Finote Hiwot የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኀኔ ዓለምና ደብረ ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት
15.3K subscribers
14.7K photos
78 videos
156 files
1.71K links
የቀጨኔ መድኃኔዓለም ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት ነሐሴ 26/ 1958 ዓ.ም ተመሠረተ።
Download Telegram
ገብርኄር፤ ስድስተኛው ሳምንት

#ገብር ኄር፥ ገብር ምዕመን ፥ ገብር ሀካይ
ስድስተኛ ሳምንት ገብርኄር ይባላል፡፡ ገብርኄር ማለት ታማኝ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ስለ ስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለኄር /ስለታማኝ/ አገልጋይ ያስተማረውን ትምህርት ይነገራል ይህንንም የሚያዘክር ምስጋና ይቀርብበታል፡፡ ይኸውም ማቴ 25፥14-30 ላይ ይገኛል፡፡ (ይህም ክፍል ጌታችን በማቴዎስ ወንጌል በምሳሌ ካስተማራቸው ትምህርቶች አንዱ ነው)፡፡
ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ዐቅሙ፡ ለአንዱ አምስት መክሊት፥ ለአንዱ ሁለት፥ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ፡፡ መክሊት የወርቅ መለኪያ /መስፈሪያ/ ነው፡፡ አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ ፡፡ አንድ ተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ፡፡
ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቈጣጠራቸው፡፡
*አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክ፤ ‹‹ ጌታ ሆይ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት›› አለ፡፡ ጌታውም፦ ‹‹መልካም አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ (ገብር ኄር)፤ በጥቂቱ ታምነሃል በቡዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ፡፡›› አለው፡፡
*ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት፡፡›› አለ፡፡ ጌታውም፡፡ መልካም፡ ‹‹ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ (ገብር ምዕመን) በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡
*አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ካልዘራህባት የምታጭድ፥ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ሌቦች እንዳይሠርቁኝ አታላዮች እንዳይቀሙኝ ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ መክሊትህ እነሆ›› አለው፡፡ ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው፡- ‹‹አንተ ክፋና ሃኬተኛ ባሪያ (ገብር ሀካይ) ካልዘራሁበት እንደማጭድ ፥ ካልበተንሁበትም እንድሰበስብ ታውቃለህን? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር፤ እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር፡፡ ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት አስር መክሊትም ላለው ስጡት፤ እሱን ደግሞ ወደ ዘለዓለም ሐዘንና መከራ ወዳለብት ወደ ጨለማው አውጥታችሁ ጣሉት›› አላቸው፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወስድበታል፡፡  አገልጋዮችም ይህንን ክፉ አገልጋይ ወደ ጨለማው አውጥተው ጣሉት፡፡ በዚህ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል፡፡
† መክሊት የተባለ ጸጋ ስጦታ ሲሆን፤ እግዚአብሔር ለእያንዳንዳችን የተለያየ ስጦታ ተሰጥቶናል በተሰጠንም ስጦታ ልናገለግልበት ያስፈልጋል፡፡
† በተጨማሪ መክሊት ቃለ እግዚአብሔር ነው፤ የሰማነውን ቃለ እግዚአብሔር ለመተግበር እየበረታን ለሌላው ማሰማት ይገባናል፤ ከእኛ የሚጠበቀው ማሰማቱ ብቻ ነው፤ በልቦናው አድሮ ሥራ የሚያሠራ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ እኛም በሃይማኖት ጠንክረን በምግባር በርትተን ታማኝ ባርያ ልንሆን ይገባል፡፡
፠፨፠ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ፠፨፠

/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/

• Facebook 👉 m.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
• Telegram 👉 t.me/finotehiwott

• Tiktok 👉 tiktok.com/@finotehiwot 
• YouTube 👉 m.youtube.com/@finotehiwot1958
17
የመጽሐፉ ስም "ሳምራዊቷ ሴት"
የመጽሐፉ አዘጋጅ ✍️ - ኢዮብ ዘገነተ ጽጌ
የመጽሐፉ ገጽ - 350
የምዕራፍ ብዛት - 27
የመጽሐፉ ይዘት - በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማርያ ሲካር መንደር በያዕቆብ ጉድጓድ አጠገብ አግኝቶ ቅዱስ ቃሉን አስተምሮ ወደ ድኅነት ያመጣትና ለማኅበረሰቧ መዳን ምክንያት ስለሆነችው የሰማርያዋ ሴት ላይ የሚያጠነጥን መጽሐፍ ነው፡፡
       መጽሐፉ በውስጡ ጌታችን ሴቲቱን ለማግኘት ከመጣበት ስድስት ሰዓት ጀምሮ ለመንደሯ ሰዎች ምስክር እስከ ምትሆንበት ድረስ  ያለውን የዮሐንስ ወንጌል (ምዕራፍ አራት) ላይ የተጻፈውን ከርሷ ሕይወት ፣ ከሰማርያ ከተማ እና ከሰው ልጅ ድኅነት ጋር በማያያዝ በስፋት ተብራርቶበታል ፡፡ ጌታችንን ካገኘችና በወንጌል ከተጻፈላት ታሪክ በኋላ ስለ ስሞቿ፣ በዘመነ ሐዋርያት ስለነበራት ተጋድሎ ከአምስት እኅቶቿና ከሁለት ልጆቿ ጋር ስለተቀበለችው መከራ እና ስቃይ ፣ በመጨረሻም ስለ ሰማዕትነቷ ተጽፎ የምናገኝበት መጽሐፍ ነው፡፡

የመጽሐፉ ዋና አከፋፋይ - ሰርዲኖን የመጽሐፍ መደብር
   አድራሻ - ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ሕንጻ Ground ላይ
39👍8🙏3