TechIn2
1.22K subscribers
1.47K photos
1 video
120 files
500 links
Technology & Innovation Institute (TechIn2), Ethiopia

የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢኒስቲትዩት

ጠቃሚና ወቅታዊ የሆኑ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ፈጠራ፣ ጤና እና ሰብአዊ-ኣቅም ግንባታ(Human Development)መረጃዎችንና ምክሮችን በየእለቱ እናደርሶታለን።
Download Telegram
ብሪታንያ አዳዲስ የሁዋዌይ ምርቶች በ5ጂ ስርዓቷ ውስጥ እንዳይገቡ አገደች
========================
ብሪታንያ ከቻይናው የሁዋዌይ ቴክኖሎጂስ የሚመጡ የ5ጂ ስርዓት ግብዓቶችን ከቀጣዩ መስከረም መጠናቀቂያ አንስቶ እንደምታግድ አስታወቀች፡፡ እገዳው የሀገሪቱን የገመድ አልባ በይነ መረብ ግንኙነት ተሳታፊ ተቋማትን ለማብዛት ያለመው የ333 ሚሊዮን ዶላር እንቅስቃሴ አካል ነው፡፡
በሐምሌ ወር በቻይናዋ ሸንዘን መቀመጫውን ያደረገው ግዙፉ የቴክኖሎጂ ተቋም ሁዋዌ በአውፓውያኑ 2027 ከእንግሊዝ የቀጣዩ ትውልደ ተንቀሳቃሽ ግንኙነት እንደሚታገድና ግዢዎችም ከ2021 አንስቶ ዝግ እንደሚሆኑ አስታውቆ ነበር፡፡ አሁን ላይ ከነዚህ እገዳዎች ጋራ ተጣጥሞ ለመስራት በሀገሪቱ የሚንቀሳቀሱ የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ተቋማት ከሁዋዌይ የሚመጡ ግብዓቶችን መጠቀም ለማቆም የሚገደዱ ቢሆንም እገዳው አሁን ተዘርግቶ ያለውን ስርዓት እንዲያድሱ ስለሚፈቅድላቸው ለዚህ እንዲሯሯጡ ያደርጋቸዋል ተብሏል፡፡
እገዳው በደህንነት ስጋቶችን ምክንያት በማድረግ አጋር ሀገራት ሁዋዌይን ከስርዓታቸው ያግዱ ዘንድ ከአሜሪካ የቀረበውን ጥሪ ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ቀድሞ የብሪታንያ ኃላፊዎች ድርጅቱ መቆጣጠር የሚችሏቸው አነስተኛ ስጋቶች ምንጭ ሊሆን እንደሚችል የገለፁ ቢሆንም አሁን ላይ ግን ከዚህ አቋማቸው በማፈግፈግ የአሜሪካንን እርምጃ ሊደግፉ ችለዋል፡፡ በዚህም ሳብያ የብሪታንያ ቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ተቋማት የሁዋዌ እገዳን ተከትሎ ትላልቅ ኮንትራቶችን ባሸነፉት በሁለቱ የስካንዲኔቪያ ቴክኖሎጂ ተቋማት ኖኪያ እና ኤሪክሰን ላይ ጥገኛ የሚሆኑ ይሆናል፡፡
ሆኖም ይህን የሁለት ተቋማት የገበያ ቁጥጥር ይቀንስ ዘንድ የሀገሪቱ መንግስት በተወዳዳሪዎች መካከል ፉክክርን ለማጎልበት እና ደህንነት ላይ ጥናት ለማድረግ ያለመውን ብሄራዊ የቴሌኮም ቤተ-ሙከራ በአውሮፓውያኑ 2022 የሚያቋቁም ሲሆን ተፎካካሪ የመሆን እምቅ አቅም ያላቸው እንደ ጃፓኑ ኤን.ኢ.ሲ ያሉ ድርጅቶችንም ይደግፋል፡፡ ቀድሞ አገልግሎት ላይ የነበሩ የ2ጂ እና 3ጂ ቴክኖሎጂዎችን ከአገልግሎት የማስወጣቱ እርምጃም የተፎካካሪ ተቋማት ብዝሀነትን እንደሚያፋጥን መንግስት ተናግሯል፡፡
እንደ ጥናቶች ከሆነ ዓለም አቀፍ የራዲዮን አክሰስ ኔትዎርክ (RAN) ገበያ 80 በመቶው በኖኪያ፣ ኤሪክሰን እና ሁዋዌይ ቁጥጥር ሰር የዋለ ሲሆን ሌላው በብሪታንያ ከፍተኛ የደህንነት ስጋትነት እየተፈረጀ ያለው ዜድ.ቲ.ኢ ደግሞ 11 በመቶ ደግሞ ድርሻን ወስዷል፤ ሳምሰንግም በዚህ ውስጥ የ5 በመቶ ድርሻ አለው፡፡ ታድያ እነዚህን ግዙፍ የቴክኖሎጂ ተቋማት ሊፎካከሩ ይችላሉ ከተባሉት ውስጥ ኤን.ኢ.ሲ፣ ፉጂትሱ፣ ፓራለል ዋየርለስ እና ሜቪኒር ሲስተምስ ተጠቅሰዋል፡፡
ምንጭ፡ Bloomberg
የቻይናዋ ባህር ሰርጓጅ መርከብ በምድራችን ጥልቁ ስፍራ መድረስ ቻለች
*************************
ፌንዲዢ የተሰኘችው የቻይና ባሕር ሰርጓጅ መርከብ ወደታች ወደ ባሕር 10,909 ሜትር ጠልቃ በመግባት ምድራችን ካሏት ጥልቅ ስፍራዎች ውስጥ አንዱ ወደሆነው ማሪያና ትረንች ግርጌ ለመድረስ ችላለች፡፡ ካሳለፍነው መስከረም 30 2013 ዓ.ም አንስቶ ለአንድ ወር በቆየው የውሃ ውስጥ ቆይታዋ ፌንዲዢ 11 ያህል በምዕራባዊ ሰላማዊ ውቅያኖስ በሚገኘው የምድራችን ጥልቁ ስፍራ ማሪያና ትረንች ግርጌ የመጥለቅ ጉዞን አከናውናለች፡፡ ከነዚህ ጉዞዎች ውስጥ ስምንቱ ከ10 ኪ.ሜ (10,000 ሜትር) ያለፉ ናቸው፡፡ ሆኖም ከማንም በላይ ወደ ባህር ጠልቆ በመግባት ከወራት በፊት በቪክቶር ቬስኮቮ የተያዘውን የ10,934 ሜትር ጥልቀት ክብረ ወሰን መስበር አልቻለችም፡፡ በታዋቂው የፊልም ዳይሬክተር ጀምስ ካሜሮን በአውሮፓውያኑ 2012 ያስመዘገበውን የ10,908 ሜትር ጥልቀት ግን ማለፍ የቻለች ሲሆን በአውሮፓውያኑ 1960 የ10,912 ሜትር ጥልቀትን ማስመዝገብ ከቻለችው ትሪኤስት ስዊዘርላንድ-ጣልያን-አሜሪካዊቷ ባሕር ሰርጓጅ መርከብም በሦስት ሜትር ብቻ ያነሰ ሆኗል፡፡
መርከቧና በውስጧ የያዘቻቸው አባላት በባህር ውስጥ ቆይታቸው እንደ ታይፉን፣ ዝናብ እና ከፍተኛ ሙቀት ያሉ የተፈጥሮ ክስተቶችን ማለፋቸው ተዘግቧል፤ በማሪያና ትረንች ማስመዝገብ የቻሉት ጥልቀትም ይህን ለማሳካት ከአስር ዓመት በላይ የዘለቀ ጊዜን ብሎም ሐብት ላፈሰሰችው ቻይና ብሄራዊ ኩራትን ያጎናጸፈ ሆኗል፡፡ በሀገሪቱ የመጀመሪያዋ የጥልቅ ባህር ሰርጓጅ መርከብ ጂአዎሎንግ የዛሬ አስር ዓመት ገደማ 3,759 ሜትር ወደ ባሕር ጠልቃ መግባት ችላ ነበር፡፡ ይህም ቻይናን እንደ አሜሪካን፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያና ጃፓንን ካሉት ከ3,500 ሜትር በላይ መጥለቅ የሚችሉ የባህር ሰርጓጆች መርከቦች ባለቤት ሀገራት ዝርዝር ውስጥ ያስቀመጠ ስኬት ነው፡፡
የመርከቧ ተሳፋሪ ተመራማሪዎቹ ከባህሩ ወለል ላይ የተለያዩ የአለት ባዮሎጂያዊ እና ሌሎች ናሙናዎችን መሰብሰብ ችለዋል፤ መርከቧም ባሳለፍነው ቅዳሜ ህዳር 19 ላይ ሄይናን ግዛት ውስጥ ወሚገኘው ወደብ ተመልሳለች፡፡
ምንጭ፡ Live Science
ደቂቅ ዘአካላት እንደ አማራጭ የታዳሽ ሀይል ምንጭ
**************************
በመደበኛነት ከውሀ፣ ከነፋስ፣ ከፀሐይና ከእንፋሎት ከምናገኘው ታዳሽ ሀይል በተጨማሪ አማራጭ ታዳሽ ሀይልን ከደቂቅ ዘአካት (microorganisms) ማግኘት እንደሚቻል መረጃዎች አመለከቱ፡፡ ተመራማሪዎች በምድራችን የሚገኙ ጥቃቅን ህይወት ያላቸውን ነገሮች ወይም ደቂቅ ዘአካላትን ከተፈጥሯዊ ዑደተ ህይወታቸው በተጨማሪ ለሀይል አማራጭ መሆን የሚችሉበትን መንገድ ለረጅም ጊዜያት ሲያጠኑ ቆይተዋል፡፡ የህም ጥናት የስነ-ህሕወት፣ የሀይል እና የኬሚስትሪ ጥምረት በመሆኑ ተመራማሪዎች bioelectrochemical system ሲሉ ሰይመውታል፡፡ በዚህ ዘገባም እነዚህ ደቂቅ ዘአካላት እንዴት የሀይል አማራጭ መሆን እንደሚችሉ ከscience X ያገኘነውን መረጃ ልናካፍላችሁ ወደናል፡፡
Bioelectrochemical ስልት የተሰኘው ደቂቅ ዘአካላትን ለታዳሽ ሀይልነት የመጠቀም ሂደት በውስጡ Microbial fuel cell (MFC) ክፍል ያለው ሲሆን ይህም እንደ ባትሪ አንድ የአኖድና አንድ የካቶድ መቀበያ ያለው ነው፡፡ ደቂቅ ዘአካላት በአኖድ ክፍል የተለያዩ ነገሮችን በማብላላት ኤሌክትሮኖችን እንዲያስገኙ ደርጋሉ፡፡ በዚህ መንገድ የተገኙት ኤሌክትሮኖች በኤሌክትሪክ አስተላላፊዎች አማካኝነት ከአኖድ (negative electrode) ወደ ካቶድ (positive electrode) የኤሌክትሪክ ሀይልን ለማመንጨት ይፈሳሉ፡፡
ተመራማሪዎቹ ትኩረታቸውን በዚህ ስራ እንዴት ታዳሽ የሀይል አማራጭ እንደሚገኝና ለዚህ አስፈላጊ የሆነን በታላላቅ ሀገራትና ከተሞች የሚገኝን ተረፈ ምርት ወይም ውጋጅን መቆጣጠር የሚቻልበት ሂደት ላይ አድርገዋል፡፡ ለማሳያም በአንድ የቻይና የቢራ ፋብሪካና በሌላ የብራዚል የውሀ ማጣሪያ የሚገኝን ውጋጅ ስራ ላይ ውሏል፡፡ በሁለቱም ሂደቶች ምርምሩ ምንም አይነት ተጨማሪ ሀይል ሳይጠቀም ታዳሽ ሀይልን ማመንጨት ችሏል፡፡
ውጤታማነቱ ከታወቀ በኋላ የተለያዩ ግዙፍ ፋብሪካዎች በተቋሞቻቸው Plant Microbial Fuel Cells (PMFCs) የተሰኘውን ታዳሽ የሀይል አማራጭ የማግኛ ዘዴ መጠቀም የጀመሩ ሲሆን ናሳም ከ2006 ጀምሮ በስራው ላ እየተሳተፈ እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በ2011 ናሳ MFCን በመጠቀም ካርቦንዳይ ኦክሳድን ወደ ኦክስጅን፣ ውሀና ሜቴን ጋዝ ለመቀየር የሚስችል ስምምነት Cambrian Innovation ከተባለ ተቋም ጋር አድርጓል፡፡

አማራጭ ታዳሽ ሀይልን ላማመንጨት ኤሌክትሮኖችን ከህዋሶቻቸው ወደ ኤሌክትሮዶች የሚያስተላልፉ ደቂቅ ዘአካላት Geobacter እና Shewnella የሚባሉት ናቸው፡፡ የመጀመሪያው አይነት በስኩየር ሜትር እስከ 3.9w ሁለተኛው ደግሞ እስከ 4.4 W/m2 የሚደርስ ሀይል ማስገኘት ይችላል፡፡
ናሳ ለህዋ አገልግሎት የሚውል ሀይልን Shewanella oneidensis ከተሰኘ ባክቴሪያ ማመንጨት የቻለ ሲሆን በተጨማሪም ሌሎች እንደ Rhodopseudomonas palustris DX1፣ Candida melibiosica፣ Saccharomyces cerevisiae እና Escherichia coli DH5α ያሉ ደቂቅ ዘአካለት ታዳሽ ሀይልን የማመንጨት አቅም እንዳላቸው ታውቋል፡፡ እነዚህንም እንደ አገልግሎት ከሰጠ ውሀ፣ ኮምፖስት፣ ፍግ፣ ከቆሻሻ፣ ከወንዝ ወይም ሀይቅ ከመሰሉ አካባቢዎች ማግኘት እንደሚቻል ተመራማሪዎች ይገልጻሉ፡፡
ምንጭ Science X
የአልኮል መጠጥና የትኩረት ማጣት
***********************
የአልኮል መጠጦችን ማዘውተር በጭንቅላታችን ውስጥ የሚገኝንና ለነገሮች ትኩረት እንድንሰጥ የሚያደርግን ኬሚካል እንደሚያቋርጥ ጥናቶች አመለከቱ፡፡ በቴክሳስ ጤና ሳይንስ ማእከል የሚገኙ ተመራማሪዎች አልኮል ተጠቃሚዎች እንዴት የትኩረት ማጣት ችግር እንደሚጋጥማቸው የተለያዩ ጥናቶችን ሲደርጉ ቆይተዋል፡፡ በዚህም ጠጭዎች የሚያጋጥማቸው የትኩረት ማጣት ችግር ለሰው ልጆች በነገሮች ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ የሚያስችላቸው norepinephrine የተሰኘ ኬሚካል በአልኮል ምክንያት ባለመመንጨቱ እንደሆነ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡
በማእከሉ ሀኪም የሆኑት ተባባሪ ፕሮፌሰር Martin Paukert ሰዎች በነገሮች ላይ ትኩረት ለማድረግ ስንፈልግ ወይም ከወንበራችን ተነስተን ንቁ ለመሆን ስናስብ ጭንቅላታችን አነቃቂውን ኬሚካል ይረጫል፡፡ ታዲያ በአልኮል ሱስ የተጠመድን ከሆነ ትኩረት ለማድረግ መፈለጋችንን ጭንቅላታችን እንዳረዳው ያደርገዋል፡፡
በዚህም ምክንያት norepinephrine የተባለው ኬሚካል ስለማይመነጭ ከፍተኛ የሆነ የትኩረት ማጣት ችግር ይገጥመናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የዚህ ዘገባ ሙሉ መረጃም ታህሳስ 2፣ 2020 በ Nature Communications ታትሞ እንደወጣ የመረጃ ምንጫችን SciTechDaily አመልክቷል፡፡
የሮኬት ማስወንጨፊያ ድሮኖች ሳተላይቶችን ወደ ህዋ ለመውሰድ
********************************
RAVN-X የተባለው የሮኬት ማስወንጨፊያ ድሮን ያለአብራሪና ያለማስወንጨፊያ ትንንሽ ሳተላይቶችን ወደ ህዋ ይዞ እንዲበር ዲዛይን ተደረገ፡፡ የመጀመሪያው በረራም ሞዴል ታህሳስ 3, 2020 ይፋ የተደረገ ሲሆን በ2021 የመጀመሪያውን ተልእኮ እንደሚፈጽምና ከሙከራ በረራም በኋላ የአሜሪካ ህዋ ሀይል (U.S. Space Force) ሳተላይትን እንደሚያጓጉዝ ታውቋል፡፡
የድሮኑ አምራቹ ተቋም አንድ ቢሊዮን ዶላር ከወታደራዊ ተቋሙ ጋር ውል ያሰረ ሲሆን የድርጅቱ መስራችና መሪ ግን ድሮኑ ከሳተላይት ማጓጓዣነት ይልቅ ለ remote-sensing ተመራማሪዎች የበለጠ ጥቅም እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡ ድሮኑ የሁለት የተማሪ አውቶቢሶችን የሚያክል መጠን ሲኖረው የወፍና የሳተላይት ውህድ ቅርጽ እንዲኖረው ተደርጎ የተሰራ ነው፡፡
ድሮኑ ከማንኘውም መንደርደሪያ መነሳት የሚችል ሲሆን ወደ ላይኛው የከባቢ አየር ክፍል ከፍ ብሎ ከወጣ በኋላ የተገጠመለትን ትንሽ ሮኬት ይለቃል፡፡ ሮኬቱ ህዋ እንደደረሰ ከ100 እስከ 150 ኪሊግራም የሚመዝኑ ባለክንፍ ሳተላይቶችን ይለቃል፡፡ ይህ ሁሉ አሰራር ራስ ገዝ (autonomous) ሲሆን ለሳተላይት ማስወንጨፊያ መሰረተ ልማት የሚወጣውን ወጭ በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንሰው ተነግሯል፡፡
እነዚህ ከላይ የተገለጹት መሰረታዊ ነገሮች የአሜሪካውን Space Force ትኩረት መሳብ የቻሉ ሲሆን ASLON-45 የተሰኘን የተቋሙን ሳተላይት ለማጓጓዝም ስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡ ይህ ሳተላይትን በድሮን የማጓጓዝ ስራ ለህዋ ሳይንስ ምርምር የሚወጣውን ወጭ በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ ብዙዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ታምኖበታል፡፡
ምንጭ www.sciencemag.org
ኢትዮጵያውያን ተመራማሪዎች የሰማይ ጠቀስ ህንፃዎች ግንባታን ከአርማታ ወደ ጣውላ ለመቀየር እየሱሩ ናቸው
=======================
ረጃጅም ህንፃዎችን ለከባቢ በተስማማ መልኩ ለመገንባት ያለው ፍላጎት በፍጥነት እያደገ ባለበት በዚህ ጊዜ ካናዳ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ምሁራን ሰማይ ጠቀስ ህንፃዎችን ለመስራት ጣውላዎች ተመራጭ እንዲሆኑ እየሰሩ ይገኛል፡፡ ብዙ ሰዎች እንጨትን እንደ ባለ 40 ወለል ላሉ ረጃጅም ህንፃዎች መስሪያነት ለማሰብ ይቸገራሉ የሚለው ካናዳ በሚገኘው የብሪቲሽ ኮሎቢ ዩኒቨርሲቲ የምህንድስና ትምህርት ክፍል ውስጥ የዶክትሬት ዲግሪውን በመማር ላይ የሚገኘው ማቲያስ በዛብህ ዘመናዊ ስልቶችን መጠቀም ከተቻለ እጅግ ጠንካራ የሆኑ ረጃጅም የጣውላ ህንፃዎችን መገንባት እደሚቻል በማሳየት ላይ መሆናቸውን ይናራል፡፡
ሰለሞን ከብሪቲሽ ኮሎምቢያ እና ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ከተውጣጡት አማካሪዎቹ ፕሮፌሰር ሰለሞን ተስፋማርያም እና ፕሮፌሰር ግርማ ብፁህአምላክ ጋር በመሆን ከ10 እስከ 40 ወለል ያላቸው ረጃጅም የእንጨት ህንፃዎች ግንባታን በዌስተርን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በሚገኝ የንፋስ ቤተ-ሙከራ (Wind Tunnel) ውስጥ እየመረመሩ ይገኛሉ፡፡ እንደ ማቲያስ አገላለፅ ህንጻዎችን አሁን ባለው የህንጻ ግንባታ መመሪያን በመጠቀም የሚሰሩት ሽቅብ እስከ 20 ወለል ከፍታ ያላቸው የጣውላ ህንፃዎች ከፍተኛ ነፋስን መቋቋም የሚችሉ ሲሆን የህንፃው ርዝመት ወደ 30 እና 40 ወለል ሲያድግ ግን የተለያዩ መዋቅራዊ እና የነፋስን እንቅስቃሴ መቋቋሚያ (aerodynamic) ማሻሻያዎችን ማድረግ እንደሚያስፈልግ ግኝታቸው ያሳያል፡፡ ማሻሻያዎቹ በነፋስ አማካኝነት ከሚመጣው የህንፃው መወዛወዝ እና በዚህም ምክንያት የሚከሰተውን በህንፃው ውስጥ ያሉ ሰዎችን ምቾት ማጣት የሚፈቱ መሆን አለባቸው፡፡
ፕ/ር ሰለሞን በበኩላቸው መሻሻል የሚገባቸው ነገሮች ያን ያህል ከባድ ጉዳዮች አለመሆናቸውንና በቀላሉ ሊከወኑ እንደሚችሉ ግኝታቸው ማሳየቱን ተናግረዋል፡፡ ይህም በኪነ-ህንፃ ረገድ አዳዲስ በሮችን የሚከፍትና አሁን ላይ በስፋት እየታዩ ያሉ ለአካባቢ የተስማማ ግንባታ የማድረግ እንቅስቃሴዎችንም እንደሚያግዝ የፕ/ር ሰለሞን ተስፋ ነው፡፡
ካናዳ በማጠናቀቅ ላይ ባለነው የፈረንጆች ዓመት 2020 ከጣውላ የሚሰሩ ህንፃዎች ላይ አስቀምጣው የነበረውን የ6 ፎቅ ከፍታ ገደብ በማላላት ወደ 12 ፎቅ ከፍ ያደረገችው ሲሆን በቅርብ የሚወጣው የ2021ዱ ዓለም አቀፉ የግንባታ ደንብም (IBC) እስከ 18 ፎቅ ድረስ ርዝማኔ ያላቸው ህንፃዎች
በስፋት እንዲገነቡ የሚፈቅድ ይሆናል፡፡
እንደ ክሮስ ላሚናትድ ቲምበር ያሉት የዘመናችን ቴክኖሎጂ ልዕቀት ውጤት የሆኑ ጣውላዎች ባላቸው ከፍተኛ ጥንካሬ፣ ውጤታማነት እና ውበት ሳብያ በዓለም ላይ እየተስፋፉ መሆኑን ማቲያስ ይናገራል፡፡ የምህንድስና ትምህርት ቤቱም በፕ/ር ሰለሞን የሚመራውን በጣውላ ግንባታ ከላይ ያተኩር ትምህርት እየሰጠ ይገኛል፡፡
ምንጭ፡ Tech Xplore
ቴክ-ሳይንስ የቴሌቪዥን ፕሮግራም፤ በነገው ዝግጅታችን
**************************
በአብይ ፕሮግራም፤ ዲጂታል ላይብረሪን፣
በብላቴናት፤ የእንቁላል መፈልፈያ የሰራውን ታዳጊ፣
የተመራማሪዎች ታሪክ፤ ዶ/ር ሀብቴ ጀቤሳ፣
በተቋማት፤ የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር፣
እንዲሁም በቴክኖሎጂ ታሪክ፤ ባሕር ሰርጓጅ መርከብን ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡
እነዚህ አስተማሪ ዝግጅቶች እንዳያመልጥዎ ነገ ቅዳሜ 10 ሰዓት ላይ የቻናል ምርጫዎን MOE ቴሌቪዥን ላይ በማድረግ ይከታተሉን፡፡
በየሳምንቱ ዕሁድ እና በድጋሚ ማክሰኞ 10 ሰዓት በ MOE ከሚቀርበው በተጨማሪ ወደ ዩትዩብ ቻናላችንም (https://www.youtube.com/channel/UC6jvUOLRSkVEQtc5Annfwvg) ጎራ በማለት አዳዲሶቹን ጨምሮ እስከዛሬ የተሰሩትን ፕሮግራሞች በሙሉ መመልከት ይችላሉ፡፡
TECHIN seminar
==========
ቴክኢን ሴሚናር የፊታችን ሐሙስ ታህሳስ ፩ ላይ የሚካሄድ ይሆናል፡፡ በዚህ ሳምንት ዝግጅታችን አቶ ብርሀን ታፈሰ “COLOR THEORY BASICS” በሚል ርዕስ ገለፃ የሚያቀርቡ ሲሆን ይህንንም ተከትሎ ታዳሚዎችን ተሳታፊ የሚያደርግ ውይይት ይኖራል፡፡
ዝግጅቱ የሚጀመርበት ሰዓት ከጠዋቱ 3፡30
TECHIN seminar will be held in Thursday (December 10) at TECHIN hall. In this week’s session Mr. Birhan Tafesse will be presenting about COLOR THEORY BASICS, followed by a brief discussion, which will include participants.
Starting time: 9:30 AM
የአለማችን የመጀመሪያው በሞባይል ስልክ የሚሰራ የ DNA መለያ መተግበሪያ
******************
የኮልድ ስፕሪን ሀርቦርድ ቤተ ሙከራ (CSHL) ተመራማሪዎች በአለማችን የመጀመሪያ የሆነውን ለዘረመል ልየታ የሚያገለግልን አዲስ የአይፎን መተግበሪያ ማበልጸጋቸው ተሰማ፡፡ iGenomics የተሰኘው መተግበሪያ የአይፎን ስልካችንን ለዚሁ ተግባር ከተዘጋጀ ተንቀሳቃሽ የዘረመል መለያ መሳሪያ ጋር በማገናኘት የዘረመል ሙከራ ማድረግ የሚያስችለን መተግበሪያ ነው፡፡
በተለይ መተግበሪያው እንደ ላፕቶፕ ኮምፒውተር ያሉ ለመስክ ስራ አመችነት የሌላቸውን መሳሪያዎች በማስቀረት በእጅ ስልካችን ስራዎችን ማከናወን የሚስችለን ሲሆን በይበልጥ ደግሞ በወረርሽኝ ወቅትና በስነ ምህዳር ስራ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ታምኖበታል፡፡ ይህንንም መተግበሪያ Aspyn Palatnick ከ14 አመቱ ጀምሮ ለስምንት ተከታታይ አመታት ሲሰራው መቆየቱን የመረጃ ምንችን SciTechDaily አስነብቧል፡፡
የአይፎን መተግበሪያው ትልልቅ ሰርቨር ላቸውን ኮምፒውተሮች ብቻ በመጠቀም ይሰራ የነበረውን የዘረመል ጥናት በቀላሉ በእጅ ስልክ መፈጸም እንደሚያስችል ተነግሮለታል፡፡ የ iGenomics አሊጎሪዝም የተለያዩ ቫይረሶችን ዘረመል በቀላሉ በመለየት በሽታዎችን ማከም የሚያስችሉ አማራጮችን እንደሚያመላክት ተገልጧል፡፡
በተጨማሪም በህዋ ሳይንስ ያለውን የዘረመል ምርምር ፍላጎት ከግምት ውስጥ በማስገባት ግኝቱን ወደ ህዋ መውሰድ የሚቻልበትን መንገድ በመፈለግ ላይ መሆኑን የመተግበሪያው አበልጻጊ ይናገራል፡፡
መተግበሪያው እንደ ጉንፋን፣ ዚካና ሳርስ የመሰሉ ቫይረሶችን ጅን መለየት እንደሚያስችል ተነግሯል፡፡
ምንጭ SciTechDaily
ከእይታ መሰወር የሚያስችለው ፈጠራ
**********************
ተመራማሪዎች በተለይ ወታደሮች ከሰዎች እይታ መሰወር የሚያስችላቸውን ፈጠራ መስራታቸው ተሰማ፡፡ ይህ ፈጠራ ወታደሮች በግዳጅ ወቅት በተለይ በጠላት ቀጠና አካባቢ ሲንቀሳቀሱ የሚለብሱትና ከአካባቢው እይታ ጋር የመመሳሰል ብቃት ያለው ሰው ሰራሽ ቆዳ ነው፡፡
በደቡብ ኮሪያ የሚገኝ የተመራማሪዎች ቡድን ወታደሮችን በአካባቢያቸው ካለ ከማንኛውም ነገር መሰወር የሚያስችላቸውን ልዩ ፈጠራ በማበልጸግ ላይ መሆናቸውን የዘገበው futurism.com ነው፡፡ ይህ ፈጠራም ወታደሮችን ከመደበኛ ካሜራም ብቻ ሳይሆን ከምሽት እይታም (infrared-based night vision) ጭምር መሰወር እንደሚችል ዘገባው አመልክቷል፡፡
ፈጠራው ከእይታ ውጭ ከመሆን በተጨማሪ እንደ አካባቢው ሁኔታ የመሞቅና የመቀዝቀዝ ብቃት ያለው እንደሆነ ተገልጧል፡፡ በወታደራዊ ሳይንስ ዘርፍ ከፍተኛ ድርሻ ይኖረዋል የተባለው ይህ ፈጠራ በየትኛውም አይነት ካሜራ ሙሉ በሙሉ ያለመታየት አቅምን እንደሚፈጥርም ተገልጿል፡፡
ምንጭ futurism
የመጀመሪያውን ውጤታማ የወባ መከላከያ ክትባትን ልናገኝ ይሆን?
=====================
በቅርቡ ኮቪድ-19 ላይ ከተሰሩት ግንባር ቀደም ክትባቶች ውስጥ አንዱ የሆነውን ክትባት ከአስትራዜኒካ ጋር በመሆን የሰራው የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ቡድን አሁን ደግሞ አዲስ የሰራው የወባ በሽታ ክትባቱ በመጨረሻዎቹ የሰው ላይ ሙከራ ደረጃዎች ላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡ እንደ ጀነር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተሩ ፕሮፌሰር አድሪያን ሂል ከሆነ የመጀመሪያ ሙከራዎቹ ተስፋ ሰጪ ውጤት ማሳየታቸውን ተከትሎ መጪው የፈረንጆች ዓመት ላይ የወባ ክትባቱ አፍሪካ ውስጥ በሚገኙ 4,800 ህፃናት ላይ ሙከራ የሚደረግበት ይሆናል፡፡
ፕሮፌሰሩ ከታይምስ ጋራ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ወባ ለማህበረሰብ ጤና አደጋ መሆኑን በመጥቀስ አፍሪካ ውስጥ በዓመት ምናልባትም ኮቪድ-19 ከሚያስከትለው እስከ 10 እጥፍ የበለጠ ሞት እንደሚያስመዘግብም ይናገራሉ፡፡ አክለውም ክትባቱ በብዛት ተመርቶ በአነስተኛ ዋጋ እንደሚቀርብ እና አሁን በሰዎች ላይ ሊደረግ የታሰበው ሙከራ ውጤታማ ከሆነም እስከ አወሮፓውያኑ 2024 ድረስ ሙሉ በሙሉ ስራ ላይ ሊገባ እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡
ይህ ታድያ እስከዛሬ ድረስ ሙሉ እውቅና ያለው የወባ መከላከያ ክትባት አለመኖሩን ስናስብ ይህን ትልቅ እርምጃ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ከዚህ ቀደም ጂ.ኤስ.ኬ የተባለ የእንግሊዝ የህክምና ግብዓት አምራች የሰራው ክትባት ብቻ ነው ከዚህ ጋራ በሚቀራረብ ደረጃ ላይ መድረስ የቻለው፤ ምንም እንኳን ምርቱ 30 በመቶ ብቻ ውጤታማነት ያለው ቢሆንም፡፡
በወባ ትንኞች አማካኝነት የሚከሰተው የወባ በሽታ ገዳይ ከሆኑ በሽታዎች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት መረጃን ያየን እንደሆን በአውሮፓውያኑ 2019 ብቻ በዓለም አቀፍ ደረጃ 229 ሚሊዮን ሰዎች በበሽታው የተጠቁ ሲሆን 409ሺህ ያህሉ ደግሞ ህይወታቸውን እንዲያጡ ሆኗል፡፡ ከዚህ ውስጥ ከፍተኛውን ዋጋ የምትከፍለው አፍሪካ ናት፤ 94 በመቶ የሚሆነው የተጠቂዎች እና ሟቾች ቁጥርን በመያዝ፡፡ በተጨማሪም ከአጠቃላይ የሟቾች ቁጥር ዕድሜያቸው ገና ከ5 ዓመት በታች የሆኑ ህፃናት 274,000 ወይም 67 በመቶውን እንደሚይዙ ይህ የዓለም ጤና ድርጅት መረጃ ያሳየናል፡፡
ምንጭ፡ The Guardian እና WHO