ስንክሳር ወግጻዌ ዘተዋሕዶ
813 subscribers
3.46K photos
104 videos
194 files
1.2K links
የየዕለቱ ስንክሳር እና ግጻዌ የሚቀርብበት ቻናል ነው፡፡

ለማንኛውም አስተያየት እና እርማት
@zetaodokos ላይ ይላኩልን።

👇👇የYoutube Channel ይቀላቀሉ👇👇
https://youtube.com/channel/UCupqpIYe_mMpSM7jMT3Njhw
Download Telegram
#መጋቢት_6

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

መጋቢት ስድስት በዚች ቀን #ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ ታማኝ የሆነ ኤጲስቆጶስ #የቅዱስ_ቴዎዶስዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #የአቡነ_አርከሌድስ እረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሰማዕት_ዲዮስቆሮስ

መጋቢት ስድስት በዚች ቀን በእስ*ላሞች ዘመነ መንግሥት ዲዮስቆሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ከእስክንድርያ ሰዎች ወገን ነው በማግባባት በመገፋፋት ከክርስቲያን አውጥተው ወደ እስ*ልምና አስገቡት በእምነታቸውም ጥቂት ጊዜ ኖረ።

ፍዮም በሚባል አገር ለአንድ ክርስቲያን ሰው የተዳረች አንዲት እኀት ነበረችው ወንድሟ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት እንደ ተወ በሰማች ጊዜ ታላቅ ኀዘንን አዘነች።

ከዚህም በኋላ እንዲህ ብላ ወደርሱ መልእክትን ላከች የክብር ባለቤት ክርስቶስን አንተ እንደ ካድከው ከምሰማ በክርስትናህ ሳለህ የሞትህ መርዶ ቢመጣልኝ እወድ ነበር። ከዚያም ከቅዱሳት መጻሕፍት ጠቅሳ ጻፈችለት በደብዳቤዋ ፍጻሜም እንዲህ ብላ ጻፈች። "ከዛሬ ጀምሮ ወደ ክርስትናህ ካልተመለስክ ይህቺ ደብዳቤ በእኔና በአንተ መካከል የፍቅር ፍጻሜ እንደሆነች ዕወቅ ከቶ ፊትህንም እንዳታሳየኝ መልእክትም ቢሆን አትላክልኝ። የእኅቱንም የመልእክት ደብዳቤ በአነበበ ጊዜ መሪር ዕንባን አለቀሰ ተጸጸተ ፊቱን ጸፋ ጽሕሙንም ነጨ ተነሥቶም ወገቡን ታጠቀ ረጅም ጸሎትንም በመጸለይ ማለደ ፊቱንም አዳኝ በሆነ መስቀል ምልክት አማተበ ከቤቱም ወጥቶ በእስክንድርያ ከተማ ውስጥ ተመላለሰ።

እስ*ላሞችም በአዩት ጊዜ ይዘው ወደ መኰንኑ አቀረቡት መኰንኑም ከእርሱ ስለሆነው ነገር ጠየቀው እርሱም ክርስቲያን ነኝ ሌላ ምንም ምን አላውቅም ብሎ መለሰ። መኰንኑም ደግሞ የክርስቲያንን ሃይማኖት ትተህ ወደእኛ እምነት ገብተህ አልነበረምን ብሎ መለሰለት።

ቅዱስ ዲዮስቆሮስም መልሶ እንዲህ አለ በወልድ የማያምን ሕይወትን አያያትም የእግዚአብሔር የቁጣው መቅሠፍት በላዩ ይወርዳል እንጂ የሚል በከበረ ወንጌል ተጽፏል። ስለዚህ እኔ በክብር ባለቤት በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ እኔም ትውልዴ ከክርስቲያን ነው አሁንም በክርስትናዬ እሞታለሁ። መኰንኑም እጅግ ተቆጥቶ ከዚህ ምክርህ ካልተመለስክ እኔ የጸና ቅጣት እቀጣሃለሁ አለው። ቅጣቱንም ፈርቶ ከመልካም ምክሩ አልተመለሰም።

ከዚያም በኋላ ታላቅ ግርፋት ገርፎ አሠረው በእሥር ጥቂት ቀናት ቆየ ከእሥር ቤትም አውጥቶ ከምክሩ ከሐሳቡ ቢመለስ ብዙ ገንዘብ ሊሰጠው ቃል ገባለት። ይህ ካልሆነ ግን በእሳት እንደሚአቃጥለው ነገረው። ቅዱሱም ሕያው በምታደርግ ከክርስቲያን ሃይማኖት በቀር በሌላ አልሞትም ብሎ መለሰለት።

መኰንኑም በእሳት እንዲአቃጥሉት አዘዘ ከከተማም ውጪ ታላቅ ጉድጓድ ቆፈሩለት። ዕንጨትም መልተው አነደዱት ነበልባሉም እጅግ ከፍ ከፍ አለ ያን ጊዜም ብዙ ገርፈው ሥጋውን በሰይፍ ሰነጣጠቁ ። ወደ እሳትም ጨመሩት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጥቶ በመንግሥተ ሰማያት የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቴዎዶስዮስ

በዚችም ዕለት ታማኝ የሆነ ኤጲስቆጶስ የቅዱስ ቴዎዶስዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። የዚህንም ቅዱስ ዜና ከዲዮቅልጥያኖስ የተሾመ የቆጵሮስ ገዥ ዮልዮስ ሰማ። ወደርሱም አስቀርቦ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክዶ ለረከሱ ጣዖቶች ዕጣን እንዲአጥን መሥዋዕትም እንዲአቀርብ ፈለገ፡፡ ቅዱስ ቴዎዶስዮስም እኔስ በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ ለእርሱም ዕሠዋለሁ በሎ መለሰ።

ትእዛዙንም ባልሰማ ጊዜ ጽኑዕ ግርፋትን ከላም ቆዳ በተሠራ ጅራፍ ገረፈው። ከዚያም ሰቅሎ ሥጋውን ሁሉ ሰነጠቀ አውርዶም በእሳት በአጋሉት በብረት አልጋ ላይ አስተኛው ጌታችንም ከዚህ ሥቃይ ጠብቆ አዳነው።

ከዚህ በኋላ እጆቹንና እግሮቹን በረጃጅም ችንካሮች ቸንክረው እስከ ወህኒ ቤት ጐትተው በዚያ ጣሉት። እግዚአብሔርም ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስን አጥፍቶ ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ እስከ ነገሠ ድረስ በወህኒ ቤት ኖረ።

ቈስጠንጢኖስም የመንግሥት ሥልጣን በያዘ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን የታሠሩትን ሁሉ እንዲፈቷቸው አዘዘ። ከዚያም በኋላ ወደ አገሩ ተመልሶ በጵጵስናው ሹመት ላይ ሁኖ ምእመናንን በበጎ አመራር እየመራ ኖረ። ዕድሜውንም ፈጽሞ በሰላም አረፈ፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_አርከሌድስ

ዳግመኛም በዚህች እለት አቡነ አርከሌድስ እረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አርከሌድስ አገራቸው ግብፅ ሲሆን ከተሰዓቱ ቅዱሳ ቀጥሎ ነው ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት፡፡ የነበሩበትም ጊዜ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡ወደ አገራችን ከመጡ በኋላ ወሎ ውስጥ ያለችውን እጅግ ጥንታዊቷን ቸር ተከል ማርያምን ቆረቆሯት፡፡ ጻድቁ የሚታወቁበት ትልቁ ገድላቸውም ሳይንት ውስጥ በቸር ተከል ማርያም ገዳም ውስጥ ለ21 ዓመታት ሳያርፉ ሳይቀመጡ በመቆም ጸሎት ያደረጉ ታላቅ አባት መሆናቸው ናቸው፡፡

አቡነ አርከሌድስ እጃቸውን ሲያጨበጭቡ 500 ርግቦች በአንድ ጊዜ ይሰበሰቡላቸው ነበር፡፡ እነርሱንም ወደፈለጉት ቅዱሳን መልእክት ይልኳቸው ነበር፡፡ በዚህ አስደናቂ ሥራቸውም በቅዱሳን ዘንድ ትልቅ ክብር ነበራቸው፡፡ለቅዱሳን የተለያየ ታሪክ አላቸው፣ ለአንዱ አንበሳ፣ ለአንዱ ጅብና አጋዘን፣ ለአንዱ ንብ፣ ለአንዱ ነብር፣ ለአንዱ አጋንንት ይታዘዙላቸው ነበር፡፡ ጻዲቁ በመጨረሻ ወደ ምረድ ግብፅ ተመልሰው ከሰማዕታት ጋር ተሰይፈው በሰማዕትነት ያረፉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢትና #ከገድላት_አንደበት)