ስንክሳር ወግጻዌ ዘተዋሕዶ
813 subscribers
3.46K photos
104 videos
194 files
1.2K links
የየዕለቱ ስንክሳር እና ግጻዌ የሚቀርብበት ቻናል ነው፡፡

ለማንኛውም አስተያየት እና እርማት
@zetaodokos ላይ ይላኩልን።

👇👇የYoutube Channel ይቀላቀሉ👇👇
https://youtube.com/channel/UCupqpIYe_mMpSM7jMT3Njhw
Download Telegram
#መጋቢት_4

መጋቢት አራት በዚች ቀን የአይሁድ ተሳታፊዎች ስለሚባሉ ክፉዎች ሰዎች በአሞር ደሴት #የአንድነት_ስብሰባ ሆነ፣ የከበረና የተመሰገነ #መኰንን_ሐኑልዮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ ኢትዮጵያዊቷ ጻድቅ #ቅድስት_ሐይመተ_ሥላሴ ዕረፍቷ ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#የቅዱሳን_ሊቃውንት_ጉባዔ

መጋቢት አራት በዚች ቀን የአይሁድ ተሳታፊዎች ስለሚባሉ ክፉዎች ሰዎች በአሞር ደሴት የአንድነት ስብሰባ ሆነ። እነርሱ የከበረ የፋሲካን በዓል በኔሳን ወር ማለት በሚያዝያ አሥራ አራት ቀን ከአይሁድ ጋር ያከብሩ ነበርና።

ሰኞ ቢሆን ማክሰኞም ቢሆን ወይም ረብዕ ወይም ሐሙስ ወይም በዓርብ ቀን ወይም በቅዳሜ ሰንበት ከአይሁድ ጋር ያከብሩ ነበርና የደሴታቸውም ኤጲስቆጶስ አወገዛቸው ግን አለተመለሱም።

ስለዚህም ወደ ሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ድምትራጥዮስ ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ ሰረባሞን ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ ድሜጥሮስ ወደ ኢየሩሳሌሙ ኤጲስቆጶስ ወደ አባ ሲማኮስ መልእክትን ላከ። የእነዚህንም ሰዎች ስሕተታቸውን ነገራቸው።

አራቱ ሊቃነ ጳጳሳት ከእነርሱ እየአንዳንዳቸው የከበረ የፋሲካ በዓልን በእሑድ ቀን ካልሆነ በቀር ከአይሁድ በዓልም በኋላ ካልሆነ በቀር አታድርጉ የሚል መልእክትን ላኩ። ይህንም ትእዛዝ የሚተላለፈውን ከምእመናን እንዲለይ አወገዙ።

በዚህም ጉባኤ አሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳት ተሰበሰቡ። እነዚያንም ሕግ ለዋጮች አቅርበው የሊቃነ ጳጳሳቱን መልእክቶቻቸውን በፊታቸው አነበቡ ከእነርሱም ከከፋች ምክራቸው የተመለሱ አሉ። በስሕተታቸውም ጸንተው የቀሩ አሉ። ረግመውና አውግዘውም ከምእመናን ለዪአቸው።
አባቶቻቸን ቅዱሳን ሐዋርያትም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተነሣባትን ዕለተ ፋሲካን ያለ እሑድ ቀን የሚያከብር እርሱ በበዓላቸው ከአይሁድ ጋራ ተሳታፊ ነውና ከምእመናን ይለይ ብለው እንዳዘዙ እንዲሁ የፋሲካ በዓል በዕለተ እሑድ እንዲከበርና ሕጉም ጸንቶና ተወስኖ እንዲኖር ተሠራ።

እግዚአብሔር ከሰይጣን ስሕተት ይጠብቀን። በተጋድሎአቸውና በትሩፋታቸው ደስ ባሰኙት በቅዱሳን ጸሎትም ከወጥመዶቹና ከሽንገላውም ያድነን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ _ሐኑልዮስ_መኰንን

በዚህችም ቀን የከበረና የተመሰገነ መኰንን ሐኑልዮስ ከጵንፍልያ አውራጃ ብርግያ በምትባል ከተማ በሰማዕትነት ሞተ።ይህንንም ቅዱስ ምስጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ስለ መውደዱና እርሱንም ስለ ማምለኩ ከዲዮቅልጥያኖስ ተልኮ የመጣ ብርይንኮስ የተባለ መኰንን ያዘው።

በመኰንኑም ፊት በቆመ ጊዜ ምስጋና ይግባውና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት ከፍ ከፍ ባሉ ቃላት አብራርቶ ገለጠ ።ብዙ ምስጋናዎችንም ለእግዚአብሔር አቀረበ የረከሱ ጣዖታትንም ረገማቸው።

መኰንኑም በዕንጨት መስቀል ላይ ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ ስለ ከበረ ስሙም ምስክር ይሆን ዘንድ ስል አደለው ምስጋና ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን አመሰገነው። ከዚያም ምስጋና ይግባውና በእግዚአብሔር እጅ ነፍሱን ሰጠ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሐይመተ_ሥላሴ

በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊቷ ጻድቅ በዝዋይ ደብረ ጽዮን ሐይቅ ውስጥ ገብታ ለአምስት ዓመት የጸለየች ታላቋ እናት ቅድስት ሐይመተ ሥላሴ ዕረፍቷ ነው፡፡ የትውልድ ሀገሯ ጎጃም ደብረ ጽላሎ ነው፡፡ ብዙ እናቶች በጣና ደሴት ውስጥ እየገቡ እንደጸለዩ ሁሉ እሷም ወደ ዝዋይ ሄዳ በዝዋይ ደብረ ጽዮን ሐይቅ ውስጥ ገብታ አምስት ዓመት ከባሕሩ ላይ የጸለየች ቅድስት እናት ናት፡፡ በታዘዘ መልአክ መሪነት ከሐይቁ ውስጥ ከወጣች በኋላ በገዳሙ ውስጥ ዐሥራ ዘጠኝ ዓመት ቆማ ጸልያለች፡፡

በመልአኩ መሪነት ወደ ቡልጋ ሄዳ በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖራለች፡፡ ሰውነቷም እጅግ ከስቶ ሥጋዋ አልቆ ይታይ ነበር፡፡ በመጨረሻም መልአኩ ተገልጦ ጊዜ ዕረፍቷን ከነገራት በኋላ ወዲያው መጋቢት 4 ቀን በሰላም ስታርፍ ሦስት አክሊላት ወርደውላታል፡፡ ቅድስት ሐይመተ ሥላሴን ስንክሳሩም "የጽድቅ ኮከብ" እያለ ይጠቅሳታል፡፡ ቅዱስ ገድሏ በደብረ በግዕ ይገኛል፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ከገድላት_አንደበት)