Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
8.9K subscribers
117 photos
1 video
18 files
141 links
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት
Download Telegram
ግንቦት 14፣ 2016 | ዙል ቂዳህ 14፣ 1445 ዓ.ሂ.
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
በሀገራዊ ምክክሩ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ ተገቢ ውክልና ሊያገኝና በንቃትም ሊሳተፍ ይገባል ተባለ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ሲዳማ |
በሀገራችን እንደሚካሄድ የሚጠበቀው ሀገራዊ ምክክር ሰላማዊ፣ አካታችና ፍሬያማ ይኾን ዘንድ፣ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ በአግባቡ ሊወከልና በንቃት ሊሳተፍ እንደሚገባ ተነገረ።

ይህ የተነገረው፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ከሲዳማ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ጋር በመተባበር በሀገራዊ ምክክርና በወቅታዊ የሰላም ጉዳይ ከክልሉ የሙስሊም ማኅበረሰብ ተወካዮች ጋር ዛሬ (ግንቦት 14) ባካሄደው የውይይት መድረክ ላይ ነው።

መድረኩ በሀገራችን እንደሚካሄድ የሚጠበቀው ሀገራዊ ምክክር ሰላማዊ፣ አካታችና ፍሬያማ ይኾን ዘንድ፣ ከሙስሊሙ ማኅበረሰብ በሚጠበቀው የነቃ ተሳትፎ ዙርያ ግንዛቤ በማስጨበጥ ዓላማ እንደተዘጋጀ ተነግሯል።

የውይይቱ ተሳታፊዎች በቀረበው አጀንዳ ዙርያ ባደረጉት ውይይት ሀገራዊ ምክክሩ ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም መሠረት በመኾኑ፣ የሙስሊሙ ማኅበረሰብ ድምጽ በአግባቡ ሊሰማበት እንደሚገባ አሳስበዋል።

ለዚህም የሀገሪቱ ሙስሊሞች በሀገራዊ የምክክር መድረኩ ላይ ተመጣጣኝ ውክልናና የተሳትፎ ዕድል ሊያገኙ እንደሚገባ የመድረኩ ተሳታፊዎች በአጽንዖት ተናግረዋል።

የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ የምክክር መድረኮች በሙሉ አካታችና የተለያዩ የሀገሪቱ ማኅበረሰቦች በአግባቡ የሚወከሉበት መኾኑን የማረጋገጥ ኃላፊነት እንዳለበት ተጠቅሷል።

የውይይት መድረኩ ተሳታፊዎች በዚህ ሐሳብ ላይ የጋራ መግበባት ላይ በመድረስ መድረኩ በስኬት ተጠናቅቋል።

በሐዋሳ ከተማ ፓራዳይስ ሆቴል አዳራሽ በተካሄደው በዚህ የውይይት መድረክ ላይ ከክልሉ ሁሉም ዞኖችና ወረዳዎች የእስልምና ጉዳይ ምክር ቤት ሥራ አስፈጻሚዎችና አባላት፣ የዑለማ ምክር ቤት አባላት፣ የመስጂድ ኢማሞች፣ ዱዓቶች፣ የማኅበረሰብ ተወካዮች፣ የወጣቶችና የሴቶች ተወካዮች ተሳትፈውበታል።

​••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 15፣ 2016 | ዙል ቂዳህ 15፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
520 የአሏህ እንግዶች መስጂደል ነበዊ በሚገኘው የረዉዷ ሸሪፍ ዚያራ አደረጉ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መዲና |

ከቀናት በፊት ወደ መዲነተል ሙነወራ ከተጓዙት የ1445 ዓ.ሒ የአሏህ እንግዶች 520 የሚኾኑት በመስጂደል ነበዊ የሚገኘውን ረውዷ ሸሪፍ በመዘየር ዱዓ አደረጉ።

የሐጃጆቹ የረውዷ ሸሪፍ ዚያራ መዲና በሚገኘው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሑጃጅ መስተንግዶ ቡድን አማካኝነት በተያዘ መርኃግብር አማካይነት እንደተካሄደ ለማወቅ ተችሏል።

በተከበረው ረውዳ ውስጥ ሶላት መስገድ የሚያስገኘውን ከፍተኛ አጅር (ምንዳ) ለማግኘት ከመላው ዓለም የሚመጡ ምዕመናን ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ በመጨመሩ አስቀድሞ በ"ኑሱክ" መተግበሪያ ማመልከትና ፍቃድ ማግኘት እንደሚያስፈልግ መዲና የሚገኘው የመስተንግዶው አስተባባሪ ሙጃሒድ አብዱልጀሊል ነግረውናል።

የ1445 ዓ.ሒ ሐጃጆች ይህን የጉብኝት ዕድል እንዲያገኙ የመስተንግዶ ቡድኑ ቀጠሮ የማስያዝ ሥራ እየሠራ በመሆኑ በቀጣዮቹ ቀናት መዲና የሚገቡ የአሏህ እንግዶች በሚያዝላቸው ቀጠሮ ተጠቃሚ እንዲኾኑ አስተባባሪው አሳስበዋል።

•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 17፣ 2016 | ዙል ቃይዳ 17፣ 1445 ዓ.ሂ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለእስላማዊ የሚዲያ ባለሙያዎችና የማኅበረሰብ አንቂዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና ሰጠ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
እስላማዊ የሚዲያ ባለሙያዎችና የማኅበረሰብ አንቂዎችን በየጊዜው አቅማቸውን የሚያሳድግ ሙያዊ ሥልጠና ተጠቃሚ በማድረግ የተወዳዳሪነታቸውን አቅም ማሳደግ እንደሚገባ ተነገረ።

ይህ የተነገረው ዛሬ በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ለእስላማዊ የሚዲያ ባለሙያዎችና የማኅበረሰብ አንቂዎች በተሰጠው የአቅም ግንባታ ሥልጠና ላይ ነው።

"የሚዲያ አጀንዳ ከመቅረፅ እስከ ማስፈፀም" በሚል ርዕስ ከእስላማዊ የሚዲያ ተቋማት ለተውጣጡ ባለሙያዎችና ማኅበራዊ አንቂዎች በዑስታዝ አህመዲን ጀበል የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተሰጥቷል።

ሚዲያን ተጠቅሞ የማኅበረሰብ ችግሮችን በመፍታት ሂደትና ሚዲያን በአግባቡ መጠቀም በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ሥልጠናው አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል ተብሎ ይጠበቃል።

በሚዲያ አጀንዳ ቀረፃ፣ ምንነት፣ ስልቶቹና የማሰራጫ ስትራቴጂዎች ላይ ያተኮረው ይህ ሥልጠና በቀጣይም ለሚዲያ ባለሙያዎችና ለማኅበራዊ አንቂዎች እንደሚሰጥ ተነግሯል።

ለአንድ ቀን በተካሄደው በዚህ ሥልጠና ላይ ከሠልጣኞች ለተነሱ ጥያቄዎች በዑስታዝ አህመዲን ጀበል ምላሽ ተሰጥቶበታል።
​•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 17፣ 2016 ዓ.ል | ዙል ቂዳህ 17፣ 1445 ዓ.ሂ.
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የአሏህ እንግዶችን ተቀብለው ወደ መካ የሚሸኙ የመዲና ሠራተኞች የሥራ ግምገማ አደረጉ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መዲና የሚገኙ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ሥራ አስፈጻሚዎች ለአሏህ እንግዶች በሚያደርጉት መስተንግዶና ወደ መካ በሚያደርጉት አሸኛኘት ዙሪያ ግምገማ አደረጉ።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ምክትል ተጠሪና የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የኾኑት ሸይኽ አብዱልሃሚድ አሕመድ እንዳሉት የሐጅ ሥርዓትን ለመፈፀም ተገቢውን መስፈርት አሟልተው የጉዞ ተራ የሚጠብቁ ሐጃጆች በሙሉ በመዲነቱል ሙነወራ ለቀናት ያህል ይቆያሉ።

ሐጃጆች የአሏህ እንግዶች በመኾናቸው፣ 'የአላህን እንግዳ' ቀልብ መጠበቅ፣ ማስደሰት አላህ ዘንድ ያለው ደረጃ ከፍተኛ መኾኑን አስታውሰዋል።

ከምናስተናግደው እንግዳ ትልቅነት አኳያ በዚህ በተቀደሰ ስፍራ ለሐጃጆች የምንሰጠውን አገልግሎት በተደጋጋሚ መገምገምና ለታዩ ክፍተቶች መፍትኄ መፈለግ እንደሚገባ አሳስበዋል።

"እስካሁን ድረስ በመዲነቱል ሙነወራ ለቀናት ያህል የቆዩትን እንግዶች ውጤታማ በሚባል ደረጃ አስተናግደናል፤ አልሃምዱሊላህ" ብለዋል።

የመዲና ቆይታቸውን ጨርሰው ወደ መካ የተሸኙ የአላህ ባሮች በጥቅሉ ከሁለት ሺህ ያነሱ ሲኾን፣ ገና ከአሥር ሺህ ያላነሱ የአላህ እንግዶች መስተንግዶ እንደሚጠበቅ ጠቅሰው፣ ሠራተኛውም በየዘርፉ ያለውን ሥራ ገምግሞ ክፍተቶችን እና መፍትኄያቸውን የሚጠቁምበት የውይይት መድረክ ከፍተዋል።

ከመጅሊሱ ሠራተኞች ጋር በጥምረት እንዲሠሩ የመዲና ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ሌሎች የሀገሩ ነዋሪ ሠራተኞችን በዋነኝነት የሚያሥተባብረው አብዱልሞይን፣ በስሩ ያሉት የዩንቨርሲቲ ተማሪዎች የአሏህ እንግዶችን ተቀብሎ ተገቢውን ግልጋሎት ከመስጠት አኳያ ማሻሻል የሚገባቸውን ለማሻሻል ዝግጅቱም ብቃቱም እንዳላቸው ተናግረዋል።

ጠቅላይ ምክር ቤቱ ሐጃጆች ከአገር ከወጡ በኋላ የሚገጥማቸውን የስልክ ግንኙነት ችግር ለመቅረፍ ከሠራው ሥራ የስልክ ግንኙነት 'ሮሚንግ' መሥራቱ ትልቅ መኾኑን ጠቅሰው፣ ይሁን እንጂ ሐጃጆች በተመዘገቡበት ሲም ካርድ በያዙት ስልክ መደወል እንደሚችሉ ባለማወቅ እዚህ ከደረሱ በኋላ፣ እንደቀዳሚዎቹ ዓመታት ሲም ካርድ ለመግዛት ሲጨናነቁና ለወጪ ሲዳረጉ ይታያል ብለዋል።

የአሏህ እንግዶች የሐጅ ምዝገባ ሲያካሂዱ ያስመዘገቡትን ስልክ ከያዙ፣ ከመዲናም ሆነ መካ ነጻ የስልክ ግንኙነት እንዲያደርጉ ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከኢትዮቴሌኮም ጋር ውል ተፈራርሞ ተግባራዊ መኾኑን ተናግረዋል።

ሐጃጆች መዲና ሲገቡ ሲም ካርድ ከመግዛት ይልቅ የመጅሊሱ ባለሙያዎች ስልካቸዉን እያስተካካሉላቸው መሆኑን ጠቅሰው፣ የ315 ያህሉ የስልክ ቁጥር ለሐጅ ሲመዘገቡ ያላስመዘገቡት ሆኖ በመገኘቱ ወደ ኢትዮጵያ ተልኮ እንዲስተካከል እየተጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ የIT ባለሙያዎች ችግሩን ለመቅረፍና ፍጥነቱን ለመጨመር በጎ ፈቃደኞችን እያሠለጠኑ ሐጃጆችን በያዙት ስልክ ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ እየሠሩ መኾኑንም ተናግረዋል።

በሥራ ግምገማው ላይ በዋነኝነት ከተጠቀሱ ችግሮች ውስጥ በሳዑዲ አየር መንገድም ሆነ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ መዲና የሚገቡ ሐጃጆች አቀባበል ላይ በአንድ ቡድን 45 ሰዎች በአንድ አሚር እንዲስተባበሩ የተደረገው ድልድል ለሀገራችን ሐጃጆች አዲስ ቢሆንም፣ ለአሠራር ምቹ ሆኖ ታይቷል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድም በሚሰጠው አገልግሎት ትልልቅ ችግሮችን እየፈታ መሆኑን እንደ ጠንካራ ጎን ተጠቅሷል።

ሐጃጆች መዲና ደርሰው የአልጋ ድልድል ላይ የአልጋ እጥረት የሌለ ቢሆንም፣ በመጡበት ፍጥነት አልጋ ለመደልደል የሰው ኃይል እጥረት እንደ ዋና ችግር ተጠቅሷል።

በዚህ ረገድ ያለውን የሰው ኃይል በተገቢው መንገድ አለመጠቀምም ሌላው ችግር መሆኑ ተጠቅሶ፣ የመዲና ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ከተቋሙ ሡራተኞች ጋር በመናበብ መፍትኄ እንዲሰጡ አቅጣጫ ተጠቁሟል።

ምግብና የጽዳት ሁኔታም በግምገማው ላይ የተነሳ ሲኾን፣ የምግብ እጥረት ባይኖርም ሴቶች በምግብ ሰዓት እንዳይሰለፋ ወይም ለብቻቸውን የሚስተናገዱበት ሁኔታ ለማመቻቸት አቅጣጫ ተሰጥቷል።

የረውዷ ጉብኝትን በተመለከተ በሐጃጆች በኩል በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ ያለመጠቀም ችግር እንደሚታይ ተጠቅሷል። ይህን ክፍተት ለመሙላት በዋነኝነት የጠቅላይ ምክር ቤቱ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሸይኽ ዛኪር ኢብራሂም እና ሸይኽ አብዱልሃሚድ አሕመድ የሰው እጥረት ሲገጥም ሌሊቱን ሊያስጎበኙ ኃላፈነት ወስደዋል።

በሴቶች በኩል ትልቅ ጫና ያለ ቢኾንም፣ ወ/ሮ ኢንትሳር አየለ የቅድመ ጥንቃቄ ማብራሪያ ከመስጠት ጋር በቦታው ከተመደበችው የጠቅላይ ምክር ቤቱ እህት ጋር ጫናውን እየተወጡ መኾኑን ሸይኽ አብዱልሃሚድ ተናግረዋል።

በ1445 ዓ.ሂ. የሐጅ ሥራ ላይ የተሰባሰብን "የጠቅላይ ምክር ቤቱ ሠራተኞችም ኾናችሁ በቅጥርና በበጎ ፈቃድ ለማገልገል የተገኛችሁ ወንድም እህቶቾ እዚህ ያሰባሰበን የአላህን ባሮች የአላህ እንግዶች ሆነው በመምጣታቸው እነርሱን ለማገልገል መሆኑ ትልቅ አማና ነው። ስለዚህም በግልም ሆነ በጋራ ኃላፊነታችንን እንወጣ" ሲሉ አሳስበዋል።

​•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 17፣ 2016 | ዙል ቃይዳ 17፣ 1445 ዓ.ሂ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
በወራቤ ከተማ ለሐጅ ተጓዦች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጠ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ወራቤ |

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ከክልሉ ሰባት ዞኖች እና ሦስት ልዩ ወረዳዎች ለተወጣጡ የሐጅ ተጓዦች በዛሬው ዕለት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ሰጠ።

ሥልጠናውን የሰጡት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፀሐፊ ሸይኽ ሳዲቅ ወጌቦ ናቸው።

በሥልጠናው ላይ ከሐጃጆች የተለያዩ ጥያቄዎች የተነሱ ሲኾን፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልወሃብ ሸይኽ በድረዲንና ሸይኽ ሳዲቅ ወጌቦ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ዘንድሮ ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከ500 በላይ ሐጃጆች ወደ ሁለቱ ቅዱሳን ከተሞች እንደሚጓዙ ሸይኽ ሳዲቅ ወጌቦ ተናግረዋል።

መስተንግዶን በተመለከተ የዘንድሮ ሐጅ ከቀዳሚዎቹ ዓመታት ለየት ያለ፣ ቀልጣፋና ሁሉም አገልግሎቶች በአንድ ማዕከል የተሰጡበት በመኾኑ ከእንግልት መዳናቸውን ሐጃጆች ነግረውናል።

ስለሐጅ አተገባበር በስልጤ ዞን ከፍተኛ ሸሪዓ ፍርድ ቤት ቃዲ ሸይኽ ሙስጠፋ ጀማል ሰፋ ያለ ማብራሪያ ተሰጥቷል።

ፓስፖርት፣ ቲኬት፣ ቪዛና የቢጫ ወባ ክትባት እዚያው ወራቤ ውስጥ እንደተሰጣቸው የተናገሩት ሐጃጆቹ ለዚህም የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤትን አመስግነዋል።

የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻው እና የክትባት መርኃ ግብሩ የተሳካ እንዲኾን በኡስታዝ ኻሊድ ሙሐመድ እና በወጣት ጀማል ጎችባሮ የተመራው የወራቤ ከተማ ወጣቶች ጥረት የላቀ ሚና እንደነበረው ተነግሯል።

የሐጃጆችን ሽኝትና የቢጫ ወባ ክትባት መርኃ ግብሩን ያስጀመሩት የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ዓሊ ከዲር ሲሆኑ፣ ሐጃጆች በተቀደሰው ሀገር ለሀገራችን ሰላም እና ልማት ዱዓ እንዲያደርጉ አደራ ብለዋል።

በዚሁ ጊዜ የስልጤ ዞንና የወራቤ ከተማ አሥተዳደር ለሐጃጆች መስተንግዶ፣ የስልጤ ባህላዊ እስካርቭና ኮፊያ ሥጦታ አበርክቷል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የስልጤ ዞንና የወራቤ ከተማ አስተዳደርን በ1445 ዓ.ሂ. ሐጃጆችና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ም/ቤት ስም ያመሰግናል።

•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 18፣ 2016 | ዙል ቃይዳ 18፣ 1445 ዓ.ሂ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
"የሀገር አንድነት የሚፀናው ሰላም ሲኖር በመኾኑ ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም የበኩላችንን አስተዋፅዖ ማበርከት ይጠበቅብናል።"
• የክብር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ኮምቦልቻ |

"የሀገር አንድነት የሚፀናው ሰላም ሲኖር በመኾኑ፣ ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም የበኩላችንን አስተዋፅዖ ማበርከት ይጠበቅብናል" ሲሉ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ተናገሩ።

ፕሬዚደንቱ የክብር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ይህን የተናገሩት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ከአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ጋር በመተባበር በኮምቦልቻ ከተማ ባካሄደው ሀገር አቀፍ የአብሮነትና የወንድማማችነት ጉባዔ ላይ ነው።

"አንድነት ማለት አንድ ዓይነትነት አይደለም" ያሉት ፕሬዚደንቱ፣ ሁሉም ባሉት ልዩነቶች ተቻችሎ፣ አንድ በሚያደርጉት ጉዳዮች ላይ ደግሞ ተከባብሮ መሥራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል ።

በሰዎች መካከል የአስተሳሰብ ልዩነቶች መኖራቸው ተፈጥሯዊ እንደኾነ የጠቀሱት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ልዩነቶችን ለማጥበብ ተመራጩ መንገድ በጠረጴዛ ዙሪያ የሰከነ ውይይት ማድረግ ነው ብለዋል።

ሁሉም ሰው ባህሉንና እምነቱን ጠብቆ፣ እምቅ አቅሙን በማስተባበር ለጋራ ሀገሩ ዕድገትና ዘለቄታዊ ሰላም የበኩሉን አስተዋጽዖ ማበርከት እንደሚጠበቅበት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም አሳስበዋል።

የእስላማዊ ወንድማማችነት መሠረቱ ላኢላሃኢለልላህ መኾኑን የተናገሩት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ እስላማዊ አንድነቱን በዚህ የሃይማኖትና የእምነት መሠረት ላይ መገንባትና ማጠናከር ይገባዋል ብለዋል።

ከዓመታት በፊት ጀምሮ በአማራ ክልል የሚገኙ ሐሪማዎችን ለመጎብኘት እቅድ እንደነበራቸው የተናገሩት ሼይኽ ሐጂ፣ በአካባቢው ባለው ወቅታዊ የሰላም ችግር ሳቢያ ሊያደርጉ ያሰቡት ለጊዜው አለመሳካቱን ተናግረዋል።

በዛሬው ዕለት በኮምቦልቻ ከተማ በሰደቃ፣ በፓናል ውይይትና በተለያዩ ዝግጅቶች ረፋዱ ላይ በጀመረው የአብሮነት፣ የወንድማማችነት እና የሰላም ጉባዔ ላይ የአዲስ አበባና የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤቶች ፕሬዚዳንቶች፣ ዓሊሞች፣ ዱዓቶች፣ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የከተማው ማኅበረሰብ አባላት ተገኝተዋል።

ክቡር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በዚሁ ዕለት
በቀጣይ ጊዜያት በኮምቦልቻ ከተማ ለሚገነቡ አዳዲስ ፕሮጆክቶች የመሠረት ድንጋይ አኑረዋል።

በክቡር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ የተመራዉ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የልዑካን ቡድን ዛሬ ጠዋት ኮምቦልቻ ከተማ ሲደርስ ደማቅ አቀባበል ተደርጎለታል።

•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 18፣ 2016 ዓ.ል | ዙል ቂዳህ 18፣ 1445 ዓ.ሂ.
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ሐጃጆች በኢትዮ ቴሌኮም ሲም ካርድ ከመካ እና ከመዲና ወደ ሀገር ቤት ስልክ መደወል በመቻላቸው መደሰታቸውን ተናገሩ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መዲና |

የ1445 ዓ.ሒ. የአሏህ እንግዶች በሐጅ ምዝገባ ወቅት ያስመዘገቡትን የኢትዮ ቴሌኮም ሲም ካርድ በመጠቀም ከመዲና እና ከመካ ወደ ቤተሰቦቻቸው ስልክ ደውለው በሰላም መግባታቸውን መግለጽ በመቻላቸው መደሰታቸውን ተናገሩ።

በሐጅ ጉዞ ላይ ውጣ ውረድና ልፋት መኖሩ የኢባዳ አካል ቢኾንም፣ ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለዘንድሮ የአሏህ እንግዶች ተገቢ አገልግሎት በመስጠት ከኢባዳቸው እንዳይዘናጉ ማድረግ በመቻሉ መደሰታቸውን ሐጃጆች ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት አገልግሎቱን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያዘመነ በመሄድ፣ የዘንድሮ የአሏህ እንግዶች የኢትዮ ቴሌኮም ሲም ካርዳቸውን በሳዑዲ ሲምካርድ መቀየር ሳያስፈልጋቸው፣ የሮሚንግ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን መዲና የተገኙት የመጅሊሱ የIT ክፍል ባልደረባ አቶ ጀማል ኢብራሂም ተናግረዋል።

ባለሙያው አያይዘው እንደጠቀሱት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ለ1445 ዓ.ሒ. ሐጃጆች ብዙ ጠቃሚ አሠራሮችን ሥራ ላይ እያዋለ ይገኛል።

ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በተስማማው መሠረት የ1445 ዓ.ሒ ሐጃጆች የሐጅ ምዝገባ ሲያካሂዱ ያስመዘገቡት ስልክ ቁጥር በሮሚንግ አገልግሎት የተመዘገበ በመሆኑ፣ ሲም ካርዳቸውን ይዘውት በመጓዝ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መኾን እንደሚችሉ አቶ ጀማል ተናግረዋል።

ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በተገባው ውል መሠረት የሮሚንግ አገልግሎቱ ተጠቃሚዎች፣ 150 ደቂቃ የድምጽ እና 500 ሜጋ ባይት ፓኬጅ መጠቀም እንደሚችሉ አቶ ጀማል ተናግረዋል።

ብዙ ሐጃጆች ከመነሻው ቴሌብር ላይ ያለውን የሐጅ ፓኬጅ ገዝተው በመምጣት ስህተት እየሠሩ እንደሚገኙ የጠቆሙት አቶ ጀማል፣ ይህን መጠቀም የሚችሉት ነባር የሮሚንግ አገልግሎት ተጠቃሚ ሐጃጆች ብቻ መኾናቸውን ተናግረዋል።

የሮሚንግ አገልግሎት ተጠቃሚ ያልነበሩ ሐጃጆች፣ በሐጅ ምዝገባ ወቅት ያስመዘገቡት ቁጥር ያለበትን ሲም ካርድ ይዘው በመምጣት የፓኬጁ ተጠቃሚ እንደሚኾኑ ተናግረዋል።

በሐጅ ቆይታቸው በእርሱ ሲጠቀሙ ቆይተው የተሰጣቸው ፓኬጅ ሲያልቅ፣ ቴሌብር ላይ ያለውን የሐጅ ፓኬጅ የሚጠቀሙበት መንገድ እንደሚመቻች አቶ ጀማል ተናግረዋል።

ወደ መዲና ለመሳፈር ተራቸውን በመጠበቅ ላይ የሚገኙ የአሏህ እንግዶች፣ ለሐጅ ሲመዘገቡ ያስመዘገቡት ስልክ ቁጥር ያለበትን ሲም ካርድ ይዘው እንዲሳፈሩ አቶ ጀማል በአጽንዖት አሳስበዋል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር ሐጃጆችን የሮሚንግ አገልግሎት ተጠቃሚ ያደረገው፣ አገልግሎቱን ከማዘመን ባሻገር ለራሳቸው ደኅንነት ሲል መኾኑንም ተናግረዋል።

የሮሚንግ (Roaming) አገልግሎት፣ በሐጅ ወቅት ብቻ ሳይኾን፣ በማንኛውም ጊዜ ከሀገር የሚወጡ ሰዎች ከየትኛውም የዓለም ሀገር ኾነው በሀገር ቤት ሲም ካርዳቸው መጠቀም የሚያስችል አገልግሎት ነው።

​•••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 19፣ 2016 ዓ.ል | ዙል ቂዳህ 19፣ 1445 ዓ.ሂ.
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አስደሳች ዜና ለ1445 ዓ.ሒ የአሏህ እንግዶች!
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ከኢትዮ-ቴሌኮም ጋር በገባው ውል መሠረት፣ የ1445 ዓ.ሒ የአሏህ እንግዶች፣ ሀገር ውስጥ በሚጠቀሙበትና በሐጅ ምዝገባ ወቅት ባስመዘገቡት ሲም ካርዳቸው ከሳዑዲ አረቢያ (ከመዲናም ኾነ ከመካ) በሀገር ቤት ከሚገኙ ወዳጅ ቤተሰቦቻቸው ጋር በሮሚንግ አገልግሎት መገናኘት የሚችሉ መኾኑን ያበስራል።

ለዚህ አገልግሎት እያንዳንዱ ሐጃጅ የ150 ደቂቃ የድምፅ እና የ500 ሜጋ ባይት ፓኬጅ ተጠቃሚ እንዲኾን መደረጉን ሲያስታውስ ደስታ ይሰማዋል።

ስለሆነም፣ ሐጃጆች በሐጅ ምዝገባ ወቅት ያስመዘገቡት ስልክ ቁጥርዎ በሚገኝበት ሲም ካርድ ከሳዑዲ ደውለው፣ ሀገር ቤት ከሚገኙ ቤተሰብዎና ወዳጅ ዘመዶችዎ ጋር ይገናኙ።

ሐጅ መብሩር!

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
Uduu Gammachiisa!!

Hujaajoota Hajji bara 1445 hundaaf
Manni Maree Dhimoota
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
Islaammumaa Etiyoophia waligalaa walligaltee Etiiyoo Teleekoomi wallin godheen hujaajoonni hajji bara Hijraa 1445 kessumma rahmaan ta'uun gara Sa'uudiitti imalan hundinuu Sa'uudii taa'ani maatiii isaanii waliin akka kaffaltti dabalataa tokko malee walqunamuu kan isaan dandeessisu paakeeji sagalee daqiiqa 150 fi pakeeji roomingii meegaa baytii 500 tti akka fayyadaman carraa ummun kennan gammachuttu nutti dhagayama.

Kanaafuu hujaajnii kammuu lakkofssa bilbilaa yokan Simkaardii etiyoo teleekomii hajji baraa hijraa 1445 galmeessisetti fayyadammun Saudi Arabiyaa irraa maatii isaatiin walqunnamtti akka godhuu danda'uu isin hubachiisna.

Manni Maree Dhimoota
Islaammumaa Etiyoophia waligalaa
ግንቦት 22፣ 2016 | ዙል ቂዳህ 22፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የ1445ዓ.ሒ የሐጃጆች የሕክምና አገልግሎት አሰጣጥ ስኬት የቡድን ሥራው መጠናከር መኾኑ ተነገረ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መካ |

የአሏህ እንግዶች ለሚገጥማቸው የጤና እክል የቅርብ ክትትል ለማድረግ ከዘንድሮ ሐጃጆች ጋር የተጓዘው የሕክምና ቡድን ባደረገው የጋራ ውይይት የሕክምና አገልግሎቱ ስኬታማ እና ውጤቱ ያማረ የሚሆነው ቅንነትና የቡድን ሥራው ሲጠናከር መኾኑን ተናገረ።

የሐጃጆች የሕክምና አገልግሎት ለመስጠት አስቀድሞ የተጓዘው ቡድን በሕክምናው ዘርፍ በተለያዩ ተጓዳኝ ሙያዎች ልምድ ያካበቱ ባለሙያዎችን ያካተተና ቅንጅት ያለው መሆኑን የሕክምና ቡድኑ መሪ ዶክተር አሚን ሙሐመድ ተናግረዋል።

የሕክምና ቡድኑ ከአገር ቤት ጀምሮ የጋራ ሥልጠና የወሰደና የቡድን መንፈስ ያዳበረ በመኾኑ፣ የእርስ በርስ መግባባቱ ሥራውን በኃላፊነት እንዲወጣ መልካም መደላድል እንደፈጠረለት ዶክተር አሚን ነግረውናል።

የቡድኑ ባልደረባ የኾኑት ዶ/ር ሙሐመድ ሳኒ ቲጃኒ በበኩላቸው፣ ምንም እንኳ የሥራ ውሉ ሕክምናን ብቻ የሚመለከት ቢኾንም፣ የቡድኑ አባላት ክፍሉን ለማደራጀት የመድኃኒቶች ካርቶን እየተሸከሙ ጭምር ሑጃጁን ዝቅ ብለው ለማስተናገድ ጥረት እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

የሕክምና ቡድኑ አደረጃጀት ለታማሚው ፈጣን ምላሽና ትኩረት ለመስጠት የሚያስችል መኾኑን የጠቀሱት ዶ/ር አሚን፣ ቡድኑ ከ20 ያላነሱ ባለሙያዎች የተካተቱበት መሆኑን ተናግረዋል።

ጠቅላይ ምክር ቤቱ የ1445 ዓ.ሒ የአሏህ እንግዶች የሐጅ ጉዞ የተሳካ እንዲኾን ለሐጃጆች የሕክምና አገልግሎት ሥራዎችን ለማደራጀት ቀድሞ በመጓዝ ሥራ መጀመሩን ዶ/ር አሚን ጠቅሰዋል።

የሕክምና ቡድኑ በአፍሪካ ከደቡብ አፍሪካ እና ከናይጀሪያ ቀጥሎ በሦስተኛ ደረጃ የሕክምና ጣቢያውን ያደራጀ ሲኾን፣ በቅርቡ ለሁለት ደረጃቸውን የጠበቁ ክሊኒኮች ፈቃድ መሰጠቱንም ዶ/ር አሚን አስታውሰዋል።

•••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | twitter.com/eiasc
ግንቦት 22፣ 2016 ዓ.ል. | ዙል ቂዳህ 22፣ 1445 ዓ.ሒ.
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
''ኑስክ" የተሰኘው የሐጃጆች ልዩ መታወቂያ ለሐጃጆች እየታደለ ነው።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መካ |

የሳዑዲ አረቢያ የሐጅ ሚኒስቴር ሐጅ ለማድረግ የሐጅ ቪዛ መያዝን ግዴታ ማድረጉን ተከትሎ፣ በሕጋዊ የሐጅ ቪዛ ለተጓዙ ሐጃጆች 'ኑስክ' የተባለ ልዩ የመታወቂያ ካርድ ማደል ጀመረ።

'ኑሱክ' የተባለው ልዩ መታወቂያ ካርድ የሕጋዊ ሐጃጅነት ማረጋገጫ በመኾኑ፣ በጠቅላይ ምክር ቤቱ በኩል ሕጋዊ ሂደቱን ተከትለው ለተጓዙ ኢትዮጵያውያን ሐጃጆች የሚኒስቴሩ ሠራተኞች ማረፊያቸው ድረስ በመምጣት እየሰጧቸው መኾኑ ታውቋል።

ሕጋዊነትን ለማረጋገጥ 'ኑሱክ' የተባለውን ልዩ መታወቂያ ካርድ መያዝ ግዴታ መኾኑን ሚኒስቴሩ ያሳወቀ ሲኾን፣ ከዞን ሁለት ጀምሮ መዲና ለሚገቡ የአሏህ እንግዶች አዉቶብስ ላይ እያሉ መታወቂያው እንደሚታደላቸው የጠቅላይ ምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪው ሸይኽ አብዱልአዚዝ ሸይኽ አብዱልዋሊ ተናግረዋል።

በመካ የኢትዮጵያ የሐጅ ጉዳይ ዋና ኃላፊ
የኾኑት ሸይኽ አብዱልአዚዝ የሐጃጆች ልዩ መታወቂያ በሳዑዲ የሐጅ ሚኒስቴር ታትሞ በጽሕፈት ቤታቸው አማካይነት ለሕጋዊ ሑጃጆች የሚታደል በመኾኑ፣ የምክር ቤቱ የሐጅ ክፍል አብሮ ከሚኒስቴሩ ጋር እየሠራ መኾኑን ተናግረዋል።

'ኑሱክ' ልዩ የሐጃጆች መታወቂያ ሥራ ላይ መዋሉ፣ ሚና እና አረፋ ላይ ሕጋዊ ባልኾኑ ሐጃጆች ሳቢያ የሚፈጠርን የመጨናነቅ ጫና ለመቀነስ ታስቦ እንደተዘጋጀ ከሚኒስቴሩ ለመረዳት መቻላቸውን ሸይኽ አብዱልአዚዝ ተናግረዋል።

"ወንድሞቻችን በቴክኖሎጂ ሲስተም ላይ ባደረጉት ጥረት፣ በሐጅ ዙሪያ የነበሩ በርካታ ችግሮች እየተፈቱ መሆኑን የጠቀሱት ሸይኽ አብዱልአዚዝ፣ መካ ላይ ያለው የዞን ድልድል መነሻ ለሚናና ለአረፋ በጣም የሚረዳ ትልቅ ሥራ መሆኑን ተናግረዋል።

የዞን አንድ ሐጃጆች ገብተው እየተጠናቀቁ በመኾኑ፣ ከሁለት ቀናት ባነሰ ጊዜ ውስጥ የዞን ሁለት ሐጃጆች መግባት እንደሚጀምሩ የጠቀሱት ሸይኽ አብዱልአዚዝ፣ በቀጣዮቹ ሁለት ሳምንታት ሁሉም ሐጃጆች ተጠቃልለው ወደ ማረፊያቸው ይገባሉ ብለዋል።

ሸይኽ አብዱልአዚዝ፣ የሳዑዲ የሐጅ ሚኒስቴር የሐጅ ቪዛ ያልያዙ ሰዎች በሐጅ መከወኛ ቦታዎች እንዳይንቀሳቀሱ ስለሚያደርግ፣ በሚና አካባቢ ሊደርስ የሚችለውን ጫና የሰው ኃይላችንን በማቀናጀት በቀለጠፈ መንገድ መልክ እናስይዘዋለን ብለዋል።

"ይህን በማድረግም፣ በአላህ ፈቃድ፣ ''የዘመነ አገልግሎት ለአልረህማን እንግዶች" የሚለውን መሪ ቃላችንን ተግባራዊ እንደምናደርግ ተስፋ አለን" ብለዋል።
​•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 24፣2016 ዓ.ል ዙል ቃዒዳ 24፣1445 ዓ.ሒ

بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ                             

"በአለም አቀፍ ደረጃ የኢትዮጵያ ስም ላስጠሩ ሀፊዞች የ1445 የሐጅ ቪዛ ስጦታ በጠቅላይ ምክር ቤቱ ስም ሳበረክት ደስታ ይሰማኛል"

የክቡር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም

አዲስ አበባ (ግንቦት 24፣2016 ዓ.ል)
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕረዚዳንት የክቡር ዶክተር ሼይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ ሀገራችን ኢትዮጵያን ወክለው በሊቢያ በተደረገው አለም አቀፍ የቁርአን ውድድር ላይ ከፍተኛ ዉጤት ላስመዘገቡ ሁለት ወጣቶች የ1445 ዓ.ሒ የሐጅ ቪዛ ፤ በተጨማሪም ለሁለቱ ተወዳዳሪዎች ና ለዘይድ ኢብን ሳቢት የቁርአን ማህበር የምስክር ወረቀት አበረከቱ።

ጠቅላይ ምክር ቤቱ በቁርዓን ውድድር ሀገራቸውን ያስጠሩትን ወጣቶች ከዚህ በደመቀ መልኩ የመቀበል ከፍተኛ ፍላጎት የነበረው ቢሆንም ወቅቱ የሑጃጆች ሽኝት ስራ ላይ ምክርቤቱ ያለ በመሆኑ ደማቅ አቀባበል ማድረግ አለመቻሉን ገልፀዋል።

የሀገራችን ኢትዮጵያዊ ስም ያስጠሩ ወጣቶችንና ዘይድ ኢብን ሳቢት የቁርአን ማህበር ለዚህ ውጤት በመብቃታቸው ሼይኽ ሐጂ ኢብራሒም በራሳቸውና በጠቅላይ ምክር ቤቱ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል

የእለቱን ፕሮግራም በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክርቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕረዚዳንት ሼይኽ አብዱልከሪም ሼይኽ በድረዲን ሱሩር እንደተናገሩት በቁርዐን ውድድር ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡት ወጣቶችን በክብር ስንቀበል ደስታ ይሰማናል ብለዋል።

ከ60 በላይ ሀገራት በተሳተፉበት በ ሊቢያው አለም አቀፍ የቁርአን ውድድር ላይ ሀገራችን ኢትዮጵያ በሁለት ዘርፍ ተወዳድራ በቂራተል አሸር 1ኛ ከጂግጅጋ አብዱልወሀብ ኢብራሂም ፤በሰላሳ ጁዝ 2ኛ ከአዲስ አበባ ሙሀመድ ማህሙድ በመውጣት አሸናፊ የሆኑት የዛሬ ተሸላሚ ወጣቶች በቀጣይ በመሠል ዉድድሮች ላይ የሐገራቸውን ስም እንደሚያስጠሩ ተስፋ እንደሚያደርጉ ሼይኽ አብዱል ከሪም ገልፀዋል።

የዘይድ ኢብን ሳቢት የቁርአን ማህበር ፍሬ የሆኑት እኚህ ወጣቶች በሊቢያ በተደረገውና ከ60 ሀገራት ከመጡ ተወዳዳሪዎች መካከል ዉድድሩን በድል ማጠናቀቃቸው ታውቋል።

በጠቅላይ ምክር ቤቱ የተደረገላቸውን የሐጅ ስጦታ ና የምስክር ወረቀት ያስደሰታቸው መሆኑን የገለፁት በሊቢያ በተደረገው የቁርዓን ዉድድር አሸናፊ የሆኑት ሁለቱ ወጣቶች ይኽ አይነቱ ማበረታቻ ለቀጣይ ሀገራቸውን ወክለው ለሚወዳደሩ ብርታት እንደሚሆናቸው ተናግረዋል።

ዛሬ በኢትዮጵያ እስልምናን ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የተደረገው በሊቢያ የቁርዓን ዉድድር አሸናፊዎች የዕውቅናና የሽልማት መርሐግብር ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ ሼይኽ ሐሚድ ሙሳ : የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕረዚዳንት የክቡር ዶክተር ሼይኽ ሱልጧን ሐጂ አማን : የኦሮሚያ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕረዚዳንት ሼይኽ ሚስባህ አብዱልከሪም ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው ታዋቂ ግለሰቦች ተገኝተዋል።

.***
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eia
ግንቦት 25፣ 2016 | ዙል ቂዳህ 25፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚደንት ከሑጃጅ መስተንግዶ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተወያዩ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መካ |

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ በመካ ከሚገኙ የሑጃጅ መስተንግዶ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተወያዩ።

ሸይኽ አብዱልአዚዝ ሸይኽ አብዱልወሊ ከሑጃጅ መስተንግዶ የሥራ ኃላፊዎች ጋር በተወያዩበት ጊዜ የሐጅ ሥርዓትን ለመከወን ወደ መካ የመጡትን የአሏህ እንግዶች በአማና እና በኃላፊነት ለማገልገል የመስተንግዶ እና የአገልግሎት ክፍል ሠራተኞች በግልና በቡድን እያሳዩት ያለውን ትጋት በማድነቅ ምሥጋና አቅርበዋል።

"ለሑጃጁ በምንሰጠው መስተንግዶና አገልግሎት ውጤታማ የምንኾነው፣ ሁላችንም በመግባባት፣ በኃላፊነት ስሜት፣ በአክብሮትና በቅንነት የአል-ረህማን እንግዶችን ማገልገል ስንችል ብቻ ነው" ሲሉ ተጠሪው ተናግረዋል።

በሐጅ ዙሪያ ቅድመ ዝግጅት አድርገን በመዲና እና በመካ ሐጃጆችን መቀበል ከጀመርን በኋላ የዞን አንድ ሑጃጆችን ጨርሰን የዞን ሁለት ሐጃጆችን ወደመቀበል ገብተናል ያሉት ሸኽ አብዱልአዚዝ፣ የዛሬው ውይይትም ሂደታችንን በመመዘን ቀጣይ ሥራችንን ይበልጥ ያማረ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል።

በውይይቱ ላይ የመዲና ቆይታቸውን ጨርሰው የሐጅ ቀናት እስከሚደርሱ በመካ ቆይታ የሚያደርጉ የአሏህ እንግዶችን በማስተናገድ ዙሪያ ከሥራ ኃላፊዎቹ ጥያቄዎች የቀረቡ ሲኾን አስተያየቶችም ተሰጥተዋል።

በዚህም ጊዜ፣ ለሐጅ አገልግሎት በተቀጠሩ የሳዑዲ ነዋሪ ሠራተኞችና በጠቅላይ ምክር ቤቱ ሠራተኞች መካከል በተዋረድ ያለመናበብ ክፍተት የተፈጠረባቸው ሁኔታዎች እንደነበሩ ተጠቅሷል።

በዚህ ረገድ ለምሳሌ የአዛዥና የሥራ ድርሻ መደበላለቅ የታየባቸው ሁኔታዎች እንደነበሩ ተጠቅሷል።

በተዘረጋው የመስተንግዶ የአሠራር ሥርዓት መሠረት በመካ የሆቴሎች አደላደልም በሦስት ዞን የተከፈለ እንደመኾኑ፣ የዞን አንድ ሐጃጆች ገብተው እንደተጠናቀቁ፣ ወደ ቀጣዩ ዞን የመስተንግዶ ሥራ በመሄድ ላይ ዩመቀዛቀዝ ስሜቶች ታይተው እንደነበረም ተነስቷል።

የወቅቱን ሥራ ሠርቶ መጨረስን ጠቅላላ ሥራውን የጨረሱ አድርጎ የመቁጠር ስሜት ተፈጥሮ እንደነበርም ተጠቅሷል።

በማረፊያ ክፍሎች ድልድል አንዳንድ ሐጃጆች የቤተሰብ (እናትና ልጅ፣ ባልና ሚስት ወዘተ.) መነጣጠልን የመሰሉ ችግሮች እንደገጠማቸው የተጠቀሰ ሲኾን፣ በዚህ ረገድ ከሐጃጆች የተሟላ መረጃ አለመቅረቡ መፍትኄ አሰጣጡ ላይ ጫና መፍጠሩ ተነስቷል።

የምግብና የጤና አገልግሎት ጉዳይን ጨምሮ በውይይቱ ላይ ከሥራ ኃላፊዎቹ ጥያቄዎችና ሐሳቦች የተነሱ ሲኾን፣ ሸይኽ አብዱልአዚዝ የተነሱ ችግሮች ሊፈቱ የሚችሉበትን መላ በመጠቆም የሥራ ኃላፊነትና አቅጣጫ ሰጥተዋል።

በዚሁ ጊዜም ሁሉም የጠቅላይ ምክር ቤቱ የልዑካን ቡድን አባላት በሥራ ላይ የመገኘት አማና እና ኃላፊነት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የዞን ኃላፊዎች በየዞናቸው ያለውን የሠራተኞች ኃይል ከሰው ኃይል ስምሪት ኃላፊው ጋር በመነጋገር የግል እና የቡድን ኃላፊነትን በማቀናጀት የጋራ ውጤት ማምጣት እንደሚገባቸው አቅጣጫ ተሰጥቷል።

የሰው ኃይል ስምሪት ኃላፊው አቶ አለልኝ አበባው ከጠቅላይ ምክር ቤቱ የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪው በተሰጠው አቅጣጫ መሠረት ሥራውን አንደሚያሳልጡ ተናግረዋል።

የሰው ኃይል ስምሪት ኃላፊው ከዞን ኃላፊዎች ጋር የተቀናጀ አሠራር በመከተል በውይይቱ ላይ ስምምነት የተደረሰባቸውን ጉዳዮች ተፈጻሚ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

ወቅታዊ ሥራን በጋራ ለመወጣት በጊዜውና በቦታው ላይ መገኘት ለአላህ እንግዶች ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችልም ተናግረዋል።

በመጨረሻም፣ የተጠያቂነት አሠራርን በመከተልና ተዋረዳዊ ትዕዛዝን ተግባራዊ በማድረግ የአልረህማን አንግዶችን በቅንነት ለማገልገል በጋራ እንሠራለን ብለዋል።

​•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 26፣ 2016 ዓ.ል | ዙል ቂዳህ 26፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
በ9933 የሐጅ መረጃ አገልግሎት በሦስት ቋንቋዎች እየተሰጠ ነው።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

ለ1445 ዓ.ሒ ሐጃጆች የመረጃ አገልግሎት ለመስጠት የተከፈተው የ#9933 ተጠቃሚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የጠቅላይ ምክር ቤቱ የመረጃ ክፍል አስተባባሪ ወ/ሮ ሲቱ ሙሐመድ ተናገሩ።

#9933 የሐጅ መረጃ አገልግሎት መስጠት ከጀመረ የወራት ዕድሜ ብቻ ያስቆጠሩ ቢኾንም፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተጠቃሚዎቹ ቁጥር እያደገ መኾኑን ኃላፊዋ ተናግረዋል።

የመረጃ ክፍሉ በሳምንት ለሰባት ቀናት ከጠዋቱ 1:00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2:00 ሰዓት ድረስ በአማርኛ፣ በኦሮሚፋ እና በሶማሊኛ ቋንቋዎች ለ1445 ዓ.ሒ የተከበሩ የአሏህ እንግዶችና ለቤተሰቦቻቸው ፈጣን መረጃ በመስጠት ላይ እንደሚገኝ ወ/ሮ ሲቱ ተናግረዋል።

የመረጃ ክፍሉ ሠራተኛና በአወሊያ መሰናዶ ትምህርት ቤት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መምህርት የኾኑት ዑስታዛ ኸዲጃ ሙሐመድ የ9933 የመረጃ አገልግሎት ጠቅላይ ምክር ቤቱ የሐጅ አገልግሎትን ለማዘመን በ1445 ዓ.ሒ. ተግባራዊ ካደረጋቸው አሠራሮች አንዱ መኾኑን አስታውሰዋል።

በሳምንት ለ98 ሰዓታት ለሐጃጆች የመረጃ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው የ9933 የመረጃ አገልግሎት፣ ኢንተርኔት በማይደርስባቸው የሀገራችን ክፍሎች ለሚኖሩ ሐጃጆች ከበረራ ጋር የተያያዘ ወቅታዊ መረጃን በመስጠት ላይ እንደሚገኝ ዑስታዛ ኸዲጃ ተናግረዋል።

ከአሁን በፊት የሐጅ ምዝገባ በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ብቻ ይካሄድ በነበረበት ጊዜ መረጃ ለማግኘት የግድ ወደ ጠቅላይ ምክር ቤቱ መምጣት ይጠበቅ እንደነበር ያስታወሱት ዑስታዛ ኸዲጃ፣ ይህም ሑጃጁን ላልተፈለገ እንግልትና ወጪ ይዳርግ እንደነበር አስታውሰዋል።

አንዳንድ ኃላፊነት የጎደላቸው ግለሰቦች ወደ 9933 በመደወል ተገቢ ያልሆኑ ንግግሮች እንደሚናገሩ የጠቀሱት ዑስታዛ ኸዲጃ፣ እኒህ ግለሰቦች ከዚህ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።

​​•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ግንቦት 27፣ 2016 | ዙል ቂዳህ 27፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለሐጃጆች 2 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ መድኃኒት ከሀገር ቤት ወደ መካ አስገባ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መካ |
ጠቅላይ ምክር ቤቱ በተቋማዊ አግልግሎት ረገድ ለትውልድ የሚሻገር ተጨባጭ የለውጥ አሻራ ለመስቀመጥ ጥረት ከሚያደርግባቸው አገልግሎቶች አንዱ የሐጅ ሥርዓቱን ማዘመን መሆኑ ተነገረ።

የሐጃጆች የጤና አገልግሎት መጎልበት የዚህ እቅድ አካል መሆኑን የጠቀሱት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚደንትና የሐጅና ዑምራ ዘርፍ ተጠሪ ሸይኽ አብዱልአዚዝ ሸይኽ አብዱልወሊ ናቸው።

ሸይኽ አብዱልአዚዝ ይህን የተናገሩት ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለሐጃጆች የጤና አገልግሎት የሚውል 2 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ መደኃኒት ከሀገር ቤት ወደ መካ ሲያስገባ በተካሄደው የርክክብ ስነ ሥርዓት ላይ ነው።

መጅሊሱ ለሐጃጆች የገዛው መደኃኒት ርክክብ በመካ በተካሄደበት ስነ ሥርዓት ላይ የጠቅላይ ምክር ቤቱ የሥራ አመራሮችም ተገኝተዋል።

በዚሁ ጊዜ፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የዑለማ ጉባዔ ምክትል ሰብሳቢና የፈትዋ ዐብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ጀይላን ኸድር እና የተለያዩ ክልሎችን የሚወክሉ የዑለማ ጉባዔ አባላት የተሰማቸውን ደስታ በመግለጽ መልዕክት አስተላልፈዋል።

የጠቅላይ ምክር ቤቱን ሁለንተናዊ የለውጥ እንቅስቃሴም አድንቀዋል።

ዶክተር ጀይላን ኸድር በዚሁ ጊዜ ባስተላለፉት መልዕክት መጅሊሱ ለአል-ረህማን እንግዶች በጤናው ዘርፍ እያደረገ ያለው መሻሻል ተቋሙ ለሚያገለግለው ሙስሊም ማኅበረሰብ ያለውን ክብር ከፍ የሚያደርግ ኃላፊነትን የመወጣት ምሳሌ ነው ብለዋል።

የ1445 የአል-ረህማን እንግዶች የሕክምና ቡድን መሪ ዶክተር አሚን ሙሐመድ በበኩላቸው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በታሪኩ ለሐጃጆች መዳኃኒት ገዝቶ መካ ሲያስገባ የመጀመሪያ ጊዜው መሆኑን ተናግረዋል።

መጅሊሱ ለአላህ እንግዶች በጤናው ዘርፍ በሰጠው ትኩረት የሕክምና ቡድኑ ልዑካን ቀደም ብለው ገብተው ከሳዑዲ የሐጅ ሚኒስቴር የሕክምና ክፍል ጋር የተለያዩ ፈቃዶችና ውሎችን እንዲፈጽም መደረጉን አስታውሰዋል።

ዶክተር አሚን ሙሐመድ አክለውም፣ "የንጉሥ አብዱልአዚዝ ቢን ሳዑድ ሆስፒታል የልብ ችግር ያለባቸውን ሐጃጆች ሊያክም ቃል ገብቶልናል" ብለዋል።

የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሐጅና ዑምራ ዘርፍ በወቅቱ 10,000 (አስር ሺህ) ኢትዮጵያውያን ሐጃጆች ቢኖሩም፣ በሐጅ ወቅት በሐጃጆች ሆስፒታል የታከሙት ከ18 ሺህ በላይ መኾናቸውን የሆስፒታሉ የታካሚዎች የምዝገባ ሰነድ ያሳያል።

ይህ ዳታ ኢትዮጵያውያን ሐጃጆች በትንሹም በትልቁም የጤና መታወክ ወደ ሆስፒታሉ መመላለሳቸውን የሚያሳይ ጤናማ ያልሆነ ዳታ እንደኾነ ተጠቁሟል።

የሕክምናው ቡድን መደራጀትና የመድኃኒቶች አቅርቦት መመቻቸት መጅሊስ በለውጥ ሂደቱ ለአል-ረህማን እንግዶች የሰጠውን ትልቅ ክብር የሚያሳይ ነው ተብሏል።

​•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
በጣም አስፈላጊ እና አስቸኳይ ማሳሰቢያ፣
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ

ለውድ የ1445 ዓ.ል. ሐጃጆች።

ከቀደሙት ዓመታት በተለየ፣ የሳዑዲ አረቢያ የሐጅ ሚኒስቴር፣ ለ1445 ዓ.ል. ሐጃጆች ኑሱክ የተሰኘ ልዩ የመታወቂያ ካርድ ወይም ባጅ ማዘጋጀቱ ይታወቃል።

ይህን ልዩ መታወቂያ አለመያዝ ሐጃጁን ከሐጅ ለመታገድና ተይዞ ያልተፈቀደለት ሐጃጅ ተብሎ ከሀገር ሊያስባርረው ይችላል።

በመኾኑም፣ የተከበራችሁ የአሏህ እንግዶች ይህን የሐገሪቱ ሕግ በማክበር፣ የኑሱክ ልዩ የመታወቂያ ካርድዎን በማንኛውም ጊዜ እንዲይዙ እናሳስባለን።

እናመሠግናለን።

​•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢት/እ/ጉ/ጠ ምክር ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | https://x.com/eiasc1
ሰኔ 6፣ 2016 ዓ.ል | ዙልሒጃ 7፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት በዞን አንድ የሚገኙ የአርረህማን እንግዶችን ጎበኙ።
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
መካ |
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶ/ር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ እና የጠቅላይ ምክር ቤቱ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚደንት ሸይኽ አብዱልከሪም ሸይኽ በድረዲን በሁለት የሐጃጆች ማረፊያ (ሆቴል) ጉብኝት አደረጉ።

የጠቅላይ ምክር ቤቱ መሪዎች ለጉብኝት በተገኙበት የዞን አንድ የሐጃጆች ማረፊያ (ሆቴል) የአርረህማን እንግዶችን አላህ ፈቅዶ እዚህ ለመገኘት በቅታችኋልና ለአላህ ምሥጋና ይገባዋል - አላህምዱሊላህ! ብለዋል።

ከሁሉ በላይ የአርረህማን እንግዶችን ማስደሰት፣ ተገቢውን ግልጋሎት መስጠት አላህ ዘንድ የሚያስገኘው ዳረጃ ከፍ ያለ በመኾኑ፣ ስለምናገኘው የአላህ ውዴታ ስንል በተቻለ መጠን በሐጅ ጉዞ አገልግሎት ላይ ያሉ ችግሮችን ኃላፊነት ከሰጣችሁን ጊዜ ጀምሮ በአላህ ፈቃድ ለማሻሻል ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስታውሰዋል።

በዚህ የእንኳን ደህና መጣችሁ ዚያራ ላይ ፕሬዚደንቱ በዞን አንድ ውስጥ ለሚገኙት ከሶማሊ እና ከአፋር ክልሎች ለመጡ የአርረህማን እንግዶች መልዕክት አስተላልፈዋል።

"ከዓመቱ ቀናት በላቁት ቀናት ላይ እንገኛለን። አላህ (ሱ.ወ) ቻይ ነው። አላህ (ሱ.ወ) ሰሚ ነው። አላህ (ሱ.ወ)
የተዓምራት ሁሉ ባለቤት ነው። ያላችሁበት ቦታ 'ዱዓ' የሚሰማበት በመኾኑ፣ የወንድምና ወንድም ደም መፋሰስ እንዲቆም፣ እነርሱም የአርረህማን እንግዶች እንዲኾኑ፣ ስለ ሰላም ስትሉ አጥብቃቹህ ዱዓ ልታደርጉ ይገባል" ብለዋል

በጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት የአርረህማን እንግዶች ጉብኝት ላይ ሐጃጆች ምሥጋና እና የተለያዩ ጥያቄዎች አንስተዋል። በዋነኛነትም 'ኑሱክ' የተባለውን ልዩ የሐጃጅ መታወቂያ ካርድ አለማግኘታቸው እንዳሳሰባቸው ተናግረዋል።

'ኑሱክ' የተባለው ልዩ መታወቂያ ካርድ የሕጋዊ ሐጃጅነት ማረጋገጫ መኾኑን የሳዑዲ የሐጅ ሚኒስቴር ቢገልጽም፣ በሁሉም ሀገር ባሉ ሐጃጆች ላይ የዚህ ቢጣቃ ችግር መከሰቱን ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባልደረቦቼ ነግረውኛል ብለዋል።

ይህን ልዩ መታወቂያ ካርድ እስካሁን እርሳቸውም እንኳ እንዳላገኙ ሸይኽ ሐጂ ተናግረዋል።

ችግሩ የተንከባለለ መኾኑን እና ሐጅ በባህሪው ዉጣ ውረድ ያለው በመሆኑ በአገልግሎት አሰጣጥ ፍፁምነት አይጠበቅም ያሉት ፕሬዚደንቱ፣ ችግሮችን በጋራ እየቀረፍን ከፊታችን በሚጠብቀንን የሐጅ ሥርዓት አላህ የሚቀበለን እንዲኾን በአው ፉታ ጀምረን የአርረህማን እንግዶች በመሆናችን ደስ ሊለን ይገባል ብለዋል።

በመጨረሻም የሐጃጆች ጉብኝት ዱዓ ተደርጎ ተጠናቅቋል።
ሰኔ 7፣ 2016 ዓ.ል | ዙልሒጃ 9፣ 1445 ዓ.ሒ.
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
ሙስሊሙ ማኅበረሰብ የአረፋን በዓል አቅመ ደካሞችን በመደገፍና በማሰብ እንዲያከብር የጠቅላይ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት አሳሰቡ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

ሙስሊሙ ማኅበረሰብ የ1445 ዓ.ሒ. የዒድ አል-አድኃ (አረፋ) በዓልን ሲያከብር ካለው ላይ ለአቅመ-ደካማ ወገኖቹ እንዲያካፍል የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የክብር ዶክተር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ አሳሰቡ።

ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሒም ቱፋ ይህን ያሳሰቡት፣ የዒድ አል-አድኃ በዓልን ምክንያት በማድረግ አስቀድሞ በተቀረፀ መልዕክታቸው ነው።

ሸይኽ ሐጂ በዚሁ መልዕክታቸው፣ በዙልሒጃ ወር የመጀመሪያዎቹ አሥር ቀናት የሚሥሠሩ መልካም ተግባራት አሏህ (ሱ.ወ.) ዘንድ በሌሎች ቀናት ከሚሥሠሩ መልካም ተግባራት በላጭ ምንዳ እንዳላቸው ከነቢያችን ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) ሐዲስ አጣቅሰው ተናግረዋል።

በሙስሊሙ ማኅበረሰብ በጉጉት ከሚጠበቁት የዙልሒጃ ወር የመጀመሪያዎቹ አሥር ቀናት ዘጠነኛዋ ቀን አል ሐጁል አረፋ የሚደረግበትና ማግሥቱ ቀን (የውመል ነሀር) የአረፋ በዓል የሚከበርበት መሆኑን ፕሬዚደንቱ አውስተዋል።

አሏህ (ሱ.ወ.) ሐጅን የወፈቃቸው የዓለም ሙስሊሞች አረፋ ላይ ሲቆሙ፣ ያልወፈቃቸው ወንድሞችና እህቶች ደግሞ በያሉበት የአረፋን ፆም በመፆም፣ ያለፉት ሁለት ዓመታት ወንጀሎቻቸው ከአሏህ (ሱ.ወ.) ምህረት የሚገኝባት ቀን መሆኗን ክቡር ሸይኽ ሐጂ የነቢያችን ሙሐመድ (ሶ.ዐ.ወ) ሐዲስን በማጣቀስ ተናግረዋል።

የአረፋ ቀን አሏህ (ሱ.ወ.) ፀጋውን የለገሳቸው ሙስሊሞች የዑድሂያ እርድ የሚያከናውኑበት መሆኑን የጠቀሱት ክቡር ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ እነዚህ ሙስሊሞች ከሚያርዱት እርድ ለተቸገሩ ወገኖቻቸው፣ በተለይም ለአቅመ ደካማና በተፈጥሮና በሰው ሠራሽ ችግሮች ሳቢያ ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ወገኖች ማካፈል ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

"እጅግ በጣም አዛኝና ርኅሩኅ የኾነው ጌታችን አሏህ (ሱ.ወ.) ይቅር ባይነትን ይወዳል" ያሉት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ "ተበድሎ ይቅር ያለን ሰው፣ አሏህ (ሱ.ወ.) የሠራውን ጥፋት ይቅር የሚለው በመኾኑ፣ ሁላችንም ይቅር ልንባባል ይገባል" ብለዋል።

የዘንድሮውን ዒድ አል-አድኃ (አረፋ) ለየት የሚያደርገው የሀገራችን የኢትዮጵያ ልጆች ሀገራዊ ምክክር እያደረጉ የሚገኙበት ወቅት ላይ መሆኑን ጠቅሰው፣ ሀገራዊ ምክክሩ ለጋራ ሀገራችን ሰላማዊነት ጠቃሚ መኾኑን በመረዳት ሙስሊሙ ማኅበረሰብ በያለበት በሀገራዊ ምክክሩ ላይ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

ሀገራዊ ምክክሩ ለሙስሊሙ ኅብረተሰብ የሚኖረውን ፋይዳ በመረዳት ጠቅላይ ምክር ቤቱ የሕግ ባለሙያዎችን፣ ዓሊሞችን፣ ምሑራንን፣ ታዋቂ ግለሰቦችንና ለሀገር የሚያስቡ ሰዎችን በማሰባሰብ የሙስሊሙን ጥያቄዎች (concerns) በማደራጀት ለሚመለከተው አካል መላኩን ፕሬዚደንቱ ሸይኽ ሐጂ ተናግረዋል።

ሰላም የሁሉ ነገር መሠረት መሆኑን የተናገሩት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም፣ ሁሉም የሰላም ዘብ እንዲሆን ጥሪ አስተላልፈው፣ ለሀገራችንና ለመላው ዓለም ሙስሊሞች በዓሉ የደስታ እንዲሆንላቸው ተመኝተዋል።

•••••••••••••••••••••​
​የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | twitter.com/eiasc1
ሰኔ 11፣ 2016 ዓ.ል | ዙልሒጃ 12፣ 1445 ዓ.ሒ
بِسْمِ ٱللَّهِ ٱلرَّحْمَٰنِ ٱلرَّحِيمِ
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሰላም ዙሪያ በጋራ ለመሥራት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
አዲስ አበባ |

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሰላም ዙሪያ በቀጣይ አብረው ለመሥራት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ።

ዛሬ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና መሥሪያ ቤት የሁለቱ ተቋማት ኃላፊዎች የመግባቢያ ሰነዱን በተፈራረሙበት ወቅት የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ዋና ፀሐፊ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ የአፍሪካ ኩራት ከኾነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በሰላም ጉዳይ ላይ አብሮ ለመሥራት የመግባቢያ ሰነድ መፈረማቸው እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል።

በሁለቱ ተቋማት ኃላፊዎች የተፈረመዉ የመግባቢያ ሰነድ አየር መንገዱ እያከናወነ ከሚገኘው ሀገራዊ ሥራ በተጨማሪ በቀጣይ ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በሀገራዊ ሰላም ዙሪያ የጋራ እሴቶችን በማስቀጠልና ሀገር ተረካቢ ወጣቶች ላይ
በመሥራት ታሪካዊ ኃላፊነትን ለመወጣት ያስችላል ተብሏል።

"የሃይማኖት አባቶች የኢትዮጵያ አየር መንገድ አምባሳደሮች ናቸው" ያሉት ዋና ፀሐፊው፣ 75 ዓመታትን በስኬት ያሳለፈው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቀጣይም ኢትዮጵያዊ ማንነቱን ይዞ በስኬት እንዲያስቀጥል የሃይማኖት አባቶቹ በሚችሉት ሁሉ ከጎኑ እንደሚቆሙ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው የአፍሪካ ኩራት የኾነው አየር መንገዱ ከጊዜ ወደ ጊዜ መዳረሻውን እያሰፋ መምጣቱን ጠቅሰው፣ በያዝነው 2016 ዓ.ል 2.6 ሚሊዮን የሀገር ውስጥ መንገደኞችን ማስተናገዱን ተናግረዋል።

አየር መንገዱ ከ26 ሺህ በላይ ለሚኾኑ ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ያወሱት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ሰዎች አብዛኛዎቹ በአየር መንገዱ የነፃ ሥልጠና ተጠቃሚዎች መሆናቸውን ተናግረዋል።

አየር መንገዱ የቱሪዝም ሥራ በሀገራችን እንዲስፋፋ ደረጃውን ከጠበቀ የሆቴል አገልግሎት በተጨማሪ የውጪ ምንዛሪ ገቢን ለሀገራችን ለማምጣት የስጋ፣ የአትክልት እና ፍራፍሬ ምርቶችን ወደተለያዩ ሀገራት የትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጠ መኾኑንም ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ መስፍን ተናግረዋል።
አየር መንገዱ እነዚህን ተግባራት የሚያከናውነው፣ ደከመኝ ሰለቸኝ በማይሉ ጠንካራ ሡራተኞቹ አማካኝነት መኾኑን ዋና ሥራ አስፈጻሚው ተናግረዋል።

በሁለቱ ተቋማት ከተደረገው የመግባቢያ ሰነድ የፊርማ ስነ ሥርዓት በተጨማሪ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት የበላይ ጠባቂ አባቶች ወደ ዩኒቨርሲቲ ደረጃ ያደገውን የአየር መንገዱን የምስለ በረራ ትምህርት ክፍል ጎብኝተዋል።

በዚሁ ጊዜም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ አራት ነፃ የቢዝነስ የአውሮፕላን ቲኬት አበርክቷል።

•••••••••••••••••••••••
የኢ.እ.ጉ.ጠ. ም/ቤት ሕዝብ ግንኙነት
ይከታተሉን | Follow us፡
ፌስቡክ | Ethiopian Islamic Affairs Supreme Council
ቴሌግራም | t.me/eiasc1
ትዊተር | twitter.com/eiasc1