የጊንር ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
277 subscribers
883 photos
16 videos
12 files
19 links
ይህ ቻናል ዓላማውን የሰንበት ት/ ቤቱን ጠቃሚ መረጃዎች እና መልእክት ማስተላለፍ አድርጎ ጥር 19/2012ዓም ሌሊት 6:50 ላይ ተከፈተ፡፡
Download Telegram
"ወእንዘ ትጸውሙ - ስትጾሙ" ማቴ፮፥፲፮
➥[ ከደብረ ዘይት የቀጠለ #ዘገብርኄር]➥

✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥

ወእንዘ ንጸውም - ስንጾም ቅንነት ባለበት አገልግሎት በመትጋት ነው

❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖❖
ዘወረደ ገብቶት በሃይማኖት የጸና፣
ቅድስት ተረድቶት መንገዱ የቀና፣
ምኩራብ መኖሪያውን ያደረገ እርሱ፣
መጻጉዕ ከመሆን የተለየች ነፍሱ፣
ደብረ ዘይት ሆኖ ጌታን የጠበቀ፣
በቅን አገልግሎት ከመትጋት ያልራቀ፣
ለእያንዳንዱ ዋጋን ሲሰጥ እግዚአብሔር፣
ያን ጊዜ ይሸለማል ነውና #ገብርኄር

❖ በገብርኄር እሁድ የተነበበው ወንጌል [ማቴ ፳፭፥፲፬- ፴] እንደሚነግረን #ለእያንዳንዳችን ጌታ መክሊት ሰጥቶናል። በዚህ ነግዶ ማትረፍ የኛ ድርሻ ነው።  ነግዶ ለማትረፍ ወደ #ማትረፊያ ገበያ መሰማራት ያስፈልጋል ወደ ምንከስርበት ከተሰማራን ግን ከስረን በእዳ መያዛችን አይቀርም

➥ስዕል የመሳል መክሊት የተሰጠው መንፈሳዊ ስዕላትን ወደሚስልበት ገበያ ተሰማርቶ ያትርፍ እንጂ ነገረ ዓለም ወደሚሳልበት ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ከመንፈሳዊነት እያወረደ አይክሰር

➥ የድምጽ መክሊት የተሰጠው በመዝሙር ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ወደ መንፈሳዊነት ማርኮ ያትርፍበት እንጂ ወደ ዘፈን ገበያ ወርዶ አይክሰር

➥ ጽሁፍ የመጻፍ መክሊት ያለው ክፉ ጽህፈትን ጽፎ ወዮታን ከሚገበይ (ኢሳ፲፥፪) የምሥራቹን ወንጌል በጽሁፍ ጥበብ አዳርሶ ሰዎችን ወደ ጥበብ ክርስቶስ ይማርክ

➥የመናገር መክሊት ያለው በአንደበቱ ጣዕም በስብከት ገበያ ተሰማርቶ ነፍሳትን ወደ በረቱ ይሰብስብ እንጂ ክፉውን ነገረ ዓለም ወደሚናገርበት ገበያ አይውረድ

ሁላችንም በየመክሊታችን ወደ ማትረፊያ ገበያ እንሰማራ!

❖ ገና ለገና እከስራለሁ ብሎ በስንፍና መቅረት አግባብ አይደለም። አለመስራትና አለማትረፍም ቅሉ መክሰር እንደሆነ የታወቀ ነው። ቸሩ ጌታችን በሚያከስር ገበያ እንድንሰማራ አልላከንም። የሚያተርፍ ውድ መክሊት እንጂ የሚያከስር መክሊትንም አልሰጠንም።

አለማገልገል የፍቅር ማጣት ነው። በሃይማኖት ጸንቶ፣ በምግባር ኖሮ፣ በቤተ ክርስቲያን ያለ ሲበድልም በንሰሀ የሚገኘውን ዕረፍት ያጣጣመ ይህን ጣዕም ሌሎቹ እንዲቀምሱ አለመጣር የፍቅር ማጣት ነው!

ሐዋርያት ወደ ዓለም ለአገልግሎት የተሰማሩት ከፍቅር ተነስተው ነው። ሰውን ሁሉ ይወዳሉና ለሰው ሁሉ የሚድኑበትን መንገድ አመለከቱ። ሰዎቹ እየደበደቧቸው እንኳ ሐዋርያቱ ግን ስለ ደብዳቢዎቻቸው ድኅነት የሚተጉበት ምክንያት ፍቅር ናት!

የከበረ ሐዋርያ ነዋየ ኅሩይ ቅ/ጳውሎስ የሚለውን ተመልከቱ "በሥጋ ዘመዶቼ ስለ ሆኑ ስለ ወንድሞቼ ከክርስቶስ ተለይቼ እኔ ራሴ የተረገምሁ እንድሆን እጸልይ ነበርና" [ሮሜ ፱፥፫] እራስን አሳልፎ እስከመስጠት ያለ ፍቅር!

ስለዚህ አገልግሎት በፍቅር ለፍቅር የሚደረግ የፍቅር መግለጫ ነው።

❖ የምናተርፍበትን ገበያ ትተን በሚያከስር ገበያ እንዳንገኝ። በምክንያተኝነት ተተብትበን፣ ከፍቅር ጎድለን፣ ዋጋ በምታሰጥ አገልግሎት ከመትጋት ተዘልለን፣ መክሊታችንን እንዳንቀብር ዛሬ ያውም አሁኑኑ ወደ አገልግሎት እንሰማራ! መልካም ንግድ ተመኘሁ.... ይቆየን!
✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥✥
        ሚያዚያ ገብርኄር ፳፻፲፮ዓም