ኢትዮጵያዊ ወጎች #Ethiopian
1.44K subscribers
314 photos
3 videos
18 files
50 links
Download Telegram
# ካነበብኳቸው_ገጾች
ከሮማን ጋር ጨርሼ ስልኩን እንደዘጋሁ ሌላ ጥሪ ወዲያውኑ
ተከትሎ መጣ። ፊያሜታ ጊላይ ነበረች።
< ከማን ጋር ነው ለግማሽ ሰዓት ስታወራ የቆየኸው አታግናይ? >
አለችኝ።
< ከማን ጋር ይመስልሻል? >
< ከእጨኛህ ጋር... >
< ልክ ነሽ... >
< ምን ነበር የምትለው? ምን ትፈልጋለች? ለእሷ ስልክ ለመደወል
ነው እኔን ዝም ብለህ ወደ ቤቴ ያመጣኸኝ? አባቴ ይሙት ፥
የሠራሁት ግፍ ሳይሆን አይቀርም እንዲህ የሚያዋርደኝ። ቅሌት
ነው... ቅሌታም ሆንኩ አባቴ ይሙት > እያለች ነገር ትፈልገኝ
ጀመር።
< እንሂድ ብዬሽ ነበር’ኮ። አንቺው ነሽ ቤቴ ውሰደኝ ያልሺኝ ፥
አይደለም እንዴ? > አልኳት።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፊት የማላውቀው አዲስ ጠባይ
ይታይባታል። ከእኔ ጋር እደሪ ስላት እሺ አትልም። በፈቃዷ
መሠረት ወስጄ ሳደርሳት ደግሞ ታኮርፈኛለች።
< ብልህስ ታዲያ! >
< እሺ ምን አድርግ ነው የምትይኝ? >
< እንጃ አባትህ ፤ ደደብ ! >
< እሺ አሁን ልምጣና ልውሰድሽ... >
< አልመጣልህም ! >
< እሺ ምን ይሁን? >
< እንጃልህ! >
< እሺ ለምነኝ የምትይ ከሆነ አሁን ልለምንሽ... >
< ቤቴ ወስደህ እንደ ዕቃ ከጣልከኝ በኋላ? እውይ ብሞት ! >
ብላ ስልኩን ዘጋችብኝ።
መልሼ ልደውልላት ፈልጌ ስልኩን ካነሳሁ በኋላ ተውኩት። ኩራቴ
ታገለኝ። ተሟገትኩት ፤ አሸነፈኝ። ጥሪዬን እንደምትጠብቅ
ቢገባኝም ጨክኜ ተኛሁ። ግን እንቅልፍ አልወሰደኝም። ምን
እንደነካኝ አላውቅም ፤ እንዲህ አልነበርኩም።
ድንገት ለራሴ ባዶ እንደሆንኩ ተሰማኝ። የፍቅር ሰመመን አባዜ
ይዞኝ ይሆናል እንዳልል ዕድሜዬ እንዲህ ዓይነቱን ነገር የሚፈቅድ
አልመሰለኝም። የአሥራ ስምንት ዓመት ጎረምሳ አይደለሁም ፥
ወይስ ሰመመን የዕድሜ ክልል የለውም? አላውቅም። ግን የያዘኝ
አባዜ ሰመመን አልመሰለኝም። ገረመኝ ፥ መከረኛው ልቤ ሁለት
ሴቶች እንዴት ብሎ እኩል ሊወድ ይችላል? ብዬ ተገረምኩ።
ሕይወት እንግዳ ነገር ነው። ብዙውን ቀልድ ነው። አንዳንድ ጊዜ
ቀልዱ ይመራል። በሁለቱ መካከል መወሰን አልቻልኩም። ለደግም
ሆነ ለክፉ መወሰን አለመቻል ስቃይ ነው። ልቤ ሲደማ ተሰማኝ።
ያሰርኩት ቃልኪዳን እንደሾህ ወጋኝ።በዘንባባዎች ጥላ ሥራ አዲስ
ያገኙት ፍቅር እና ደስታ እንዲህ በቀላሉ የሚርረሰ ባለሞሆኑ
የሚደማውን ልቤን የባሰውኑ ጨመቀው።
ከፍቅርም ሌላ በፊያሜታ ሕይወት ላይ የሚያንዣብበው የአደጋ
ጥላ ፥ ይሉኝታ ፈጠረብኝ። አሁን ልለያት አልችልም። እንዴት
ብዬ? ሰው ወዶ ፣ ወዶ ድንገት በቃሽኝ ወይም በቃኸኝ ለማለት
እንዴት ይቻላል? እንዲህ ለማድረግ የሚችሉት የታደሉ ብርቱዎች
ናቸው። እኔ በዚህ አልታደልኩም። በዚህ ረገድ ደካማ ነኝ።
ተዋውቆ መለየት ያቅተኛል ፥ አንጀቴ አይችልም። ትዝታዬን መርሳት
ያስቸግረኛል። ስቃይ ይሆንብኛል።
የማደርገው ነገር ሁሉ ስሜቴን ስለሚነካ የኔ የራሴ ፥ የግሌ
አድርጌ ላስቀረው እፈልጋለሁ። እና እንዲህ ዓይነቱ ነገር ደሞ
ጅልነት ነው።
ምን ላድርግ? ጅል ነኝ !
______________
ደራሲ - # በዓሉ_ግርማ
ርእስ - # ኦሮማይ
1975 ዓ.ም
#የነበባችሁ ደግማችሁ አንብቡት
#ያላነበባችሁ ፈልጋችሁ አንብቡት

ሠናይ ቅዳሜ ከሙሉ ጤና ጋር ተመኘንላችሁ