የኀብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ
822 subscribers
2.14K photos
47 videos
265 links
Download Telegram
የኀብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ
Photo
ዓድዋን በደማችን፤ ዓባይን በላባችን!

(ፍቃዱ ከተማ)

ታሪክ በሁለት መልኩ ይፃፋል፤ አንድም በደም ሌላም በላብ፡፡ ታሪክ ሠሪዎቹ ኢትዮጵያውያን እነዚህን ገድሎች በደም ዓድዋ ላይ ፤ በላብ ደግሞ ጉባ ላይ ፈጽመውታል፡፡

የካቲት 23/1833 በሰው ልጆች ታሪክ እስከዚያኔው ያልተፈጸመን አንድ ገድል ኢትዮጵያውያን በደማቸው ጻፉ፡፡ ይኽ ገድል ድሆችና ኋላ ቀሮች ናቸው በሚል ንቀት ኢትዮጵያን በወረረው የፋሺስት ወራሪ ኃይል ላይ ዓድዋ ላይ የተመዘገበ ነበር፡፡ በዚህም ፍትሃዊነትና ሃገር ወዳድነት በተግባር እስካሉ ድረስ ተጨቋኞች ጨቋኞችን፤ ጥቁሮች ነጮችን በሚገባ እንደሚያሸንፉ ለዓለም እስተምረዋል፡፡

በዓድዋ ጦርነት ኢትዮጵያውያን በጊዜው የነበራቸውን የውስጥ ልዩነት ወደ ጐን ትተው ብሔር፣ እምነት፣ ጾታ፣ ዕድሜ፣ ባህል ወዘተ… ሳይለያቸው ደማቸውን በአንድነት አፍስሰውና አጥንታቸውን ከስክሰው ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለጭቁን ሕዝቦችና ለጥቁሮች ኩራት የሆነ ወርቃማ ድል በክብር ጽፈዋል፡፡

ሲተባበሩ ታሪክ መስራት የሚቀላቸው ኢትዮጵያውያን፤ ከዓድዋ ድል ከ129 ዓመታት በኋላ በደም ሳይሆን በላባቸው ዓለምን የሚያስገርምና ኢፍትሃዊነትን የሚሰባብር ድል ጉባ ላይ ደገሙ፤ በታላቁ የዓባይ ግድብ!

ከዓባይ ግድብ ዕውን መሆን በፊት የዓባይ ወንዝ ለኢትዮጵያውያን የሚያዩት ግን የማይጠቀሙበት የቁጭት ምንጭ ነበረ፡፡ ለዓባይ የሚዘፈኑ ዘፈኖች ሁሉ ቁጭትንና ሃዘንን የሚያንጸባርቁም ነበሩ፡፡ በደጃፏ የዓባይ ወንዝ ውኃ የሚፈስ ኢትየጵያዊ እናትም የኤሌክትሪክ ኃይል አጥታ ዓይኗ በከሰልና ማገዶ ጭስ እየተጨናበሰ ዘመናትን በችግር ገፍታለች፡፡

ዓባይ በሱዳን በተለይም በግብጽ የኃይል፣ የመስኖ የመዝናኛ ምንጭ ከመሆን አልፎ መጫወቻ ተደርጎ ወደ በረሃ በመውሰድ ውኃው ሲባክን፣ ከ85% በላይ የውኃው አመንጪ የሆነችው ኢትዮጵያ ግን በሴራ በገዛ ሃብቷ እንዳትጠቀም ተደርጋ ኖራለች፡፡

ይኸ እውነታ ግን በ2003 መጋቢት 24 የዓድዋ የመንፈስ ልጆች በሆኑ ኢትዮጽያውያን ላብ ለአንዴና ለመጨረሻ እንዲለወጥ ተወሰነ፡፡ ተወስኖም አልቀረ፤ በማህፀን ካለ ጽንስና በመቃብር ካለ አስክሬን በስተቀር ኢትዮጵያውያን ደመወዛቸውን፣ ጡረታቸውን፣ እንስሳታቸውን ወዘተ… ለግድቡ እውን መሆን አዋጥተው የዘመናት ቁጭትን ወደላቀ ኩራት አሸጋገሩ፡፡ ከቀጥተኛ የመንግሥት በጀት ውጪ በሀገር ውስጥና በውጪ ያሉ ኢትዮጵያውያን የ23 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል፡፡

በዚህም በዓባይ ወንዝ እንዳንጠቀም አይኤምኤፍ እና ዓለም ባንክን ጨምሮ አበዳሪ ተቋማት ገንዘብ እንዳይሰጡ ለማድረግ ተጋርጦ የነበረው የጅሎች ሴራ በኢትዮጵያውያን ተደረመሰ፡፡

ዛሬ ላይ ኢትዮጵያውያን የግድቡን ሥራ ለፍጻሜ አብቅተው የመስከረም ሙሽራቸውን የዓባይ ግድብን ምረቃ ለማብሰር ድል ያለ ሠርግ እየደገሱ ነው፡፡ በሠርጉም በዓድዋ በደም፤ በዓባይ ደግሞ በላብ ኢትዮጵያውያን አሳምረው ድል ማድረጋቸው ለዓለም ይበሠራል፡፡ ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሠረት የመጣሉም ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቃል የሚገባበት ይሆናል!
👍1
ህዳሴ በእኛ የታሰበ፣ በእኛ የተጀመረ፣ በእኛ ተገንብቶ በእኛ የተጠናቀቀ የእኛ ትውልድ ድል ነው።
👍42
በጎነት- የእድሜ፣ የፆታ፣ የሀብት፣ የቋንቋ፣ የእውቀት፣ የቀለም... ድንበር የለውም! ሁሉም በጎ ማድረግ ይችላል።
👍1
የኀብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ
Photo
የቅዱስ ፓውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የህክምና ኮሌጅ ከ100 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ነጻ የሕክምና አገልግሎት እንደሚሰጥ ገለፀ።

በተያዘው ክረምት በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ100 ሺህ በላይ ለሚሆኑና ከፍለው መታከም ለማይችሉ ዜጎች ነጻ ህክምና አገልግሎት የመስጠት ሥራውን በዛሬው እለት መጀመሩን የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የህክምና ኮሌጅ ገልጿል፡፡

የሜዲካል ኮሌጁ ምክትል ሥራ አስፈፃሚ ጀማል ሺፋ፤ "የክረምት በጎ ፈቃድ ሥራ ሁሌም የሚሰራ ቢሆንም በዚህ ዓመት ከሐምሌ 21 እስከ ሐምሌ 27 ቀን 2017 ዓ.ም ባሉት ሰባት ተከታታይ ቀናት ብቻ በሚሰጠው የነጻ ምርመራ 100 ሺሕ ሰዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እቅድ ተይዟል" ብለዋል፡፡

በ2016 ዓ.ም. ተመሳሳይ ወቅት ከ94 ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የነጻ ሕክምና አገልግሎት እንደተሰጠ አስታውሰው፤ የዘንድሮውን መርሃ-ግብር "በጎ ፈቃደኝነት ለጤናማ ማኅበረሰብ" በሚል መሪ ቃል እየተከናወነ እንደሚገኝም አብራርተዋል፡፡

ነጻ ምርመራው በተለይ የካንሰር፣ የጎሮሮ፣ የዓይን እና መሰል ትላልቅ የበሽታ አይነቶችን የነጻ ምርመራ እንደሚያደርጉ ከ50 በላይ የሕክምና መሳሪያዎች ተዘጋጅተዋል ብለዋል፡፡

የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ በምርመራ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን ለአቅመ ደካሞችን ቤት ማደስ፣ ደም መለሰገስ፣ እና ሌሎችም የበጎ አድራጎት ሥራዎች ላይ መሳተፍን እንደሚጨምር አሀዱ ሬድዮ ዘግቧል፡፡
👍6
የወርቃማ ሰኞ የዕውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ መድረከ ተካሔደ።

በዛሬው የኮሚሽኑ የወርቃማ ሰኞ መርሀ ግብር ልምዳቸውን ያካፈሉት የበጎ ፈቃድ ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ወይዘሮ አስራት ንጉሴ ናቸው፡፡
በተለየዩ የኃላፊነት ደረጃዎች ማገልገላቸውን የገለጹት ወይዘሮ አስራት በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወገንን ማገልገል የሚሰጠው የሕልና እርካታ የላቀ መሆኑን ገልፀዋል። ምክትል ኮሚሽነሯ በማህበራዊ ትረስት ፈንድ ተቋም የነበራቸው ቆይታ በሕይወታቸው ትልቅ ቦታ የሚሰጡት እንደሆነ ነው የተናገሩት፡፡

በማኅበራዊ ትረስት ፈንድ ጽህፈት ቤት ይተገበሩ የነበሩ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ከበጎ ፈቃድና ኅብረተሰብ ተሳትፎ ማስተባባሪያ ኮሚሽን ጋር እንዲዋሀዱ መደረጋቸው ተግባራት ይበልጥ እንዲጠናከሩና ውጤታማ እንዲሆኑ አስተዋዖ እንደሚኖራቸው አብራርተዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የአስፈፃሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር እንደገና በማሻሻል ማኅበራዊ ትረስት ፈንድ ፅህፈት ቤትን ከኮሚሽኑ ጋር እንዲዋሃድ ማድረጉ ይታወሳል።

የኮሚሽኑ አመራሮችና ሰራተኞች ለምክትል ኮሚሽነሯ የእንኳን ደህና መጡ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
👍2
የኀብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ
Photo
በቦሌ ክፍለ ከተማ በክረምት በጎ ፈቃድ ፕሮግራም ለ5,000 ከፍለው መታከም የማይችሉ ነዋሪዎች ነፃ የጤና ምርመራና ሕክምና አገልግሎት ተጀመረ፡፡

የቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ከጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ጋር በመተባበር ለሦስት ተከታታይ ቀናት የሚቆይ የክረምት በጎ ፍቃድ ነፃ የጤና ምርመራና የሕክምና አገልግሎት ዛሬ አስጀምረዋል። በፕሮግራሙ ላይ የቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር እሸቱ ለማ ባደረጉት ንግግር በጎነት በቅንነት የሚከናወን መልካም ሥራ መሆኑን አውስተው፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ በልዩ ልዩ መስኮች እየተከናወኑ ያሉ የበጎ ፍቃድ አገልግሎቶች ድጋፍ የሚሹ ወገኖችን በማገዝና አብሮነትን በማጠናከር ረገድ ከፍተኛ ድርሻ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፍቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ አሥራት ንጉሤ በመድረኩ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት በክረምት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ከሚከናወኑ ተግባራት አንዱ በሆነው የጤና ዘርፍ ክፍለ ከተማው በነፃ ሕክምና እና በደም ልገሣ ሰፊ ሥራ እያከናወነ እንደሚገኝ ገልፀው “ዛሬ የተጀመረው የነፃ የጤና ምርመራና ሕክምና አገልግሎት የጤና ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች ትልቅ እድል መሆኑን ተናግረዋል።

በመዲናዋ ይህ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ምክትል ኮሚሽነሯ የተናገሩት። ወ/ሮ አስራት መርሐ ግብሩን ያዘጋጁትን የቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደርን እና የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልን ምስጋና አቅርበዋል።

የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል እንደ ጤና እና የትምህርት ተቋምነቱ ከመደበኛ ሥራው ጎን ለጎን ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት በስፋት እንደሚንቀሳቀስ የሆስፒታሉ ዋና ሥራ አስፈጻሚው ዶ/ር አብዱራዛቅ አሕመድ ገልፀው ሆስፒታሉ ባለፈው ዓመትም በተመሳሳይ በቦሌ ክፍለ ከተማ ነፃ የጤና ምርመራና ሕክምና አገልግሎት በመስጠት ለወገን ደራሽነቱን በተግባር ማሳየቱን ጠቅሰዋል።

ከሐምሌ 28-30/2017 ዓ.ም ለሶስት ቀባት በሚቆየው በዚህ ነፃ የህክምና አገልግሎት 180 የጤና ባለሙያዎች እንደሚሳተፉ ተመላክቷል።
4👍2
በቂርቆስ ክፍለ ከተማ በክረምት በጎ ፈቃድ ፕሮግራም የ12 አቅመ ደካሞችን የመኖሪያ ቤት ችግር የሚቀርፈው የG+3 ህንፃ ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ ነው።

 በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 05 በክረምት የበጎ ፈቃድ ፕሮግራም በመንግስት የልማት ድርጅቶች አማካኝነት 12 አቅመ ደካሞችንና አረጋውያንን ተጠቃሚ የሚያደርግ ባለአራት ወለል ህንፃ ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ ይገኛል።

 የመኖሪያ ህንፃው ሲጠናቀቅ ከ60 በላይ ቤተሰቦችን የመኖሪያ ቤት ችግር ይቀርፋል ተብሎ ይጠበቃል። የግንባታ ስራው እየተፋጠነ መሆኑንና በቅርብ ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች እንደሚተላለፍ የክፍለ ከተማው የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብራሂም አባስ ተናግረዋል።

ከተማ አስተዳደሩ በ90 ቀናት የክረምት በጎ ፈቃድ ፕሮግራም በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር 2 ሺህ 500 መኖሪያ ቤቶችን ገንብቶ ለአቅመ ደካሞች፣ አረጋውያንና ለሀገር ባለውለታዎች ለማስተላለፍ እየሰራ ይገኛል። 

"በጎ ፈቃደኝነት ለማኅበረሰብ ለውጥ!"
2👍1
ኤካ ኮተቤ ጠቅላላ ሆስፒታል በነገው ዕለት ከ100 ሺህ በላይ ከፍለው መታከም ለማይችሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ነፃ የጤና ምርመራና የህክምና አገልግሎት መስጠት ይጀምራል።

በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ላይ የኢፌድሪ ጤና ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ኮሚሽን የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም የየካ ክፍለ ከተማ እና የኤካ ኮተቤ ሆስፒታል አመራሮች እንደሚገኙ ይጠበቃል።

በክረምት የበጎ ፈቃድ መርሀ ግብር ከ100 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርገው ይህ አገልግሎት በየካ ክፍለ ከተማ ግቢ ውስጥ ለአንድ ሳምንት የሚሰጥ ሲሆን በርካታ ስፔሻሊስትና ሰብ ስፔሻሊስት በጎ ፈቃደኛ ሀኪሞች ይሳተፉበታል።

መርሃ ግብሩን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሕብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ ከየካ ክፍለ ከተማ አስተዳደርና ከኤካ ኮተቤ ጠቅላላ ሆስፒታል ጋር በመተባበር አዘጋጅቶታል። ከፍለው መታከም የማይችሉ በመዲናዋ የሚኖሩ አቅመ ደካሞች ይህን እድል በመጠቀም ጤናቸውን እንዲጠብቁ የመርሃ ግብሩ አዘጋጆች ጥሪ አቅርበዋል።
5👍1
የኀብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን - አዲስ አበባ
Photo
ኤካ ኮተቤ ጠቅላላ ሆስፒታል ከ100 ሺህ በላይ ከፍለው መታከም የማይችሉ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነፃ የህክምና አገልግሎት አስጀመረ።

ኤካ ኮተቤ ጠቅላላ ሆስፒታል ከአዲስ አበባ ከተማ የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽንና ከየካ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር ከ100 ሺህ በላይ ከፍለው መታከም የማይችሉ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነፃ የህክምና አገልግሎት "በጎ ፈቃደኝነት ለጤናማ ማኅበረሰብ!" በሚል መሪ ሃሳብ በዛሬው ዕለት አስጀምሯል።

በየካ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ግቢ ውስጥ በተካሄደው የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የኢፌድሪ ጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ይመር ከበደን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

የሀገራችን የጤና ፖሊሲ ቅድመ መከላከልን ማዕከል ያደረገ እንደመሆኑ ጤናማና አምራች ዜጋ ማፍራት ተቀዳሚ ተልዕኮ መሆኑን የገለፁት ክብርት ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ ነዋሪዎች በየጊዜው ምርመራ በማድረግ ራሳቸውን ማወቅና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን መከላከል እንደሚገባ ተናግረዋል። የጤና ሙያ በጎ ፈቃደኝነትን የሚጠይቅ ማኅበረሰብ የማገልገል ዲሲፕሊን እንደሆነ ያወሱት ሚኒስትሯ በየዓመቱ ነፃ የህክምና አገልግሎት የመስጠት ባህል እየዳበረ መምጣቱንም ነው የገለፁት። ሚኒስትሯ በዚህ ሰብዓዊ አገልግሎት እየተሳተፉ ያሉ በጎ ፈቃደኛ የህክምና ባለሙያዎችን፣ ተቋማትንና ኃላፊዎችን አመስግነዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ይመር ከበደ በበኩላቸው በህክምናው ዘርፍ ባህል እየሆነ የመጣው አገልግሎት ነፃ ህክምናን ነጮች የሚሰጡት እንደሆነ ተደርጎ ይቆጠር የነበረውን አስተሳሰብ የሰበረ አዲስ ባህል መሆኑን ተናግረዋል። ለነፃ የህክምና አገልግሎት ባህል መዳበርና መስፋፋትም ጤና ሚኒስትር ከፍተኛ አስተዋፅዖ እንዳለው የገለፁት ኮሚሽነሩ የማህበረሰቡን ጤና መጠበቅ በሁሉም ዘንድ ሊዘወተር የሚገባ ሰብዓዊ ሥራ መሆኑን ጠቁመዋል።

የኤካ ኮተቤ ሆስፒታል በየዓመቱ ለበርካታ ዜጎች ነፃ የህክምና አገልግሎት በመስጠት ማኅበራዊ ኃላፊነቱ እየተወጣ እንደሆነና ዛሬ ባስጀመረው አገልግሎትም ከ100 ሺህ በላይ ከፍለው መታከም ለማይችሉ ዜጎች ለአንድ ሳምንት የሚቆይ የነጻ ምርመራ፣ የህክምናና የምክር አገልግሎት መስጠር መጀመሩን የሆስፒታሉ ዋና ስራ አስኪያጅ ዶ/ር ሙሉቀን ተስፋዬ ተናግረዋል።
3👍1
የአፍሪካ ኅብረት ሰራተኞች በቀበና ወንዝ ዳርቻ ከ1 ሺህ 500 በላይ ችግኞችን ተክለዋል።

የአፍሪካ ኅብረት ሰራተኞች ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ጋር በመተባበር "በመትከል ማንሰራራት!" በሚል መሪ ቃል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል።

የአፍሪካ መዲናና 3ኛዋን የዓለም የዲፕሎማሲ ከተማ የሆነችውን አዲስ አበባ ለኑሮ ምቹ ለማድረግ ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል አረንጓዴ አሻራ  አንዱ መሆኑን የተናገሩት የአዲስ አበባ ከተማ የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ይመር ከበደ የኅብረቱ ሰራተኞች በዚህ ታሪካዊ ተግባር ላይ ላደረጉት ተሳትፎ ምስጋና በማቅረብ ዛሬ የተከሏቸውን ችግኞች እስኪፀድቁ ድረስ እንዲንከባከቡ ጠይቀዋል።

ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎችን ለመቋቋም ለአካባቢ ጥበቃ ስራ ትኩረት ሰጥታ በመስራት ላይ ትገኛለች ሲሉ የጠቀሱት ኮሚሽነሩ የኢትዮያን የአረንጓዴ አሻራ ተነሳሽነት ሁሉም አፍሪካውያን ሊተገብሩት ይገባል ብለዋል። 

የኮሚሽኑ የበጎ ፈቃድ ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ አስራት ንጉሴ በበኩላቸው የአፍሪካ ኅብረት ሰራተኞች ማኅበር ባለፉት ሰባት አመታት ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ሲወጣ መቆየቱን ገልፀው ዛሬ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ላይ የኅብረቱን ሰራተኞች አስተባብሮ ላደረገው ተሳትፎ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

የኅብረቱ ሰራተኞች በችግኝ ተከላ መርሀ ግብር ላይ መሳተፋቸውና ለአካባቢ ጥበቃ ስራ አስተዋፅዖ በማበርከታቸው መደሰታቸውን ገልፀው በቀጣይ ጊዜም በመሰል የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ላይ ተሳትፏቸውን ለማጠናከር ቃል ገብተዋል።

"በጎ ፈቃደኝነት ለማኅበረሰብ ለውጥ!"
👍2
በጎ ፈቃደኝነት በማኅበረሰቡ ውስጥ እንዲያድግና ልማድ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ።

በጎ ፈቃደኝነት በማኅበረሰቡ ውስጥ እንዲያድግና ልማድ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር ይመር ከበደ ገለፁ።

የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሀኪሞች ማኅበር፣ ከግልና ከመንግስት ተቋማት ጋር በመተባበር በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከሁለት ሺህ በላይ ከፍለው መታከም ለማይችሉ የክፍለ ከተማው ነዋሪዎች ነፃ የህክምና አገልግሎት አስጀምሯል።

በማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት ኮሚሽነሩ በማኅበረሰባችን ውስጥ ያለውን ጉድለት በራሳችን አቅም መሙላት እንደምንችል የበጎ ፈቃድ ስራዎቻችን ማሳያ ናቸው ብለዋል። ከዚህ ቀደም የውጭ የህክምና ቡድኖች ወደ ሀገር ውስጥ እየመጡ ይሰጡት የነበረውን ነፃ አገልግሎት በራሳችን ባለሙያዎች መስጠት ጀምረናል ያሉት ኮሚሽነሩ ለችግሮቻችን መፍትሔዎች እኛው ራሳችን እንደሆንን በተግባር አሳይተናል ሲሉ ገልፀዋል።

ኮሚሽኑ ነፃ አገልግሎት መስጠት ባህል ሆኖ እንዲቀጥል የተለያዩ ፕሮግራሞችን ነድፎ ወደ ተግባር መግባቱን የገለፁት ኮሚሽነሩ የኅብረተሰቡ የመረዳዳት ባህል እንዲሁም የበጎ ፈቃደኞች ተሳትፎ ከዓመት ዓመት እድገት እያሳየ ነው ብለዋል።

በከተማችን በየዓመቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት እያገኙ መሆኑን የጠቀሱት ኮሚሽነር ይመር በጎነት ገንዘብ ያላቸው ብቻ የሚያደርጉት ሳይሆን ጊዜ፣ ጉልበትና እውቀት ያላቸው ሁሉ የሚያከናውኑት አገልግሎት እንደሆነ ሁሉም ሊገነዘብ ይገባል ብለዋል።

ከለውጡ ወዲህ በጤናው ዘርፍ እየተለመደ የመጣው ማኅበረሰብን በነፃ የማገልገል ባህል በሌሎች የሙያ መስኮችም ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል ኮሚሽነሩ።
2👍1
መስጠትን የሚለማመድ ትውልድ ለመፍጠር የበጎ ፈቃድ ተግባራት ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ተገለፀ ።

የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ወረዳ 13 የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በ90 ቀናት ተግባራት የቤት ግንባታ ምርቃት ፣ የማዕድ ማጋራትና የደም ልገሳ መርሃ ግብር አካሂዷል።

በመርሃ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፍቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ ፀሐይ ኪባሞን ጨምሮ ኦየክፍለ ከተማውና የወረዳው ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ ፀሐይ ኪባሞ በከተማችን እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የበጎ ፈቃድ ተግባራት በገንዘብ የማይተመኑ፣ ሚናቸውም የጎላ መሆኑን ገልጸዋል። ብልፅግናችን እውን ለማድረግ ሰው ተኮር ተግባራት በማከናወን አዲስ አበባን ለመለወጥ የሀገር ባለውለታዎች፣ የአቅመ ደካማ ቤቶችን መገንባት፣ በጎ ፈቃደኝነትን ባህል ማድረግ እንዲሁም የኢንሼቲቭ ተግባራትን በማስፋፋት አካባቢያያችን ለነዋሪዎችና ለህፃናት ምቹ ስፍራ መፍጠር የሚያስችል መሆኑንን ተናግረዋል ።

የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ ፋክያ ሸሪፍ በበኩላቸው ኅብረተሰቡና ባለሀብቶች በቅንነት የበጎነት መርህን በመቀበል የነቃ ተሳትፎ በማድረግ በ90 ቀናት ተግባራት፣ የአረጋውያን የቤት ግንባታ፣ የማዕድ ማጋራት፣ የህፃናት መጫወቻና መዝናኛ ስፍራዎች ግንባታ ሰራዎች መከናወናቸውን መግለፃቸውን ከክፍለ ከተማው ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
3👍2
የግልፅ ጨረታ ማስታወቂያ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ለ2018 በጀት ዓመት ልዩ ልዩ አገልግሎቶችንና እቃዎችን በግልፅ ጨረታ አወዳድሮ መግዛት ይፈልጋል።

👉ሎት 1- ልዩ ልዩ የኅትመት አገልግሎቶች
👉ሎት 2 - የሁነትና መድረክ መምራት አገልግሎቶች
👉ሎት 3 - የሆቴል አገልግሎት
👉ሎት 4 - የከተሪንግ አገልግሎት
👉ሎት 5 - አላቂ፣ የፅዳት እቃዎች፣ ደንብ ልብሶችና ውኃ አቅርቦት
👉ሎት 6- የትራንስፖርት አገልግሎት
👉ሎት 7- ቋሚ እቃዎች (ኮምፒውተሮች፣ ካሜራና የካሜራ እቃዎች)
👉ሎት 8- የጋራዥ አገልግሎት
👉ሎት 9- የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች ጥገና አገልግሎት
👉ሎት 10- የማስታወቂያ፣ የሚዲያና የፕሮዳክሽን አገልግሎት
👉ሎት 11- የክህሎትና የባህሪይ ስልጠና አገልግሎቶች

ስለሆነም በዘርፉ ህጋዊ ፈቃድ ያላቸው ተጫራቾች ይህ ማስታወቂያ ከወጣበት ነሐሴ 12/2017 ዓ.ም ጀምሮ ባሉት 10 ተከታታይ የስራ ቀናት ፒያሳ ቀይ ባህር ኮንዶሚኒየም ፊት ለፊት በሚገኙው ቢሯችን ቢቲ ታወር 3ኛ ወለል ፋይናንስ ዳይሬክቶሬት የማይመለስ 200 ብር የጨረታ ሰነዱን መግዛትና መወዳደር ይችላሉ።

ጨረታው በ11ኛው የስራ ቀን ተጫራቾች ወይም ህጋዊ ወኪሎቻቸው በተገኙበት ከሎት 1 እስከ ሎት 6 4:30 ሰዓት ላይ እንዲሁም ከሎት 7 እስከ 11 በ12ኛው ቀን በተመሳሳይ ሰዓት ይከፈታል።

ኮሚሽኑ የተሻለ አማራጭ ካገኘ ጨረታውን ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል የመሰረዝ መብቱ የተጠበቀ ነው።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን
👍32