Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
11.4K subscribers
5.19K photos
76 videos
20 files
871 links
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት
Download Telegram
ሐምሌ 7፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 8፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የታላቁን ንጉሥ አል-ነጃሺ መስጂድ በዩኔስኮ ለማስመዝገብ እየተሠራ መሆኑ ተነገረ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መቀለ |
የትግራይ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት፣ የትግራይ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ፣ የመቀለ ዩኒቨርሲቲ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በጥምረት ያዘጋጁት በጥንታዊው አል-ነጃሺ መስጂድ መልሶ ግንባታ ላይ ያተኮረ ሀገር አቀፍ ኮንፈረንስ በመቀለ እየተካሄደ ነው።

የትግራይ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ሸይኽ አደም አብዱልቃድር በኮንፈረንሱ ላይ፣ ንጉሥ አል ነጃሺ በነቢዩ ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) የተመሰከረላቸው ፍትኃዊ እና በዓለም ሙስሊሞች ዘንድ ትልቅ ስፍራ ያላቸው መሪ መሆናቸውን ተናግረዋል።

የትግራይ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አጽብሃ ትግራይ የአል ነጃሺ መስጂድን ጨምሮ በሺህ የሚቆጠሩ ጥንታዊ ቅርሶች የሚገኙበት ክልል እንደኾነ አስታውሰው፣ እነዚህን ቅርሶች መንከባከብ፣ ማልማትና ማስተዋወቅ የሁሉም የትግራይ ተወላጆችና ኃላፊነት ነው ብለዋል።

የአል ነጃሺ የተሃድሶና ልማት ኢኒሼቲቭ የቦርድ ሰብሳቢ የኾኑት ዶክተር አብራር ፍትዊ በበኩላቸው የአል-ነጃሺ መስጂድ የሁሉም ሕዝብ ነው ካሉ በኋላ፣ መስጂዱ ታሪካዊ በመኾኑ በዓለም ሙስሊም ማኅበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ ክብር እንዳለው ተናግረዋል።

በኮንፈረንሱ ላይ የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አመራሮች፣ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች መገኘታቸውን የትግራይ ቴሌቪዥንን ዋቢ አድርጎ ሀሩን ሚድያ ዘግቧል።
••••••••••••••••••
​የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሐምሌ 12፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 13፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••
የዳዒዎች ሥልጠና ተጠናቀቀ።
•••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ስር ያለው የዑለማ ጉባዔ ጽ/ቤት ከአል ቡንያን ዓለምአቀፍ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የአቅም ግንባታ ሥልጠና የሰጣቸውን 105 ዳዒዎች በሰርተፊኬት አስመረቀ።

የሥልጠናው ተሳታፊዎች በዚህ ሥልጠና እስልምናን ሙስሊም ላልሆነው ማኀበረሰብ የማስተማር ክህሎት ወይም ወደ እስልምና የመጣራት ክህሎትን እንደቀሰሙ በኢትዮጵያ የአል ቡንያን ዓለምአቀፍ ዩኒቨርሲቲ አስተባባሪ የኾኑት ዑስታዝ አብዱልጀዋር ቢያ ተናግረዋል።

በሥልጠናው ላይ የተሳተፉት ዳዒዎች ከተለያዩ የሀገሪቱ ክልሎች የመጡና የተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪዎች መሆናቸውንም አስተባባሪው አስታውሰዋል።

ሌላው የሥልጠናው አስተባባሪ አቶ አብዱሰላም ጫጮ በበኩላቸው በሥልጠናው ለተሳተፉት ዳዒዎች ዘመኑን የዋጀ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ ወደ እስልምና የመጣራት ቁርኣናዊ ስነ-ምግባር፣ ከሽብርና ከግጭት የራቀ የአቃፊነት ክህሎት ማጎልበቻ ትምህርቶች እንደተሰጣቸው ተናግረዋል።

በምረቃው ስነ ሥርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት የሀገር አቀፉ የዑለማ ጉባዔ ምክትል ሰብሳቢና የፈትዋ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢው ዶክተር ጀይላን ኸድር ሥልጠናው የእስልምና እውቀታችሁን ሙስሊም ላልኾኑ ወገኖች የምታደርሱበትን ክህሎት የሚያዳብር በመሆኑ ትልቅ አቅም የሚፈጥርላችሁ ነው ብለዋል።

ዶክተር ጀይላን አክለውም፣ በሥልጠናው የተሳተፋችሁ ዳዒዎች በአይማዎች በኩል ያለውን ክፍተት የምትሞሉ እንደመኾናችሁ፣ ለዓሊሞች ክብር እየሰጣችሁ፣ ዝቅ ብላችሁ እውቀት በመጨመር የእስልምናን ጥሪ በስፋት የማሰራጨትና ትልቅ ኃላፊነት ወድቆባችኋል ብለዋል።

በኢትዮጵያ የአል ቡንያን ዓለምአቀፍ ዩኒቨርሲቲ ዋና ኃላፊ የኾኑት ዶክተር ሙሐመድ አል-ቁረይሺ ኢትዮጵያ ለዓለም ሙስሊሞች ባለውለታ መሆኗን ጠቅሰው፣ ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች ለሃይማኖታቸው ያላቸው ጽናት እና ለማወቅ ያላቸው ተነሳሽነት የሚያበረታታ ነው ብለዋል።

ዩኒቨርሲቲው ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጋር ያለውን ግንኙነት በማጠናከር በትብብር ለመሥራት ዝግጁ መኾኑንም ተናግረዋል።

የዑለማ ጉባዔ ጽ/ቤት ኃላፊ ሸይኽ ሙሐመድዘይን ዘኽረዲን በምረቃው ስነ ሥርዓት ላይ ሲናገሩ ከሥልጠናው ለየትኛው ዓይነት ደዕዋ ማን አቅም እንዳለው፣ አቅሙን ለየትኛው ዘርፍ መጠቀም እንደምንችል አመላክቶናል ብለዋል።

ሸይኽ ሙሐመድዘይን አክለውም፣ ገና ጀመራችሁ እንጂ ጨረሳችሁ ማለት አለመሆኑን ተረድታችሁ ለተሻለ ሥልጠና መነቃቃት አለባችሁ ካሉ በኋላ፣ ይህ ሥልጠና ምን አቅም እንዳላችሁ ብቻ ሳይኾን፣ ምን እንደጎደላችሁም አሳይቷችኋል ብለዋል።

ሥልጠናውን ወስደው ዛሬ በሰርተፊኬት የተመረቁት ዳዒዎች በምረቃው ስነ ሥርዓት ላይ በአረብኛ የተለያዩ ዝግጅቶችን አቅርበዋል።

በዚህ ሥልጠና ኢማም ቡኻሪ ኢስላሚክ አሶሴሽን ትልቅ ተባባሪ እንደነበር ከመድረኩ ተገልጿል።

በዝግጅቱ ላይ የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚደንት ሐጂ ፈትሁዲን ሐጂ ዘይኑ፣ ታላላቅ ዓሊሞች እና ታዋቂ ዳዒዎች ተገኝተዋል።
****
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ኢንና ሊላሂ ወኢንና ኢለይሂ ራጅዑን

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በደቡብ ኢትዮጵያ፣ ጎፋ ዞን፣ ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በድንገተኛ የመሬት ናዳ በወገኖቻችን ላይ በደረሰው የሞት አደጋ የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን ይገልጻል።

በተለይም በመጀመሪያው የመሬት ናዳ ጉዳት የደረሰባቸውን የአካባቢውን ነዋሪዎች ለመታደግና የጉዳቱን መጠን ለመቀነስ የአካባቢው ማኅበረሰብ በስፋት በመውጣት ጥረት እያደረገ በነበረበት ሰዓት በተከሰተው ሁለተኛ ዙር የመሬት ናዳ ምክንያት ተጨማሪ የዜጎች ሕይወት መጥፋቱና ከፍተኛ የንብረት ውድመት መከሰቱ ሐዘናችንን የከፋ አድርጎታል።

በዚህ የከፋ አደጋ ውስጥ፣ ኢትዮጵያዊነት አንዱ ለሌላው ችግር ፈጥኖ የመድረስና ለወንድም እህቶቹ ሕይወት እስከ መክፈል የሚደርስ መስዋዕትነት የታየበት ክስተት ኾኖ አልፏል።

በእንዲህ ዓይነት ድንገተኛ አደጋ ወቅት ሕዝባችን እርስ በርሱ የመረዳዳት ባህሉን እንደቀድሞው በማድረግ ጉዳት ከደረሰባቸው ወገኖቹ ጎን በመቆም የተለመደ የአብሮነት ባህሉን እንዲያዳብር ጠቅላይ ምክር ቤታችን በዚህ አጋጣሚ ጥሪውን ያስተላልፋል።

ምክር ቤቱ በአደጋው ቤተሰቦቻቸውንና ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ላጡ በሙሉ ፈጣሪያችን አሏህ ጽናቱን እንዲሰጣቸው ይለምናል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት
ሐምሌ 17፣ 2016 ዓ.ል | ?፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ፕሬዚደንቱ በሩሲያ፣ ካዛን ከተማ እየተካሄደ በሚገኘው የብሪክስ (BRICS) የቁርኣን ቲላዋ ውድድር ላይ ተገኙ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በብሪክስ (BRICS) የቁርኣን ቲላዋ (ጆሮ ገብ አቀራር) ውድድር ላይ ተገኙ።

ፕሬዚደንቱ የBRICS አባል የኾነችውን ሀገራችን ኢትዮጵያን ወክለው በውድድሩ ላይ በክብር እንግድነት የታደሙት የሩስያዋ ታታርስታን ግዛት መዲና ከኾነችው የካዛን ከተማ ሙፍቲ በተደረገላቸው ግብዣ መሠረት ነው።

በካዛን ከተማ በመካሄድ ላይ የሚገኘው ቁርአንን አስውቦ የመቅራት ውድድር በብሪክስ ማዕቀፍ ሲካሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲኾን፣ በውድድሩ ላይ ከብሪክስ አባል ሀገራት ቻይና፣ ኢትዮጵያ፣ ሕንድ እና ብራዚል እንደተሳተፉበት ከፕሬዚደንቱ ጋር ወደ ስፍራው የተጓዘው ቃል አቀባያችን ነግሮናል።

ከብሪክስ አባል ሀገራት በተጨማሪም በድምሩ ከ22 ሀገራት የተውጣጡ ቃሪኦች በውድድሩ ላይ እየተሳተፉ እንደኾነም ከቃል አቀባያችን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በዝግጅቱ መክፈቻ ላይ የሩሲያ ሙስሊሞች የሃይማኖት ልሂቃን አስተዳደር ምክትል ሊቀ መንበር ሩሻን አቢያሶቭ "በብሪክስ ማዕቀፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው ይህ ዓለም አቀፍ የቁርኣን ውድድር፣ ለBRICS ትልቅ ክስተት ነው" ማለታቸውን ቃል አቀባያችን ጠቅሷል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በነገው ዕለት እዚያው ካዛን ውስጥ በሚከፈተው 5ኛው ዓለምአቀፍ የሳይንስ እና የስነ መለኮት ጉባዔ ላይ እንደሚሳተፉም፣ ከቃል አቀባያችን የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

ጉባዔው "Spiritual Silk Road: the importance of religious values in the space of Greater Eurasia" በሚል ርዕስ የሚካሄድና በትልቁ የዩሮኤዥያ ቀጠና ውስጥ ሃይማኖታዊ እሴቶች በሚኖራቸው ጠቀሜታ ላይ ያተኮሩ ጽሑፎች የሚቀርቡበት እንደኾነ ቃል አቀባያችን ነግሮናል።

ጉባዔው ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲኾን፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በመክፈቻው ዕለት ጠቅላይ ምክር ቤቱን ወክለው ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ለማወቅ ተችሏል።

በዚህ ጉባዔ ላይ ከተለያዩ ሀገራት በመጡ ሙፍቲዎች፣ ስመ ጥር ዳዒዎች፣ እንዲሁም ምሁራን የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች እንደሚቀርቡ ተነግሯል።

የሩሲያ ሙፍቲዎች ምክር ቤት ምክትል ሊቀ-መንበርና የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ ሩሻን አቢያሶቭ፣ "እኛ ታዋቂ የሃይማኖት ዲፕሎማቶች፤ የሙስሊም ሀገራት ተወካዮች እና የBRICS ሀገራት ተወካዮች በዚህ ጉባዔ የጋራ ትብብራችንን ማሳየት እንፈልጋለን" ሲሉ ለዜና አውታሮች መናገራቸውን ከቃል አቀባያችን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

****
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ሐምሌ 18፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 19፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ፕሬዚደንቱ "ሁሉም ሃይማኖቶች በሰላም ዙሪያ ተደጋግፈው በጋራ መሥራት ይጠበቅባቸዋል" ሲሉ ተናገሩ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በሩስያዋ የታታርስታን ግዛት መዲና፣ ካዛን በመካሄድ ላይ በሚገኘው የብሪክስ ሀገራት ጉባዔ ላይ ንግግር አደረጉ።

ፕሬዚደንቱ በጉባዔው ላይ ሁሉም ሃይማኖቶች በመደጋገፍ በሰላም ዙሪያ በጋራ መሥራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል።

የእስልምና መሠረቱ ፍትኃዊነትና እኩልነት መኾኑን ያወሱት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ሙስሊሞች በሰላም፣ በፍትኅ እና በእኩልነት አጀንዳዎች ዙርያ ከማናቸውም ሃይማኖቶች ጋር ለመሥራት ዝግጁ መኾናቸውን ተናግረዋል።

በጉባዔው መክፈቻ ላይ የሩስያው ሙፍቲ ባደረጉት ንግግር የጉባዔውን ጠቀሜታ አስረድተዋል።

ሙፍቲው ሙስሊሞች ከሃይማኖታችንና ከማንነታችን አኳያ ምን ማድረግ አለብን? በብሪክስ ማዕቀፍ ለሚፈጠረው የሀገራት አጋርነትስ ምን ማድረግ ይጠበቅብናል? የሚል መጠይቃዊ ሐሳብ ማንሳታቸውን በስፍራው የተገኘው ቃል አቀባያችን ነግሮናል።

የሩስያው ሙፍቲ የብሪክስ ጉባዔ ዘንድሮ ለ5ኛ ጊዜ መካሄዱን አስታውሰው፣ ኢትዮጵያ እና ኤምሬትስ በዘንድሮው ጉባዔ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ መሳተፋቸውን ጠቅሰዋል።

ኢትዮጵያን የወከሉት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ከተለያዩ ዓለማት ከመጡ ታላላቅ የእስልምና ልሂቃንና ሙፍቲዎች ጋር በሰላም ሐሳብና አብሮነትን በማጎልበት ዙርያ ውይይት አድርገዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት በጉባዔው ላይ ካገኟቸው ከተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች፣ ዲፕሎማቶችና የሙስሊም ሀገራት ተወካዮች ጋር በሰላም ጉዳይ ላይ በጋራ በመሥራት አስፈላጊነት ዙርያ ሐሳብ ተለዋውጠዋል።

ጉባዔው በነገው ዕለት እንደሚጠናቀቅ ለማወቅ ተችሏል።

****
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ሐምሌ 19፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 20፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ፕሬዚደንቱ ኢትዮጵያን ወክለው የተሳተፉበት 5ኛው ዓለምአቀፍ የሳይንስ እና የስነ መለኮት ጉባዔ ተጠናቀቀ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ኢትዮጵያን ወክለው የተሳተፉበትና በሩስያ፣ የታታርስታን ዋና ከተማ ካዛን ለሁለት ቀናት የተካሄደው 5ኛው ዓለም አቀፍ የሳይንስ እና የስነ መለኮት ጉባዔ ተጠናቀቀ።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ የብሪክስ (BRICS) አባል የኾነችውን ኢትዮጵያን ወክለው የተሳተፉበት ጉባዔው፣ በዛሬው ዕለት ባለ 9 ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቅቋል።

"Spiritual Silk Road: the importance of religious values in the space of Greater Eurasia" በሚል ርዕስ ለሁለት ቀናት በተካሄደው በዚህ ጉባዔ ላይ በታላቁ የዩሮኤዥያ ቀጠና ውስጥ ሃይማኖታዊ እሴቶች በሚኖራቸው ጠቀሜታ ላይ ያተኮሩ የተለያዩ ጽሑፎች እንደቀረቡ ከፕሬዚደንቱ ጋር ወደ ስፍራው የተጓዘው ቃል አቀባያችን ነግሮናል።

በጉባዔው ላይ ከብሪክስ አባል ሀገራት በተጨማሪ ከአረብና ሙስሊም ሀገራት የተጋበዙ የበርካታ ሀገራት ተወካዮች እንደተሳተፉ ለማወቅ ተችሏል።

በሃይማኖታዊ እሴቶች ፋይዳ (አስፈላጊነት) ላይ ባተኮረውና
በዚህ ጉባዔ ላይ፣ በዚህ ዓመት የብሪክስ አባል የኾነችው ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፉ ተወክላ ተሳትፋለች።

ጉባዔው ባለ 9 ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት የተጠናቀቀ ሲኾን፣ መንፈሳዊ እና ሞራላዊ እሴቶች የዓለም ሚዛንን ለመታደግ እጅግ አስፈላጊ መኾናቸው በአቋም መግለጫው ላይ አጽንዖት እንደተሰጠው ለማወቅ ተችሏል።

በተጨማሪም፣ ጽንፈኝነት እና አሸባሪነት ምንም ዓይነት የሃይማኖት መሠረት እንደሌለው በአቋም መግለጫው ላይ መስፈሩን ከቃል አቀባያችን የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

ዘንድሮ ለአምስተኛ ጊዜ የተካሄደው ይህ ጉባዔ ለመጀመሪያ ጊዜ እ.ኤ.አ. በ2016 በቻይናዋ ኡሩምኪ ከተማ የተካሄደ ሲኾን፣ ከዚያ ወዲህ ታታርስታን፣ ኪርጊስታን እና ካዛክስታንን ጨምሮ በተለያዩ ሀገራት እንደተካሄደ ለማወቅ ተችሏል።

••••••••••••••••••

የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ሐምሌ 23፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 24፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ማሳሰቢያ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
በ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ ጉዞ ዋስትና ብር ላስያዛችሁ ሐጃጆች።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በ1445 ዓ.ሒ. (2016 ዓ.ል.) እድሜያቸው ከ35 ዓመት በታች ለሆኑ የሐጅ ተጓዦች ብር 160,000.00 (አንድ መቶ ስድሳ ሺህ) የጉዞ ዋስትና ብር መያዙ ይታወሳል።

ምክር ቤቱ አስፈላጊውን ማጣሪያ አድርጎ በቀጣዮቹ አሥራ አምስት ቀናት ውስጥ የጉዞ ዋስትና ብር ባስያዘው ሐጃጅ ስም በተከፈተው የባንክ ሒሳብ ቁጥር ገንዘቡን ገቢ የሚያደርግ መኾኑን ለማሳወቅ ይወድዳል።
•••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሐምሌ 24፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 25፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለጎፋ ዞን አደጋ ተጎጂዎች 3 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ድጋፍ አደረገ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
ሐምሌ 24፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 25፣ 1446 ዓ.ሒ

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ለጎፋ ዞን የመሬት መንሸራተት አደጋ ተጎጂዎች 3 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው የደረቅ ምግብና የቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ።

ለአደጋው ተጎጂ ወገኖች የታለመውን እርዳታ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ አስረክበዋል።

በርክክቡ ወቅት ሼይኽ ሐጂ እንደተናገሩት በወገኖቻችን ላይ ይህ አደጋ ሲደርስ የጠቅላይ ምክር ቤቱ አመራሮች ለሥራ ጉዳይ ከሐገር ውጪ በመሆናቸው ምክንያት በወቅቱ በአካል በመምጣት ድጋፍ ማድረግ አለመቻላቸውን ተናግረዋል።

በዛሬው ዕለት ጠቅላይ ምክር ቤቱ ያደረገው ድጋፍ የመጀመሪያ እንጂ የመጨረሻው እንዳልኾነም ሸይኽ ሐጂ ተናግረዋል።

እሁድ ሐምሌ 14 እና ሰኞ ሐምሌ 15፣ 2016 ዓ.ል. በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖቻችን በዘላቂነት ለማቋቋም ከኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ አባል ቤተ እምነቶች ጋር በመሆን በቀጣይ ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ አቅርበዋል።

ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም በአደጋው ዘመድ ወዳጆቻቸውን ላጡ ወገኖቻችን ፈጣሪያችን አሏህ ፅናቱን እንዲሰጣቸው ምኞታቸውን ገልፀዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ልዩ አማካሪ ዶክተር ብርሐኑ ጋቦ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ላደረገው ድጋፍ በራሳቸውና በክልሉ መንግሥት ስም ምሥጋናቸውን አቅርበዋል።

በቀጣይ ጊዜያት 7 መቶ አባዎራዎችን አደጋው ከደረሰበት ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ ወደ ሌላ ቦታ ለማስፈር የክልሉ መንግሥት ሥራ መጀመሩን ልዩ አማካሪው ተናግረዋል።

በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ 236 ሰዎች ሕይታቸውን እንዳጡ የጠቀሱት ልዩ አማካሪው፣ የአስክሬን ፍለጋው አሁንም እንደቀጠለ ተናግረዋል።

ዛሬ በተደረገው የእርዳታ ድጋፍ ርክክብ መርኃ ግብር ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሼይኽ አብዱልከሪም ሼይኽ በድረዲን፣ የፌደራልና የክልል መጅሊስ ሥራ አስፈፃሚዎች ተገኝተዋል።
••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሐምሌ 25፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 26፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የሃይማኖት አባቶች ለዘመናት የቆዩ የአብሮነት እሴቶችን የሚሸረሽሩ ተግባራት ስር እንዳይሰዱ በጋራ እንዲሠሩ ጥሪ ቀረበ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የሃይማኖት አባቶች ለዘመናት የቆዩ የአብሮነት እሴቶቻችንን የሚሸረሽሩ ተግባራት ስር እንዳይሰድዱ በጋራ እንዲሠሩ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ጥሪ አቀረቡ።

ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ይህን ጥሪ ያቀረቡት "በጎ የዋሉልንን እናመስግን፤ ሰላማችንን እንጠብቅ" በሚል መሪ ሐሳብ በአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የስብሰባ አዳራሽ የተጀመረውን የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ 16ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔና የእውቅና መርኃ ግብር በንግግር በከፈቱበት ወቅት ነው።

ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ በዚሁ ንግግራቸው የሃይማኖት አባቶች በምዕመናን ዘንድ ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው በመኾኑ፣ በሀገራችን ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ጠንክረው እንዲሠሩ አሳስበዋል።

የሃይማኖት አባቶች ለዘመናት የቆዩ የአብሮነት እሴቶቻችንን የሚሸረሽሩ ተግባራት ስር እንዳይሰድዱ ተባብረው ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ፕሬዚደንቷ አሳስበዋል።

በሰላም ሚኒስቴር የሰላም ግንባታና ብሔራዊ መግባባት ዘርፍ ሚኒስትር ዴዔታ ከረዲን ተዘራ (ዶ/ር)፣ ኢትዮጵያ የሃይማኖት ሀገር በመሆኗ፣ ስትደሰት የሚደሰቱ፣ ስትከፋ የሚከፉ ምዕመናን ሀገር መሆኗን ተናግረዋል።

በቅዱሳን መጻሕፍት ላይ በተለያዩ ቦታ የተጠቀሰችውን የሀገራችን ኢትዮጵያን ዘላቂ ሰላም ለማስጠበቅ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታቸው ከሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ጋር ተቀራርቦ እንደሚሠራ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ የኾኑት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ጉባዔው የጋራ በሆኑ የሰላም ጉዳዮች ላይ እንደሚሠራ ተናግረዋል።

ተቋሙ "ሌሎች እንዲያደርጉላችሁ የምትሹትን፣ ለሌሎች አድርጉ" የሚለውን የቅዱሳን መጻሕፍት ወርቃማ መርኅ መሠረት በማድረግ፣ በጋራ ሰላምን፣ መከባበርን፣ አብሮነትን፣ ይቅርታንና መሰል በጎ ሥራዎችን በማስተማር መልካም እሴቶቻችን እንዲጠናከሩ በጋራ እየሠራ መሆኑን ሰብሳቢው ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ጥቅምት 25፣ 2003 ዓ.ል በአምስት መሥራች የሃይማኖት ተቋማት በመዲናችን አዲስ አበባ የተመሠረተ ሲሆን በአሁን ሰዓት የአባላቱ ቁጥር ወደ ሰባት ቤተ እምነቶች አድጓል።

ተቋሙ በዚሁ ጉባዔ ላይ ለ21መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ለሁለት ግለሰቦች ምሥጋና አቅርቧል።
.••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሐምሌ 28፣ 2016 ዓ.ል | ሙሐረም 29፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ለክልል መጅሊስና ለዑለማ አመራሮች የተዘጋጀ ሥልጠና ተጠናቀቀ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት፣ የዑለማ ጉባዔ ጽሕፈት ቤት ለክልል መጅሊስ እና ለዑለማ አመራሮች ያዘጋጀው የ10 ቀናት ሥልጠና ተጠናቀቀ።

የዑለማው ጉባዔ ጽሕፈት ቤት ከአል ቡንያን ዓለምአቀፍ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባባር ያዘጋጀው ይህ ሥልጠና አሥተዳደራዊ እና ዲናዊ ክፍተቶችን ለማጥበብ ያለመ እንደሆነ ተነግሯል።

በሥልጠናው መዝጊያ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ለሠልጣኞቹ ባስተላለፉት መልዕክት ይህን መሰል ሥልጠናዎች ያለንን እውቀት ለማደስ እና ከዘመን ጋር ለመራመድ አስፈላጊ ናቸው ብለዋል።

ሠልጣኞች ከሥልጠናው ያገኙት እውቀት በየሥራ መስካቸው ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ያግዛቸዋል ብለዋል።

የሀገር አቀፉ የዑለማ ጉባዔ ምክትል ሰብሳቢ እና የፈትዋ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢው ዶክተር ጀይላን ኸድር በበኩላቸው አብዛኞቹ የሥልጠናው ተሳታፊዎች አንጋፋ ዓሊሞች ቢሆኑም ሥልጠናውን እንደ ተራ ተማሪ በትጋት መከታተላቸውን በመጥቀስ አመስግነዋል።

የሥልጠናው ተሳታፊ ዓሊሞች በሥልጠናው ብዙ ነገር የቀሰሙ በመኾኑ በአሠራራቸውም ኾነ በትምህርት አሰጣጥ ስልታቸው ላይ ለውጥ እንዲያመጡ ያግዛቸዋል ብለዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ለሠልጣኞቹ የምስክር ወረቀት የሰጡ ሲኾን፣ ለሥልጠናው ስኬት የተለያዩ አካላት ላበረከቱት አስተዋጽዖ ምሥጋና አቅርበዋል።

በሥልጠናው የመዝጊያ መርኃ ግብር ላይ ከባለድርሻ አካላት የተለያዩ መልዕክቶች የተላለፉ ሲኾን፣ ለሥልጠናው ተሳታፊዎች የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል።

በኢትዮጵያ የአል ቡንያን ዓለምአቀፍ ዩኒቨርሲቲ ዋና ኃላፊ ዶክተር ሙሐመድ አል-ቁረይሺ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅ እና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሥራ አመራሮች፣ ዓሊሞች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
****
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ሐምሌ 29፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 1፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ዮርዳኖስን እንዲጎበኙ ጥሪ ቀረበላቸው።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በኢትዮጵያ የዮርዳኖስ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር የኾኑትን ዶ/ር ኤማድ ማሳልሜህን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

በዚሁ ጊዜ አምባሳደር ኤማድ ሲናገሩ፣ ዮርዳኖስ እንደ ኢትዮጵያ ሙስሊሞችንና ክርስቲያኖችን በጋራ አቅፋ ከመያዟ ባሻገር፣ በርካታ የታሪክ አሻራዎች ያላት ሀገር ነች ብለዋል።

አምባሳደሩ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም እንደ ማኀበረሰብ እና እንደ ሀገር የጋራ ትብብር ለመፍጠር በመስከረም ወር ዮርዳኖስን እንዲጎበኙ ጥሪ አቅርበውላቸዋል።

አምባሳደር ኤማድ በዚሁ ወቅት በሀገራቸው መንግሥት ስም ለጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንትሥጦታ አበርክተዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በአምባሳደሩ ለተበረከተው ሥጦታ እና ለተደረገላቸው የጉብኝት ግብዣ አመሥግነዋል።

ፕሬዚደንቱ አያይዘውም ኢትዮጵያ በሃይማኖታቸው ምክንያት ግፍ እና መከራ የደረሰባቸውን የታላቁ ነቢይ (ሶ.ዐ.ወ.) ባልደረቦች ተቀብላ ያስተናገደች ሀገር ከመኾኗ ባሻገር፣ ነቢዩ ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ.) ያከበሯት ትልቅ ሀገር መሆኗን አስታውሰዋል።

አምባሳደር ኤማዳ በጠቅላይ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ሲደርሱ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የውጪ ጉዳይ ክፍል ተጠሪ ረዳት ፕሮፈሰር አደም ካሚል አቀባበል አድርገውላቸዋል።

አምባሳደር ኤማዳ ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ምክር ቤቱን በጎበኙበት ወቅት፣ በዮርዳኖስ የልምድ ልውውጥ ጉብኝት የማድረግ ፍላጎት ካለ ኤምባሲያቸው ይህን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚያመቻችና የትምህርት ዕድሎችን እንደሚሰጥ መናገራቸው ይታወሳል።

••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሐምሌ 29፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 1፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم

•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የፌደራሉ እና የክልል መጅሊስ አመራሮች፣ እንዲሁም ዓሊሞች በጠቅላይ ምክር ቤት አዳራሽ የጋራ ውይይት አደረጉ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት መሪዎች ከክልል መጅሊስ ኃላፊዎችና ዓሊሞች ጋር የጋራ ውይይት አደረጉ።

የጋራ ውይይቱን የከፈቱት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ ውይይቱ ከመደበኛው ጠቅላላ ጉባዔ በፊት ኃላፊዎቹ ለሥልጠና የመጡበትን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የተደረገ የጋራ ምክክር መሆኑን ተናግረዋል።

ዋና ጸሐፊው በዚሁ ጊዜ ጠቅላይ ምክር ቤቱ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ስላከናወናቸው ዋና ዋና ተግባራት ለመደበኛ ጠቅላላ ጉባዔው ሪፖርት ለማድረግ ዝግጅቱን እንደጨረሰ ለተሳታፊዎቹ ተናግረዋል።

ዋና ፀሐፊው ሸይኽ ሐሚድ የክልል መጅሊስ ኃላፊዎች እቅዳቸውን መሠረት በማድረግ ለመደበኛ ጠቅላላ ጉባዔው የሚያቀርቡትን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት እንዲያጠናቅቁ ጠይቀዋል።

ውይይቱን የመሩት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፉ ሥልጠናው በተጠናቀቀ ማግስት ዳግም ተገናኝቶ ለመመካከር በመብቃታቸው አላህን አመሥግነው፣ ለክልል መጅሊስ ኃላፊዎችና ዓሊሞች መልዕክቶች አስተላልፈዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የዑለማ ጉባዔውም ፕሬዚደንት በመኾኑ በአንድ ጥላ ስር በአንድ መሪ ተናብበው ሕዝበ ሙስሊሙን የሚያገለግሉ መሆናቸውን ተናግረዋል።

የየክልሉ መጅሊስ ፕሬዚደንቶችም የክልላቸው የዑለማ ጉባዔ ጽ/ቤት ፕሬዚደንትም መሆናቸውን ያስታወሱት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ዑለማ የዲን መሪ በመኾኑ የክልል መጅሊስ ለዑለማው ትኩረት ከማድረግ አይዘናጋ ሲሉ አሳስበዋል።

ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ለዑለማ ክብር ያልሰጠ መጅሊስ አደጋ ነው ሲሉም በአጽንዖት ተናግረዋል።

የምርጫ ጊዜ በመምጣቱ ለማኅበረሰቡ ፍትኀዊ እና ከጣልቃ ገብ ጫና የጸዳ ምርጫ መደረግ ስላለበት፣ የመጅሊስ እና የዑለማ መሪዎች በየመዋቅሩ አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አስታውሰዋል።

በስብሰባው ላይ የተገኙት የክልል መጅሊስ ኃላፊዎች እና ዓሊሞችም ለጠቅላይ ምክር ቤቱ ኃላፊዎች ጠቃሚ ያሉትን ሐሳብና አስተያየት አቅርበው ጥያቄዎችንም ጠይቀዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንትም ከየክልሎቹ የመጅሊስ መሪዎችና ዓሊሞች የተሰጡ አስተያየቶችን እና የቀረቡ ጥያቄዎችን አስተናግደዋል።

በየክልሎቹ የሚንቀሳቀስ ኮሚቴ ተዋቅሮ ችግሮችን በማጥናት በጠቅላይ ምክር ቤት የሚሸፈነውን በጠቅላይ ምክር ቤቱ፣ በክልሉ የሚፈታውን ለክልሉ እንደሚያቀርብ ተናግረዋል።

አያይዘውም በጋራ ውይይቱ ላይ የተነሱ አንዳንድ ሐሳቦችና ጥያቄዎች በመደበኛው ጉባዔ ላይም ሊነሱና የጋራ ውሳኔ ሊያገኙ የሚችሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

የክልል መጅሊሶች ከጠቅላይ ምክር ቤቱ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር የጉባዔ ሪፖርት ብቻ በቂ አይደለም ሲሉም ተናግረዋል።

በጋራ ውይይት መድረኩ ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ፣ የዑለማ ጉባኤ ጽ/ቤት ኃላፊዎች፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሐጂ ከማል ሐሩን እና የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሥራ አመራር አባላት ተገኝተዋል።
••••••••••••••••••

የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ነሐሴ 2፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 4፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የኢራኑን አምባሳደር ተቀብለው አነጋገሩ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ አምባሳደር የኾኑትን ዓሊ አክበር ረዛኢ በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም እና በኢትዮጵያ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ አምባሳደር ዓሊ አክበር ረዛኢ በልማት እና አብሮ በመሥራት ዙሪያ ሰፋ ያለ ውይይት አድርገዋል።

ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በዚሁ ጊዜ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ በድንገተኛ የሄሊኮፕተር አደጋ የቀድሞውን ፕሬዚደንት ኢብራሂም ረኢሲን ያጣችበትን ክስተት በሐዘን አስታውሰው፣ የሀገሪቱ ሕዝብ አዲሱን መሪውን ለመምረጥ በመቻሉ የተሰማቸውን ደስታ በራሳቸውና በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ስም ገልፀዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት አያይዘውም በኢራን ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን የሱኒ ፈለግ ተከታይ ሙስሊሞች በቴህራን የሱኒይ መስጂድ እንዲሠራላቸው መንግሥታቸውን አንዲጠይቁላቸው ጠይቀዋል።

ፕሬዚደንቱ በተጨማሪም የኢራን መንግሥት ከኢትዮጵያ ሙስሊሞች የሃይማኖት ተቋም (መጅሊስ) እና ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በልማት ጉዳዮች ላይ የጋራ ትስስር እና ትብብሩን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል።

ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም አምባሳደር ዓሊ አክበር ረዛኢን ባነጋገሩበት ወቅት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን፣ ዋና ጸሐፊው ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሥራ አስፈጻሚና የትምህርትና ማህበራዊ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ተጠሪ የሆኑት ኢንጅነር አንዋር ሙስጠፋ፣ እንዲሁም የጠቅላይ ምክር ቤቱ የፈትዋና ምርምር ተጠሪ ሸይኽ እንድሪስ ዓሊ ደጋን ተገኝተዋል።
••••••••••••••••••

የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ነሐሴ 3፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 5፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
እውቁ ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ሼይኽ ዓሊ ሱፊ በሰላም መስጂድ የጁምዓ ሶላት አስሰገዱ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

ዓለም አቀፍ አውቅና ያላቸው ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ሼይኽ ዓሊ ሱፊ በአዲስ አበባ፣ ቄራ አከባቢ በሚገኘው ሰላም መስጂድ የጁምዓ ሶላትን አስሰገዱ።

ኢትዮጵያዊ የዘር ሐረግ እንዳላቸው የሚነገርላቸው ሼይኽ አብዱረሺድ በሰላም መስጂድ የጁምዓ ኹጥባ በማድረግ ሶላቱን በኢማምነት አስሰግደዋል።

በአሥር ዓመታቸው ሙሉውን ቁርኣን በቃላቸው በመያዝ ሐፊዝ ለመሆን የቻሉት ሼይኽ አብዱረሺድ ወደ ግብፅ ተጉዘውም በአሥሩም የአቀራር ዘይቤዎች እውቅና እና ኢጃዛ አግኝተዋል።

በተለያዩ ዓለም አቀፍ የቁርኣን ውድድር መድረኮች ላይ በዳኝነት የሚያገለግሉት ሼይኽ አብዱረሺድ ከተለያዩ  የዓለማችን ክፍሎች ለሚመጡ ቁራዖችም ኢጃዛ በመስጠት ላይ ይገኛሉ።

እውቁ የዓለማችን ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ በኳታርም በአነስ ኢብኑ ማሊክ መስጂድ በኢማምነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ።

ዛሬ በሰላም መስጂድ በተደረገው የጁምዓ ሶላት ስግደት ላይ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋን ጨምሮ፣ የፌደራልና የአዲስ አበባ መጅሊስ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ ዓሊሞች፣ ዱዓቶች እና በርካታ ቁጥር ያላቸው የከተማዋ ምዕመናን ተገኝተዋል።
•••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ነሐሴ 4፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 6፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከተባበሩት ዓረብ ኤሚሬትስ መንግሥት የተሽከርካሪዎች ሥጦታ ተበረከተለት።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |
የኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ከተባበሩት ዓረብ ኤሚሬትስ መንግሥት ሦስት ዘመናዊ ተሽከርካሪዎች እና 30 ላፕቶፖች በሥጦታ ተበረከተለት።

የሥጦታው ርክክብ በጠቅላይ ምክር ቤቱ ቅጥር ግቢ በተካሄደበት ስነ ሥርዓት ላይ የምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ፣ ለኢትዮጵያ ሙስሊሞች ተቋም የተበረከተው ሥጦታ ከተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ጋር ለሚኖረን ትስስር ትልቅ ፈር ቀዳጅ እንደኾነ በመጥቀስ በሕዝበ ሙስሊሙ እና በተቋሙ፣ እንዲሁም በራሳቸው ስም ምሥጋና አቅርበዋል።

ፕሬዚደንቱ አክለውም የተባበሩት አረብ ኤሚሬት መንግሥት ከሀገራችን መንግሥት ጋር በተለያዩ የልማትና ኢንቨስትመንት እንዲሁም የበጎ አድራጎት ተግባራት የሚያደርጋቸውን ትብብሮች በማውሳት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ "በዛሬው ዕለት የተረከብናቸው ተሽከርካሪዎች በሥጦታ ሊያበረክቱልን ቃል ከገቧቸው ውስጥ መንገድ ላይ ካሉት ቀድመው የደረሱት ናቸው" ሲሉ ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ቅጥር ግቢ በተካሄደው የርክክብ ስነ ሥርዓት ላይ የሙሐመድ ዛይድ ዩንቨርሲቲ ፕሬዚደንት ዶክተር ኸሊፋ ሙባረክ አዛሃሪ፣ "ዛሬ እኛ እዚህ የተገኘነው በአላህ ተልዕኮ ጥላ ስር ወንድማማችነታችንን በማጠናከር፣ መልካም ግንኙነታችንን፣ ፍቅርና መተሳሰብን ለመግለጽ ነው" ሲሉ ተናግረዋል።

"ከመሪ ተቋሙ ጋር ትስስራችንን በማጠናከር፣ የመጅሊሱን ትልልቅ ዓላማዎች ለማገዝ እና ከጎናችሁ ለመቆም ፍላጎት አለን" ሲሉ የተናገሩት ዶክተር ኸሊፋ አያይዘውም፣ በሥጦታ የተበረከቱት ላፕቶፖች መጅሊሱ አሠራሩን በቴክኖሎጂ ለማዘመን በሚያደርገው ሂደት ትልቅ እገዛ እንደሚያደርጉለት ተናግረዋል።

ዶክተር ኸሊፋ አክለውም ትስስራችንን በማጠናከር መጅሊሱ የሚሠራቸውን ትልልቅ ሥራዎች ለመደገፍ፣ በመስጂዶች ግንባታ እና የሃይማኖት ተቋማትን በማጠናከር ዙሪያ ትብብር ለማድረግ በመካከላችሁ በመገኘቴ ታላቅ ክብር ይሰማኛል ብለዋል።

የዛሬው ሥጦታ፣ የጋራ ግንኙነታችንን በማጠናከር በታላላቅ ፕሮጀክቶች ላይ አብረን ለመሥራት መሸጋገሪያችን ነው ሲሉም ተናግረዋል።

በመጨረሻም ዶክተር ኸሊፋ ሙባረክ አዛሃሪ የጋራ ግንኙነታችንን ይበልጥ ለማጠንከር የመጅሊሱ አመራር በቅርቡ የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስን እንዲጎበኙ ጥሪ አቅርበዋል።

ለጠቅላይ ምክር ቤቱ የተበረከቱትን ተሽከርካሪዎችና ላፕቶፖች በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ምክትል አምባሳደር ክቡር ሱዑድ አልጢኔጂ ለኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ አስረክበዋል።

በጠቅላይ ምክር ቤቱ ቅጥር ግቢ በተካሄደው የሥጦታ ርክክብ ስነ ሥረዓት ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ፣ በጠቅላይ ምክር ቤት ስር ያለው የዑለማ ጉባዔ ጽ/ቤት የሀገር አቀፉ የዑለማ ጉባዔ ምክትል ሰብሳቢ እና የፈትዋ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢው ዶክተር ጀይላን ኸድር፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ጸሐፊ ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ፣ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኸይረዲን ተዘራ፣ ሌሎች የመጅሊሱ ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ተወካዮች ተገኝተዋል።
****
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ነሐሴ 5፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 7፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ባቡ ረህማን እስላማዊ ማኅበር 'የዘካን ገንዘብ ለሚግገባቸው ለማድረግ የባንክ አካውንት መክፈቱን ተናገረ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የማኀበራት ፈቃድ ካገኙት ተቋማት አንዱ የኾነው 'ባቡ ረህማን እስላማዊ ማኅበር' ከዘካ በሰበሰበው ገንዘብ ድህነትን ለመቅረፍ እና የሥራ ዕድል ለመፍጠር የዘካ የባንክ አካውንት መክፈቱን የማኅበሩ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተናገሩ።

ዋና ሥራ አስኪያጁ አቶ ኢብራሂም አደም፣ 'ማኅበሩ የዘካን ገንዘብ ለሚግገባቸው እናድርግ' በሚል መሪ ቃል የሚንቀሳቀስ መኾኑን እና ዘካ ድህነትን ለመቀነስ እያበረከተ ያለውን አስተዋጽዖ እና ሥራ አብራርተዋል።

'ባቡ ረህማን እስላማዊ ማኅበር' በቀድሞው የሰሜናዊ ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበር አባላት የተመሠረተ እንደኾነ የጠቀሱት የማኅበሩ ሥራ አስኪያጅ፣ ዓላማውም በትውልድ ሀገራቸው አቅመ ደካሞችና ረዳት ያጡ አረጋውያን እና ወላጅ አልባ ሕጻናት ተቸግረው በማየታቸው ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ኃላፊነትን መወጣትን መሠረት ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

የማኅበሩ አባላት ከ2011 ዓ.ል. ጀምሮ ተቋማዊ ባልሆነ መንገድ ድጋፍ ሲያደርጉ የቆዩ መሆናቸውን አስታውሰው፣ ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የማኅበር ፈቃድ ካገኙ ጀምሮ የዘካ ገንዘብን ለሚገባቸው የሃይማኖቱ ተከታይ አገልግሎት እያዋሉ መሆኑን ተናግረዋል።

ማኅበሩ በአማራ ክልል ምሥራቅ ጎጃም አካባቢ አረጋውያንን የመርዳት፣ የመኖሪያ ቤት ጥገና የማድረግና በአቅም ችግር ሳቢያ በህመም የሚሰቃዩ ወገኖች ሕክምና እንዲያገኙ የማድረግ ሥራ ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰዋል።

የባቡ ረህማን እስላማዊ ማኅበር' በ2014 የዘካ አካውንት በመክፈት መሥራት እየቻሉ ሥራ አጥ ለኾኑ መስሊሞች ከዘካ በሰበሰበው ገንዘብ የሥራ ዕድል እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል።

ዘካ ችግርን በዘላቂነት ለመቅረፍ እና የዛሬ ደሀ ነገ የሌሎች ችግር ተካፋይ የማድረግ ዓላማ ያለው በመሆኑ፣ ማኅበሩ የዘካን ገንዘብ ለሚገባቸው እንዲውል ፕሮጀክት ቀርጾ ለተፈጻሚነትቱ ዘካ ማውጣት የሚመለከታቸው ሙስሊም ወገኖች ከጉኑ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርቧል።

በመጨረሻም የባቡ ረህማን እስላማዊ ማኅበር' ትኩረት ባደረገበት አካባቢ ከዘካ በሚሰበስበው ገንዘብ የሥራ ዕድል ሊፈጥርበት ያዘጋጀውን የምግብ ቤት እቃ፣ የልብስ ማጠቢያ፣ የልብስ ስፌት መኪናዎችና የጀበና ቡና የመሳሰሉ አዳዲስ ቁሳቁሶችን አስጎብኝቷል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ማቋቋሚያ አዋጅ፣ ተቋሙ ለሃይማኖታዊ ማኅበራት እና የበጎ አድራጎት ድርጀቶች ፈቃድ የመስጠት ሥልጣን ይሰጠዋል።
ነሐሴ 9፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 11፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ከእውቁ ዓለምአቀፍ ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ሱፊ ጋር ተነጋገሩ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በአዲስ አበባ የሚገኙትንና በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የኾኑትን ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ሱፊን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

ክቡር ፕሬዚደንቱ፣ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ሱፊ ለዚያራ ጽሕፈት ቤታቸው ድሩስ በመምጣታቸው የተሰማቸውን ደስታ በመግለጽ በራሳቸውና በጠቅላይ ምክር ቤቱ ስም ምሥጋናቸውን አቅርበዋል።

አያይዘውም ቁርኣንን በመሃፈዝና በመማር አርያዓቸውን የሚከተሉ የነገ ትውልዶችን ለመርዳት በጠቅላይ ምክር ቤቱ ስር ካለው የዑለማ ጉባዔ ጽሕፈት ቤት ጋር በጋራ መሥራት በሚቻልበት ሁኔታ ዙርያ ተነጋግረዋል።

ዓለም አቀፍ እውቅና ያላቸው ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ከኢትዮጵያ የዑለማ ጉባዔ ጽሕፈት ቤት ጋር ተቀራርበው ለመሥራት ፈቃደኛ መኾናቸውን ተናግረዋል።

ስመ ጥሩ ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ በጠቅላይ ምክር ቤቱ የወቅቱን ሶላት ካስሰገዱና አጠር ያለ ደዕዋ ካደረጉ በኋላ በጆሮ ግቡ ድምፃቸው ቁርኣን ቀርተዋል።

እውቁ ዓለም አቀፍ ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ሱፊ ከጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ጋር በተነጋገሩበት ጊዜ
በጠቅላይ ምክር ቤት ስር የሀገር አቀፉ የዑለማ ጉባዔ ምክትል ሰብሳቢና የፈትዋ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢው ዶክተር ጀይላን ኸድር፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ፣ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የትምህርትና ማኀበራዊ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር አብደላ ኸድር ታዋቂ ኸጢቦችና የዑለማ ጉባዔ አባላት ተገኝተዋል።

ቃሪዕ ሼይኽ አብዱረሺድ ዓሊ ሱፊ ኢትዮጵያዊ የዘር ግንድ ያላቸውና በአሥሩም የቁርኣን አቀራር ስልቶች እውቅና እና ኢጃዛ እንዳላቸው ይታወቃል።
***
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር |https://x.com/eiasc1
ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከሐምሌ 27 ቀን 2016 ዓ.ል. ጀምሮ ሲያካሂድ የቆየውን የ2016 ዓ.ል. ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ በዛሬው ዕለት አጠናቅቋል፡፡

ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለ13 ተከታታይ ቀናት ሲያካሂድ በቆየው በዚህ ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ፣ በበጀት ዓመቱ በምክር ቤቱ የተለያዩ ዳይሬክቶሬቶች እና የሥራ ክፍሎች የተከናወኑ ተግባራት በጥልቀት ተገምግመዋል፡፡

ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከሙስሊሙ ማኅበረሰብ የተሰጠውን ኃላፊነት የመወጣት አቅሙን ከጊዜ ወደ ጊዜ በማሳደግ፣ ተስፋ ሰጪ ውጤት ላይ መድረሱን የሥራ አስፈጻሚ አካሉ በግምገማው ለማረጋገጥ ችሏል፡፡

በዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ግምገማው (ተቅዪም) ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ልዩ ልዩ የሥራ ዘርፎች የ2016 የበጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቶች ቀርበው መጠነ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ የእያንዳንዱን የሥራ ዘርፍ ጠንካራ እና ደካማ ጎን በመለየት በአዲሱ የበጀት ዓመት ጠንካራ ጎኖችን ይበልጥ በማሳደግ፣ የታዩ ውስንነቶችን ለመቅረፍ የሚያስችል አቅጣጫ ተመላክቷል፡፡

የሥራ አስፈጻሚ አካሉ በጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ጽሕፈት ቤት በተከናወኑ የሀገር ዉስጥና የዉጪ ሀገራት የሥራ እንቅስቃሴዎች የተገኙ ውጤቶችን ጨምሮ፣ የሁሉንም ዳይሬክቶሬቶች እና ጽሕፈት ቤቶች የሥራ አፈጻጸም በጥልቀት ፈትሿል፡፡

በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የሁለተኛ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ፣ የ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶን የተመለከተ ዝርዝር ሪፖርት ቀርቦ ጥልቅ ውይይት ተደርጎበታል፡፡

በጠቅላይ ምክር ቤቱ ታሪክ 12 ሺህ ሐጃጆች የተስተናገዱበት የ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ አፈጻጸም ከቅድመ ዝግጅት ጀምሮ የሀገር ውስጥ የምዝገባ ሥርዓቱ መዘመን እና በሳዑዲ አረቢያ የነበረው መስተንግዶ ከፍተኛ መሻሻል የታየበት መሆኑ በግምገማው እንደ ጠንካራ ጎን ተጠቅሷል፡፡

በሚና የሐጃጆች ማረፊያ ድንኳኖች ላይ የተስተዋለው ችግር በቀጣይ እንዲሻሻል የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የአፈጻጸም አቅጣጫ አመላክቷል፡፡

በጠቅላይ ምክር ቤቱ የግማሽ ምዕተ ዓመት ታሪክ አገሪቱን እና ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን በሚያኮራ መልኩ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ በመሳተፍና ጥናታዊ ጽሑፎችን በማቅረብ ተቋሙ የራሱን አሻራ ያሳረፈበት፣ በዚህም ከምንጊዜውም የተሻለ የውጪ ግንኙነት ውጤት የተመዘገበበት ዓመት መኾኑን የሥራ አስፈጻሚ አካሉ አረጋግጧል፡፡

በተለይም የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በBRICS ሐገራት ጉባዔ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ በማቅረብ ጭምር ያደረጉት ተሳትፎ የሀገራችን መልካም ገጽታ እና የሕዝበ ሙስሊሙ ተቋም ስም ከፍ ያለበት መኾኑን በመጥቀስ፣ መሰል ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ውሳኔ ተላልፏል፡፡

ሙስሊሙን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ ከሚያደርጉ ፕሮጀክቶች መካከል በጠቅላይ ምክር ቤቱ በእቅድ የተያዘው የነጃሺ መስጂድ ግንባታ በአፋጣኝ ወደ ትግበራ ምዕራፍ እንዲገባ ውሳኔ ተላልፏል፡፡

የዑለሞች የአንድነትና የትብብር ሰነድን መሠረት በማድረግ የሙስሊሙን አንድነት በሚያረጋግጥ መልኩ በብሔራዊ ኮሚቴው የተከናወኑት ሥራዎች የሚያስመሠግኑ መኾናቸውን ያወሳው ይኸው የግምገማ መድረክ፣ መሰል የሙስሊሙን አንድነት የሚያጠናክሩ ሥራዎች የሚሠሩበት አቅጣጫ ተመላክቷል፡፡

ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከሌሎች ቤተ እምነቶች ጋር የጋራ የኾኑ የሰላምና የልማት ሥራዎችን ለመሥራት የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔን በመመሥረት እየተንቀሳቀሰ መሆኑ የተጠቀሰ ሲኾን፣ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በጉባዔው ውስጥ የሙስሊሙ ውክልናና ተሳትፎ ፍትኀዊነትን ጉዳይ የሚያጠና ኮሚቴ አዋቅሯል፡፡

ጠቅላይ ምክር ቤቱ የጀመራቸውን ሁሉን አቀፍ የሃይማኖትና የልማት ሥራዎች በቀጣይም በተቀናጀ መልኩ አጠናክሮ ተግባራዊ እንዲያደርግ፣ ውሱንነት በታየባቸው ዘርፎች ላይ ስር ነቀል የማስተካከያ ሥራዎች ከወዲሁ እንዲሠሩ አቅጣጫ በማስቀመጥ ግምገማውን በዛሬው ዕለት አጠናቅቋል፡፡

ነሐሤ 10 ቀን 2016 ዓ.ል. | ሰፈር 12፣ 1446 ዓ.ሒ.
አዲስ አበባ፡፡
ነሐሴ 11፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 13፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለክልል የእስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ም/ቤት አመራሮች የ1445 ዓ.ል. የሐጅ መስተንዶ ሪፖርት አቀረበ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ለክልል የእስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት አመራሮች የ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶ ሥራ ክንውን ሪፖርት አቀረበ።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በመሩት በዚሁ መድረክ ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢና የዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ በሪፖርታቸው በ1445 ዓ.ሒ. ሐጅ በአገር ውስጥ እና በውጪ ሀገር የተሠሩ ሥራዎችን በዝርዝር አቅርበዋል።

ኃላፊው በ1445ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶ ከቅድመ ዝግጅቱ እስከ አፈጻጸሙ መጠነኛ ችግሮች የታዩ ቢኾንም፣ ከቀደሙት ዓመታት አንጻር ከፍተኛ መሻሻል የታዩበት መኾኑን ተናግረዋል።

የሐጅና ዑምራ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢው ያቀረቡትን ሪፖርት ተከትሎ የክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ አመራሮች የተለያዩ ጥያቄዎችን እና በሐጅ ወቅት ያስተዋሏቸውን ክፍተቶችም አንስተዋል።

እንደ ክፍተት ከቀረቡ ነጥቦች መካከል፣ ሚና እና አረፋ ላይ የሕክምና አገልግሎት "የለም" በሚባል ደረጃ መኾኑ እና በሌላም በኩል ሑጃጁን ለማስተናበር የሚሄዱ አባላት ቁጥር እና ኮታ ለክልሎች ትኩረት የሰጠ አልነበረም የሚሉ ይገኙበታል።

በተጨማሪም፣ "ለሐጅ ሥርዓት መመሪያ አላችሁ ወይ?" እና "የተጋባዥ ሑጃጆች መረጣ መርኅን የተከተለ ነው ወይ?" የሚሉ ጥያቄዎችም ተነስተዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ኃላፊው ሸይኽ አብዱልዓዚዝ ለተነሱት ጥያቄዎች፣ በተለይም ትልቅ ብዥታ ታይቶባቸዋል ባሏቸው ጉዳዮች ላይ፣ ምላሽና ማብራሪያዎች ሰጥተዋል።

ኃላፊው ከሳዑዲ አረቢያ የሐጅ ሚኒስቴር በነፃ የሚሰጥ ኮታ እንደሌለ ጠቅሰው፣ በ100 ሑጃጅ ለአንድ አገልግሎት ሰጪ እንደሚፈቀድ ተናግረዋል።

በ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ ሥርዓት ለመፈፀም በጠቅላይ ምክር ቤቱ በኩል 12 ሺህ ሐጃጆች የተስተናገዱ ሲሆን፣ ይህን ተከትሎ 120 የሑጃጅ አገልግሎት ሰጪዎች ወደዚያው መሄዳቸውን ተናግረዋል።

ሚና ላይ የመኝታ ስፍራ ጥበትና የርቀት ችግሮች እንደነበሩ የጠቀሱት ኃላፊው፣ በወቅቱ ለሳዑዲ የሐጅ ሚኒስቴር ቀድመን ገንዘብ ለመክፈል ዶላር እስከምናገኝ እና የጠቅላላ ሑጃጁ ቁጥር ኮታ ባለመታወቁ፣ ቦታ ከሚያዝበት ዘግይተን በመክፈላችን ችግሩ የተፈጠረ መሆኑን አስረድተዋል።

መድረኩን የመሩት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ባለፈው የሐጅ መስተንግዶ በዶላር የምንዛሪ ተመን ከፍና ዝቅ ማለት፣ እንዲሁም እጥረት ሳቢያ ከሐጅ የቀረ ሰው ባይኖርም፣ የመስተንግዶ ሥራው ግን አድካሚና ከእንከን የሚጠራ አለመኾኑን ተናግረዋል።
•••••••••••
​የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር |https://x.com/eiasc1
ነሐሴ 11፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 13፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የሐጅ መስተንግዶ ሥራን 'ለግል ኤጀንሲዎች' ለማስተላለፍ የቀረበ ሐሳብ በከፍተኛ ድምጽ ውድቅ ተደረገ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሐጅና ዑምራ ዐብይ ኮሚቴ የ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶ ሥራ ክንውን ሪፖርት ባቀረበበት መድረክ፣ የሐጅ መስተንግዶ ሥራን 'ለግል ኤጀንሲዎች' ለማስተላለፍ የቀረበ ምክረ-ሐሳብ በከፍተኛ ድምጽ ውድቅ ተደረገ።

የሐጅ መስተንግዶ ሥራን 'ለግል ኤጀንሲዎች' በማስተላለፍ ላይ ያተኮረውን ምክረ-ሐሳብ ያቀረቡት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ፣ ምክረ ሐሳቡ ያሉትን አዎንታዊ እና አሉታዊ ገጽታዎች አብራርተዋል።

ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ የሐጅ መስተንግዶ ሥራ 'ለግል ኤጀንሲዎች" ቢተላለፍ የሚለውን ምክረ ሐሳብ አስመልክቶ ለክልል የእስልምና ጉዳይ ከፍተኛ አመራሮች ማብራሪያ ሰጥተዋል።

"የሐጅ መስተንግዶ ገቢ ከማስገኘት አኳያ ለተቋሙ የጀርባ አጥንት ቢሆንም፣ የጀርባ ውጋትም ነው" ያሉት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ በኃላፊነት ላይ ያለው መጅሊስ በተቻለው መጠን የሐጅ መስተንግዶን እያዘመነ መምጣቱን ጠቅሰዋል።

ምንም እንኳን በ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶ በዶላር የምንዛሪ ተመን ከፍና ዝቅ ማለት እንዲሁም እጥረት ሳቢያ ከሐጅ የቀረ ሰው ባይኖርም፣ የመስተንግዶ ሥራው ግን አድካሚና ከእንከን የሚጠራ አለመኾኑን ተናግረዋል።

"የሐጅ ሥራ ለግል ኤጀንሲዎች ቢስሰጥ የገንዘብ አቅም ስላላቸው ዶላር ፍለጋው ጭንቀት ውስጥ የሚከታቸው አይሆንም፤" ያሉት ፕሬዚደንቱ፣ ኤጀንሲዎቹ በሐጃጆች ተመራጭ ለመኾን በሚያደርጉት ውድድር ሑጃጁ የተሻለ መስተንግዶ ተጠቃሚ የሚኾንበት ሁኔታ እንደሚፈጠርም ተናግረዋል።

ፕሬዚደንቱ የመስተንግዶ ሥራውን የግል ኤጀንሲዎች ይሥሩት እንጂ፣ ጉዳዩ የሃይማኖት እንደመኾኑ ጠቅላይ ምክር ቤቱ አስፈላጊ ደንብና መመሪያዎችን በማውጣት ሥራቸውን በበላይነት የመቆጣጠር ኃላፊነት እንደሚኖረው ተናግረዋል።

የክልል የእስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት አመራሮች የሐጅ መስተንግዶ ሥራ ለግል ኤጀንሲዎች ቢፈቀድ በሚል በፕሬዚደንቱ የቀረበውን ምክረ ሐሳብ በከፍተኛ ድምጽ ተቃውመውታል።

የክልል የእስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት አመራሮቹ የሐጅ መስተንግዶ ሥራ እንደነበረው በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት አስተባባሪነት ማዕከላዊነቱን ጠብቆ ሊካሄድ ይገባዋል ብለዋል።

በዚህ የክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ አመራሮች ውይይት ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከሐምሌ 27 ቀን 2016 ዓ.ል. ጀምሮ ሲያካሂድ በቆየው የ2016 ዓ.ል. ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ሪፖርት በጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ጸሐፊ ሸይኽ ሀሚድ ሙሳ ቀርቧል።
****
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc
ነሐሴ 11፣ 2016 ዓ.ል | ሰፈር 13፣ 1446 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيم
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የክልል መጅሊስ አመራሮች በተገኙበት መድረክ ለትግራይ መጅሊስ የ7 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ተደረገ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ አስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሐጅና ዑምራ ዐብይ ኮሚቴ የ1445 ዓ.ሒ. የሐጅ መስተንግዶ ሥራ ክንውን ሪፖርት ባቀረበበት መድረክ፣ ለትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የ7 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ተደረገ።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ የትግራይ ክልል መጅሊስ ከአምስት ዓመታት በኋላ የፌደራል መጅሊሱ አካል ሆኖ የውይይቱ ተሳታፊ በመኾኑ ደስታቸውን ገልጸዋል።

የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ሸይኽ አደም አብዱልቃድር የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ከጠቅላይ ምክር ቤቱ ተነጥሎ የቆየው አሁን ያለው የመጅሊስ አመራር ከመመረጡ በፊት መሆኑን አስታውሰው፣ የለውጡ መጅሊስ የወንድሞቹን ችግር ተረድቶ "ሕብረታችን አንዲጠነክር" ላደረገው ጥረት አመሥግነዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ
"የትግራይ ክልል ከጦርነት እያገገመ የሚገኝና ብዙ ችግሮች ያሉበት መኾኑን በክልሉ ተገኝተን ያየነው በመሆኑ፣ የክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ አመራሮች የክልሉን ከፍተኛ ምክር ቤት ልናግዘው ይገባል" የሚል ሐሳብ አቅርበዋል።

ይህን ሐሳብ የክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ አመራሮቹ ተቀብለውት በዚያው ጊዜ በተደረገው የእገዛ እንቅስቃሴ፣ ከተለያዩ ክልሎች የትግራይ መጅሊስን ለመደገፍ የሚውል በድምሩ 7 ሚሊዮን ብር የሚደርስ መዋጮ ቃል ተገብቷል።

የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ሸይኽ አደም አብዱልቃድር፣ "የጠቅላይ ምክር ቤታችን ፕሬዚደንት እና የክልሎች የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት መሪዎች የኾናችሁ ወንድሞቻችን የትግራይ መጅሊስ ችግርን ለመቅረፍ ያደረጋችሁት መረባረብ ልባችንን የነካ ነው" ሲሉ በጥልቅ ስሜት ካመሠገኑ በኋላ፣ "ሀገራችንን ሰላም ያድርግልን፤ የተሻለ ነገን እናያለን" ብለዋል።

•••••••••••
​የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር |https://x.com/eiasc1