TechIn2
1.22K subscribers
1.47K photos
1 video
120 files
500 links
Technology & Innovation Institute (TechIn2), Ethiopia

የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢኒስቲትዩት

ጠቃሚና ወቅታዊ የሆኑ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ፈጠራ፣ ጤና እና ሰብአዊ-ኣቅም ግንባታ(Human Development)መረጃዎችንና ምክሮችን በየእለቱ እናደርሶታለን።
Download Telegram
በቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ተመራማሪዎች የተሰራ ሳኒታይዘር በማከፋፈል ላይ ነው
=====================
በኢንስቲትዩታችን ባሉ ተመራማሪዎች አማካኝነት ተሰራው ይህ የእጅ ንፅህና መጠበቂያ (ሳኒታይዘር) የዓለም የጤና ድርጅት ባስቀመጠው ቀመር መሰረት የተሰራ ነው፡፡
በሀገራችንም በግለሰብ እንዲሁም በተቋም ደረጃ በሽታውን ለመከላከልና ስርጭቱንም ለመቀነስ አቅም ያለው በገንዘብ እውቀት ያለው በእውቀቱ ለወገኑ አለው በማለት የሰባዊነትና የዜግነት ግዴታዉን እየተወጣ ይገኛል፡፡ ተቋማችን የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩትም በሽታው በሀገራችን ገባ ከተባለበት ስዓት ጀምሮ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ የስልክ መተግበሪያ (አፕሊኬሽን) በመስራት፣ በሀገራችን እንዲሁም በአለም ላይ ስለ በሽታው ወቅታዊ የሆኑ ዜናዎችንና መከላከያ መንገዶችን የሚጠቁሙ መረጃዎችን በማሰራጭት፣ አቅም ለሌላቸው ወገኖች ደግሞ የተቋሙ ሰራተኞች የአንድ ወር ደሞዛቸውን ከ1.3 ሚሊዬን ብር በላይ ሲለግሱ፤ አሁን ደግሞ ራሳቸውን ከበሽታው ይጠብቁ ዘንድ በተቋሙ ተመራማሪዎች የተመረተውን የእጅ ማፅጃ (ሳኒታይዘር) ለሰራተኞቹ እያከፋፈለ ይገኛል፡፡ በቀጣይም ይህንን ወረርሽን በሀገራዊ ፍቅር ስሜት በእውቀት በመዋጋት የበኩሉን እንደሚወጣ ተቋሙ ያስታውቃል፡፡
በኮቪድ 19 ዙርያ የተሰሩ የፈጠራ ስራዎች ተመርጠው ቀረቡ
======================
በሀገራችን ካለው የኮቪድ 19 ስርጭት ጋራ በተያያዘ የተሰሩት የፈጠራ ፕሮፖዛሎች ዛሬ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በውድድሩ አጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥ በሶስት የማጣርያ ዙሮች ተጣርተው ያለፉ 30 ፈጠራዎች ዝርዝር ውድድሩ የሚያስተናብረው የብሄራዊ የኢኖቬሽን ግብረ ኃይል አስተባባሪ በሆኑት አቶ አዲሱ ማሞ አማካኝነት ቀርቧል፡፡
በውይይቱ ጅማሮ የስራውን የእስካሁን ሂደት አስመልክቶ የቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክረተርና የዚህ ግብረ ኃይል መሪው አቶ ሙሉቀን ቀሬ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡በሪፖርታቸውም 446 የፕሮጀክት ፕሮፖዛሎች መቅረባቸውን ገልፀው ከነዚህም ውስጥ 43 በመቶው ለምርት የተዘጋጁ፣ 31 በመቶው የተለያዩ የማበልፀጊያ ስራዎችን የሚሹ ሰርቶ ማሳያዎች እንዲሁም 26 በመቶው በሀሳብ ደረጃ ያሉ መሆናቸውን አስቀምጠዋል፡፡ ከፈጠራዎቹ ግማሽ ያህሉም የሶፍትዌር እና የሞባይል መተግበሪያዎች መሆናው እንዲሁም በአጠቃላይ ከተመዘገቡት ውስጥም በአንፃራዊነት ጥቂቶቹ የተሸለ ሀሳብ ይዘው መምጣታቸው በሪፖርታቸው ተካቷል፡፡
ፈጠራዎቹ የመተንፈሻ ማሽኖች፣ የእጅ መታጠቢያ፣ የሶፍትዌር ስራዎችን ጨምሮ በስድስት የተለያ ዘርፎች ተከፋፍለው ነው የቀረቡት፡፡ ከቀረቡት ስራዎች መካከልም የእጅ መታጠቢያ ላይ ያተኮሩ ፈጠራዎች፣ ካሉበት በመሆን ትምህረትን መከታተል የሚያስችል የስልክ መተግበሪያ ስርዓት፣ የኮቪድ-19 መከታተያ ስርዓት እና ሌሎች ምርቶችም ይገኙበታል፡፡
ዛሬ በቀረቡት ስራዎች ላይ በተሰበሰቡት ታዳሚያን በተለይ በሚሰጠው የድጋፍ አይነት እና ለየትኞቹ ፈጠራዎች ድጋፍ መደረግ እንዳለበት ከተሳታፊው ጥያቄና አስተያየቶች ተነስተው በአቶ አዲሱ እና አቶ ሙሉቀን አማካኝነት ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
የፈጠራ ስራዎቹን የሚገመግመው ከቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ኢኖቬተርስ አሶሴሽን፣ የኢትዮጵያ ባዮቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ የተውጣጡ 25 ባለሙያዎች ያሉት ቴክኒክ ቡድን ነው፡፡
ቬንትሌተር እና ሌሎች የፈጠራ ስራዎችን ያበረከተው ወጣት
=================================
የኮቪድ 19 ወረርሽኝ በሃገራችን ከገባ ወዲህ የስርጭት መጠኑን ለመቀነስ የሚያግዙ የተለያዩ ፈጠራዎች በወጣቶች እና በቴክኖሎጂ ተቋማት እየተሰሩ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ዩሃንስ ኪዳኔ መሰል የፈጠራ ስራዎችን በመስራት ላይ የሚገኝ የፈጠራ ባለሙያ ሲሆን መደመር የፈጠራ ስራዎች በተባለ ድርጅት ውስጥም በግልና በህብረት እየተንቀሳቀሰ ያለ ባለሙያ ነው፡፡
ወጣቱ በኮቪድ 19 ዙሪያ ትኩረታቸውን ያደረጉ ከአምስት በላይ ፈጠራዎችን በግሉ እና ከሌሎች ተቋማት ጋር በትብብር የሰራ ሲሆን፤ ከኮቪድ 19 ውጭ ያሉ ሌሎች ብዙ ፈጠራዎችም ከድርጅቱ ጋር በመሆን እንደሰራ ተናግሯል፡፡ ከስራዎቹ መካከል በኤሌክትሪክና በባትሪ የሚሰራ ቬንትሌተር፣ የእጅ ንክኪ የማያስፈልገው መታጠቢያ፣ በባንኮች አካባቢ የሚቀመጥ የእስኪቢርቶ ማስቀመጫ ዋና ዋናዎቹ ፈጠራዎች ሲሆኑ፤ ከዚያ በተጨማሪም የእግር መጠራረጊያ፣ ሳቢነት ያለው የግንዛቤ መስጫ ቦርድ በሽታውን ለመከላከል ከሰራቸው ስራዎች መካካል የሚመደቡ ናቸው፡፡
የፈጠራ ባለሙያው ቬንትሌተሩን ሲሰራ በሰው አገዛ ብቻ የሚሰራውን ሜካኒካል መሳሪያ በቀላል ግብዓቶች በመጠቀም በራሱ የሚንቀሳቀስ እና በኤሌክትሪክ ወይም በባትሪ እንዲሰራ ያደረገው ቢሆንም ከሌሎች የጤና በለሙያዎች ጋር በመተባባር ጥራቱ የሚጨምርበት እና የተሻለ ግልጋሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ ለማድረግ በጥረት ላይ መሆኑን ገልፆልናል፡፡ የፈጠራ ባለሙያው ከቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር በአራዳ ክፍለከተማ በሚገኘው የፒያሳ አውቶብስ ማቆሚያ ቦታ ላይ የሰራው የግንዛቤ መስጫ ቦርድ ሌላው ፋጠራው ሲሆን፤ ከዚህ በኋላም ከሌሎች ተባባበሪ አካላት ጋር በመሆን ተጨማሪ ስራዎችን ለመቅረብ እንደሚሞክር ግልፆልናል፡፡
በኮሮናቫይረስ ዙሪያ የሚሰሩ ኢኖቬሽን ተኮር የምርምርና የፈጠራ ስራዎች ቫይረሱን ለመከላከል በሚደረገው ሁለንተናዊ ጥረት ትልቅ ጥቅም እንዲሰጡ ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተሰናስሎ መስራት እጀግ አስገፈላጊ እንደሚሆንም ባለሙያው ያስረዳል፡፡
የዩሃንስ ኪዳኔን የፈጠራ ስራዎች ሙሉ ማብራሪያ በቅርቡ በቪዲዮ የምናቀርብ ይሆናል፡፡
የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል በኢትዮጵያ ሊገነባ ነው
=================================
ቦሌ በሚገኘው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ዋና ፅ/ቤት ፕሮፌሰር ሂሩተ ወ/ማርያም የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚንስትር እንዲሁም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚንስትር ዶ/ር አብርሃም በላይና ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር የጋራ ስምምነት ሰነድ ተፈራርመዋል፡፡
የስምምነቱ ዋና አላማ የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል ማቋቋም፤ በኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ ዘርፍ የጋራ ምርምር ለማካሄድ፤ በማስተርስና ፒኤችዲ ደረጃ የኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ ዘርፍ ትምህርት ለመክፈት እንዲሁም ለሃገር እድገት ጠቃሚ በሆኑ ሌሎች የስፔስ ሳይንስ ምርምር ዘርፎች ዙሪያ ተባብሮ ለመስራት የሚያስችል ስምምነት እንደሚሆን ተገልጿል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ የመጀመሪያ የሆነው የሳተላይት ፋብሪካ፣ መገጣጠሚያና ሙከራ ማዕከል ፕሮጀክት ሶስት ዓመት የሚፈጅ ሲሆን ፤ እስከ 500ኪ.ግ የሚመዝኑ ሳተላይቶችን ለማምረት የሚያስችል እንደሆነ ዶ/ር ይሹሩን አለማየሁ በኢ.ስ.ሳ.ቴ.ኢ ስፔስ ኢንጂነሪንግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተርና የፕሮጀክቱ ተቆጣጣሪ ጠቁመዋል፡፡ 50 ሚሊየን ዩሮ በሚፈጀው ፕሮጀክት 25 ሚሊየን ዩሮዉን የአዉሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ የሚሸፍን ይሆናል፡፡ የተቀረዉን ደግሞ የፈረንሳዩ አርያን ግሩፕ ለሳተላይት ቴክኖሎጂ ማምረቻ የሚሆኑ ማሽኖችን በማቅረብ እንዲሁም በኢትዮጵያ መንግስት በአይነቱ ልዩ የሆነ እና ለሳተላይት ማምረቻ ምቹ የሆነ ማዕከል በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ዉስጥ የሚገነባ ይሆናል፡፡
ኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት
የኮሮናቫይረስ በጤና አገልግሎቱ ላይ በሚያሳርፈው ከፍተኛ ተፅዕኖ ምከንያት 6,000 ህፃናት በየቀኑ ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ Unicef አስታወቀ
=======================
የኮሮናቫይረስ በሚያስከትላቸው ተያያዥ ችግርች እና የጤና አገልግሎት መዳከም ጋር ተያይዞ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት ውስጥ ስድስት ሺ የሚጠጉ ህፃናት በየቀኑ ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችል የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት አሳስቧል፡፡ ዩኒሴፍ በዘገባው እንደሚለው የዕለት ተዕለት የጤና አገልግሎቶች በወረርሽኙ ምክንያት ከመጎደታቸው አኳያ የቤተሰብ እቅድ፣ ከወሊድ በፊትና በኋላ የሚኖር የጤና ክትትል እንዲሁም የህፃናት የክትባት ሁኔታዎች በወረርሽኙ ምክንያት ይበልጥ ከባድ ሊሆኑ እንደሚችሉ ገልጿል፡፡
ወረርሽኙ ባለፉት አስርት ዓመታት የህፃናትን ሞት ለመቀነስ የተደረጉትን አበረታች እንቅስቃሴዎች ወደኋላ የመመለስ ስጋት እንደሚኖረው የሚያነሳው ድርጅቱ ይህን አደጋ በስፋት በመገንዘብ ከመቼውም ጊዜ በላይ የጤና አገልግሎቱን መደገፍ ወሳኝ እንደሚሆን ያስረዳል፡፡ አሁን የተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽ አለማችን ለመጨረሺያ ጊዜ ካስተናገደችው የሁለተኛ አለም ጦርነት መዓት በኋላ ሌላኛው ፈተና መሆኑን የሚናገሩት በእንግሊዛ የዩኒሴፍ ዋና ዳይሬክተር ሳቻ ዳሽሞክ በቫይረሱ ተዘዋዋሪ ተፅዕኖ የተነሳ ብዙ ህፃናት መከላከል በሚቻሉ ምክንያቶች ህይወታቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ ያስረዳሉ፡፡ እንደሳቸው ገለፃ ከሆነ ከወረርሽኙ ጋር ተያይዞ ህፃናት ድጋፍ የሚያገኙበት ሁኔታ መሳሳቱ፣ ድንበሮች መታገዳቸው፣ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸው እና የምግብ አቅርቦት ሁኔታው አደጋ ላይ መውደቁ የችግሩ ስፋት ጥልቅ እንዲሆን ዋና ምክንያት ናቸው ይላሉ፡፡
በድርጅቱ ትንተና መሰረት ሊያጋጥም ይቸላል የሚባለው አደጋ በመጠኑ (optimistic scenario) ሲታይ የጤና አገልግሎቱን በ15 በመቶ በመቀነስ የህፃናትን ሞት በ9.8% ከፍ የሚደርገው ሲሆን፤ የእናቶችን የሞት መጠን ደግሞ 8.3% በማድረስ በየቀኑ 1,400 የሚሆኑ ህፃናት ህይወታቸውን እንዲያጡ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ በሌላ በኩል አደጋው በከባድ ሁኔታ ሲታይ (worst-case scenario) በወረርሽኙ ምክንያት የጤና አገልግሎቱ በ45 በመቶ በመቀነስ የህፃናቱን የሞት መጠን ወደ 44.7% ሊያደርሰው እንደሚችል እና የእናቶችም የሞት መጠን ወደ 38.6% ከፍ ሊል እንደሚችል በዘገባው ገልጿል፡፡
ይህ አደጋ አንዣቦባቸዋል የሚባሉት ሃገራት የጤና ስርዓታቸው እጅግ ደካማ ነው ሊባል ባይችልም ከሌሎች ተያያዥ ውስጣዊ ችግሮች ጋር ተያይዞ ለአደጋው ተጋላጭ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡ ከእነዚህ ሃገራት መካከል ባንግላዲሽ፣ ብራዜል፣ ፓኪስታን እና ኡጋንዳ በወናነት የሚጠቀሱ ሲሆን፤ ኢትዮጵያም ለአዳገው ተገላጭ ከሆኑት ሀገራት ማካከል አንደኛዋ ነች፡፡
The Guardian
ኮሮናቫይረስ ከሰዎች ጋር ለረዥም ጊዜ ሊኖር ይችላል
=================================
የአለም አቀፉ የጤና ድርጅት በትላንትናው እለት በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ በኮቪድ 19 ወረርሽኛ ዙሪያ ወደፊት በሚጠበቁ ሁነቶች እና ተያያዥ ምልከታዎች ላይ ሰፊ ገለፃ ሰጥቷል፡፡ በዕለቱ በነበረው የጋራ መግለጫ የተቋሙ ኢመርጀንሲ ዳይሬክተር ዶ/ር ማይክ ርያን ከወረርሽኙ የወደፊት እጣፋንታ ጋር በተያያዘ እንደተናገሩት ምንም እንኳን ለበሽታው የሚሆን ክትባቶች በቅርብ ጊዜ ሊደርሱ ቢችሉም፤ ቫይረሱን ለመቆጣጠር የሚያስፈልገው አቅም ግን እጅግ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
ወረርሽኙ በአለም አቀፍ ደረጃ 4.3 ሚለዮን ሰዎችን በማጥቃት ለ300,000 ሰዎች ደግሞ የሞት ምክንያት በሆነበት በአሁን ወቅት ብዙዎች ለጭንቀት እና ለአዕምሮ ህመም የመጋለጥ እድል እንደሚኖራቸው በመገንዘብ ሁሉም መንግስታት ለአዕምሮ ጤና የሰጡትን ትኩረት ማሳደግ እንደሚገባቸውም ድርጅቱ በመግለጫው አሳስቧል፡፡ የኮሮናቫይረስ ከዚህ ቀደም በማህበረሰባችን እንደተከሰቱት ሌሎች ቫይረሶች ሁሉ ከሰዎች ጋር ለረዥም ጊዜ ሊቆይ እንደሚችል መገንዘብ ያስፈልጋል የሚሉት ዶ/ር ማይክ ርያን፤ ኤች አይ ቪ ከሰዎች ጋር የሚኖርበትን ሁኔታና ሰዎችም ለቫይረሱ የሚሰጡትን ምላሽ እንደምሳሌ እንስተው ያስረዳሉ፡፡
አሁን ላይ በስፋት እየተነገረ እንደሚገኘው ቢያንስ 100 የሚጠጉ የኮሮናቫይረስ ክትባቶች የተለያዩ ሙከራዎችን በማለፍ በጥሩ ደረጃ ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡ ይሁንና እንደ ዶ/ር ማይክ ርያን ገለፃ አሁን ላይ የትኛውም አካል ቫይረሱ የሚጠፋበትን ትክከለኛ ጊዜ በእርግጠኝነት ማወቅ እንደማይችል እና ምናልባት የኩፍኝ በሽታ ክትባት ተገኘቶለት እንኳን ከሰዎች ጋር ለረዥም ጊዜ እንደቆየ ሁሉ የኮሮናቫይረስም እንዲሁ ከሰዎች ጋር ለረዥም ጊዜ ሊዘልቅ እንሚችል መገንዘብ አስፈላጊ ነው ይላሉ፡፡ ዶ/ር ርያን ይህን ሃሳብ በመግለጫው ላይ ቢያነሱም የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም እየተደረጉ ያሉ እርምጃዎች እና ጥንቃቄዎች አሁን ካለው ተጠናክረው ቢቀጥሉ ወረርሽኙን ለማቆም አሁንም እድል እንዳለ ይናገራሉ፡፡
ብዙ ሃገራት ወረርሽኙን ለመቆጣጠር የወሰዱትን ትልልቅ እርምጃዎች በመጠኑም ቢሆን እያላሉ እና የቆመውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ወደነበረበት ለመመለስ እየጣሩ የሚገኝ ቢሆንም፤ የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ግን ይህ ሁኔታ ለሌላ አደጋ ሊያጋልጥ እንደሚችል ያስጠነቅቃሉ፡፡ ሃገራት እየወሰዷቸው የነበሩ እርምጃዎች እያቀለሉ መምጣታቸው የሚመከር አይደለም የሚሉት ዋና ዳይሬክተሩ በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥም ሆነን ቫይረሱን የምንቆጣጠርበትን መንገድ መፈለግ እጅግ የሚበጅ ነው ይላሉ፡፡
ቢቢሲ
CDC ኮሮናቫይረስ በህፃናት ላይ ሊያስከትል ስለሚችለው ከባድ የጤና ቀውስ እያስጠነቀቀ ነው
=================================
የአሜሪካው የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ መዕከል (CDC) በትላንትናው ዕለት ለብዙ ሺ የሃገሪቱ ዶክተሮች በሰጠው ማስጠንቀቂያ ከኮቪድ 19 ጋር ተያይዞ ህፃናት ላይ ሊከሰቱ ስለሚችሉ የተለያየ የበሽታ ምልክቶች ወይም (syndromes) በሚገባ እንዲያጤኑ እና በትኩረት እንዲከታተሉ ጥሪ አስተላልፏል፡፡ በህፃናት ላይ ሊታይ ይችላል የሚባለው ይህ ሲንድረም multisystem inflammatory syndrome (MIS-C) ተብሎ የሚታወቅ ሲሆን በአውሮፓ በተለያዩ ሀገራት እና በአሜሪካ በ18 ግዛቶች ሊገኝ እንደቻለም ተገልጿል፡፡
በእንግሊዝ የሚገኙ የህክምና ባለሙያዎች ይህን መሰሉን ሲንድረም ለመጀመሪያ ጊዜ ያጤኑት በሚያዚያ ወር መጀመሪያ ላይ ቢሆንም ከሶስትና ከአራት ሳምንታት በኋላ ቁጥሩ አይሎ በሌሎች ሃጋራት እየተስተዋለ መምጣቱም ተነግሯል፡፡ በቦስተን የጤና ትምህርት ቤት እና የህፃናት ህክምና ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ጄፍሪ በርንስ እንደሚያስረዱት ከአምስትና ከስድስት ሳምንታት ቢፊት ጉዳዩን ስንምለከተው በባክቴሪያ የተመረዘ የሰውነት ጥቃት (toxic shock) መስሎን የነበረ ቢሆንም፤ ቆይቶ ግን ቁጥሩ እየጨመረና ሌላ መለክ እየያዘ መምጣቱን ተረድተናል ብለዋል፡፡ ይህ ሲንድረም Kawasaki ተብሎ ከሚታወቀው ተያያዥ የህፃናት በሽታ ጋር በብዛት ቢመሳሰልም በህፃናት ላይ ከሚኖረው ከባድ የጤና ቀውስ አንጻር በጥንቃቄ ሊታይ እንደሚገባው CDC ያስገነዝባል፡፡
ተቋሙ በኒውዮርክ አገኘኋቸው የሚላቸውን 110 ተመሳሳይ የሲንድረም ኬዞች በመጥቀስ በጉዳዩ ላይ የሚያደርገውን ተጨማሪ ምርመራ እስከሚያጠናክር የጤና ባለሙያዎች ከኮቪድ 19 ጋር በተያያዘ በህፃናት ላይ የሚመለከቷቸውን ተቀራራረቢ ምልክቶች በሚገባ እንዲያጤኑ እና መረጃዎችንም ለጤና ተቋማት እንዲልኩ አሳስቧል፡፡ ይህ ሲንድረም በሰውነታችን ውስጥ በሚከሰቱ ጎጂ ተህዋሲያን (pathogens) የተነሳ በአካላችን የሚሰጡ ባዮሎጂካል ምላሾችን የሚሳይ ሲሆን፤ ትኩሳት ተቅማጥ እና ሌሎች ተያያዥ ምልክቶች በስፋት የሚታዩበት ነው፡፡ ሲንድረሙ በተለይም የተለያዩ የሰውነት ክፈሎች ስራቸውን በትክክል እንዳይከውኑ ሊያደርጋቸው ሲለሚችል የሰውነት መቆጣት እና እብጠት አልፎ አልፎ ሊታይ እንደሚችል ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ይህ አይነቱ ሲንድረም በህፃናት ላይ አልፎ አልፎ የሚከሰት ቢሆንም በልጆች ላይ የሚኖረው ከባድ የጤና ቀውስ ከፍተኛ በመሆኑ ተያያዣ ምልክቶች የሚታዩባቸውን ህፃናት ተኝተው እንዲታከሙ በማድረግ፣ እንደ Kawasaki ያሉ በሽታዎች የታዩባቸውን ህፃናት በሚገባ በመከታተል እና ከዚህ በፊት በዚህ ሲንድረም ተይዘው የሞቱ ካሉ በመመርመር አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ ተቋሙ ያስገንዝባል፡፡
ምንጭ፡ CNN እና Healthy Children
የሁዋዌይ የኢትዮጵያ ሀላፊ በቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንስቲትዩት ተገኝተው በጋራ በሚሰሩባቸው ጉዳዮች ዙርያ ተወያይተዋል
===================
በኢትዮጵያ የሁዋዌይ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ቻርለስ ዲንግ እና የአካውንት ማናጀሯ ወ/ሮ ሰላም አብረሀም በቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኢንቲትዩት ተገኝተው በጋራ ሊሰሩባቸው በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙርያ ውይይት አድርገዋል፡፡ በውይይቱ መግቢያ ስለ ኢንስቲትዩቱ አጠቃላይ ገፅታ የሴክተር ሞደርናይዜሽን ዳይሬክተር በሆኑት አቶ በረከት ገለፃ የተደረገላቸው ሲሆን ሁለቱ ተቋማት በትብብር ሊሰሩባቸው የሚችሉባቸው ተግባራትም በገለፃው ተካቶ ቀርቧል፡፡
ሁዋዌይ በኢትዮጵያ በተለያዩ ስራዎች ላይ ያለውን ተሳትፎና በተለይም የዳታ ሴንተሮች ግንባታና ለተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተሰጡና በመሰጠት ላይ ያሉ ስልጠናዎችን አቶ ቻርለስ ዲንግ እና ወ/ሮ ሰላም አብረሀም በውይይቱ ወቅት ያብራሩ ሲሆን ከኢንስቲትዩቱ ጋራም ወደፊት በትብብር ለመስራት ያላቸውን ፍቃደኝነት ገልፀዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የሙቀት መለኪያ መሳርያ፣ የፊት መሸፈኛ ጭንብል እና ሳኒታይዘሮችን ለመለገስ ቃል ገብተዋል፡፡
የኢንስቲትቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳንዶካን ደበበ በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ በጥቂት ጊዜያት ውስጥ ለተለያዩ ችግሮች ቴክኖሎጂያዊ መፍትሄ የሚሰጡ ስራዎችን ለብዙ ሀገር አቀፍ ተቋማት ሰርቶ ማስረከቡን ለእንግዶቹ አስረድተዋል፡፡ አያይዘውም ሁዋዌይ ግንባር ቀደም የቴክኖሎጂ ኩባንያ ከመሆኑም ባሻገር ለታዳጊ ሀገራት አጋር ሆኖ እየሰራ መሆኑን ገልጸው ከኩባንያው ጋራ ኮቪድ-19ኝን ጨምሮ በኢኖቬሽን ማዕከላት እንዲሁም በዲጂታላይዜሽን ረገድ ያለውን ልዩነት ለማጥበብ ታልሞ በተቀረፀው የቴክ ፎር ኦል ፕሮጀክት ዙርያና ሌሎችም የትብብር መስኮች ኢንስቲትዩቱ በጋራ መስራት እንደሚፈልግ ተናግረዋል፡፡