አትሮኖስ
224K subscribers
104 photos
3 videos
41 files
304 links
╔╦╦╦═╦╗╔═╦═╦══╦═╗
║║║║╩╣╚╣═╣║║║║║╩╣
╚══╩═╩═╩═╩═╩╩╩
ግጥሞች አዳዲስና ቆየት ያሉ የታዋቂ ደራሲያን መፅሐፍቶችን በ PDF እንዲሁንም
ያልተነበቡ ድርሰቶችን ግጥሞችን ታሪኮችን ያገኙበታል።


Contact. @atronosebot
please dont touch the leave button.😔😳😳
Download Telegram
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_ስድስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ፔሩ/አማዞን ወንዝ
ዳግላስን ከኑሀሚ ነጥለው በአማዞን ወንዝ ላይ የተወሰነ ይዘውት ከተጓዙ በኋላ ሌላ እጅግ በጣም የተቀናጣ ግን ደግሞ መለስተኛ ዘመናዊ ጀልባ አጠገብ አቆሙና አሸጋገሩት፡፡ምንም እየገባው ነገር ባይኖርም ግን ደግሞ መከራከርና መጨቃጨቅ ባለመፈለጉ እንዳደረጉት እየሆነላቸው ነው፡፡ልክ ከትንሿ ጀልባ ወደቅንጡ ውሀና ዘመናዊው ጀልባ አሸጋግረውት ገና ወለሉ ላይ እንዳረፈ..አንድ ሀያዎቹ መጀመሪያ ላይ የምትገኝ ፤ደማቅ ጥቁር ፀጉሯ መቀመጫዋ ላይ የደረሰ ፤መልኳ ጉርድርድ ያለ ግን ደግሞ ሳቢ የሚባል የደም ግባት ያላት ሴት ከውስጥ ወጣችና ተንደርድራ መጥታ ተጠመጠመችበት፡፡ግራ ገባው፡፡ብዥም አለበት፡፡ይህችን ሰውነቱ ላይ ተጠምጥማ በእንባ በመታጀብ እየሳመችው ያለችውን ልጅ የሆነ ቦታ የሆነ ጊዜ ያውቃታል..አዎ በአእምሮ ብልጭ ድርግም እያለችበት ነው ..ግን የት እና እንዴት እንደሚያውቃት ምንም ትዝ ያለው ነገር የለም፡፡
‹‹ቤብ..ሰላም ነህ…?ወይኔ በኢየሱስ……ምንም አልሆንክም…?›› መላ እሱነቱን እየተሸከረከረች አያች  ግንባሩን ጉንጮቹን እጆቹን እያፈራረቀችና እያገለባበጠች ትሰመው ጀመር፡፡ በዙሪያቸው ያሉ ወጠምሻና አብረቅራቂ መሳሪያ የታጠቁ ሰዎች አንገታቸውን አቀርቅረው ዙሪያቸውን ከበው እየሆነ ያለውን በቆረጣ እየተመለከቱ ናቸው፡፡ልጅቷ እየጎተተች ወደውስጥ ይዛው ገባች ፡፡ደረጃውን እየወረዱ ወደውስጠኛው መኝታ ክፍል ይዛው ገባች፡፡ ሰፊውን ክፍል አልፋ አልጋ ወደ ተነጠፈበት መለሰተኛ ክፍል ይዛው ገባቸው፡፡ባለመሳሪያዎቹ ባሉበት በረንዳ እንደቀሩ ናቸው፡፡

ዳግላስ በገባበት የቅንጡ ጀልባዋ መኝታ ቤት ውስጥ የምታምር ድንብሽብሽ ያለች በግምት ሶስት ወይም አራት አመት የሚሆናት ጥቁር ሉጫ ፀጉሯ ግንባሯ ላይ ድፍት ብሎ ግማሽ ፊቷን የሸፈናት ልጅ ጭልጥ ያለ የሰላም እንቅልፍ ውስጥ ገብታለች፡፡ህፃኗን በትኩረት ሲያያት የሆነ ብዙ ቀለማቶች በአእምሮው ብልጭ ድርግም ብልጭ ድርግም እያሉ ይረብሹት ጀመረ፡፡በፀጥታ አልጋው ጠርዝ ላይ ተቀመጠና ቀኝ እጁን ወደ ልጅቷ ልኮ በቀስታ ግንባሯ ላይ የተደፋውን ፀጉሯን ከግንባሯ ላይ እያነሳ ትራሱ ላይ አስተኛው..እናትዬዋ ስሩ በፀጥታ ቆማ የሚያደርገውን እየተመለከተች ነው፡፡አሁን ሙሉ በሙሉ የልጅቷ ገፅታ ይታያል፡፡ይህቺ ልጅ ልብ ውስጥ ብቻ ሳይሆን ነፍሱ ውስጥም እንዳለች እርግጠኛ ነው፡፡ይሄንን የተረዳው ደመነፍሳዊ በሆነ ስሜቱ ነው፡፡በትክክለኛው ግን ምንም ትዝ እያለው ያለ ነገር የለም፡፡
አንገቱን ቀና አደረገና ጎኑ የቆመችውን አማላይ ሴት ተመለከታት‹‹የምታግዢኝ ነገር የለም?››ሲል ጠየቃት፡፡
የሚፈልገውን ሁሉ ለማድረግ ሙሉ ፍቃደኛ እንደሆነች በሚያረጋግጥ ንግግር ‹‹ምን ላድርግልህ የእኔ ፍቅር? የፈለከውን ጠይቀኝ››አለችው፡፡
‹‹አሞኛል ..በፊት የምወስዳው መድሀኒት ወይም ኪኒን ነገር ይኖራል?፡፡››
ደነገጠች….የእሷን   መደንገጥ  ተከትሎ  እሱም  ደነገጠምም  ግራ ተጋባምም‹‹ዛሬ መድሀኒትህን አልወሰድክም እንዴ?››ስትል ጠየቀችው፡፡
‹‹እስከማስታውሰው ድረስ ለበርካታ ቀናት ምንም አይነት መድሀኒት የወሰድኩ አይመስለኝም፡፡››
‹‹ይሄ የፓብሎ ተግባር ነበር፡፡ግን እሱ ራሱ የት እንደገባ ምንም የሚታያውቅ ነገር የለም፡፡ቆይ መጣሁ›› ብላ ሔደችና ከሁለት ደቂቃ በኃላ ሁለት ኪኒኒ ከእሽግ ውሀ ጋር ይዛ መጣች፡፡ኪኒኖቹን ከእሽጉ ፈልቅቃ አቀበለችው….‹‹ውሀውን ከፈተችና በል ዋጥና ለአንድ ሰዓት ያህል ጋደም በል… ስትነሳ ሰላም ትሆናለህ….››
‹‹አልገባሽም ..አመመኝ ስልሽ እኮ ህመም አይደለም..ምንም የማስታውሰው ነገር የለም እያልኩሽ ነው..አንቺን ጭምር ማንንም አላስታውስም››የተረዳችው ስላልመሰለው ፍርጥ አድርጎ እውነቱን ነገራት፡፡
‹‹ገባኝ የእኔ ፍቅር ..ሁሉ ነገር ይስተካከላል… ብቻ ያልኩህን አድርግ… መድሀኒቱን ዋጥና ከልጅህ ጎን ተኛ፡፡››እንዳለችው መድሀኒቱን ተቀበላትና ዋጠ፡፡ጫማውን አወለቀና ቀስ ብሎ አልጋው ላይ ወጣና ከልጁ ጎን ተኛ፡፡ፊት ለፊት ካለው የልብስ ማስቀመጫ ሳጥን ውስጥ አልጋ ልብስ አወጣችና አለበሰችው፡፡ ቀስ ብላ ክፍሉን ዘግታለት ወጣችና ከጠባቂዎቹ ራቅ ብላ የጀልባዋ በረንዳ ላይ ባላ ወንበር ተቀምጣ ከወንዙ ባሻገር ያለውን ጥቅጥቅ የአማዞን ደን በተመስጦ መመልከቷን ቀጠለች፡፡

ኑሀሚ ያለችበት ጎጆ የተወታተፈ በራፍ ሲከፈት ሰማችና የጨፈነ አይኗን ከፈተች፡፡ከአጋቾቾ መካከል አንዱ ነው፡፡፡አሁን እጆ ላይ ተጣብቆ ከወዲህ ወዲያ በተንቀሳቀሰች ቁጥር ቅጭልቅል እያለ የሚረብሻትን ሰንሰለት ተቆራኝቷት የነበረው ልጅ ነው፡፡በእጁ የሚበላ ነገር በሰሀን እና የሚጠጣ ውሀ በላስቲክ ኩባያ ይዞል፡፡ወደእሷ ተጠጋና በርከክ ብሎ ምግብን አስጠግቶ አስቀመጠላትና የስፓንሽ ቋንቋ ዘየ በተጫነው ግን ደግሞ ባልተደነቃቀፈ እንግሊዘኛ፡፡‹‹ተነሽ ይሄን ምግብ ብይ…ከጥቂት ጊዜ በኃላ በእግር ረጅም መንገድ መጓዛችንን ስለምንቀጥል ጥንካሬው ያስፈልግሻል፡፡››አላት፡፡
ጎኑ ላይ የያዘውን አብረቅራቂ ኮልት ሽጉጥ በጎሪጥ እየተመለከተች‹‹ወደየት ነው የምትወስዱኝ?››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹እሱን ለአንቺ ለመናገር ፍቃዱ የለኝም፡፡››ሲል መለሰላት፡፡

‹‹እባክህ…እህት የለህም..እኔ እኮ በጣም ከሩቅ አህጉር የመጣው ምስኪን ወጣት ነኝ…ምን ላደርግላችሁ ነው እንዲህ ከእኔ ጋር የምትሰቃዩት?››አሳዛኝ መስላ ለመቅረብ ሞከረች፡፡
‹‹እህት አለኝ ….ግን ላደርግልሽ የምችለው ነገር ቢኖር  አንድ ምክር ላንቺ መስጠት ብቻ ነው፡፡››

‹‹ምንድነው? እባክ ንገረኝ፡፡››

‹‹ፈፅሞ የሞኝ ስራ እንዳትሰሪ…››
ያልጠበቀችው የምክር አይነት ስለነበር‹‹ምን ማለት ነው?››በማለት ጠየቀችው፡፡

‹‹ጥዋት በምንጓዝበት ጊዜ በየመሀከሉ ሁኔታሽን ስከታተለው ነበር… ለማምለጥ ወይም ለመፋለም የመፈለግ አዝማሚያ አይቼብሻለው፡፡ በእርግጠኝነት ትንሽ እንቅስቃሴ ወይም ሙከራ ካደረግሽ ከመሀከላችን አንድ ወዲያው ነው የሚደፋሽ… እመኚኝ ሌሎቹ እንደእኔ ልስልስ እና ደካማ ነገር አይደሉም፡፡ከፍተኛ ወታደራዊ ስልጠና ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ ጭካኔም ያላቸውና ሰውን በመግደልና ድመት በመግደል መካለከል ምንም ልዩነት የማይታያቸው ገዳዬች ናቸው..እንደውም አጋነንከው ከላልሺኝ ለእነሱ ወሲብ ማድረግና ሰውን መግደል ተመሳሳይ አይነት እርካታ ነው የሚያጎናፅፋቸው፡፡››ሲል መስማት ከምትፈለገው ተቃራኒ የሆነ አስቀያሚ ዜና ነገራት፡፡

‹‹እና መጨረሻዬን ምንም ሳላውቅ ልክ እንደፋሲካ በግ ዝም ብዬ ልነዳ ?››

‹‹እኔ እንግዲህ እንደዛ የሚሻል ይመስለኛል፡፡በህይወት ነገ ተነገ ወዲያ ምን እንደሚከሰት አይታወቅም፡፡ነገ ይዛ የምትመጣውን እድል ለመጠበቅ ደግሞ ዛሬ በህይወት ቆይቶ ነገ ላይ መገኘት ያስፈልጋል፡፡በይ እንዳልኩሽ የቀረበልሽን ብይ…  የእግር ኮቴ እየተሰማኝ ነው፡፡
‹‹ልሂድ››ብሎ ቁጢጥ ካለበት ምንጭቅ ብሎ ተነሳና በራፉን ከፍቶ እንደአመጣጡ ተመልሶ ሄደ፡፡
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_ሰባት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ጥያቄዋ እሱን በጣም ነበረ ያሳቀቀው ፤ ወዲያው ነበር ከተቀመጠበት ተስፈንጥሮ በመነሳት ወደእሷ የተጠጋው፡፡ከዛ ከጎኗ ተቀመጠና ወደራሱ ስቦ አቀፋት..በዛ ልስልስና ጣፋጭ አንደበቱ‹‹እንደውም በጣም የምወድሽማ አሁን ነው፡፡በጣም እኮ ነው የምታሳዝኚኝ፡፡አንቺ ብቻ ነሽ እኮ ያለሺን፡፡እንዴት አንቺን ላለመወደድ እችላለሁ?ከአንቺ ውጭ እኮ ምንም ነገር የለኝም፡፡››ብሎ በመረረና በጠነከረ ንግግር ስለፍቅሩ ጥልቀት አስረዳት፡፡

በጣም ነበር ያሳዘናት‹‹አንተም እነአባቢን ተከትለህ ጥለኸኝ ሄደህ ቢሆን ኖሮ ምን እሆን ነበር….?››አለችው ፡፡ያንን ስትለው መላ ሰውነቷ በፍራቻ እየተንቀጠቀጠባት እንደነበረ ትዝ ይላታል፡፡ናኦል ከገቡበት ከጨላማ ውስጥ ከሚመዘዝ የትዝታ ጉዞ በከፊልም ቢሆን እንዲወጡ ፈለገና የጫወታቸውን ርዕስ ቀየረ፡፡‹‹በቃ አሁን ልደሽን እናክብር….››አላት

‹‹ልደቱ የእኔ ብቻ ነው እንዴ…?የሁለታችንም እኮ ነው፡፡››

‹‹ታውቂያለሽ እኔ ልደቴን ማክበር እንደማልወድ››

‹‹እንዳልክ እሺ… ግን መጀመሪያ የእኔን ሻማ እንለኩስና የእነአባቢን የሙት አመት መታሰቢያ እናክብር››ብላ መለሰችለት፡፡

እሱ  ግን‹‹አይ  ልደቱም  ሀዘኑም  የእኛው  አይደል  ..ሁለቱንም  ሻማዎች  አንድ  ላይ እንለኩሳቸው››አላት

አልተከራከረችውም‹‹ ክብሪቱን የት አደረከው?››
ከኪሱ ውስጥ ፈልጎ አወጣና ሰጣት ..ጫረችና የመጀመሪያውን የራሷን ሻማ በመለኮስ አባቷ መቃብር ላይ በማንጠባጠብ እረሱን ችሎ እንዲቆም አደረገች፡፡ከዛ ሌለናውን ሻማ ከወንድሟ እጅ ተቀበለችና ለኩሳ ወደግራዋ ዞራ እናቷ መቃብር ላይ በተመሳሳይ መልኩ አስቀመጠች፡፡በመቀጠል የራሷን የተቀዳደደ የጃኬት ኪስ ፈተሸችና ሁለት ብስኩት አወጣች፡፡ወደ ወንድሟ   በስስት   እያየች‹‹ወንድሜ   ለልደቴ   ሻማ   ስለለኮስክልኝ አመሰግናለው .. ለእንተም መልካም ልደት ይሁንልህ..ለእኔ ስትል አብረኸኝ ስለተወለድክ አመሰግናለው፡፡››አለችውና ከኪሷ ያወጣችውን ብስኩት  እጁ ላይ አደረገች፡፡
ትዝ ይላታል በጣም ነበር ደስ ያለው፡፡ያንን ብስኩት መያዟን አያውቅም ነበር፡፡ሳንቲሙን ከየት አግኝታ? መቼ ገዝታ? እንዴት ከእሱ ደብቃ ይዛ እንደመጣች አያውቅም፡፡እሱም ግን ሊያስደምማት ለሳምንት ሲያስብበት ነበረ፡፡እጁን ወደኪሱ ሰደደና አንድ ቸኮሌትና አንድ ጦር ማስቲካ በማውጣት .‹‹እህቴ እንኳን ተወለድሽ..ደግሞ ልደቱን የሚያከብር ሰው ስጦታ ይቀበላል እንጂ ስጦታ አይሰጥም›› ብሎ እጆ ላይ አስቀመጠላት፡፡

ኑሀሚ ቸኮሌትና መስቲካውን በጣም እንደምትወደው ያውቃል፡፡ ወላጆቻቸው በህይወት እያሉ እናትዬው የመስቲካ ሱሰኛ አባትዬው ደግሞ የቸኮሌት ሱሰኛ አድርገዋት ነበር፡፡ያኔ በሰላሙ ጊዜ በቀን ሁለቴ ወይም ሶስቴ ሰበብ እየፈጠረች ታለቅስ ነበር፡፡ለቅሶዋን ምታቆመው ደግሞ ወይ ቸኮሌት ወይም ደግሞ መስቲካ ሲሰጣት ብቻ ነበር፡፡ይሄም በደንብ ስለሚታወቅ ቀደም ተብሎ ይገዛና ተደብቆ ይቀመጥላታል፡፡ …..እና በወቅቱ የወንድሟ ስጦታ እናትና አባቷን በአንድ ላይ በጥልቀት እንድታስታውስ ነበር ያደረጋት፡፡ መልካቸው ብቻ ሳይሆን ጠረናቸውም ነበር ትዝ ያላት፡፡

‹‹ወንድሜ በጣም ነው ያስደሰትከኝ፡፡አንተ ስላለህልኝ በጣም እድለኛ ነኝ፡፡›› አለችው፡፡

‹‹እህቴ ስናድግ የቸኮሌት ፋብሪካ ይኖረኛል፡፡እና ያንን ፋብሪካ ላንቺ ስል ነው የምከፍተው፡፡ሁል ጊዜ የፈለግሽውን ያህል ቸኮሌት መብላት እንድትቺይ እፈልጋለሁ፡፡››ሲል ከጥልቅ ልቡ የመነጨውን ምኞቱን በፍቅር እና በስስት አይን አይኗን እያየ ነበር ቃል የገባላት፡፡ወደእዚህ አሁን ወዳለችበት ደቡብ አሜሪካ ከመምጣቷ በፊት ወንድሟ የዛን ጊዜ በልጅነታቸው ቃል የገባላትን ቸኮሌት ፋብሪካ ለመገንባት ማሽኑ የሚተከልበትን ዌርሀውስ ማስገንባት ጀምሮ ነበር፡፡ምን አልባት እስከአሁን አጠናቆትም ሊሆን ይችላል፡፡በጣም የሚያሳዝነውና መራሩ ሀቅ ግን ቸኮሌት ፋብሪካው ተተክሎ ማምረት ቢጀምር እንኳን እህቱን ማብላት አይችልም፡፡እህቱን በሰው ሀገር ምድር ላይ በሞት መነጠቋን ካወቀ ፋብሪካውን ያቃጥለዋል፡፡በዛ እርግጠኛ ነች፡፡
በወቅቱ በዛ የልጅነት ጊዜያቸው በወላጆቻቸው መቃብር ስር ስለቸኮሌት ፋብሪካው ቃል ሲገበላት‹‹ወንድሜ ቸኮሌት ፋብሪካ ለመክፈት እኮ ብዙ ብር ነው የሚያስፈልገው…ሀብታም መሆን አለብህ..ያ እንዴት ሊሆን ይችላል? ፡፡››ብላ ነበር የጠየቀችው፡፡
ወንድሟ እጆቹን ዘርግቶ ግራና ቀኝ ትከሻዋን በመያዝ ትኩር ብሎ አይኖቹን አይኖቾ ላይ ተክሎ‹‹አዎ ሀብታም መሆን አለብኝ፡፡እኔ ብቻ ሳልሆን አንቺም ሀብታም መሆን አለብሽ፡፡ለእኛ ሀብታም መሆን የግድ ነው፡፡እኔ ላንቺ ስል ሀብታምና ብዙ ብር ያለው ሰው መሆን እፈልጋለሁ፡፡አንቺም ለእኔ ስትይ እንደዛው ሀብታም መሆን አለብሽ፡፡››ነበር ያላት
‹‹እንዴት ግን..?ትምህርታችንን ከሶስተኛ ክፍል እንዳቋረጥን ነው፡፡ሳንማር እንዴት ነው ሀብታም ልንሆን የምንችለው?››
‹‹እንችላለን፡፡ማለቴ ሳይማሩ ሀብታም መሆን የሚቻል ይመስለኛል፡፡ያለበለዚያ ቡዙ የተማሩ ሆነው ምንም ብር የሌለቸውና አንዳንድ ያልተማሩ ሰዎች ደግሞ ሀብታሞች ሆነው አናገኝም ነበር፡፡አዎ እንዴት እንደሆነ ለጊዜው ባላውቅም ሳይማሩም ሀብታም መሆን እንደሚቻል እርግጠኛ ነኝ፡፡››አላት፡፡
አዎ..የወደፊት ህልማቸውን በተመለከተ ወንድሟ የሚያወራው ነገር በጣም መሳጭ እና አጓጊ ሆኖ ነበር ያገኘችው፡፡ቢሆንም ግን እንዴት ተግባራዊ ሊሆን እንደሚችል በወቅቱ ምንም  ፍንጭ  አልታያትም፡፡ግን  ደግሞ  የወንድሟን  ንግግር  የሞኝ  ቅዠት  አድርጋም አልወሰደችውም፡፡ ወንድሟን አይደለም በዛን ጊዜ አሁንም ታምነዋለች፡፡ከፍቅር የመነጨ እምነት፡፡

እርግጥ እሷም ከእሱ ጋር ተቀራራቢ የሆነ ሀሳብ ሁሌ በውስጧ ታሰላስል ነበር፡፡ስታድግ የተወለዱበትንና ያደጉበትን የወላጆቾን ቤት መልሳ መግዛት የዘወትር ምኞቷ ነበር፡፡አዎ በወቅቱ እቤቱን የአባታቸው የልብ ጓደኛው በነበረ ሰው ባለቤትነት ተይዟል፡፡ ወላጆቻቸው ሞተው ወር እንኳን ሳይሞላው ነበር ከመሟቱ በፊት ለስራ ብሎ ብዙ ሚሊዬን ብር ተበድሮኛል ብሎ የተናገረው፡፡ብዙም ሳይቆይ የተናገረውን የሚያረጋግጥለት ሰንድ አቀረበ፡፡ከዛ በቀላሉ በፍርድ ቤት ከሶ ወላጆቻቸው ሞተው በተቀበሩ በሶስተኛው ወር እቤቱን ተረክበ፡፡ለእነሱ ቀርቦ የሚከራከርላቸውም ሆነ ወስዶ የሚያሳድጋቸው አንድም ዘመድ መቅረብ ስላልቻለ …ሰውዬው ጎዳና ጣላቸው የሚለውን የሰው አፍ ብቻ በመፍራት ወስዶ ለማደጎ ቤት አስረከባቸው፡፡ኑሀሚ በዛ ጮርቃ እድሜዋ ላይ ሆና እንኳን ያ ሁሉ የተወሳሰበ ቲያትር መሰል አሻጥር ፈፅሞ አይዋጥላትም ነበር፡፡ያንን ቤት በጣም ትወደዋለች፡፡ልጅነቷ ያለው እዛ ቤት ውስጥ ነው፡፡ሳቅና ደስታዋ እዛ ቤት የሆነ ቁምሳጥን ወይም የኮመዲኖ ኪስ ውስጥ የተቆመለፈበት ነበር የሚመስላት፡፡እና አንድ ቀን ተሳክቶላት ያንን ቤት ማስመለስና የራሳቸው ማድረግ ብትችል እናትና አባቷንም በከፊልም ቢሆን ከሞት አለም ማስመለስ እንደሆነ አድርጋ ነበር የምትቆጥረው ፡፡ዘወትር ትንሽ በከፋት ቁጥር የሚተኙበትን መኝታ ቤት ትዝ ይላታል፤እናቷ ምግብ የምታበስልበት ኪችን ሙሉ ስዕሉ በአእምሮዋ ይመላለስባት ነበር፡፡አባቷ በእረፍት ቀኑ ቢጃማ ለብሶ በረንዳ ላይ ቁጭ ብሎ መፅሀፍ ሲያነብ …እሷ ድክ ድክ እያለች ከሳሎን መጥታ ታፋው ላይ በመቀመጥ ከኪሱ ስልኩን አውጥታ ጌም ስትጫወት….
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_ስምንት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ባለ ኮፍያ ጀኬት አወጣና ሰጣት፡፡በፈገግታ አመሰገነችውና እርምጃዋና ሳታቆም ለበሰች፡፡

ፊት ለፊታቸውም ያሉት እራቅ ብለዋል ኋላም ያሉት ቢያንስ በ20 እርምጃ ወደኃላ ቀርተዋል፡፡፡ስለዚህ በምቾት ታወራው ጀመረ፡፡

‹‹ቁራኛዬ..ስለመልካምነትህ አመሰግናለሁ››አለችው፡፡
‹‹ቁራኛዬ ማለት ምን ማለት ነው?››ጠየቃት፡፡
‹‹በሀገራችን የጥንት ጊዜ ቁራኛዬ የሚባል ባህላዊ የፍርድ ስርዓት ነበር፡፡ በዳይና ተበዳይ፤ሰራቂና ተሰራቂ ፤ገዳይና የተገደለበት ፍርድ የሚሰጥበት ቦታ እስኪደርሱ ድረስ እንዲህ እንደእኔና እንደአንተ በአካባቢው ሽማግሌ ሸማቸውን አንድ ላይ ይቋጥርሩትና እርስ በርስ አቆራኝተው ይልኳቸዋል፡፡በጉዞቸው ታዲያ አንድ ሌላውን በመንከባከብ..ከአደጋ በመጠበቅ ፍርድ እስከሚያገኙበት ቦታ ድረስ በሰላም የመድረስ ግዴታ አለባቸው፡፡ከዛ ተከራክረውና ማስረጃቸውና አቅርበው የተወሰነው ከተወሰነ በኃላ ነገሩ ይደመደማል ፡፡
‹‹የሚገርም ባህል ነው፡፡››
‹‹አዎ ነው..ለመሆኑ ትክክለኛ ስምህ ማን ነው?፡፡››
‹‹ካርሎስ››
‹‹የእኔ ኑሀሚ ነው ..ኢትዬጵያዊ ነኝ፡፡››
‹‹ኢትዬጵያ የት ነች..?ኢስያ አህጉር ውስጥ ነች?››
‹‹አይ አፍሪካ ነች….ምስራቅ አፍሪካ፡፡››
‹‹እ አዎ አስታወስኩ…ታዲያ እዚህ እንዴት ተገኘሽ?››
‹‹በናንተ ተጠለፍኩ እንጂ… የተባበሩት ድርጅት የተፈጥሮ ጥበቃ ፅ/ቤት ባዘጋጀው አለምአቀፍ ሴሚናር ላይ ለመካፈል ነበር አመጣጤ፡፡››
‹‹እ የተፈጥሮ ጥበቃ ላይ ነው የምትሰሪው?››በአድናቆት ጠየቃት፡፡
‹‹አዎ …ነበር፡፡››
‹‹እድለኛ ነሽ…የተፈጥሮ ጥበቃ ወታደር መሆን ከምንም በላይ የሚያኮራ ስራ ነው፡፡በአሁኑ ጊዜ የሰው ልጅ በከፍተኛ ትጋትና ጥረት ምድርን ለማውደም እየሰራ ነው….ያ በጣም አሳሳቢ እና አደገኛ ጉዳይ ነው..ግን ደግሞ ተስፋ እንዳንቆርጥ የሚያደርገን እንደአንቺ አይነት ጀግኖች ያንን ጥፋት ለማክሰም ሲለፉና ሲጥሩ ስለምናይ ነው፡፡ ››
እሷ ለተፈጥሮ ጥበቃና እንክብካቤ እሱ በሚያስበው ልክ ቁርጠኝነቱ ሆነ ፍላጎቱ እንደሌላት ብታውቅም ያንን በግልፅ ልትነግረው አልፈለገችም፡፡ስለእሷ አሁን እየተሰማው ባለው አድናቆትና ክብር እንዲቀጥል ፈልጋለች..ምን አልባት በሆነ አጋጣሚ ሊጠቅማት አንደሚችል አሰበች፡፡
‹‹ተፈጥሮ ላይ ያለህ ፍላጎት ጥልቅ ይመስላል?፡፡››

‹‹አዎ እዚህ በምታይው መልኩ ለመኖሬ ምክንያቴ ለተፈጥሮ ካለኝ ቀናኢነት የተነሳ ነው፡፡ከአማዞን ጫካም ሆነ ከአማዞን ወንዝ ፍቅር ይዞኛል፡፡ይሄው እዚህ ከገባሁ አምስት አመት አለፈኝ…በተቻለኝ አቅምና ዕውቀት የዚህ ደን ውስጠ ሚስጥሩን በርብሬ እያጠናሁ ነው፡፡እስከአሁን ሁለት መፅሀፍ አሳትሜያለሁ….አሁን ደግሞ ሶስተኛውን እየሰራው ነው፡፡››ብሎ አስደመማት፡፡
‹‹የእውነትህን ነው የምታወራኝ?››
‹‹አዎ እውነቴን ነው፡፡››
‹‹እስኪ ስለአማዞን ጥቂት ንገረኝ፡፡››አለችው
‹‹ምን ልንገርሽ…?››
‹‹ስለአጠቃላይና መሰረታዊ ነገሮች፡፡››
 
‹‹እሺ …አማዞን የአለማችን ትልቁ ደን ሲሆን 40 በመቶ በሚሆኑት የደቡብ አሜሪካ ሃገራት ላይ አርፏል፡፡ የአማዞን ጥቅጥቅ ደን 9 ሀገራት ላይ የረፈ በዓለም ላይ ትልቁ ሞቃታማ ደን ሲሆን የሚያካትታቸው ሀገሮችም ብራዚልን  60% ፣ ፔሩ  13% የደን ሽፋን ፣ ኮሎምቢያ 10% እና ቀሪው 17% ቬንዙዌላ ፣ ኢኳዶር ፣ ቦሊቪያ ፣ ጉያና ፣ ሱሪናሜ እና የፈረንሳይ ጓያና የአማዞን ደን የጋራ ባለቤቶች ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የአማዞን ስፋት የህንድን ሁለት እጥፍ ያክላል፡፡ያ ማለት አማዞን አንድ ላይ ተካሎ እራሱን የቻለ አንድ ሀገር ይሁን ቢባል ከ30ሚሊዮን በላይ ዜጎች ያሉት የአለማችን 9ኛው ትልቁ ሃገር ይሆን ነበር ማለት ነው፡፡››
‹‹ይገርማል፡፡››ብላ አድናቆቷን ገለፀችለት፡፡
በዛ ተበረታቶ ማብራሪያውን ቀጠለ‹‹ሌላው በአማዞን ደን ከ350 በላይ ነበር ጎሳዎች በውስጡ ተበታትነው ሲኖሩበት ከእነዛ ጎሳዎች መካከል ከ75 በላይ የሚሆኑት ጎሳዎች እርስ በእርስ ተገናኝተው የማያውቁ እራሳቸውን ከሌላው ማህበረሰብ፤ከመንግስትም ሆነ ከማንኛውም ቴክኖሎጂ ያራቁ ናቸው፡፡ ስለእንስሳቱ ንገረኝ ካልሺኝ ደግሞ አማዞን በአለማችን ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አጥቢ አንስሳት፤አዕዋፋት እና በደረት የሚሳቡ ፍጡራን የሚገኙበት ደን ነው፡፡በዛ ጥቅጥቅ ደን 400 ቢሊዮን ዛፎች፤40 ሺህ የእጽዋት እና 1300 የአዕዋፍ ዝርያዎች በውስጡ ይገኛሉ፡፡››
በገለፃው የእውነት ከልቧ ተደምማበት‹‹እውነትም ከዚህ ደን ጥልቅ የሆነ ፍቅር ይዞሀል››የሚል አስተያየት ሰጠችው፡፡
‹‹አዎ…በትክክል ገልጸሸዋል፡፡››

ንግግሩን ያቋረጠው ከኃላቸው የፉጨት ድምፅ ሲሰማ ነው፡፡ፈጠን አለና ክንዷን ጨምድዶ እየሄድበት ካለው ጠባብ መንገድ ዞር አድርጎ በመውሰድ አንድ ግዙፍ ዛፍ ጋር አጣብቋት በሰውነቱ ጋርዷትና ቆመ ፡፡እሷን በግንዱና በራስ መካከል አድርጎ ስላቆማት ትንፋሽ አጠራት፡፡ቢሆንም እንደምንም ችላው ‹‹ምን ተፈጥሮ ነው?››ስትል ጠየቀችው፡፡
በእጅ ላይ ያለውን ሽጉጥ እንዳቀባበለ ወደፊት ደቅኖ የሚሆነውን እየጠበቀ ነው….እጁን አፉ ላይ በመጫን ዝም እንድትልና ድምፅ እንዳታሰማ ጠየቃት ፡፡ወዲያው ሰቅጣጭ የሚያጎራ አይነት የሰው ድምፅ ተሰማ …እሱን ተከትሎ…ሶስት ተከታታይ ፉጨት ተሰማ፡፡
የሆነ አደጋ ተፈጥሮል፡፡እርዳታ እየጠየቁ ነው፡፡ከጀርባዬ ተከልለሽ በጥንቃቄ ተከተይኝ አለና ወደፊት መንቀሳቀስ ጀመረ…በአንድ እጇ ትከሻውን ይዛ ከወጋቧ ወደታች አጎንብሳ ልክ እንደእሱ እየተሹለከለከች ወደኃላ መጎዝ ጀመሩ፡፡ ከሶስት ደቂቃ በኃላ ተፈላጊው ቦታ ሲደርሱ የሚዘገንን ነገር ገጠማቸው…የሆነ ኩሬ መሳይ እረግረግ ቦታ ላይ ስድስት ሚሆኑት አጋቾቾ ክብ ሰርተው መሳሪያቸውን አቀባብለውና ደቅነው እንተኩስ አትኩሱ እየተባባሉ ይጨቃጨቃሉ፡፡መሀከል ላይ ያ ሲነሱ ከቤት ክንዷን ጨምድዶ ያወጣት አውሬ መሳየ ሰው ተዘርሯል፡፡ እሱ መሆኑን ያወቀችው በተንጨፈረረ ፀጉሩ እና በለበሰው ጃኬት ነው፡፡በሙሉ ሰውነቱ አንኮንዳ ዘንዶ ልክ እንደጥምዝ ቀለበት ተጠምጥሞበት ወደረግረጉ ጉድጓድ እያሰመጠው ነው፡፡እዲህ አይነት ነገር እንኳን በአካል በፊልም አንኳን አይታ አታውቅም፡፡ዝግንን አላት፡፡አረ በፈጣሪ የሆነ ነገር አድርጉና አድኑት››ጮኸች፡፡
ሁሉም ዞር ዞር እያሉ አዮት››መናገሯን እንጂ ምን እንዳለች የገባው የለም፡፡››ለካ ያወራችው በአማርኛ ነው፡፡ሁል ጊዜ ከልክ በላይ ስትደነግጥና ስትናደድ ከአማርኛ ቋንቋ ውጭ በአንደበቷ ለምን ሌላ ቋንቋ እንደማይገባ ሁሌ እንደገረማት ነው፡፡ትዝ ሲላት ወዲያው ስህተቷን አረመችና በእንግሊዘኛ ደገመችላቸው፡፡እነሱ በእስፓኒሽ ተነጋገሩና መተኮስ ጀመሩ …ደም እየተንኮለለ መፍሰስ ጀመረ ..የሰውዬው ይሁን የአናኮንዳው አላወቀችም፡፡ሁለቱም ኩሬ መሳይ እረግረግ ውሀ ውስጥ ሰመጡና ከእይታቸው ተሰወሩ፡፡ከተወሰነ ደቂቃዎች መደናገጥ እና ቁዘማ በኃላ ሁሉም እንደቀድሟቸው በሰልፍ ገብተው መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_ዘጠኝ


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ናኦል የእህቱን ድምፅ ከሰማ አራት ቀናት አልፎታል፡፡ይሄ ያልተለመደና ሊታሰብ የማይችል ነገር ነው፡፡እህቱ ቢዚ ብትሆን እንኳን አራት ቀን ሙሉ ቢያንስ ሚሴጅ ትልክለታለች ወይም ኢሜል ትልክለታለች እንጂ እንዲሁ ዝም ልትለው አትችልም፡፡እንዲህ አይነት ነገር አላስለመደችውም፡፡በተለይ የመጨረሻ ጊዜ ስትደውልለት በመጥፎ አየር ፀባይ ወደብራዚል መድረስ አቅቷቸው ያልሆነ ከተማ አርፋ አልጋ ክፍል ሆና ነበር የደወለችለት፡፡የአየር ፀባዩ ከተስተካከለ በማግስቱ ወደብራዚል በረራውን እንደምትቀጥልም ነግራው እሱም አምኗት ነበር፡፡በማግስቱ ትደውልልኛለች ብሎ ጠብቆ ነበር፡፡ማህበራዊ ሚዲያ ላይም ደጋግሞ ሊያገኛት ሞክሯል ፡፡፡ግን ምንም አይነት እንቀስቃሴ የለም፡፡ሚሲጅም ላከላት.. ኢሚልም ደጋግሞ ፃፈላት፡፡መልስ የለም፡፡መስራቤቷ ሄዶ አመለከተ..የሚያውቁት ነገር እንደሌለና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የተፈጥሮ ጥበቃ መስሪያ ቤት ጋር ተፃፅፈው የሚያገኙትን አዲስ መረጃ ከለ ወዲያውኑ እንደሚያሳውቁት ነገረው ሸኑት፡፡የሄደችበትን ድርጅት ድህረ-ገፅ ፈልጎ መረጃ ማሰስ ጀመረ…በአራተኛው ቀን ማታ እቤቱ ቁጭ ብሎ በትካዜ ላይ ሳለ ሰውነት የሚያርድ ልብ የሚያቆም ዜና ከድህረ ገፅ ላይ አነበበ፡፡
‹‹ለተግባራዊ ስልጠና ከፔሩ ወደብራዚል ስትሄድ በአየር ፀባይ መበላሸት ምክንያት ፔሩ ኢኩዩቶስ ከተማ አርፋ የነበረችው ኢትዬጴያዊቷ የተፈጥሮ ጥበቃ ባለሞያ ኑሀሚ በቀለ የገባችበት ጠፋ፡፡ወጣቷ የተፈጥሮ ጥበቃ ኢኬስፐርት አንድ ሆቴል ውስጥ ከአንድ ግለሰብ ጋር አብራ ያደረችና ጥዋትም በታክሲ ተሳፍራ ወደኤርፖርት ጉዞ እንደጀመረች ከሆቴሉ ሰራተኞች ማጣራት ቢቻልም ከዛ በኃላ ግን ኤርፖርት እንዳልደረሰች ታውቋል፡፡ምን አልባትም ወደሀገሯ መመለስ ስላልፈገች እራሷን ሰውራ ሊሆን እንደሚችል የአካባቢው ፖሊሶች ግምታቸውን የተናገሩ ሲሆን ፍለጋው ግን መቀጠሉን ታውቋል›› ይላል፡፡
ጮኸ…ኡ..ኡ ብሎ ጨኸ፡፡ግድግዳው ላይ የተንጠለጠለውን መስታወት በቦክስ ነረተው፡፡መስታወቱ ተፈረካክሶ ወለሉን ሞላው፡፡እጁን ሁለት ቦታ ሸረከተውና በደም ታጠበ…ሰራተኛዋ በርግጋ በውስጥ ልብሷ ብቻ መኝታዋን ለቃ መጥታ ፊቱ እስክትቆም ድርስ እራሱን እንደመሳት አድረጎት ነበር…በሶስት መቶ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ ቤታቸው የተኙ ጎሮቤቶች ከእንቅልፋቸው ባነው ግራ እስኪጋቡ ድረስ ነው የጮኸው፡፡
‹‹እህቴ የደሀዋ ኢትዬጵያ ዜጋ ልትሆን ትችላለች..ግን ደግሞ የእኔ እህት ነች…..እኔን ትታ ገነትም ቢሆን መቅረት አትፈልግም…እህቴ አንድ ነገር ሆናለች፡፡እህቴ ታፋናለች፡፡››
‹‹ምንድነው …..ምን ሆነህ ነው…..?ኑሀሚ ምን ሆነች?››ሰራተኛዋ ነች የምትጠይቀው፡፡
‹‹በሄደችበት ሀገር ጠፋች ነው የሚሉት..ሰው እንዴት ዝም ብሎ ይጠፋል….?እህቴን ወንጀለኞች አፍነዋት ነው፡፡››
ከእጁ እየተንጠባጠበ ያለውን ደም በጨርቅ እያሰረችለት‹‹ተረጋጋ እስኪ…የሰው ሀገር አይደለች ያለችው ..ምን አልባት መንገድ ጠፍቷት ያልሆነ ስፍራ ገብታ ያልሆኑ ሰዎች እጅ ወድቃ ሊሆን ይችላል ፡፡››ስትል
…ልታፅናናው ሞከረች፡፡
‹‹አንቺ ደግሞ ከፊቴ ጥፊ …መንገድ የሚጠፋት እንደአንቺ ደንባራ ነገር አደረግሻት እንዴ?፡፡›› አበሳጨችው፡፡
‹‹ያው ማንኛውም ሰው በሰው ሀገር ሲሆን መደናበሩ ይቀራል?››
ከተቀመጠበት ተነሳና ጀኬቱን ከሶፋው ላይ አነሳ …ወደመኝታ ቤቱ ሄደና የመሳቢያውን ኪስ ከፍቶ የሆነ ያህል ብር በማውጣት በኪሱ ጨመረ …ከሌለኛው መሳቢያ ሽጉጥ አወጣና በጀርባው ሽጦ ወጣ ፡፡ሰራተኛዋ ሳሎኑ መሀከል ተገትራ ግራ በመጋባት እየጠበቀችው ነበር፡፡ቀጥታ ወደሳሎኑ በራፍ ሄዶ መክፈት ጀመረ፡፡
‹‹እንዴ ብቻህን በውድቅት ለሊት ወዴት ነው…?በዛ ላይ ቆስለሀል…ልብስ ልልበስና አብሬህ ልምጣ›››አለችው፡፡
‹‹ወዴት ነው የምትመጪው?››
‹‹ወዴት ማለት ምን ማለት ነው…?ለእኔም እኮ እህቴ ነች …ልፈልጋት ነዋ፡፡››
‹‹አሀ ልትፈልጌት ..ደቡብ አሜሪካ?››
‹‹የትስ ቢሆን እንኳን ሰው ከብትም ጠፍቶ ዝም ተብሎ መቀመጥ ይቻላል እንዴ?፡፡››
እንግዲያው ደቡብ አሜሪካ ትንሽ እራቅ ስለሚል ወፈር ያለ ልብስ ልበሺ ደግሞም የእግር መንገድ ስላለው ደህና ጫማ አድርጊ››አላት፡፡
‹‹ደግ…መጣሁ ቆየኝ ››አለችና ተንደርድራ ወደመኝታ ቤቷ ሄደች፡፡ይንን ንግግር በሰላሙ ጊዜ ሰምቶት ቢሆን ኖሮ ሆዱን ይዞ እስኪያመው ይስቅ ነበር፡፡ዛሬ ግን አይችልም፡፡
‹‹አለማወቅ ደጉ ››አለና ሳሎኑን ከፍቶ ወጣና ዘግቶ ቀጥታ ወደውጨኛው የአጥር በራፍ ሔደ..ወለል አድርጎ ከፈተውና ፒካፕ መኪናውን አስነስቶ ግቢውንም አካባቢውን ለቆ ወጣ፡፡
አስራአምስት ደቂቃ ከነዳ በኃላ ስልኩን አንስቶ አንድ አእምሮ ውስጥ በስውር የተቀመጠ ቁጥር አስታወሰና‹‹አስቸኳይ›› ብሎ ፃፈበትና ላከው፡፡እዚህ ቁጥር ላይ ሲፅፍ ከሶስት አመት በኃላ ለመጀመሪያ ጊዜው ነው፡፡የሞትና የሽረት ጉዳይ ካልሆነ እንዳይደውል ተነግሮታል፡፡እና ሁል ጊዜ መደወል ወይም መልዕክት መላክ ይፈልግና ግን ደግሞ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ እንደቀልድ ችላ ማለት ስለማይችል ውጦ ስሜቱን ያዳፍነዋል፡፡ያም ቢሆን ግን ስለጤንነቷና ስለለችበት ሁኔታ በተዘዋዋሪም ቢሆን በየጊዜው ያረጋግጣል፡፡ ግን አሁን ጊዜው ደርሷል…ለእሱ ከእህቱ መጥፋት በበለጠ የህይወት እና የሞት ሽረት ጉዳይ የለም...ለዛ ነው ይሄን መልዕክት በድፍረት የላከላት፡፡
መልዕክቱ የተላከው ምስራቅ የምትባል በእሱም ሆነ በእህቱ ህይወት ላይ ከፍተኛ ድርሻ እና ተፅዕኖ ያላት የደህንነት ሰው ስልክ ላይ ነው፡፡አሁን ካጋጠመው ችግር መፍትሄ ልታስገኝለት የምትችል በምድር ላይ አንድ ትክክለኛ ሰው ብትኖር እሷ ነች፡፡እሷ ከሀገር ውስጥም ሆነ ከአለም አቀፍ የዲፕሎማሲው ማህብረሰብ ጋር ጥብቅ የሆነ ግንኙነት ስላላት የሆነ ነገር ልታደርግለት እንደምትችል እርግጠኛ ነው፡፡
ቀጥታ ወደ እስታዲዬም ነው የነዳው፡፡መስቀል አደባባይ ሲደርስ መኪናውን አቆመና ወደ መቀመጫወቹ በመሄድ ኩርምት ብሎ ተቀመጠ፡፡በዛ በውድቅት ለሊት በሰባት ሰዓት አልፎ አልፎ ውር ውር ከሚሉ መኪኖች ውጭ አካባቢው ጭር እንዳለ ነው፡፡ብርዱ ግን ያንሰፈስፋል፡፡የጃኬቱን ዚፕ አንሸራተተና ወደላይ ቆለፈው፡፡ይሄንን ብርድ እና ስቃይ ያውቀዋል ፡፡ሰውነቱ ውስጥ ብቻ ሳይሆን ነፍሱ ውስጥም ጭምር ነው ያለው፡፡ በርካታ አመታት በዛ በጮርቃ እድሜው ከአንዲቷና ከተወዳጅ እህቱ ጋር በረንዳ ኖሮ ያውቀዋል፡፡አሁን መልዕክት ልኮላት እስክትመልስለት ድንጋይ ላይ ቁጭ ብሎ በብርድ እየተጠበሰ የሚጠብቃት ልጅ ለመጀመሪያ ጊዜ እንዴት እንዳገኘቻቸው በትዝታ አመታትን ወደኃላ ተመልሷ ማመንዠግ ጀመረ ፡፡የ12 አመት ጮርቃ ታዳጊ እያሉ እንደተለመደው 22 በሚገኝ በረንዳቸው ላይ በተለመደው መልኩ ተኝተው ነበር፡፡ሰዓቱ ልክ አሁን ባለበት ተመሳሳይ ሰዓት ላይ ነው ፡፡ከለሊቱ ሰባት ሰዓት ፡፡እሱና እህቱ እርስ በርስ ተቃቅፈው አሮጌ ብርድልብስና ከላይ ጆንያ ደርበውበት ጋደም ብለው ወጪ ወራጁን በማየት ላይ ነበሩ፡፡
‹‹ምነው ወንድሜ እንቅልፍ እምቢ አለህ እንዴ?››ስትል ኑሀሚ ጠየቀችው፡፡
‹‹አዎ እህቴ…ያቺን ሴትዬ አየሻት?››
‹‹የቷን?››
‹‹ያቺ ከስልክ ፖሉ አጠገብ ያለችው ልጅ፡፡››
ከትከሻዋ ቀና አለችና አየቻት‹‹አዲሷን ልጅ እያልከኝ ነው?››
‹‹አዎ…አዲሷን ልጅ…፡፡››
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስር


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ከዛ በኃላ ኑሀሚ በመገረም እንደተዋጠች ፊቷን አዙራ ወደወንድሟ ነበር የተመለሰችው፡፡ እንደደረሰች ጆንያውንና አሮጌ ብርድልብሱን ገለጠችና ወንድሟ እቅፍ ውስጥ ገባች፡፡
‹‹ምነው አኮረፍሽ?››
‹‹አረ ይህቺ ደነዝ ነች…ጭራሽ ታሾፋለች፡፡››
‹‹ይገልሻል አላልሻትም?››
‹‹አይገባትም አልኩህ እኮ …የጨለለች ሳትሆን አትቀርም ፡፡››
ወዲያው ንግግራቸውን ሳያገባድዱ ነበር የቾንቤ ድምፅ የተሰማው .. እያጓራና እየለፈለፈ ወደእነሱ እየቀረበ ነበር…‹‹ተሸፋፈኚ ..ተሸፋፈኚ….››ናኦል እህቱን አስጠነቀቀ፡፡ሁለቱም ተሸፋፈኑና  አይኖቻቸውን  በብርድልብሱ  ቀዳዳ  አጨንቁረው  የሚሆነውን  ለመመልከት ዝግጁ ሆኑ፡፡እንደጠበቁት ቾንቤ እየለፈለፈና እየፎከረ ቀጥታ ወደልጅቷ ነበር የሄደው፡፡ዘና ብላ ከተቀመጠችበት ነቅነቅ ሳትል እየጠበቀችው ነበር፡፡
‹‹ወንድሜ አለቀላት..ስታሳዝን››ኑሀሚ በቀጣይ የሚሆነውን እየገመተች ተሸማቀቀች፡፡

ቾንቤ ደረሰባትና ዘፍ ብሎ ስሯ ቁጭ አለ፡፡ያ ሁሉ ሲሆን ከልጅቷ ምንም አይነት እንቅስቃሴ እየታያቸው አልነበረም ፡፡
‹‹ምንም እየተንቀሳቀሰች እኮ አይደለም፡፡››
‹‹አዎ መሞት እንደምትፈልግ ነግራኛለች…እንዲገድላት ነው የምትፈልገው፡፡›› ከልጅቷ ጋር ባደረገችው ንግግር የገባት የመሰላትን ለወንድሟ አብራራችለት፡፡
ቾምቤ ሲያቅፋት ተመለከቱ…ወደኃላ ሊያስተኛት እየሞከረ ነበር፡፡ከዛ እጇን አዙራ ስታቅፈው አዩ…..‹‹እንዴ ልጅቷ እራሷ መከካት ፈልጋለች መሰለኝ?›› ናኦል ነበር ተናጋሪው፡፡
ቀስ ብላ ወደኃላ አስተኛችውና እሷ ተነስታ ቆመች፡፡ከዛ ልብሷን ረገፍ ረገፍ አደረገችና ስሯ የነበረውን አንድ ጥቁር ፔስታል ይዛ ሁለት ሜትር ያህል ከእሱ ራቅ አለችና ተቀመጠች..ቾምቤ እንደተዘረረ ነው..እየተንቀሳቀሰ አይደለም፡፡››
‹‹ወይኔ አይንቀሳቀስም እኮ፡፡››
‹‹ምን አደረገችው?››
‹‹እኔ እንጃ…ሁለቱም ከተሸፋፈኑበት ገልጠው ወጡ፡፡አስር ደቂቃ ያህል ጠበቁ….፡፡ምንም የተለየ ነገር እየታያቸው አልነበረም…፡፡እንደውም ልጅቷ ከፔስታሏ ውስጥ ሻርፕ ነገር አውጥታ ፊቷን ተሸፋፈነችና ሸርተት ብላ ግንቡን ተደግፋ እንደመተኛት አለች፡፡
‹‹እንዴ ገደላት ስንል ገደለችው እንዴ….?››እሱ የለበሰውን ከላዩ ገፎ ተነሳ
‹‹ወዴት ነው?››ኑሀሚ ጠየቀችው፡፡
‹‹ …ሄጄ ላጣራ?›››

‹‹ቆይ አብረን እንሂድ ፡፡››አለችና እሷም ተነሳች፡፡ፈራ ተባ እያሉ ተጠጉ፡፡ ደረሱ…. ቾምቤ እጥፍጥፍ ብሎ እንደተኛ ነበር፡፡
‹‹እ ጩጬዎቹ ምንነው?››
‹‹ደየመብሽ እንዴ?››ናኦል ፈራ ተባ እያለ ጠየቃት፡፡
‹‹ጎንበስ ብለህ እየው…..እኔ እንዲተኛ ብቻ ነው ያደረኩት፡፡ሞቶም ከሆነ የእኔ የእጅ የለበትም፡፡››
‹‹ካራቲስት ነገር ነሽ እንዴ..?እንዴት አድርገሽ ቆለፍሽው?››
ናኦል ጎንበስ አለና ትንፋሹን አዳመጠው፡፡እውነትም አልሞተም፡፡ ትንፋሹ በደንብ ይሰማል፡፡
‹‹አይ ሰላም ነው፡፡››
‹‹ኑ እስቲ ከጎኔ ተቀመጡ፡፡››
ሁለቱ ታዳጊዎች እርስበርስ ተያዩ፡፡ የዚህችን እንግዳ ሴት ግብዣ እንቀበል ወይስ ይቅርብን ሚለውን በአይን እየተነጋገሩ ይመስል ነበር፡፡ከዛ እንደተግባባ ሰው ወደእሷ ቀረቡና እሱ በቀኟ እሷ ደግሞ በግራዋ በኩል ተቀመጡ፡፡
‹‹እዚህ ቆያችሁ…ማለቴ በርንዳ ላይ?››ጠየቀቻቸው፡፡
‹‹አዎ አንድ አመት ሊሞላን ነው፡፡››
‹‹ታዲያ አይተናኮሏችሁም…በተለይ አንቺን፡፡››
‹‹አይ እንደመጣን ሰሞን ያስቸግሩን ነበር..ግን እዛ ፖሊስ ጣቢያ የሚሰራ ፓሊስ አባታችንን በደንብ ያውቀው ነበር..እና እዚህ ሰፈር ላሉት ጉልቤዎች በጠቅላላ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷቸዋል፡፡አንድ ሰው እኛን ቢያጠቃ ሁሉንም እንደሚያጠፋችው ስለነገራቸው አይነኩንም፡፡››በሰላም እየኖሩ ያሉበትን ምክንያት በግልፅ አብራሩላት፡፡
‹‹ለጊዜው ጥሩ ነው..ግን እዚህ ጎዳና ላይ እስከኖራችሁ ድረስ በሌላ ሰው ላይ ተማምናችሁ እስከመጨረሻው  ከጥቃት  ተጠብቃችሁ  መኖር  አትችሉም፡፡ያላችሁት  ፖሊስ  አዛዥ የመንግስት ቅጥረኛ ነው፡፡መንግስት ደግሞ ነገ ተነስቶ ሌላ ወረዳ ወይም ሌላ ከተማ ሊመድበው ይችላል፡፡የዛን ጊዜስ ምን ትሆናላችሁ?››በውድቅት ለሊት ቀን እንኳን ቢሆን መመለስ ሚከብድ ጥያቄ ነበር የጠየቀቻቸው፡፡፡
‹‹እውነትሽን ነው..ይሄ ጉዳይ ሁሌ ያስጨንቀኛል….ለእኔ ሳይሆን ለእህቴ?››የሚል መልስ እንደሰጣት ያስታውሳል፡፡
‹‹እንዴ እንዲህ እንደምታስብ እኮ አንድም ቀን ነግረኸኝ አታውቅም…?›› ኑሀሚ በጭለማው ውስጥ አፈጠጠችበት፡፡
‹‹እንዴት እንዲህ ብዬሽ እንድትፈሪ አደርጋለሁ?››
ልጅቷ ቦርሳዋን በረበረችና ትንሽ የመጠጥ ብልቃጥ በማውጣት ክዳኑን አሽከርክራ ከፈተችና ተጎነጨችለትና መልሳ በመክደን ከፊት ለፊቷ አስቀመጠች፡፡
‹‹የት ነበርሽ..?ማለቴ እዚህ ሰፈር እንዴት ልትመጪ ቻልሽ?››
‹‹እንዲሁ በዚህ ሳልፍ ሰፈሩ ደስ አለኝና እዚሁ አረፍ አልኩ፡፡››
‹‹እና ነገ ትሄጂያለሽ ማለት ነው?››
‹‹እኔ እንጃ… ሂጂ ሂጂ ካለኝ እሄዳለሁ፡፡››
ናኦል‹‹ብትቆይ ግን ደስ ይለኛል፡፡›› አላት፡፡እንደዛ ያላት ልጅቷ በእድሜ በጣም ታላቁ ብትሆንም ገና እንዳያት በጣም ስለወደዳት ነበር…የዛን ጊዜ ስለእሷ የተሰማው ስሜት ዛሬም ድረስ በልቡ ላይ ተቋጥሮ እንደቆረቆረው ነው፡፡
ዞር ብላ አየችውና እጆቾን ዘርግታ ፀጉሩን እያሻሸች‹‹ጎረምሳው…ተከየፍክብኝ እንዴ?››ነበር ያለችው፡፡
እንደማፈር አለና …አቀርቅሮ ዝም አላት፡፡በወቅቱ ብዙ ነገር ሊመልስላት ፈልጎ ነበር፡፡ግን ከንፈሮቹ ተነቃንቀው ቃላት ከአንደበቱ ማውጣት አልቻሉም፡፡
‹‹አይዞኝ ስቀልድ ነው፡፡ለማንኛውም አሁን ሂዱና ተኙ፡፡.ነገ እናወራለን፡፡››
‹‹እሺ›› አሉና ሁላቱም ከግራና ከቀኞ ተነስተው ባዶ መሬት ላይ ዘና ብሎ በመዘረጋጋት ተኝቶ እያንኳራፋ ያለውን ቾንቤን በጎሪጥ እያዩ በስሩ አልፈው ወደመኝታቸው ሄዱ፡፡ኑሀሚና ናኦል ጥዋት ተነስተው አካባቢውን ሲቃኙ የለሊቷ ልጅ ተነስታ ልክ እንደደላው የቤት ልጅ ስፖርት እየሰራች ነበር ያገኞት፡፡…ሳንቾ በአካባቢው የለም፡፡ሌሎች ጓደኞቻቸው የተወሰኑት ተኝታዋል…የተቀሩትም ወደሚሄድበት ሄደዋል፡፡ለብሳው ያደሩትን አሮጌ ብርድልብስ እና ጆንያ ከስር የሚያነጥፉትን ካርቶን ስብስበውና አጣጥፈው ወደጥግ በማድረግ ዘወትር እንደሚያደርጉት በላዩ ላይ ድንጋይ ጭኑበት እና ወደልጅቷ ሄዱ ፡፡
‹‹እ ጩጬዎች ..ተነሳችሁ፡፡››በሚል ጥያቄ ነበር የተቀበለቻቸው፡፡
‹‹አዎ…ቡሌ ፍለጋ ልንሄድ ነው… ትመጪያለሽ?››
‹‹አዎ…››አለችና እስፖርቷን አቋርጣ ..ፔስታሏን ያዘችና ተከተለቻቸው፡፡
‹‹እ የት ነው ምንበላው?
ሁለቱም አፍጥጠው አዮት‹‹እንዴ ገና ሆቴል ሄደን ተመላሽ ጠይቀን ነዋ››ኑሀሚ ነበረች በመኮሳተር የመለሰችላት፡፡
‹‹አይ ብር አለኝ ..ለምን ገዝተን አንበላም…፡፡››
ሁለቱም በደስታ ፈገግ አሉ…‹‹ስንት አለሽ..?››ናኦል ነበር ጠያቂው፡፡
‹‹ጅንስ ሱሪ ኪሷ ውስጥ እጇን ሰደደችና ሁለት መቶ ብር መዛ አወጣች…››
‹‹አይበቃም…››
‹‹አረ ይበቃል..ነይ ዝናሽ ጋር እንሂድ፡፡››
‹‹ዝናሽ ማነች…?››
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስራ_አንድ


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ

አማዞን ደን ኮሎንቢያ ግዛት
ጫካውን እየሰነጠቁ ከአውሬውና ከነፋሳት ጋር እየተጋፉ መጓዝ በጀመሩ አራት ቀን ሆኗቸዋል፡
በጉዞቸው ከዛፍ ዛፍ ሲንጠለጠል አንድ ገራሚ እንስሳ አየች፡፡ትንሽ ነው፡፡ ድመት ነው የሚመስለው፡፡ ግን ጸጉር የለበሰ በመሆኑ ከመጠኑ ገዝፎ እንዲታይ እረድቶታል፡፡ ዝንጀሮም አንበሳም ይመስላል፡፡ከዚህ በፊት በምስል ላይ ፎቶውን እንኳን አይታ አታውቅም፡፡
‹‹ምንድነው ይሄ እንስሳት?››ቁራኛዋን ካርሎስን ጠየቀችው፡፡
‹‹እ ታማሪን ወይም ሮሳሊያ ይባላል፡፡ወይም በቀላሉ ወርቃማው አንበሳ ይሉታል፡፡››

‹‹አዎ እውነትም ወርቃማው አንበሳ፡፡ፀጉሩ እኮ ወርቅ መሳይና አብረቅራቂ ነው…ትክክለኛ ስሙ ይሄኛው ነው፡፡››
‹‹አዎ ዝርያው የዝንጀሮ ቢሆንም እንደምታይው ግን አንበሳ ነው የሚመስለው፡፡የዚህ ፕሪሜት ልዩ ቀለም ምናልባትም በጠንካራ የፀሐይ ብርሃን ጥምረት እና በአመጋገቡ ውስጥ በሚገኙ የካሮቲኖይዶች ብዛት ላይ የተመሠረተ ነው የሚል መላምት አለ።እንደምታይው አስደናቂ ገጽታ አለው: ወፍራም፤ ለስላሳ፤ ደማቅ ቀይ ፀጉር፤እንዲሁም ጥቁር ፊት እና ትልቅ ቡናማ አይኖች ያሉት አስደማሚ ፍጡር ነው››
‹‹ስላየሁት ደስ ብሎኛል፡፡የማልሞት ቢሆን ኖሮ እዚህ መጥቼ ስላየሁት እያንዳንዳንዱ ድንቅ እና አስደሳች ነገር… ስለእንስሳቱና ስለጥቅጥቁ ዳን… ስለሚንዠቀዠቀው የአማዞን ወንዝ ለወንድሜም ለጓደኞቼም በደስታ እንግራቸው ነበር..ግን ምን ዋጋ አለው….››ከገባችበት ጊዜያዊ የደስታ ስሜት ወጣችና ሀዘን ውስጥ ገባች፡፡
‹‹አይዞሽ …እሰክአሁን በህይወት አለሽ ..ለጊዜው ያ በቂ ነው፡፡››አላት፡፡

‹‹እንዳልክ ይሁንልህ››አለችውና ዝምታ ውስጥ ገባች፡፡
እኩለ ቀን ላይ ኣማዞን ወንዝን ታካ የተመሰረተች የደቡብ ኮለምቢያ የጠረፍ ከተማ ከሆነችውና 35 ሺ ኑዋሪዎች ከሚኖሩባት ላቲሲያ ከተማ ደረሱ፡፡ይህቺ ከታማ ሶስት ሀገሮች ማለት ፔሩ ኮሎቢያን ብራዚል የሚገናኙባት ነጥብ ከሆነችው ትሬስ ፎረንቴራስ ትንሽ ወደላይ ፈቅ ብላ ምትገኝ በዓሳ ምርቷ የታወቀች እጥር ምጥን ያለች ከተማ ነች፡፡የኮሎምቢያ መንግስት ግዙፍ የሆነ የዓሳ ምርቱን ከአካባቢው እየሰበሰበ በጀልባ በመጫን ወደ ማአከላዊ የሀገሪቱ ስፋራዎች የሚጫንባት ወሳኝ ከተማ ነች፡፡ከታማዋን በሩቅ ሲያዮት እና ጉዞቸውንም በዛ አቅጣጫ ሲያቀና ቀጥታ ወደከታማው ዘልቀው ሚገቡ መስሏት ተደስታ ነበር፡፡የዛም ምክንያቱ ህዝብ ያለበትና የመንግስት ተቋማት ሚንቀሳቀሱበት ስፍራ ላይ ከደረሰች በተቻላት መጠን ለማምለጠ ትሞክራለች፤ያ ከሆነ ደግሞ ጥረቷ የመሳካት እድሉ ከፍተኛ እንደሆነ ስሌቱን ስለሰራች ነው፡፡ይሁን እንጂ አጋቾቻ
የገመተቻቸውን ያህል ጥንቃቄ አልባ አልነበሩም፤በዛም ምክንያት ወደከታማዋ አልገቡም፡፡ይልቅስ ከተማዋን በቅርብ ርቀት ታካ አማዞን ጉያ ውስጥ ተወሽቃ ከምትገኝ ነባር ጎሳዎች ወደሚኖሩባት ወደአንድ መንደር ነው ጎራ ያሉት፡፡

‹‹እርግጠኛ ነኝ ይሄ የመጨረሻ የጉዞ መዳረሻችን ነው፡፡››ካርሎስን ነው የምትጠይቀው፡፡
‹‹አይመስለኝም..ግን የተወሰኑ ቀናትን እዚህ የምናርፍ ይመስለኛል››ሲል መለሰላት፡፡
‹‹በሩቅ ወደምትታየው ከተማ ምንገባ መስሎኝ ነበር››
‹‹እ..ወደ ላቲሲያ ማለትሽ ነው..ወደእዛ አለመግባታችን ጥሩ ነው…ለአንቺ ምንም ሚጠቅም ነገር አይገኝበትም…ከኑዋሪዎቹ ከግማሽ በላይ የእኛ ሰውዬ ሰዎች ናቸው››

ተስፋ ቆረጠችና… ዝም አለች፡፡..የቡድኑ ሰዎችን ለመቀበል ሶስት የሆኑ የመንደሩ ሰዎች መጡና አወሯቸው፡፡ ከተወሰኑት ጋር የሞቀ ሰላምታ ተለዋወጡ፡፡ አንድ ወለሉ በአየር ላይ የተንጠለለ በስሩ ውሀ የሞላበት በጣውላ እርብራብ የተሰራ የሳር ክዳን ቤት ከፊት ለፊታቸው ይታያል፡፡ወደዛው መጓዝ ጀመሩ፡፡ቤቱ ሰፋ ያለ ግን ደግሞ እቃ አልባ ነበር፡፡ቁራኛዋ ሰንሰለቱን ከላዩ ላይ አላቀቀና ለብቻዋ ተወላት፡፡ሁሉም በተርታ መቀመጫ ይዘው ተቀመጡ…ምግብ ቀረበላቸው፡፡ ሁሉም ተርበው ስለነበር የምግብ አይነቱ ሳያስጨንቃቸው በፍቅር በሉ ፡፡የሚጠጣ ነገር ቀረበላቸው…ጠንከር ያለ የአልኮል መጠጥ ነው፡፡እሷ መጠጣት አልፈቀደችም፡፡፡ውሀ ቀረበላት፤እሱን ጠጣች፡፡የምግብ ስርአቱ ካለቀ በኃላ እሷን እዛው ቤት ውስጥ ተዋትና ከውጭ ቆልፈውባት ወጥተው ሄዱ፡፡

ቤቱን ክፍት ትተውት ቢሄዱም ወደምትሄድበት ቦታ የላትም፡፡መቼስ በቃ ተመልሰሽ ሂጂ ቢሏት እንኳን የአራት ቀን መንገድ በእንደዛ አይነት ጥቅጥቅ የአማዞን ደን ከጇጓርና ከአናኮንዳ ጋር እየታገለች…አረንጎዴ መርዛማ እንቁራሪቶችና ሰውነት ላይ ከተጣበቁ ማይላቀቁ ጉንዳኖችን ተቋቁማ ወደኃላ ተመልሳ ፔሩ ገባለው የሚል ግምት የላትም፡፡እርግጥ ወደፊት ቀጥላ በአምስት ኪሎ ሜትር እርቀት ላይ ከምትታየው ላቲሲያ ከተማ ልትሄድ ትችላለች፡፡ግን ሙሉ ከተማው የራሳቸው የጋንግስተሮቹ ግዛት እንደሆነ ካርሎስ በግልፅ ነግሯታል...ምክሩን ችላ ብላ ብትሄድና ምንም አይነት የመንግስት ተቋም ሆነ የሚታደጋት ተቋም በቦታው ባይኖርስ…?፡፡ጠቅለል አድርጋ ስታስበው ከዚህ አሁን ካለችበት ስፍራ አምልጦ ነፃ መውጣት የማይተገበር ምኞት ሆኖ ነው ያገኘችው፡፡
ደክሞት ስለነበረ እቤቱ ውስጥ ያለች አንድ መተኛ ፍራሽ ነገር ላይ ሄዳ ጋደም አለች፡፡፡ሰውነቷን በቀላሉ እንዳሳረፈችው አእምሮዋን ልታሳርፍ አልቻለችም፡፡ በእነዚህ ሰዎች እጅ ከገባች ቀን ጀምሮ እንዲህ ለብቻዋ በመሆን ጥቂት ሳዕታትን ባገኘች ቁጥር ወዲያውኑ ሀሳቧ በሮ ወንድሟ ጋ ነው የሚሄደው፡፡የትናንት ትዝታዋ ጋር ነው የሚለጠፈው፡፡ናኦል ይሄኔ ለአራት ቀን ድምፆ ሲጠፈበት እና ስልኳም አልሰራ ሲለው የሚያደርገው ጠፍቶት መስሪያ ቤቷ ሄዶ እህቴን ውለዱ እያለ እያስጨነቃቸው አንደሚሆን ገመተች..ብቻ በዛ ችኩል ባህሪው የሆነ ሰውን ውለዷት ብሎ አፍንጫ እንዳይሰብር ነው የሰጋችው፡፡ምን አልባትም ምስራቅ ጋር ሊሄድ እንደሚችል ገመተች፡፡እንዲህ አይነት ጭንቅ ውስጥ ሲገባ ከምስራቅ ቀድሞ ወደአእምሮ የሚመጣ ሌላ የተሻለ የሚቀርባቸውና የሚረዳቸው ሰው እንደሌለ ታውቃለች፡፡እሷም በእሱ ቦታ ብትሆን እንደዛ ነው የምታደርገው፡፡

ከምስራቅ ጋር በወዳጅነት መቀራረብ ብቻ ሳይሆን የስራ ባለደረባም ሆነው እንደሀለቃና ምንዝር ለረጅም አመት ሰርተዋል፡፡ለዛውም በሀገሪቱ የደህንነት መስሪያ ቤት፡፡እርግጥ እሷም ሆነች ወንድሟ ቀጥታ የደህንነት መስሪያ ቤቱ ተወዳድረው አይደለም የተቀጠሩት፡፡በወቅቱ ለእዛ የሚያበቃ እድሜ ላይም ሆነ ሁኔታ ላይ አልነበሩም፡፡ ..የእዛ መስሪያ ቤት አባል የሆኑት በእሷ በኩል ተመልምለው ..በእሷ ጥረት ወደስልጠና እንዲገቡ ተደርገው…በእሷ በኩል ተልዕኮ እየተሰጣቸው ነው፡፡ከዛ ብዙ ብዙ የሚባል ተልዕኮዎችን ተወጥተዋል…ለሀገር የሚጠቅሙ አንዳንዴም የተሳሳቱ ሰራዎችን ሰርተዋል፡፡ ያኔ እዛ በረንዳ ላይ ረዳት አልባ በነበሩበት ጊዜ ካገኘቻቸው በኋላ እንዴት እንደመለመለቻቸው ትዝ አላት፡፡
ኢትዬጵያ/አዲስ አበባ
አንድ ቀን አስራሁለተኛ አመታቸው ላይ ከምስራቅ ጋር በተዋወቁ በሁለተኛው ቀን በየእለቱ ለደምበኞች ጫት የማመላለስ ስራ ሰርተው ከጨረሱ በኃላ ምስራቅ እመጣለሁ ብላቸው ስለነበረች ቦታቸው ላይ ቁጭ ብለው እየጠበቋት ነበር፡፡ዘጠኝ ሰዓት ተኩል ላይ ምስራቅ እንዳለችው መጣች፡፡ ከመቀመጫቸው ተነስተው በፈገግታ ተቀበሏት፡፡ይዛ የሄደችው አንድ ፔስታል ቢሆንም አሁን ግን ሌላ አንድ ጥብሰቅ ያለ እቃ የታጨቀበት ፔስታል ይዛ መጥታለች፡፡
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስራ_ሁለት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ

ፔሩ/አማዞን ወንዝ ላይ

ዳግላስ ሚስቱ የሰጠችውን መድሀኒት ወስዶ ከተኛ ከሁለት ሰዓት በኃላ ነቃ፡፡አይኑን ሲገልጥ የቅንጡ ጀልባዋ መኝታ ቤት ውስጥ ብቻዋን ነው ያለው፡፡ ከነቃም በኃላ አይኑን ብቻ ገልጦ ዙሪያ ገባውን እየቃኘ ባለበት ሆኖ 15 ደቂቃ አሳለፈ፡፡፡ከዛ ተነሳና በራፉን ከፍቶ ‹‹ማሪያ…ማሪያ እያ ተጣራ››ስሙ ሳያስበው ነው አፉ ውስጥ የገባለት፡፡ ሚስቱ ተንደርድራ መጣችን ፊቱ ቆመች፡፡ ወደራሱ ጎትቶ አቀፋትና ደረቱ ላይ ለጥፎ ከንፈሯን ለረጅም ደቂቃ መጠጣት፡፡እሷም እጆቾን ዘርግታ በአንገቷ ዙሪያ አሽከርክራ አቀፈችውና እላዩ ላይ ተንጠለጠለችበት፡፡
‹‹ማሪያ የእኔ ውድ ..አንጀሊናስ?››
‹‹ከእነ ሳንዲያጎ ጋር ነች፡፡እጇን ይዞ እየጎተተ ወደጀልባዋ በረንዳ ወጣ፡፡ሲደርስ እስከ አፍንጫቸው የታጠቁ አስፈሪ ጠባቂዎች ከየተቀመጡበት በድንጋጤ ተነሱና ቀጥ ብለው ቆሙ….አንጀሊና አባቷን ስታይ ወደእሱ ተንደረደረች…በአየር ላይ ቀለባትና ግራና ቀኝ ክንዶን ይዞ አሽከረከራት፡፡ መርከቡ ላይ ያሉት ሁሉ ደስ አላቸው፡፡አሁን እራሱን ዳግላስን ሆኖል ማለት ነው፡፡ከልጁ ና ከሚስቱ ጋር ሀያ ለሚሆኑ ደቂቃዎች በማሳለፍ በመጠኑ ናፍቆቱን ከተወጣ በኃላ እነሱን ወደውስጥ ገብተው እንዲጠብቁት አዞ …ቀጥታ መርከቡ ላይ ካሉት 5 ታጣቂዎች ጋር ስብሰባ ተቀመጠ፡፡
‹‹እሺ እየሰማዋችሁ ነው፡፡››
የታጣቂዎች ሀለቃ የሚመስለው ግዝፍ ሰው አንገቱን እንደደፋ መናገር ጀመረ‹‹ሀለቃ በተፈጠረው ነገር በጣም እናዝናለን፡፡በእውነቱ ችግሩ እንደተፈጠረ ስንሰማ ወዲያው ነበር እርምጃ የወሰድነው››
‹‹እኮ ምን አደረጋችሁ?››
‹‹ያው ብራዚሊያ አየር ማረፊያ ገብታችሁ ነበር… አንተ ወደፕሌኑ ማለፍ ብትችልም አብሮህ የነበረው ፓብሎ ግን በፖሊስ እጅ ወደቀ፡፡አንተን ማሳለፍ ቢችልም እሱ እራሱን ግን ከፖሊሶች እጅ ማስመለጥ አልቻለም፡፡እና ምንም ልንረዳው ባለመቻላችን…ጠበቀ ያለ ምርመራ ሲደረግበት ስለአንተ የሆነ ሚስጥር ሊያወጣ ይችላል ብለን ስለሰጋን እዛው የገባበት እስር ቤት እርምጃ እንዲወሰድበት አድርገናል፡፡
አንተን ወደ ብራዚሊያ ይዛ የሚበረው አውሮፕላን በአየር ፀባይ ምክንያት ኢኩዩቶስ እንደረፈ ስንሰማ እኔ እራሴ ነኝ አንድ ቡድን እየመራሁ በቻርተር አውሮፕላን ወደዛ ያመራሁት፡፡ከዛ ምን አልባት የመንግስት ሰዎች ሆኑ የሲ.አይ.ኤ ሰዎች እጅ እንዳትገባ ተጠንቅቀን ከሆቴል ስትወጣ አፈነንህ ከኢኩዬቶስ አስወጣንህ፡፡
‹‹ጥሩ ስራ ነው….እርግጠኛ ነኝ ምንም ያዝረከረካችሁት ነገር የለም፡፡››
‹‹አረ የለም..ሁሉን ነገር በጥንቃቄ ነው የተከወነው…ግን….››
‹‹‹ግን ምን?››
‹‹አንድ የአንተን ውሳኔ የሚጠብቅ ጉዳይ አለን፡፡››

‹‹ምንድ ነው?››
‹‹ልጅቷን ምን እናድረጋት …?ምን አልባት የምትለው ነገር ይኖራል ብለን..ወደ ዋናው ሳንቺዋሪ እየወሰድናት ነው፡፡አሁን ላቲሲያ ደርሰዋል፡፡ለሁለት ቀን እዛ ቆይተው…ወደሳንቹዋሪ ይዘዋት ይመጣሉ፡፡
‹‹ምንድነው የምታወራው ..?የቷ ልጅ?››
ሰውዬው አንዴ ዳግላስን አንዴ ደግሞ ወደመርከቡ የውስጠኛ በራፍ እያየ ለመናገር ጊዜ ወሰደ‹‹እየጠየቅኩህ እኮ ነው..የምን ልጅ?››
ድምፁን ቀነሰና …‹‹ሆቴል ስናገኝህ ከሆነች አፍሪካዊት ልጅ ጋር ነበርክ….፡፡ ከኤርፖርት አብራችሁ ወጥታችሁ ሆቴልም አንድ ክፍል ነው ያደራችሁት፡፡››ለምን ድምፁ ቀንሶ እንደሚያወራ አሁን ገባው፡፡ከሴት ጋር አንድ ክፍል ውስጥ ማደሩን ሚስቱ ሰምታ ግርግር እንዳትፈጥር ነው፡፡አሱ ግን ያ ብዙ አላስጨነቀውም፡፡
‹‹እርግጠኛ ነህ..እንደዛ አድርጌለሁ?››
‹‹አዎ እርግጠኛ ነኝ…ምን አልባት ስለአንተ ማንነት ያወቀችው ነገር ይኖር ይሆናል ብለን ስለሰጋን ልንለቃት አልፈለግንም፡፡››
‹‹እና አሁን ወደሴንቸዋሪ ከሚጓዘው ቡዱን ጋር እየወሰድናት ነው እያልከኝ ነው፡፡››
‹‹አዎ፡፡››
‹‹ሽጉጥህን ስጠኝ ፡፡››ኮሰተር ያለ ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ሁሉም በያለበት ሽምቅቅ አሉ፡፡ዳግላስ ሽጉጥ ስጠኝ ካለ የሆነ ችግር ሊፈጠር እንደሆነ ሁሉም ያውቃሉ፡፡ሽጉጥ እጁ ከገባ ይተኩሳል፡፡ሲተኩስ ደግሞ አየር ላይ አይደለም..ወይ አንዱ ደረት ላይ ወይ ደግሞ ጭንቅላት ላይ ነው የሚያሳርፈው፡፡በሚንቀጠቀጡ እጆቹ ሽጉጡን ከጎኑ መዞ ሰጠው…ግንባሩ ላይ ደቀነበት፡፡
‹‹እንዴት አንድ ምንነቷን የማታውቃትን መንገደኛ ሴት እየነዱ ወደግዛቴ ይዘዋት እንዲመጡ ትዕዛዝ ታስተላልፋለህ….?ምን ተልዕኮ እንዳላት ታውቃለህ…?ማን እንዳሰማራትስ?››
‹‹ጌታዬ ከፍተኛ ጥንቃቄ አድርገናል…ሙሉ እቃዋን ሆነ ጠቅላላ ሰውነቷን አብጠርጥረን ፈትሸናል፡፡ አታስፈልግም ካልከን አሁን ባለችበት እንዲያስወግዶት ማድረግ እችላለሁ፡፡››በፍርሀት በራደና በሚንቀጠቀት ድምፅ ሊያስረዳው ሞከረ፡፡
‹‹አይ መጀመሪያ አንተን አስወግድህና ትዕዛዙን እራሴ አስተላላፋለሁ፡፡››የሽጉጡን መጠበቂያ አላቀቀ….እጠቱን ምላጩ ላይ አሳረፈ…በዚህ ቅፅበት ልጁ‹‹አባዬ…አባዬ›› እያለች የጀልባውን በራፉ ከፍታ ወደእሱ ተንደረደረች….ቶሎ ብሎ የደቀነውን ሽጉጥ ከሰውዬው ግንባር ላይ አላቀቀና ጠረጴዛ ላይ ወርውሮ ከተቀመጠበት በመነሳት ወደ ልጅ ተንደረደረ፡፡አቃፋትና አባበላት፡፡ዝም ስትል ወደ ታጣቂዎች ዞረና ትዕዛዙን አሰስተላለፈ‹‹ በሉ አሁን ጉዞ እንቀጥል፡፡ እስከአሁን ያባከነው ሰዓት ይበቃል ፡፡ዛሬ ካምፕ ገብተን ማደር አለብን፡፡››
‹‹እሺ ጌታዬ ..ልጅቷን በተመለከተ ትዛዙን ላስተላልፍ?፡፡››
እንደማሰብ አለና‹‹..አይ ያንን ዕድልማ አጥተኸዋል…አሁን እራሴ የሚሆነውን አደርጋለው፡፡››ብሎ ወደውስጥ ገባ…..ጀልባዋም ተንቀሳቀሰችና ጉዞ ጀመረች፡፡
ወዲያው ነበር እጃቸው ላይ ያለችውን ሴት ገድለው ማንም እንዳያገኛት አድርገው እንዲቀብሯት ላቲሲያ ለሚገኙት ገዳዬቹ ትዕዛዝ የስተላለፈው፡፡
ኮለምቢያ
/ላቲሲ(አማዞን ወንዝን ታካ የተመሰረተች በአሳ ምርቶ የምትጣወቅ ከተማ) ካርሎስ  ከገዳይ  አጋሮቹ  ፈንጠር  ብሎ  አንድ  ግዙፍ  ዛፍ  ስር  ቁጭ  ብሎ በማስታወሻ ደብተሩ ላይ የቀን ውሎውንና ገጠመኞቹን በምጥን ቃላት እያሰፈረ ሳለ በቡድኑ ሀለቃ ተጠራ፡፡ማስተወሻ ደብተሩን አጣጥፎ ጎኑ ያለው የጉዞ ቦርሳው ውስጥ ከተተና መሳሪያውን በአንድ ተከሻው አንጠልጥሎ ቦርሳውን በእጁ ይዞ ወደተጠራበት ቦታ ሄደ፡፡
ቀጥታ ‹‹ግባና ግደላት፡፡››የሚል ትዕዛዝ ነበር የሰጠው፡፡

‹‹ምን ?››ካርሎስ ሀላቀውን በድንጋጤ ጠየቀ፡፡

‹‹ትልቁ ሀለቃችን ትገደል ብሏል…ግባና ግደላት፡፡››ኮስተር ብሎ በድጋሚ ትዕዛዙን አስተላለፈ፡፡
‹‹እርግጠኛ ናችሁ ትገደል ብሏል?››

‹‹ሰውዬ ያምሀል እንዴ? እኔ የተሳሳተ ትዕዛዝ ሳስተላልፈ አይተሀኝ ታቃለህ..?ነው ወይስ ፈራህ?ከፈራህ ግድ የለም ሌላ ሰው በደስታ ያድርገዋል፡፡እኔ እኮ ስለምትወዳት በፍቅር እንድትገድላት እድሉን ልስጥህ ብዬ ነው እንጂ ሌሎች በደስታ የሚፈፅሙት ትዕዛዝ መሆኑን አጥቼው አይደለም …ምንም ቢሆን እሷን እዚህ ድረስ በማጓጓዙ ከአንተ እኩል የለፋ የለም፡፡››
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስራ_ሶስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


‹‹ይሄ መንገድ ግን ወደ መጣንበት አቅጣጫ የሚወስድ አይደል እንዴ?››በጥርጣሬ ጠየቀች፡፡
‹‹አይ አይደለም…..ትንሽ ከተጓዝን በኃላ እንታጠፋለን፡፡››ሲል ድጋሜ ዋሻት፡፡

ከዛ በኃላ ለ10 ደቂቃ ያህል ጫካውን ቁጥቆጦ እየገፉና እሾክና እንቅፋቶችን ከፊታቸው እያስወገድ ወደፊት ከመጓዝ ውጭ በሶስቱም መካከል ምንም ንግግር አልነበረም፡፡
ኑሀሚ የህይወቷ የመጨረሻ ጫፍ ላይ እንደደረሰች ተስምቷታል፡፡ከቡድኑ ነጥለው ወደጫካው እየነዷት ያለው ለሰላም እንዳልሆነ ወዲያው ነው የገባት፡፡ በተለይ የካርሎስ መርበትበትና በፊቱ ላይ እየተመለከተችው ያለው ሀዘን በጥርጣሬዋ እርግጠኛ እንደትሆን አድርጓታል፡፡ በዛ ላይ ከኃላ ሆኗ የሚከተላቸው ፊቱ የማፈታው ታጣቂ በጀርባው ባነገተው ቦርሳ አካፋም መቆፈሪያም ሆኖ የሚያገለግል ወታደሮች ምሽግ ለመስራት የሚጠቀሙበትን መሳሪያ ይዞ በማየቷ ሌላ እርግጠኛ እንድትሆን ያደረጋት ምልክት ነው፡፡
አካባቢን ማጥናት..ማንኛውንም እንቅስቃሴ በንቃት መከታተል..ከዛ የይሆናል ትንበያዎችን አስቀምጦ ከቅርቃሩ ለመውጣት የሚያስችሉ አማራጮችን በፍጥነት ማስላት….በስለላ ህይወቷ የቀሰመችው ትምህርት ነው፡፡
እና ዝም ብላ መሞት እንደሌለባት እራሷን እያሳመነች ነው፡፡በህይወቷ እንዲህ መሰል በህይወትና በሞት ቅርቃር መካከል የመውደቅን አጋጣሚ ብዙ ጊዜ ገጥሞት ያውቃል፡፡ በአምስት ሰዎች ተከባ ልትገደል ብላ ግማሹን ገንድሳ ግማሹን ገድላ ነፃ የወጣችበትና ህይወቷን ያተረፈችበት አጋጣሚ ነበረ፡፡ከእዛ አንጻር ሲታይ ይሄ ቀላል ይመስላል..ምክንያቱም ከሁለት ታጣቂዎች ጋር ነው የምትፋለመው፡፡ ካላት ወታደራዊ እውቀትና ልምድ አንፃር አነሱን ገድላ ወይ ፌንት አስበልታ የማምለጥ እድሏ ከ50 ፐርሰንት በላይ ነው ፡፡..ችግሩ ካመለጠች በኃላ ነው፡፡ፊቷ ያፈጠጠው ምኑንም የማታውቀው በየት ገብታ በየት መውጣት እንዳለባት ምንም እውቀት የሌላት የአማዞን ጫካ ነው፡፡ጫካ ውስጥ ያሉት አስፈሪና በስም እንኳን ለይታ የማታውቃቸው አውሬዎችና አንድ ጠብታ መርዛቸው እንኳን ሰውነት ላይ ሲያርፍ በሰከንድ ውስጥ የሚያደርቅ ተሳቢ እንስሳትና በራሪ ነፍሳት ጋር ነው፡፡ቢሆን በሰው ተቦጫጭቆ ከመበላት በአውሬ ጋር ለመፋለም ቁርጠኛ መሆን ይሻላል
፡፡በዚህ ቅፅበት አንድ ታሪክ ትዝ አላትና ለካርሎስ ልትተርክለት ፈለገች፡፡

‹‹አንድ ጣፍጭ ታርክ ልንገርህ?››

እንደ እሱ ግንዛቤ ሰዓቱ ታሪክ መንገሪያም ሆና ማዳመጪያ እንዳልሆነ ቢያምንም ለእሷ ግን ምን አልባት የመጨረሻ ቃሏ ሊሆንላት ይችላል ብሎ ስላሰበ እንድትነግረው ተስማማ፡፡
‹‹ጨቋኝ ገዢ ወይም የሰው ልጅ  ከገዳይ ነብር የበለጠ አስፈሪ እንደሆነ የሚያስረዳ ታሪክ ነው፡፡
‹‹ገባኝ ንገሪኝ…››

ከአንድ የድሮ መፅሀፍ ላይ ያነበብኩት ታሪክ ነው፡፡በአንድ ወቅት በቻይና ግዛት ውስጥ በምትገኘው በታይ ተራራ ስር በሀዘን ተቆራምዳ እንባዋን እያዘራች የምትኖር ሴት ነበረች፡፡የዚህችን ሴት ታሪክ ኮንፌሽዬስ ሰማና አስጠራት፡፡ከዛም"አንቺ ሴት ምን ሆነሽ ነው እንዲህ ሀዘን የበላሽ?"ሲል ጠየቃት።ሴቲቱም ‹‹በተራራው ላይ የሚኖረው ነብር ባሌን ፣የባሌን አባት እና ብቸኛ ልጄን በየተራ እየቀረጣጠፈ በላብኝ-በዛ ምክንያት ነው ሀዘኔ ጥልቅ የሆነው›› ብላ መለሰችለት።
እሱም መልሶ "ታዲያ መላ ቤተሠቦችሽን የበላው ነብር አሁንም በተራራው ላይ መኖን እያወቅሽ .እንዴት ከአካባቢው ሳትሸሺ?››ሲል በመገረም ጠየቃት።
ሴቲቱም‹‹ቦታውን ለቅቄ ያልተሠደድኩት ጨካኝ ገዢ የሌለበት ብቸኛ  ስፍራ ስለሆነ ነው።"ስትል መለሠችለት
ኮንፌሽዬስም ወደ ደቀመዛሙርቱ ዞሮ" አያችሁ ጨቋኝ ገዢ ከገዳይ ነብር የበለጠ አስፈሪ እንደሆነ ከዚህች ሚስኪን ሴት ታሪክ ተማሩ፡፡›› አላቸው።
እኔም አሁን እዚህ አማዞን ደን ውስጥ ካሉት አውሬዎች በላይ ጨካኝ የሆኑ የሰው ልጆች ናቸው እያሰፈሩኝ ያሉት››ብላ ታሪኩን ደመደመች፡፡
‹‹አልተሳሳትሽም….የሰው ልጅ መጨከን ከጀመረ ወሰኑ አይደረስበትም…››

‹‹እኔ ምልህ ..አሁን ልትገድሉኝ ነው አይደል?››

ጥያቄዋ አስደነገጠው…ምን ብሎ እንደሚመልስላት ግራ ስለገባው…ዝም አለ…‹‹አትጨነቅ..ግን ያልገባኝ እንዲህ ልትገድሉኝ ይሄን ሁሉ ቀን እኔንም ማንከራተት እናንተም ከእኔ ጋር መንከራተት ለምን አስፈለገ?››
‹‹ትዕዛዙ የደረሰን አሁን ነው…››

‹‹ትዕዛዙን የሚሰጠው ማን ነው››

‹‹ሀለቃችን ነው…ካለበት ቦታ በሳተላይት መገናኛ ነው ከደቂቃዎች በፊት ትገደል ያለው፡፡››

‹‹ይገርማል…ቆይ ግን ከእኔ ጋር ያገኛችሁትን ሰውዬ ገድላችሁታል አይደል?››

ፈገግ አለ፡፡

የፊቱን ፈገግታ በቆረጣ እይታ አየችውና ተበሳጨችበት…‹‹ምነው? የሰው መገደል ያስቃል እንዴ?››
‹‹አረ በፍፅም … እንደውም በተቃራኒው ልቤን ነው የሚሰባብረው፡፡››

‹‹አይ ስትስቅ አየሁህ ብዬ ነው፡፡››

‹‹ጥያቄሽ ነው ያሳቀኝ …አንቺ እንድትገደይ ትዕዛዙን ያስተላለፈው ሀለቃችን አሁን አንቺ የምትጨነቂለት ዳግላስ መሆኑን ሳስብ ነው ያሳቀኝ..አየሽ አለም በእንደዚህ ይነት ገራሚ ምፀቶች የተሞላች ነች፡፡››
እርምጃውን ገታችና ባለችበት ቆመች..ከኃላ እየተከተላቸው ታጣቂ አይኑን አጉረጠረጠ…የጓደኛውም ሆነ የተገዳዮ ነገረ ስራ ምንም አላማረውም…ጣልቃ ላለመግባት ነው እንጂ ወሬያቸውም አልተመቸውም.. ምክንያቱም እሱ ስፓኒሽኛ ተናጋሪ ሲሆን እንሱ እያወሩ ያሉት በእንግሊዘኛ ነው..እሱ ደግ እንግሊዘኛ ጆሮውን ቢቆርጡጥ አይሰማም፡፡
‹‹ማለት ከእኔ ጋር ያገታችሁት በሌላ ጀልባ ወደሌላ ስፍራ የወሰዳችሁት ዳግላስ የእናንተ ሀለቃ ነው?››ማመን ስላልቻለች ደግማ ጠየቀችው፡፡
‹‹አዎ እሱ የእኛ ብቻ ሳይሆን በሺ ሚቆጠሩ ሌሎች የታጣቂ ቡድኖች መሪ የጫካው ንጉስ እየተባለ   የሚጠራ   ከፍተኛ   ቢሊዬን   ዶላሮች   የሚያንቀሳቅስ   ከፔሩ፤ ኮሎምበያ፤ ፓናማ፤ ነካረጎ፤ ጉታማላ፤  ሚክሲኮ አልፎ አሜሪካ ድረስ እሱ የሚቆጣጠረው የንግድ መስመር ያለው በሶስት በአራት ሀገራት የደህንነት ሰዎች ሚፈለግ አለማ አቀፉ የኢንተርፖል የተፈላጊዎች ስም ዝርዝር ውስጥ የመጀመሪያው ገፅ ላይ የሰፈረ ተአምረኛ ሰው ነው፡፡››የሚላትና ማመን ነው እያቃታት፡፡‹‹እና እሱ እንደእዛ አይነት ሰው ከሆነ ለምን ከእኔ እኩል አፈናችሁት?፡፡››ስትል ጠየቀች፡፡
‹‹ሰውዬው መድሀኒቱን በጊዜ ካልወሰደ ከፍተኛ የመርሳት ችግር አለበት..ማለት እራሱንና ማንነቱን ሙሉ በሙሉ እስኪዘነጋ ድረስ ይደርሳል፡፡ከንቺ ጋር ሊማ አየር ማረፊያ ተገናኝታችሁ ኢኩቶስ እስክታርፉ ድረስ ከዛም ሆቴል ይዛችሁ ስታድሩ ሁሉ ያገጠማችሁ ያ ነው፡፡በወቅቱ ችግሩ እንደተፈጠረ ስናውቅ በግል ቻርተር አውሮፕላን እናንተ ወዳላችሁበት መጣን፡፡ ቀጥታ ሄደን ብናናግረው..አላውቃችሁም ሊለን ይችላል፡፡ ክርክር ብንገጥም ጭቅጭቅ ቢነሳ ደግሞ ትኩረት እንስባለን…እንዳልኩሽ በአለም አቀፍ ደረጀ የሚፈለግ ሰው ነው…ስለዚህ ሁኔታውን አመቻችተን ማፈን ነበረብን፡፡ለዛ ነው እንደዛ ያደረግነው፡፡››
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስራ_አራት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ

ኮሎምቢያ/አማዞን ደን ውስጥ

ኑሀሚና ካርሎስ አምስት ሰዓት ያለምንም ረፍትና መንቀርፈፍ ነው የተጓዙት፡፡በቀንም ቢሆን እንኳን ፀሀይ የተንጣለሉትን የግዙፍ ዛፎችን ቅርንጫፍ ሰንጥቃ ወደመሬት መድረስ አይሆንላትም፤ ማታ ሲሆን ደግሞ ለጨረቃዋ በጣም ከባድ ስራ ነው የሚሆንባት፡፡ በዚህም ምክንያት በማታ አይደለም በቀንም ከፍተኛ ሀይል ያለው ባትሪ ሳይጠቀሙ መጓዝ አዳጋች እና በቀላሉ ለአደጋ የሚያጋልጥ ስራ ነው፡፡
‹‹አሁን ማረፍ ያለብን ይመስለኛል››አላት ካርሎስ

‹‹ይሻላል ብለህ ነው?››አለችው በዛለና በደከመ ድምጽ፡፡

‹‹አዎ አሁን የተወሰነ የራቅናቸው ይምስለኛል…ባይሆነ ለሊቱን አርፈን ንጊት ላይ በሙሉ አቅም ጉዞችንን እንቀጥላለን፡፡››አላትና ተስማሙ፡፡ቅጠል እየቆረጠች ግዘፉ ግንድ ስር መጓዝጎዝ ጀመረች፡፡
‹‹ምን እየሰራሽ ነው?፡፡››

‹‹መሬት ላይ ከመቀመጥ ቅጠሉ ይሻለናል ብዬ ነዋ፡፡››

‹‹እዚህ የአማዞን እንብርት ላይ መሬት ላይ ተዝናተን መተኛት አንችልም…››

‹‹ለምን? ጃጓር ምናምን ፈርተህ ነው?››

‹‹እሱም አንድ ነገር ነው..ካዛ በላይ ግን ጥቃቅን መርዛማ ነፍሳቶች ናቸው የሚያስፈሩት…..ለምሳሌ የአማዞን ሸረሪት ሰውነትሽን ጥቂት ከጫረችሽ ወይ ከቦጨቀችሽ….በቀጥታ እራስሽን ለሞት ማዘጋጀት መጀመር ነው ያለብሽ፡፡በጣም ብርቱ ከሆንሽ አንድ ሰዓት ብቻ ነው የምትኖሪው፡፡መርዙን አርክሶ ከሞት የሚያድንሽ ምንም አይነት ባህላዊም ሆነ ዘመናዊ መድሀኒት የለም፡፡እና ይህችን ሸረሪት በቁጥር አንድ ደረጃ ነው የምፈራት፡፡››
ፍራቻው ወደእሷም ተጋባበትና‹‹እና ምን እናድርግ?፡፡››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹ሊያስተኛን የሚችል ዛፍ ነው መፈለግ ያለብን ..››ብሎ አይኖቹን በአካባቢው ወደሉት ግዙፍ ዛፎች ባትሪውና በማብራት መምረጥ ጀመረ…ከዛ ‹‹አዎ ይሄኛው የተሻለ ነው….፡፡››ስል ምራጫውን አሳወቃት፡፡
‹‹እንዴት አድርገን ነው እዚህ ላይ ምንወጣው?››

‹‹እንደምንም መውጣት ነዋ….መቼስ ቢከብድ ቢከብድ የሰው ህይወት ከማጥፋት በላይ አይከብድም፡፡››
በንግግሩ ድንግጥ አለች፡፡እስከአሁን እዛ ለእሷ በተቆፈረው መቃብር አካባቢ ስለሆነው ነገር አንሰተው አላወሩም‹‹ሰው መግደሉን ፈልጌው ወይም ቀላል ሆኖልኝ መሰለህ..?ጨንቆኝና የሞት ሽረት ጉዳይ ሆኖብኝ ነው፡፡››
‹‹እኮ እኔስ ምን አልኩ…?ይሄም የህይወት እና የሞት ትግል ነው፡፡ከዚህ ደን በአውሬ ሳንበላ ወይም በነፍሳት ሳንነደፉ በሰላም ወጥተን የሆነ መንግስት የሚቆጣጠረው ትንሽዬም ቢሆን ከተማ ወይም መንደር እስክንገባ የህይወትና የሞት ሽረት ላይ እንደሆን እንዳትዘነጊ…. በይ ቦርሳሽን ለእኔ ስጪኝና ለመውጣት ተዘጋጂ …እኔ ከኃላ ሆኜ እደግፍሻለሁ፡፡››
የተወሰነ ጊዜ እንደማሰብ አለችና ትከሻዋ ላይ ያንጠለጠለችውን ቦርሳ አቀበለችው፡፡ተቀበላትና ካንጠለጠለው ቦርሳ ጋር አንድ ላይ በቀኝ ትከሻው ደርቦ አንጠለጠለው፡፡በግራ ትከሻው ላይ ክላሽ አለ፡፡
እሷ በረጅሙ ትንፋሽ ወሰደችና ለመውጣት ዝግጁ ሆነች፡፡ቀኝ እግሯን አስቀደመች…ወገቧን ይዞ ደጋፋት፡፡ በእጆቿ ቅርብ ያለውን ቅርንጫፍ ተንጠራርታ ያዘችና ግራ እግሯን አስከተለች፡፡ እንዳዛ እያለች ወደ ላይ መንቀሳቀሷን ቀጠለች፡፡እሱ ከስር ሆኖ ትወድቅ ይሆን በሚል ስጋት በጭንቀት እየተከታተላት ነው፡፡እንደፈራው ሳይሆን እንደውም ይበልጥ አንድ ርምጃ ወደላይ ከፍ ባለች ቁጥር ይበልጥ እየፈጠነችና በራስ መተማመን እየታየባት መጣች፡፡ ለመተኛት ምቹ ነው ብሎ ያሰበበት ቦታ ስትደርስ ‹‹በቃሽ…እዛው ጠብቂኝ›› አላት፡፡እሱም በእፎይታ ወደላይ መውጣት ጀመረ፡፡እሱ ከልጅነቱ ጀምሮ የብዙ አመት ልምድ ስላለው ዛፍ መውጣት ለእሱ በምድር እንደመራመድ ቀላሉ እና ተራ ነገር ነው፡፡
ስሯ ደረሰና ከጎኗ ቁጭ ብሎ የእሷንም የእሱንም ቦርሳ ከአንደኛው ቅርንጫፍ ላይ አሰረው፡፡መሳሪያውንም እንደዛው አንጠለጠለውና በእፎይታ ደገፍ ብሎ ተቀመጠ፡፡ ካልተመቸሽ እግርሽን በቅረንጫፉ መሀከል አድርጊና ጭንቅላትሽን እኔ ላይ አስደግፊ አላት፡፡››እንዳለት አደረገች፡፡ጭንቅላቷን ደረቱ ላይ ለጥፋ አረፍ ስትል የልብ ምቱ ድውድውታ ተሰማት፡፡
‹‹ልብህ በጣም ይመታል፡፡›› አለችው፡፡

‹‹አንቺን የመሰለች ፀይም መልዐክ ደረቴ ላይ ተኝታ የልብ ምቴ ባይጨምር ነበር የሚገርመው››አላት፡፡
‹‹አይገርምም …የዛሬን አያድረገውና አለቃህም በሰላሙ ቀን ፀይም መልአክ ብሎኝ ነበር››

‹‹እንደዘ በማለቱ እንኳን ተሳስቷል ማለት አልችልም…የእሱም ልብ እንደእኔው በውበትሽ ደንዝዛ ነበር ማለት ነው፡፡››
‹‹በዚህ ጣር ላይ ሆነህ ትቀልዳለህ አይደል?››

‹‹በጣር ላይ ሆንሽ በምቾት ላይ ልብሽ ጉዳዩ አይደለም እኮ …ከተነካ ተነካ ነው..በሲኦሉ ውስጥም ሆነ በገነት እጅ መስጠቱ አይቀርም፡፡››
‹‹ይሁንልህ…ውሀው አለቀች እንዴ?››ስትል ጠየቀችው፡፡ውሀ ጠምቷት ብቻ ሳይሆን የጀመሩትን የወሬ ርዕስ አቅጣጫ ማስቀየርም ስለፈለገች ነው፡፡የእሱን ልብ አታውቅም የእሷ ልብ ግን በዚህ ጊዜ ነፍሷን ለወንድሟ ስትል ከማትረፍ ውጭ ሌላ ተልዕኮ የላትም፡፡እጁን ወደተንጠለጠለው ቦርሳ ሰደደና ኮዳውን አውጥቶ ሰጣት፡፡ክዳኑን ከፈተችና ተጎነጨችለት፡፡መልሳ ከድና አቀበለችው፡፡ወደቦታው መለሰ፡፡
‹‹አሁን የት ነው ያለነው?፡፡››ስትል ጠየቀችው፡፡

‹‹የአማዞን ጥቅጥቅ ደን ውስጥ ነዋ፡፡››

‹‹እሱንእማ እያየሁት ነው…ሀገሩን ነው የጠየቅኩት፡፡
‹‹ብራዚል እና ኮሎምቢያ ድንበር ላይ ነን፡፡››
‹‹እንዴ …!ወደየት ነው እየሄድን ያለነው?››

‹‹ወደብራዚል ነው…››

‹‹ወደኮሎምቢያ ወይም ወደመጣንበት ወደፔሩ የምንሄድ ነበር የመሰለኝ፡፡››

‹‹አይ …ያንን ማድረግ አልመረጥኩም…ከፔሩ ፤ኮሎምቢያ ሜክሲኮ አልፎ አሜሪካ ድረስ ሰውዬው በብዙ ሺ የሚሆኑ ሰዎች አሉት…በየደረስንበት ሁለ ታዳኞች ነው የምንሆነው፡፡ይሄኔ ሁሉም እኛን በደረስንበት ቀጨም አድርጎ ወይ በህይወት ካለሆን ደግሞ እሬሳችንን ለእሱ በማስረከብ እና ደለብ ያለ ሽልማቱን ለመቀበል ቋምጠው እየጠበቁን ነው፡፡››
‹‹ብራዚልስ ሰው የለውም?››

‹‹አይ ብራዚል ተፅእኖው በጣም የሳሳ ነው፡፡በዛ ላይ አሁን እየተጓዝን ያለነው ወደግዙፍ ጥቅጥቅ የአማዞን ደን ነው..በቀደም እንደነገርኩሽ 60 ፐርሰንቱ የአማዞን ደን ያለው ብራዚል ውስጥ ነው፡፡ወደእዛ ጠልቀው ይገባሉ ብሎ ማንም አያስብም፡፡ገብተዋል ብለው ቢያስብ እንኳን ያን ሁሉ ደን ሰንጥቀን ከአውሬዎቹም ከተናዳፊ መራዛማ ነፍሳትም ተርፈን በህይወት የሆነ ቦታ እንደማንደርስ እርግጠኞች ናቸው..ስለዚህ ወደዚህ አይፈልጉንም፡፡ለዛ ነው በጣም ከባዱን መንገድ የመረጥኩት፡፡በህይወት እንዲሳካልሽ አንዳንዴ ቀላሉን መንገድ መምረጥ አዋጪ አይደለም…፡፡››
ፈገግ አለችና‹‹አሳምነኸኛል..ግን አንተስ ከፊታችን እንደፓስፊክ ውቅያኖስ የተዘረጋውን አስፈሪ ጥቅጥቅ ደን ሰርቫይቭ አድረገን ሕይወታችንን እንደምናተርፍ እንዴት ልታምን ቻልክ?፡፡››
‹‹በቀደም በነገርሺኝ ታሪክ ነዋ››

‹‹የትኛው ታሪክ?፡፡››

‹‹የሴትዬዋ… ጨካኝ ንጉስ ያለበት ግዛት ውስጥ ከመኖር አዳኝ ነበር ያለበት ጫካ ውስጥ መኖር እንደሚሻል መምረጦን የነገርሺኝን…››
በጨለማ ውስጥ ፈገግ ብላ‹‹ጥሩ ተማሪ ነህ፡፡››አለችው ፡፡

‹‹አዎ ጥሩ ተማሪ ነኝ..በዛ ላይ ሶስት ነገሮች ያግዙናል ብዬ አስባለው፡፡››

‹‹እስኪ ንገረኝ እነዚሀ ሶስት ነገሮች ምንድናቸው?፡፡››
#ኢትዬጵያዊቷ_ሰላይ
( በአመዞን ደን ውስጥ)


#ክፍል_አስራ_አምስት


#በዘሪሁን_ገመቹ_ዋቤ


ደረቱ ላይ እንደተጋደመች..አይኖቾን ጨፍና ሀሳብ ውስጥ ገባች…በትዝታ ወደሚስኪን ሀገሯ ተመለሰች፡፡እንዴት ለጀመሪያ ጊዜ ከጓዳና ህይወት እራሳቸውን እንዳላቀቁ ነው ትዝ ያላት፡፡
ከ15 ዓመት በፊት /ኢትዬጵያ/አዲስ አበባ/

መንትዬዎቹ ከኩማደሩ ቢሮ እንደወጡ ቀጥታ ተንደርድረው ፊት ለፊት ያገኙት ካፌ ነበር የገቡት፡፡ሁለቱም ምሪንደ አዘው ውስጣቸውን እያቀዘቀዙ ለበርካታ ደቂቃዎች ያለንግግር በየራሳቸው እያወሩ አሳለፉ…
‹‹ወንድሜ ..ተይዘን ቢሆን ኖሮ የሆነ ነገር ያደርጉብኛል ብዬ በጣም ሰግቼ ነበር….››

‹‹እንዴ ትቀልጂያለሽ እንዴ? ተይዘን ቢሆን ኖሮኮ ሁለታችንንም ነው የሆነ ነገር የሚያደርጉን..ወፌ ላላ ሁሉ ሊገርፉን ይችሉ ነበር…፡፡››ሲል መለሰላት
‹‹አውቃለሁ…ግን እኔ እችለዋለው..አንተን ግን በጣም ያምሀል››አለችው፡፡ አሁን የሆነ ይመስል በሰንበር የበላለዘ ጀርባውንና የቆሰለ ሰውነቱን በምናቧ እያይች ዝግንን አላት፡፡
‹‹አይ እህቴ ..አንዳንዴ እናቴ የሆንሽ ነው የሚመስለኝ..የ0 ደቂቃ ታላቅ ወንድምሽ መሆኔን ዘነጋሽው እንዴ?ለማንኛውም አሁን ስራችንን በስኬት አጠናቀናል፡፡ብዙ ገንዘብም አግኝተናል፡፡›
‹‹አዎ እሱ ጥሩ ነገር ነው….››
‹‹አዎ ..ጥሩ ነው ደጋግማ እንዲህ አይነት ስራዎችን እያሰራች እንዲህ ብዙ ብር ብትከፍለን በጣም ደስ ይለኝ ነበር…››
‹‹እስኪ መጀመሪያ የሰራንበትን ቀሪ ሂሳባችንን ትስጠን››
‹‹አረ ኑሀሚ…አሁንም ያቺን ልጅ ኣታምኚያትም ማለት ነው?››

‹‹ለምን ብዬ አምናታለው…ወላጆቼ ሰው በማመን ምን አተረፉ..ይገባሀል እኔ በዚህ ምድር ላይ ካንት በስተቀር ማንንም ሰው ማመን አልፈልግም››አለችው፡፡
‹‹በቃ አትቆጪ እንዳልሺ ይሁንልሽ..አሁን ሂሳብ ክፈይና እንውጣ፡፡››
‹‹ከብዙ ድፍን ብሮች መካከል አንድ ነጠላ መቶ ብር መዛ የሁለት ለስላሳ ሂሳብ ለአስተናጋጁ ሰጠችው፡፡ሂሳብን ቆረጠና መልሱን አመጣላት፡፡አምስት ብር ቲፕ አስቀመጠችለት..ናኦል ያደረገችውን አየና ፈገግ አለ…፡፡››
‹‹ምን ትገለፍጣለህ..እኛም ወግ ይድረሰን እንጂ፡፡ይሄን ያህል ብር ለሰው በቲፕ መልክ ስንሰጥ እኮ ይሄ የመጀመሪያ ቀን ታሪካችን ነው፡፡››አለችው፡፡
‹‹እሱስ እውነትሽን ነው፡፡ሳናስበው ታሪክ መስራት ጀመርን ማለት ነው?››በገረሜታ ጠየቃት፡፡
‹‹አዎ..እየሰራን መሰለኝ፡፡››በዚህ ጊዜ ወደበረንዳቸው ተመልሰው ዘወትር የሚቀመጡበት ጥርብ ድንጋይ ላይ ጎን ለጎን ተቀምጠዋል፡፡…ያንን ሁሉ ብር በኪሳቸው አጭቀው ይዘው ብዙ ብዙ ቦታ ሄደው ዘና ማለት እየቻሉ እዛ መቀመጥ አልነበረባቸውም፡፡ለምሳሌ ፊልም ቤት ገብተው ፊልም ማየት የሁለቱም ምርጫ ነበር፡፡ካልሆነም እናትና አባታችው መቃብር ጋር ሔደው ዛሬ የሰሩትን አስደናቂ ጀብዱም ሊነግሯቸው ይችሉ ነበር፤ግን አላደረጉትም ፡፡ ምክንያታቸው ምስራቅ እነሱን ፍለጋ ወደቋሚ ቦታቸው ስትመጣ እንዳታጣቸው ነው፡፡ግን በቀላሉ የምስራቅ ዱካ ሊሰማ አልቻለም፡፡ቦታው ላይ ስድስት ሰዓት የተቀመጡ እስከስምንት ሰዓት አልተንቀሳቀሱም ነበር፡፡
‹‹ወንድሜ ይህቺ ልጅ አብርታናለች መሰለኝ፡፡››

ኑሀሚ የተናገረችው እሱም በውስጡ እያሰላለስለ የነበረው ነገር ስለነበረ ለስለስ ባለ ቃል‹‹ለምን እንደዛ አልሺ?››ሲል ጠየቃት፡፡
‹‹ይሄው እንደምታያት ቀረቻ….ጉዳዮ ከተፈፀመላት ለምን ብላ መጥታ ሁለት ሺ ብር ሙሉ ትሰጠናለች?››

‹‹ግድ የለሽም እንደዛ አታደርግም…ትንሽ እንጠብቃት፡፡››

‹‹አይ እኔ ደግሞ የምታደርገው ነው የሚመስለኝ…ጥዋት ሁለት ሺ ብር ብላን አልነበር..አይሆንም አራት አድርጊው ስላት…..አይሆንም ባይሆን ሶስት እንኳን ይሁን አላለችንም፡፡በአንዴ ነው የተስማማችው፡፡በወቅቱ እንደውም በውስጤ ምነው ስድስት ሺ ወይ ስምንት ሺ ባልኳት እያልኩ ነበር፡፡ግን ይሄው እሷ እኛን ለማበረታታት እና ስራዋን በሞራል እንድንሰራላት እንጂ እንደማትከፍለን ታውቅ ነበር፡፡

‹‹እና ተመልሳ አትመጣም እያልሺኝ ነው?››

‹‹አዎ እንደዛ ነበር ያሰብኩት ..ግን ተሳስቼያለሁ መሰለኝ››አለችው፡፡

ናኦል በእህቱ ንግግር ግራ ተጋባ..‹‹መቃዠት ጀመረች እንዴ?›› ሲል በውስጡ አልጎመጎመ፡፡
‹‹እህቴ አልገባኝም፡፡››

‹‹ያቹት መጣችልህ..››አለችው ከመንገድ ማዶ እየጠቆመችው፡፡

ናኦል በደስታ ፈንጥዞ ከተቀመጠበት ተነስቶ ቆመ…‹‹እውነትሽን ነው እህቴ? የታለች?››

ሱሪውን ያዘችና ወደታች እየጎተተች‹‹አረ ሼም ነው..ቁጭ በል፡፡ምንድነው እንዲህ መንሰፍሰፍ?እናትህ መሰለችህ እንዴ?››

ተመልሶ ቁጭ አለና.‹‹ነግሬሽ ነበር እኮ..እሷ እንደሌላው ሰው አይደለችም፡፡አትቀርም ብዬሽ ነበር…፡፡››
‹‹በቃ አፍህን ዝጋ እየቀረበች ነው፡፡››

ዝም አለና ሁለቱም አይኖቻቸውን እያቁለጨለጩ ስራቸው እስክትደርስ ይጠብቋት ነበር፡፡ምስራቅ እንደደረሰች በዝምታ መሀከላቸው ሰቅስቃ ገብታ ተቀመጠችና….‹‹እሺ ጩጬዎቹ እንዴት ሆነላችው?››ስትል ምንም ነገር እደማታውቅ ሆና ትጠይቃቸው ጀመር፡፡
‹‹አድርገናል…እንዳልሺን አስቀምጠናል፡፡››ሊያብራራላት ሞከረ፡፡
ኑሀሚ ኮስተር እንዳለች….‹‹ቀሪውን ብር ይዘሽ መተሻል››ስትል ጠየቀቻት፡፡
‹‹እህቴ ብሩ የት ይሄድብናል..?መጀመሪያ ስራውን በትክክል መስራታችንን ታረጋግጥና ቀስ ብላ ትሰጠናለች፡፡››በልምምጥ ሊያረጋጋት ሞከረ፡፡
‹‹አታርፍም እንዴ…በትክክል እንደሰራነውማ ገና ድሮ ነው ያወቀችው፡፡››በኑሀሚ ንግግር ምስራቅም ሆነች ወንድሟ ደነገጡ፡፡ናኦል..እነሱ ካልነገሯት እንዴት ታውቃለች ብላ ልታስብ እንደቻለች ስላልገባው ነው..ምስራቅ የደነገጠችው በልጅነቷ የአእምሮ ስልነት ስለተደመመች ነው፡፡
‹‹ማወቋን እንዴት አወቅሽ?››ሲል ጠየቀት፡፡
‹‹ነግረሺናል እኮ ..ዕቃውን እዛ ያስቀመጥነው አንቺ እዚ ሆነሽ ዛፓው የሚሰራውን ሁሉ ለመከታተል ነው፡፡አስቀምጠን እንደወጣን አንቺ ሰውዬውን መከታተል ጀምረሻል፡፡ያ ባይሆን ኖሮ ስትመጬ ፊትሽ ላይ ቁጣና ንዴት ይታይ ነበር፤አሁን ግን እርካታና ደስታ ነው የማነበው፡፡››አብራራችላት፡፡
ምስራቅ ኪሶ ገባችና የታጠፈ ብር በማውጣት ..‹‹ይሄው ሶስት ሺ ብር..አንድ ሺ ብሩ እንዳልሺው ስላስደሰታችሁኝ ቦነስ ነው፡፡››አለችና እጇ ላይ አስቀምጣላት…ከተቀመጠችበት ተነሳችና ናኦልን በፍቅር ጭንቅላቱን በመነቅነቅ ቀጥ ብላ ተለይታቸው ሄደች፡፡
‹‹ምስራቅ…መች ነው የምትመጪው?››ጮክ ብሎ ጠየቃት፡፡
‹‹እዛ ቆቆር ቤት ወስደህ ቁርስ ምትጋብዘኝ ከሆነ ነገ ጥዋት እመጣለው፡፡››አለችው፡፡ ደስ ብሎት‹‹እጋብዝሻለሁ..እንዳትቀሪ፡፡››አላት ፡፡
‹‹እሺ አልቀርም፡፡››አለችውና ከእይታው ተሰወረች፡፡
ምስራቅን በአይኖቹ እስከመጨረሻው ሸኝቶ ወደ እህቱ ሲዞር የሰጠቻትን ብር እየቆጠረች ነበር፡፡በትዝብትና በገረሜታ ይከታተላት ጀመር፡፡
ጨረሰችና‹‹አዎ ትክክል ነች..ሶስት ሺ ብር ነው፡፡››

‹‹አይገርምም? ››አላት፡፡
ምን እንዳስገረመው ስላልገባት‹‹ምኑ?›› ስትል ጠየቀችው፡፡