Sost Kilo
5.11K subscribers
998 photos
45 videos
7 files
107 links
Stories | ሦስት ኪሎ

@leoulz
Download Telegram
🔥1
ች ግ ራ ች ን ፡ ም ን ፡ ነ በ ር ?

[ ል ዑ ል ፡ ዘ ወ ል ደ ]

ሌላ ያልነገርኩሽ ፥ የልደትሽ ቀን አበባ ገዝቼ ነበር ። አዎ ! እኔ ። የሚገርምሽ ባገሩ እንደጠፋ ሁሉ የትናየት ሄጄ መሰለሽ ? መጨረሻ ላይ ወሰን ምናምን እሚሉት ሰፈር ትንሽዬ ኪዮስክ ውስጥ ትልቅ መቀስ የያዘች ሻጭ አየሁ ፤ ፈንታቸው መርገፍ የሆኑ ቅጠሎችን እየከረከመች።

እንዲሁ ልጅ ሳለሁ ፥ ከትምህርት መልስ ሙሽራ የሚሉትን አበባ ከሰው አፀድ ቀጥፌ ወደቤቴ እሮጥልሻለሁ ። ቤት ልደርስ 'ከባቢ እጄ ከአበባው ተሻሽቶ ኖሮ ፥ ወየበ ። ከቆረጡት ኋላ ቶሎ የሚሞት አይነት ዘር ሆኖም ይሆናል ። ብቻ እጄ ላይ ከስሞ ፥ ነደደኝ ።

የቀጠፍኩት እንዲያ እንዳማረበት ለ'ናቴ ልሰጣት ነበር ። ያም ሆኖ አልተውኩትም ። ከስራ መምጫዋን ጠብቄ (አስራ ሁለት ሰዓት እንደምንም ሞልቶልኝ) ሰጠኋት ። የኔ ንጉሥ ብላ አቀፈቺኝ ፥ ከመቀበል ያለፈ ቁብ ሳትሰጠው ። ጭራሽ ወርውራው መክሰስ መብላቴን እየጠየቀች ወደቤት ይዛኝ ገባች ። እጄን ይዛኝ ስትዘልቅ ፊቴ ወደወደቀው አባባ እንደዞረ ነበር ።

እናልሽ ቤሎንዥ...

ኪዮስኩ ውስጥ ያለችው ልጅ የሚቀባውን ነገር ቀብታ የሆነ የሚነፋ ነገር'ም ነፍታበት አጋጊጣ ምናምን ሰጠችኝ ። እንዴት እንዳማረበት ። ገዝቻት ስወጣ አመስግኜ ፥ መልካም በዓል ! አልኹ ። የምን በዓል ደሞ ? በሚል ግርምታ ታየሁ ፥ ሃሃ።

እዝነ ገመዴን ከጆሮዬ ስላልተነሳ ዘፈን እንደምሰማ ሁሉ ምንም ሳልል እግሬን አዙሬ መንገዴን ጀመርኩ ። ለካ ሌላ ሰው የአንቺን ልደት አይቀድስም ። የለም? ፥ ለካ የነሱ ካለንደር በንግስሽ ቀን አይዘጋም ።

ከናቴ ለጥቆ አበባ ልሰጠው የነበረው ላንቺ ነበር ። የገዛሁት አበባ በትራንስፖርት ግፍፊ እንዳይጎዳ ወክ ማድረግን መረጥኩ ። አበባውን እንደያዝኩ ይዤ በቀትር ስንከላወስ አላፊ መንገደኛ እያየኝ በልቡ የሆነ ነገር ይላል ። መቼም አበሻ "ምኗ እድለኛ ነች ፥ አበባ የሚሰጣት " ማለት አይቀናውም ። ...አ...ዬ ባህላችን.. ገለመሌ ...እያሉ ይሆናል ።

ሰባት ሰዓት ላይ የሜክሲኮው ቶታል (ቦንዡ ካፌ) ደረስኩ ። ተረከዜን ከማቃጠል ውጪ በጉዞው ብዙ አልተሰማኝም ። ትዝ ይልሽ ከሆነ አራቴ ስደውልና በአምስተኛው ጥሪውን ስትጠረቅሚው ፥ እዛ ቁጭ ብዬ ነው ። ከተቀመጥኩ ሰዓት ሊደፍን ምናምን ደቂቃ ሲቀረኝ ያ...!...ሜሴጅ ገባ።

- Sorry, Je ne peux pas venir.

መምጣት አልቻልኩም ። እንደው እንደቀላል ፤ የአንድ ግድንግድ መፅሀፍን ግፍ በአንድ ነጠላ መስመር ። አለ አደል ፥ ሲቻኮሉ ከሰው ተገጫጭተው ይቅርታ እንደመጠየቅ አይነት ያለ ።

እና አበባው ሳይደርስሽ ከእጄ ቀረ ። እናቴም ያኔ አበባውን ስሰጣት እንዴት ሆኜ እንዳመጣሁት አልጠየቀችም ። ማለት ፥ ስላልጠየቀች ለመቅጠፍ የከፈለኩትን መስዋዕትነት አልተረዳችም ። በልጅ ሩሄ አበባ ያህል ነገር ከሰው አጥር ላይ አርጄላት ፥ በቅጡ እንኳ አልባረከችኝም ። ከንቱ ድካም ነበር ። አበርክቶቴ መገፋት የጀመረው ከያኔ አንስቶ ነው ፤ እርኩስ እንደሚሠዋው በግ ፥ እሳት ከራማ ወርዶ እንደማይበላው ...።

የዛን ቀን እራሮቴ ተፈቅፍቆ ከልቤ አልወድቅ አለኝ ። የልደትሽ ቀን ባለፈ በሆነኛው ቀን ስልኬን አውጥቼ መርዕዩ ላይ Qu'est-ce qui ne va pas entre nous , bel ange? ብዬ ፃፍኩ ። ችግራችን ግን ምን ነበር ...?

ችግራችን ፥ የፍዮሪ በእጄ ላይ መሞት ሳይሆን ፥ ተቀባይ ማጣት ነው ። አንዳችኝ ጉም ሰንጠቀን አንዳችንን ከህዋ ስናስስ ሌላችን ጣርማበር ጓሣ ውስጥ ለሽ ብለን ነበር ። በተራሽ ደሞ አንዳችን ባነን ሌላችንን ስናስስ የሂማልያ ክምር ጋርዶን ለአይን እንሰወራለን ።

መልሱን እያወቅሁ ያረቀቅሁትን ጥያቄ ላንቺ መላክ አልፈለኩም ። ከደመና በታች እንደቀረ ፀሎት ፥ ካፍ እንዳልወጣ ቃል ፥ እንዳልተኖረ ምኞት ፥ ሲባኑ እንደረሱት ህልም ፥ ደርሰው እንዳልሰበኩት ወንጌል ...

በድህሪት መደለዣ የፃፍኩትን የቃላት ድርድር አንድ በአንድ ከስልኬ መርዕይ ሰረዝኩ ። ሰሌዳው እስኪራቆት ፤ የመተየቢያዋ ከርሰር ግራዋን ሄዳ ውልብ ውልብ እስክትል። ፥ እ ...ን...ዲ..ሁ •••|

------------------------------------------------------------
ያ ል ተ ላ ኩ ፡ አ ም ስ ት ፡ ቴ ክ ስ ቶ ች [ M e s s a g e -1 ]
ሥዕል፡ I see flowers in your eyes | Agathe Marty.
ᵀʰᵉʳᵉ ʷᵉʳᵉ ᵃˡˡ ᵏⁱⁿᵈˢ ᵒᶠ ˢᵗᵒʳⁱᵉˢ ᵗᵒˡᵈ ᵃᵇᵒᵘᵗ ᵗʰᵉ ʷᵃʳ ᵗʰᵃᵗ ᵐᵃᵈᵉ ⁱᵗ ˢᵒᵘⁿᵈ ᵃˢ ⁱᶠ ⁱᵗ ʷᵃˢ ʰᵃᵖᵖᵉⁿⁱⁿᵍ ⁱⁿ ᵃ ᶠᵃʳᵃʷᵃʸ ᵃⁿᵈ ᵈⁱᶠᶠᵉʳᵉⁿᵗ ˡᵃⁿᵈ° ᴵᵗ ʷᵃˢⁿ'ᵗ ᵘⁿᵗⁱˡ ʳᵉᶠᵘᵍᵉᵉˢ ˢᵗᵃʳᵗᵉᵈ ᵖᵃˢˢⁱⁿᵍ ᵗʰʳᵒᵘᵍʰ ᵒᵘʳ ᵗᵒʷⁿ ••• | 𝙸𝚜𝚑𝚖𝚊𝚎𝚕 𝙱𝚎𝚊𝚑 | 𝙰 𝙻𝚘𝚗𝚐 𝚆𝚊𝚢 𝙶𝚘𝚗𝚎: 𝙼𝚎𝚖𝚘𝚒𝚛.
Podcast, tonight ! ችግራችን ምነበር ? | S |ያልተላኩ አምስት ሜሴጆች ፥ መልዕክት አንድ | EP | 01.
ያ ን ፡ ቀ ን ፥ ባ ታ ቆ ላ ም ጪ ኝ ስ ?

[ ል ዑ ል ፡ ዘ ወ ል ደ ]

ከወፍራም ብርጭቆ ላይ እያበረደች የምትቀምሰው ወተት የከንፈሯን ዳር በስልባቦት ይኩላል ። የአፏን ወተት ለመግፈፍ እጄን ሰድጄ ግልፋፊውን በጣቴ አስቀረሁ ። ያስቀረሁትን ቀመስኩ ። የላስኩትን ኬሚስትሪ ጣዕም ለማስረዳት ይቸግራል ። ሀይድሮጅን ደርድረው በቦንድ ቢስሉት ዘርፉ ከአሮጌ ዋርካ ይገዝፋል።

ቤሎንዥ ፥ ዛሬ ንጋት ላይ ከፓሪስ-ቻርል የገባች ነው ። ስለሚደክም ፥ ችላ የምትመጣም አልመሰለኝም ነበር ። ለገሃር ሳባ ኬክ ቤት ተገናኘን ። ሳፊ ወተት ጋበዝኳት ። ግብዣው የይቅርታ ነው ። ከአምስት ቀን መዘጋጋት በኋላ የሀቅ ኩርፊያዬን ካድኩ ። ጥፋቱ የርሷ ሆኖ የይቅሩ ምንጭ የፈለቀው ከእኔ ነው ። ለምን ? ለሚል ጠያቂ ፥ በቃ ተፈጥሮ አንድ ህግ የላት (አጭር ቀጫጫ መልስ ፥ ሃሃ) ።

ጉንጬን ነፍቼ ለጠፉት ውድ ቀናት ራሴን ገስፄ ፤ ማሪኝ አልኹ ። ኩርፊያ የአፍቃሪ ወጉ ቢሆንም ለርሱ አልታደልኩም ። ኩራቴን ገርስሼ ...የኔ ቤሎንዥ ፥ ስላጠፋሽ መልሰሽ እኔኑ ማሪኝ ፥ ከወዲህ አትያዢብኝ ...አልኩ ።

ማህተም ሳያገኙ ልብን ከሰጡ እንዲ ነው ፤ የቁልቋል ማሳ ውስጥ እንደለቀቁት ፊኛ ። ካሁን አሁን እሾህ ወጋብኝ እያሉ ንፋስን ሲማፀኑ እንደመኖር ። ጧ'ን ላለመስማት ጆሮን ከድኖ በነሲብ እንደመከተል ። ዉል አልባ አፈቃቀር ፥ ተሳደው የሚያሳዱት ፍቅር።

ታድያ ግን ያነጫንጫል ። መነጫነጩ ብዙ ሳይበስል እንደዛሬው በውስጥ ተግሳፅ ይሻራል ። ሽረቱ ርትዕ ስላልሆነ ቁስል ይተዋል ። ቁስሉን ደግሞ ...ቁ...ል...ም...ጫ...ያክመዋል ፥ ያው ከጠባሳ ባያድንም ።

የኔ ቤሎንዥ በቃላት መጮት ትወዳለች ። የቃሎቿ አያይዛ ትርጉም የምትመሰርተው በፈገግታዋ እርጥበት ነው ። ሁለት ነጥብ ይሉትን ስርዓተ ነጥብ ለእንደኔ አይነቱ ፋራ ይተውታል ። የምትመሰርተው ንግግር ከደራሲ ተረክ ይረቃል። ደብተራ ፍቆ ቢደግምባቸው ከሰማይ አንድርቢ ያወርዳሉ ። መሳፍንት ድምፇን ተውሰው ክተት ቢያውጁ ዲዳ እንጂ ማንም አይወሰልትባቸውም።

ከሁሉ ስሜን ስታቀብጥ ደስ እሰኛለሁ ። ቀድሳ ስትጠራው እንዳጣፈጠኝ በታምቡሬ ልሞ ይወርዳል ። ሲወርድ ከሆዴ የታፈነው መውደድ እንደቫይረስ እየተጋመሰ ራሱን በራሱ ያበዛል ።

መጀመሪያ አቆላምጣ የጠራቺኝ የዛሬ ዓመት ክረምት ፥ በስልክ ሽቦ ወስጥ ነው ። በቅጡ አልሰማኋትም ፥ ደረቴ ተረብሾ መሸከም አቃተኝ ። ላይፈነዳ ነገር እየተብላላ አንጀቴ ውስጥ የሚፈላ ዩራንየም ሆነ ። ቤት ለእራት ስቀርብ የውስጤ ውሮ ወሸባ ከፊቴ እንዳይነበብኝ ፈራሁ ። እየበላን አባቴ ፊት መዝለል ሁሉ አሰኝቶኝ ነበር ፥ሃሃ ።

ከእጄ የነበረው መፍትሄ ሳይክሌን ይዞ ከቤት መውጣት ነው ፤ ወጣሁ ። እንደጣቃ ጠቅልዬ ያፈንኩትን ስሜት አስፋልት ላይ በትኜ ፥ ወዴት እንደሆነ ሳላውቅ ፥ በሰርክ ውርጭ እየተገረፍኩ ፥ መሪዬን ለቅቄ ስሟን እየጠራሁ ... ጋ... ለ... ብ... ኩ ... ። ሄጄ-ሄጄ የማላውቀው መንገድ መሃል ሰስደርስ ድንገት ወደ ራሴ ተመለስኩ ፥ አማትቤ እየዘነበብኝ ወደቤት ስመለስ ትንሽ ቀዘቀዝሁ።

የካፌው ጫጫታ (የወራሪ አንበጣ ድምፅ አይነት ጥዝታ) አልረበሸንም ። በኩርፊያዬ የመጣ ኩርፊያዋን ማሳረጊያ ብዙ አወራን ። ደሞ ብዙ ዝም ብለን ተያየን ፤ አይኖቻችን ውሃ አዝለው እስኪያንፀባርቁ። በዝምታ ስታየኝ ከአርያም ወድቃ መሄጃ እንደጠፋባት መሊክ ነው ። መተያየቱ እንዳበቃ ስፈራ የኖርኳቸውን ሚስጥራት ለመንገር ወሰንኩ ።

እንደፋርሰ ዕፅ ህቡዔን ምን እንዳጦዘው እንጃ ሌላ ግዜ የሚከብዱኝ ሶስት ቃላት እንደነገሩ ተወረወሩልኝ ። ከቤሎንዥ ጋር የሚለየን ይሄ ነው ። አያሳስበኝም እንጂ (ወይ ማሰብ አልፈልግም) ከርሷ ቃል ላይ ሁሌም ነብስ ይጎድላል ። ቃሎቿ ቢያምሩም ፥ እዛው አፏ ውስጥ ነው የሚጋገሩት ። እዛው ተመርቶ ከሰዓት መርካቶ ሃሃ

ብዕሬ ሶስተኛውን ከስኒው ስር በነበረ ቅዳጅ ሶፍት ላይ ደምቶ እንደጨረሰ 'ኦ! መሄድ አለብኝ' አለች ። ሁለቱን በቅጡ ያየቻቸው አልመሰለኝም ሶስተኛው 'Moi-même a besoin de toi' ...ቤሎንዥ ፥ ታስፈልጊኛለሽ የሚል ነበር ። እሱን በደንብ አይታዋለች ።

-ትንሽ አትቆዪም ? አልኹ ለአመል

-ኖ ፥ ሌላ ቀን ። አሁን ልሂድ

ውስጤ እንሂንም ደቂቃዎች ከሱ ቀንሳ የሰዋችልህ እርሷ ሆና ነው ይለኛል ። ሌላ ግብዣ እንደሚጠብቃት አውቃለሁ ፥ የባሏ እራት ። ( ለካ ባል እንዳላት እስካሁን አልተናገርኩም ፥ የኔ ነገር )

በባሏ አልቀናም ። አንድ ነገር ግን ይረገርመኛል ስማችን አንድ ነው ። ታዲያ ቀጥሎ ምን ያሳስበኛል እርሱንም ለኔ በሰጠችው ቁልምጫ ትጠራው ይሆን ? ... (አፍቃሪ አያስበው የለ)

የቁልምጫዋ ስግብግብ ነኝ ። ከኔ ውጪ ማንም እንድትጠራበት አልፈልግም ። እናም አስባለው እሱንም እንደዛ ትለው ይሆን ? ... በሆነ ቀን የእጅ ስልኳን እንደያዘች እየተላፋን ነበር ። የስልኳ መተየቢያ ስሜን ሸምድዶ ኖሮ የስሜን የመጀመሪያ ቃል ስትጫን በራሱ ተሞላ ። ይታይ ፥ አሁን ሰው በዚህ ይደሰታል ? ልቤ በጮቤ የወር ቀለቡን ሰፈረ ፥ ጌታን ።

Bonsoir ! ብላኝ እንደወጣች ከአይኔ እስክትጠፋ በካፌው ሻተር አሻግሬ ተከተልኳት ። አብራኝ እንድትሆን ብዙ ተመኝቼ ነበር ። ከሷ ሆኜ የምገድላቸው ሰኮንዶች ሰማይ ቤት ታስበው ቢቀነሱብኝ አይቆጭም ።

እንዲህ ባሉ ቀናት ፥ ብቻዬን ስትተወኝ ውስጤ የሚቀረውን ስሜት አልወደውም ። የልቤ ዙርያ ይንቦለቦላል ። የት እሄዳለሁ ፍቅርን እንደረኛ ገሳ ለብሼ አልጠለለው ፥ ሮጬ አላመልጠው ነገር ።

በአፍታዎች ውስጥ መልሶ ከፋኝ ። ሀድራዬ እንዲህ ነው ፍቅሬን ሳይሆን ማፍቀሬን ያስረግመኛል ። ልቤን የሆነ መካነ ልብ አዘጋጅታ ብትቀብረው አልኹ ። እንደዛ ሆኖ በወጣልኝና ያለእንባ የደስታ ጉንጉን ባስቀመጥኩ ።

ካፌው ውስጥ ሳልንቀሳቀስ እንደደረቅሁ ለአራት ክፉ ሰዓታት ተቀመጥኩ ። አስር ደቂቃን ጮቤ ረግጦ ለሁለት መቶ አርባ ደቂቆች በልዕለ-እሳቤ ተወጋጋሁ ። ጉዳቴን መልሳ እንድታክመኝ አልፈለኩም ። ከሁሉ ቃላቶቿ ያስቀይሙኛል...ሜርድ ! ። ልነግራት ስልኬን አወጥቼ የመልዕክት መላኪያውን ከፈትኩ ።

- Toujours à jouer avec les mots

ቤሎንዥ ፥ ሁሌም በቃል ትጫወቻለሽ ።

ማስወንጨፊያውን ከመጫኔ በፊት አሁን እንዴት ትሆን የሚል ሀሳብ ሰረቀኝ ። ከአቶ ባል ጋር እየተሳሳቁ ? እየሳማት ? ተኝተው ። ራሴ ለራሴው ሲያሰጣኝ ደግሞ በፀሊም ድምፆች ይቀጣኛል ። ለባሏ የነፈግከው ክብር ፣ የጣስከው ህግ ፣ የረገጥካት ሞራልን እያጣቀስክ አስብ እንጂ ...ሰልፊሽ ።

የመላኬ የመጨረሻዎቹ ቅፅበቶች ላይ 'ስልኳ በርሱ እጀታ ላይ ቢሆንስ' የሚል ሀሳብ ገብቶ ነገሬን ቀያየረው ። ባሏ ቢያውቀኝና በወንጀሌ ባጣትስ ? እሳቤዬ እንደጎመዘዘኝ ዋጥኩ ። ሸምጋይ ጓደኛ እንኳ የለን ። ደሞ ኋላ በማን ላስለምናት ነው ? በእንዲ እንዲ ጣዖቴ እንድትቆጣ አልፈቀድኩም ። እየተጣሉ ማጣት አለመፈለግ ምን እንደሆነ እንጃ ፥ አላውቅም ። የተየብኳቸውን ፊደላት ግን አሟጥጬ ሰረዝኩ ። ቤ ሎ ን ዥ ፥ ታ ስ ፈ ል ገ ኛ ለ ች ።

------------------------------------------------------------
ያ ል ተ ላ ኩ ፡ አ ም ስ ት ፡ ቴ ክ ስ ቶ ች
[ M e s s a g e -2 ]
1