን ያለበትን ሳጥን ፣አስከሬን የገነዙትን ሆነ አስከሬኑ የነካካቸውን ቦታዎች ወይም ቁሳቁሶች፣ሟቹ የነበረበትን አልጋ፣የተለያዩ የመገልገያ እቃዎች፣የቤቱን ወለል ፣የተጓዘበትን መኪና እና አጠቃላይ እቃዎች በበረኪና ውህድ እንዲጸዳ ማድረግ
• አስከሬን የሚያጓጉዙ ሰዎች ጓንት ማድረግ የግድ ሲሆን
በጓንታቸው የተለያዩ እቃዎችን ያለመነካካት እና አስከሬኑን ከቦታ ወደ ቦታ አለማንቀሳቀስ
• አስከሬን ከግነዙትም ሆነ ከሟች ቤተሰቦች ሁለት የአዋቂ እርምጃ መራቅ እንዳለ ሆኖ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ መጠቀም
• የሟች ቤተሰቦች በተቻለ መጠን አስከሬኑን በሞተበት አካባቢ መቅበር ይኖርባቸዋል፤ወደ ሌላ ቦታ የማጓጓዝ ግዴታ በሚፈጠርበት ጊዜ ከፍተኛ ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡
• የእምነት ተቋማት ሃላፊዋች እና የሃይማኖት አባቶች አስከሬኑ ወደ ቀብር ቦታ ከመምጣቱ በፊት የኮቪድ-19 የላቦራቶሪ የምርመራ ናሙና መወሰዱን የማረጋገጥ ግዴታ አለባቸው፡፡
• በቀብር ስነ-ስርዓቱ ወቅት ከ50 የማይበልጡ ሰዎች መሆናቸውን መከታታል እና ከጤና ተቋማት የሚሰጡ መመሪያዎችን መከታተልና ተግባራዊ ማድረግ እንዳለባቸውም የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና አደጋ ማስተባበሪያ ማእከል አሳስቧል፡፡
በመዲናዋ በኮሮና ቫይረስን ተከትሎ በወጣው የትራንስፖርት አገልግሎት ታሪፍና የመጫን አቅም መመሪያ ላይ ማሻሻያ ተደረገ
********************************
(ኢ ፕ ድ)
በአዲስ አበባ ከተማ የኮሮና ቫይረስ መከሰትን ተከትሎ በወጣው የትራንስፖርት አገልግሎት ታሪፍና የመጫን አቅም መመሪያ ላይ ማሻሻያ ተደረገ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ባለስልጣን ማሻሻያውን አስመልክቶ በዛሬው እለት መግለጫ ሰጥቷል።

በመግለጫውም የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ሚኒባስ፣ የአንበሳ አውቶብስ፣ ሸገር እና ሀይገር ባሶች በወንበራቸው ልክ እንዲጭኑ ተወስኗል።

የሚኒባስ ታክሲዎች ከኋላ ባለው መቀመጫ ከ2 ሰው በላይ መጫን አይችሉም ብሏል ቢሮው በመግለጫው።

እንዲሁም ባለ ሶስት እና ባለ አራት እግር (ባጃጅ) ተሽከርካሪዎች እስከ ሹፌሩ 3 ሰው መጫን እንደሚችሉም ነው የተገለፀው።

ቀላል ባቡር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ በ25 በመቶ የመጫን አቅም ብቻ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው አሁን ላይ ወደ 75 በመቶ ክፍ እንዲል መደረጉንም አስታውቋል።

ከታሪፍ ጋር በተያያዘም በእጥፍ ሲከፈል የነበረው ቀርቶ መጠነኛ ማሻሻያዎች መደረጋቸውንም ባለስልጣኑ አስታውቋል።

በዚህም መሰረት የሚኒባስ ታክሲ ታሪፍ እንደሚከተለው ማስተካከያ ተደርጎበታል።

እስከ 2 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 1 ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን ላይ 2 ብር

ከ2 ነጥብ 6 እስከ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 3 ብር የነበረው አሁን 4 ብር

ከ5 ነጥብ 1 እስከ 7 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 4 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን 6 ብር

ከ7 ነጥብ 6 እስከ 10 ኪሎ ሜትር በፊት 6 ብር የበረው አሁን 8 ብር

ከ10 ነጥብ 1 እስከ 12 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር 7 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን 10 ብር

ከ12 ነጥብ 6 እስከ 15 ኪሎ ሜትር በፊት 9 ብር የነበረው አሁን 12 ብር

ከ15 ነጥብ 1 እስከ 17 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 10 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን 13 ብር

ከ17 ነጥብ 6 እስከ 20 ኪሎ ሜትር በፊት 12 ብር የነበረው አሁን 15 ብር

ከ20 ነጥብ 1 እስከ 22 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 13 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን 17 ብር

ከ22 ነጥብ 6 እስከ 25 ኪሎ ሜትር በፊት 15 ብር የነበረው አሁን 19 ብር

ከ25 ነጥብ 1 እስከ እስከ 27 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር በፊት 16 ብር ከ50 ሳንቲም የነበረው አሁን 20 ብር

ከ27 ነጥብ 6 እስከ 30 ኪሎ ሜትር በፊት 18 የነበረው አሁን 22 ብር ሆኖ ማሻሻያ መደረጉንም የከተማ አስተዳደሩ ትራንስፖርት ባለስልጣን በመግለጫው አመላክቷል።

እንደ ኤፍቢሲ ዘገባ ከተፈቀደው ሰው በላይ መጫን ከ1 ሺህ ብር ጀምሮ ከታሪፍ በላይ ማስከፈል 1 ሺህ 500 ብር ጀምሮ እንደሚያስቀጣም ባለስልጣኑ አስታውቋል።

ይህንን ለመቆጣጠር ከትራፊክ ፖሊስ በዘለለ የፖሊስና የፀጥታ አካላት መሰማራታቸው የተገለፀ ሲሆን፥ ህብረተሰቡ ከታሪፍ በላይ የሚያስከፍሉ እና ትርፍ የሚጭኑትን ለመጠቆም የሚጠቁምበት የስክል ቁጥር በቅርቡ ይፋ ይሆናል ብሏል።
ሞትን አይቼ ተመለስኩ
የ27 ዓመት ወጣት ነኝ፤ በአዲስ አበባ ከተማ ሽሮ-ሜዳ አካባቢ ነው የምኖረው፡፡ አስታውሳለሁ ቀኑ ሰኔ 16 ሐሙስ ዕለት ነው፤ ካለወትሮዬ ምቾት የሚነሳ ስሜት ተሰማኝ፡፡ ቀኑን ሙሉ እንዲሁ ስረበሽ ነበር የዋልኩት፡፡ ማታ ላይ ምግብ ባያሰኘኝም በግድ ቀምሼ ተኛሁ፡፡
እኩለ ሌሊት ብን ብን የሚል ደረቅ ሳል ድንገት ከእንቅልፌ ቀሰቀሰኝ፤ ሰውነቴም በሚነድ እሳት ውስጥ እንዳለ ሆኖ አገኘሁት፡፡ ባኞ ቤት ገባሁና በቀዝቃዛ ውሃ ፊቴን ታጠብኩ ሊበርድ አልቻለም፡፡ አፌ ስለደረቀና ስለመረረኝ በውሃ ተጉመጠመጥኩት፤ እንደማቅለሽለሽ አለኝ፡፡
ተከራይቼ ስለምኖር በወቅቱ አጠገቤ የሚረዳኝ ሰው አልነበረምና እማደርገው አጣሁ፡፡ ቆይቼ ለጓደኛዬ ደውዬ እንደታመመኩ ነገርኩት፡፡ መኪና ይዞ መጣና ወደ አቅራቢያዬ ወደሚገኝ ጤና ጣቢያ ወሰደኝ፤ እነሱም ሁኔታውን አይተው ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ላኩኝ፡፡ የሆስፒታሉ ሃኪሞችና ነርሶች ተረባረቡና አስገቡኝ፡፡ ወዲውኑ ምርመራ ታዞልኝ ናሙና እንድሰጥ ተደረገ፡፡ ትኩሳቱ እየጨመረ መጣ፤ አጠገቤ የሚረዱኝን የጤና ባለሙያዎች ጭምር የሰውነቴ ግለት ይታወቃቸው ነበር፡፡ ቀስ በቀስ እየደከመኝ እየደከመኝ መጣ፡፡
የምርመራ ውጤቴ ደረሰ፤ ውጤቱም የኮሮና ቫይረስ በሽታ መሆኑ ተረጋገጠ፡፡ ከዚያ በኋላ የሆንኩትን ሁሉ በውል አላቀውቅም ነበር፡፡
ከ7 ቀናት በኋላ ከሰመመን ስሜቴ ወጥቼ ራሴን ሳውቅ በአፍንጫዬ ቱቦ እና በእጄ ላይ ደግሞ ግሉኮስ ተተክሎልኛል፤ በዙሪያዬ ደግሞ መላ አካላቸውን በተሸፈኑ ጤና ባለሙያዎች ተከብቤ አገኘሁት፡፡ ድንጋጤ አይሉት የመረበሽ ሰሜት ተሰማኝ፤ ከአጠገቤ የነበረ ሃኪም ሊያረጋጋኝ ሞከረ፡፡ አይኖቼ በእምባ ተሞሉ፡፡
ቀስ በቀስም ራሴን እያወቅሁ ስሄድ ወደኋላ እንደህልም ያየሁትን ማስታወስ ጀመርኩ፤ ነጭ የለበሱ የለበሱ ሰዎች አጅበውኝ ይዘውኝ ሲሄዱ ያየሁት ታወሰኝ፡፡ ሰፊ አዳራሽ ያለው ዙሪያ ገባው በአበቦች ያጌጠ ውብ ቦታም ይታወሰኛል፡፡ እንዲህ አይነት ስፍራ በምድር ላይ ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ፤ ምንድን ነው ነገሩ ብዬም ራሴን ጠየኩ፡፡
በተደረገልኝ ህክምናና እንክብካቤ ራሴን በደንብ እያወኩኝ ስመጣ ያ ያየሁት ነገር በሞትና በህይወት መካከል የነበርኩበትን ወቅት በማስታወስ ላይ እንደነበርኩ ተረዳሁ፡፡ ሳልሞት ሞትን አይቼ እንድመለስ የረዳኝን ፈጣሪ እጅግ አድርጌ አመሰግነዋለሁ፡፡
እኛ የምናውቀው በሽታ ሲያመን ሰው እንዳያስታምመንና እንዳይጠይቀን እስከ መከልከል የሚያደርስ አልነበረም፡፡ ኮሮና ግን የተለየ ነው፤ ቤተሰብ እንኳ ከጎኔ ሆኖ እንዲያስታምመኝ ያለፈቀደልኝ ጨካኝ በሽታ ነው፡፡
ከምንም በላይ ግን የህክም እርዳታና እንክብካቤ ያደረጉልኝን የጤና ባለሙያዎች በእጅጉ ላመሰግናቸው እወዳለሁ፤ በህይወት ዘመናቸው ሁሉ ክፉ አይንካቸው፡፡
ቀድሞ ያልታዬኝ ስህተቴ አሁን ላይ ቁልጭ ብሎ ታይቶኛል፤ ለበሽታው የነበረኝ ግዴለሽነት ዋጋ አስከፍሎኛል፡፡ እኔ እድሉን አግኝቼ ታክሜ መዳኔ ቢያስደስተኝም አሁን ላይ ጤና ተቋማት ወደ መጨናነቅ ደረጃ እየደረሱ መሆኑን ስሰማ በእጅጉ አሳዝኖኛል፤ ችግሩን ቀምሸዋለሁና፡፡ እናም ወገኖቼ ከእኔ ተማሩ፤ በተቻለ መጠን ጥንቃቄ በማድረግ ከኮሮና በሽታ ራሳችንና ቤተሰባችንን እንጠብቅ መልዕክቴ ነው፡፡
(ከኮሮና ቫይረስ በሽታ ያገገመ ግለሰብ ታሪክ፤ ስሙ በግል ጉዳዩ ምክንያት ያልተጠቀሰ)
በክፍል ውስጥ የተማሪዎችን ቁጥር በመመጠንና ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም ትምህርት ለማስጀመር ጥናት ተደርጓል - አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ የትምህርት ሚኒስተር ዴኤታ
*****************************
(ኢፕድ)
ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሊያጋልጥ በማይችልና ጥንቃቄ በተሞላበት መልኩ የመማር ማስተማር ሂደቱን በአዲሱ ዓመት ለማስጀመር ጥናት መደረጉን ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።
ሚኒስቴሩ እንዳለው በአንድ ክፍል የሚማሩ ተማሪዎችን ቁጥር በመመጠንና ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም ትምህርት ማስጀመር በሚቻልበት መንገድ ላይ ጥናት ተደርጓል።
የትምህርት ሚኒስተር ዴኤታ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ የ2013 የትምህርት ዘመን የተማሪዎች ምዝገባ መጀመሩን አመልክተዋል።
ኮሮናቫይረስ በፖለቲካ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚያዊ ዘርፍ በሳደረው ጫና ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ውጭ እንዲሆኑ መደረጉንም አስታውሰዋል።
አቶ ሚሊዮን እንዳሉት ትምህርት መቋረጡ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭትን ለመግታት አስተዋፅኦ ቢኖረውም በተማሪዎች በተለይም ከህጻናት እድገት አንጻር ከፍተኛ ጫና አሳድሯል።
በተለይ ህጻናት ትምህርት ዝግ ሆኖ ቤት በመዋላቸው ለአስገድዶ መደፈርና ያለዕድሜ ጋብቻ መዳረጋቸውን ሚኒስቴር ዴኤታው ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ባሉ ከ42 ሺህ በላይ ትምህርት ቤቶች ከ700 ሺህ በላይ መምህራንና ከ26 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች ይገኛሉ።
“ወቅቱ ኮሮናቫይረስ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ ያለበት በመሆኑ ትምህርት ቤቶች መከፈታቸው ህብረተሰቡን እያነጋገረ ነው” ያሉት አቶ ሚሊዮን፣ ወረርሽኙ የሚቆምበት ጊዜ ባለመታወቁ ትምህርት እንደሚጀመርና ይህም የጤና ጥበቃ የሚያስቀምጠውን መስፈርት ተግባራዊ በማድረግ እንደሚከናወን ገልጸዋል።
ባለፈው የመማር ማስተማር ሂደት በአማካይ ከ60 እስከ 80 ተማሪዎች በአንድ ክፍል ውስጥ ይማሩ የነበረበት ሁኔታ እንደነበር አቶ ሚሊዮን አስታውሰዋል።
በቀጣይ ትምህርት ሲከፈት በቅድመ መደበኛ 14 በመቶ የሚሆኑትን ትምህርት ቤቶች ከ20 እስከ 25 ተማሪዎችን ብቻ በአንድ ክፍል እንዲያስተምሩና አንድ ተማሪ በአንድ ዴስክ ብቻ እንዲቀመጥ ለማድረግ መታቀዱን አስረድተዋል።
አቶ ሚሊዮን እንዳሉት ቀሪዎቹ 80 በመቶ ተማሪዎች በፈረቃ እንዲማሩና 6 በመቶ የሚሆኑ ተማሪዎች ደግሞ ትምህርት ቤት በመገንባትና አማራጭ ማህበራዊ ተቋማትን በመጠቀም ለማስተማር ታቅዷል።
በአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 24 በመቶ ወይም ከ20 እስከ 25 ተማሪዎች በአንድ ከፍል ውስጥ እንዲማሩ፣ 56 በመቶ በፈረቃ እንዲሁም 20 በመቶ ተጨማሪ ክፍል በመገንባት እንዲማሩ ተወስኗል።
በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 19 በመቶ ተማሪዎች ወይም ከ20 እስከ 25 የሚሆኑት በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲማሩ እንዲሁም 50 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ በፈረቃ የሚማሩ ይሆናል።
ሌሎች 31 በመቶ ተጨማሪ ክፍሎችን በመገንባትና አማራጭ ማህበራዊ ተቋማትን በመጠቀም ለማስተማር መታቀዱንም አመልክተዋል።
በሽታን በመከላከል የትምህርት ተቋማትን ስራ ለማስጀመር ተቋማቱን ማስፋት እንደሚገባም አቶ ሚሊዮን ተናግረዋል።
ኦሮሚያ ክልል ሃብት በማሰባሰብ 30 ሺህ አዳዲስ ክፍሎችን መገንባቱን የጠቆሙት ሚኒስትር ዴኤታው፣ “አማራ ክልልም በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ያለውን የክፍል እጥረት ችግር ለመቅረፍ ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው” ብለዋል።
ተማሪዎች በተረጋጋ ሁኔታ እንዲማሩ የቀደመው የመማር ማስተማር ስልት በአዲስ መልክ እንደሚሆን ጠቁመው፣ ይህም የቡድን ስራን ጨምሮ የተማሪዎችን አካላዊ ንክኪን ሊያስቀር በሚችል መልኩ እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
አቶ ሚሊዮን እንዳሉት የትምህርት ቤቶች አከፋፈት ጥናቱን መሰረት ያደረገ ይሆናል።
ትምህርት ቤቶች በተመሳሳይ ወቀት አንድ ላይ ሊከፈቱ እንደማይችሉና ደረጃ በደረጃ የመክፈት ሂደት እንደሚኖር ገልጸው፣ አጀማመሩ ከክልል ክልልና ከዞን ዞን ሊለያይ እንደሚችል አመልክተዋል።
ይህንን ተከትሎ አንዳንድ የግል ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ጭማሪ እየጠየቁ መሆኑን ገልጸው፣ ይህን በሚያደርጉ ተቋማት ላይ ትምህርት ሚኒስቴር ትምህርት ቤቶችን እስከመዝጋት የሚደርስ እርምጃ እንደሚወስድ አመልክተዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።
ጠቅላይ ሚኒስትሬን ላለማመስገን ምክንያት የለኝም፤ አመሰግናለሁ !
በተንቀሳቃሽ ስልኬ የማኅበራዊ ትስስር ገጼን ከፍቼ መረጃ ፍለጋ እጆቼን ከላይ ወደታች እያንሸራተትኩ ድንገት አንድ ተንቃሳቃሽ ምስል እይታዬን ገታው። ያየሁትን በቀላሉ ለማመንም ከበደኝ። ምክንያቱ ደግሞ ያየሁት ሰው ሙሉ ገጽታው በፊት መሸፈኛ ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መለየት ቢያስቸግረኝም ድምፁ ግን ቁርጥ እሱን ነው። የእኔን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አህመድ።
እኔ ደስም ግርምም ብሎኛል። ይህ በኢትዮጵያ ተደርጎ አላየሁም። ይህንን ብቻ በማድረጉ እኮ ምን ያህል ወደ ህዝብ መቅረብ እንደሚፈልግ መረዳት ይቻላል። ያዩትና ያናገራቸው እንደመዝለልም እንደመደንገጥም አርጓቸዋል። እኔን እንዲህ አጋጥሞኝ ቢሆን ኖሮ ስል አሰብኩ፤ እኔ እንጃ! እጮህ ነበር። ታድያ ይህን ድንቅ መሪ እንዴት ነው አለማመስገን የሚቻለው።
መሪዬ የትራፊክ ፍሰቱ የተሳለጠ ይሆን ዘንድ በአንድ በኩል ሲያስተናብር በሌላ በኩል ደግሞ በፍቅር በተሞላ አንደበት መልካም ዘመንን ለወገኖቹ ሲመኝና የፍቅርም ስጦታ ሲያበረክት ላየ በእርግጥ ልብን በሐሴት ይሞላል። እኔ ሁሌም አንድ ነገር በአገሬ ኢትዮጵያ ይሆን ዘንድ እመኝ የነበረውን ድርጊት በመፈጸሙም ላመሰግነው ወደድኩ። በእርግጥም ብዙዎቻችሁ ልክ እንደ እኔው ተመሳሳይ ግርምታን ሳያጭርባችሁ እንዳልቀረ አስባላሁ።
ወርዶ ጫማ ለመጥረግ በቂ የሞራል ስንቅ ያለው! እንዳለመታደል ሆኖ ነው እንጂ እ ይህን ማን አድርጎ አይተናል? ማንም፤ እንዲያው ግን መመሰጋገን ምን ወጪ አለው? ምንም፤ መልካምና ልብን በሐሴት የሚሞላ ተግባር ለፈጸመ ቢመረንም ቢጣፍጠንም ማመስገንን መልመድ አለብን።
እርግጥ ነው ብዙዎቻችን በልባችን አድንቀን አሊያም ደግሞ ገርሞንም ይሆናል። ነገር ግን አድናቆቱንም ሆነ ምስጋናውን ከአንደበታችን ሲወጣ ድል እንነሳበታልና ይልመድብን። ስናመሰግን እናከብራለን።
እንከበራለን፤ ተመስጋኝም አመስጋኝም ዋጋቸው ከፍ ያለ ነውና።
የአንዳንድ አገር መሪዎች ኧረ እንዲያውም የጥቂት አገር መሪዎች ድንገት በህዝባቸው መካከል በመከሰት የህዝቡን እውነተኛ ስሜት ሲያስተውሉና ወደህዝቡ ወረድ ብለው የልቡን ሲያዳምጡ ሳይ በእጅጉ እቀና እንደነበር አልሸስግም። አንዳንዶቻችሁ ይህ ምን ያስደንቃል ትሉ ይሆናል፤ በኛ ባለ ስልጣናት ስለልቦና ለዚያውም በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ !
እኔ ጠቅላይ ሚኒስትሬን የትራፊክና የፖሊስን የደንብ ልብስ ለብሶ ሰዎችን ስላናገረ ብቻ ሳይሆን ከዚህ ቀደምም ሲያደርጋቸው በነበሩ ሰው ሰው በሚሸቱ ድርጊቶቹ አለማመስገን አይቻለኝም። ለማመስገን ብዕሬን የቀሰርኩት ባደረጋቸው በርካታ ማህበረሰባዊ ትርጉማቸው ከፍ ባሉ ዘመን ተሸጋሪ ጉዳዮች ነው።
ፖለቲካዊ የሆኑ ነገሮቹን ለጊዜው ወደጎን እናደርጋቸው፤ ስብዕናው ለእኔ ከምገምተው በላይ ነው። በእርግጥም መሪዬን በቅርብ ሆኖ ላየው ፍጹም የሆነ ፈገግታና ትህትና ስለማይለየው ማንንም ቢሆን በዚያ ፍቅሩ መሸነፉ አይቀርም። ከትልልቆቹ ጋር እንደትልቅ፣ ከሕፃናቱ ጋር እንደእነርሱ፣ ከጎዳና ተዳዳሪውም ሆነ ከየትኛውም ሰው ጋር የሚያሳየው ትህትና የሚገርም ነው።
የልብን መዝገብ አንደበት ይተርከዋል እንዲል እኔ ጠቅላይ ሚኒስትሬን እንዲህ አመሰገንኩ። እናንተም አመስግኑ፤ የምስጋና ንፉጋን አትሁኑ እናመስግን፤ በምስጋና አለማመስገንን። በምስጋና ውስጥ በረከትም ኃይልም አለ።
አዲስ ዘመን ጳጉሜን 4/2012
ቅድስት ሶሎሞን ከሽሮ ሜዳ
የኢትዮጵያ የምንጊዜም ባለውለታ የጦር ሜዳ ጀግኖቻችን በያላችሁበት ታላቅ ምስጋና ይደረሳችሁ !!
ለኢትዮጵያ ሀገራችን ባላውለታ ለሆናችሁ በደምና በአጥንታችሁ ክስካሽ ታላቅ መስዋእትነት ከፍላችሁ የተሰነዘረብንን ጥቃት መክታችሁ ኢትዮጵያን በክብር ላስረከባችሁን የኢትዮጵያ ጀግኖች በሙሉ ያለእናንተ ታላቅ ተጋድሎ የዛሬዋን ሀገር አናገኛትም ነበርና በዚህ የምስጋና ቀን የሀገር ባለውለታ ናችሁና ታላቅ ምስጋና ይድረሳችሁ !!
በጠላት ወረራ ዘመን የኢጣሊያን ፋሽስት ወረራ መክታችሁ በዱር በገደል ተንከራታችሁ ያለበቂ ስንቅና ትጥቅ ኢትዮጵያዊ ቁርጠኝነትንና ጀግንነትን ሰንቃችሁ እምቢ ለሀገሬ ብላችሁ ተዋግታችሁ ድል አድርጋችሁ የተፈራች የተከበረች ሀገር ላስረከባችሁን አባቶቻችንና አያቶቻችን በሕይወት ላላችሁትም ለሌላችሁትም ጀግኖች በዚህ የምስጋና ቀን ታላቅ ምስጋና ይድረሳችሁ !!
በሶማሊያ ወረራ ወቅት የእናት ሀገር ጥሪ ሲደረግልህ የእርሻ ማሳህን ጦሙን አድሮ አንተ ሞፈርና ቀንበርህን ሰቅለህ፤ ትዳርህን ልጆችህን ትተህ፤ ቅሌን ማቄን ሳትል ዘምተህ ታላቅ ተጋድሎ በማድረግና መስዋእትነት በመክፈል ኢትዮጵያን ላስከበርካት የቀድሞው የኢትዮጵያ መደበኛ ሰራዊትና የሚሊሽያው ሰራዊት አባላት በህይወት ላላችሁትም ለሌሉትም ያለእናንተ ታላቅ መስዋእትነት ይህችን ውብ ሀገር መረከብ አይቻልም ነበርና በዚህ የምስጋና ቀን ታላቅ ምስጋና ይድረሳችሁ !!
ለኢትዮጵያ የቀድሞውም የአሁኑም የጦር መሪ ጀነራሎች ከፍተኛ መኮንኖች፤ መስመራዊ መኮንኖች፤ ባለሌላ ማዕረጎች፤ ጀግናው ተዋጊ ሰራዊት፤ የኢትዮጵያ የምድር ጦር፤ የአየር ኃይል፤ የባሕር ኃይል፤ የፖለስ ሠራዊት አባላት በሕይወት ላላችሁትም በመስዋዕትነታችሁ ታላቅ የተከበረች ሀገር ላስረከቡንም ጀግኖች፤ ኢትዮጵያን በደማችሁ አጽንታችሁ ላስረከባችሁን ውድ ጀግኖች በዚህ የምስጋና ቀን ለጀግኖቻችን ታላቅ ምስጋና እናቀር ባለን!!
ከመርደቂዮስ
አዲስ ዘመን ጳጉሜን 4/2012
ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ አዲስ አመትን አስመልክተው ካስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ከተናገሯቸው የተወሰዱ፤
- ምንም ያልተነካ አንድ ዓመት ሙሉ ከፊታችን አለን፤ብልህ ይመጥቅበታል ሞኝ ይወድቅበታል እኛ ግን ከብልሆዎች ወገን ልንሆን ይገባል፤
- ባገኘናቸው ድሎች ረክተን አንቀርም ባሳለፍናቸው ድሎች ታስረን አንቆምም ወደ ልዕልና እንመጥቃለን፤
“መምጠቅ ወደ ከፍታ መዝለቅ ነው፤ ልክ እንደ መንኩራኩር፣ ልዕልና ከከፍታ ይለያል ክብር አለው፤ በቀላሉ ከሚደረስበት መዳረሻ ወደላይ እጅግ መላቅን ይፈልጋል፤
- እንመጥቃለን ገና ወደ ልዕልና ስንል መታፈርና መከበር ወዳለው ከፍታ እንደ ምድር ስበት የሚስቡን ችግሮቻችንን አልፈን ለዚህ በተዘጋጁ እና በቆረጡ መጣቂዎች እና ባዘጋጀነው የ10 ዓመት ፍኖተ ብልፅግና መንኩራኩርነት ህብረ ብሄራዊነት በተሰኘ ማምጠቂያ ስፍራ ብልፅግና ወደተባለ ደርሰንበት ወደ ማናውቀው የመንፈስ፣ የቁስ እና የኢኮኖሚ ከፍታ እንመጥቃለን ማለታችን ነው”
- 2012 በደስታና ሀዘን፣ በክብርና ውርደት፣ በኩራትና ሀፍረት የተሞላ ዓመት ነበር፤
-የኢትዮጵያ ፈታኞች አሉን ያሉትን ድንጋዮች ሁሉ ወርውረዋል፤ ሆኖም የኢትዮጵያ ጀግኖች የቻሉትን ሁሉ ለሀገራቸው ሰውተዋል፤ ትርፍ ነብስ ያላቸው እስከሚመስል በጀግኖቿ ብርታት መከራውን ሁሉ አልፋ ኢትዮጵያችን ዛሬም አለች፤
- ኢትዮጵያ ጨለማ የማይበግራት የብርሃን ሀገር፣ የብርቱ ህዝብ የፅኑ ዜጋ ሀገር ናት፤
-ወደ ብልፅግና ማማ ሊያወጣ ራእይ የሰነቀው፣ ከፋፋይ እና ኋላ ቀር አስተሳሰቦችን በፍቅር እና በመተባበር የተካው፣ ሀገሪቱን ወደሚገባት ከፍታ ሊያወጣት የሰነቀው ብልጽግና ጥይት እንኳን ኮሽ ሳይል የነበረውን አሮጌ አስተሳሰብ አስወግዶ የተወለደው በዚህ ዓመት ነበር፤
- ከጨለማ በኋላ ብርሃን፣ ከፈተና በኋላ ተስፋ፣ ከመለያየት በኋላ መገናኘት፣ ከውድቀት በኋላ መነሳት አለ፤
- ከዘመን ወደ ዘመን የምናደርገው ሽግግር ትርጉም እንዲኖረው ካለፈው ዘመን ጋር አሮጌና ጎታች አስተሳሰባችንን ተሰናብተን አዲስ እና ተራማጅ አስተሳሰብን ልንላበስ ይገባል፤
- የፖለቲካ አሰራራችንን እና ባህላችንን በቅንነት ለማሻሻል፣ በመካከላችን የፈጠርነውን የልዩነት አጥር ለማፍረስ፣ የመለያየትን ገደል ለመሻገር ምን ያህል ተዘጋጅተናል፤
- መጪው ዓመት ስላለፈው የምንቆዝምበት፣ ስላለፈው ቂም ቋጥረን በቀልን የምናስብበት ሳይሆን በይቅርታ እና በእርቅ ሰላምን አውርደን በመተሳሰብና በመደማመጥ ልዩነታችንን አጥብበን ህዝባችንን እና ሀገራችንን በማስቀደም ወደ ልዕልና የምንመጥቅበት እንዲሆን ሁላችሁንም እጋብዛለሁ፤
----
ፍርድ ቤቶች በመስከረም ወር በከፊል ዝግ ሆነው ይቆያሉ ተባለ
***********
(ኢ.ፕ.ድ)

የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በመስከረም ወር 2013 ዓ.ም በከፊል ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አስታወቀ፡፡

ይህም ፍርድ ቤቶች የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል ከመጋቢት 10 - እስከ ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም በከፊል ዝግ ሆነው ከቆዩበት ሁኔታ ለመውጣትና ተቋርጠው የነበሩት አገልግሎቶችን ደረጃ በደረጃ ለማስጀመር ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም ባወጣው መመሪያ መሰረት ዳኞች በመስከረም ወር እረፍት አንዲያደርጉ በመወሰኑ ነው ተብሏል፡፡

ዳኞች ዓመታዊ እረፍታቸውን በነሃሴ እና በመስከረም ወር የሚወስዱ በመሆኑ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች አስቸኳይነት ያላቸውን ጉዳዮች ብቻ በተረኛ ችሎቶች በማስተናገድ በከፊል ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ ማድረግ የተለመደ አሰራር መሆኑን ያስታወሰው ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በዚህ ዓመት ዳኞች አጭር የእረፍት ጊዜ እንደሚኖራቸው ገልጿል፡፡

ከፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ያገኘነው መረጃ እንዳመለከተው ፍርድ ቤቶቹ በከፊል ዝግ ሆነው በሚቆዩባቸው የመስከረም ወር 20 የስራ ቀናት አስቸኳይና ጊዜ የማይሰጡ ከዜጎች መሰረታዊ መብቶች እንዲሁም ከአገር ሰላምና ፀጥታ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ጉዳዮች እንደሚመለከቱ ተገልጿል፡፡

ለአብነትም እንደ የጊዜ ቀጠሮ፣ የዋስትናና የዕግድ ጥያቄዎች፣ የመያዣና የብርበራ ትዕዛዞች፣ በተፋጠነ ስነ-ስርዓት የሚታዩ የእጅ ከፍንጅ ወንጀሎች እንዲሁም ከቤተሰብና ከሕፃናት ቀለብና አስተዳደግ ጋር የተያያዙ አጣዳፊ መሰረታዊ ጉዳዮች በተረኛ ችሎቶች የሚስተናገዱ መሆኑ ተነግሯል፡፡

የአዲሱ ዓመት የመጀመሪያው ወር ለዳኞች የእረፍት ጊዜያቸው አንዲሆን የተወሰነ ቢሆንም በፍርድ ቤቶች የተለመደ አሰራር አብዛኛዎቹ ዳኞች በፈቃዳቸው ውዝፍ መዛግብትን በማጥራት ስራ ላይ ይቆያሉ።