Ethio Fm 107.8
19.4K subscribers
5.74K photos
16 videos
4 files
2.26K links
በፍቅር ላይ የተመሰረተ ኢትዮጵያዊነት እንዳይላላ ከልቡ የሚተጋ፣ መከባበርና መተሳሰብን የሚያስቀድም ኤፍ ኤም ሬዲዮ ነው!!!
Download Telegram
መጭውን በዓላት ምክንያት በማድረግ 108 አማራጭ የገበያ ቦታዎች ማዘጋጀቱን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ገለጸ፡፡

ቢሮዉ ቀጣዩን የዘመን መለወጫ በዓል ምክንያት በማድረግ እየሰራ ካለው ስራ አንዱ ህብረተሰቡ አማራጭ እና ተደራሽ የገበያ ስፍራ እንዲያገኝና የሚፈልጋቸውን ምርቶች በቀጥታ ከአምራች ገበሬው ማግኘት እንዲችልና እየተስተዋለ የሚገኘውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት እየሰራ መሆኑን ቢሮዉ ለጣቢያችን በላከዉ መግለጫ አሳዉቋል፡፡


በአዲስ አበባ ከተማ 108 የመገበያያ ቦታዎችን እና ከ250 ሺህ ኩንታል በላይ ተጨማሪ የግብርና ምርት የተዘጋጀ መሆኑን ቦሮዉ ጠቁሟል፡፡

በሁሉም ክፍለ ከተሞች ስራ የጀመሩት መሸጫዎቹ በከተማዋ የሚስተዋለዉን የኑሮ ዉድነት በማረጋጋት በተለይም የግብርና ውጤት የሆኑ የሰብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን እንዲሁም ለበዓል አስፈላጊ የሆኑ እንደ እንቁላል እና አይብ ያሉ የእንስሳት ተዋጽኦ አቅርቦትን ይበልጥ ለማሻሻል ከፍተኛ አስተዋፆ እንደሚኖራቸውም ተገልጿል።

ከነዚህም ውስጥ 56 የቁም እንሰሳት የገበያ ስፍራዎች ሲሆኑ 52ቱ የአትክልትና ፍራፍሬ መሸጫዎች ናቸው ተብሏል፡፡

አዳዲስ የግብይት ቦታዎቹ በሁሉም ክፍለ ከተሞች አገልሎት መስጠት የጀመሩ ሲሆን መሸጫ ስፍራዎቹ ከአርሶ አደሩ በቀጥታ ተቀብለዉ ለሸማቹ ህብረተሰብ ምርት በቀጥታ ከአርሶ አደሩ ከማቅረባቸው በተጨማሪ ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ እንዲችሉ የተዘጋጁ አማራጭ የገበያ ስፍራዎች መሆናቸዉ ተነግሯል፡፡

በረድኤት ገበየሁ
ነሃሴ 28 ቀን 2013 ዓ.ም
ነገ ጳጉሜ 1 ቀን 2013 ዓ.ም "የኢትዮጵያዊነት ቀን" አስመልክቶ  በመስቀል አደባባይ በሚካሄደው ዝግጅት ምክንያት  ከጠዋቱ 11:30 ጀምሮ ፕሮግራሙ እስከሚጠናቀቅ ድረስ ለተሽከርካሪ ዝግ የሚሆኑ መንገዶች:-

- ከመገናኛ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ አሽከርካሪዎች ኡራኤል ቤ/ክ
- ከቦሌ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ ኦሎምፒያ
- ከሸራተን ሆቴል ወደ መስቀል አደባባይ ሀራምቤ ትራፊክ መብራት
- ከሜክሲኮ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ ለገሃር ትራፊክ መብራት ላይ
- ከአራት ኪሎ ወደ መስቀል አደባባይ  ብሄራዊ ቤተ መንግስት
- ከተክለሀይማኖት  ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ አሽከርካሪዎች  ብሔራዊ ቲያትር
- ከቸርቸል ጎዳና ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ አሽከርካሪዎች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዋና መስሪያ ቤት
- ከጎተራ  ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ ጥላሁን አደባባይ ዝግ የሚሆን ሲሆን
ለከባድ ተሽከርካሪ ከጎተራ ወደ መስቀልአደባባይ ለሚመጡ መንገዱ አጎና ሲኒማ ላይ የሚዘጋ ይሆናል።

ከዚህም በተጨማሪ በነዚህ መንገዶች ላይ ተሽከርካሪን ለአጭርም ሆነ ለረጅም ሰዓት አቁሞ መሄድ ተከልክሏል።

ስለሆነም አሽከርካሪዎች አማራጭ መንገዶችን እንዲጠቀሙ የአዲስ አበባ ፖሊስ መልዕክት አስተላልፏል።
                                                 
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል ድረ ገጻችንን https://ethiofm107.com/ ይጎብኙ::
ነሐሴ 30 ቀን 2013 ዓ.ም
የሱዳን መንግስት ጦር መምዘዙን አቁሞ ከኢትጵያ ጋር በሰላማዊ መንገድ እንዲደራደር የአገሪቱ ምሁራን ጠየቁ፡፡


ከኢትዮ ኤፍ ኤም ጋር ቆይታ ያደረጉት ሱዳዉያን ምሁራን፣ ኢትዮጵያና ሱዳን በቀላሉ የሚለያዩ ባለመሆናቸዉ መንግስታቸዉ ወደ ሰላማዊ ድርድር እንዲመጣ ግፊት እንደሚያደርጉም አስታዉቀዋል፡፡

የኢትዮጵያ እና የሱዳን ዉጥረት መነሻዉ ምን ይሆን? የሱዳን ህዝብ ፍላጎትስ ምንድነዉ? ስንል ከሱዳናዉያን ምሁራን ጋር ቆይታ አድርገናል፡፡


ዶክተር ኦማር ላሚን አህመድ በሱዳን ዩንቨርሲቲ የታሪክ ተመራማሪ ናቸዉ፡፡

እርሳቸዉ ዘመናትን ስላስቆጠረዉ ስለ ኢትዮጵያና ሱዳን ቤተሰባዊ ግንኙነት አንስተዉ የድንበር ዉዝግቡ የሁለቱ አገራት ፍላጎት ሳይሆን የቅኝ ዘመን ርዝራዦች ፍላጎትና ሃሳብ ነዉ ይላሉ፡፡

ኢትዮጵያ እና ሱዳን የድንበር ዉዝግባቸዉን በአፈ ሙዝ ሳይሆን የሁለቱን አገራት ህዝብ በማቀራረብ የዲፕሎማሲ ስራን በመስራት ነዉ የሚሉት ሱዳናዊ ምሁር፤ ለዚህም የሁለቱ አገራት መሪዎች የህዝቡን ፍላጎት ማዳመጥ አለባቸዉ ነዉ ያሉት፡፡


ከድንበር ዉዝግቡ ባለፈ ሱዳን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ያልተገባ ጥያቄ እንደምተነሳ ይታወቃል፡፡

ለመሆኑ ግድቡ የሁለቱ አገራት መጨቃጨቂያ መሆን ነበረበት ስንል ዶክተር ኦማር ላሚንን የጠየቅን ሲሆን፤ ሁለቱም አገራት በቂ ዉሃ አላቸዉ፤ ግድቡ የልማት እንጅ የልዩነት አጀንዳ ሊሆን አይገባም ብለዋል፡፡

ሌላኛዉ የሱዳን ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩንቨርሲቲ ተመራማሪዉ ፕሮፌሰር አብዱ ኦስማን በበኩላቸዉ፣ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ እና ሱዳን ጦር እንዲማዘዙ እንቅልፋቸዉን አጥተዉ ትርፋቸዉን ለማጋበስ የሚጠባበቁ ሃይሎች ስለመኖራቸዉ አንስተዉ፤ በዚህም ሁለቱ አገራት የእነዚህ መጠቀሚ መሳሪያ እንዳይሆኑ ብልህ ሊሆኑ ይገባል ነዉ ያሉት፡፡


መንግስት ለመንግስት ከሚደረገዉ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በተጨማሪ፣ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ማጠናከር እንደሚገባ ያሳሰቡት ሱዳናዊ ፕሮፌሰር አብዶ ኦማር፣ ለዚህ ደግሞ የምሁራን ሚና ከፍተኛ መሆን አለበት ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ እና ሱዳን በቀላሉ የሚለያዩ አይደሉም የሚሉት እነዚህ የሱዳን ዩንቨርሲቲ ምሁራን፤ ይልቁንም ሁለቱ አገራት ጦር እንዲማዘዙ አሰፍስፈዉ የሚጠባበቁ ሃይሎችን ምኞት በጋራ ማምከን ይገባል ብለዋል፡፡


የህዳሴ ግድቡም ሆነ የድንበር ጥያቄዉ በሃይል የሚመለስ አይደለም ያሉት ምሁራኑ፣ የሱዳን ህዝብ ከኢዮትጵያ ወገኑ ጋር ወደ ግጭት መግባት አይፈልግም፤ ስለዚህ የሱዳን ባለስልጣናት በሌሎች ሃይሎች መገፋታቸዉን ትተዉ የህዝባቸዉን ስሜት እንዲያዳምጡ ግፊት እንደሚያደርጉም አስታዉቀዋል፡፡

በአባቱ መረቀ
ጳጉሜ 03 ቀን 2013 ዓ.ም
ግብጽ ከቱርክ ጋር ያላትን የሻከረ ግንኙነት ለማሻሻል ያልተቆጠበ ጥረት እያደረገች ነዉ፡፡

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በትናንትናዉ እለት እንዳስታወቁት ሀገራቸው ከቱርክ ጋር የነበራትን ግንኙነት ወደ ነበረበት ለመመለስ የምትፈልግ መሆኗን እና ከህዳሴ ግድቡ ጋር ተያይዞም ከኢትዮጵያ ጋር በትጥቅ ግጭት ውስጥ ለመግባት ፍላጎት እንደሌላት ተናግረዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሳሜህ ሽክሪ ከብሉምበርግ ቲቪ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ግብፅ “ከአንካራ ጋር መደበኛ ግንኙነቷን ወደ ቀድሞ ሁኔታው ለመመለስ” እና ፈጣን እርምጃዎችን ለማግኘት ጓጉታ የነበረ ቢሆንም ተጨማሪ ሥራ መሰራት አለበት ብለዋል።

በቱርክ ዋና ከተማ እየተካሄደ ባለው የሁለተኛ ዙር ውይይቶች “አሁንም ውጤቱን መገምገም አለብን” ብለዋል።
ግብፅ ያልተፈቱ ጉዳዮች እንዲፈቱ ለተጨማሪ እድገት በሩ ክፍት ይሆናል ብለዋል ሽክሪ።
ቱርክ ለሙስሊም ወንድማማቾች ህብርት ድጋፍ ታደረጋለች በሚል ቅራኒ ውስጥ ገብተው እንደነበር ይታወሳል፡፡


ይባስ ብሎም ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ሙርሲ በ 2013 በወታደራዊ ሀይል ከሥልጣን መውረድ ጋር ተያይዞም ግንኙነታቸው ተዳክሟል።

ቱርክ ትሪፖሊ ውስጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ያገኘውን የሊቢያ መንግሥት ስትደግፍ ፣ ግብፅ ደግሞ በምሥራቃዊው ኃያል ካሊፋ ሃፍታር የሚመራውን ትደግፋለች።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን በኅዳር ወር መመረጣቸውን ተከትሎ ሁለቱ አገራት በክልሉ ውስጥ ያለውን የሀይል ሚዛን ለመከፋፈል እየተገፋፉ ነው፡፡


የዓባይ ግድብን በተመለከተም ከኢትዮጵያ ጋር በተፈጠረው ውጥረት ላይ ግብፅ ለድርድር ቁርጠኛ መሆኗን እና ከማንኛውም ዓይነት ወታደራዊ ግጭት ለመራቅ ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል።
የግብፅ ባለሥልጣናት ቀደም ሲል ሁሉም አማራጮች ክፍት እንደሆኑ ተናግረው ነበር ሲል ሚዲል ኢስት ሞኒተር ዘግቧል።

እንዲሁም የግብፅ ፕሬዝዳንት አብዱልፈታህ ኤልሲሲ የውሃ ድርሻ ለሀገራቸው የብሔራዊ ደህንነት ጉዳይ መሆኑን እና ሊታለፍ የማይችል “ቀይ መስመር” ነው ሲሉ መደመጣቸውን አናዶሉ ዘግቧል።

በያይኔአበባ ሻምበል
ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
ሱዳን ከተሳሳተው መንገዷ እንድትመለስ አሁንም ኢትዮጵያ ትጠይቃለች ሲሉ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ አስታወቁ

ሱዳን በተጠናቀቀው አመት የኢትዮጵያን ድንበር አልፋ የተለያዩ ትንኮሳዎችን ማድረጓን ያስታወሱት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፣ አሁንም ሱዳን ከተሳሳተው መንገዷ እንድትመለስ ኢትዮጵያ ትጠይቃለች ብለዋል ።

የኢትዮጵያ መንግስት ከሱዳን ጋር ያለውን የድንበር ውዝግብ በትዕግስት መከታተሉንም አንስተዋል።

በተጠናቀቀው 2013 ዓ.ም ኢትዮጵያ ከገጠሟት ችግሮች መካከል የሱዳን ድንበር ውጥረት አንዱ መሆኑን ያስታወቁት ቃልአቀባዩ ፣ችግሩ ባይፈታም ኢትዮጵያ ግን ጉዳዩን በበሳል ዲፕሎማሲ እይታ ተከታተለዋለች ብለዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ሱዳን እየሄደችበት ያለው መንገድ የተሳሳተና የማይጠቅማት በመሆኑ ከድርጊቷ ብትቆጠብ መልካም እንደሆነ ተናግዋል፡፡

ከእንደዚህ አይነት ድርጊት በዘለለ የአፍካውያን ኩራት በሆነው አየር መንገዳችን ስም ለማጠልሸት የሚደረገውንም ድርጊት ኮንነዋል፡፡

በአባቱ መረቀ
ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
ቡሩንዲ ከኢትዮጵያ ግድብ ግንባታ ይልቅ ለግብፃውያን የመኖር መብት ቀዳሚ ነው አለች

ቡሩንዲ የግብፅን የመኖር መብት ከኢትዮጵያ የማልማት መብት ከማግኘት በፊት ሊቀድም ይገባል ብሎ እንደሚያምን የሀገሪቱ ከፍተኛ ዲፕሎማት አስታወቁ።

ኢትዮጵያ ለኢኮኖሚ ዕድገቷ እና ለኃይል አቅርቦት ወሳኝ ነው ብላ በምትከራከረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ነው አስተያየት የሰጡት።

ፕሮጀክቱ በግብፅ እና በሱዳን የውሃ እጥረት እና ደህንነት ላይ ስጋት ፈጥሯል ፣ እነሱም በአባይ ወንዝ ውሃ ላይ ጥገኛ ናቸው ብለዋል አናዶሉ እንደዘገበው።

በመዲናይቱ ካይሮ ከግብፁ አቻቸው ሳሜህ ሹክሪ ጋር በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አልበርት ሺንሺሮ እንደተናገሩት የውሃ ኃይል ፕሮጀክቱ በጣም ስሱ ጉዳይ ቢሆንም የውሃ ተደራሽነት የግብፃውያን “የሕይወት ወይም የሞት” ጉዳይ ነው።

“የመኖር መብት ሁል ጊዜ ከእድገት መብት በፊት መቅደም አለበት ምክንያቱም የሕይወት መብት ከሌለ የልማት መብት ሊከበር አይችልም እዚህ ያለው ምርጫ ግልፅ ነው ”ብለዋል ሺንጊሮ።

ከፍተኛው የቡሩንዲ ዲፕሎማት ጉዳዩን ለመፍታት ወታደራዊ አማራጭን በማስወገድ የግድቡን ውዝግብ በድርድር ፣ በትብብር እና በሕጋዊ ስምምነቶች ለሁሉም ወገኖች በሚስማማ መልኩ መፍታት እንዳለበት አስምሮበታል።

ሺንጊሮ “በዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች እና በመልካም ሥራዎች ኃይል እናምናለን” ብለዋል።

በያይኔአበባ ሻምበል
ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
አዲስ አበባ በህገ ወጥ እርድ ምክንያት በአመት 1.2 ቢሊዮን ብር ታጣለች

አዲስ አበባ በአመት በህገ ወጥ እርድ ምክንያት በአመት 1.2 ቢሊዮን ብር እንደምታጣ የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት የኢንፎርሜሽንና ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አታክልቲ ገብረሚካኤል ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል፡፡

ለመጪውን የዘመን መለወጫ በአል የስጋ ውጤቶችን በጥራትና በተመጣጠነ ዋጋ ለማድረስ ዝግጅት መደረጉን ነግረውናል፡፡

በመሆኑም ድርጅቱ ለ2014 አዲስ ዓመት በአል ከ2 ሺህ 500 በላይ የዳልጋ ከብት እና ከ1 ሺ 500 በላይ በግና ፍየሎችን ለተጠቃሚዎች ለማቅረብ መዘጋጀቱን ተናግረዋል።

ድርጅቱ ለአንድ በሬ የእርድ አገልግሎት 867 ብር፣ ለፍየል እና ለበግ ደግሞ 120 ብር በማከፈል ቤት ድረስ ለማቅረብ እንደሚጠየቅ እና ለዚህም ከ40 በላይ ዘመናዊ የቄራ ተሽከርካሪዎች መዘጋጀታቸውን ጠቁመዋል።

ለበዓሉ ህብረተሰቡ ከንጋቱ 11 ሰአት ጀምሮ ወደ ድርጅቱ በሬ፣ በግና ፍየል በማምጣት ከ30 እስከ 40 ደቂቃ ባለ ጊዜ አሳርዶ መውሰድ ይችላል ብለዋል።

ለቅርጫ የተዘጋጁም ካሉ በሬውን አምጥተው በማስመርመር የእርድ አገልግሎት ማግኘት ይችላሉ ነው ያሉት።

ከእርድ በኋላ ድርጅቱ የሚፈለግበት ቦታ ድረስ የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚያቀርብም ገልጸዋል።

በዋናው መስሪያ ቤት እና አቃቂ በሚገኘው ቅርንጫፍ ቢሮ በሚገኙ ሱቆች በኪሎ የበግ ስጋ 210 ብር እንዲሁም የበሬ ስጋ በ285 ብር መግዛት እንደሚችሉም ጠቁመዋል።

የአዲስ አበባ ቄራዎች ደርጅት በቀን በአማካይ 3 ሺህ 500 ሰንጋዎችን በማረድ ለተጠቃሚዎች የማቅረብ አቅም አለው ሲሉ ሃላፊው ነግውናል።

በረድኤት ገበየሁ
ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
ቮዳፎን ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ ከአዉሮፓ ኮሚሽን ፈቃድ አገኘ፡፡

ኮሚሽኑ ቮዳፎን ከሳፋሪ ኮም ጋር በሚኖረዉ ሽርክና ያልተገባ የንግድ ዉድድር ሊፈጠር ይችላል በሚል ምርመራ ሲያደረግ መቆየቱን የኢስት አፍሪካን ሪፖርት ያሳያል፡፡

ይሁንና ኮሚሽኑ ያደረገዉ የምርመራ ዉጤት ጥምረቱ ፍትሃዊ ዉድድር ለማድረግ ምንም የሚገድብ ነገር እንደሌለ አመላክቷል፡፡
በዚህም ቮዳፎን ሳፋሪ ኮም በሚመራዉና የእንግሊዝ የልማትና ፋይናንስ ኤጀንሲ ሲዲሲ ግሩፕ እና የጃፓኑ ሱሚቶሞ ኮርፖሬሽን በሚገኙበት ጥምረት እንዲቀላቀል ፈቃድ ማግኘቱ ታዉቋል፡፡

ከአዉሮፓ ህብረት ጋር የሚሰሩ ድርጅቶች ጥምረት በሚፈጥሩበት ወቅት በመካከላቸዉ ምንም አይነት ያልተገባ የንግድ ዉድድር እንዳይፈጠር ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸዉ ህብረቱ እንደሚያዝዝ ሪፖርቱ ያመላክታል፡፡


“የግሎባል ፓርትነርሽፕ ፎር ኢትዮጵያ” ድርጅት አንዱ የሆነው የጃፓኑ ሱሚቶሞ፣ በቴሌኮም ኦፕሬሽን ፈቃድ ጨረታውን ማሸነፉ የሚታወቅ ሲሆን በቀጣይ አምስት ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ በቴሌኮም ዘርፍ ከሁለት ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እንዳለው መግለጹ ይታወሳል፡፡


ምንጭ፡- Mobaile Europe.com

በሙሉቀን አሰፋ
ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
በከተማችን አዲስ አበባ 51 ህገ-ወጥ እርድ ተይዞ በግብረ-ሃይሉ እርምጃ እንደተወሰደባቸው ተገለጸ፡፡

በአራት ክፍለ ከተሞች በተለዩ ቦታዎች በተደረገ አሰሳ 51 ህገ-ወጥ እርድ ሲያከናኑ መያዛቸውን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታዉቋል፡፡

በከተማ ደረጃ ገበያን ለማረጋጋት ከሳምንታት በፊት የተቋቋመው ግብረ-ሀይል በአራት ክፍለ ከተሞች ማለትም ቦሌ፤ ንፍስ ስልክ ላፍቶ፤ ኮልፌ ቀራንዮ ና ለሚ ኩራ ክፍለ ከተሞች ውስጥ ህገ-ወጥ እርድ የሚከናወንባቸው ቦታዎችን ለይቶ ባደረገው ክትትል መሰረት በዛሬው እለት 51 በህገወጥ መንገድ እርድ ሲያከናን እጅ ከፍንጅ በመያዝ እርምጃ መውሰዱን ቢሮው አስታውቋል፡፡

በተጨማሪም በእነዚህ አካባቢዎች 229 በግና ፍየሉች በህገ-ወጥ መንገድ ሊታረዱ ሲሉ መያዛቸውን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የሆኑት አቶ ዳንኤል ሚዬሶ ለኢትዮ ኤፍ ኤም አስታውቀዋል፡፡

በረድኤት ገበየሁ

ጳጉሜ 04 ቀን 2013 ዓ.ም
በህገ ወጥ መንገድ የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው የኮቪድ -19 ህክምና ማዕከል በመክፈት አገልግሎት እየሰጠ የነበረ ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገለፀ።

በአዲስ አበባ ከተማ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 2 ጃፓን ኤምባሲ አካባቢ የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው ክሊኒክ በመክፈት የኮሮና ቫይረስ ህክምና ለተለያዩ ሰዎች ሲሰጥ ነው፡፡

የአየር መንገድ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ከቦሌ ክፍለ ከተማ የምግብ እና መድኃኒት ቁጥጥር ባለሥልጣን ባለሙያዎች ጋር በሰሩት ጥናት ፍቃድ ሳይኖረው ክሊኒክ በመክፈት የኮሮና ቫይረስ ህክምና አገልግሎት ሲሰጥ የነበረውን ግለሰብ በቁጥጥር ስር ውሎ ምርመራ እየተደረገበት እንደሆነ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገልጿል።

በክፍለ ከተማው የወረዳ 2 የምግብ እና መድሀኒት ቁጥጥር ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ጦና እንደተናገሩት ግለሰቡ ምንም አይነት የህክምና ፍቃድ ሳይኖረው በከፈተው የህክምና ማዕከል የውጪ ሃገር ዜግነት ያላቸው ሰዎች ጭምር ህክምና ፈልገው መምጣታቸውን ገልፀዋል፡፡

በወቅቱ በርካታ መድሀኒቶች የተገኙ ሲሆን ለምን አይነት ህመም የሚያገለግሉ መድሃኒቶች እንደሆኑም በማጣራት ላይ እንደሚገኙ የአዲስ አበባ ፖሊስ ገልጿል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን
ጳጉሜ 05 ቀን 2013 ዓ.ም
እንቁጣጣሽ ሎተሪ ጷጉሜን 5 ቀን 2013 ዓ.ም በብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ዕድል አዳራሽ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ላይ በህዝብ ፊት ወጥቷል፡፡

በዚህም መሰረት የወጡት የአሸናፊ ዕጣ ቁጥሮች እንደሚከተሉት ሆነዋል፡፡

1ኛ. 20,000,000 ብር የሚያስገኘው የ1ኛ ዕጣ ቁጥር 0580856

2ኛ. 10,000,000 ብር የሚያስገኘው የ2ኛ ዕጣ ቁጥር 0470508

3ኛ. 5,000,000 ብር የሚያስገኘው የ3ኛ ዕጣ ቁጥር 1973063

4ኛ. 3,000,000 ብር የሚያስገኘው የ4ኛ ዕጣ ቁጥር 0612715

5ኛ. 1,500,000 ብር የሚያስገኘው የ5ኛ ዕጣ ቁጥር 0816001

6ኛ. 750,000 ብር የሚያስገኘው የ6ኛ ዕጣ ቁጥር 1963913

7ኛ. 300,000 ብር የሚያስገኘው የ7ኛ ዕጣ ቁጥር 0716025

8ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 20,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 37510

9ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 10,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 79593

10ኛ. 20 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 5,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 27663

11ኛ. 200 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 2,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 8326

12ኛ. 200 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 1,000 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 2843

13ኛ. 2,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 500 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 022

14ኛ. 20,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 300 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር 42

15ኛ. 200,000 ዕጣዎች እያንዳንዳቸው ብር 100 የሚያስገኘው ዕጣ ቁጥር (የማስተዛዘኛ ዕጣ) ደግሞ 2 ቁጥር በመሆን ወጥቷል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የ2014 ዓ.ም አዲስ ዓመትን ከሠራዊቱ ጋር ለማክበር ማይጠብሪ ግንባር ተገኝተዋል።

በማይጠብሪ ግንባር ከሠራዊቱ ጋር በዓልን ለማክበር የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ፣ ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ሌትናል ጄኔራል አበባው ታደሰ፣ የመከላከያ ኅብረት ዘመቻ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሜጄር ጄኔራል ዘውዱ በላይ፣ የምእራብ እዝ እና የማይጠብሪ ግንባር አዛዥ ሜጄር ጄኔራል መሠለ መሠረት ጨምሮ ከፍተኛ የጦር መኮንኖች ተገኝተዋል።

የሠራዊት አባላት ተልዕኳቸን በላቀ ብቃት በመወጣት በአዲሱ ዓመት በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እናሰፍናለን ብለዋል። ሕዝባችን ያሳየንን ከፍተኛ ድጋፍ የሞራል ስንቅ አድርገን በአዲሱ ዓመት ለሕዝባችን ታላላቅ የድል ብሥራቶችን ለማሰማት እንዘጋጅም ማለታቸውን አሚኮ ዘግቧል።
ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያውያን
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
ከእስራኤል እስር ቤት አምልጠው ከነበሩ ስድስት እስረኞች መካከል አራቱ ተያዙ፡፡

የእስራኤል ፖሊስ ከሳምንት በፊት ከእስርቤት አምልጠው ከነበሩት ስድስት ፍልስጤማውያን እስረኞች መካከል አራቱን መያዛቸውን አስታውቀዋል፡፡

በከፍተኛ ሁኔታ ጥበቃ ከሚደረግለት የእስራኤል እስር ቤት ካመለጡት ስድስት ፍልስጤማውያን መካከል አራቱን አስሳ እንደያዘች እስራኤል አስታወቀች።

እስራኤል መልሳ ከያዘቻቸው ፍልስጤማውያን መካከል ሁለቱ የተገኙት የመኪና ማቆሚያ አካባቢ ሲሆን ሌሎች ሁለቱ ደግሞ ናዝሬት ከተማ አካባቢ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ተገልጿል።

እስረኞቹ በሰሜን እስራኤል ከሚገኘው ጊልቦዋ እስር ቤት ያመለጡት በሹካ መሬት ሰርስረው እንደነበረ ነው በወቅቱ የተገለጸው፡፡

ከእስረኞች መካከል ዋነኛ የእስራኤል ጠላት ተደርጎ የሚወሰደው የአል አቃሳ ቡድን መሪ እንደሆነ የሚነገርለት ዘካሪያ ዙቤይዲ ነው፡፡

እነዚህ እስረኞች በእስራኤል ለተፈጸመው ጥቃት ዋነኛ አቀነባባሪዎች ናቸው በሚል የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶባቸው የነበሩ ናቸው፡፡

የእስራኤል ፖሊሶች የተቀሩትን ሁለቱ እስረኞችን አድነው ለመያዝ በአየር ላይ የታገዘ አሰሳ እያካሄዱ እንደሆነ አልጀዚራ አስነብቧል፡፡

ሔኖክ ወ/ገብርኤል
መስከረም 01 ቀን 2014 ዓ.ም
በመዲናዋ በአዲስ ዓመት ዋዜማና በበአሉ ዕለት በትራፊክ ግጭት የሶስት ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ::


በዋዜማው ዕለት በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 ልዩ ቦታው ብስራት ትምህርት ቤት አካባቢ በተከሰተ የትራፊክ ግጭት በግምት የ35 ዓመት ወጣት ህይወቱን ሊያጣ ችሏል፡፡

እንዲሁም ልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ባጋጠመ የትራፊክ ግጭት በግምት የ60 ዓመት እናት ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡

በበዓሉ እለት ከቀኑ 11፡00 አካባቢ በየካ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ወረዳ 7 አካባቢ በተከሰተ የባቡር አደጋም የአንድ የ30 ዓመት ወጣት ህይወት ሊያልፍ ችሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በበአሉ ዋዜማ እና በበአሉ ቀን ምንም አይነት የእሳት አደጋ እንዳልተከሰተ ነው የተገለጸው፡፡

የእሳት እና የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የህዝብ ግኑኝነት ሀላፊ አቶ ጉልላት ጌታነህ ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት ጀሞ አካባቢ ከደረሰው አነስተኛ የጎርፍ አደጋ ውጪ ምንም ድንገተኛ አደጋ አለመድረሱን ተናግረዋል፡፡

በሄኖክ ወ/ገብርኤል
መስከረም 03 ቀን 2013 ዓ.ም
ከሰሜን ወሎ ዞን የተፈናቀሉ ዜጎች የደሴ ከተማ ከሚያስተናግደዉ አቅም በላይ በመሆኑ ወደ ኮምቦልቻ እየተላኩ ነዉ ተባለ፡፡


ከሰሜን ወሎ ዞን በርካታ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች በደሴ እና ኮምቦልቻ መጠለላቸው ይታወቃል።

በአሁኑ ሰዓትም በደሴ ከተማ በመንግስትና በግል ትምህርት ቤቶች ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ ዜጎች ቁጥር 275ሺህ መድረሱን የደሴ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሰኢድ የሱፍ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል።

ምክትል ከንቲባው እንዳሉት የተፈናቃዮች ቁጥር እጅግ ከፍተኛ በመሆኑና ደሴ ከተማ ከዚህ በኋላ ተፈናቃዮችን መቀበል ስለማትችል ወደ ኮምቦልቻ እየላክናቸው ነው ብለዉናል።

ከተፈናቃይ ዜጎች ቁጥራቸው እየጨመረ መምጣት አንጻር ደሴ ከተማ የቦታ እጥረት አጋጥሟልም ተብሏል።

ከሰሜን ወሎ የተፈናቀሉት 275ሺህ ዜጎች በመንግስት የተመዘገቡት ብቻ ናቸው ያሉት አቶ ሰኢድ፣ከቤተሰብ ጋር የተጠለሉት ቁጥር በዉል እንደማይታወቅና ቁጥሩ ከዚህም ከፍ ሊል እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

ከተፈናቃይ ቁጥር መጨመር ጋር ተያይዞም የእርዳታ ተደራሽነት ችግር መኖሩን የተናገሩት ምክትል ከንቲባዉ፣እስካሁን ዩኒቨርሲቲዎች ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን ዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች ግን ወደ አካባቢው እንዳልሄዱም አረጋግጠዉልናል።


በመቅደላዊት ደረጄ
መስከረም 04 ቀን 2014 ዓ.ም
ኢትዮጵያና ኬንያ የሞያሌን የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎትን ወደ ሥራ ለማስገባት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ

የሁለቱን አገራት የንግድ ትስስር ያጠናክራል የተባለውን የመግባቢያ ስምምነት የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቀበታና፣ የኬንያ የአገር ግዛት ደህንነት ኃላፊና የኬንያ ልዑክ መሪ ዊልሰን ጋቾከኪ በዛሬው እለት ተፈራርመዋል።

ስምምነቱ የተካሄደው በዛሬው እለት በአዲስ አበባ ከተማ ሲሆን ከሁለቱም አገራት የተወጣጡ የግል ዘርፍ ተወካዮች ተገኝተው ውይይት በማድረግ ላይ ናቸው።

በፊርማ ስነ-ስርዓቱ ወቅት የጉምሩክ ኮሚሾነሩ አቶ ደበሌ ቀበታ ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያ እና ኬንያ ረጅም ዕድሜ ያስቆጠረ ግንኙነት እንዳላቸው ገልፀው፣ የሁለቱን አገራት የንግድ ልውውጥ ለማጠናከር የሞያሌ አንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል።

አገራቱን ድንበር ቢለያያቸውም ንግድ ያስተሳስራቸዋል ያሉት ኮሚሽነሩ፣የሞያሌ የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት የንግድ ልውውጡን ከማጠንከሩ ባለፈ ለግሉም ዘርፍ ይበልጥ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል።

ስምምነቱ ፣የንግድ፣ የትራንስፖርት፣ እና የዜጎችን እንቅስቃሴ የሚያቀላጥፍ በመሆኑ ለኢትዮጵያና ለኬንያ የንግድ ልውውጥ ወሳኝ ምዕራፍ እንደሆነ ዊልሰን ጋቾከኪ ተናግረዋል፡፡

በተለይም የላፕሴት ኮሪደር መገንባት የሁለቱን አገራት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እንደሚያሳድገውም ነው ኃላፊው ያነሱት።

ባለፈው አመት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድና የኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የሃዋሳ ሞያሌ የጋራ ፍተሻ ጣቢያን መመረቃቸው የሚታወስ ነው።

በአባቱ መረቀ
መስከረም 05 ቀን 2014 ዓ.ም
በትግራይ ፤ በኤርትራ ስደተኞች ላይ የጦር ወንጀል እየተፈፀመ እንደሆነ የአለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዎች ገለፀ

የኤርትራ ስደተኞች ትግራይ ውስጥ ባለው ሀይል ታፍነው ይታሰራሉ፣ ይደፈራሉ፣ ይገደላሉ ብሏል ሂዩማን ራይትስ ዎች፡፡

እንደ አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት በኤርትራ ስደተኞች ላይ የሚፈፀሙት እነዚህ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በህወሀት ብቻ ሳይሆን ከኢትዮጵያ ፌደራል ሀይል ጎን ቆመው በሚዋጉት የኤርትራ ሀይሎች ጭምር እንደሆነም አንስቷል፡

በሺዎች የሚቀጠሩ ኤርትራውያን ስደተኞች በትግራይ ካምፕ ተጠልለው ይገኛሉ፡፡

የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ የአፍረካ ቀንድ ዳይሬክተር እንደተናገሩት ፤ በትግራይ ዘግናኝ ግድያዎች፣ አስገድዶ መድፈሮች እና ዘረፋዎች በኤርትራ ስደተኞች ላይ እየተፈፀሙ ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ ግልፅ የጦርነት ወንጀሎች ናቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ኤርትራ ለዚህ ክስ እስካሁን ምንም አላለችም፤ ከዚህ ቀደም ግን ክሱን ውድቅ አድርጋ ነበር፡፡

ቢቢሲ ሮይተርስ የዜና ወኪልን ጠቅሶ እንደዘገበው ከፍተኛ ቁጥር ያለው የኤርትራ ጦር በትግራይ ይገኛል፡፡

ሔኖክ አስራት
መስከረም 06 ቀን 2014 ዓ.ም
በአባይ ግድብ ቀውስ ላይ ግብፅ ከወታደራዊ ግጭት መራቅ እንደምትፈልግ ገለጸች

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሾክሪ ከብሉምበርግ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንዳሉት ግብፅ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ቀውስ ላይ ለመነጋገር ቁርጠኛ መሆኗን እና ከማንኛውም ወታደራዊ ግጭት መራቅ እንደምትፈልግ ተናግረዋል።

የግብፅ የውሃ ሀብቶች እና መስኖ ሚኒስትር መሐመድ አብደል አቲ በበኩላቸው ግድቡን በተመለከተ ዲፕሎማሲያዊ እርምጃዎች እንደ ቀጠሉ ናቸው ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ፍሬያማ እስኪሆኑ ድረስ ተጨማሪ ዝርዝር መረጃ አልሰጥም ’’ በማለት ለአልጀዚራ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት አባል የሆኑት ራካ ሐሰን ለአል ሞኒተር ሲናገሩ “የወታደራዊ አማራጭ ለግብፅ የማይታሰብ እንደሆነ ገልፀው ከዚህ ይልቅ ፓለቲካዊ ጫና መፍጠር አስፈላጊ እንደሆነ’’ ተናግረዋ፡፡

ከዚህ ጎን ለጎንም ግድቡን ከሚሰሩት ጀርመን እና ኢጣሊያን ኩባንያዎች ጋር መነጋገርን ጨምሮ ኢትዩጲያን ከሚደግፉት የአፍሪካ አገራት ጋርም መቀራረብ ያስፈልጋል ነው ያሉት፡፡

በየአፍሪካ ህብረት ድርድሮች ይከሽፉ እንደሆነ የተጠየቁት ሀሰን “መደምደሚያውን መናገር አይቻልም ምክንያቱም ዲፕሎማሲ አይታወቅም” ብለዋል።

በሚያዚያ 6 ቀን በግብፅ ፣ በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል በኪንሻሳ ከተደረገው የመጨረሻ ዙር ድርድር በኃላ ለአምስት ወራት ድርድር ሳይደረግ መቆየቱን ተከትሎ ግብፅ የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ጉዳዩን እንዲመለከት ጠይቃለች።

ሐምሌ 8 የተባበሩት መንግስታት በአፍሪካ ኅብረት ሥር ድርድር እንዲጀመር ማሳሰቡ ይታወሳል።

በያይኔአበባ ሻምበል
መስከረም 07 ቀን 2014 ዓ.ም