ወግ ብቻ
17.1K subscribers
526 photos
11 videos
21 files
52 links
በየቀኑ ምርጥ ምርጥ የጥበብ ስራዎችን ለማግኘት የቻነላችን ተከታይ ስለሆኑ እናመሰግናለን።

@getem @serenity13
@wegoch @Words19
@seiloch
@zefenbicha

Creator @leul_mekonnen1
Download Telegram
Gize Wegoch, [Oct 21, 2024 at 8:57 PM]
አይጠሩ
...........

   በአማት መወደድ ለጥቂት ዕድለኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ የተሰጠ ፀጋ ይመስለኛል።በተለይ ደግሞ በቁመት የምትበልጥህን ሴት ልታገባ እየተዘጋጀህ ከሆነ!ነፍሳቸውን ይማርና ጎረቤታችን አብዬ በላቸው
"ፍቅር ምን ድረስ ክፉ ነው?"ተብለው ሲጠየቁ
"እኔና ሰዋለምን እስቲያጋባን ድረስ" ይሉ ነበረ አብረው ሲቆሙ በጡታቸው ትክክል የሚሆኑትን ሚስታቸውን እያሰቡ።የሞቱት አብሯቸው የኖረው አስም በሌሊት አፍኗቸው ነው ቢባልም የመንደራችን 'ፓፓራዚዎች' እንደሚሉት ከሆነ ግን ለሞት ያበቃቸው አስሙ ብቻ ሳይሆን በባለቤታቸው ጡቶች መሃል አፍንጫቸው መታፈኑ ነበር።
እሰቡት 1.50 ሆኜ 1.75 የምትረዝም እጮኛ ስይዝ! አብዬ በላቸው ከነሚስታቸው ድቅን ይሉብኛል። ከመጋባታችን አንድ ወር አስቀድማ ከቤተሰቦቿ ጋር አስተዋወቀችኝ።ያደገችው ከአሽሙረኛ እናቷና ከጉልቤው ወንድሟ ጋር ነው።ውበቷን ያየ የእናቷን ወግ አጥባቂነት እና የወንድሟን ኃይለኝነት መገመት አያቅተውም።ልታስተዋውቀኝ ቤቷ የወሰደችኝ ቀን እናቷ እትየ ዘውዴ ከእግር እስከራሴ አልቢን በሚያስንቅ አይናቸው እንደሽንኩርት ከላጡኝ በኋላ የሚያበሽቅ ሳቃቸውን አስከትለው
"እንዴት ያለ ኮረሪማ አግኝተሻል ሚጡ!ና እስቲ ሳመኝ"ብለው ሱባኤ እንደገባ ገዳምተኛ ወገባቸዉን በነጠላቸዉ አሰሩና ከምድር ወገብ የሚሰፋ ሽክርክሪት መቀነታቸዉን እየቋጩ ጎንበስ አሉ። መና እንደወረደለት ሰዉ ወደ ላይ ቀና  ስል ከመቅፅበት ትከሻዬን እንደቅቤ ቅል እየናጡ አገላብጠው ሳሙኝ።ልጃቸው በሷ እንደወጣች ቁመታቸው ይናገራል።ከፊት ለፊታቸው ስቆም ከአይናቸው ይልቅ ከጡታቸው ጋር ነው የምፋጠጠው።ጃንሆይም እንደሳቸው ጡት መውደቃቸውን እጠራጠራለሁ።እንኳን የሳቸው ጡት ሁለት ልጅ የጠባው ይህች ጉደኛ ሀገር ራሷ ደርግ አይጥ እንደቀመሰው ካልሲ ቦትርፏት፣ኢህአዴግ እንደ ገና ዳቦ በላይ በታች አንድዷት፣የአሁኑ ጉድ በወሬ ፓትራ እስከጥግ ነፋፍቷት...የሳቸውን ጡት ያህል ዝቅ አላለችም።

  ሳሎናቸው ግድግዳ ላይ የተሰቀለውን የቤተሰብ ፎቶ ሳይ "አቤት ግጣም በልክ ሲገኝ!" አሰኘኝ።ባለቤታቸው ከእሳቸው የበለጡ ብቅል አውራጅ ቢጤ ናቸው።ወንዱ ልጃቸው ከሚጡ ትንሽ ይረዝማል።ደፍሬ ሳሎናቸውን የረገጥኩ የመጀመሪያው ስንዝሮ እኔ ሳልሆን አልቀርም።

ወደ ምግብ ጠረጴዛው ስናዘግም አሽሙር የተካነ አፋቸውን አሸራመው እየቃኙኝ
"ሶፋው ላይ እንሁን መሰል ጠረጴዛው አለቅጥ ረጅም ነው" አሉኝ።ጠረጴዛው የረዘመብኝ እንደሁ ሌላ ዝርጠጣ ስለሚከተለኝ ጥያቄአቸውን ተቀብዬ ወደ ሶፋው አመራን።ከመቀመጣችን ሌላ ብቅል አውራጅ ባልቴት እየተንጎማለሉ ዘለቁ።ሚጡ ወደ ጆሮዬ ጠጋ ብላ
"አክስቴ ናት ኃይልሻ" አለችኝ።
እትየ ዘውዴ
"ህብስቴ መጣሽ?ቀረሽ ብየ ነበር'ኮ እመዋ" አሉና አገላብጠው ከሳሟቸዉ በኋላ አቆልቁለው እያዩኝ
"ነይ ሳሚው የሚጡን ባል...እየውልሽ እንዴት ያለውን ምጥን የወንድ አውራ እንዳመጣችው"
"ኧግ!የቢያዝኔ ምትክ...እምጷ...የአባቷ ምትክ...እምጷ...የት አገኘሃት?... እምጷ ይችን መለሎ...እምጷ"
የሞት ሞቴን  ፈገግ ብዬ ከመቀመጤ በእህታቸው እግር ተተክተው ይወጉኝ ገቡ።
"ዋዋዋዋዋ...እንደው ከየት አገኘሃት?ማነበር ያልከኝ ስምህን"

"ኃይሌ"
"ምንድን ነዉ ስራህ?"
 'ገጣሚ ነኝ' ልላቸው ፈለኩና የዘመኔ ገጣምያን  በህሊናየ ድቅን አሉብኝ።
በእዉቄ እንኳን ቁመቱ ጊዜ ጠብቆ የሚጨምረዉ ግጥም ወይም ወግ ሲያነብ ብቻ ነዉ። ምክንያቱም ተመልካቹ ሁሉ ተቀምጦ ስለሚያዳምጠው።
ብዙዎችን በአይምሮዬ ማሰላሰል ስጀምር ገጣሚነቴ ተኖ ጠፍብኝ ።
"ምን አልከኝ ?"ሲሉኝ
"እ የዩኒቨርሲቲ መምህር ነኝ" አልኳቸዉ በደባልነት የያዝኩትን ሙያዬን።
"እ...መምህርነት ሸጋ ነው!...እና ከየት አገኘሃት በል ይችን መለሎ?"
"እህ...ህ...ህ...ትውውቃችን እንኳን ከድሮም ነው...ከትምህርት ቤት"
"ኧረግ ኧረግ ኧረግ ኧረግ!!...መቸም ተፊት ተቀምጣ እየከለለችህ አስቸግራህ ነው እሚሆን...እሂ...ሂ...ሂ...ሂ"
'ጥርስዎት ለሙቅ አይትረፍ!ድዳም'

"ኧረ በነገር አትያዣቸው ህብስቴ ምሳው ይቅረብ" አሉና አማቴ ሰፋ ባለ ትሪ ዶሮ ወጣቸውን በአይብ አጅበው አቀረቡት።
'ሰው ከረዘመ ሞኝነት አያጣውም' የሚለው አባባል እዚህ ቤት አይሰራም።እንደውሃ ሙላት እያሳሳቁ መግደልን ተክነውበታል።

ህይወቴ በረጃጅም ሴቶች ዙሪያ እንዲሽከረከር ማን እንደፈረደብኝ ባላውቅም 8ኛ ክፍል እያለን በደብዳቤ የጠየቅኋት መለሎዋ ማህሌት ራሱ  ደብዳቤውን ለስም ጠሪ ሰጥታ ተማሪዎች ፊት ከማስነበብ የከፋ አልጨከነችብኝም። የልብ ስእል ለመሳል የቀደድኩትን ወረቀት እናቴ ሰብስባ ሶስት እንጀራ ከነ ካሲናዉ እንዳወጣችበት ሳስታዉሰዉ ይደንቀኛል።
በጦር ተወግቶ ለሚደማው ልቤ ማሳያ ይሆነኝ ዘንድ አባቴ በፀሀፊነት ከሚያገለግልበት የሰፈሩ እድር የተቀበለውን ብቸኛ ቀይ እስኪብሪቶ በማገንፈሌ አንድ ፌርሜሎ ከሰል ተቀጣጥሎ ለሳምንት ወጥ መስሪያ የሚሆን በርበሬ ታጥኜ ነበር።ይህን ሁሉ መስዋዕትነት ከፍዬ
"ያም አለ ያም አለ የአተር ገለባ ነው
ሰው ይዋደድ እንጅ ቁመት ለአገዳ ነው" ብዬ መጻፌን ሳስታውስ እንደቂል በራሴ እስቃለሁ።

  ዶሮው ተበልቶ ሲያበቃ ያመጣሁት ውስኪ ተከፈተና አንድ ሁለት እያልን ጨዋታ ቀጠልን።በመሃል አማቴ ግድግዳ ላይ የተሰቀለውን የባለቤታቸውን ፎቶ አዩና አንደ መሳቅም እንደማልቀስም እያደረጋቸው

"አየ....የ...የ...ቢያዝኔ ዛሬ ነው  የሞትክ!አየ የኔ ጠምበለል!"ወዲያው ወደ ሚጡ ዞረው
"አይደለም እንዴ አንች?ዛሬ አይደለሞይ የሞተው?እንዲህ አለምሽን ሳያይ...አይ ቢያዝኔ!" ብለው በተቀመጥኩበት ከአፈር የሚደባልቅ አስተያየት አከሉልኝ።

የቁመቴን ማጠር የኪሴ መወፈር አካካሰው እንጂ እናትየው የዛኑ ቀን ከኔ በሚረዝም በቡሀቃ ማማሰያቸው እያጠደፉ ቢያባርሩኝ እንዴት ደስ ባላቸው!ባስተዋወቀችን በሳምንቱ የኔዋ ጉድ ከሰርጉ በኋላ የምንገባበትን ቤት እናቴ ካላየችው ብላ እየጎተተች አመጣቻቸው።ሳሎኑን በገረፍታ አዩና ምኝታ ቤት ዘው ብለው ገቡ።አልጋው ላይ አፍጥጠው
"ምነው እንዲህ ሰፋ?በራይ ልትወጡበት ነው?ባይሆን ቁመቱን ጨምሩት!" አሉ።የልጃቸውን ቁመት ያህል በእግዚሀሩ እንኳን መመካታቸውን እንጃ!

  ሰርጉ ሳይሰረግ እንዲህ የቋንጃ እከክ የሆኑብኝ ከተሰረገ ወዲያ ሊኖረኝ የሚችለውን ህይወት ሳስበው ሚጡን ማውራት እንዳለብኝ ተሰማኝ።
"እትየ ዘውዴ ከሰርጉ በኋላ ለበዓል ካልሆነ እንዲመጡ አልፈልግም!"አልኩ ምርር ብዬ

"ምን ማለትህ ነው ኃይልሻ?እናቴ'ኮ ናት!"

"ለኔ ደግሞ አማቴ ናቸው!የማይወዱኝ አማቴ!ጣልቃ ገብነትም'ኮ ልክ አለው።አንቺ ለምታገቢኝ የሳቸው አቃቂር አውጭነት ምን ይሉታል?"

"ኢሂ...ሂ...ሂሂሂ...እማዬ'ኮ ተጫዋች ስለሆነች ነው...ደግሞም የምትወደው ሰው ላይ ነው የምትቀልደው...አትቀየማት"ብላ በጥርሷ አዘናጋችኝ።

ሰርጉ 3 ቀን ሲቀረው ለንቦጯን ጥላ መጣች።
"ምን ሆነሽ ነው?" ዝም

"አንቺ ሚጡ ምን ሆነሽ ነው?" ዝም

"አትናገሪም እንዴ?"

"ከእማዬ ጋር ተጣላን"ብላ ለንቦጯን ይብስ ዘረጋችው።

"በምን?ምን ተፈጠረ?"

የስልኳን ፎቶ ማከማቻ ከፍታ አንድ ሂል ጫማ አሳየችኝና
"ይሄን ጫማ ለሰርጌ አደርገዋለሁ ብዬ የዛሬ ወር ነው የገዛሁት።ትናንትና ማታ አይታው 'የዘውዴ መቃብር ሳይማስ ይኸን ለብሰሽ አትሞሸሪም!' " አለችኝ።
Gize Wegoch, [Oct 21, 2024 at 8:57 PM]
👍46😁135🥰1🤔1
'ለምን' ብዬ ልጠይቅ ከማሰፍሰፌ ምክንያታቸው ተገለጠልኝና አስችለኝ ብዬ
"ታዲያ ከሳቸው ደስታ የሚበልጥ ምን አለ ሚጡዬ?በቃ የመረጡልሽን አድርጊ እናትሽ አይደሉ?" ብዬ አባበልኳትና አቅፌአት የጨጓራዬን ጭስ ወደ ባዶው አየር ለቀቅሁት።

የመሞሸሪያችን ቀን እሳቸውን የቻለ ትዕግስቴን ጎረቤቶቻቸውና ወዳጆቻቸው ሲፈታተኑት ዋሉ።እዮብም እንዲህ መፈተኑን እንጃ!ታላቅ ወንድሟ ካሳሁን ጓደኞቹን ሰብስቦ ሰርጌን የጀማሪ ክብደት አንሺ የቅርፅ ዉድድር አስመሰሉት።   በሌባ ጣቱ መሬቱን እየጠቆመ
"ሎ...ሎጋው  ሽቦ...ቦ" ሲል
"ኧረ የምን ሎጋው ሽቦ?እስቲ ሌላ ትከሻ እሚፈትን ዘፈን አምጡ"አሉ  ጎረቤታቸው እትየ አስካል።የቀለም ትምህርቱም ሆነ ህይወት ራሷ ባስተማረችኝ ልፈታው ያልቻልኩት ትልቁ እንቆቅልሽ ሴት ስታርጥ ለምን አሽሙረኛ እንደምትሆን ነው።አዛውንቱን ቀርቶ ወጣቱን የሚያስት ጥርሳቸውን ብልጭ እያደረጉ ያቀነቅኑ ገቡ።
አንች የኔ አበባ ነሽ የኔ አበባ...
አንች የኔ አበባ ነሽ የኔ አበባ(ተቀባይ)
....
መላ ነው ነይ መላ
እነው መላ መላ(ተቀባይ)(2x)
የዘውድነሽን ልጅ ነይ መላ
እነው መላ መላ(ተቀባይ)
ወዴት አገኛት       "      "
አለ እናቷ ጓዳ      ''      "
መታያም የላት      "      "
የኔማ ዘውድነሽ       "        "
እጇ ያረፈበት           "        "
ለአልፎ ሂያጅ ይበቃል  "       "    
ማጠር አያውቅበት  "     "
እየው እየው መላ

አሉና ለ ሁለት ደቂቃ ያህል ትከሻቸው እስኪገነጠል ተንዘፍዝፈው ከከበባቸው ተቀባይ መሃል ወጡ።የሳቸውን መንዘፍዘፍ ተከትሎ አማቴ በኩርፊያ ተነፋፍተው ወደ ጓዳ እያቶሰቶሱ ሲገቡ ታዝቤ ነበር።
በነጋታው  የተከራየነዉን ቬሎ መልሰን በአማቴ ሰፈር በኩል አለፍን...ሰይጣን ሹክ ብሎን ነው መቼስ!እትየ ዘውዴ ቤት ስንደርስ በርከት ያለ ሰው ተሰብስቦ ስላየን  ጠጋ አልን።አማቴ እያማረሩ ለተሰበሰበው ህዝብ ስሞታ ያቀርባሉ።

"ምነው ነገር በኔ መግነኑ?አጭር አምቻ በኔ አልተጀመረ!ምነው ዘቢዳር በርጩማ እሚያህል አምቻ ስታመጣ ምን ተባለ?ደሞ ደግሸ ባበላሁ እኔ ላይ አሽሙር አስካል?እኔ ላይ?... ቁመት ቢረዝም ምን ሊረባ??በቁመት የጎዳውን በጠባይ ክሶት የለ?...እንደአንች አምቻ ነጋ ጠባ ከሚጎረጉጫት ኧረ የሽቶ ጠርሙስ አክሎ መኖር በስንት ጣዕሙ?..."እያሉ የጥያቄ ናዳ ሲያዥጎደጉዱ እትየ ዘቢዳር የተሰበሰበውን ሰው እየገፈታተሩ እትየ ዘውዴ ላይ ደረሱ

"እከከከከከከ!ይች ናት ዘቢዳር!የማን አምቻ ነው በርጩማ አንች?የኔን አምቻ ነዋ ምሽቱ ብብትና ብብቱን ይዛ አልጋ ላይ እምታሰቅለው!አልሰማንም'ኮ አሉ...አልሰማንም...አሁን ማን ይሙት ከአንች አምቻ የሚወደለው እንቅፋት ሆኖ የሰው ጥፍር አይልጥም? " እያሉ ሲውረገረጉ
ሹልክ ብዬ ወጣሁና ከጥቂት እርምጃ በኋላ ያገኘኋቸውን አንድ የኔ ቢጤ አባት ሰላም ብዬ ጥያቄዬን አስከተልኩ።

"አባቴ እንደው መዘጋጃ ቤቱ በየት በኩል ይሆን?"
"ማን ሞቶ ነዉ?" ደንገጥ ብለው ጥያቄዬን በጥያቄ መለሱት።
ቃል አጠሮኝ ጉዞየን ቀጠልኩ።ለካ ፍታትና ቀብር ለሞተ ብቻ ነዉ።

ዘማርቆስ

@wegoch
@wegoch
@paappii
👍43😁187👏4
Forwarded from Studio Anaya (Ribka Sisay)
አዲስ አበባ የምትገኙ ብቻ ከትምህርት ጋር የተገናኙ ማስታወቂያዎችን ለመስራት ከ10-15 አመት ያሉ ሴት እና ወንድ ካስቶች እየመለመልን ስለሆነ 3 የተለያዩ ፎቶዎችን ወላጆች ከስልካቹ ጋር @Ribki30 ላይ ላኩልን።
👍32
እማማ አፀደ የሚባሉ ጎረቤት አሉን የእናቴ ጓደኛ ናቸው። እማማ አፀደ አመም አድርጓቸው ህመማቸው በባሰ ቁጥር እናቴን ጠሏት።

ይሰድቧታል ሌባ ናት ይላሉ።
መሰሪ ናት ይላሉ።
ልትገለኝ ትፈልጋለች ይላሉ።
መርዝ አበላቺኝ ይላሉ ። አትምጣብኝ ብለው ስሞታ ይናገራሉ ሌሊት እቤቴ ልትገባ ነበር ይላሉ ።

ሰው እንዳትመስላችሁ ይላሉ ። እናቴ ቤታቸው መሄድ አቆመች ።

ከቤት መውጣት እያቆሙ ግቢያቸው መዋል ጀመሩ ....

እናቴ እሷ መሆኗን አትንገሩ ብላ ፤ ምግብ ትልክላቸዋለች ። በእህታቸውን ልጅ ፤ ምን ጎደለ ጤናቸው እንዴት ነው እያለች ትሰልላቸዋለች...

ንዴት ሊገድለኝ ይደርሳል ። እቆጣታለሁ << ስምሽን እያጠፉሽ እየሰደቡሽ እየጠሉሽ አትተያቸውም ወይ?>> እላታለሁ!!

<<ጭንቅላታቸው እጢ ወጥቶባቸዋል እሱ ነው ትንሽ ቀየር ያደረጋቸው እንጂ ፤ እሳቸው እንኳን ሳልበድል ብበድላቸው እንኳን በክፉ አያነሱኝም>> ትለኛለች።

ምግብ ትልክላቸዋለች ። በእህታቸው ልጅ በኩል የሚያስፈልጋቸውን መድኃኒት መግዣ ከኛ ወስዳ ... ተበድራም ቢሆን ትገዛላቸዋለች ። እሳቸው ያቺ ምናምንቴ ፣ ድግምታም ያቺ ነጠላ እያሉ ጮክ ብለው እናቴን ሲሰድቧት ይውላሉ ።

ጠላኋቸው !!

አንድ ቀን ለምን ግን እንዲ ስምሽን እያጠፉ እየጠሉሽ እያልፈለጉሽ አልጠላሻቸውም? ብዬ እናቴን ጠየቅኋት።

<<ጓደኛዬ ናቸው! እዚህ ሰፈር ስመጣ እሳቸው ናቸው ያለመዱኝ ። እድር ያስገቡኝ ፥ የሌለኝን እቃ ያዋሱኝ ፥ የተቆረቆሩልኝ ፥ የአረሱኝ ፣የመከሩኝ...

እንዲህ አይባልም እያሉ መንገድ ያሳዩኝ እርሳቸው ናቸው ። ድንገት ታመው ነው የተቀየሩት ።ከሁሉም ጋር ነው መጣላት የጀመሩት እኔ ላይ ትንሽ ጠንከር አሉ እንጂ ...

በክፉ ግዜ እንኳን ወዳጅ ላይ ጠላት ላይ አይጨከንም!!

የጨዋ ሰው ልክ የሚታየው ሲጣሉት ነው ። በፍቅር ግዜ ሰው አይመዘንም ክፉ ግዜ ነው ሰው የሚያጠለው ....

አፀዱ እንዴት አይነት ጥሩ ሰው መሰሉህ ዛሬ ህመም ተጣብቷቸው እን'ጂ ። ስንት ቀን መሰለህ እጦት በሳቸው ሳብያ ከቤታችን የተባረረው ።
አፀደ ደግ 'ሩህሩህ ናቸው...

እናንተ ሳትወለዱ ማንም ሳይኖረኝ ነው ከኔ ጋር የነበሩት...

የአፀደ ውለታ አለብኝ !>>

By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
71👍34🔥6🥰2👏2
ያከሸፈቻቸው ያከሸፏት አገር!
(አሌክስ አብርሃም)

የ8ኛ ክፍል ተማሪወች እንደነበርን ነው። አንድ ቀን የሆነ አስተማሪ ቀረ። በዛ ክፍት ክፍለጊዜ ሁላችንም ደስ ያለንን ስንሰራ (አብዛሀኞቻችን ወሬና መንጫጫት) አንድ ምስጋናው? የሚባል የክፍላችን ልጅ ብላክቦርድ ላይ በወዳደቀ ቾክ ሁለት ሰወችን ሳለ። ስዕል ስላችሁ ይሄ ዝም ብሎ የልጅ ስዕል አይደለም፣ ባስታወስኩት ቁጥር የሚገርመኝ የግንባራቸው መስመር፣ ፊታቸው ላይ ያረፈው ጥላ ልብሳቸው ላይ ያለው ፓተርን ሳይቀር ፎቶ የሚመሳስሉ ፖርትሬቶች። ደግሞ የሳለው ምንም እያየ አልነበረም። እማሆይ ቴሬሳ ሁለት እጆቻቸውን እንደህንዶች ሰላምታ አገናኝተው ግንባራቸውን እንዳስነኩ እጃቸው መሀል መቁጠሪያ ተንጠልጥሎ፣ እንዲሁም ቀዳማዊ ሀይለስላሴ ከነንጉሳዊ ልብሳቸው። ወደጎን ዞር ብለው። ሁላችንም ተገረምን ተደነቅን። የስእሎቹ መጠን የእውነት ሰው ያክሉ ነበር።

ቀጣዮ ክላስ ጅኦግራፊ ነበር። ኮስታራው አስተማሪያችን ገባና ስዕሎቹን አየት አድርጎ "ማነው የሳለው?" አለ ። በአንድ አፍ "ምስጋናው" አልን በአድናቆት ጭምር። ራሱ ወደምስጋናው ወንበር ተራምዶ የያዘው ልምጭ ተሰባብሮ እስከሚያልቅ ቀጠቀጠው። እና በቁጣ "ይሄ የተከበረ የትምህርት ገበታ ነው ! ማንም እየተነሳ የሚሸናበት አይደለም ደደብ" ብሎ ደነፋ። ዳስተሩን አንስቶ አንዴ እጁን ሲያስወነጭፈው ሀይለስላሴን ለሁለት እማሆይ ቴሬሳን አናታቸውን ገመሳቸው። አጠፋፍቶ ማስተማሩን ቀጠለ። ምስጋናው ከዛ በኋላ እንኳን ሰሌዳ ላይ ወረቀት ላይ ሲስል አላስታውስም።

ብዙ ዓመታት አለፉ። አንድ ቀን አዲስ አበባ ፒያሳ መርከብ የምትባል ምግብ ቤት ምሳ በልተን ስንወጣ በር ላይ አንድ የጎዳና ተዳዳሪ በፌስታል ፍርፋሪ ሲበላ አየሁ ምስጋናው ነበር። ቢጎሳቆልም አልጠፋኝም። ዛሬ በምን አስታወስኩት? አንድ አሜሪካዊ ህፃን ሰሌዳ ላይ በቾክ የሳለው ስእል በአስተማሪዎቹና በትምህርት ቤቷ ርዕሰ መምህር ስለተደነቀ በቀስታ ሰሌዳውን አንስተው አንድ ቢሮ ግድግዳ ላይ እንደሰቀሉት አነበብኩ። ስዕሉ ለዓመታት እንዲቆይ የሆነ ነገር እናስደርጋለን ብላለች ርዕሰ መምህርቷ። አገር ባከበረቻቸው ትከብራለች ባከሸፈቻቸው ትከሽፋለች። ይህ ሒሳብ የገባቸው ብፁአን ናቸው። ለትውልድ ፍቅር ያወርሳሉና።

@wegoch
@wegoch
@paappii
110👍52😢41🔥1
Poem.ogg
2.1 MB
#yohabi ደብዳቤ
የማይድን ናፍቆት.... 'የተረሳው ክፍል'

"ስትሄድ ያልከኝን መርሳት አቅቶኛል"

@wegoch
@wegoch
@paappii
👎54👍2🔥1
አልቃሽና አጫዋች
(በእውቀቱ ስዩም)

ቦጋለ በሚባል ስም የሚታወቁ ሁለት ስመጥር ሰዎችን አውቃለሁ፤ የመጀመርያው የ”ፍቅር እስከመቃብሩ” ገበሬ፥ ቦጋለ መብራቱ ነው፤ ሁለተኛው በገሀድ ኖሮ አልፏል፤ድሮ በጎጃም ሽማግሌዎች ክፉ ሰው ሲራግሙ፥ “ ቦጋለ ያይኔ አበባ ስምህን ይጥራው “ይሉ ነበር ይባላል፤

ቦጋለ ያይኔ አበባ ስመጥር አልቃሽ ነበር፤ የጥንት አልቃሾች ቀላል ሰው እንዳይመስሏችሁ፤ በለቅሶ ወቅት የሚታየውን ትርምስ እና ጫጫታ ወደ ኪነጥበብ ትርኢት የሚቀይሩበት ተሰጥኦ ነበራቸው ::

ቦጋለ ያይኔ አበባ በወጣትነቱ ያገሩን መሬት አርሷል፤ እንዲሁም ያገሩን መሬት በእግሩ አዳርሷል፤ ወደ አልቃሽነት ሙያ እስኪገባ ድረስ ግን የረባ ስኬት አላገኘም ነበር፤ ይህንን በማስመልከት፥ እንደ ግለ-ታሪክ እና Cv በምትቆጠርለት እንጉርጉሮው እንዲህ ብሎ ነበር፤

“አርሼም አየሁት ፥
ነግጄም አየሁት
አልሰሰመረም ሀብቴ
አልቅሼ እበላለሁ እንደ ልጅነቴ “

ቦጋለ ያይኔ አበባ ከዘመናት ባንዱ ወግ፥ ደርሶት ሴት ልጁን ዳረ፤ እንጀራ ሆኖት የቆየው ሞት አሁን በሌላ ገጹ ተከሰተ፤ ሙሽሪት በሰርጓ በሳምንቱ ተቀጠፈች፤ እልልታው ወደ እሪታ የተቀየረበት ቦጋለ በተሰበረ ልብ ይቺን ውብ እንጉርጉሮ ወረወረ፦

“እንዲህ ያለ አምቻ፥ ክብሩን የዘነጋ
በፈረስ ሰጥቼው ፥ መለሰልኝ ባልጋ”

ኪነጥበብ ፥ አስቀያሚ መከራን ወደ ውበት መቀየር እንደምትችል ይቺ እንጉርጉሮ ምስክር ናት፤

ከሞት ሁሉ ቅስም ሰባሪው የልጅ ሞት ይመስለኛል ፤ ከወሎ የፈለቀች ከወዳጄ የሰማሁዋት ፥አንድ ጨዋታ ትዝ ትለኛለች፤ አያ ሙሄ የተባለ ገበሬ ልጁ ሞቶበት ፥ጎጆው በርንዳ ላይ ከርትም ብሎ ይቆዝማል ፤ ባለንጀራው አዋ ይመር አጠገቡ ተቀምጧል፤ አዋ ይመር ወዳጁን በቃል ማጽናናት በቂ ሆኖ አላገኘውም ፤ የወዳጁን ልጅ የቀሰፈውን ፈጣሪ ለመበቀል ስለፈለገ ፥ ጠመንጃውን አነጣጥሮ ወደ ሰማይ ተኮሰ፤

ተኩሱ በረድ ሲል አዘንተኛው አያ ሙሄ ወዳጁን እያየ እንዲህ አለ፤

“ካገኘከው ገላገልኸን፤ ከሳትኸው ግን አስፈጀኸን”🙂

@wegoch
@wegoch
@paappii
👍5230👏10👎8😁6😱1😢1
ቀልድ
*

ልጅቷ ለትምህርት ቻይና ሄዳ ( በርግጥ አንዳንዶች ለንግድ ነውም ይላሉ፤ እኛ ለምን ለካራቴ ውድድር አትሄድ ምንም አያገባንም) ... ቻይና ሄዳ አንድ ቻይናዊጋ ጾታዊ ፍቅር መጀመር ከዛ በቃ ተጋቡ

ሀገር ቤት ይዛው ስትመጣ እናቷ ማመን ያቃታቸው ቻይናዊ የማግባቷ ነገር ሳይሆን የቀለቡ ነገር ነው

ቢያዩ ጊንጥ፤ ቅንቡርስ በረሮ የጉንዳን ቆሎ ወዘተረፈ

አንድ ቀን እነዚህን ነገሮች ይዞ መጥቶ ይሰራልኝ አለ

እናትየው: እውውይይ እንደው አደራ የውሻው አጥንት በሚቀቀልበት ድስት ስሩለት የኔን እቃ እንዳታነካኩ😂

የቻይናው ምግብ በኮረሪማ በበሶብላ የመሳሰሉት ቅመሞች አብዶ ተሰራለት እና ጣቱን እስኪቆረጥም አነከተ

ሆንቾፖ ኪሊቾቺቿቶኮዃ ሲንፊቻቹዎ አላቸው

እናትየው: ምንድን ነው የሚለኝ ሰውዬሽ

ልጅቷ: እማዬ ጣት ያስቆረጥማል በጣም አመሰግናለሁ ነው ያለሽ

ሾሆ ሲጆቾ ፖጂሊሃኪቾ ቺኒማማ

ኧረረረረ በቃ ምንም አይናገር አፉን እንደቆረበ ሰው አፍኖ ይቀመጥ ፌንጣዎቹ ዘለው እንዳይወጡ ይተወኝ ዝም ይበል ምስጋናው በቃኝ

ልጅቷ: አይ እማዬ እሱማ እያለ ያለው በጣም ጠግቤአለሁ የተረፈውን ከድናችሁ አስቀምጡልኝ በኋላ እበላዋለሁ

🧐: ኧ? ከድናችሁ? ምን እንዳይ ገባበት? በረሮው ውስጥ በረሮ እንዳይገባ ነው? ጊንጣ ጊንጥ ውስጥ ጉንዳን እንዳይገባ ነው?

🙄

በማስተዋል አሰፋ የተፃፈ

@wegoch
@wegoch
😁87👍3012🔥1
ጥገኛን ተውና ታታሪውን አሳድገው!

የሆነ ጊዜ የዩናይትድ አረብ ኤመሬትስ መስራች ሼህ ረሺድን ኢንተርቪው አድርጌው ነበር። ስለነገዋ ዱባይ ስጠይቀው የሰጠኝ መልስ አስገርሞኝም አስደንቆኝም ነበር

ምን አለ?

"አያቴ ግመል ይጋልብ ነበር፣ አባቴም ግመል ይጋልብ ነበር፣ እኔ ደግሞ መርሰዲስ እየነዳሁ ነው። የኔ ልጅ ላንድሮቨር ይነዳል። የልጅ ልጄም እንደዚያው ላንድሮቨር ይነዳል። የልጅ ልጅ ልጄ ግን ግመል መጋለቡ አይቀሬ ነው!"

"ለምን ?"
ለምን ካልከኝማ!

"ክፉ ጊዜ ጠንካራ ሰዎችን ይፈጥራል። ጠንካራ ሰዎች ደግሞ ሁሉ ነገር ቀላል የሆነበትን ጊዜ ይፈጥራሉ።ቀላል ጊዜያት በተራቸው ደካማ ሰዎችን ይፈጥራሉ። ደካማ ሰዎች ደግሞ ክፉ ጊዜን መልሰው ያመጡታል። ብዙዎች አይገነዘቡት ይሆናል ፣ ነገር ግን ይህ እንዳይመጣ ታታሪዎችን ማሳደግ አለብን። ያ ሲሆን ጥገኞች አይፈጠሩም።"

By Melaku Berhanu

@getem
@getem
@paappii
77👍38🔥7👏6🥰3
አልፈልግም ስትለኝ እምባዬ እንዳይመጣ ታግዬ ፈገግ አልኩኝ ። ለእምባዬ ፊት መስጠት አልፈለኩም ። የሄደን ሰው እምባ አይመልሰውም ብዬ ነው መሰለኝ !

ግን ከፋኝ ፦

ተደግፌባት ነበር ። አደጋገፌ በጥርጣሬ አልነበረም ። ከኔ እሷን አምናት ነበር ፣ እንዳልጎዳት ስጣጣር ነበር ። እንዳላሳዝናት ሁኔታዬን ሁሌ አየው ነበር !

አልፈልግህም ስትለኝ ....

ጭር አለብኝ በግርግር ውስጥ ጭርታ ስሜት እንዴት ይወለዳል ? ጭርታው አስፈራኝ ጭርታው ድብርት ወለደ ። ስታብራራ መልስ መስጠት አልፈለኩም ። እንዲ ስለው እንዲ ይላል ብላ ምላሽ ተሸክማ እንደመጣች ገብቶኛል ።

ምላሽ ካጠና ሰው ጋር ውይይት ትርፍ የለውም ። ማን ለማን ብሎ ከማን ጋ ይሆናል ? ይሄ መስቀል ሳላጉረመርም የምሸከመው ነው !!

ግን ይሄን ሁሉ ሲሰማኝ ፈገግ ብዬ ነበር ።

እሷም አልፈልግህም ስለው ፈገግ ብሎ ነበር ትል ይሆናል ።

By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
😢61👍4014👏8🥰2👎1😁1😱1
እንኳን አገር አጥበው ቀሽረው ሊያወርሱን ...
(አሌክስ አብርሃም)

በፈረንጆቹ 2011 ጃፓን ውስጥ Fukushima የተባለ አካባቢ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ። ያውም በሬክተር ስኬል 9.0 የተመዘገበ። በሰዓታት ውስጥ 20 ሺ ህዝብ በዘግናኝ ሁኔታ አለቀ ፣6ሺ ሰው ከከፍተኛ እስከቀላል የአካል ጉዳት ደረሰበት ፣ 2500 ሰው የደረሰበት ጠፋ ፣ ግማሽ ሚሊየን ህዝብ ቤት ንብረቱን ጥሎ ተፈናቀለ። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚሉት የኛ አበወች ከነገሩ በላይ ዓለምን ያስደነገጠ ሌላ ዜና ተሰማ ። ለልጅ ልጅ የሚተላለፍ ጣጣ!

ይሄ ጦሰኛ አደጋ የተከሰተባት ከተማ ወጣ ብሎ የሚገኝ የኒውክሌር ማብለያ ተቋም አለ። Fukushima Daiichi nuclear power plant ይባላል። በዓለማችት ካሉ 25 የኒውክሌር ሀይል ማምረቻወች አንዱ ነው። በአደጋው ከዚህ ግዙፍ ተቋም የራዲዮ አክቲቭ ጨረር አፈትልኮ ወጣ። ራዲዮ አክቲቭ በቀጥታ ካገኘ ማንኛውንም ህይወት ያለው ፍጡር የሚገድል እንዲሁም ውሃ ይንካ ድንጋይ ሁሉንም ቁስ በመበከል ወደገዳይ ቁስነት የሚቀይር መራዢ ጨረር ነው። በአካባቢው ላይ ለአመታት በመቆየትም ይታወቃል። ከዚህም የከፋ ነው ኬሚስትሪው። ተጠቅቶ ከአደጋ መትረፍ ቢቻል እንኳን መትረፍ አይበለው። ዓለማችንን የሚያስጨንቃት የኒውክሌር መሳሪያ የሚፈራበት አንዱ ምክንያት ይሄው ነው።

አደጋው ጋፕ ሲል ከአካባቢውን ከገዳዮ ብክለት ለማፅዳት መላው ጃፓናዊ ተረባረበ። ይሄን ሁሉ መከራ ያወራኋችሁ ቀጥሎ ለምነግራችሁ የሚያስቀና ጉዳይ ነው። በእርግጥ ብክለቱን ማፅዳት፣ ጉዳቱንም መቀነስ ይቻላል ፣ ግን መጥረጊያህን አንስተህ በሞራል ዘው የምትልበት ዘመቻ አይደለም! የረቀቀ ሳይንስ ነው። በክር ላይ የመራመድ ያህል ጥንቃቄ ልምድና ዕውቀት እንዲሁም ዕድል የሚጠይቅ ነገር! በደመነፍስ ቦታው ላይ መገኘት ወዲያው ከመሞት የእድሜ ልክ ካንሰር ፣ለሌሎችም ዘግናኝ ጉዳቶች ሊዳርግ ይችላል። መቸስ ችግር ጀግኖችን ይፈጥራል። መላው ዓለም
"Fukushima 50"ብሎ የሰየማቸው ጡረታ የወጡ ሽማግሌወች ይህን ራዲዮ አክቲቭ ጉዳት ለመከላከል በፈቃደኝነት ከፊት ተሰለፉ።

እነዚህ ሰወች የጡረታ ክፍያቸው ያነሰባቸው ፣ ከዚህ ኑሮ ሞት ይሻላል ያሉ ጧሪ አልባ ሽማግሌወች እንዳይመስሏችሁ ፣ ከፍተኛ የኒውክሌር ኢንጅነሮች፣ ተመራማሪወች የነበሩ ጡረታ ወጥተው የተንደላቀቀ ኑሮ የሚኖሩ ጃፖናዊያን አባቶች እንጅ። ብቸኛ ዓላማቸው የድርሻችንን ኑረናል ይህን የኒውክሌር ተቋም የመሰረትነውም እኛ ነን ሀላፊነቱን መውሰድ ያለብን እኛ ነን፣ ልጆቻችንና ለቀጣዮ ትውልድ ይሄን ገዳይ ቆሻሻ አናወርስም! የድርሻውን ንፁህ አገር ይረከብ ዘንድ ሞትም ቢሆን ዋጋ እንክፈል የሚል ነበር። አንዷ የ72 ዓመት ጡረተኛ እንዲህ አለች "My generation built these nuclear plants. So we have to take responsibility for them. We can't dump this on the next generation,"እናም ወጣቶቹንና ብዙ ሊሰሩ የሚችሉትን ኢንጅነሮች ተክተው በዛ ቀውጢ ወቅት ወደተበከለው ተቋም ባጭር ታጥቀው ገቡ።

በእርግጥም ይህን ከባድ ሀላፊነት በመወጣት አደገኛውን ስራ በመፈፀም ከኋላ ለሚመጡ ወጣት ኢንጅነሮች እና ብክለቱን ለማፅዳት ለተሰለፉ ሁሉ መንገድ ጠረጉ። ጣቢያው ውስጥ ለቀናት በመቆየትና ሪአክተሩን በማቀዝቀዝ ጃፓን ይገጥማት ከነበረ የሚሊየኖች ሞት ታደጓት! ትውልድን ከቆሻሻና የሀዘን ታሪክ ውርስ ታደጉ!! የሚደንቀው ነገር አንድኛቸውም በአደጋው አልሞቱም!! አገር ለትውልድ እንዲህ ታጥቦ ተቀሽሮ በውርስ ይሰጣል ። እኛስ? እንኳን አገር አጥበው ቀሽረው ሊያወርሱን የኛን ዕድሜ የሚቀሙ፣ የቀጣዮ ትውልድ ዕጣፋንታ ላይ የጥላቻ ቆሻሻ ደፍተው የሚፎክሩ አባቶች ልጆች ሆንን ! አየህ ወጣትን እየማገዱ ኑሯቸውን ለሚያመቻቹ የጠነዙ ፖለቲከኞቻችን ይሄ ጅልነት ነው። ጃፓን እንደምን ሰለጠነች ይሉናል አገራችን እንደምን ሰየጠነች ብለን ስንጠይቅ!

@wegoch
@wegoch
@paappii
👏96👍4626😢5
Forwarded from ግጥም ብቻ 📘 (Leul M.)
የዱር አበባ

የገጣሚ ቴዎድሮስ ካሳ የግጥም መፅሐፍ የፊታችን ቅዳሜ ሕዳር 28 ከ ቀኑ 11 ፡ 00 ጀምሮ መገናኛ በሚገኘው ሞሰብ የሙዚቃ ማዕከል ቅጥር ግቢ ውስጥ በድምቀት ይመረቃል ።

በእለቱ ሁላችሁም ተጋብዛችኋል።

@getem
10👍8
መተውን የመሰለ ነገር የለም!
(አሌክስ አብርሃም)

ይታያችሁ ሴቶች በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በቀን ብዙ ጊዜ የሚነካኩት የሰውነታቸው ክፍል ምናቸውን ይመስላችኋል? (ወንዶች አትባልጉ በቃ ከሱ ሌላ ሀሳብ የላችሁም?) ፀጉራቸው ነው። በትንሹ በቀን ከ96- 140 ጊዜ ይነካኩታል ይላል አንድ ጥናት። ምን ይሄ ብቻ አንዲት መደበኛ ሴት ፀጉሯን እንደነገሩ ለመንከባከብ (መታጠብ ፣ ማድረቅ መፈሸን ወዘተ) በሳምንት በትንሹ 9 ሰዓታትን ስትወስድ ለውበት ከፍ ያለ ቦታ የምትሰጥ ሴት ደግሞ እስከ 16 ሰዓት ታጠፋለች። በወር ካሰላነው 64 ሰዓት በዓመት 768 ሰዓት ማለት ነው። እንደኛ ባለው አገር የፀጉር ቤት ወረፋ ሲደመርበት የትየለሌ ነው። ይሄ የጊዜ ጉዳይ ነው ወደገንዘብ ከመጣን ለሻምፖ ኮንዲሽነር፣ የተለያየ ትሪትመንት፣ ለቀለም፣ ለቅባት፣ ለፍሸና አንዲት ሴት የምታወጣው ወጭ ጆሮ ጭው ያደርጋል። ይሄ ሁሉ ሆኖ አሳዛኙ ነገር የሴቶች ፀጉር ካለፉት አምስት አስርተ ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ጥንካሬው ብዛቱ እና ርዝመቱ በግማሽ ቀንሷል። ይህም ከመዋቢያ ኬሚካሎች፣ ከአየር ፀባይ ፣ ከአመጋገብ፣ ከውሃ ከአኗኗር ስታይልና እና ረፍት ከማጣት ጋር ይያያዛል። እና ምን ተሻለ ....ተማር ያለው ከዙሪያው ይማራል፤ የአውሮፓን ዴርማቶሎጅስቶች ዝብዘባ ተውትና ወዲህ ተመልከቱ!

ሰሞኑን "የኦነግ ሸኔ አባላት የነበሩ እጅ ሰጥተው ወደሰላም ተመለሱ" የተባሉ ሰወችን አይተናል፣ እነዚህ ሰወች በዱር በገደል ከረሙ የተባሉ ፣በጦርነት ያለፉ ወዘተ ናቸው እንደተነገረን። በሚገርም ሁኔታ ግን ከተማ ሴቶቻችን በፆም በፆሎት፣ በዘመነ ትሪትመንት ኢንች ማስረዘም የተሳናቸው ፀጉር እነዚህ ጫካ የከረሙ ተዋጊወች ላይ ተዘናፍሎና ትከሻቸው ላይ እየተርመሰመሰ የህንድን ዊግ አስንቆ መገኘቱ አስገራሚ አይደለም? ምን ቢያደርጉት ነው? ምንም! በቃ ስለተውት ነው! ቢበዛ ቅቤ ይቀቡት ይሆናል።

የእነዚህ ተዋጊወች እጅ መስጠት ለህብረተሰቡ ያስገኛል ከተባለው "ሰላም" ይልቅ ለሴት እህቶቻችን የፀጉር እንክብካቤ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው። እህቶቸ! ፀጉራችሁን የትም በሚመረት ኬሚካል ፍዳውን ከምታበሉት ጊዜና ገንዘባችሁን ከምታቃጥሉ መፍትሄው ቀላል ነው ተውት! መተውን የመሰለ ነገር የለም፤ ተፈጥሮ እድል ሲሰጣት ራሷን ማከም ትችላለች። (ደግሞ ፀጉር ለማሳደግ ብላችሁ ጫካ እንዳትገቡ...እናተና ውበትኮ...) እዳሪ መሬት ስለሚባል ነገር ሰምታችኋል? የተጎዳ እርሻን ለተወሰነ ጊዜ ሳያርሱ ሳይዘሩ ክፍቱን መተው ማለት ነው፤ ተፈጥሮ ታክመዋለች! በቀጣይ ሲዘራበት እንደጉድ ያመርታል። ያደከማችሁን ነገር እስኪ ተውት...ለሁሉም ነገር መተውን የመሰለ ነገር የለም። ለተፈጥሮ የማሪያም መንገድ ስጧት!

@wegoch
@wegoch
@paappii
😁92👍7831🔥1
አደፍርስ


አብዬ አደፍርስ የሚስታቸውን ግልምጫ ያመልጡበት፣የልጆቻቸውን ሆድ ይሞሉበት መላው ቸግሯቸዋል።የዛሬ አራት ወር ገደማ በጥበቃነት ይሰሩበት የነበረው ባንክ የዘረፋ ሙከራ ተደርጎበት የነበረ ጊዜ ዘራፊዎቹን በጉልበታቸው መመከት እንደማይችሉ ሲያውቁት በድረሱልኝ ጥሪ ቢዘርሯቸውም የባንኩ ማናጀር እሳቸውን አባሮ በቦታቸው ከሳቸው በእድሜ አነስ የሚል ጎልማሳ ከመቅጠር ወደኋላ አላለም።ይኸው ከተባረሩ አንስቶ ሁሌ ማለዳ ማለዳ ከስራ ሰዓት ቀደም ብለው ያደረ ሽንታቸውን ከቤት ይዘውት ይወጡና ባንክ ቤቱ አጥር ስር ሲደርሱ ነው ቀበቷቸውን የሚፈቱት።

ስጋ ለበስ ብትራቸውን አራግፈው ከሱሪያቸው ስር እየወሸቁ
"ኡኡ ባልኩ?እንደ ሴት ጮሄ ባስጣልኩ?" ይላሉ።አሁን አሁን ግን ረሀቡ ጠናባቸው።የሶስት ልጆቻቸው አንጀት እግርና እግራቸውን ተብትቦ ይዞ አላራምድ አላቸው።ሚስታቸው ከጉሊት ውለው ሲመጡ ከሬሳ የከረሰሰ ሽሮ ያቀርቡላቸውና
"አንቱ የሴት ገንዘብ ምን ምን ይላል?እስቲ ቀምሰው ይንገሩኝ" ይሏቸዋል።
ሁለመናው ከትዕግስታቸው ቋት እየፈሰሰ አልሆን ሲላቸው ሂሩትን አማከሯት...የመንደራቸውን አድባር።ሂሩት በመንደሩ ብቸኛዋ አጭር ቀሚስና ሂል ጫማ የምትለብስ የመንግስት ሰራተኛ ናት።እንዳማከሯትም አላሳፈረቻቸውም ማንበብና መፃፍ የሚችል ሰው ሁሉ ሊሰራው የሚችል ስራ አገኘችላቸው።አላምናት ብለው
"አየ ሂሩት...ይኸን ሽማግሌ ልቀልድበት ብለሽ ነው መቸም"
"አባቴን ይንሳኝ የምሬን ነው!"
"እንዴት ያለ ነው ስራው?"
"አልጋ ቤት ነው የሚሰራው አብዬ...አንድ ቀን በቀን ፈረቃ ሌላ ቀን በማታ ሆኖ አልጋ የሚይዘውን ሰው መታወቂያ ይዘው ስም እየመዘገቡ ብር ተቀብሎ ማሳደር ነው።የማታ ሲሆኑ ማደሪያዎትን ቆንጆ አልጋ ይዘጋጅልዎታል።"

"አልጋ ቤት?"አሉ ቅሬታ በተሞላ ድምፀት።
"አዎ...መንገደኛና የሰው አገር ሰዎች...ነጋዴዎች አልጋ ተከራይተው ሲያድሩ እነሱን መመዝገብ ነው አብዬ።"
"እንዴት ነው እነሱ ተኝተው እኔ ስጠብቃቸው ላድር ነው?ተይ ተይ ቤቱን ዘርፈውት የሄዱ እንደሁ በጉዴ እወጣብሻለሁ ሂሩቴ"
"ኧረ ቤቱ የራሱ ጥበቃ አለው!የርስዎ ስራ መዝግቦ መተኛት ነው"ስትላቸው እያቅማሙም ቢሆን ተስማሙ።

የመጀመሪያውን ቀን በቀን ፈረቃቸው አቀላጥፈው ሰሩ።ይጠፉብኛል ብለው የፈሯቸው ፊደላት ሁሉ እንደ ይስሐቅ ታዘዟቸው።ያሞጨሞጩ አይኖቻቸውም የዋዛ አልነበሩምና ከየሰዉ መታወቂያ ላይ ጥቁሩን ከቀዩ፣ጠይሙን ከቀይ ዳማው አበጥረው ለዩት።አመስግነው ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ከወትሮው በተለየ በትኩስ ሽሮ ተቀበሏቸው።አቦል ይሁን በረካ ባይለይም ቡና ተፈልቶላቸው አንድ ሲኒ ጠጡ።ለወትሮው ጀርባቸውን ይሰጧቸው የነበሩት እመይቴ አማረች ጡትና ጡታቸው መሃል አስተኝተው ራሳቸውን ሲዳብሷቸው አመሹ።
በሁለተኛው ቀን በማታ ፈረቃቸው ሰዓታቸውን አክብረው ተገኙ።አንድ ሶስት መንገደኞችን መዝግበው ቁልፍ ከሰጡ ወዲያ ሁለት ወጣቶች ተቃቅፈው መጡና አጠገባቸው ቆሙ።ሲታዩ እድሜአቸው እምብዛም አይራራቅም።ሴቲቱ ከማውራት ይልቅ ፈገግታና መሽኮርመም ይቀናታል።ወንዱ የጤና በማይመስል ሁኔታ ይቁነጠነጣል...ችኩል ችኩል ይላል።

"እ ፋዘር...አልጋ አለ ኣ?"
"አለ...ሁለት ነው አንድ የፈለጋችሁ?"
"ኧረ ቆጥበን እንጠቀማለን ሃሃሃ...ባለ አንዱ ስንት ነው?"
"ሁለት መቶ ብር"
"ሁለ'መቶ?" አለና ግንባሩን ክስክስ አድርጎ አጠገባቸው ያለውን አልጋ እያየ
"እንደዚህ ነው እንዴ አልጋው?"ጠየቀ።
"ኧረ ይች የኔ የብቻየ ስለሆነች ነው...ውስጥ ያለው ሰፋፊ ነው"አሉ እያፈሩ።ልጅቷ የልጁን ጎን በስስ ቦክስ ነካ አርጋ በዝግታ "አንተ አታፍርም?"ትላለች።
" ሀዬ በቃ መዝግቡና ፋዘርዬ" አለ መታወቂያውን ፍለጋ ኪሱን እያመሰ።ወዲያው ነገር በድንገት ብልጭ እንዳለለት ሰው እያደረገው
"ውውውውውይ በናትሽ!...ለካ አይ.ዲ.ዬን ያ ዘበኛ እንደያዘው ነው...ያንቺን አምጪው በቃ" ሲላት ቅር እያላት መታወቂያዋን አውጥታ ሰጠች።አብዬ አደፍርስ ፎቶዋን አበጥረው አዩና ወደ ስሟ ወረዱ።ለአፍታ ከመረመሩት በኋላ የሚያውቁት ፊደል ሲያጡ ቀና አሉና።
"ማነው ስምሽ"? አሉ።
"የኋላ'ሸት"
"እና ምነ በአማርኛ ቢፃፍ?" አሉና ስሟን ሊመዘግቡ ፊደላቱን ከአዕምሯቸው ጓዳ ያተራምሷቸው ጀመር።እየተንቀጠቀጡ ስሟን ፅፈው ሲጨርሱ
"የአባትሽስ?"
"ይበልጣል"
አሁንም እየተንቀጠቀጡ ሊመዘግቡ ሲያቀረቅሩ ልጁ ትዕግስቱ ተሟጦ
"ፋዘር እኔ ልመዝግበው የፈጠነ?"
"እ?"
"የፈጠነ...እኔ ፃፍ ፃፍ ላርገው?"
"ቆይ እስቲ...ይ...በ...ል...ጣ...ል...ይበልጣል"አሉና ቀጠል አርገው
"ስራ?"
"ተማሪ ነን"
"ተ...ማ...ሪ...ተማሪ"ይህንንም በዘገምታ አስፍረው ስልክ ቁጥር ከመዘገቡ በኋላ ክፍያ ተቀብለው ቁልፉን አስረከቧቸው።ለክፋቱ የዚያን ቀን የቀረው ብቸኛ ክፍል ከሳቸው ምኝታ ቤት ቀጥሎ ያለው ነበር።

አገር አማን ብለው ሊያሸልባቸው ሲል ከመሬት መንቀጥቀጥ ያልተናነሰ መናወጥ ከሰመመናቸው አባነናቸው።ተገስ እስኪል ጠበቁና ወደ ክፍሏ በር ጠጋ ብለው አንኳኩ።

"የኔ ልጅ"
"ምንድነው ፋዘር?"
"እንደው አደራህን የኔ ዓለም የአልጋው ብሎን እንዳይረግፍ...ደሃ ነኝ የምከፍለውም የለኝ...ወይ ፍራሹን ታወርዱት"?
"ሀዬ በቃ ይወርዳላ!"
ወደምኝታቸው ተመልሰው ፀሎታቸውን እያነበነቡ በድጋሚ ሊያሸልባቸው ሲል የድረሱልኝ ጥሪ የሰሙ መስሏቸው ብርግግ ብለው ተነሱ። ጆሯቸውን ቀስረው ሲያዳምጡ ጩኸቱ ከጎረቤት ነው።ጭንቅ ሲላቸው የስልካቸውን ራዲዮ ከፍተው ወደ ጆሯቸው ለገቡት።
"እንግዲህ አድማጮቻችን ከምሽቱ 12:00 የጀመረው የመዝናኛ ዝግጅቻችን እንደቀጠለ ነው።በያላችሁበት እጅግ ያማረ ጊዜን እያሳለፋችሁ እንደሆነ አንጠራጠርም።ታሪኳ ይነበብ ከሞጣ 'አትጠገቡም' ብላናለች።...ሆዴ ሞላ ከደጀን...እግዜሩ ባይከዳኝ ከጎንደር...ብርአልጣ ዘለዓለም ከማርቆስ 'ዝግጅታችሁ ተወዳጅ ነው' ብለውናል።ከኤፍሬም ታምሩ ሙዚቃ በኋላ ተመልሰን የምንገናኝ ይሆናል።አብራችሁን ቆዩ"

"...ወይ ዘንድሮ(2X)...ወይ ዘንድሮ(2X)
ወይ ዘንድሮ አያልቅም ተነግሮ"
ሙዚቃው ሲያልቅ የስልካቸውን ራዲዮ እየዘጉ
"ወይ የአንት ያለህ!!!እንዴት ያል ዘመን መጣብና?ወንዱ እንደ ሴት እየጮኸ? ኧረግ የእንድማጣው!ቱ!ቱ!ቱ! ሞት ይሻል የለም ወያ አንድ ፊቱን!"እያሉ ይብሰለሰሉ ጀመር።ለሊት ከሞቀ እንቅልፋቸው ሶስቴ ተቀስቅሰው፣አልጋው ረገበ አልረገበ በስጋት ተሰቅዘው አደሩና እንዳይነጋ የለ ነጋላቸው።ልጆቹ መታወቂያ ሊወስዱ ሲመጡ አብዬ አደፍርስ አልጋውን ሳላይ ገመድ ባንገቴ አሉ።አገላብጠው ካዩትና ከመረመሩት በኋላ
"እውነትም ላያስችል አይሰጥ!"ብለው አልጎመጎሙና ልጆቹን አሰናበቷቸው።በቀን ፈረቃ የሚሰራው ተተኪ ሰራተኛ እስኪመጣ ጠብቀው ስራ መልቀቃቸውን ነግሩትና ወደ ቤታቸው አዘገሙ።እመይቴ አማረች ወሬውን ቀድመው ከሂሩት ሰምተውት ኖሮ መሸት ሲል መጥተው የከረሰሰ ፊት ከከረሰሰ ሽሮ ጋር አቀረቡላቸው።
"አንቱ የሴት ገንዘብ ምን ምን ይላል?እስቲ ቀምሰው ይንገሩኝ "

ዘማርቆስ
@wogegnit

@wegoch
@wegoch
@wegoch
👍58😁198👏5
ከአዲስ አበባ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ የሚመበር የኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ ከባለቤቴ ጋር የተመደበልልን ቦታ ቀደም ብለን ይዘናል፡፡

ግዙፉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለቀጣይ አሰራ ሁለት ሰዓታት ለሚያደርገው ጉዞ ዝግጅቱን አጧጡፎታል፡፡

እኔና ባለቤቴ መቀመጫችንን የሚጋራውን ሶስተኛውን ሰው ስንጠብቅ አንዲት በአምሳዎቹ መጨረሻ ላይ የሚገኙ ሰው ከተፍ አሉ፡፡ በእጃቸው ከዘራ በሌላኛው እጃቸው የሚጎተት ሻንጣ ይዘዋል፡፡

ሻንጣቸውን ከላይ የሚገኘው ማስቀመጫ ላይ እንዳኖርላቸው ለጠየቁኝ እርዳታ ፈጠን ብዬ ተቀብዬ ሰቀልኩኝ፡፡

ምስጋናዬን ተቀብዬ ከመቀመጤ መዳረሻችን ስንደርስ ካወረድክላቸው በኃላ ላግዞት፣ ልግፍ አንዳትል አለች፡፡

ደግሞ ምን ችግር አለው፡፡ የሀገሬ ሰው ባግዝ፡፡ አንድ ሁለት ተባባልን፡፡

ቀጥላ ይህንን የአንዲት ተሳፋሪ ታሪክ አጫወተችኝ፡፡

አንድ መዳረሻውን ዱባይ ያደረገ አውሮፕላን ውስጥ ከእኔ ቀጥሎ አንዲት ተለቅ ያለች ሴት ትመጠጣና የያዘቸውን የእጅ ቦርሳ ከላይ ባለው የእቃ ማስቀመጫ ላይ እንዳኖርላት ትጠይቀኛለች፡፡ ነገር ግን ከእኔ ትይዩ ተቀምጦ የነበረው ሰው ቀልጠፍ ብሎ ተቀብሎ የተጠየኩትን ድጋፍ አደረገ፡፡

ሴትዩዋ ከጎኔ መቀመጫዋን ካመቻቸችና መታጠቂያ ቀበቶዋን ካሰረች በኃላ አክብሮት የተሞላ ወሬ ጀመረችኝ፡፡ በረራችን አንደተጀመረ ብዙም ሳንጓዝ ሆዷን ቁርጠት እንዳጣደፋት ነገረችኝ፡፡ የበረራ አስተናጋጅ ጠርቼ አባካችሁን እርዷት አልኩኝ፡፡ እነሱም መጥተው ድጋፍ አደረጉ፡፡ ከዚያች ቅፅበት ጀምሮ ሴትዩዋ ልጄ እያለች እኔን መጥራት ጀመረች፡፡ ያው ላደረጉት ነገር ይሆናል ብዬ ተቀበልኩ፡፡ ሁሉም ሰው አብረን እንደሆንን ማሰብ ጀመረ፡፡

ልክ ዱባይ ስንደርስ መጀመሪያ ሻንጣውን በማስቀመጥ የረዳት ሰው ሻንጣውን ካወረደላት በኃላ ወደእኔ ጠጋ ብሎ በፍጥነት ከሴትዮዋ እንድርቅና ለበረራ አስተናጋጆቹ አብረን እንዳልሆንን እንዳሳውቃቸው ነገረኝ፡፡

ማስጠንቀቂያው ዋጋ አልነበረውም፡፡

የበረራ አስተናጋጆቹ ከሴትዮዋ ጋር ያለንን ግንኙነት ጠየቁኝ፡፡ እዚሁ አውሮፕላን ላይ መገናኘታችንን ተናገርኩ፡፡ ሴትዮዋ የእጅ ቦርሳዋን እንዳግዛት ለመነችኝ፡፡ ትንሽ ተወዛገብኩ፡፡ ያ ሰው በምልክት እንዳላግዛት አልፎም የበረራ አስተናጋጆቹ አገዛ መጠየቅ እንደሚቻል በቃል ተናገረኝ፡፡

ስሜቱ ቀላል አልነበረም ድንገት የታመመ ሰው አግዙኝ ሲል ጥሎ መሄድ ግን የሰውየውን ምክር ተቀብዬ ዊልቼር እንድትጠብቅ አድርጌ ትቻት መራመዴን ቀጠልኩ፡፡ በደቂቃዎች ውስጥ ከባድ ረብሻ ተፈጠረ፡፡ ከመጣላት ዊልቸሩ ላይ ቦርሳዋን ይዛ ለመራመድ ስትሞክር የኤርፖርት ፖሊስ በቁጥጥር ስር አዋላት፡፡

ከመቅፅበት ልጄ ልጄ እያለች ወደእኔ መጣራት ጀመረች፡፡ ጥያት እየሄድኩ እንደሆነ ወነጀለችኝ፡፡

ለካንስ ሴትዮዋ ከህገወጥ አደንዛዥ እፅ ዝውውር በተያያዘ ተይዛ ነው፡፡

እኔም ተያዝኩ፡፡ የሆነውን አስረዳው፡፡ ፖሊስ ሙሉ ስሜን እንድትናገር ጠየቃት፡፡ መጥራት አልቻለችም፡፡ ቦርሳዬ ተበረበረ፡፡ አሻራዬ ተመሳከረ፡፡ ምንም አይነት ትስስሮች ማግኘት ስላልተቻለ በመጨረሻ ነፃ ወጣው፡፡

ይህ ገጠመኝ በህይወቴ ትልቁን ትምህርት አስተማረኝ፡፡ በጉዞ ላይ ምንም አንኳ ሰውን መርዳት ጥሩ ቢሆንም ቅሉ የራስ ሻንጣ የራስ ነው፡፡ የሰው ሻንጣ ደግሞ የሰው፡፡

ታሪኩን ሰምቼ ስጨርስ ከጎኔ የተቀመጡትን ሴትዬዋን ተመለከትኩ፡፡

ከአስራ ሁለት ሰዓት በረራ በኃላ ስንደርስ አንደመጀመሪያው ሳይሆን በግማሽ ልቤ የሰቀልኩትን ቦርሳ አውርጄ ሰጠውኝ፡፡

አመሰገኑኝ፡፡

የገረመኝ መዳረሻችን የሆነው Washington Dulles International Airport የተቀበለን ባለማቋረጥ የሚነገረው የሰው ሻንጣ እንዳትይዙ፣ እንዳትረዱ . . . የሚለው ማስጠንቀቂያ ነበር፡፡

መልካም ሁኑ ግን ህይወታችሁ መልካምነታችሁን ብቻ ዋጋ ሊያስከፍለው ይችላልና መጠንቀቁ አይከፋም፡፡

ደግ አይለፍችሁ❤️

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Tesfaye Haile
👍7843🤔2👏1
የሆነ ሰዓት እሽኮለሌሌሌ ያሉ ጥንድ ጓደኞች ነበሩኝ። ነገራቸው ሁሉ እንዳይሆን እንዳይሆን ነበረ(እንኳንም ትለያያላችሁ የምንለው አይነት😅)

ከዛ በቃቸው መሠለኝ በአሪፍ ፀብ ተጣሉ ፥ በመኻል የእሱ እናት ሞተች።

ኧረ ይደብራል መኼድ አለብሽ ምናምን ብዬ ሰባብኬ በሰልስቱ ይዣት ሄድኩ ።

ወግ ነው መቼም ብላ ጠጋ ብላ "እንዴት ነህ በረታህ ?" ስትለው ምን አላት :-

"ሀዘኔን ልትቀሰቅሺብኝ ነው ከተፅናናሁ በኋላ የመጣሽው ?" 😂

By beza wit

@wegoch
@wegoch
@paappii
😁54👍12🤔52👎2
ይህም ባህሌ ነው

ከሃያ ስድስት አመት በፊት፣ ገና ወደ ሆላንድ እንደመጣሁ ጓደኞቼ 'አምስተርዳም ውስጥ የምናሳይሽ ድንቅ ነገር አለ' ብለው ይዘውኝ ሄዱ። ከሮተርዳም በባቡር የ45 ደቂቃ መንገድ ተጉዘን እስክንደርስ ድረስ እነዚህ በሰው በሰው ያወቅኳቸው ሃበሻ ጓደኞቼ “የነጮቹን ጉድ ታያለሽ---” እያሉ እስክንደርስ ድረስ ልቤን በጉጉት ሰቀሉት። አይደረስ አይቀር Red light destrict የሚባል ቦታ ደረስን። ሴተኛ አዳሪዎች በተገለጠ መስታዎት ውስጥ ጡት ማስያዢያ እና የውስጥ ሱሪ ብቻ ለብሰው ሰው በሚያማልል አኳኋን ተቀምጠው ሚውዝየም እንደሚታይ እንሰሳ ወይም ዕቃ በጎብኚዎች ይታያሉ። አየሁ፣ ዞር ዞር ብዬ የሚያይዋቸውንም ቃኘሁ፣ የነጭ ገላ እንዲህ ተገላልጦ ሳይ የመጀመሪያዬ በመሆኑ በመጠኑ ተገረምኩ። ነገር ግን ጓደኞቼ እንደጠበቁት በጣም አልተደመምኩም። አለመደንገጤ ወይም በስመአብ ብዬ አማትቤ አገሬ መልሱኝ አለማለቴ አወዛገባቸው። ከጎኔ እየተራመደች ስትመራኝ የነበረችው ጠይሟ ፍንጭት ልጅ “ከባህላችን ጋር ስለማይሄድ ብዙ ሃበሾች ይደነግጣሉ” አለችና መልስ ፍለጋ ትቃኝኝ ጀመር። ነገሩን አይቼ አለማጋነኔ ያበሳጫት ትመስል ነበር። አልፈረድኩባትም። ግን ምን ልበላት?

አኔ፣ ትግስት፣ የቤት ስሜ ሚሚ፣ የአቶ ሳሙኤል ማቴዎስ በቀለ ልጅ፣ መርካቶ ከፍተኛ 5 ቀበሌ 17 የቤት ቁጥር 475 ነበር መኖሪያዬ ልበላት? ከሰፈሬ አንድ አስፋልት ከፍ ብሎ የነበረው የሴተኛ አዳሪዎች ሰፈር ቀበሌ 12 ይባል ነበር ልበላት? ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ያጠናቀቅኩት አዲስ ከተማ ትምህርት ቤት ነው ልበላት? ከቤቴ ወደ ትምህርት ቤቴ ለመድረስ በ12 ቀበሌ ሰፈር ውስጥ ውስጡን ስጓዝ ያልተሳለምኩት ሴተኛ አዳሪ አልነበረም ልበላት? አንዷ በጉርድ ቀሚስ፣ አንዷ በቀይ ጫማ፣ አንዷ በውሰጥ ልብስ፣ አንዷ ስትታጠብ፣ አንዷ ስትቀባ፣ አንዷ ስታማልል ጠባብ ሱሪ አጥልቃ፣ አንዷ በጠዋቱ፣ አንዷ በከሰአት፣ አንዷ አመሻሽ ላይ፣ በነጻነት ቆመው ሁሉን አይቻለሁ ልበላት? የትዬ እንትና ባል፣ ያ ጠጅ አዘውታሪው፣ 3 ቀን ሙሉ ተፈልጎ ጠፋ። ሚስቲቱ ሰክሮ ቦይ ውስጥ ወድቆ ሞቷል ብላ ተንሰቅስቃ አለቀሰች። የሰፈሩ ሰው ተገልብጦ ወጥቶ ባልየው ሲፈለግ፣ የ12 ቀበሌዋ ሴተኛ አዳሪ ስላጽ “አኔ ጋር ነው ግን አልከፈለኝም” ብላ ያሳበቀች ዕለት፣ ሰውዬው ተጎትቶ ከቤቷ ሲወጣ፣ እኔም እዛ ነበርኩ ልበላት?

አባቴ የአትዮጵያ አየር መንገድ ይሰራ ስለነበር የተለያዩ አገሮች ለስራ ሲጓዝ የሚሸጡ አልባሳትና ጫማዎች ያመጣ ነበር። አንድ ጊዜ ከታይላንድ ሲመለስ ብዙ የሚሸጡ ቦርሳዎች አምጥቶ ለእናቴ እና ለእህቶቹ ሸጠው አንዲያተርፉ አከፋፈላቸው። በጣም የምወዳት አክስቴ አራት ቦርሳ አስይዛኝ ወደ ሴተኛ አዳሪዎቹ ሰፈር ላከችኝ። ትጠብቅሻለች የተባልኩት ስሟን በቅጡ የማላስታውሰው ቀይ ዳማዋ ሴተኛ አዳሪ ቤት ስደርስ ከደንበኛዋ ጋር ነበረች። በጣም ያረጀ፣ አውራ ጣቱ ጫፍ ተበላልቶ የተቀደደ፣ ቡናማ የወንድ ቆዳ ጫማ አልጋው ስር ይታያል። ከንፈሩ ሳይሳም ከሚያድር ቢታረዝ የሚመርጥ ሰውዬ አልጋዋ ላይ እደነበረ ከጫማው ገምቼ ነበር። በመጋረጃ ከተከለለው አልጋዋ ተስፈንጥራ ወጥታ ይዤ የነበረውን አራቱንም ቦርሳዎች አንድ በአንድ ቃኝቻቸው። ከመጋረጃው ጀርባ ሰውዬው በስሱ ያስላል። የቱን እንደምትመርጥ ዓይንአዋጅ ሆነባት መሰለኝ በርጩማ ላይ አስቀምጣኝ ትንሽ እንድጠብቃት አዝዛኝ ወደ ደንበኛዋ ተመለሰች።

ታዲያ የአምስተርዳም አስጎብኚዬን ምን ልበላት? እኔ ትግስት፣ የአቶ ሳሙኤል ማቴዎስ በቀለ ልጅ፣ አንዲት የቀይ ዳማ ሴተኛ አዳሪ በመጋረጃ ተከልላ ከደንበኛዋ ጋር አንሶላ ስትጋፈፍ አኔም እዛው ክፍል ነበርሁ ልበላት? አራት ከታይላንድ የመጡ ቦርሳዎች አቅፌ፣ እሱ ዚፑን ሲከፍት፣ የአልጋ ላይ ግብግብ፣ አሷ ስታቃስት፣ እሱ ሲያለከልክ፣ እንዳልተቃኝ ማሲንቆ የሽቦ አልጋዋ ሲያለቅስ ሰምቻለሁ ልበላት? በኋላም ሰውዬው ከመጋረጃ ጀርባ ሲለባብስ፣ ከፍሎ ሲወጣ ትዝ የሚለኝ ጀርባው ነበር። ደርዙ የተተረተረ ሱሪው .... ልበላት? አጠገቤ መጥታ እንደገና ቦርሳ ስትመርጥ፣ የሩካቤ ምርቃናዋ ሳይበርድ፣ ላብ ያዘፈቀውን ሰውነቷን አይቻለሁ ልበላት? ይህም ባህሌ ነው ልበላት?

By ትግስት ሳሙኤል

@wegoch
@wegoch
@paappii
👍42😢268😁2🔥1😱1
አባቴ ካጠገቡ የማትጠፋ ራዲዮ ነበረችው። ኹለት ስፒከር አላት ካሴትም ታጫውታለች...

ፀሐይ በራኺን አስሬ ይሰማታል። አክስቴ ትመስለኝ ነበር፤ ድምጿ እኛ ቤት አይጠፋም ስትዘፍን እኩል እላለሁ ከሙዚቃው ጋር...

"መጀመርታ ፍቅሪ
ኣብ መን ተጀመረ
ኣዳምን ሔዋንን
አለም ምስተፈጥረ
ኣነ ከይፈለጥኩ
አብ ልበይ ሐደረ
እንታይ እሞ ክገብር
ዕድለይ ካብ ኮነ አይ..አይይ*

አባቴ ወታደር ነበር። ጠይም ነው መከፋቱ ፊቱ ላይ ብዙ አይታይም፤ ማጣቱ በየምክንያቱ አንደበቱ ላይ አይንፀባረቅም ....ዝምም ይላል

ረጋ ያለ ነው ።

ጥርሱን ሳያሳይ ነው ደስ ብሎኛል ፈገግታ ፈገግ የሚለው፤ ተገርሜያለሁ ፈገግታ ፈገግ የሚለው ተበድያለሁ ፈገግታ ፈገግ የሚለው አጠገቤ ሲሆን እረጋጋለሁ።

ሰሞኑን ሰውነቴ እንደከሳ፤ ፊቴ ማዘን እንደታከከው፤ ድብርት ነገር እንዳንጃበበብኝ አወቀ። አባትም አይደል? ንብረቱም አይደለሁ? ዋጋ ከፍሎብኝም የለ?

ፊቴን አይቶ "ደህና ነህ ህሉፌ ...?" አለኝ።

'እ ...ትንሽ ደከመኝ...
አሻግሬ ማየት እያቃተኝ... ቶሎ ቶሎ እጅ እየሰጠው ..." አልኩት።

ረጅም ሰዓት ዝም አለ ...

"ታስታውሳለህ በረሃ እያለሁ የምፅፍላችሁ ደብዳቤ፤ በርቱልኝ፥ ምን ጎደላችሁ፥ እወዳችኋላሁ፥ በቅርብ እደውልላችዋለሁ፥ እመጣለሁ፥ ዓይነት ይዘት ያለው ፅሁፍ ?! ።"

"ባሩድ እየሸተተኝ ነበር፥ አብሬው የዋልኩት ጓደኛዬ ሞቶብኝ፥ ፍንጣሪ ጥንት መ'ቶኝ፣ ጠላት ሊፈጀን እያቀደብን፣ ጀኔራላችን ምሽግ ሰብራችሁ ግቡ ሊለን እንደሚችል እያወቅን፥ የተቀበረ ቦንብ ልንረግጥ እንደምችል እያወኩ፥ ከአውሮፕላን የተወረወረ ፈንጅ ሊያወድመን እንሚችል እያወኩ፥ ነበር...አሻግሬ ተስፋ የማየው..."

ፋታ ወስዶ ቀጠለ...

"ልጆቼን እንደማገኛቸው፥ አባት እንደምሆንላቸው፥ ሚስቴን ዳግም እንደማገኛት ፤ቤተክርስትያን እንደምሳለም የፈንጂ ድምፅ ሳልሰማ እለት እለት የወደቀ ሬሳ ሳልሻገር እንደምኖር ተስፋ አደርግ ነበር ...

ስለመግደል የሚታቀድበት ስፍራ ላለመሞት የሚዘየድበት ቦታ አንድ ቀን እንደማልኖር አምን ነበር ...!

ተስፋን ሙጥኝ ብዬ ነው ዛሬን ያየሁት ። ያጋጠመኝን መውደቅ እና ሃዘን ህመም ችላ ብዬ ነው ያን በርሀ የተሻገርኩት !!

አጆኻ ዝወደይ ..
ሁሉም ሰው መስቀል አለው ልዩነቱ አይነቱ እና አሸካከሙ ነው !!"

By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
103👍54😁2🔥1
አንድ አስናቀች
(ገብርኤላ ይመር)

እንደ ኑሮአችን እነርሱም ተደጋግፈው ከተሰሩት   ከምኖርባት መንደራችን በአዲስ ዓመት ጠዋት  ላይ አበባይሆሽ የሚጨፍሩ ልጆች ድምጽ  ከተንጋለልኩበት ፍራሼ ላይ ሆኜ በስሱ የከፈትኳትን ሙዚቃ ሰብሮ ገርብብ ያለ በሬን አልፎ በጆሮዬ ዘለቀ

"የመስቀል ለታ
የደመራው
ንፍሮ ቀቅዬ ብላ ብለው ጉልቻ አንስቶ ጎኔን አለው ከጎኔም ጎኔ ኩላሊቴን እናቴን ጥሯት መድሓኒቴን እሷን ካጣችሁ መቀነቷን አሸተዋለሁ እሷን እሷን..." ይላሉ።

ኩላሊቴን ሳይሆን ልቤን ካለው ነገር እንደ ወጌሻ የእናት ፍቅሯ አሽቶ እንዳይጠገኝ እናትዬ ካረፈች ልክ 3 ዓመቷ ነው። እርሷን እርሷን የማሸተው መቀነት ባትተውልኝ ዘመኗን አብሪያት ስኖር የምትከፍታት አስናቀች ወርቁ ስቀመጥ፣ ስነሳ፣ስተኛ ስጓዝ እሰማታለሁ፣ በትዝታ ክራሯ አንጀቴን እየከረከረች፣ ከምናፍቃት እናቴ እቅፍ ትጥለኛለች።

ከአመሻሽ ገበያተኛ መኖሪያችንን ልትቃርም ወደ ጉሊቷ ልትመለስ ስትል  "እንቅልፍ ጥሎሽ ማደሪያ እንዳታሳጪኝ  ሳትሸነቁሪ ገርበብ አርገሽ በሩን  ተይው እሺ " ትለኝና ፣ መለስ ብላ ደግሞ "እንዳይደብርሽ  ቴፑን ክፈቺ" ብላኝ እስክትመጣ የተገረበበ በሬ ላይ ዓይኔን ጥዬ ከአስናቀች ወርቁ ጋር የምጠብቃት፣ ተመልሳ  ለራታችንን የሚሆን ስታዘገጃጅ ከጎኗ ተቀምጬ የእርሷን ወግና አስናቀችን እኩል እየቀዳሁ ዝም ብዬ የማያት፣  ስነሳ እንደ ጠዋት ዜና ከቁርሳችን እኩል ት/ቤት እስክሄድ የምሰማት፣ እናቴ ስትደሰት፣ ስታዝን፣ ስትሰራ፣ ስትቆዝም ሁሉ ከዚህች ሴት ወዲያ የማታውቅ የምትመስለኝ እንደውም ዘመድ ረግጦት የማያውቅ ቤታችን ውስጥ አስናቀችና ክራሯ የልብ ዘመዶቻችን ነበሩ።

አሁንም በትመጣ እንደው ገርበብ ያረኩት በሬ ኩላሊቴን ሳይሆን፣ ልቤን ወዳለው ሰው በረርኩ።
ሳገኘው ሁለተኛ ዓመት የግቢ ተማሪ ነበርኩ።

እንደለመድኩት  ኤርፎኔን በጆሮዎቼ ከትቼ አስናቀችን እየሰማሁ፣ ቦርሳዬን ይዤ ልወጣ ስል በአንዱ አልጋ ከላይ ጸጉሯን እየሰራች ያነበረችው ማሂ " እንደለመድሽው ገርብብ አድርገሽ ሄደሽ ከዚህ እንዳታስወርጂኝ ፣ በሩን ገጥመሽ ዝጊው አለችኝ ፈገግ ብላ  በፍጹም ሰው ካላስታወሰኝ በቀር በር እስከመጨረሻው ዘግቼ አልወጣም፣  እንደ እናትዬ ገርበብ እንዳለ ነው የምተወው እንደኔ በተስፋ የሚጠብቀኝ ካለ ብዬ ይሆናል።

በሩን እንዳለቺኝ ገጥሜ ከላየረብሪው  ስደርስ ከውስጥ በፍጥነት እየተመናቀረ የሚወጣ ልጅ ገፈታትሮኝ በእጄ ያለውን ስልክ አስጣለኝ
"ቀስ አትልም? ያምሀል" ልለው ስዞር  ቀድሞኝ "ያምሻል" ብሎ እየጠራ ያለው ስልኩን አንስቶ ወደ ላይ ሄደ

በሆዴ "ሆ ያምሻል? " አልኩና የወደቀ ስልኬ  ደህና መሆኑን አገላብጬ አይቼ ወደ ለመድኩት ቦታዬ ስሄድ ተይዞ ተበቀኝና ከአጠገቡ ካለው 4 ሰው የሚያስቀምጥ ወንበር  ሄጄ ከፊትለፊቴ የተከፈተ ላፕቶፕ ቦርሳውን ዞር አድርጌ ተቀመጥኩ። ትንሽ ቆይቶ ወዳለሁበት ወንበር በፍጥነት እርምጃ የደረሰ፣ የሚያለከልክ ልጅ ተቀመጠ። ያ የገፈተረኝ። ራሱ ገፍትሮ ደርሶ ያምሻል ማለቱ አናዶኝ ነበርና ፊቴን አጠቆርኩ እርሱ ግን ሀሳቡ ሁሉ በስልኩ ላይ ነበርና የሆነ ነገር ሊሰማ ወደ ጆሮው ሲያስጠጋ አልሰማ ስላለው   ያጠቆርኩበት ፊቴን ሳያይ  ላፕቶፑ ላይ የተሰካውን ኤርፎን ሲነቅለው ሲሰማ የነበረው ሙዚቃ ላይብሪውን አመሰው።

በራኬብ ቤት እንደተንጠለጠለ ቀይ ግምጃ  የጠላው ውቃቢዬን አባሮ መውደድ ሰፈረበት፣ "ያመሃል እንዴ" ብላ በጩኸት እንደ ኢያሪኮ ልታፈርሰው የነበረች ምላሴን መሰብሰቤ በጀኝ።  እንደ ራኬብ ከመፍረስ የሚታደገው ቀይ ግምጃ ከላፕቶፑ ወጣች ።አስናቀች ወርቁ
ፈገግ አልኩ

ሰው ሁሉ ወደርሱ በማየቱ አይኖቹን የሚያሸሽበት ነገር ሲፈልግ ፈገግ ብለው የሚያዩት ዓይኖቼ ላይ አረፈ።
  ግራ በተጋባ ፊቱ ገረመመኝና፣ የተከፈተውን ለመዝጋት አቀረቀረ።

"ደህና ነህ "አልኩት ቀስ ብዬ
ከሰው ጋር ገጥሞ አለማውራቴ ጉድ ባስባለበት ግቢ የማላውቀውን ልጅ ደርሼ ደህና ነህ ማለቴ ጉድ ነበረ።

ከዚያ ቀን በኋላ ከዚያች ወንበር ከፊትለፊቱ መቀመጥ ልማዴ ሆነ። በመተያየት፣ ሰላምታ፣ ከሰላምታ ወደ መጠያየቅ ወደ መተዋወቅ ተሻገርን። በላይብሪ የታጠረ ድንበራችንን ሰብረን የቀንተቀን ጓደኛ ሆንን
"የት ነሽ?" ለሚለው ጥያቄ
"ሱራፌል ጋር "የሁልጊዜ መልሴም ሆነ።

ብዙውን ጊዜ  የዛ ቀን እርሱንም ልቡንም ስላመናቀረችው ቤዛ የምትባል ሴት  ይነግረኛል፣ ልክ የእናትዬን ወግና አስናቀችን ዝም ብዬ እንደምሰማ ሁሉ እንዴት፣ ወዴት፣ መቼና ምን ሳልል ዝም ብዬ እሰማዋለሁ።  አውርቶኝ፣ አውርቶኝ  ሲበቃው "አውርተሽኝ አታውቂም አውሪኝ እንጂ" ይለኛል። ዝም እለዋለሁ። እጆቼን ይይዝና "ነገ ስንገናኝ አንቺ ነሽ የምታወሪው" ይለኝና የያዛቸው እጆቼን ከዛ ግንባሬን ይስመኛል ። ዝም ብዬ አየዋለሁ። "ከመሄዳችን በፊት ግን  አንድ አስናቀችን" ብሎ አንዱን የኤርፎን ጆሮ ይሰጠኛል። ትከሻው ላይ ራሴን ጥዬ፣እርሱ በጸጉሮቼ እየተጫወተና ለምን ለእርሱ የምትዘፍን እንደሚመስለው እየነገረኝ ዳግም እንደ እናትዬ የእርሱን ወግ ከአስናቀች ጋር አደምጣለሁ።
እኔ ዝም ብሎ በማዳመጥ ብኖርም ግን ህይወት ዝም አትልምና የት፣ ምን፣ እንዴት ያላልኳት ቤዛ ዳግም ተመለሰች። እንዲሁ አንድ ቀን ከመሄዳችን በፊት አስናቀችን እየሰማን ስልኩ ጠራ አየሁት "ቤዝዬዬዬዬዬ"  ይላል ብዙ ዬ ነበረው። ከስልኩ የነበረቀውን ኤርፎን ነቅሎ ሊያወራት ከኔ ራቅ አለ። ከዚያች ቀን በኋላም ከእኔ ራቅ ራቅ እያለ ሄደ ። እኔም  በኋላ ማናት ብዬ መልኳን እንኳን ለማየት ያልጠየኳት ቤዛን አወኳት፣ አብረው። ወትሮ ነገርን መዝጋት የማያውቀው ጎኔ ባስለመደኝ ሰዓት እስኪደውል እጠብቃለሁ፣ በየሄድንባቸው ቦታዎች ልክ እንደናትዬ እስኪመጣ አያለሁ ግን አልነበረም። እርሱ ገርበብ አድርጎ የጠበቃት ፍቅሩ ስትመለስ፣ የኔን በር ገርበብ አድርጎት ሄደ።

ሶስተኛ ዓመት ከዛም ወደ መመረቂያ ዓመቴ ስገባ ገርበብ ያረኩትን ልቤን ለራሴ ስል ዘጋሁት። ግን እሰማለሁ "ቤዛ እኮ ጥላው ሄደች በናትሽ የታባቱ" የዶርሜ ልጆች እኔን ሊያስደስቱ እየተሳሳቁ  ያወጉኛል። ዝም።" ደግሞ ሌላ ሴት ይዟል ማን ነው ስሟ" ይጠያየቃሉ። ዝም።
የቤዛን እጆቿን አይዛትም ነበር ፣ በጸጉሮቿ አይጫወትም፣  በመሀላቸው ገርበብ ያለ ክፍተት አለ፣ ሌላም ካሏት፣ ከሌላዋም፣ ከቀጣየም አብሯቸው ሆኖ አየዋለሁ ፣  በሴቶቹና እሱ መሀል እንደ በሬ የተገረበበ ክፍተት አለ። ዝም።  ባለበት ቦታ ካለሁ  ዓይኖቹ ግን የሆነ ነገር ሊሉኝ በመፈለግ  እኔ ላይ ናቸው።
የመመረቂያ ቀናችን ደርሶ፣ ተመርቀን እንደ ነገ ልንሄድ እንደ ዛሬ ከግቢው ቡና ቤት ተሰይመናል። በአንድ ጓደኛችን ስልክ እዛው ካለው ሞንታርቦ ስልኩን አገናኝተን ሙዚቃ እየከፈትን የስንብት እንጨዋወታለን። የነርሱ ዲፓርትመንት ለመመረቅ ሁለት ዓመት ቢቀረውም  እግር ጥሎት ከጓደኞቹ ጋር እኛ ከተቀጥንበት ፊትለፊት መጥቶ ተቀመጠ። ዓይኖቹ ሰውነቴ ላይ እንደሆኑ አውቄዋለሁ ግን ወደ ማብቃቱ አካባቢ ከመሄዳችን በፊት" አንቺ የምትፈልጊው ሙዚቃ የለም?" አለኝ ስልኩን ከሞንታርቦ ጋር ያገናኘው ጓደኛችን። ያለችኝን አንድ አስናቀችን  ላኩለትና ከፈታት። ቀና ብዬ ፊትለፊት አየሁ፣ አየኝ  እስከ መጨረሻው ከመሄዴ በፊት አንድ አስናቀች። በዝምታ

By Gabriela

@wegoch
@wegoch
@paappii
👍4831😢8😁5
አልጣሽ

ገፃቸው በመታከት ዳምኗል።አይኖቻቸውን ቡዝዝዝዝ አድርገው ፊትለፊታቸው የሚነታረኩትን የልጅ ልጆቻቸውን በአርምሞ ሲያዩ ከቆዩ በኋላ "አይ አለመታደሌ!" ብለው በረጅሙ ተነፈሱና እያዘገሙ ወደ ኩሽናው ዘለቁ። ተንበርክከው የምጅጃውን እሳት በእፍታ የሚታገሉትን ባለቤታቸውን በጨረፍታ ቃኝተው አለፉና መደቡ ላይ በቁማቸው ወደቁበት።

አያ ቢምር እና እመይቴ አልጣሽ በስተርጅና የልጅ ልጆቻቸው ሞግዚት ሆነው የአፍታ እረፍት የሰማይ ያህል እንደራቃቸው ውለው ሌላ የድካም ቀን እስኪመጣ ያሸልባሉ።የመጀመሪያ ልጃቸው  ሁለቱን የእራት አመት መንታ  ልጆቿን፣ሁለተኛው ልጃቸው ደግሞ እህል በአፏ ከሌለ አርፋ የማትቀመጠዋን የሁለት አመት ልጁን ጥለውባቸው ወደ አጨዳ ያቀናሉ።
"እመይ...አበይ...ደኅና አድራችኋል?ንሱ ልጆይን ፍቀዷቸው...ህደናል" ይሏቸዋል።

ዛሬም እንደወትሯቸው ሶስቱ ህፃናት የወላጆቻቸው ዳና ከመጥፋቱ እየተፈራረቁ ጎጆይቱን በአንድ እግሯ ያቆሟት ጀመር።መንትዮቹ ፍቅሩ እና ሰውነት ከውልደታቸው አንስቶ ተስማምተው አያውቁም።እንደውም የቆዬው የልምድ አዋላጅ "አይ ሰውነት!ያኔም የእናታቸው ምጥ ሲመጣ...ወይ እሱ አይወጣ...ወይ ወንድሙን አያስወጣ...አናቱን በእግርና በእግሩ መሃል ደፍጥጦ  ይዞ ብርሌ አስመስሎት ቀረ...ይኸው አድጎም አልተወው"ይላሉ መንትዮቹ ሲጣሉ ባዩ ቁጥር።ረፋዱ ላይ እመይቴ አልጣሽ  ያቀጠኑትን ሊጥ ተሸክመው ወደ ምጣዳቸው አቀኑ።ሊጡን በኩባያ እየጠለቁ እንደ ረሀብተኛ ልዥ ሆድ መሃሏ የጎደጎደው ምጣዳቸው ላይ ያፈሱትና በክብ ቅርፅ በተሰራችው የጣውላ ማለስለሻቸው ዙሪያዋን ያለብሷታል።እንደ ሽማግሌ ጥርስ ዙሪያው የተፈረካከሰ ሙግዳቸውን አንስተው ምጣዳቸውን ከመክደናቸው ሰውነት ሲከንፍ መጥቶ ሊጡ ላይ አንድ ጆግ ውሃ ይሞጅርበትና እያሽካካ ይሮጣል።የ 80 አመት ጉልበታቸው አሯሩጦ መያዝን ባይፈቅድላቸው
"ሃይ!...ሃይ!...ሃይ!...ምነ ምነ አንዳች ያልታሰበ ቢያጥለቀልቅህ!"ረግመውት  ወደ ሊጡ ይዞሩና
"አይ አለመታደሌ!"ብለው ከጎን ያለው ምድጃ ላይ አብሲት ሊጥዱ ገለባ መማስ ይጀምራሉ።ከእሳት ጋር ሲታገሉ አልፈዋቸው ከመደቡ የወደቁትን ባለቤታቸውን እየቃኙ
"ይኸ ተንከሲስ... ሊጡን አቅጥኖ አፈር አልብሶኝ አያ ቢምር!...አብሲት እስክጥል ማታ ከድኘ ያኖርኳት ሞሳ ባጨላ አለች በሳህኔይቱ...ይህዱ ጓዳ እሷን እየቀመሱ ይቆዩኝማ" ብለው አባብለው አሰወጧቸው።አያ ቢምር በጋሬጣና በእንቅፋት ጥፍሮቻቸው የወለቁ እግሮቻቸውን እየጎተቱ ወደ ጓዳ አቀኑ።መሃል ወለል ላይ ትንሿ የልጅ ልጃቸው በሁለቱም ጉንጮቿ ሞልታ የምታኝከው ባቄላ መፈናፈኛ አሳጥቷት በጭንቅ ስትቃትት አገኟት።ከ60 አመት በላይ ሞፈር የታዘዘለት እጃቸውን ወደ ማጅራቷ ሰደው መሬትን በአፍንጫ አስልሰው ካቃኗት በኋላ
"ኧረ አፈሩን ብይው!ይችን የመጋዣ ልጅ መጋዣ! "ሲሉ ተራግመው እመይቴ አልጣሽ የጠቆሟቸውን ሳህን ሲያማትሩ ከአጠገቧ እርቃኑን ተቀምጦ አዩት።እጆቻቸውን ወደላይ ሰቅለው
"አይ አለመታደሌ!" ካሉ በኋላ እንደ አመጣጣቸው እያገዘሙ ወደ ባለቤታቸው ተመልሰው መደቧ ላይ ተጠቅልለው ተኙ።

እንጀራና ወጡ ተዘጋጅቶ የምሳ ወጉ ከደረሳቸው በኋላ አያ ቢምር ከልብ ወዳጃቸው ጋር ሊያወጉ ወደ መንደር ዘለቁ።እመይቴይቱ ግን ፣ ቁሞ በመዋል የተብረከረኩ ጉልበቶቻቸውን ታቅፈው፣እሳት ያሟሸሻቸውን አይኖቻቸውን ከመክደናቸው እዛው ኩሽናው ወለል ላይ እንደተጋደሙ የልጅ እንቅልፍ ወሰዳቸው።ለአፍታ ካሸለቡ በኋላ ከአለት የከበደ አንዳች ነገር ጆሯቸውን ሲጫናቸው እየጮኹ ተነሱ።ዙሪያቸውን እየተፈራረቁ ከሚስቁት ሶስት ህፃናት ጋር  እላያቸው ተበግራ የቆመችዋን ጥጉቧን አህያቸውን እያባረሩ የተረገጠ ጆሯቸውን በሻሻቸው ጥፍንግ አድርገው አስረው እዬዬአቸውን ያወርዱት ጀመር።ፍቅሩ ፈገግታው ከገፁ ሳይጠፋ እየተጠጋቸው
"እመይ...ሰውነት'ኮ ነው የኩሽናውን በር ከፍተን አህያይትን እናስገባትና ምጣዱን ትስበረው ያለኝ"አለ ወንድሙን በስርቆሽ እያየ።
"ይሄይ?ይኸ?ይኸማ ቢሆንለት በተኛሁበት ቢያነደኝ ነበር ደስታው...ምነ አንተ ዝም ያልከው እንግዲያ?"
" 'አፍርጨ ነው የምጥልህ' እ...እያለኝ"
"ፈ...ርጠህ ቅር በለ...ው እንደ እ...ንቧይ"ከማለታቸው በተረገጠው ጆሯቸው በኩል አንዳች ነገር 'ጭውውውውውውው' ሲልባቸው ታወቃቸው።

አመሻሽ ላይ ተረኛው እረኛ ታሪክ
"እመይቴ አልጣሽ....ከብቶይን አምጥቻቸዋለሁ አስገቧቸው" ብሎ ጮኸና ምላሻቸውንም ሳይሰማ ወደሌሎች ባለከብቶች አቀና።

አያ ቢምር ከዋሉበት ወግ ሲመለሱ መንትዮቹ እንደወትሯቸው እየተነታረኩ፣ትሁንም ከምሳ አትርፈው የከደኑት መሶብ ላይ ለብቻዋ ሰፍራ እየታገለች፣ከብቶቻቸውም የጎረቤታቸው ማሳ ላይ ሲምነሸነሹ አገኟቸው።ከብቶቹን ከበረታቸው ጨምረው ባለቤታቸውን ጥሪ ገቡ።
"አልጣሽ!...ኧረ አልጣሽ!ኧረ 'ምኑ ገባሽ?"እያሉ ዋናውን ቤት ቆጡ ሳይቀራቸው አሰሱት።እየተጎተቱ ወደ ኩሽናው ሲዘልቁ እመይቴ አልጣሽ እጥፍጥፍ ብለው ተኝተዋል።
"ኧግ የደረባኑ መልአክ!ምነ አልጣሽ ምነ?አስርና ክያ እነጀራ አወጣሁ ብለሽ እስካሁን መኝታ?ኧረግ የኔይቱ ወይዘሮ!"ብለው እላያቸው ላይ ጣል ያረጉትን ኩታ ሲገልጡት አፀድ የመሰለው ሻሻቸው በደም ርሶ፣የጆሮ ግንዳቸውና የአንገታቸው ስር የደም ድልህ ተጋግሮበት አገኙት።ያዩትን ስለተጠራጠሩ ኩታውን ወደነበረበት መልሱና አይኖቻቸውን ማሻሸት ገቡ።ፍቅሩ ሲበር መጣና
"አበይ...ይኸ ሰውነት እመይን በተኛይበት ጥጉቢትን አህያ አስረገጣት።ጥሩ ውሃ ስጭኝ ብየ ብጠራት ብጠራት አኩርፋ ነው መሰል ዝም አለችኝ።ናማ አንተ ስጠኝ"

የእመይቴ አልጣሽ ቀብር ላይ አንድ ወዳጃቸው እንዲህ ሲሉ ሙሾ አወረዱላቸው።
"አንች የኔ ጉልበታም እንዲህ ነበርሽ ወይ
ክያ እንጀራ አውጥተሽ ማረፍሽ ነወይ
አንች ተደከመሽ እኔ እጋግራለሁ
ጠጅሽን ያሉ እንደሁ እንዴት አደርጋለሁ
ቀና በይ አልጣሽ ቅጅልኝ ከጠጁ
የጠላሽ አይጠፋም ሞልቷል የልጅ ልጁ"

ዘማርቆስ
(@wogegnit)

@wegoch
@wegoch
@wegoch
😢56👍429👏4👎2
እንኳን አደረሳችሁ✝️

@wegoch
👍272