Ethio Fm 107.8
19.5K subscribers
6.18K photos
16 videos
4 files
2.27K links
በፍቅር ላይ የተመሰረተ ኢትዮጵያዊነት እንዳይላላ ከልቡ የሚተጋ፣ መከባበርና መተሳሰብን የሚያስቀድም ኤፍ ኤም ሬዲዮ ነው!!!
Download Telegram
በከተማችን አዲስ አበባ 51 ህገ-ወጥ እርድ ተይዞ በግብረ-ሃይሉ እርምጃ እንደተወሰደባቸው ተገለጸ፡፡

በአራት ክፍለ ከተሞች በተለዩ ቦታዎች በተደረገ አሰሳ 51 ህገ-ወጥ እርድ ሲያከናኑ መያዛቸውን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታዉቋል፡፡

በከተማ ደረጃ ገበያን ለማረጋጋት ከሳምንታት በፊት የተቋቋመው ግብረ-ሀይል በአራት ክፍለ ከተሞች ማለትም ቦሌ፤ ንፍስ ስልክ ላፍቶ፤ ኮልፌ ቀራንዮ ና ለሚ ኩራ ክፍለ ከተሞች ውስጥ ህገ-ወጥ እርድ የሚከናወንባቸው ቦታዎችን ለይቶ ባደረገው ክትትል መሰረት በዛሬው እለት 51 በህገወጥ መንገድ እርድ ሲያከናን እጅ ከፍንጅ በመያዝ እርምጃ መውሰዱን ቢሮው አስታውቋል፡፡

በተጨማሪም በእነዚህ አካባቢዎች 229 በግና ፍየሉች በህገ-ወጥ መንገድ ሊታረዱ ሲሉ መያዛቸውን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የሆኑት አቶ ዳንኤል ሚዬሶ ለኢትዮ ኤፍ ኤም አስታውቀዋል፡፡

በረድኤት ገበየሁ

ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
በህገ ወጥ መንገድ የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው የኮቪድ -19 ህክምና ማዕከል በመክፈት አገልግሎት እየሰጠ የነበረ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገለፀ።

በአዲስ አበባ ከተማ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 2 ጃፓን ኤምባሲ አካባቢ የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው ክሊኒክ በመክፈት የኮሮና ቫይረስ ህክምና ለተለያዩ ሰዎች ሲሰጥ ነው፡፡

የአየር መንገድ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ከቦሌ ክፍለ ከተማ የምግብ እና መድኃኒት ቁጥጥር ባለሥልጣን ባለሙያዎች ጋር በሰሩት ጥናት ፍቃድ ሳይኖረው ክሊኒክ በመክፈት የኮሮና ቫይረስ ህክምና አገልግሎት ሲሰጥ የነበረውን ግለሰብ በቁጥጥር ስር ውሎ ምርመራ እየተደረገበት እንደሆነ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገልጿል።

በክፍለ ከተማው የወረዳ 2 የምግብ እና መድሀኒት ቁጥጥር ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ጦና እንደተናገሩት ግለሰቡ ምንም አይነት የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው በከፈተው የህክምና ማዕከል የውጪ ሃገር ዜግነት ያላቸው ሰዎች ጭምር ህክምና ፈልገው መምጣታቸውን ገልፀዋል፡፡

በወቅቱ በርካታ መድሀኒቶች የተገኙ ሲሆን ለምን አይነት ህመም የሚያገለግሉ መድሃኒቶች እንደሆኑም በማጣራት ላይ እንደሚገኙ የአዲስ አበባ ፖሊስ ገልጿል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን
ጳጉሜ 05 ቀን 2013 ዓ.ም
እንቁጣጣሽ ሎተሪ ጷጉሜን 5 ቀን 2013 ዓ.ም በብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ዕድል አዳራሽ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ላይ በህዝብ ፊት ወጥቷል፡፡

በዚህም መሰረት የወጡት የአሸናፊ ዕጣ ቁጥሮች እንደሚከተሉት ሆነዋል፡፡

1ኛ. 20,000,000 ብር የሚያስገኘው የ1ኛ ዕጣ ቁጥር 0580856

2ኛ. 10,000,000 ብር የሚያስገኘው የ2ኛ ዕጣ ቁጥር 0470508

3ኛ. 5,000,000 ብር የሚያስገኘው የ3ኛ ዕጣ ቁጥር 1973063

4ኛ. 3,000,000 ብር የሚያስገኘው የ4ኛ ዕጣ ቁጥር 0612715

5ኛ. 1,500,000 ብር የሚያስገኘው የ5ኛ ዕጣ ቁጥር 0816001

6ኛ. 750,000 ብር የሚያስገኘው የ6ኛ ዕጣ ቁጥር 1963913

7ኛ. 300,000 ብር የሚያስገኘው የ7ኛ ዕጣ ቁጥር 0716025

8ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 20,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 37510

9ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 10,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 79593

10ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 5,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 27663

11ኛ. 200 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 2,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 8326

12ኛ. 200 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 1,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 2843

13ኛ. 2,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 500 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 022

14ኛ. 20,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 300 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 42

15ኛ. 200,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 100 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር (የማስተዛዘኛ ዕጣ) ደግሞ 2 ቁጥር በመሆን ወጥቷል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የ2014 ዓ.ም አዲስ ዓመትን ከሠራዊቱ ጋር ለማክበር ማይጠብሪ ግንባር ተገኝተዋል።

በማይጠብሪ ግንባር ከሠራዊቱ ጋር በዓልን ለማክበር የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ፣ ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ሌትናል ጄኔራል አበባው ታደሰ፣ የመከላከያ ኅብረት ዘመቻ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሜጄር ጄኔራል ዘውዱ በላይ፣ የምእራብ እዝ እና የማይጠብሪ ግንባር አዛዥ ሜጄር ጄኔራል መሠለ መሠረት ጨምሮ ከፍተኛ የጦር መኮንኖች ተገኝተዋል።

የሠራዊት አባላት ተልዕኳቸን በላቀ ብቃት በመወጣት በአዲሱ ዓመት በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እናሰፍናለን ብለዋል። ሕዝባችን ያሳየንን ከፍተኛ ድጋፍ የሞራል ስንቅ አድርገን በአዲሱ ዓመት ለሕዝባችን ታላላቅ የድል ብሥራቶችን ለማሰማት እንዘጋጅም ማለታቸውን አሚኮ ዘግቧል።
ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
ከእስራኤል እስር ቤት አምልጠው ከነበሩ ስድስት እስረኞች መካከል አራቱ ተያዙ፡፡

የእስራኤል ፖሊስ ከሳምንት በፊት ከእስርቤት አምልጠው ከነበሩት ስድስት ፍልስጤማውያን እስረኞች መካከል አራቱን መያዛቸውን አስታውቀዋል፡፡

በከፍተኛ ሁኔታ ጥበቃ ከሚደረግለት የእስራኤል እስር ቤት ካመለጡት ስድስት ፍልስጤማውያን መካከል አራቱን አስሳ እንደያዘች እስራኤል አስታወቀች።

እስራኤል መልሳ ከያዘቻቸው ፍልስጤማውያን መካከል ሁለቱ የተገኙት የመኪና ማቆሚያ አካባቢ ሲሆን ሌሎች ሁለቱ ደግሞ ናዝሬት ከተማ አካባቢ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ተገልጿል።

እስረኞቹ በሰሜን እስራኤል ከሚገኘው ጊልቦዋ እስር ቤት ያመለጡት በሹካ መሬት ሰርስረው እንደነበረ ነው በወቅቱ የተገለጸው፡፡

ከእስረኞች መካከል ዋነኛ የእስራኤል ጠላት ተደርጎ የሚወሰደው የአል አቃሳ ቡድን መሪ እንደሆነ የሚነገርለት ዘካሪያ ዙቤይዲ ነው፡፡

እነዚህ እስረኞች በእስራኤል ለተፈጸመው ጥቃት ዋነኛ አቀነባባሪዎች ናቸው በሚል የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶባቸው የነበሩ ናቸው፡፡

የእስራኤል ፖሊሶች የተቀሩትን ሁለቱ እስረኞችን አድነው ለመያዝ በአየር ላይ የታገዘ አሰሳ እያካሄዱ እንደሆነ አልጀዚራ አስነብቧል፡፡

ሔኖክ ወ/ገብርኤል
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
በመዲናዋ በአዲስ ዓመት ዋዜማና በበአሉ ዕለት በትራፊክ ግጭት የሶስት ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ::


በዋዜማው ዕለት በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 ልዩ ቦታው ብስራት ትምህርት ቤት አካባቢ በተከሰተ የትራፊክ ግጭት በግምት የ35 ዓመት ወጣት ህይወቱን ሊያጣ ችሏል፡፡

እንዲሁም ልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ባጋጠመ የትራፊክ ግጭት በግምት የ60 ዓመት እናት ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡

በበዓሉ እለት ከቀኑ 11፡00 አካባቢ በየካ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ወረዳ 7 አካባቢ በተከሰተ የባቡር አደጋም የአንድ የ30 ዓመት ወጣት ህይወት ሊያልፍ ችሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በበአሉ ዋዜማ እና በበአሉ ቀን ምንም አይነት የእሳት አደጋ እንዳልተከሰተ ነው የተገለጸው፡፡

የእሳት እና የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የህዝብ ግኑኝነት ሀላፊ አቶ ጉልላት ጌታነህ ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት ጀሞ አካባቢ ከደረሰው አነስተኛ የጎርፍ አደጋ ውጪ ምንም ድንገተኛ አደጋ አለመድረሱን ተናግረዋል፡፡

በሄኖክ ወ/ገብርኤል
መስከረም 03 ቀን 2013 ዓ.ም
ከሰሜን ወሎ ዞን የተፈናቀሉ ዜጎች የደሴ ከተማ ከሚያስተናግደዉ አቅም በላይ በመሆኑ ወደ ኮምቦልቻ እየተላኩ ነዉ ተባለ፡፡


ከሰሜን ወሎ ዞን በርካታ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች በደሴ እና ኮምቦልቻ መጠለላቸው ይታወቃል።

በአሁኑ ሰዓትም በደሴ ከተማ በመንግስትና በግል ትምህርት ቤቶች ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ ዜጎች ቁጥር 275ሺህ መድረሱን የደሴ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሰኢድ የሱፍ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል።

ምክትል ከንቲባው እንዳሉት የተፈናቃዮች ቁጥር እጅግ ከፍተኛ በመሆኑና ደሴ ከተማ ከዚህ በኋላ ተፈናቃዮችን መቀበል ስለማትችል ወደ ኮምቦልቻ እየላክናቸው ነው ብለዉናል።

ከተፈናቃይ ዜጎች ቁጥራቸው እየጨመረ መምጣት አንጻር ደሴ ከተማ የቦታ እጥረት አጋጥሟልም ተብሏል።

ከሰሜን ወሎ የተፈናቀሉት 275ሺህ ዜጎች በመንግስት የተመዘገቡት ብቻ ናቸው ያሉት አቶ ሰኢድ፣ከቤተሰብ ጋር የተጠለሉት ቁጥር በዉል እንደማይታወቅና ቁጥሩ ከዚህም ከፍ ሊል እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

ከተፈናቃይ ቁጥር መጨመር ጋር ተያይዞም የእርዳታ ተደራሽነት ችግር መኖሩን የተናገሩት ምክትል ከንቲባዉ፣እስካሁን ዩኒቨርሲቲዎች ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች ግን ወደ አካባቢው እንዳልሄዱም አረጋግጠዉልናል።


በመቅደላዊት ደረጄ
መስከረም 04 ቀን 2014 ዓ.ም
ኢትዮጵያና ኬንያ የሞያሌን የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎትን ወደ ሥራ ለማስገባት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ

የሁለቱን አገራት የንግድ ትስስር ያጠናክራል የተባለውን የመግባቢያ ስምምነት የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቀበታና፣ የኬንያ የአገር ግዛት ደህንነት ኃላፊና የኬንያ ልዑክ መሪ ዊልሰን ጋቾከኪ በዛሬው እለት ተፈራርመዋል።

ስምምነቱ የተካሄደው በዛሬው እለት በአዲስ አበባ ከተማ ሲሆን ከሁለቱም አገራት የተወጣጡ የግል ዘርፍ ተወካዮች ተገኝተው ውይይት በማድረግ ላይ ናቸው።

በፊርማ ስነ-ስርዓቱ ወቅት የጉምሩክ ኮሚሾነሩ አቶ ደበሌ ቀበታ ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያ እና ኬንያ ረጅም ዕድሜ ያስቆጠረ ግንኙነት እንዳላቸው ገልፀው፣ የሁለቱን አገራት የንግድ ልውውጥ ለማጠናከር የሞያሌ አንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል።

አገራቱን ድንበር ቢለያያቸውም ንግድ ያስተሳስራቸዋል ያሉት ኮሚሽነሩ፣የሞያሌ የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት የንግድ ልውውጡን ከማጠንከሩ ባለፈ ለግሉም ዘርፍ ይበልጥ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል።

ስምምነቱ ፣የንግድ፣ የትራንስፖርት፣ እና የዜጎችን እንቅስቃሴ የሚያቀላጥፍ በመሆኑ ለኢትዮጵያና ለኬንያ የንግድ ልውውጥ ወሳኝ ምዕራፍ እንደሆነ ዊልሰን ጋቾከኪ ተናግረዋል፡፡

በተለይም የላፕሴት ኮሪደር መገንባት የሁለቱን አገራት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እንደሚያሳድገውም ነው ኃላፊው ያነሱት።

ባለፈው አመት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድና የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የሃዋሳ ሞያሌ የጋራ ፍተሻ ጣቢያን መመረቃቸው የሚታወስ ነው።

በአባቱ መረቀ
መስከረም 05 ቀን 2014 ዓ.ም
በትግራይ ፤ በኤርትራ ስደተኞች ላይ የጦር ወንጀል እየተፈፀመ እንደሆነ የአለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዎች ገለፀ

የኤርትራ ስደተኞች ትግራይ ውስጥ ባለው ሀይል ታፍነው ይታሰራሉ፣ ይደፈራሉ፣ ይገደላሉ ብሏል ሂዩማን ራይትስ ዎች፡፡

እንደ አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት በኤርትራ ስደተኞች ላይ የሚፈፀሙት እነዚህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በህወሀት ብቻ ሳይሆን ከኢትዮጵያ ፌደራል ሀይል ጎን ቆመው በሚዋጉት የኤርትራ ሀይሎች ጭምር እንደሆነም አንስቷል፡

በሺዎች የሚቀጠሩ ኤርትራውያን ስደተኞች በትግራይ ካምፕ ተጠልለው ይገኛሉ፡፡

የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ የአፍረካ ቀንድ ዳይሬክተር እንደተናገሩት ፤ በትግራይ ዘግናኝ ግድያዎች፣ አስገድዶ መድፈሮች እና ዘረፋዎች በኤርትራ ስደተኞች ላይ እየተፈፀሙ ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ ግልፅ የጦርነት ወንጀሎች ናቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ኤርትራ ለዚህ ክስ እስካሁን ምንም አላለችም፤ ከዚህ ቀደም ግን ክሱን ውድቅ አድርጋ ነበር፡፡

ቢቢሲ ሮይተርስ የዜና ወኪልን ጠቅሶ እንደዘገበው ከፍተኛ ቁጥር ያለው የኤርትራ ጦር በትግራይ ይገኛል፡፡

ሔኖክ አስራት
መስከረም 06 ቀን 2014 ዓ.ም
በአባይ ግድብ ቀውስ ላይ ግብፅ ከወታደራዊ ግጭት መራቅ እንደምትፈልግ ገለጸች

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሾክሪ ከብሉምበርግ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንዳሉት ግብፅ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ቀውስ ላይ ለመነጋገር ቁርጠኛ መሆኗን እና ከማንኛውም ወታደራዊ ግጭት መራቅ እንደምትፈልግ ተናግረዋል።

የግብፅ የውሃ ሀብቶች እና መስኖ ሚኒስትር መሐመድ አብደል አቲ በበኩላቸው ግድቡን በተመለከተ ዲፕሎማሲያዊ እርምጃዎች እንደ ቀጠሉ ናቸው ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ፍሬያማ እስኪሆኑ ድረስ ተጨማሪ ዝርዝር መረጃ አልሰጥም ’’ በማለት ለአልጀዚራ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት አባል የሆኑት ራካ ሐሰን ለአል ሞኒተር ሲናገሩ “የወታደራዊ አማራጭ ለግብፅ የማይታሰብ እንደሆነ ገልፀው ከዚህ ይልቅ ፓለቲካዊ ጫና መፍጠር አስፈላጊ እንደሆነ’’ ተናግረዋ፡፡

ከዚህ ጎን ለጎንም ግድቡን ከሚሰሩት ጀርመን እና ኢጣሊያን ኩባንያዎች ጋር መነጋገርን ጨምሮ ኢትዩጲያን ከሚደግፉት የአፍሪካ አገራት ጋርም መቀራረብ ያስፈልጋል ነው ያሉት፡፡

በየአፍሪካ ህብረት ድርድሮች ይከሽፉ እንደሆነ የተጠየቁት ሀሰን “መደምደሚያውን መናገር አይቻልም ምክንያቱም ዲፕሎማሲ አይታወቅም” ብለዋል።

በሚያዚያ 6 ቀን በግብፅ ፣ በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል በኪንሻሳ ከተደረገው የመጨረሻ ዙር ድርድር በኃላ ለአምስት ወራት ድርድር ሳይደረግ መቆየቱን ተከትሎ ግብፅ የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ጉዳዩን እንዲመለከት ጠይቃለች።

ሐምሌ 8 የተባበሩት መንግስታት በአፍሪካ ኅብረት ሥር ድርድር እንዲጀመር ማሳሰቡ ይታወሳል።

በያይኔአበባ ሻምበል
መስከረም 07 ቀን 2014 ዓ.ም
ቻይና የአሜሪካ-እንግሊዝ-አውስትራሊያ ስምምነትን ኃላፊነት የጎደለው በማለት ኮንናለች

ቻይና በአሜሪካ ፣ በእንግሊዝ እና በአውስትራሊያ መካከል የተደረገውን ታሪካዊ የደህንነት ስምምነት “እጅግ ኃላፊነት የጎደለው” እና “ጠባብ አስተሳሰብ” በማለት ገልፃለች።

በስምምነቱ መሰረት አሜሪካ እና እንግሊዝ ለመጀመሪያ ጊዜ በኑክሌር ኃይል የሚሠሩ የባህር ሰርጓጅ መርከቦችን ለመሥራት የሚያስችሉ ቴክኖሎጂን ለአውስትራሊያ ይሰጣሉ።

ሶስቱ ሀገራት ያደረጉት ስምምነት በደቡብ ቻይና ባህር ውስጥ የቻይናን ተፅእኖ ለመከላከል ያለመ መሆኑ ተሰምቷል።

ቀጠናው ለዓመታት የሀይል ሚዛን ማሳያ ሆኖ የቆየ ሲሆን እዚያ ያለው ውጥረት አሁንም እንደቀጠለ ነው እንደ ቢቢሲ ዘገባ።

የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዣኦ ሊጂያን እንዳሉት ህብረቱ “የአካባቢያዊ ሰላምን በእጅጉ ይጎዳል ... እና የመሳሪያ ውድድሩን ያጠናክራል” ብለዋል።

‹‹ ጊዜው ያለፈበት የቀዝቃዛው ጦርነት ... አስተሳሰብ ›› ብለው የጠሩትን ስምምነት ተችተው ሦስቱ አገሮች “የራሳቸውን ጥቅም እየጎዱ ነው” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

የቻይና መንግስታዊ ሚዲያዎች ስምምነቱን የሚያወግዙ ተመሳሳይ ርዕሶችን የያዙ ሲሆን በግሎባል ታይምስ ጋዜጣ ላይ አውስትራሊያ አሁን “እራሷን የቻይና ጠላት አድርጋለች” ብሏል።

በያይኔአበባ ሻምበል
መስከረም 07 ቀን 2014 ዓ.ም
ኢትዮጵያ ውስጥ እየተፈጸመ ነው ባሉት የሰብአዊ ቀውስ ምክንያት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ተጨማሪ ማዕቀብ እንዲጣል ትእዛዝ ሰጡ።

የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ከትግራይ ክልል ቀውስ ጋር በተገናኘ ተጠያቂ ባደረጓቸው፣ የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግስት ፣የአማራ ክልል ባለስልጣናት ፣ የህወሓት አመራሮች እና የኤርትራ መንግስት አመራሮች ላይ ተጨማሪ ማዕቀብ እንዲጣል ትዕዛዝ ሰጥተዋል።

ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ዛሬ በፈረሙት የስራ አስፈጻሚ አካል ትዕዛዝ (executive order) የትግራይ ክልል ግጭት እንዲራዘም ፤ ለትግራይ ክልል ሰብዓዊ እርዳታ እንዳይቀርብ ያስተጓጎሉ እና የተክስ አቁም ስምምነት እንዳይደረስ እንቅፋት ሆነዋል ባሏቸው ላይ ተጨማሪ ማዕቀብ እንዲጣል ወስነዋል።

ማዕቀቡ እንዲጣል ያዘዙትም ከላይ ለተጠቀሱት ጉዳዮች ተጠያቂ ናቸው በተባሉ የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግስት እና የአማራ ክልል መስተዳደር ባለስልጣናት ላይ፤ እንዲሁም በህወሓትና በኤርትራ መንግስት አመራሮች ላይ እንደሆነ የአሜሪካ መንግስት ያወጣው መግለጫ ያመለክታል።

ተጠያቂ ናቸው የተባሉት የመንግስት ባለስልጣናት እና የህወሓት አመራሮች ማንነት ግን ይፋ አልተደረገም።
ይሁን እንጂ የአሜሪካ የመንግስት ግምጃ ቤት ከአገሪቱ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ጋር በመተባበር ተጠያቂ መሆን የሚገባቸውን እየለየ ማዕቀቡን ተግባራዊ የማድረግ ኃላፊነት ተሰጥቶታል።

ማዕቀቡ በተመረጡ ግለሰቦች ላይ ብቻ ተግባራዊ እንደሚደረግ እና የኢትዮጵያ ህዝብን በማይጎዳ መልኩ እንደሚተገበር የአገሪቱ መንግስት ያወጣው መግለጫን ጠቅሶ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን
መስከረም 07 ቀን 2014 ዓ.ም
ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዐብይ አህመድ ለፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ደብዳቤ ጽፈዋል፡፡

በደብዳቤያቸዉም ታዳጊ ሃገራት ከአሜሪካ የሚጠብቁት ከግለሰቦች ፍላጎት የጸዳና በዉስጥ ጉዳይ ጣልቃ የማይገባ እንዲሆን ነዉ ብለዋል፡፡

ጠቅላይ ሚንስትሩ በደብዳቤያቸዉ በህወሃት ምክንያት ህጻናትና እናቶችን ጭምሮ በርካታ ንፁሃን ዜጎች በስቃይ ላይ መሆናቸዉን አንስተዋል፡፡
ደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪዎች ከአብይ ግዛት መውጣታቸውን እንደማትቀበል አስታወቀች።


የደቡብ ሱዳን መንግስት በአብይ ግዛት በሰላም ማስከበር ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ የኢትዮጵያ ወታደሮች እንዲወጡ ሱዳን ያቀረበችውን ጥያቄ ውድቅ አደረጓል።

የተባበሩት መንግስታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ረዳት ሚኒስትር ዣን ፒዬር ላክሮይክስ ባለፈው ሳምንት ደቡብ ሱዳንን መጎብኘታቸውን ተከትሎ መግለጫ ሰተዋል።

የደቡብ ሱዳን የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስቴር በተባበሩት መንግስታት የሰላም አስከባሪ ልዑክ እና በከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እንዲሁም በፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ማያርዲት ፣ በአብይ የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪዎች ሁኔታ ላይ ያተኮረ ውይይት አድርገዋል እንደ ሱዳን ፖስት ዘገባ።

የደቡብ ሱዳን መንግስት መግለጫው በተጨማሪ በአወዛጋቢው ክልል ውስጥ የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ኃይልን ለመተካት ሱዳን ያቀረበችውን ጥሪ ውድቅ ማድረጎን አስታውቋል።

“በዚህ ሁኔታ የደቡብ ሱዳን ሪፐብሊክ ይህ ኃይሉ የተሰጠውን ተልዕኮ በሙያ እና በገለልተኝነት እያከናወነ ባለበት ወቅት የኢትዮጵያ ጦር እንዲወጣ በሚደረገው ጥሪ እንደማይስማማ ለመግለፅ እንወዳለን” ብሏል መግለጫው።

የደቡብ ሱዳን መንግሥት የአብይን ግዛት ለመጨረሻ ጊዜ እልባት እንዲያገኝ ፓለቲካዊ ሂደት እንዲጀመር ጥሪውን በድጋሚ ያቀርባል ሲል አክሏል።

በያይኔአበባ ሻምበል
መስከረም 08 ቀን 2014 ዓ.ም
የሞሮኮ ትልቁ ኩባንያ፣ ኦሴፒ በድሬ ዳዋ የማዳበሪያ ፋብሪካ ሊገነባ ነው

በመጀመሪያው ምዕራፍ 2.4 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር እንዲሁም በድምሩ በሁለተኛው ምዕራፍ እስከ 3.7 ቢሊዮን ዶላር ድረስ ኢንቨስት ይደረጋል።

በድሬዳዋ የአፈር ማዳበሪያ ማምረቻ ፕሮጀክት
በአመት 3.8 ሚሊዮን ቶን ማዳበሪያ ማምረት ይችላል ተብሏል።


በኢትዮጵያ የፋይናንስ ሚንስትር አቶ አህመድ ሺዴ የተመራ ልዑክ በሞሮኮ ጉብኝት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

ኦሲፒ ከተባለው የሞሮኮ መንግስት ኩባንያ ጋር የተፈረመው ስምምነት በድሬዳዋ የማዳበሪያ ፕሮጀክት ለመተግበር የሚያስችል ስለመሆኑ ተገልጿል፡፡

በኢትዮጵያ የማዳበሪያ ፍላጎት እያደገ በመሄዱ በ2022 ከውጭ የሚገባው ማዳበሪያ 1 ቢሊዮን ዶላር ወጭ እንዳለው ሲገመት ይህ መጠን በ2030 2 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያድግ ይጠበቃል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 08 ቀን 2014 ዓ.ም
የጉጂ አባ ገዳዎች 'ሸኔ' የኦሮሞ ጠላት ነው ሲሉ አወጁ

የጉጂ አባ ገዳዎች በአንዳንድ የኦሮሚያ አካባቢዎች እንደሚንቀሳቀስ የሚነገረው ታጣቂው ቡድን 'ሸኔ' የኦሮሞ ጠላት ነው ሲሉ አወጁ።

አባገዳዎቹ መንግሥት ሸኔ የሚለው እና እራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር እያለ የሚጠራው ቡድን 'የኦሮሞ ጠላት ነው' ሲሉ የፈረጁት በቡድኑ በርካታ ንጹሃን ዜጎች በመገደላቸው ነው ብለዋል።

ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ የቦረና አባ ገዳ የሆኑት ኩራ ጃርሶ ታጣቂ ቡድኑን በተመሳሳይ 'የኦሮሞ ጠላት ነው' በማለት አውጀው ነበር።

የአገሪቱ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ባለፈው ዓመት ይህንን ታጣቂ ቡድን 'ሸኔ'ን እና ህወሓትን አሸባሪ ድርጅቶች ሲል መፈረጁ ይታወሳል።

በቅርቡም እራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር የሚለውና መንግሥት ሸኔ የሚለው ታጣቂ ቡድን መንግሥትን ለመጣል ከህወሓት ጋር በትብብር እንደሚንቀሳቀስ ይፋ አድርጓል።

ባህላዊው መሪዎቹ፣ ታጣቂው ቡድን ላይ ውግዘት ያስተላለፉት "ኦሮሞ ሆኖ ኦሮሞን የሚገድል ጠላት ነው" በማለት እንደሆነ የጉጂ አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ባለፉት ሦስት ዓመታት በጉጂ ሕይወት እጅጉን ፈታኝ ሆኗል የሚሉት አባ ገዳ ጂሎ፤ "የኦሮሞ ነጻነት ጦር ለኦሮሞ ሕዝብ ነው የምታገለው ይላል። ለኦሮሞ የሚታገል ከሆነ ኦሮሞን መግደል የለበትም" ብለዋል።

በሁለቱ የጉጂ ዞኖች ማለትም በጉጂ ዞን እና በምዕራብ ጉጂ ዞን ባለፉት ሦስት ዓመታት ከ2000 በላይ ንጹሃን ሰዎች መገደላቸውን አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ ይናገራሉ።

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 08 ቀን 2014 ዓ.ም