ብራና ሚድያ - Birana Media
664 subscribers
1.66K photos
40 videos
4 files
572 links
+ የወጣቶች መንፈሳዊ ሕይወት
+ ገዳማትና ታሪካዊ ስፍራዎች
+ የቅዱሳን አበው መንፈሳዊ ተጋድሎና ታሪክ
+ እንዲሁም በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች የውይይት መድረክ በማዘጋጀት ወደ እናንተ ውድ ተከታታዮች መንፈሳዊ ይዘቱን ጠብቆ በየእለቱ ይቀርባል።
ቻናላችንን Subscribe በማድረግ ይቀላቀሉን።
https://www.youtube.com/c/BiranaMedia
ጥያቄ ካሎት በዚህ ይጻፉልን @birana259
Download Telegram
በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደረጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም እና የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ መምህር ዋሲሁን በላይ ዛሬ ሚያዚያ 24/2016 ዓ.ም ከመኖሪያ ቤታቸው በጸጥታ አካላት መወሰዳቸው ታውቋል።

የሁለቱ አገልጋዮች መኖሪያ ቤት መፈተሹም ተገልጿል።

በአሁኑ ሰዓት ሜክሲኮ ፌዴራል ፓሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ የሚገኙ ሲሆን የተያዙበት ምክንያት አልታወቀም።

ዝርዝር እንደደረሰን እናቀርባለን።
ዓርብ ስቅለት (የድኅነት ቀን)

እንኳን አደረሰን!

ዓርብ ስቅለት የዕዳ ደብዳቤያችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለመጨረሻ ጊዜ የተደመሰሰበት፤ ከአጋንንት አገዛዝ ነጻ የወጣንበት ዕለት ስለኾነ ‹የድኅነት ቀን› ይባላል፡፡ ጌታችን ከተያዘባት ሰዓት አንሥቶ አይሁድ ከቀያፋ ወደ ሐና፣ ከሐና ወደ ቀያፋ ሲያመላልሱት አደሩ፡፡ ሲነጋ ከቀያፋ ወደ ጲላጦስ አደባባይ አስረው ወሰዱት (ማቴ. ፳፯፥፩-፶፯)፡፡ አይሁድ ይህን አጥፍቶአል የሚሉት ነጥብ ሳይኖራቸው ነውና ጌታችንን ለፍርድ ያቀረቡት ጲላጦሰ እነርሱ ወደ ተሰባሰቡበት ቦታ ወጥቶ ‹‹ይህን ሰው ወደ እኔ ያመጣችሁበት በደል ምንድን ነው?›› ሲል በጠየቃቸው ጊዜ በቂ ምላሽ አላቀረቡም፡፡

‹‹ክፉ የሠራ ባይኾንስ ወደ አንተ ባላመጣነውም ነበር›› በሚል የሸፍጥ ቃል ሲያጕረመርሙ ጲላጦስ መልሶ ‹‹እኔ ምንም ጥፋት አላገኘሁበትም፤ እናንተወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት፤›› አላቸው፡፡ አይሁድም ኦሪት ‹‹ኢትቅትል ብእሴ ጻድቀ ወኀጥአ ኢታኅዩ፤ ጻድቅን ሰው አትግደል፤ ኀጥኡንም ከፍርድአታድን፤›› ትላለችና ‹‹እኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም፤›› ብለዋል (ዮሐ. ፲፰፥፳፰-፴፩)፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስ ‹‹በሕጋችን ጻድቀ ባሕርይክርስቶስን መግደል አይገባንም ሙሉ በሙሉ ጥፋተኞች ነን፤›› ሲያሰኛቸው ነው፡፡ በኋላም እርሱ ሞቶ ዓለም ይድን ዘንድ ወደ ምድር መጥቷልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ጥፋቱ ሞት ተፈረደበት፡፡ ስለዚህም ገርፈው ሰቀሉት፡፡

ጌታችን ሲሰቅልም የሚከተሉት ሰባት ተአምራት ተፈጽመዋል፤

፩. ፀሐይ ጨለመ፤

፪. ጨረቃ ደም ኾነ፤

፫. ከዋክብት ረገፉ፤

፬. የቤተ መቅደስ መጋረጃ ተቀደደ፤

፭. አለቶች ተፈረካከሱ፤

፮. መቃብራት ተከፈቱ፤

፯. ሙታን ተነሡ (ማቴ. ፳፯፥፶፩-፶፬)፡፡

ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ የሚከተሉትን ሰባት ዐበይት ቃላት አሰምቶ ተናግሯል፤

፩. ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ (አምላኪየ አምላኪየ ለምን ተውኸኝ?)››፤

፪. ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ››፤

፫. ‹‹አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው››፤

፬. እመቤታችንን ‹‹ሴትዮ ሆይ፣ እነሆ ልጅሽ››፤ ደቀ መዝሙሩንም ‹‹እናትህ እነኋት›› በማለት የቃል ኪዳን እናትነትና ልጅነት ማከናወኑ፤

፭. ‹‹አባት ሆይ በአንተ እጅ ነፍሴን አደራ እሰጣለሁ››

፮. ‹‹ተጠማሁ››፤

፯. ‹‹ዅሉ ተፈጸመ›› (ማቴ. ፳፯፥፵፭-፵፮፤ ሉቃ. ፳፫፥፵፫-፵፮፤ ዮሐ. ፲፱፥፲-፴)፡፡

ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ጨለማ ኾኖ ከቈየ በኋላ ከዘጠኝ እስከ ማታ እንደ ተለመደው ብርሃን ኾኖአል፡፡ ‹‹ወፍና ሠርክ ይበርህ ብርሃነ ፀሐይ›› እንዲል (ዘካ. ፲፬፥፯)፡፡ በዚህ ዕለት ሰባት መስተፃርራን (ጠበኞች) ታረቁ፤ ተስማሙ፡፡ እነዚህም፡- ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሕዝብና አሕዛብ፣ ነፍስና ሥጋ ናቸው (ኤፌ. ፪፥፲፤ ቈላ. ፩፥፳)፡፡ ጌታችን ጠዋት በሦስት ሰዓት ተገረፈ፤ በስድስት ሰዓት ተሰቀለ (ማቴ. ፳፯፥፩-፴፯፤ ሉቃ. ፳፫፥፩-፵፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፩)፡፡

በዘጠኝ ሰዓት ጌታችን በውኃው ተጠምቀን፣ ደሙን ተቀብለን የእግዚአብሔር ልጆች እንኾን ዘንድ ከቀኝ ጎድኑ ጥሩ ውኃ፣ ትኩስ ደም አፈሰሰልን (ዮሐ. ፲፱፥፴፬)፡፡ በዐሥራ አንድ ሰዓት ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል አውርደው ሽቶ እየረበረቡ በድርብ በፍታ ገንዘው ቀበሩት (ሉቃ. ፳፫፥፶-፶፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፴፰-፵፪)፡፡ ቅድስት ነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዳ ነፍሳትን ነጻ አወጣች (፩ኛ ጴጥ. ፫፥፲፱)፡፡ በዚህ ጊዜ በርሃነ መለኮቱ በሲኦል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር›› እየተባለ ይዘመራል፡፡ ከሆሣዕና አንሥቶ ተከልክሎ የነበረው ኑዛዜ ይናዘዛል፤ ጸሎተ ፍትሐት ይደረጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡
✥••┈┈┈••✞••┈┈┈••✥
ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን = በዓቢይ ሃይል ወሥልጣን
አሰሮ ለሰይጣን = አግአዞ ለአዳም
ሰላም = እምእዘየሰ
ኮነ = ፍሰሃ ወሰላም
+++
ክርስቶስ በታላቅ ሃይሉና ሥልጣኑ ከሙታን መካከል ተለይቶ ተነሳ፤
ሰይጠንን አሰረው፤ አዳምን ነፃ አወጣው፤
ከእንግዲህ ወዲህ ፍሰሃ፣ ሰላም፣ ደስታ ሆነ።
እንኳን ለጌታችንና መድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ ትንሣኤ በሰላምና በጤና አደረሰን: አደረሳችሁ። የሰላም የፍቅር የጤና በዓል ያድርግልን : አሜን።
ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ

ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ ባሉት ዕለታት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ሳምንቱ እሑድ ድረስ የሚገኙት ዕለታትም ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ ይጠራሉ፤ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ዕለተ ሰኞ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች፡፡ ይህቺውም ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ናት (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

ማክሰኞ

ይህቺ ዕለት፣ ለሐዋርያው ቶማስ መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቶማስ› ተብላ ትጠራለች፡፡ የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በመጣ ጊዜ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ እርሱ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

ረቡዕ

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀናት በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ናት፡፡ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡

ኀሙስ

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡

ዐርብ

የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ተብላ ትጠራለች፡፡ በቤተ ክርስቲያን ደግሞ ጌታችን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጕልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ጊዜ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችንን ከዅሉ ቀድሞ ለማየት ለበቁት ሴቶች መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

እሑድ ሰንበት

በዋናው ትንሣኤ ሳምንት የምትመጣዋ ዕለተ እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብላ ትዘከራለች፡፡ ከላይ እንደ ተጠቀሰው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት ‹‹በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግን ‹ሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም›› አለ፡፡

ስለዚህም የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው የወዳጆቹን የልብ ዐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡ ቶማስንም ‹‹ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤›› ብሎ አሳየው፡፡

እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ ‹‹ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ›› የክርስቶስን ትንሣኤ አመነ፡፡ የሳምንቷ ዕለተ ሰንበት፣ የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡
"#የትናንት ሊቃውንት አባቶቻችን ጦም እያደሩ  የጠበቋትን ቤተ ክርስቲያን እኛ እየበላን አሳልፈን መስጠት አይገባም"  ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ከ200 በላይ የአብነት መምህራን የተሳተፉበት የምክክር ጉባኤ በመንበረ ፓትርያርክ ጽርሐ ተዋሕዶ እየተካሔደ ይገኛል።

አዲስ አበባ (ግንቦት ፲፭/፳፻፲፮ ዓ/ም / ብራና ሚድያ )

በመንበረ ፓትርያርክ ትምህርትና ማሰልጠኛ መምሪያ ከሊቃውንት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው  ሀገር አቀፍ የምክክርና የውይይት ጉባኤ ማካሔዱን ጀምሯል።

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሕር ዳር ሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የበላይ ሊቀ ጳጳስ፣የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሐላፊዎች  ከየ አህጉረ ስብከቱ የመጡ ከ200 በላይ ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያንና የጉባኤ መምህራን  ተገኝተዋል።

ጉባኤው በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን በማስከተልም የደብረ ምሕረት ሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያምና ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ካቴድራል ሊቃውንት
"ያሬድ ካህኑ ለእግዚአብሔር
ትርድአነ ነዐ በህየ መካኑ ያሬድ ነዐ ትርድአነ" የሚለውን ወረብ አቅርበዋል።

የመምሪያው ሐላፊ  መልአከ መዊዕ ሳሙኤል እሸቱ ሊቃውንቱ ከየጉባኤ ቤቱ የመጡትን ሊቃውንት አስተዋውቀዋል።
በዚህም የድጓ፣ የዝማሬ መዋስዕት ፣ የቅኔ ፣የአቋቋም ፣ የሐዲሳትና የብሉያት  መጻሕፍት ትርጓሜ መምህራን መሆናቸው ተገልጿል።

መልአከ መዊዕ ሳሙኤል እሸቱ ለጉባኤ መሳካት የበኩሉን ድርሻ የተወጡትን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የትምህርትና ስልጠና ዋና ክፍልንና ሌሎችን አመስግነዋል።

አክለውም ጉባኤ  ሁልጊዜ በየዓመቱ ከግንቦቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ከመጀመሩ በፊት ጉባኤ እንዲዘጋጅና እውቅና እንዲሰጠው ጥያቄ አቅርበዋል።

የእንኳን ደህና መጣችሁ አባታዊ መልእክት ያስተላለፉት ብፁዕ አቡነ አብርሃም  ብዙ ኪሎ ሜትሮችን አልፈው ወቅታዊ የሀገሪቱ ሁኔታ ተቋቁመው   የተገኙትን ሊቃውንት እንኳን ደህና መጣችሁ ያሉ ሲሆን የምክክር ጉባኤውን  ያሰናደውን የትምህርት ማሰልጠኛ መምሪያ  አመስግነዋል።

ብፁዕነታቸው  አክለውም ለዘመናት የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ቤተ ክርስቲያናችንን በበላይነት በሚመሩበት ጊዜ  "አማኙን ከሀገሩ" "እምነቱን ከታሪኩ" ጠብቀው ያቆዩ ሊቃውንት መሆናቸውን በማስታወስ አሁንም የበኩላችሁን የሊቅነት ድርሻችሁን በመወጣት ቤተ ክርስቲያናችንን ልታስከብሩ ይገባል ብለዋል።

በዚህ ዘመን በሕይወት የሚያገለግሉትን ሊቃውንት በኑሯቸውም ልናስባቸውና የት አሉ ልንል ይገባልም ብለዋል።

"የትናንት ሊቃውንት አባቶቻችን ጦም እያደሩ  የጠበቋትን ቤተ ክርስቲያን እኛ እየበላን አሳልፈን መስጠት አይገባም" ሲሉ ገልጸዋል።

ስለሆነም ሊቅነትን ከቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ውጤት ጋር በማጣመር ዘመኑን የዋጀና ትውልዱን የሚያተርፍ  አገልግሎት እንድታገለግሉ ወደፊት መምጣት ይገባችኋል ብለዋል።
 
ጉባኤው ለሁለት ቀናት የሚቆይ እንደሆነ ከወጣው መርሐ ግብር ለማወቅ ተችሏል።
#Ethiopia 
#Birana_Media
#BM_Addia_Ababa

ብራና ሚዲያ
የኦርቶዶክሳዊያን ድምፅ

የዩቲዩብ ቻናላችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ
https://www.youtube.com/c/BiranaMedia

የቴሌ ግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ ፤ ፈጣን መረጃዎችን ያግኙ
https://t.me/birana3

በፌስቡክ ገጻችን ትምህርቶች እና ወቅታዊ መረጃዎችን ያግኙ
https://www.facebook.com/birana22

አጫጭር ትምህርታዊ እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት የቲክ ቶክ አማራጫችንን ይመልከቱ
https://www.tiktok.com/@birana16

የኢንስታግራም ገጻችንን
www.Instagram.com/birana96
መጋቤ ኅሩያን የማነብርሃን ጌታኹን
(የኔታ የማነብርሃን)

©️አለምነህ ዓይናለም

እውነትም ስም የሚስማማላቸው ኅሩይ ምርጥ መምህረ ቅዳሴ መምህረ ምግባር ወትሩፋት ናቸው። የማናይ ናቸው። የእኛን ድንቁርና ገፍፈው የሚጥሉ ብሩሃ አእምሮ የተሰጣቸው አሰላሳይ ዘመኑን የዋጁ የቤተ ክርስቲያናችን መምህር የኔታ የማነብርሃን።

ለአርብዓ ዓመት ያለመታከት በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም መደበኛ እና ኢመደበኛ ደቀ መዛሙርት የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን በተለይም ይህን ዘፈን ዘፈን የሚለውን ‘መዝሙር‘ ሰው እንዲለይ ከዜማ ሊቅነታቸው አንፃር እየተመለከቱ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማንቃት (በነገራችን ላይ የተሐድሶ ሤራን ቀድመው በመረዳት ቀዳሚ ጉባኤ በጽ/ጽዮን እና ጎላ ሚካኤል ሰ/ት/ቤት አዳራሽ እንደተጀመረ ነው የማውቀው 1997/98።) በማንቃት እና መድኃኒቱንም ጭምር በማዘጋጀት እጅግ ከፍተኛ ሚና የተወጡ የኔታችን ናቸው። የሊቀ ጉባኤ ጌታኹን ደምፀ Getahun Demtse Ayele ሚናቸው እጅግ ከፍተኛ ነው።

የግእዝ ሥርዓተ ንባብ በማስተማር በመጽሐፍ አሳትመው በማሰራጨት በድምፅ ወምስል ተሰጥኦዎችን ሰዓታትን ወዘተ ከቴክኖሎጂ ጋር የተፋለሙ ሰው በርህቀት እንዲማር ትጉ አባት።

የዜማ ምልክቶች በጽሑፍ ወደ ኮምፒዩተር ለማስገባት ሲያደርጉ የነበረው ጥረት: ሰው በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ይኖርበታል እንጂ ምንም ዓይነት ሰበብ ማቅረብ እንደሌለበት የሚመክሩት ቋሚ መጽኛችን የኔታ የማነብርሃን :ኅሩይ: ናቸው።

የኔታ የማነብርሃን እና ኮሜርስ ግቢ ጉባኤ የማይነጣጠሉ ናቸው። ዝማሜ በማጥናት መመረቅ: ከቅኔ ማኅሌት ያለውን ያሬዳዊ ውብ ዜማን በሰርግ መርሐ ግብር ላይ ለምእመናን ከታደሙበት ኹሉ በዝማሜ ወረብ ማጀብ እንዲቻል ማድረግ የየኔታ ውጤት ነው።

በማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ሕግን ሥርዓትን በማውጣት ዝማሬው ዝማሜው የየኔታ አሻራ ቀዳሚ ሳይሆን ይቀራል?

የሁላችን አባት የኔታ የማነብርሃን እንኳን ደስ ያለዎ። ረጅም ዕድሜ ከሙሉ ጤንነት ያድልዎ። ጸጋ በዲበ ጸጋ ያብዛልዎ።

ዘንድሮ የአብነት መምህራን ጉባኤ ላይ ከቅዱስ ፓትርያርካችን ለአርብዓ (40) ዓመታት ላገለገሉበት የቅዳሴ መምህርነት የዕውቅና ሰርተፊኬት በመሰጠትዎ እጅግ ደስስስ ብሎናል የኔታ።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዛሬ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፱፲ወ፮ ዓ/ም ባደረገው የጠዋቱ የግንቦት ርክበ ካህናት የቅዱስ  ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ሰባት አበው ሊቃነ ጳጳሳትን በመወያያ አጀንዳ አርቃቂነት ሰየመ።
በዚሁም መሰረት በመወያያ አጀንዳ አርቃቂነት የተሰየሙት ሰባት አበው ሊቃነ ጳጳሳት  ሕገ ቤተ ክርስቲያን በሚያዘው መሰረት ከቋሚ ሲኖዶስ ለምልአተ ጉባኤ እንዲቀርቡ የተመሩ እና ተጨማሪ የሚባሉ አጀንዳዎችን በመቅረጽ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የማስጸደቅ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል።
በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴነት የተመረጡት አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚከተሉት ናቸው።

1.ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ
2.ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ
3.ብፁዕ አቡነ ማርቆስ
4. ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ
5. ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል
6. ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ
7. ብፁዕ አቡነ ገብርኤል
የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የብፁዓን አባቶች የሀገረ ስብከት ዝውውር መደባ ላይ ውሳኔ አሳለፈ።

ግንቦት ፳፬/፳፻፲፮ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የብፁዓን አባቶች የሀገረ ስብከት ዝውውር መደባ ላይ ውሳኔ አሳለፈ።

የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ለኢኦተቤ ቴቪ (#EOTCTV) በላከው መረጃ ጉባኤው ከግቦት 21 ቀን 2016 ዓም ጀምሮ ባካሄደው ስብሰባ በበርካታ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን፡- በ4ኛ ቀን ውሎው የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትንና የጳጳሳትን ዝውውር ላይ ውሣኔ ማሳለፉን ገልጽዋል፡፡
በዚህም መሠረት፡-
1. ብፁዕ አቡነ አብርሃም፣ ከምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ወደ ኤድመንተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

2. ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ፣ ከኢትዮ ሶማሌ ሀገረ ስብከት ወደ የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

3. ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ዳውሮ ኮንታ ሀገረ ስብከትን እንደያዙ የከንባታ አላባ ጠምባሮ ሀገረ ስብከትን ፣

4. ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ከምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት ወደ የኢትዮ ሶማሌ ጅግጅጋ ሀገረ ስብከት ጳጳስ፣

5. ብፁዕ አቡነ ዳንኤል፣ ከምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ወደ የአፋር ሀገረ ስብከት ጳጳስ፣

6. ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ፣ ከሆሮ ጉድሩ ወለጋ ሀገረ ስብከት ወደ የምሥራቅ ጉራጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ፣

7. ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል፣ ሌሎች አህጉረ ስብከታቸውን እንደያዙ የምሥራቅ ወለጋ ፣ የምዕራብ ወለጋ እና የሆሮ ጉድሩ ወለጋ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ሆነው እንዲያገለግሉ መመደባቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ለኢኦተቤ ቴቪ በላከው መረጃ ገልጽዋል።
©EOTC TV

#ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን
በአማን ተንሥአ እሙታን

#የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ