TechIn2
1.22K subscribers
1.47K photos
1 video
120 files
500 links
Technology & Innovation Institute (TechIn2), Ethiopia

የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢኒስቲትዩት

ጠቃሚና ወቅታዊ የሆኑ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ፈጠራ፣ ጤና እና ሰብአዊ-ኣቅም ግንባታ(Human Development)መረጃዎችንና ምክሮችን በየእለቱ እናደርሶታለን።
Download Telegram
ኮቪድ 19ኝን በመከላከል ረገድ ከሩቅ ምስራቅ ሀገራት ስኬት የተገኙ ትምህርቶች
====================
በአሁኑ ሰዓት የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመግታት መደረግ ያለባቸው የጥንቃቄ ስራዎች በግልፅ ቢቀመጡም በዓለም ላይ ያሉ ሀገራትና መንግስታት እነዚህን እርምጃዎች ተግብረው ህዝባቸውን ከቫይረሱ ለማስጣል ፈታኝ ሆኖባቸዋል፡፡ የቫይረሱን መነሳት ቻይና ለዓለም ጤና ድርጅት ያሳወቀችበት ዕለት (ታህሳስ 21) ሀገራት የጥንቃቄ እርምጃዎችን እንዲወስዱ የማንቂያውን ደውል ደውሏል፡፡ ታድያ በዚህ ጊዜ በቀደሙት ዓመታት ውስጥ ሳርስ እና መርስ በተባሉ የኮሮና ቫይረስ ቤተሰቦች ተጠቅተው የነበሩት ደቡብ ኮርያ፣ ታይዋን እና ሆንግ ኮንግ ፈጥነው ወደ እርምጃ ለመግባት የመጀመሪያዎቹ ነበሩ፡፡ ሌላው ዓለም ግን ቫይረሱ በፍጥነት መስፋፋት እስከሚጀምርበት ሰዓት ድረስ ተገቢውን እርምጃ ሳይወስድ ቀርቷል፡፡ የሩቅ ምስራቅ ሀገራቱ የቫረሱን ስርጭት ለመግታት ከተጓዙባቸው እርምጃዎች ተከታዮቹን አባይት ነጥቦች መረዳት ይገባል፡፡
• የመጀመሪያው ቫይረሱ የት የት እንደሚገኝ ማወቅና ስርጭቱን ባለበት መግታት ነው፡፡ ይህም የመመርመር፣ መከታተል እና መለየት ስራን፤ ማለትም ምርመራን በስፋት ማከናወን፣ በሳምንት ውስጥ ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች ጋራ ግንኙነት የነበራቸውን ሰዎች መለየትና በለይቶ ማቆያዎች ውስጥ በግዴታ ማስገባትን ይጠይቃል፡፡ መንግስታቱ ለዚህ ተግባር ወታደሮችን በማሰልጠን አሰማርተዋል፡፡ ምንም እንኳን መመርመር በራሱ መፍትሄ ባይሆንም የቫይረሱን ሰርጭት መቆጣጠር ከማይቻልበት ደረጃ ከመድረሱ በፊት ለመግታትና በህክምና ተቋማት፤ ከፍ ሲልም በምጣኔ-ሐብቱ ላይ ቀውስ ሳይፈጠር ነገሮችን ለመቆጣጠር ትልቅ መሳርያ ነው፡፡
• ሁለተኛው እርምጃ ለቫይረሱ ከፍተኛ ተጋላጭነት ያላቸውን የጤና ባለሙያዎች ደህንነት መጠበቅ ነው፡፡ ይህ እርምጃ ባለሙያዎቹ የቫይረሱን ምርመራ ከማንም አስቀድሞ እንዲያገኙ በማድረግ ብቻ ሳይወሰን አስፈላጊው የመከላከያ መሳርያ ሁሉ በአስቸኳይ እንዲደርሳቸው ማድረግን ይጨምራል፡፡ በፍጥነት ማምረት እማይቻሉትን እንደ መተበንፈሻ ማሽን፣ አልጋ እና ኦክስጅን ያሉትን መሳርያዎች አቅርቦት በሽታውን ከፊት ሆነው እየተዋጉ ላሉት ለነዚህ የጤና ባለሙያዎች ማቅረብ ላይም ትኩረት መሰጠት ይኖርበታል፡፡
• ሶስተኛው የትኛው የሀገሪቱ ክፍል በበሽታው ስርጭት በስፋት እየተጠቃ መሆኑን ሰዎች ተጠጋግተው የሚኖሩባቸው ስፍራዎች ለቫይረሱ በከፋ ተጋላጭ መሆን አለመሆናቸውን የሚለይ ስርዓት መዘርጋት ነው፡፡
• የድንበር ቁጥጥር፤ በተወሰኑ ሀገራት ላይ የጉዞ እገዳን ማድረግ ቫይረሱን በመከላከል ረገድ ያለው ውጤታማነት አነስተኛ በመሆኑ ከየትኛውም ሀገራት የሚመጡ ተጓዦችን ወደ ለ14 ቀናት ወደ ለይቶ ማቆያዎች ማስገባት በቫይረሱ ተጠቂ የሆኑትን ለመለየት ሁነኛ መንገድ ተደርጎ ተወስዷል፡፡
• አምስተኛው ህዝቡ በመከላከል ፖሊሲዎቹ ላይ እምነቱን ያሳድር ዘንድ ግልፅነት እና እውነተኝነት ላይ የተመሰረተ የመረጃ ልውውጥን ማድረግ ነው፡፡ እነዚህ ወቅቶች በህዝቡ ዘንድ አለመረጋጋት ያለባቸው በመሆኑ መንግስታተት በመከላከያ ፖሊሲዎቹ ዙርያ ቀጥተኛና ዘላቂነት ያለው መረጃን ማድረስና በሚወስዷቸው እርምጃዎች ዙርያ ግልፀኝነትን ማስፈን ይኖርባቸዋል፡፡
• በስድስተኛነት የተቀመጠው የትኛውም እርምጃ ነገሮች በፍጥነት ቀድሞ ወደነበሩበት የማይመልሳቸው መሆኑን ማወቅ ነው፡፡ ይህ የህዝቡ ዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ በመከላከያ እርምጃዎች የታጀበ ማድረግን ያካትታል፡፡ በዋነኝነትም፤ አካላዊ ርቀትን በሚቻለው መጠን መተግበር፣ ወደማንኛውም የህዝብ መገልገያ ህንፃዎችና ቢሮዎች የሚገቡ ሰዎችን ሙቀት መለካትን እንዲሁም ሰው በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎች ሁሉ የፊት ጭምብሎችን ማድረግ ይገኙበታል፡፡
• ሰዉ በቤት እንዲቆይ ማስገደድ ሌላኛው እርምጃ ነው፡፡ ሰውን በቤት እንዲቆይ ማስገደድን አስቀድሞ መተግበር የቫይረሱን ስርጭት ለመቀነስ ይረዳሉ፡፡ ሆኖም ይህ በራሱ ሁነኛ መፍትሄ አይሆንም፤ በምጣኔ ሐብቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ እርምጃ ስለሆነ ሁሌ መተግበርም የለበትም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ለመንግስታት ጊዜን መስጠቱና የጤና መሰረተ-ልማታቸውን ለማጎልበት ዕድል እንደሚሰጣቸው እሙን ነው፡፡
• የመጨረሻው ከላይ የተጠቀሱት እርምጃዎች ሁሉ የአጭር ጊዜ ስትራቴጂ ከሞሆን ስለማያልፉ በየጊዜው በሚወጡ ሳይንሳዊ ግኝቶች ላይ የተመሰረቱ እርምጃዎችን ከመውሰድ ጎን ለጎን ሀገራት የራሳቸውን ሁነኛ መፍትሄ መመፈለግ ይኖርባቸዋል፡፡
ምንጭ፡ The Guardian
ለ96 ዓመታት ሳይቀበር በእንክብካቤ የቆየው የሌኒን ሬሳ
========================
የ20ኛውን ክፍለ ዘመን ታሪክ ከለወጡ የአለማችን ሰዎች መካከል ከቀዳሚዎቹ ይቀመጣል፤ የኮምዩኒስት አብዮተኛው ቭላዲሚር ኢሊች ዑሊያኖቭ ወይም ሌኒን፡፡ የሶቭየት ህብረት መስራች እና የመጀመሪያው መሪ በመሆንም ህይወቱ እስካለፈበት ወርሀ ጥር 1916 ዓ.ም አገልግሏል፡፡ ሆኖም የሌሊን መሞት ከአፈር ዘንድ እንዲገባ አላደረገውም፡፡ ላለፉት 96 አመታት ሬሳው በጥንቃቄ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ ሌኒን ሲሞት ለዚህ ጊዜ ያህል ሬሳው ሳይቀበር እንደሚቆይ አልታቀደለትም ነበር፡፡ ሬሳውን የማቆየት ስራው መጀመሪያ የተከናወነው ለአራት ቀናት ያህል ሊካሄድ ለታሰበው ሬሳውን ለህዝብ የማሳየት ስነ-ስርዓት ሳይጎዳ እንዲቆይ ታስቦ ነው፡፡ በሩስያ የክረምት ወቅቶች በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሶቭየታዊያን ቢጎበኙትም የደረቀውን ሬሳ ለማየት የሚጎርፈው ሰው ግን አላቆመም፡፡ ወቅቱ ቀዝቃዛ መሆኑን ተከትሎ ለ56 ቀናት በቀዩ ጎዳና ላይ በተሰራለት ጊዜያዊ የመቃብር ቤት ቆይቷል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው የሙቀት ወራቱን መምጣት ተከትሎ በዘላቂነት የማቆየት ስራው መሰራት የተጀመረው፡፡ በመጀመሪያ ቀርቦ የነበረው እቅድ ሬሳውን በኬሚካል ከማከም ይልቅ በቅዝቃዜ ውስጥ ማቆየት ነበር፤ ቭላዲሚር ቮሮበዮቭ እና ቦሪስ ዝባርስኪ የተባሉት ዕውቅ ኬሚስቶች ሬሳውን ከመበስበስ በሚታደግ የኬሚካል ውህድ የማከም፣ የማድረቅ፣ እንዲሁም የቅርፅ እና ቀለም ለውጥ የማድረግ ሀሳብን እስከሚያመመጡት ድረስ፡፡
ስራው ከተፈቀደ በኋላ በሶቭየት መሪዎች ጥብቅ ቁጥጥር ታጅበው ተመራማሪዎቹ የሬሳውን ቆዳ የማንፃት እና በቂ የሆነውን የኬሚካል ውህድ ምጣኔ የማስላላት ስራዎችን ለወራት ሲሰሩ ቆዩ፡፡ በመጨረሻም በሞስኮ ቀዩ አደባባይ ዳግም ለህዝብ ክፍት ሆኖ መጎብኘት ጀመረ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ሬሳውን ሳይበሰብስ የማቆየት ስራው የሚሰራ የተመራማሪዎች ቡድን ተመድቦለት እንክብካቤን በማግኘት ላይ ነው፡፡ በዘመነ ሶቭየት በቤተ-ሙከራው ውስጥ የሚሰሩት ተመራማሪዎች ቁጥር እስከ 200 ደርሶ ነበር፡፡ ይህ ቁጥር አሁን ወደ ጥቂት ተመራማሪዎች ቢወርድም ስራው ግን በተመሳሳይ መልኩ ይሰራል፡፡ አስክሬኑ ያለበት ክፍል በጥንቃቄ ተሰልቶ የተመጠነ የብርሀን እና ሙቀት መጠን የሚያገኝ ሲሆን፤ በጥቂት ቀናት ልዩነት ውስጥ ተመራማሪዎቹ ወደ ክፍሉ በማምራት ሬሳውን ይጎበኛሉ፡፡ በየ 18 ወራት ልዩነትም ከተቀመጠበት በፈዘዘ ብርሃን የታጀበ የመመልከቻ ክፍል በታች ወዳለው ቤተ-ሙከራ እየተወሰደ የእጥበት እና የማቆያ ስራዎች ይሰሩለታል፡፡
ምንም እንኳን ሳይንቲስቶቹ የሌኒንን አጥንት፣ ጡንቻ፣ ቆዳና ሌሎችንም ህዋሳቶቹን ማቆየየት ቢችሉም የውስጥ አካላቱ ግን ከሬሳው እንዲወጡ ተደርጓል፡፡ አዕምሮው የድንቅ ችሎታ ባለቤቶችን ለመመርመር ብቻ ታስቦ ከሌኒን ሞት ብዙም ሳይቆይ ወደተቋቋመው የአዕምሮ ኢንስቲትዩት ተወስዷል፡፡ አሁን ድረስም የአዕምሮው የተወሰነ አካል በሩሲያ አካዳሚ ኦፍ ሳይንስ በሚገኘው የኒውሮሎጂ ማዕከል ተቀምጧል፡፡
ይህ በሶቭየታዊያኑ ዘንድ የበለፀገው ለየት ያለ ሬሳን የማቆያ ዘዴ ከውጪ ሀገራትምም ቢሆን ደንበኞችን አላጣም፡፡ በዚህ ስልት ሬሳቸው ከቆየላቸው የኮምዩኒስቱ ዓለም ታዋቂ መሪዎች መካከል መካከል የቪየትናሙ ሆ ቺ ሚን፣ የቡልጋሪየው ጊኦርጂ ዲሚትሮቭ እና የሰሜን ኮርያው ኪም ጆንግ ኢል ይገኙበታል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ከስታሊን ሞት በኋላ ሶቭየትን አንቀጥቅጦ የገዛው ጆሴፍ ሳታሊንም ከአውሮፓውያኑ 1953 እስከ 1961 ድረስ ከሌኒን ጎን ሬሳው ተጠብቆ ተቀምጦለት ነበር፡፡
እነዚህ ሁሉ ሬሳን የማቆየት ስራዎች ታድያ ይከወኑ የነበሩት በሚስጥር ነበር፤ ሳይንቲስቶቹ የጥገና ስራዎችን ለማከናወን ወደ ቪየትናም ወይም ሰሜን ኮርያ የሚበሩትም አልፎ አልፎ ነው፡፡ ከአውሮፓያኑ 1987-97 በቤተ-ሙከራው ይሰራ የነበረው ቫዲም ሚሎቭ እንደሚናገረው በወቅቱ እርሱን መሰል ጀማሪ ባለሙያዎች በጊዜው ምንም አይነት ዝርዝር ጉዳዮችን እንዲያውቁ አይደረግም ነበር፡፡ ዘ ጋርዲያን በቤተ-ሙከራው የሚሰራ አንድ ባለሙያን ቃለ-መጠይቅ ለመስራት ያደረገው ተደጋጋሚ ጥረት አለመሳካቱንና ኋላም የመላው ሩሲያ ኢንስቲትዩት ኦፍ አሮማቲክ እና ሜዲካል ፕላንት ዳይሬክተሩ ኒኮላይ ሲድልኒኮፍ የሀገርና የንግድ ሚስጥር ስለሆነ ወደ ስፍራው መግባትን እንደተነፈገ አሰቀምጧል፡፡ የሌኒንን አካል ለዓመታት ሲያጠና የቆየው ዩርቺያክ ስፍራው ቀድሞ አሁን ባለው ልክ ሚስጥራዊ እንዳልነበር ይናገራል፡፡ እንዲያውም በ1980ዎቹ እነዚህ ባለሙያዎች ብዙ ጊዜ ቃለ-መጠይቅ ሲሰጡ መቆየታቸውንና አንድ የሩሲያ የቴሌቪዥን ጣብያም በስፍራው ተገኝቶ በቤተ-ሙከራው ላይ ጥልቅ ዘጋቢ ፊልም መስራቱን ጠቅሷል፡፡ ሆኖም ጋዜጠኞች ስራውን ወደ ቀልድነት እንዳያወርዱባቸው በመሰስጋትን (ጋዜጠኞቹም ይህን ማድረጋቸው የተለመደ ስለነበር) አዳዲሶቹ የቦታው አስተዳዳሪዎች የትኛውም ጋዜጠኛ ዝር እንዳይልባቸው እንደማይፈልጉ ተናግሯል፡፡
ከ1984ቱ የሶቭየት ህብረት መፈረካከስ በኋላ ስፍራው ከባድ ፈተና ገጥሞት ነበር፤ አዳዲሶቹ ዲሞክራሲን አቀንቃኝ ሩስያዊያን አስተዳዳሪዎች ሙሉ ህንፃው እንዲፈርስና ሌኒንም ወደ ሌላ ቦታ ተወስዶ እንዲቀበር ጥሪ ማቅረብ ጀምረው ነበር፡፡ ሆኖም ይህ ሀሳብ ሰፊ ህዝባዊ ተቃውሞን ስለጠራ እንዲቆም ተደርጓል፡፡ መንግስት ግን ለስራው የሚያደርገውን ድጋፍ በዚያው ዓመት ማቆሙን ተከትሎ የሩስያ ኮምዩኒስት ፓርቲ ገንዘብ በመሰብሰብ ስራውን ሙሉ በሙሉ መደገፍ ጀመረ፡፡ ሆኖም ትልቁ ፈተና ስራውን የሚሰሩት ሳይንቲስቶች ማርጀትና አዳዲስ ሳይንቲስቶችም በዘርፉ ለመስራት አለመፈለጋቸው ነው፡፡
አሁንም ድረስ ስፍራው በሞስኮ ቀዩ አደባባይ የሚገኝ ሲሆን ሬሳውን ለህዝብ በሚፈቀድበት ክፍልም ገብቶ በነፃ ማየት ይቻላል፡፡
ምንጭ፡ the guardian፣ cnn እና ሌሎችም
የቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት የሀገራችንን የኢኖቬሽን ሁኔታ የሚያሳይ ጥናት በቅርቡ ይፋ ማድረጋችን ይታወሳል፡፡ በዚህም መሰረት ሙሉ ጥናቱን ለመመልከት የምትችሉ ሁሉ በተቀመጠው ሊንክ አማካኝነት ወደ ድረ-ገፃችን ገብታችሁ በነፃ ማግኘት ትችላላችሁ፡፡ http://
www.techin.gov.et/post/136/
በቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ተመራማሪዎች የተሰራ ሳኒታይዘር በማከፋፈል ላይ ነው
=====================
በኢንስቲትዩታችን ባሉ ተመራማሪዎች አማካኝነት ተሰራው ይህ የእጅ ንፅህና መጠበቂያ (ሳኒታይዘር) የዓለም የጤና ድርጅት ባስቀመጠው ቀመር መሰረት የተሰራ ነው፡፡
በሀገራችንም በግለሰብ እንዲሁም በተቋም ደረጃ በሽታውን ለመከላከልና ስርጭቱንም ለመቀነስ አቅም ያለው በገንዘብ እውቀት ያለው በእውቀቱ ለወገኑ አለው በማለት የሰባዊነትና የዜግነት ግዴታዉን እየተወጣ ይገኛል፡፡ ተቋማችን የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩትም በሽታው በሀገራችን ገባ ከተባለበት ስዓት ጀምሮ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ የስልክ መተግበሪያ (አፕሊኬሽን) በመስራት፣ በሀገራችን እንዲሁም በአለም ላይ ስለ በሽታው ወቅታዊ የሆኑ ዜናዎችንና መከላከያ መንገዶችን የሚጠቁሙ መረጃዎችን በማሰራጭት፣ አቅም ለሌላቸው ወገኖች ደግሞ የተቋሙ ሰራተኞች የአንድ ወር ደሞዛቸውን ከ1.3 ሚሊዬን ብር በላይ ሲለግሱ፤ አሁን ደግሞ ራሳቸውን ከበሽታው ይጠብቁ ዘንድ በተቋሙ ተመራማሪዎች የተመረተውን የእጅ ማፅጃ (ሳኒታይዘር) ለሰራተኞቹ እያከፋፈለ ይገኛል፡፡ በቀጣይም ይህንን ወረርሽን በሀገራዊ ፍቅር ስሜት በእውቀት በመዋጋት የበኩሉን እንደሚወጣ ተቋሙ ያስታውቃል፡፡
በኮቪድ 19 ዙርያ የተሰሩ የፈጠራ ስራዎች ተመርጠው ቀረቡ
======================
በሀገራችን ካለው የኮቪድ 19 ስርጭት ጋራ በተያያዘ የተሰሩት የፈጠራ ፕሮፖዛሎች ዛሬ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በውድድሩ አጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥ በሶስት የማጣርያ ዙሮች ተጣርተው ያለፉ 30 ፈጠራዎች ዝርዝር ውድድሩ የሚያስተናብረው የብሄራዊ የኢኖቬሽን ግብረ ኃይል አስተባባሪ በሆኑት አቶ አዲሱ ማሞ አማካኝነት ቀርቧል፡፡
በውይይቱ ጅማሮ የስራውን የእስካሁን ሂደት አስመልክቶ የቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክረተርና የዚህ ግብረ ኃይል መሪው አቶ ሙሉቀን ቀሬ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡በሪፖርታቸውም 446 የፕሮጀክት ፕሮፖዛሎች መቅረባቸውን ገልፀው ከነዚህም ውስጥ 43 በመቶው ለምርት የተዘጋጁ፣ 31 በመቶው የተለያዩ የማበልፀጊያ ስራዎችን የሚሹ ሰርቶ ማሳያዎች እንዲሁም 26 በመቶው በሀሳብ ደረጃ ያሉ መሆናቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ከፈጠራዎቹ ግማሽ ያህሉም የሶፍትዌር እና የሞባይል መተግበሪያዎች መሆናው እንዲሁም በአጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥም በአንፃራዊነት ጥቂቶቹ የተሸለ ሀሳብ ይዘው መምጣታቸው በሪፖርታቸው ተካቷል፡፡
ፈጠራዎቹ የመተንፈሻ ማሽኖች፣ የእጅ መታጠቢያ፣ የሶፍትዌር ስራዎችን ጨምሮ በስድስት የተለያ ዘርፎች ተከፋፍለው ነው የቀረቡት፡፡ ከቀረቡት ስራዎች መካከልም የእጅ መታጠቢያ ላይ ያተኮሩ ፈጠራዎች፣ ካሉበት በመሆን ትምህረትን መከታተል የሚያስችል የስልክ መተግበሪያ ስርዓት፣ የኮቪድ-19 መከታተያ ስርዓት እና ሌሎች ምርቶችም ይገኙበታል፡፡
ዛሬ በቀረቡት ስራዎች ላይ በተሰበሰቡት ታዳሚያን በተለይ በሚሰጠው የድጋፍ አይነት እና ለየትኞቹ ፈጠራዎች ድጋፍ መደረግ እንዳለበት ከተሳታፊው ጥያቄና አስተያየቶች ተነስተው በአቶ አዲሱ እና አቶ ሙሉቀን አማካኝነት ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
የፈጠራ ስራዎቹን የሚገመግመው ከቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ኢኖቬተርስ አሶሴሽን፣ የኢትዮጵያ ባዮቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ የተውጣጡ 25 ባለሙያዎች ያሉት ቴክኒክ ቡድን ነው፡፡
ቬንትሌተር እና ሌሎች የፈጠራ ስራዎችን ያበረከተው ወጣት
=================================
የኮቪድ 19 ወረርሽኝ በሃገራችን ከገባ ወዲህ የስርጭት መጠኑን ለመቀነስ የሚያግዙ የተለያዩ ፈጠራዎች በወጣቶች እና በቴክኖሎጂ ተቋማት እየተሰሩ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ዩሃንስ ኪዳኔ መሰል የፈጠራ ስራዎችን በመስራት ላይ የሚገኝ የፈጠራ ባለሙያ ሲሆን መደመር የፈጠራ ስራዎች በተባለ ድርጅት ውስጥም በግልና በህብረት እየተንቀሳቀሰ ያለ ባለሙያ ነው፡፡
ወጣቱ በኮቪድ 19 ዙሪያ ትኩረታቸውን ያደረጉ ከአምስት በላይ ፈጠራዎችን በግሉ እና ከሌሎች ተቋማት ጋር በትብብር የሰራ ሲሆን፤ ከኮቪድ 19 ውጭ ያሉ ሌሎች ብዙ ፈጠራዎችም ከድርጅቱ ጋር በመሆን እንደሰራ ተናግሯል፡፡ ከስራዎቹ መካከል በኤሌክትሪክና በባትሪ የሚሰራ ቬንትሌተር፣ የእጅ ንክኪ የማያስፈልገው መታጠቢያ፣ በባንኮች አካባቢ የሚቀመጥ የእስኪቢርቶ ማስቀመጫ ዋና ዋናዎቹ ፈጠራዎች ሲሆኑ፤ ከዚያ በተጨማሪም የእግር መጠራረጊያ፣ ሳቢነት ያለው የግንዛቤ መስጫ ቦርድ በሽታውን ለመከላከል ከሰራቸው ስራዎች መካካል የሚመደቡ ናቸው፡፡
የፈጠራ ባለሙያው ቬንትሌተሩን ሲሰራ በሰው አገዛ ብቻ የሚሰራውን ሜካኒካል መሳሪያ በቀላል ግብዓቶች በመጠቀም በራሱ የሚንቀሳቀስ እና በኤሌክትሪክ ወይም በባትሪ እንዲሰራ ያደረገው ቢሆንም ከሌሎች የጤና በለሙያዎች ጋር በመተባባር ጥራቱ የሚጨምርበት እና የተሻለ ግልጋሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ ለማድረግ በጥረት ላይ መሆኑን ገልፆልናል፡፡ የፈጠራ ባለሙያው ከቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር በአራዳ ክፍለከተማ በሚገኘው የፒያሳ አውቶብስ ማቆሚያ ቦታ ላይ የሰራው የግንዛቤ መስጫ ቦርድ ሌላው ፋጠራው ሲሆን፤ ከዚህ በኋላም ከሌሎች ተባባበሪ አካላት ጋር በመሆን ተጨማሪ ስራዎችን ለመቅረብ እንደሚሞክር ግልፆልናል፡፡
በኮሮናቫይረስ ዙሪያ የሚሰሩ ኢኖቬሽን ተኮር የምርምርና የፈጠራ ስራዎች ቫይረሱን ለመከላከል በሚደረገው ሁለንተናዊ ጥረት ትልቅ ጥቅም እንዲሰጡ ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተሰናስሎ መስራት እጀግ አስገፈላጊ እንደሚሆንም ባለሙያው ያስረዳል፡፡
የዩሃንስ ኪዳኔን የፈጠራ ስራዎች ሙሉ ማብራሪያ በቅርቡ በቪዲዮ የምናቀርብ ይሆናል፡፡
የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል በኢትዮጵያ ሊገነባ ነው
=================================
ቦሌ በሚገኘው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ዋና ፅ/ቤት ፕሮፌሰር ሂሩተ ወ/ማርያም የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚንስትር እንዲሁም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚንስትር ዶ/ር አብርሃም በላይና ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር የጋራ ስምምነት ሰነድ ተፈራርመዋል፡፡
የስምምነቱ ዋና አላማ የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል ማቋቋም፤ በኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ ዘርፍ የጋራ ምርምር ለማካሄድ፤ በማስተርስና ፒኤችዲ ደረጃ የኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ ዘርፍ ትምህርት ለመክፈት እንዲሁም ለሃገር እድገት ጠቃሚ በሆኑ ሌሎች የስፔስ ሳይንስ ምርምር ዘርፎች ዙሪያ ተባብሮ ለመስራት የሚያስችል ስምምነት እንደሚሆን ተገልጿል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ የመጀመሪያ የሆነው የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል ፕሮጀክት ሶስት ዓመት የሚፈጅ ሲሆን ፤ እስከ 500ኪ.ግ የሚመዝኑ ሳተላይቶችን ለማምረት የሚያስችል እንደሆነ ዶ/ር ይሹሩን አለማየሁ በኢ.ስ.ሳ.ቴ.ኢ ስፔስ ኢንጂነሪንግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተርና የፕሮጀክቱ ተቆጣጣሪ ጠቁመዋል፡፡ 50 ሚሊየን ዩሮ በሚፈጀው ፕሮጀክት 25 ሚሊየን ዩሮዉን የአዉሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ የሚሸፍን ይሆናል፡፡ የተቀረዉን ደግሞ የፈረንሳዩ አርያን ግሩፕ ለሳተላይት ቴክኖሎጂ ማምረቻ የሚሆኑ ማሽኖችን በማቅረብ እንዲሁም በኢትዮጵያ መንግስት በአይነቱ ልዩ የሆነ እና ለሳተላይት ማምረቻ ምቹ የሆነ ማዕከል በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ዉስጥ የሚገነባ ይሆናል፡፡
ኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት
የኮሮናቫይረስ በጤና አገልግሎቱ ላይ በሚያሳርፈው ከፍተኛ ተፅዕኖ ምከንያት 6,000 ህፃናት በየቀኑ ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ Unicef አስታወቀ
=======================
የኮሮናቫይረስ በሚያስከትላቸው ተያያዥ ችግርች እና የጤና አገልግሎት መዳከም ጋር ተያይዞ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት ውስጥ ስድስት ሺ የሚጠጉ ህፃናት በየቀኑ ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችል የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት አሳስቧል፡፡ ዩኒሴፍ በዘገባው እንደሚለው የዕለት ተዕለት የጤና አገልግሎቶች በወረርሽኙ ምክንያት ከመጎደታቸው አኳያ የቤተሰብ እቅድ፣ ከወሊድ በፊትና በኋላ የሚኖር የጤና ክትትል እንዲሁም የህፃናት የክትባት ሁኔታዎች በወረርሽኙ ምክንያት ይበልጥ ከባድ ሊሆኑ እንደሚችሉ ገልጿል፡፡
ወረርሽኙ ባለፉት አስርት ዓመታት የህፃናትን ሞት ለመቀነስ የተደረጉትን አበረታች እንቅስቃሴዎች ወደኋላ የመመለስ ስጋት እንደሚኖረው የሚያነሳው ድርጅቱ ይህን አደጋ በስፋት በመገንዘብ ከመቼውም ጊዜ በላይ የጤና አገልግሎቱን መደገፍ ወሳኝ እንደሚሆን ያስረዳል፡፡ አሁን የተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽ አለማችን ለመጨረሺያ ጊዜ ካስተናገደችው የሁለተኛ አለም ጦርነት መዓት በኋላ ሌላኛው ፈተና መሆኑን የሚናገሩት በእንግሊዛ የዩኒሴፍ ዋና ዳይሬክተር ሳቻ ዳሽሞክ በቫይረሱ ተዘዋዋሪ ተፅዕኖ የተነሳ ብዙ ህፃናት መከላከል በሚቻሉ ምክንያቶች ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ ያስረዳሉ፡፡ እንደሳቸው ገለፃ ከሆነ ከወረርሽኙ ጋር ተያይዞ ህፃናት ድጋፍ የሚያገኙበት ሁኔታ መሳሳቱ፣ ድንበሮች መታገዳቸው፣ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸው እና የምግብ አቅርቦት ሁኔታው አደጋ ላይ መውደቁ የችግሩ ስፋት ጥልቅ እንዲሆን ዋና ምክንያት ናቸው ይላሉ፡፡
በድርጅቱ ትንተና መሰረት ሊያጋጥም ይቸላል የሚባለው አደጋ በመጠኑ (optimistic scenario) ሲታይ የጤና አገልግሎቱን በ15 በመቶ በመቀነስ የህፃናትን ሞት በ9.8% ከፍ የሚደርገው ሲሆን፤ የእናቶችን የሞት መጠን ደግሞ 8.3% በማድረስ በየቀኑ 1,400 የሚሆኑ ህፃናት ህይወታቸውን እንዲያጡ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ በሌላ በኩል አደጋው በከባድ ሁኔታ ሲታይ (worst-case scenario) በወረርሽኙ ምክንያት የጤና አገልግሎቱ በ45 በመቶ በመቀነስ የህፃናቱን የሞት መጠን ወደ 44.7% ሊያደርሰው እንደሚችል እና የእናቶችም የሞት መጠን ወደ 38.6% ከፍ ሊል እንደሚችል በዘገባው ገልጿል፡፡
ይህ አደጋ አንዣቦባቸዋል የሚባሉት ሃገራት የጤና ስርዓታቸው እጅግ ደካማ ነው ሊባል ባይችልም ከሌሎች ተያያዥ ውስጣዊ ችግሮች ጋር ተያይዞ ለአደጋው ተጋላጭ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡ ከእነዚህ ሃገራት መካከል ባንግላዲሽ፣ ብራዜል፣ ፓኪስታን እና ኡጋንዳ በወናነት የሚጠቀሱ ሲሆን፤ ኢትዮጵያም ለአዳገው ተገላጭ ከሆኑት ሀገራት ማካከል አንደኛዋ ነች፡፡
The Guardian