የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
2.58K subscribers
6.1K photos
67 videos
60 files
1.7K links
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
Download Telegram
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_6

ታኅሣሥ ስድስት በዚህች ዕለት የታላቋ #ሰማዕት_የቅድስት_አርሴማ ቤተ ክርስቲያኗ የከበረችበትና የሥጋዋ ፍልሰት የተከናወነበት፣ ቅዱስ አባት የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት #የአባ_አብርሃም_ሶርያዊ የዕረፍቱ እና #የቅዱስ_ስምዖን_ጫማ_ሰፊውም መታሰቢያው ነው።
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_7

ታኅሣሥ ሰባት በዚችም ዕለት ከቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚወለድ #በከበሩ_ነቢያት አፍ ለመሰበኩ መታሰቢያ ነው፣ በደብረ ሲሐት የሚኖር #አባ_ዳንኤል አረፈ፣ #ቅዱስ_አባት_አባ_ማቴዎስ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ስብከተ_ነቢያት

ታኅሣሥ ሰባት በዚህችም ዕለት ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ እንደሚወለድ በከበሩ ነቢያት አፍ ለመሰበኩ መታሰቢያ ሆነ ።

ይህች ዕለት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት "ስብከት" ትባላለች። ስብከት ማለት በቁሙ "የምስራች፣ አዲስ ዜና መንገርን" የሚመለከት ሲሆን ዋናው ምሥጢር ግን ከነገረ ድኅነት (ከመዳን ትምሕርት) ጋር የተገናኘ ነው።

በዚህ ዕለት (ሳምንት) ሁሉም ነቢያት ከነ ትንቢታቸው ይታሰባሉ። ዘመነ ስብከትም ከታሕሳስ 7 እስከ 13 ያለውን ይይዛል። ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦ እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ። በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ፣ በርደተ መቃብር፣ ርደተ ገሃነም ተፈረደበት። በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው።

ከዚህ በሁዋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር። ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር፣ ሱባኤ ይቆጠር፣ ምሳሌም ይመሰል ገባ።

ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ። ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል:: ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት/ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል።

ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም፣ በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል። እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል። መድኅን ክርስቶስም ተወልዶ አድኗቸዋል።

ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር) መጻዕያትን (ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው። ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው በጸጋ ይሰጠዋል:: እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ።

ዘመነ ነቢያት ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም። በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ። (ሐዋ.11፥27) ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ: ይገስጻሉ።

ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል፣ "እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር: ወተናጸሩ ገጸ በገጽ" እንዳለ አባ ሕርያቆስ። (ቅዳሴ ማርያም)

የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ አንዳንዶቹም በእሳት፣ አንዳንዶቹም በሰይፍ፣ አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል። ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል።

ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል። ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ: እናንተ በድካማቸው ገባችሁ" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል። (ዮሐ.4፥36)

ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል ሽተዋልም። "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ" እንዳለ ጌታ በወንጌል። (ማቴ. 13፥16፣ 1ዼጥ.1፥10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው: ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ።

ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት 15ቱ አበው ነቢያት: 4ቱ ዐበይት ነቢያት: 12ቱ ደቂቀ ነቢያት እና ካልአን ነቢያት ተብለው በ4 ይከፈላሉ::

#15ቱ_አበው_ነቢያት ማለት፦ ቅዱስ አዳም አባታችን፣ ሴት፣ ሔኖስ፣ ቃይናን፣ መላልኤል፣ ያሬድ፣ ኄኖክ፣ ማቱሳላ፣ ላሜሕ፣ ኖኅ፣ አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ፣ ሙሴ እና ሳሙኤል ናቸው።

#4ቱ_ዐበይት_ነቢያት ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል፣ ቅዱስ ኤርምያስ፣ ቅዱስ ሕዝቅኤልና፣ ቅዱስ ዳንኤል ናቸው።

#12ቱ_ደቂቀ_ነቢያት የሚባሉት ሆሴዕ፣ አሞጽ፣ ሚክያስ፣ ዮናስ፣ ናሆም፣ አብድዩ፣ ሶፎንያስ፣ ሐጌ፣ ኢዩኤል፣ ዕንባቆም፣ ዘካርያስ እና ሚልክያስ ናቸው።

#ካልአን_ነቢያት የሚባሉት ደግሞ፦ ኢያሱ፣ ሶምሶን፣ ዮፍታሔ፣ ጌዴዎን፣ ዳዊት፣ ሰሎሞን፣ ኤልያስ እና ኤልሳዕ ሌሎችም ናቸው::

ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ፦
*የይሁዳ (ኢየሩሳሌም)፣ የሰማርያ (እሥራኤል) እና የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ::

በዘመን አከፋፈል ደግሞ:-
* ከአዳም እስከ ዮሴፍ #የዘመነ_አበው_ነቢያት
* ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ነቢዩ ሳሙኤል #የዘመ_መሳፍንት_ነቢያት
* ከቅዱስ ዳዊት እስከ ዘሩባቤል ያሉት #የዘመነ_ነገሥት_ነቢያት
* ከዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ #የዘመነ_ካህናት_ነቢያት ይባላሉ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን በጻድቅ በነቢያት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_8

ታኅሣሥ ስምንት በዚህች ዕለት #የአቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ ተወለዱ፣ በዚህች ቀን የድባው #አቡነ_ሙሴ ልደታቸው ነው፣ #ብፅዕት_እንባመሪና ተወለደች፣ ታላቅ አባት #የአባ_ኪሮስ አረፈ፣ የከበሩ ሴቶች #ቅድስት_በርባራና_ቅድስ_ዮልያና በሰማዕትነት አረፉ፣ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ #አባ_ያሮክላ አረፈ፣ #አባ_ሳሙኤል_ዘደብረ_ቀልሞን አረፈ፣ #ቅዱሳን_አባ_ኤሲና_እኅቱ_ቴክላ በሰማዕትነት አረፉ፣ #አባ_ዮሐንስ_ዘደማስቆ አረፈ፣ የደብረ ድማሕ #ቅዱስ_ተክለ_አልፋ አረፈ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አና ጻድቃን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥ እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_9

#ቅዱስ_አባት_አባ_በአሚን

ታኅሣሥ ዘጠኝ በዚች ቀን ያለ ደም መፍሰስ ታማኝ የሆነ ቅዱስ አባት አባ በአሚን በሰማዕትነት አረፈ።

እርሱም በደቡብ ግብጽ በእስሙናይን አውራጃ ለሀገረ ቴርሳ አቅራቢያ ከሆኑ ከሐፂብ ተወላጆች ወገን ነው። ለአንድ ባለጸጋም በጅሮንድ ሆኖ ሳለ ስለ ንጽሕናውና ስለ ቅድስናው በሁሉ ዘንድ ተወዳጅ ሆ። የባለ ጸጋውም ሚስት አባ በአሚንን እጅግ የምትወደውና የምትተማመንበት ሆነች።

እርሱ ግን የዚህን ዓለም ፍጻሜ አሰበ፤ የባለጸጋውንም አገልግሎት ትቶ ወደ ገዳም ሒዶ መነኰሰ። ባለጸጋውም መሔዱን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ። ሚስቱንም ይዞ አባ በአሚን ወዳለበት በአንድነት ሔዱ። ወደ እርሳቸው እንዲመለስም ለመኑት፤ እንዲህም አሉት "ከአንተ እንለይ ዘንድ ከቶ አንችልም ስለዚህ አንተውህም" አሉት።

አባ በአሚንም "እኔ ራሴን ብፅዓት አድርጌ ለእግዚአብሔር ሰጥቻለሁ እኮን" አላቸው። ይህንንም ሲሰሙ ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑ ተትውት ተመለሱ።

ከዚህም በኋላ በአማረ ተጋድሎ ሁሉ ታላቅ ተጋድሎን በመጋደል ብዙ ዘመናት እግዚአብሔርን አገለገለው ። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ሁኖ ደሙን ሊአፈስ ወዶ ወደ እንዴናው ከተማ ሔደ። ብዙዎች ምእመናንም ሲያሠቃዩአቸው አገኛቸው። እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመ፣ ጽኑ ሥቃይንም አሠቃዩት፣ ሥጋውን በእሳት ለበለቡ፣ ሕዋሳቱንም ሠነጣጥቀው ከመንኰራኲር ውስጥ ጨመሩት፣ ዳግመኛም በአጋሏቸው የብረት ዘንጎች አቃጠሉት። በዚህም ሁሉ ጸና ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለ ጉዳት በጤና ያስነሣው ነበር።

እንዲህም እየተሠቃየ ሳለ ጣዖት የሚመለክበት ወራት አለፈና ጻድቅ ቈስጠንጢኖስ ነገሠ። ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ዲዮቅልጥያኖስ ያሠራቸውን እሥረኞች ሁሉ እንዲፈቷቸው አዘዘ። ጌታችንም ለአባ በአሚን ተገለጠና ከሰማዕታት ጋር እንደቆጠረው አስረዳው።

ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ከእሳቸው ቡራኬ ሊቀበል ሽቶ ከውስጣቸው ሰባ ሁለት እሥረኞችን ወደርሱ ያመጡ ዘንድ አዘዘ። አባ ኖብ ከእርሳቸው ጋር በዚያ ነበረ ከእርሳቸውም አንዱ ይህ አባ በአሚን ነው። ከዚህም በኋላ ከእሥሙናይነረ ውጭ በሆነች ገዳም የሚኖር ሆነ። ጌታችንም ታላቅ ጸጋን ሰጥቶት በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውሳቸው ሆነ ዜናውም በቦታው ሁሉ ተሰማ።

በዚያም ወራት የሮም ንጉሥ ሚስት የሆነች አንዲት ንግሥት ነበረች። እርሷም ከእርሷ ጋር ስለሚኖር የወንጌላዊውን ዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ ሁልጊዜ የሚፈራ ስለ አንድ ዲያቆን እጅግ የታመመች ናት። ከንጉሥ ሹሞች አንዱ በቀናበት ጊዜ ወደ ንጉሡ ሒዶ "ጌታዬ ንጉሥ ሆይ ዕወቅ ይህ ዲያቆን ዮሐንስ ሁልጊዜ የዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ በማንበብ እያመካኘ ከእመቤቴ ንግሥት ጋር ይተኛል" አለው።

ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ በዚያንም ጊዜ ተነሥቶ ንግሥቲቱ ወዳለችበት ቤተ መንግሥት ገባ ያንንም ዲያቆን በፊቷ ቁሞ የዮሐንስን የራእዩ መጽሐፍ ሲያነብ አገኘውና ከነመጽሐፉ ወስደው ዲያቆኑን ከባሕር እንዲአሠጥሙት አዘዘ። ሁለት ሰዎችም በታናሽ ጀልባ ጭነው ወስደው ከባሕር መካከል ወረወሩት። ወዲያውኑ ብርሃንን የለበሰ ሰው ከሰማይ ወርዶ ያንን ዲያቆን ከመጽሐፉ ጋር ነጥቆ ወስዶ ከአንዲት ደሴት ላይ አኖረው። እንዚያ ሁለት ሰዎች ሲያዩ ነበር እጅግም እያደነቁ ተመለሱ ያዩትንም ለንጉሡ አልነገሩትም።

ንግሥቲቱም በዲያቆኑ ላይ የተደረገውን በአየች ጊዜ እጅግ አዘነች። በእርሷም ደዌ ጸናባት ሆድዋም ቆስሎ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረች። ወደርሷም ብዙ ጥበበኞች ባለመድኃኒቶች መጥተው ነበር ግን ሊፈውሷት አልቻሉም። አንድ አዋቂ ሰውም እንዲህ ብሎ መከራት በግብጽ አገር ወደሚኖሩ ቅድሳን ብትሔጂ ከደዌሽ በተፈወስሽ ነበር። በዚያን ጊዜ ተነሣች ከእርሷም ጋር ብዙ ሠራዊት አለ። ወደ ግብጽ አገርም ደርሳ ገዳማቱንና አብያተ ክርስቲያንንም ሁሉ ዞረች ግን አልዳነችም።

ወደ እንዴናው ከተማም በደረሰች ጊዜ ስለ መምጣቷ የአገሩ መኳንንት አደነቁ። እርሷም ችግርዋን ሁሉ ነገረቻቸው። እነሱም ወደ ቅዱስ አባ በአሚን እንድትሔድ መከሩዋት። በመርከብም ተሳፍራ ወዲያውኑ ቅዱስ አባ በአሚን ወዳለበት ገዳም ደረሰች። "እነሆ ንግሥት ወዳንተ መጥታለች ከአንተም ልትባረክ ትሻለች" ብለው ነገሩት። እርሱም ከምድር ንግሥት ጋር ምን አለኝ ብሎ መውጣትን እምቢ አለ። መነኰሳትም ወደርሷ እንዲመጣ አጽንተው ለመኑትና ወጣ በአየችውም ጊዜ ከእግሩ በታች ወድቃ ሰገደችለት። እርሱም በዘይት ላይ ጸልዩ ቀባት በዚያንም ጊዜ ዳነች።

ቅዱስ አባ በአሚንም "ንጉሥ ከባሕር በአሠጠመው በዚያ ዲያቆን ምክንያት ይህ ሁሉ እንደደረሰብሽ ዕወቂ፤ እርሱ ግን በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት ይኖራል፤ የአቡቀለምሲስ ዮሐንስ የራእይ መጽሐፍም ከእርሱ ጋር አለ" አላት። ንግሥቲቱም ሰምታ እጅግ አደነቀች ደስ አላትም ስለዚያ ዲያቆን በሕይወት መኖርና እርሷም ፈውስ ስለማግኘቷ ለቅዱስ አባ በአሚንም እጅ መንሻ ብዙ ገንዘብ አቀረበችለት። ከንዋየ ቅዱሳት በቀር ምንም ምን ገንዘብ አልተቀበለም።

ከዚህም በኋላ እግዚአብሔርን እያመሰገነች ወደ ሮሜ አገር ተመለሰች። በእርሷ ላይ የሆነውን ሁሉ፣ ወደ ባሕር ስለ አሠጠሙት ስለዚያ ዲያቆንም፣ እርሱም እስከ ዛሬ በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት እንዳለ ለንጉሡ ነገረችው። ንጉሡም ይህን ነገር ሰምቶ እጅግ አደነቀ ይፈልጉትም ዘንድ መልክተኞችን ላከ። በደሴትም ውስጥ በሕይወት አገኙት መጽሐፉም ከርሱ ጋር አለ። ተመልሰውም ለንጉሡ ነገሩት ሁለተኛም ወደርሱ እንዲመጣ እየማለደ ላከ። ከመልክተኞችም ጋር ወደ ንጉሡ መጣ። ንጉሡም በአየው ጊዜ ታላቅ ደስታ አደረገ ከእግሩ በታችም ወድቆ "በአንተ ላይ ስለአደረግሁት በደል ይቅር በለኝ" አለው እርሱም በአንድነት እግዚአብሔር ይቅር ይበለን አለ።

ከዚህም በኋላ ያ ዲያቆን በሮሜ ሀገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ። ያንንም የዮሐንስ አቡቀለምሲስ ራእይ ተረጐመው። ቅዱስ አባ በአሚንም በቀንና በሌሊት ያለማቋረጥ የሚጋደል ሆነ።

በአቅራቢያውም አንድ ደግ ኤጲስቆጶስ አለ። በአንዲት የሰማዕታት ገዳም ከምእመናን ጋር በዓልን ሲያደርግ አርዮሳውያንም ለራሳቸው ሐሰተኛ ኤጲስቆጶስ ይዘው ሕዝብን የሚያስቱ ሆኑ። የሀገሩም ኤጲስቆጶስ ወደ አባ በአሚን መጥቶ ስለ እሊህ ከሀድያን የደረሰበትን ኃዘኑን ሁሉ ነገረው። የሰማዕታትም በዓል በሆነ ጊዜ የእሊህን ከሀድያን ምክር እግዚአብሔር ይበትን ዘንድ ቅዱስ አባ በአሚን ከሕዝብ ጋር በመለመንና በመስገድ ጸለየ። ከዚህም በኋላ የሽመል በትር ያዘ ሕዝቡም ሁሉ እየአንዳዱ በትሮችን ይዘው ወደእነዚያ ከሀድያን ሔዱ። ከሀድያንም በአዩ ጊዜ ተበተኑ ወደዚያ ዳግመኛ አልተመለሱም እግዚአብሔር ምክራቸውን በትኖባቸዋልና።

ቅዱስ አባ በአሚንም ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ የሞት ደዌን ታመመ። መነኰሳቱንም ሁሉ ሰብስቦ ዕድሜው እንደ ቀረበ ነገራቸውና አጽናናቸው። እነርሱም ከእርሱ ስለመለየታቸው አዘኑ ከዚህም በኋላ በፈጣሪው እግዚአብሔር እጅ ነፍሱን ሰጠ። መነኰሳቱም እንደሚገባ እያመሰገኑና እየዘመሩ መልካም አገናነዝን ገነዙት ሥጋው በእምነት ወደርሱ ለሚመጣ ሁሉ መጠጊያ ሆነ ወይም በቀናች ሃይማኖት ጸንቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሒዶ በስሙ ለሚለምን ሁሉ የለመነው ይሆንለታል።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ታኅሣሥ 16 ጉባኤ ጽዮን በሠዓት በመገኝት በመርሐግብሩ ይሳተፉ
እሁድ ታኅሣሥ 17 አርቲስቶች የሚገኙበት ልዩ የሥነ ጽሑፍ ምሽት ትኬቱን በመቁረጥ ቀድመው ቦታ ይያዙ
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_10

ታኅሣሥ ዐስር በዚህች ዕለት የአንጾኪያው ሊቅ #ቅዱስ_አባት_አቡነ_ሳዊሮስ ፍልሠተ ሥጋው ነው፣ #ቅዱስ_አባት_አባ_ኒቆላዎስ አረፈ፣ #አባ_ጥዋሽ ዕረፍቱ ነው፣ የከበረች #ቅድስት_ሱርስት ዐረፈች፣ ቅዱሳን ሰማዕታት #ቅዱስ_ተላስስና_ቅዱስ_አልዓዛር በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሱርስት

ይኽችም ቅድስት ከቁስጥንጥንያ አገር እጅግ ከከበሩ ወገኖች የአንዱ ልጅ ናት፡፡ ለአንድ ለከበረ ሰው ልጅ በታጨች ጊዜ አባቷን ‹‹አባቴ ሆይ! አስቀድሜ ወደ ቤተ መቅደስ ሄጄ እሰግድ ዘንድ ፍቀድልኝ በምመለስበት ጊዜ እግዚአብሔር እንደፈቀደ ይሁን›› አለችው፡፡ አባቷም ‹‹አስቀድመሽ ወደ ባልሽ ግቢ፣ ሠርግሽ ከተፈጸመ በኋላ ከእርሱ ጋር ወደ ወደድሽው ሄደሽ ስዕለትሽን ትፈጽሚያለሽ›› አላት፡፡ እርሷም መልሳ ‹‹በድንግልናዬ ሳለሁ ወደዚያች የከበረች ቦታ ሄጄ ልጸልይ ለእግዚአብሔር ቃል ገብቻለሁና ቃሌን ብዋሽ ፈጣሪ በእኔ ላይ ይቆጣል›› ስትለው አባቷ ከሚያገለግሏት ወንዶችና ሴቶች አሽከሮች ጋር ለምጽዋትም የምትሰጠው 300 የወርቅ ዲናር ሰጥቶ ላካት፡፡
ሱርስትም እዚያ በደረሰች ጊዜ የከበሩ ቦታዎችን ሁሉ እየዞረች ተሳለመች፣ ወደ ግብጻውያን ገዳምም በደረሰች ጊዜ አንድ አረጋዊ መነኩሴ ማቅ ለብሶ አገኘችውና የልቧን ሀሳብ ሁሉ ማለትም ልትመነኩስ እንደምትፈልግ ነገረችው፡፡ እርሱም ‹‹የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን›› አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሊሄዱ በተዘጋጁ ጊዜ ወደ ስውር ቦታ ገብታ ለወላጆቿ ‹‹እኔ ሰውነቴን ለእግዚአብሔር አቅርቤያለሁ አታገኙኝምና አትፈልጉኝ›› ብላ ደብዳቤ ጻፈች፡፡ ደብዳቤውንም በልብሷ አሥራ ከዕቃ ውስጥ አኖረችው፡፡ ሰዎቹም ከእነርሱ ጋር አብራ የምትሄድ መስሏቸው ዕቃ ጭነው በቀደሟት ጊዜ አንዱን አገልጋይ ይዛ አስቀረችውና ‹‹ወደ ጎልጎታ ገብቼ ልጸልይ እሻለሁና›› ብላ ምሥጢሯን እንዲጠብቅ ነገረችው፡፡

ከዚህም በኋላ ወደዚያ ሽማግሌ መነኩሴ ዘንድ ተመልሳ የያዘችውን 300 የወርቅ ዲናር ለድኆችና ጦም አዳሪዎቸ እንዲያከፋፍለው ሰጠችውና ያመነኩሳት ዘንድ ለመነችው፡፡ እርሱም ጽናቷን አይቶ ፈቃደ እግዚአብሔርም መሆኑን ዐውቆ ራሷን ላጭቶ የምንኩስና ልብስ አለበሳት፡፡ እርሷም እግዚአብሔር ወደፈቀደላት ወደ አንዲት ዋሻ ሄዳ በዚያ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረች፡፡ በዚህም ጊዜ ዕድሜዋ ገና 12 ዓመት የነበረ ቢሆንም የሰውን ፊት ሳታይ በዚያች ዋሻ ውስጥ ለ27 ዓመታት በተጋድሎ ኖረች፡፡

ቃህራ ከሚባል አገር በገድል ሥራ የሚኖር ሲላስ የሚባል መነኮስ ነበር፡፡ በቀልሞን ዋሻ የሚኖር አንድ ጓደኛ መነኮስ አለውና ፋሲካ በደረሰ ጊዜ እርሱን ጎብኝቶ በረከት ለመቀበል ሄደ፡፡ በሄደም ጊዜ አላገኘውምና እርሱን ፍለጋ ተራራ ለተራራ ዞረ፡፡ በዚያም የእግር ዱካ አገኘና ዱካውን ተከትሎ በመሄድ መግቢያው ላይ ሲደርስ ‹‹የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ ባርከኝ›› አለ፡፡ ከውስጥም ያለው ድምጽ ስሙን ጠርቶት ‹‹ሲላስ ሆይ አንተ ካህን ነህና ልትባርከኝ ይገባል›› አለው፡፡ ሲላስም ወደ ውስጥ እንደገባ ቅድስት ሱርስትን አገኛት፡፡ እርሷም ምሥጢሯን ሁሉ በዝርዝር ነገረችው፡፡ ወዲያውም በሰላም ዐረፈች፡፡ ሲላስም በዚያች ዋሻ ውስጥ በክብር ገንዞ ቀበራት፡፡ ገድሏንም ጻፈላት፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ሁሉ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታኅሣሥ እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
☝️☝️☝️☝️☝️#እንኳን_አደረሳችሁ☝️☝️☝️☝️☝️
የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ምክንያት በማድረግ ጌታችን የተወለደበትን ግርግም እየሰራ በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ ሊቀርብ ጥቂት ቀናት ቀርተውታል እርስዎት #ለቤትዎ#ለቤተሰብዎ#ለመኪና እንዲሁም #ለወዳጅ_ዘመድ ሥጦታ ለመስጠት ካሰቡ ፈጥነው ይግዙ

ተጨማሪ መረጃ
ሰንበት ት/ቤታችን ልማት ሱቅ ደውለው ይዘዙ በፈለጉት ሳይዝ እንሰራለን
0910665119 ፍትሐነገሥት
0913728785 ቤተሌሔም
Share
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_11

ታኅሣሥ ዐስራ አንድ በዚህች ዕለት ታላቁ አባት #ቅዱስ_አባ_በኪሞስ ዐረፈ፣ ታላቁ ሰማዕት #ቅዱስ_ገላውዲዮስ ልደቱ ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ሰማዕት_ቅዱስ_ገላውዲዮስ

ዳግመኛም በዚህች ዕለት ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዲዮስ ልደቱ ነው፡፡ ገላውዴዎስ ማለት ‹‹ዕንቈ ጳዝዮን›› ማለት ነው፡፡ የመላእክት አርአያ ያለቅ ቅዱስ ገላውዴዎስ አባቱ አብጥልዎስ የሮሙ ንጉሥ የኑማርያኖስ ወንድም ነው፡፡ አባቱን የአንጾኪያ ሰዎች እጅግ ይመኩበትና ይወዱት ነበር፡፡ በሕይወት እያለም በጦርነት ድል ሲያደርግ የሚያሳይ ሥዕሉን በከተማው ላይ አሠርተው ያከብሩት ነበር፡፡ ልጁ ቅዱስ ገላውዴዎስ ግን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየተማረ አደገ፡፡ የሮሙ ንጉሥም ዜናውን ሰምቶ ሊያየው ወደደና ልጁን እንዲልክለት መልእክት ላከ፡፡ ሄዶ ሲያየውም ንጉሡ ከነሠራዊቱ ወጥቶ በክብር ተቀበለው፡፡

ጣዖት አምላኪ የሆኑ የቁዝና የሌሎችም ሀገሮችን ቅዱስ ገላውዴዎስ ድል እያደረጋቸው ጣዖቶቻቸውንም ይሰባብርባቸው ነበር፡፡ ወደ አንጾኪያም በተመለሰ ጊዜ ዲዮቅልጥያኖስ ጌታችንን ክዶ ጣዖት ማምለክ መጀመሩን ባየ ጊዜ እጅግ አዘነ፡፡ ከቅዱስ ፊቅጦርም ጋር ሆነው የመጻሕፍትን ቃል ዕለት ዕለት ያነቡ ነበር፡፡ ሁለቱም ስለ ጌታችን ክብር ሰማዕት ሆነው ደማቸውን ያፈሱ ዘንድ በምክር ተስማሙ፡፡ ሰይጣንም በሽማግሌ አምሳል ተገልጡ ያዘነላቸው በመምስል ‹‹ልጆቼ ሆይ መልካም ጎልማሶች ናችሁ፣ የነገሥታት ልጆችም ናችሁ፣ እኔ ስለ እናንተ አዝንላችኋለሁ ስለዚህም ከንጉሡ ጋር ተስማምታችሁ አማልክቶቹን እያጠናቸሁ ትእዛዙንም እየፈጸማችሁ ኑሩ፡፡ ነገር ግን ክርስቶስን በቤታችሁ አምልኩት ይህ ዲዮቅልጥያኖስ ግን እጅግ ጨካኝና ኃይለኝ ነው›› እያለ መከራቸው፡፡ እግዚአብሔርንም ይህን የሚናገራቸው ሰይጣን መሆኑን ገለጸላቸውና ‹‹አንተ የሐሰት አባት ሁልጊዜ የእግዚአብሔርን ሀሳብ ትቃረናለህ›› ብለው በገሠጹት ጊዜ መልኩን ለውጦ ጥቁር ባሪያ ሆነ፡፡ ‹‹እነሆ ከንጉሡ ጋር አጣልቼ ደማችሁን እንዲፈስ አደርገዋለሁ›› ብሎ ወደ ከሃዲው ንጉሥ ወደ ዲዮቅልጥያኖስ ዘንድ ሄዶ ‹‹ፊቅጦርንና ገላውዴዎስን ካልገደልካቸው በአንተ ላይ ይነሱብሃል፣ አንተንም ገድለው መንግሥትህን ይወስዳሉ፣ እነርሱም የመንግሥት ልጆች መሆናቸውን ዕወቅ›› አለው፡፡

ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም ቅዱስ ገላውዴዎስን አስጠርቶ የአባቱን ሹመት እንደሚሾመው ቃል ከገባለት በኋላ ለጣዖቱ እንዲሠዋ አዘዘው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስ ግን በድፍረት ጣዖቱንና ንጉሡን ሰደባቸው፡፡ የቅዱስ ፊቅጦር አባት ኅርማኖስ የተባለው ባለሟሉ ‹‹እንደ ልጄ ፊቅጦር ዐመፀኛ ነውና ወደ እስክንድርያ ልከነው በዚያ እንዲገድሉት እናድርግ›› ብሎ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስን መከረው፡፡ አሠቃይተው እንዲገድሉትም ከደብዳቤ ጋር አድርገው ወደ እንዴናው ሀገር ገዥ ወደ ጨካኙ አርያኖስ ላኩት፡፡

አርያኖስም ቅዱስ ገላውዴዎስን ባየው ጊዜ ደንግጦ በክብር ተቀበለው፡፡ እጅ ነሥቶም ከሳመው በኋላ ‹‹ጌታዬ ስለምን የንጉሡን ትእዛዝ ትተላለፋለህ?›› እያለ መከረው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስም ‹‹ንጉሡ ያዘዘህን ትእዛዝ ልትፈጽም እንጂ በነገርህ ልታስተኝ አልተላኩም›› አለው፡፡ መኮንኑም እስኪቆጣ ድረስ ብዙ ጊዜ እያባበለው ተነጋገሩ፡፡ ከዚህም በኋላ አርያኖስ እጅግ ተቆጣና በያዘው ጦር ወግቶ ቅዱሱን ገደለው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ፡፡ ምእመናንም የመከራው ዘመን እስኪፈጸም ቅዱስ ሥጋውን ወስደው ከቅዱስ ፊቅጦር ጋር በሣጥን አኖሩት፡፡ የቅዱስ ፊቅጦርም እናት ቅድስት ሶፍያ ወደ እንዴና ሀገር መጥታ የሁለቱን ቅዱሳን ሥጋቸውን ወደ አንጾኪያ ወስዳ በክብር አኖረችው፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አና ጻድቃን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥ እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር#ታኅሣሥ_12

ታኅሣሥ ዐስራ ሁለት በዚህች ዕለት ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑ #አቡነ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ ዕረፍታቸው ነው፣ #ቅዱሳን_አንቂጦስ እና #ቅዱስ_ፎጢኖስ በሰማዕትነት ዐረፉ፣ #ዳግማዊ_ቂርቆስ የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ልጅ ብሔረ ብፁዓን የገባበት ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ

ታኅሣሥ ዐስራ ሁለት በዚህች ዕለት ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑ አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ዋሊ ዕረፍታቸው ነው፡፡ ጻድቁ የተወለዱት በአክሱም ጽዮን ነው፡፡ ነገዳቸው የአክሱም ገበዝ ከነበረው ከጌድዮን ነው፡፡ የአባታቸው እስጢፋኖስና እናታቸው አመተ ማርያም ምግባር ሃይማኖታቸው የቀና ትሩፋት ተጋድሏቸው የሰመረ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ገና በ12 ዓመቱ ማይ ሹም በተባለው ባሕር ገብቶ ሲጸልይ ባሕሩ በብርሃን ተከቦ ይታይ ነበር፡፡ ከባሕሩም ወጥቶ ወደ ቤተክርስቲያን ገብቶ እያለቀሰና እያዘነ ሲጸልይ ካህናቱ ‹‹ይህ ሕፃን የእኛ ኃጢአት እየታየው? ወይስ ምን ኃጢአት ኖሮበት ነው እንዲህ የሚያዝነውና የሚያለቅሰው?›› እያሉ ያደንቁና ይገረሙ ነበር፡፡

አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ እናቱ አመተ ማርያም ቤተሰቧንና ቤት ንብረቷን ትታ ከመነኮሰች በኋላ እርሱም ካልመነኮስኩ በማለት አባቱ እስጢፋኖስን ቢለምነውም እምቢ ስላለው በራሱ ፈቃድ ከአንድ ሽማግሌ ጋር ወደ አባ መድኃኒነ እግዚእ ገዳም ደብረ በንኰል ገብቶ መነኮሰ፡፡ በዚያም ነፍሱን ‹‹ነፍሴ ሆይ! እነሆ ለክርስቶስ ታጨሽ፣ የቅዱሳንን ቀንበር እንሆ ተሸከምሽ፣ የመላእክትን ንጽሕና ትጠብቂ ዘንድ ዛሬ በእግዚአብሔርና በቅዱሳኑ ሁሉ ፊት ቃልኪዳን ገባሽ፣ ቃልኪዳንሽን ብትጠብቂ መላእክት ይደሰቱብሻል፣ ባትጠብቂ ግን አጋንንት ይዘባበቱብሻል…›› እያለ ብዙ መከራን በራሱ ላይ በማብዛት ሰባት ዓመት በዚያች ገዳም ኖረ፡፡ እህልም አይቀምስም ነበር ይልቁንም የሚሰጡትን እንጀራ ለሕጻናትና ለውሾች እየሰጠ አሠር ይመገብ ነበር፡፡

ዳግመኛም በሌላ ጊዜ ቅጠልን እየቀቀለ እስከ አምስት ቀን ከድኖ ያስቀምጠዋል፣ እስከሚተላም ድረስ ይጠብቀውና ያን ይመገባል፡፡ ኩስይ የምትባል ከሣር ሁሉ የምትመርን ሣር ምግቡ አደረገ፡፡ በኋላም አባቱም ልጁን ሳሙኤልን ተከትሎ ወደ እርሱ መጥቶ በአባ እጅ መነኮሰ፡፡ ለአባቱም መምህር ሆኖት እያገለገለው ያስተምረው ነበር፡፡ በሌላም ጊዜ 17 ዓመት ከተቀመጠባት ወይና በምትባል ቦታ ሲኖር ከውኃ በቀር ምንም ሳይቀምስ 12 ዓመት ተቀምጧል፡፡ ለ50 ዓመትም ያህል ሣር፣ ቅጠል፣ የዛፍ ሥርና ፍሬን እነዚህንና የመሳሰሉትን እየበላ ኖረ እንጂ እህል የሚባል አልበላም፡፡

ወጥቶም ወደ ዋሻ እየገባ ብዙ ጊዜ 40 ቀንና 40 ሌሊት በጾም በጸሎት እየኖረ እንቅልፍም እንዳያሸንፈው እስከሚነጋ ድረስ ሳይቆም ሳይተኛ እንደቆመ በጽኑ ተጋድሎ ተቀመጠ፡፡ ትልቅ ጉድጓድ ቆፍሮ በውስጡ እየገባ ሳይቀመጥ ሳይተኛ ሰውነቱ እንደ እንጨት እስኪደርቅ ድረስ በጾም በጸሎት በእጅጉ ይተጋ ነበር፣ በዚህም ወቅት ጌታችን ተገልጦለት ሰውነቱን በሙሉ ምራቁን ስለቀባለትና አውራ ጣቱን ስላጠባው ከዚህ ጊዜ በኋላ ርሀብና ጥሙ ጠፍቶለት ሰውነቱም ታድሶለታል፡፡ ዳግመኛም በአፉም ድንጋይ ጎርሶ፣ እግሩንም ታስሮና ማቅ ለብሶ ወደ ባሕር እየገባ ይጸልይ ነበር፡፡

አባታችን አባ ሳሙኤል በሕይወተ ሥጋ ሳለ እጅግ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን አድርጓል፡፡ እንደሙሴ ባሕርን የከፈለበት ጊዜ አለ፤ በልዑልም ዙፋን ፊት እየቀረበ ከቅዱሳን መላእክት ጋር የሚያመሰግንበት ጊዜ አለ፣ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይም ጋር ሆኖ የሚያጥንበት ጊዜ አለ፤ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም ሆኖ ከእነ ቅዱስ ጴጥሮስና ከሁሉ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ጋር በአንድ ላይ ማዕድ የሚቀርብበት ጊዜ አለ፤ በእጆቹ የያዛቸው መጻሕፍቶቹ ምንም ሳይርሱ ትልቅ ወንዝን በውስጡ እያቋረጠ የሚሻገርበት ጊዜ አለ፤ እመቤታችንንም ሲያመሰግናት ከምድር ወደ ላይ አንድ ክንድ ያህል ከፍ የሚልበት ጊዜ አለ፤ በቤትም ውስጥ ሆኖ ምስጋናዋን ሲጀምር የቤቱ መሠረት እየተናወጠ ዝናብ እንደያዘ ደመና ቤቱ ከምድር ከፍ ብሎ የሚቆምበት ጊዜ አለ፤ መንፈስ ቅዱስም በብርሃን ክንፍ እየወሰደው ወደተለያዩ ገዳማት ያደርሰውና ሥጋ ወደሙን እንዲቀበል ያደርገው ነበር፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልም የሁልጊዜ ጠባቂው ነውና በሁሉ ነገር ይራዳውና እንደ ጓደኛም ያማክረው ነበር፡፡ በአንዲት ዕለትም በጎዳና ሲጓዝ ወንዝ መልቶበት አገኘው፡፡ አባታችንም መጻሕፍቶቻቸውንና እሳት በእጃቸው እንደያዙ በወንዙ ውስጥ ለውስጥ ውኃውን አቋርጠው ሲሻገሩ መጻሕፍቶቻቸው አልራሱም በእጃቸው የነበረው እሳትም አልጠፋም ነበር፡፡

አባታችን ሊያስቀድሱ ወደ በተ መቅደስ በሚገቡ ጊዜ ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ ይወርድላቸው ነበር፡፡ የእመቤታችንንም ውዳሴዋን ሲደግሙ ክንድ ከስንዝር ያህል ከምድር ከፍ ይሉ ነበር፡፡ እመቤታችንም እየተገለጠች ንጹሕ ዕጣንንና የሚያበራ እንቁን ሰጥታቸዋለች፡፡

ቅዱስ አባታችን ለክቡር ሥጋ ወደሙ እጅግ ትልቅ ክብር አላቸው፡፡ በቤተክርስቲያን አስቀድሰው ሁሉም ሥጋ ወደሙን ተቀብለው ወደ ቤታቸው ሲወጡ ከአራቱ መነኮሳት ውስጥ አንዱ አስታወከ፣ በቤተክርስቲያንም ዳርቻ ተፋው፡፡ ያዩትም ሁሉ ደንግጠው ቆሙ፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ብፁዕ ሳሙኤል ግን ሁሉንም በአፉ ተቀበለው፣ በምላሱም መሬቱን ላሰው፡፡ ይህን ጊዜ ከሰማይም ‹ሳሙኤል ሳሙኤል› የሚልን ድምጽ ሰማና ወደላይ ባንጋጠጠ ጊዜ ሰባቱ ሰማያት ተከፍተው አየ፡፡ ከላይ ያለው ያ ቃልም መለሰ፡- ‹በሰው ፊት እንዳመሰገንኸኝና ፈጽሞም እንዳከበርከኝ የባልንጀራህን ትውኪያ ትቀበል ዘንድ እንዳላፈርህ እኔም እንዲሁ አከብርሃለሁ፤ በሰማያት ባለው በአባቴም ፊት በመላእክት ማኅበር አመሰግንሃለሁ› አለው፡፡›› ሌሎቹም ቅዱሳን እነ አቡነ ተክለሐዋርያትም እንዲሁ ለሥጋ ወደሙ ክብር ሲሉ የቆረበ ሰው ሲያስመልሰው የዚያን ሰው ትውኪያ ይጠጡት እንደነበር በቅዱስ ገድላቸው ላይ በሰፊው ተጠቅሷል፡፡ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን ለክርስቶስ ያላቸው ክብር እስከዚህ ድረስ ነው፡፡

አንድ ቀን አባታችን በገዳም ውስጥ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይጎበኘው ዘንድ ወደ እርሱ መጣ፡፡ ከእርሱም ጋር ተቀምጦ ‹ወዳጄ ሆይ! ሰላምታ ይገባሃል፡፡ አንተ ግን ከትንሽነትህ ጀምሮ አገለገልኸኝ፣ ምን አደርግልህ ዘንድ ትወዳለህ?› አለው፡፡ ትሑት ሳሙኤልም ‹የነፍሴ ወዳጅ ጌታዬና አለቃዬ ሆይ! መልካም ሀብት ሁሉ ከአንተ ዘንድ ነውና ምሕረትህንና ብሩህ ፊትህን ታሳየኝ ዘንድ እሻለሁ› አለ፡፡ ጌታችንም ‹አገልጋዬ ወዳጄ ሆይ! የፈለግኸውን እሰጥሃለሁ፣ ዳግመኛም ያልፈለግኸውንም እጨምርልሃለሁ› አለው፡፡ አባ ሳሙኤልም ‹ጌታዬ ሆይ! አንዲት ልመናን እለምንሃለሁ፤ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ኃጢአቴን አይ ዘንድ እወዳለሁ፡፡ የሌላውን ኃጢአት ግን አታሳየኝ› አለው፡፡

አባ ሳሙኤልን የዱር አራዊትም ሁሉ ይገዙለት ነበር፡፡ ታላቅ የሆነ ዘንዶ፣ ነብር፣ ጅብ፣ ቶራህ፣ ዝሆን፣ አንበሳና ሌሎችም የዱር አራዊት ሁሉ እየመጡ እግሩን እየላሱት ወደ ቦታቸው ይመለሱ ነበር፡፡ አንበሶቹንም እሾህም በወጋቸውና እግራቸው መግል በያዘ ጊዜ በመርፌ እያነቆረ ያድናቸው ነበር፡፡ ስንጥርም ሲወጋቸው ወደ እርሱ እየመጡ ያሳዩትና ያወጣላቸው ነበር፡፡ አንበሳም አጋዘንን ገድሎ ሲበላ ሲያየው ‹‹አንዴ ዞር በልልኝ ቆዳዋን ለልብሴ እፈልገዋለሁ›› ባለው ጊዜ ይለቅለት ነበር፡፡ እንዲሁም አንበሳው ለአባታችን ምግብም ትሆነው ዘንድ ጅግራን
እየያዘ በሕይወት ሳለች ያመጣለት ነበር፡፡ አባታችንም ከገዳም ወጥቶ መሄድ በፈለገ ጊዜ አንበሶችን እንደ ፈረስና በቅሎ ይጋልባቸዋል፣ መጻሕፍቶቹንም ይጭንባቸዋል፤ መንታ የወለደች አንበሳም ብትኖር ልጆቿን እየታቀፈ በየተራ ያጠባቸው ነበር፡፡

ወደ ደብረ ዋሊም በሄደ ጊዜ ጌታችን ተገልጦለት በዕለቱ የእመቤታችን በዓል ስለነበር እንዲቀድስ ነግሮት ከሰማይ ኅብስትና ጽዋ መጥቶለት ቅዱሳን ሐዋርያት በቀኝ በግራ እየተራዱት ሲቀድስ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ ኅብስቱንና ጽዋውን ጋርዶታል፡፡ ጌታችንም ቦታዋንና በዚያ ያሉትን መነኮሳት ሁሉ ልጆቹ ይሆኑ ዘንድ አስራት አድርጎ ሰጠው፡፡ ዋልድባ የተመሠረተው በቀደምት ጥንታዊያን አበው ቢሆንም አባ ሳሙኤል ሲገቡበት ምድረ በዳ ሆኖ ጠፍቶ ቋያ በቅሎበት የወባ ትንኞች መፈልፈያ ሆኖ ነበር፡፡ አባታችን ግን የተበታተኑትን መነኮሳት ሰብስበው ዋልድባን እንደገና አደራጅተውና አድሰው አቀኑት፡፡ የተባሕትዎ ኑሮንም አጠናከሩበትና ገዳሙን የመናንያን አበው መሰብሰቢያ አደረጉት፡፡ አባታችን ዋልድባን እንደ ሞሰብ አንስተው አስባርከዋታል፡፡

አባ ሳሙኤል ጊዜው ደርሶ ከማረፉ በፊት ቅዱስ ሚካኤል ነሐሴ 16 ቀን ወደ ገነት ነጥቆ ወስዶ ከዕረፍቱ በኋላ ከልጆቹ ጋር የሚኖርበትን ሥፍራ አሳይቶታል፡፡ በገነት ያሉ ቅዱሳንን ሁሉ ካሳየው በኋላ በእግዚአብሔርም ዙፋን ፊት ቀርቦ ምስጋናና ቃልኪዳንን ተቀብሎ ወደ በዓቱ ተመልሶ ታኅሣሥ 12 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፎ ነፍሱን ጌታችን በእጆቹ ተቀብሏታል፡፡

መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለአባ ሳሙኤል ዘዋልድባ የገባላቸው ልዩ ቃልኪዳን፡- ‹‹መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልም ወደ ገነት ነጥቆ ወስዶ በዚያ ያሉ ቅዱሳንን ሁሉ መኖሪያቸውንና ክብራቸውን አሳየኝ፡፡ ‹እነሆ የተጋድሎህን ሥራ ፈጽመሃልና አንተም ወደተዘጋጀችልህ ትመጣ ዘንድ ጊዜህ ቀርቧል› ብሎ ጌታዬ የሰጠኝን መኖሪያዬን አሳየኝ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ልዑል ዙፋን ወደ አርያም አደረሰኝ፡፡ በዚያም በክብሩ ዙፋን በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ተወዳጅ ወልድን አየሁት፡፡ በዚያም እመቤታችን ማርያምን ከተወዳጅ ልጁዋ ቀኝ አየኋት፡፡ የብዙ ብዙ ቅዱሳን መላእክትና ጻድቃን ሰማዕታት ሁሉ በየወገናቸው ‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ፍጹም አሸናፊ እግዚአብሔር የክብር ምስጋና ሰማያትንና ምድርን መላ› እያሉ በፊቱ ይዘምሩ ያመሰግኑ ነበር፡እኔም በአምላኬ ፊት ሰገድኩ፡፡ ተወዳጅ ወልድም ተናገረኝ፣ እንዲህም አለኝ፡- ‹ወዳጄ ሳሙኤል ሆይ! ሰላምታ ይገባሀል፣ ደስ ይበልህ፡፡ በጥቂቱ የታመንህ ባሪያዬ ሆይ በብዙ እሾምሃለሁ፡፡ እኔን በመውደድ ብዙ ደክመሃልና የመስቀሌንም መከራ በመሸከም እኔን መስለሃልና እኔም በመንግሥቴ መልካም የሆነውን የድካምህን ዋጋ እሰጥሃለሁ፡፡ እነሆ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የተካከለ መቀመጫህንና አክሊልህን አዘጋጀሁልህ፣ ዕድል ዕጣህም ከአሥራ ሁለቱ ቅዱሳን ሐዋርያቶቼ ጋር ነው፡፡ አፅምህ በተቀበረበት፣ የገድልህ መጽሐፍ በተነበበት፣ መታሰቢያህ በተደረገበት፣ ሥፍራ ሁሉ ምሕረትና ድኅነት ይሁን፡፡ በጸሎትህ የሚታመነውን፣ መታሰቢያህን የሚያደርገውን ሁሉ ለአንተ አሥራት ሰጥቼሃለሁ፡፡ ስለ እኔ የተቀበልከውን ድካም ሁሉ ዛሬ ያገኘኸውን የአንዲት ቀን የደስታ ልክ አይሆንም፡፡››

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አና ጻድቃን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥ እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12