"ኤልሮኢ ዘተዋህዶ"
1.2K subscribers
26 photos
3 videos
5 files
21 links
ኤልሮኢ
"በእውኑ የሚያየኝን ጌታ አየሁት"
በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ
አምላክ አሜን።
ይህ መንፈሳዊ ቻናል
የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ አስተምህሮና ስርዓትን የጠበቁ:- +ዝማሬ
+ ምክሮች
+ ስነፅሁፎች
+ አጫጭር ትርክቶች እንዲሁም
+ ምስባክና
+ ወንጌል ይለቀቁበታል።

ለበለጠ መረጃ @AleroeBot
ግሩፑን ለማግኘት @alero
Download Telegram
ኤልሮኢ:

ቤተክርስቲያን ጋር መጣላት ከራስ ጋር መጣላት ነው። ይቅርብህ ወገኔ
ይቅርብሀህ ወዳጄ ይቅርብህ ግዴለም ስማኝ በቤተክርስቲያን ላይ እጅህን
አታንሳ። አጻፋው ይከፋብሃል የሚመጣብህን ቁጣና መቅሰፍት የዲያቢሎስ እራት
ያደርግሀል ወዳጄ ዝቅ ብዩ ልለምነህ ሕይወትህ ትቢያ እንዳይሆን አትጣላ
እንኳን አንተ የሲኦል ደጆች አይችሏትም።
ዝም ስትል ኃይል እንደሌላት አስበህ ከሆነ ተሳስተሀል በደሙ የገዛት ክርስቶስ
በወጋሪዎቹ ፊት ዝም እንዳለ ስለምታውቅ ዝም ትላለች እንጂ። ዝምታዋን
አይተህ አትዳፈር እሳቱን አቀጣጥለህ አትሩጥ ቤኒዚን አታርከፍክፍ ካህን
አትረድ ግዴለህም ስማኝ ።
ካላወቅሀት ወዳጄ ቤተክርስቲያን ማለት:
ካንተ ጋር ካለው ብዙ ኃይልና ጸጋ ያላት
ምድራዊ ሳትሆን አምሳለ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ናት
ዓለምን የፈጠረው የእግዚአብሔር አካል ነች
በደሙ የተገዛች በደሙ የተዋጀች ውድ አካሉ ናት
ዘወትር የእግዚአብሔር ዓይኖች የሚመለከቷት ናት
የአጋንት መንጋ የማያስደነግጣት ጽኑ እመቤት ናት
የክርስቶስ ስጋና ደም የሚፈተትባት ንጹህ በዓት ናት
የአበው ቅዱሳን ካህናት በዓት
የመንግስተ ሰማያት መንገድ
ያዘኑት የሚጽኑባት የሰላም ሰገነት ናት
ለአመኑት ሁሉ መጠለያ የሆነች ናት ይህን እወቅ
የድሆች መጠጊያ
የምህረት ሰገነት
የጥበብ እመቤት
የታሪክ ባለቤት ናት እንጂ
አንተ እንደምታስበው:-
የአውሮፓ አይደለችም
የአፍሪካ አይደለችም
የአማራ አይደለችም
የትግሬ አይደለችም
የሀረሬ አይደለችም
የኦሮሞ አይደለችም
የአፋር አይደለችም
የወላይታ አይደለችም
የሲዳማ አይደለችም
የጋምቤላ አይደለችም
የጉምዝ አይደለችም
የሀድያ አይደለችም
የጉራጌ አይደለችም
የከንባታ ወ ዘ ተ አይደለችም 100%
# # የእግዚአብሔር ናት##
እና እሷን ስትነካ እግዚአብሔርን እየነካህ ነው። ከፈጣሪህ ጋር ደግሞ አትጣላ
አጻፋና መቅሰፍቱ ይከብዳል ሕይወትህ እርባናቢስ እንዳይሆን ቆም ብለህ
አስብ።
እሷን ያፈረሱ እሷን ያቃጠሉ አፈርበልቷቸዋል
እሷ ግን ዛሬም አለች በክብር
ስታከብራት ትከበራለህ
ካቃጠልካት ትቃጠላለህ

@aleroe
ኤልሮኢ:

የያሬድ ዉብ ዜማ
የያሬድ ዉብ ዜማ ድንግል እመቤቴ ስጦታዬ ነሽ/ 2/
በምን አንደበቴ እንደምን ባለው ቃል ማርያም ልበልሽ/ 2
ምድርና ሰማዩ ተአምርሺን ይንገሩ
ፍጥረታት በሙሉ ስለ አንቺ ይመስክሩ
ተነግሮ የማያልቅ ድንቅ ነው ስራሽ
ድንግል ሆይ እናተ አምሳያም የለሽ
ማርያም ድንግል እረዳቴ
የምትደርሺልኝ ነይ ስልሽ በጭንቀቴ
ታምርሺን በአይኔ አይቻለሁ
ጽዮን ሆይ ስልሽ ድንግል ሆይ እጠግባለሁ
አዝ - - -
የእግዚአብሄር ጥበቡ በአንቺ ተገለጠ
የአዳም ዘር በሙሉ ከሞት አመለጠ
ለፍጥረቱ ሁሉ መሰላል የሆንሽ
ነገን ባላውቅ እኔም ቢያስፈራኚ
አንቺ ካለሺኝ በፍጹም አልወድቅም
በፊትሽም እንድቆም ለምስጋና
ማርያም ልበልሽ በትህትና
አዝ - - -
ትውልዱ በሙሉ ለምስጋና ይቁም
ባንቺ ስለሆነ የቀረለት መርገም
አዳም ከነልጁ በሰማይ በምድር
ማርያም ማርያም ይበል ተአምርሽን ይናገር
ጨለማው ከፊቴ ተገፈፈ
ማርያም በምልጃሽ ልቤ አረፈ
ከጎኔ ነይ ስልሽ እጽናናለሁ
እሳት ገደሉን ሁሉንም አልፈዋለሁ
@aleroe
ኤልሮኢ:
ምን ይል ይሆን

ዛፍ ቆራጩ የዛፉን ቅርንጫፍ መልምሎ ሲያበቃ ዛፉ እንደቆመ ራሱን ከዛፉ ጋር አስሮ ከግንዱ ጋር ሊታገል ወደ ላይ ተስቦ ከጫፍ ደርሷል። አሳቡ ቅርንጫፉ ተመልምሎ ያለቀለትን ብቻውን የቆመውን ዛፍ ከላይ ጀምሮ እየቆረጠ ወደ ታች ለመውረድ ነው።
መጥረብያውን ወደ ላይ ሲያነሳ ግን ንፋሱ ወደ ኋላ እያስጎነበሰውና በፍጥነት እያቃና ያንገላታዋል። ይሄኔ በሁለት እጁ ግንዱን አፈፍ ያደርግና ዥዋዥዌ ይጫወታል።
ንፋሱ እንኳንስ ስራ ሊያሰራው ቀርቶ ለህይወቱም አስጊ ሆነ። ይሄኔ ሁሉንም ርግፍ አርጎ ዐይኖቹን ወደ ሰማይ በማቅናት "ፈጣሪዬ ሆይ ከዚህ በሰላም ካወረድከኝ በኪሴ ያለውም 50 ብር አምጥቼ አስገባለሁ" ሲል ይሳላል
ወድያው ይህን ተናግሮ ሲጨርስ ነፋሱ ይቆምና በሰላም ይወርዳል። ነገር ግን እግሩ መሬት ሲነካ ፍርሃቱ ሁሉ በኖ ስለጠፋ 50 ብሩን ለማስገባት ሳስቶ ምክንያት ይፈልግ ጀመር
"አዎ በርግጥ ከዚህ ዛፍ ላይ ካወረድከኝ ብዬ ተስያለሁ ነገር ግን የወረድኩት እኔ ራሴ ነኝ። ተሸክሞ ያወረደኝ ሳይኖር ለምንድነው 50ብሬን የማወጣው"  ብሎ እራሱን በማሳመን ወደ ቤቱ ጉዞ ቀጠለ።
ዳሩ ግን ትንሽ እየተራመደ ትከሻው ቀለለውና ቢዳብሰው መጥረብያው የለም። መጥረብያው ከዛፉ ጫፍ እንደተሰካ ነው። አሁንስ ምን ይል ይሆን።
የሰው ልጅ ፍጡር ነው ሁሌ ከፈጣሪ እጅ አይወጣም እንድያው ይመስለናል እንጂ ያለ እግዚአብሔር መኖር አንችልም። ያለእኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም ይለናል ዮሐ 15፣5

@aleroe
ኤልሮኢ:

"ምዕመናን በቤተመቅደስ ሊኖራቸው የሚገባ ሥርዓት

፦በቤተክርስቲያን ቅፅር ግቢ ገበያ ክልክል ነው። /ማቴ 21፡12 ዮሐ 2፡13-18 ፍትሀነገስት አንቀጽ 1/

፦በቤተክርስቲያን ቅፅር ግቢ ግብዣ ማድረግ፣መብላት፣መጠጣት ክልክል ነው። /የሎዶቅያ ሲኖዶስ (ዶቅ) 44 ፍ.ነገ 1/

፦ማንኛውም መብልም ሆነ መጠጥ ከቤተ መቅደስ 40 ክንድ(20 ሜትር) መራቅ አለበት! በመቅደሱ ሕብስቱና ወይኑ ብቻ ይፈተታልና። /ፍ.ነገ 1/

፦በታቦቱ ፊት ለመስገድ ወይም ለመፀለይ ወይም ለማስቀደስ ካልሆነ በቀር ማንም ወደ ቤተመቅደስ ገብቶ እንዲቀመጥ አይፈቀድም

፦ከካህን በስተቀር(ዲያቆናት፣ካህናት፣ቀሳውስት፣ጳጳሳት..) ከምዕመናን ወገን ወደ መቅደስ(ታቦቱ ያለበት) ገብቶ ሥጋ ወደሙን ሊቀበል(ሥጋ ወደሙን የሚያቀብሉ ካህናት ራሳቸው ሁሌም ከማቀበላቸው በፊት በመቅደስ ውስጥ ይቀበላሉ) ታቦቱን ሊጠጋ አይገባም /ፍ.ነገ 1፣ ቀኖና አብሉዲስ ፣ኢያሱ 3፡4/

፦ሴቶች ወደመቅደስ (ታቦቱ ያለበት) እንዲገቡና እንዲፀልዩ አልተፈቀደም። /የሎዶቅያ ሲኖዶስ(ዶቅ) 44፣ ፍ.ነገ 1/

፦ከቤተ ክርስቲያን አንዴ ለአገልግሎት ተመርጦ የገባውንና የተቀደሰውን ንዋየ ቅድሳት እንደገና ወደውጭ አውጥቶ መጠቀም አይገባም። /ፍ.ነገ 1፣ 1ቀለሚንጦስ (ረስጣ) 28/

፦ያላመኑ፣ ያልተጠመቁ፣ ተወግዘው የተለዩ ወደ ቤተክርስቲያን እንዳይገቡ ተከልክሏል። /ፍ.ነገ 1፣ ድድስቅሊያ (ድስቅ) 12/

፦ለፀሎትና ቅዱስ ቁርባን ለመቀበል ወደ ቤተክርስቲያን በሚኬድባቸው ዕለታት፣ በጾምና በሰንበት፣ በበዓላት ወቅት ወንድና ሴት ግንኙነት ክልክል ነው። /ዘፀ 19፡15፣ 1ቆሮ 7፡5-7/ (ለባለትዳር ብቻ ነው! ያላገባማ በየትኛውም ጊዜ ከጋብቻ በፊት አይፈቀድም)

፦ነውር ያለበት ወደ ቤተክርስቲያን አይገባም። /ፍ.ነገ 13/

፦ሴት ልጅ ወር አበባዋ ሲመጣ ለ7 ቀን፣ ስትወልድ ወንድ ከወለደች እስከ 40 ቀን፣ ሴት ከወለደች እስከ 80 ቀን ወደ ቤተመቅደስ መግባት አይፈቀድም። (ዘሌ 12፡1__፣ ዘሌ 15፡19-28፣ ፍ.ነገ 6፣ ዘኒቂያ 29)

፦ወንድም ቢሆን ከአፉ ወይም ከአፍንጫው የሚወጣ ፈሳሽ ፣ነስር ሲኖርበት ወደ ቤተ መቅደስ አይገባም! ይህም ቤተመቅደሱን ስለሚያረክስ ወይም ለሌላ #ሳይሆን በቤተ መቅደስ ውስጥ የክርስቶስ ደም ብቻ መፈተት ስላለበት ነው።

፦ወንድ ልጅ ሕልመ ሌሊት ከመታው(ህልመ ዝኔት ካየ(ስጋዊ ህልም ካየ) በዕለቱ ወደ ቤተ መቅደስ አይገባም። (ዘሌ 15፡2)

፦ጠዋትና ማታ ቤተክርስቲያን ለመሳለም መትጋት ያስፈልጋል። (ምሳ 8፡34)

፦ወደ ቤተክርስቲያን ሲገባ በቅፅረ ቤተክርስቲያን በር ላይ ሲደርሱ መሳለም ይገባል (መዝ 28፡2፣ መዝ 95፡9፣ ኤር 26፡2፣ ሕዝ 46፡3)

፦ወደ ቤተክርስቲያን (ቤተመቅደስ) ሲገቡ ጫማን አውልቆ ወገብን ታጥቆ አደግድጎ መግባት ይገባል። (ዘፀ 3፡5-6 ፣ ሐዋ 7፡33፣ ኢያሱ 5፡15፣ ፍ.ነገ 12)

፦በቤተክርስቲያን ውስጥ ተስለው የሚገኙ ቅዱሳን ሥዕላትን እጅ መንሳትና መስገድ ይገባል።

፦በቤተክርስቲያን ውስጥ መሳቅ፣ ስለ ዓለማዊ ነገር መነጋገር ክልክል ነው። /ዮሐንስ አፈወርቅ 19፡32 ፤ 48፤6 አቡሊዲስ 7/

፦አጭር፣ ያደፈ፣ የሰውነት ቅርጽን የሚያሳይ ልብስ ለብሶ ወደ ቤተክርስቲያን መሔድ ፈጽሞ የተከለከለ ነው /ዘፀ 19፡10 ፣ ዮሐ.አፈ 4፡49-72/


ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

@aleroe
ኤልሮኢ:
#ሁሉም_በምክንያት_ነው

ለስራ ሲሄዱ አባት ከልጁ ጋር
ሲደክማቸው አረፉ በአንድ የሾላ ዛፍ ስር
ትንሽም ሳይቆዩ ልጅየው ለማረፍ መሬት ላይ ተንጋሎ
አባቱን አላቸው የሾላውን ፍሬ በደንቡ አስተውሎ
አባቴ ተመልከት አምላክ ግን ሞኝ ነው
እንዴት ባክህ ልጄ ምን እያልከኝ ነው
ይህንን በሚያህል ትልቅ ዛፍ
የጥበቡን ስራ ሲያሳርፍ
እፍኝ የማይሞላ ትንሽዬ ፍሬ እንዲያፈራ ፈጥሮ
ግን ለአቅመ ቢሱ ዱባ ትልቅ ፍሬን ፈጥሮ ታዲያ ሞኝ አይደለም ብሎ ሳይጨርሰው
አባት ጣልቃ ገብቶ ልጁን አቋረጠው
አምላክ አላማ አለው ሲፈጥረው ሁሉንም
በም/ክ ነው እንጂ በአጋጣሚ አይደለም
መቼም እንዳትገባ በፈጣሪ ስራ
ከዛሬ በኋላ እንዲህም አታውራ
ቢሆንም አባቴ አምላክ ልክ አይደለም
ብሎ ተናገረ ሳያስበው ምንም
ትክክል መሆኑን ሊያስረዳ ሲቃጣው
አንዲት ፍሬ ወድቃ ግንባሩን መታችው
አባትም አየና ይናገር ጀመረ
አልሰማም አልክ እንጂ ነግሬህ ነበረ
ልክ አንተ እንዳልከው ይሄ የሾላ ፍሬ ዱባን ቢያክል ኖሮ
ዛሬ ሞተህ ነበር አብቅቶልህ ኑሮ
ስለዚህ አትግባ በሱ ስራ ድንገት
ምክንያቱ ከገባህ ይከተላል ቅጣት

@aleroe
ኤልሮኢ:

ቀርበን እንስተካከል

አንድ ሰው ጸጉሩን ሊስተካከል ወደ አንድ ጸጉር ቤት ይሄዳል ተራው ደርሶም ጸጉሩን መስተካከል ይጀምራል:: በመካከልም ከፀጉር አስተካካዮ ጋር መጨዋወት ይጀምራሉ ::
ጸጉር አስተካካዮ :- ወንድሜ ግን እግዚአብሔር ያለ ይመስልሃል? ሲል ይጠይቀዋል
ተስተካካዮ :- "አዎና አለ እንጂ በደንብ ነዋ" ሲል ይመልስለታል
ጸጉር አስተካካዮ:- አይ አይ የለም ቢኖርማ ይህ ውሉ ተንኮለኛ ይህ ሁሉ ውሸታም ይህ ሁሉ አመንዝራ ይኖር ነበር? አየኸ የለም ማለት ነው:: ...ብሎ በኩራት ተነፈሰ.....................
ተስተካካዮም ግራ ገብቶት ዝም አለ በመጨረሻም ተስተካክሎ ሲጨርስ ልብሱን አራግፎ ገንዘቡን ከፍሎ ከጸጉር ቤቱ ይወጣ........
በመንገድም ሲሄድ ብዙ ሰዎች ጸጉራቸውን ሳይስተካከሉ ተንጨብርረዘው ሲሄዱ አየና በጣም ተገርሞ በፍጥነት ወደ አስተካካዮ ይመለሳል
ተስተካካዮ:-ወንድሜ በሀገሩ ጸጉር አስተካካይ የለም እንዴ? ...አለው
ጸጉር አስተካካዮ :-አረ ሞልተናል አንተንስ ያስተካከልኩክ እኛ ፀጉር አስተካካዮች ስላለን አይደለም እንዴ?.......... አለው
ተስተካካዮ :- ታድያ እናንተ ጸጉር አስተካካዮች ካላችሁ ለምን ብዙ ሰዎች ተንጨብረው ይዞራሉ ?...... ሲል ይጠይቀዋል
ጸጉር አስተካካዮ:- እሱ እንኳን የኛ ችግር አይደለም ለመስተካከል ወደኛ ካልመጡ ያለ ፍቃዳቸው ቆርጠን ልናስተካክላቸው አንችልም እነርሱ መቆረጥን ጠልተው ተንጨብርገው ስለዞሩ እኛ ጸጉር ቆራጮች የለንም ማለት አይደለም::
በጣም ጥሩ አየህ እግዚአብሔርም ሳይኖር ቀርቶ ሳይሆን እኛ ወደ እርሱ ቀርበን ከክፋታችን ሁሉ አስተካክለን ስላላልነው ነው !!:: ታስታው እንደሆነ መጻዕጉን እንኳን ልትድን ትወዳለህን ብሎ አስፈቅዶ ነው ያዳነው::

ኦኦኦ.........በጣም ልክ ነህ ይቅርታ አድርግልኝ
"ወደ ንሰሐ አባቶቻችን
ቀርበን እንስተካከል"

@aleroe
ኤልሮኢ:
​ነሐሴ 13/12/2010 ዓ.ም
ደብረ ታቦር
በዕለቱ ቅዳሴ ሰዓት የሚነበቡ መልዕክታት፣ወንጌልና ምስባክ።

ዲያቆን፦ ዕብ 11÷23-30
ንፍቅ ዲያቆን፦ 2 ጴጥ 1÷15-ፍ.ም
ንፍቅ ካህን፦ ግብረ ሐዋርያት፦ 7÷44-51
#ምስባክ ፦ መዝ 88፥12-14
ታቦር ወአርሞንዔም በስመ ዚአከ ይትፌስሁ ወይሴብሑ ለስምከ
መዝራዕትከ ምስለ ኀይል

#ትርጉም
ታቦር እና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል
ስምህንም ይመሰግናሉ
ክንድክ ከኃይልክ ጋር ነው

ወንጌል ፦ ሉቃ 9÷28-38
ቅዳሴ ፦ ዘእግዝእትነ

@aleroe
ኤልሮኢ:
{ደብረ ታቦር}

ደብረታቦር ተሞላ በግርማ
ብርሀን ከበበዉ
አሸብርቋል ረጅሙ ተራራ ክብሩ ሲያበራ
ጴጥሮስና ያእቆብ ደሞም ይዋንስ
ይዟቸዉ ተጉዋዘ የመረጣቸዉን
በፊታቸዉ ሳለ ድንገት ተለወጠ
እየሱስ ሲያበራ ልባቸዉ ቀለጠ
ሙሴና ኤልያስ ከሱ ጋር ታዪዋቸዉ
ጴጥሮስ በተመስጦ ዳስ እንስራ አላቸዉ
ቅጥሩን የገመሰ አይመችም ሌላ
ክርስቶስ ነዉና እዉነተኛ ተድላ
በርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይሄ ነዉና
ስለመዳናችሁ ስሙት በፅሞና
ይሄው ሲመሰክር ከሰማይ ንጉሱ
ከእየሱስ በቀር አላዪም ሲነሱ
ተገለጠ በግርማ ሸሸ ጨለማ
እንደፀሀይ ሲያበራ ማነዉ ማይፈራ
ሆያሆዬ
የተሰቀለዉ በክብር ይመጣል
ሰማይና ምድር በቃሉ ያልፋል
ከማድጋችሁ ይጠመቅ ወይኑ
አንተን እንጠብቅ ቅርብ ነዉ ቀኑ
ድምፅህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄዉ ብርሀን ለኛ በራልን
የቃሉን ሙልሙል እንሞልሙለዉ
ከዜማችን ጎን እንድንለኩሰዉ
የምነት ደመራ ይደመርና
ለከርሞ ያድርሰን ይለኮስና
አመት አዉዳመት
የማምዬን ቤት ፍቅር ይፍሰስበት
ያባብዬን ቤት ሰላም ይብዛበት
መልካም ቡሄ

@aleroe
ኤልሮኢ:
ማርያም ዐርጋለች

ማርያም አርጋለች ወደ ገነት (2)
የሰማይ መላእክት እያጀቧት
እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታለች
የአባቷ ዳዊትን ትንቢት ልትፈጽም
ወርቁን ተጎናጽፋ በቀኙ ልትቆም
ወደ አምላክ ማደሪያ ወደ ሰማያት
ዐረገች በእልልታ ድንገል የኛ እናት
ዐርጋለች ማርያም ተነሥታለች

ማርያም አርጋለች ወደ ገነት (2)
የሰማይ መላእክት እያጀቧት
እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታለች
ሰማይም ይከፈት ደመናም ይዘርጋ
ዝምታ አይኖርም እመ አምላክ ዐርጋ
አንደበት ይከፈት ማርያምን ያመስግን
ከዘለዓለም ጥፋት በምልጃዋ እንድንድን
ዐርጋለች ማርያም ተነሥታለች

ማርያም አርጋለች ወደ ገነት (2)
የሰማይ መላእክት እያጀቧት
እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታለች
የአምላክ ማደርያ ያ ቅዱስ ሥጋሽ
አምላክን ያቀፉት እነዚያ እጆችሽ
ሙስና መቃብር ይዞ አላስቀራቸው
ተነሥተዋል በክብር በእምነት አየናቸው
ዐርጋለች ማርያም ተነሥታለች

ማርያም አርጋለች ወደ ገነት (2)
የሰማይ መላእክት እያጀቧት
እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታለች
ሐዋርያት አበው እንኳን ደስ ያላችሁ
በክብር ዐረገች ማርያም ሞገሳችሁ
ወደ ዓለምም ውጡ ሰበኗን ይዛችሁ
የድንግል ዕርገቷን ንገሩ ተግታችሁ
ዐርጋለች ማርያም ተነሥታለች

@aleroe
ኤልሮኢ:

“መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡” ምሳ. 31፡29

ክርስቶስን ያከበሩ፤ መንገዱን የተከተሉ ብዙ ሴቶች አሉ፤ እውነትን የመሰከሩ፤ ስለ ቃሉ የኖሩ ብዙ ሴቶች አሉ፤ መስዋዕትነትን የከፈሉ በሰማዕትነት ያለፉ ብዙ ሴቶች አሉ፤ ታላላቅ የምድር ነገስታትን፤ ታላላቅ ነቢያትን የወለዱ ብዙ ሴቶች አሉ፤ ከነዚህ ሁሉ ግን አንቺ ትበልጫለሽ፡፡

ቅድስት ድንግል ሆይ አንቺ እኮ፡- ሰማይ ዙፋኑ ምድር መረገጫው የሆነ፤ ድንቅ መካር ኃያል አምላክ የሰላም አለቃ፤ ሁሉ በእርሱ የሆነ ከሆነውም አንዳችም እንኳን ያለርሱ ያልሆነ፤ ዓለምን ሁሉ ከሞት ወደ ሕይወት የመለሰ፤ መንበሩን የሚሸከሙ ኪሩቤልና ሱራፌል የሚንቀጠቀጡለት፤ የሁሉ ፈጣሪ፤ የሁሉ አምላክ እናት ነሽ፡፡ በፊትም አሁንም ወደፊትም ካንቺ በቀር ፈጣሪዋን ልጄ ብላ የምትጠራ ሴት አልነበረችም፤ የለችም፤ አትኖርምም ክርስቶስም እናቴ ብሎ የሚጠራት ብቸኛዋ ሴት አንቺ ነሽ በእውነት ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡

እናት ስትሆኝ ድንግል፤ ድንግል ስትሆኝ እናት በእውነት ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡ ትውልድ ሁሉ ብጽዕት ብሎ የሚጠራሽ ብቸኛዋ ሴት በእውነት ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡ እግዚአብሔር መርጦና ጠብቆ ያስቀረሽ ዘር በእውነት ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡ ለዓለም ሁሉ ድህነት ምልክት የሆንሽ በእውነት ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡

እናቴ ሆይ እንግዲህ እኔ ምን ልናገር? ሺህ ቃላትን ብደረድር ያንቺን ክብር ልገልፀውስ እንደምን እችላለው? አዎ አሁንም እላለሁ “መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡” ምሳ. 31፡29
የቅድስት ድንግል ማርያም በረከቷ በሁላችን ላይ ይደር፤ ምልጃ ቃል ኪዳኗ ይጠብቀን፡፡ አሜን!!!

@aleroe
ኤልሮኢ:
✞ እናት አለኝ ✞

እናት አለኝ የምታስብ እንባ
አያታለሁ ስወጣ ስገባ
ኪዳነ ምህረት ኪዳነ ምህረት
አንባ መጠጊያ ናት


ሔዋን ሰታኝ ከበለሱ ፍሬ
እራቁቴን ብቆምም አፍሬ
ልብሴን ይዘሽ ወደኔ መተሻል
ደጓ እናቴ ቤቴን አድምቀሻል

አዝ------

ለዘለዓለም ንጽህት በመሆኗ
ከእኔ ጋር ነው ህያው ቃልኪዳኗ
ደስተኛ ነኝ ሃዘኔን አልፌ
አጽናኝ ሆናኝ የመስቀል ስር ትርፌ

አዝ---------

ከጥፋቱ ውሃ ማረፊያዬ
መርከቤ ነሽ ከሞት ማምለጫዬ
የአምላክ እናት ምልጃሽ ሆኖኝ ክብሬ
በሕይወት አለሁ ጥልቁን ተሻግሬ

አዝ-----

በእናትነት ሕይወቴን ጎብኝታው
ልቤ አረፈ ተነቅሎ በሽታው
ሰንሰለቴ ከእጄ ተቆረጠ
መራራዬን በልጅሽ ጣፈጠ

@aleroe
ኤልሮኢ:

ልጅ መንጃ ፍቃድ ያወጣና አባቱ ጋር ሄዶ
ልጅ፦ አባዬ መኪና ግዛልኝ?
አባት፡-ሶስት ነገሮችን ካሟላህ እገዛልሃለሁ 1. የትምህርትውጤትህ ከ 80 አቬሬጅ በላይ ከሆነ 2.መጸሃፍ ቅዱስን አዘውትረህ ካጠናህና 3. ይሄን ራስታ ጸጉርህን ከተቆረጥክ
እገዛልሃለው ይለዋል፡፡ ልጅና አባት በዚህ ይስማማሉ
ከስድስት ወር በኋዋላ
:
ልጅ፡:- አባዬ ሁሉንም ነገር በሚገባ አሟልቻለሁ አሁን መኪና ግዛልኝ?
አባት፡- ውጤትህ በጣም ተሻሽሎ ከ 80 በላይ ሆኑዋል መጸሃፍ ቅዱስም አዘውትረህ እያነበብክ ነው ግን ጽጉርህን አልተቆረጥክም!
ልጅ:- ታውቃለህ አባዬ በመጽሃፍ ቅዱስ ንባቤ ሳምሶን፤መጥምቁ ዮሃንስ፤ሙሴ ጸጉራቸውን ያሳድጉ ነበር ለዛ ነው።
አባት:- ጎበዝ ልጄ፧ ታዲያ አሁን የጠቀሰቃቸው ቅዱስ ሰዎች በሙሉ በእግራቸው እንጂ በመኪና እንዳልሄዱስ አስተውለሃል!?
:
ምን ለማለት ፈልጌ ነው

እራስህን ከሌላ ሰው ጋር አታፎካክር፦ ሁላችንም እንደ አሻራችን ሁሉ ባህሪያችን እና ፍላጎታችንም በጣም ይለያያል። ደስታን ከሚያጠፉ ምክንያቶች አንደኛው እራስን ከሰው ጋር ማፎካከር ነው። አሳ ደስታዋን እንደ ወፍ በሰማይ ልፈልግ ብትል፤ ወፍ ደግሞ እንደ አሳ በውሃ ውስጥ ልፈልግ ብትል፤ ሁለቱም ሳይደሰቱ ይቀራሉ። ስለዚህ ደስታህን በራስህ መለኪያ ለካው። አንተ በሌሎች ስትቀና ሌሎችም ባንተ እንደሚቀኑ እወቅ። በዚህ ምድር ላይ ሌላውን ለመምሰል እንደ መሞከር ከበድ ነገር ምን አለ? ሌላውን ለመምሰል ስትሞክር፤ የምትጣላው ከሰው ጋር ሳይሆን ከገዛ እራስህ ጋር ነው።
ማስተዋልን ይስጠን!
@aleroe
ኤልሮኢ:
#ፍቅር_ማለት

ያን_ሁሉ መስዋእት ያን ሁሉ ግርፋት
ልጅን_ከአባት ጋር አባትን ከልጅ ጋር
           አስታርቆ ለማየት ፤
እኔ ያ ሰው ነኝ የከበረ ዋጋ የተከፈለበት
እኔ ያ. ሰው ነኝ በደሙ_ታጥቤ
 ነፃ የሆንኩበት ፤
ታድያ ለዚህ ከንቱ አለም ላልወደደው
         በትንሽነቱ ሰው ሁሉ ለናቀው ፤
እንዴትስ ተገብቶት ጌታ ሊሞትለት
እንዴትስ ተደርጎ ክብሩን ሊተውለት ፤

ይህ_ፍጡር ማን ቢሆን ነው ከቶ
የሰማዩን_ንጉስ ግዛቱን አስትቶ
በሀጥያቷ ክርፋት ወደ ገማች ምድር
ጠርቶና ጎትቶ ፤
ሞትን_ያቀመሰው የትኛው ፍቅር ነው
የቱ ቅድስና የቱ ማንነቴ የቱ ንፅህና ፤
ንፁህ_የሆነውን ፅድቅ የለበሰውን
ስጋ ያለበሰው ሀጥያት ያደረገው
የቱ እኔነቴ እሱነቱን ትቶ እንዲያ
ሚያዋርደው ? ፤

ያንን_ፍቅርማ ቃላት ተቆፍረው
ያንን_መውደድማ ፊደላት ተጣምረው ፤
ከቶ አይገልፁትም ፍፁም አይደርሱትም
ብርሀን አያደምቀው ጨለማ አይጋርደው
የቀናት መገስገስ የአመታት መንጎድ
        ዘመን የማይሽረው ፤
ፍ ቅ ር ማለት ያ ያ ነው
ፍቅር_ውልደቱ ነው ፍቅር መከራው ነው
ፍቅር_መሞቱ_ነው ፍቅር ትንሳኤው ነው ፤
በዘመን ጅማሬ በዘመን ፍፃሜም
የፍቅር  ስንኙ   የፍቅር ሀረጉ
         ኢ  የ  ሱ  ስ ብቻ ነው !
__________________
@aleroe
ኤልሮኢ:
ተስፋችን ነህ አንተ

ተስፋችን ነህ አንተ እስከ ዘላለም(2)
የድንግል ማርያም ልጅ መድኃኔዓለም(2)
ደምህን አፍሰህ ስጋህን ቆርሰህ(2)
ብሉ ጠጡ ብለህ ለዓለም ሰጠህ(2)
አእላፍ መላእክት የሚቀድሱህ(2)
ቀራንዮ ታየህ በመስቀል ሆነህ(2)
ተገርፈ ተሰቅለህባትሆን መድኃኒት(2)
እንኖር ነበረ ሰልጥኖብን ሞት(2)
በቆረስከው ስጋህ ባፈሰስከው ደምህ(2)
ቤቱ ተመለሰ ቁስለኛው አዳም(2)
በጎነት ሳይኖረን እንዲሁ ወደድከን(2)
ሞታችንን ወስደህ ህይወትን ሰጠኸን(2)
ሞትን አሸነፍን ሀይላችን ታደሰ(2)
የጥሉ ግድግዳ በመስቀል ፈረሰ(2)
ግርግም አስተኝቶ በመስቀል የዋለ(2)
እንዲ ያለ ፍቅር ከቶ ለማን አለ (2)
የበደሉት ሁሉ ፀደቁ በደሙ(2)
ነጭ ልብስን ለብሰው ከሰርጉ ታደሙ (2)
የዘላለም ህይወት እንድናገኝ ሆነ(2)
በመድኃኔዓለም ሁሉ ተከወነ(2)

@aleroe
ኤልሮኢ:

አላማህን ለማሳካት ያለህን አቅም ሁሉ ተጠቀም!-;

አባትና ልጅ በጫካ ውስጥ በመጓዝ ላይ ሳሉ ልጁ አባቱን ጥያቄ ይጠይቀዋል። "አባቴ ይህን ዛፍ ብገፋው ቅርንጫፎቹን ማነቃነቅ አልችልም?" አለው። "እንዴታ! ሙሉ አቅምህን ተጠቅመህ ከሞከርክ የማትችለው ነገር የለም።" ሲል መለሰለት። ልጁም ሙከራውን ጀመረ። ይሁንና ግን ዛፉ ትልቅ በመሆኑ ቅርንጫፎቹን ሊወዘውዝ አልቻለም።
"አባቴ ተሳስተሀል። እኔ ይህን ማድረግ አልችልም" አለው።
"እንደገና ሞክር!" አለው አባቱ።
ልጁ የቻለውን ያህል ዛፉን ቢገፋም ቅርንጫፎቹ አልነቃነቅ አሉ። ብዙ ሞከረ ግን አልሆነም። "አባቴ አልችልም!" አለው ተስፋ በመቁረጥ።
አባቱም "ልጄ አቅምህን በሙሉ ተጠቀምና ሞክር ነበር ያልኩህ ግን አላደረከውም" ሲል መለሰለት።
"ከዚህ በላይ?" ልጁ ግራ ተጋባ።
"አዎ! እኔን መች ለእርዳታ ጠየከኝ?" ሲል ያልጠበቀውን ምላሽ መለሰለት።
በዙሪያችን ያሉትን አማራጮች፣ እድሎች፣ ድጋፎች፣ ተስፋዎች፣ ብርታቶች...ሳንጠቀም አንድ ነገር "አልተሳካልኝም!" ብለን ተስፋ መቁረጥ አይገባንም። ማንም በራሱ ሙሉ አይደለም። ድጋፍ ይፈልጋል፣ እርዳታ ይፈልጋል። በሌላው ተስፋ አለመቁረጥ ውስጥ፣ በሌላው ብርታት ውስጥ፣ በሌላው መጽናናት ውስጥ ሀይላችንን ልናገኘው እንችላለን። .......እርዳታ የጠየቅናቸው ሰዎች ባይተባበሩን የተሳሳተ ሰው መጠየቃችንን እንጂ፣ ወይም አጠያየቃችንን መለወጥ እንዳለብን እንጂ፣ ወይም በሌላ ጊዜ መጠየቅ እንዳለብን እንጂ እርዳታ መጠየቃችን ነውር ነው ማለት አይደለም። በዙሪያችን ያለውን እድል ሁሉ አሟጠን መጠቀም ለህልማችን መሳካት መሰረት ነው።

@aleroe
ኤልሮኢ
#ፆመኛ_ነኝ!

ከምግብ እርቄ
ሰዓቷን ጠንቅቄ
ሥርዓት አከብራለሁ
ከሥጋ ከወተት ንክች አላደርግም በደንብ እጾማለሁ
በእርግጥ ወዳፍ ሚገባ ነውና የማያረክስው
ጾምን ባልበላበት ሰዶቤበታለሁ
እጄ ሥጋም ባይዝ ሰውን ይጠቁማል
ሰው ይወነጅላል
እግሬ አመድ ሆኖበቅቤ ባዮወዛም
ወደ ጥፋት መንገድ መሮጡ አልቀረም
የውስጡ አካሌ ያ ድብቁ ነገር
ያ የልቤ ወዳጄ ቅቤና ቅባቱ
አልፎ ባይነካካው እዚያ ተደብቆ
ሰዎች ላይ ለማሴር
ክፋት ለማውጠንጠን
እንደምን ይሳነው!
አዎን ይሄ ሳይቆጠር
በርግጥ እጾማለሁ
ነጠላ አድርጌ
ቅዳሴ አስቀድሼ
በአንድ እግሬ ቆሜ
ጸሎት አደርሳለሁ
አዎን ጾመኛ ነኝ
በደንብ አከፍላለሁ
ሩጫዬን ያለግብ እደመድማለሁ።


@aleroe
ኤልሮኢ:

​ነሐሴ 26/12/2011 ዓ.ም
መዝሙር "ይሁበነ ዝናመ"

በዕለቱ ቅዳሴ ሰዓት የሚነበቡ መልዕክታት፣ወንጌልና ምስባክ።

ዲያቆን፦ ዕብ 3÷1-ፍ.ም
ንፍቅ ዲያቆን፦ ያዕቆ 5÷1-12
ንፍቅ ካህን፦ ግብረ ሐዋርያት፦ 22÷1-22

#ምስባክ፦ 144÷16

ዐይነ ኲሉ ነፍስ ይሴፎ ኪያከ
አንተ ትሁቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ
ትሰፍሕ የማነከ ወታጸግብ ለኲሉ እንስሳ ዘበሥርዓትከ።

ትርጉም፦

የሰው ሁሉ ዐይን አንተን ተስፋ ያደርጋል
አንተ ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ
ቀኝህን ትዘረጋለህ በሥርዓትህ ለሚኖሩ እንስሳ ሁሉ ታጠግባለህ

ወንጌል፦ ዮሐ ፮፥፵፩ - ፍጻሜ

ቅዳሴ፦ ዘኤጲፋንዮስ

👉 @aleroe
ኤልሮኢ:
ለእኔስ ወደ እግዚአብሔር

ለእኔስ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ይሻለኛል /2/
መታመኛዬ እርሱ ነውና ይገባዋል ክብርና ምስጋና

ፍቅሩን እያሰብን እንቅረብ ወደ እርሱ
ይምረናልና መሐሪ ነው እርሱ
በልባችን ይንገሥ ይግባ ከቤታችን
የሕይወታችን ዋልታ እርሱ ነው ተስፋችን /2/

ከቶ አላገኝም እርሱን የሚመስል
ነፍሴን የሚያከብራት የሚሰጠኝ ሃይል
በመከራ ሰዓት ከክፉ የሚያድነኝ
ከየት አገኛለሁ መጠጊያ የሚሆነኝ /2/

የለመለመ መስክ መሸሸጊያዬ ነው
በሰላም ወጥቼ ሰላም እገባለሁ
ተስፋዬ እርሱ ነው ይጠራኛልና
ዘወትር አቀርባለሁ ክብርና ምስጋና
ዘወትር አቀርባለሁ ለአምላኬ ምስጋና

እኔስ ይሻለኛል መቅረብ ወደጌታ
ጋሻዬ ነውና የነፍሴ አለኝታ
ስለዚህ እቀርባለሁ አልርቅም ከደጁ
ጠግቤ እኖራለሁ በበረከት እጁ /2/

@aleroe
ኤልሮኢ:
#ጎርፍና_ግፍ

አንድ ሰው የጠፋች የአካባቢው ግመል ፍለጋ ጫካ ይገባል፡፡ ከብዙ መከራ በኋላ ያቺን ግመል አግኝቶ ከተማ ገባና ግመሏን ለባለቤቱ ሳይመልስ ሐሳቡን ቀይሮ ራሱ ያልባትና ይጋልባት ጀመር፡፡ ግመሏን ከአውሬ ለማዳን ጫካ ገብቶ የነበረው ሰውዬ እርሱ ራሱ ግመሏን መውሰዱ ብዙዎችን አስገረማቸው፡፡ ትንሽ ቆየና ከዚያች ከአንዷ ግመል ወተት እያለበ በግመሏ ላይ ተቀምጦ እየዞረ ለአካባቢው ሰው ወተት መሸጥ ጀመረ፡፡ ነገር ግን የግመሏ ወተት በአንድ ጊዜ ሀብታም ሊያደርገው አልቻለምና ሌላ ነገር አሰበ፡፡ በወተቱ ውስጥ ውኃ እየጨመረ ቀላቅሎ መሸጥ፡፡ ‹‹ሰውም ምነው የሰውየው አመሉም ወተቱም ተቀየረሳ›› እያለ ዝም ብሎ ይገዛ ጀመር፡፡ (ይገዛ የሚለው ቃል ጠብቆ እንዳይነበብ አሳስባለሁ)
ሰውዬውም በግመል ወተቱ ላይ ውኃን እያበዛው፤ የግመሉም ቁጥር እየጨመረ ሄደ፡፡ እየቆየም በግመልና በግመል ወተት ከሚታወቁት የሀገሩ ነጋዎች በላይ እኔ ነኝ ያለ፣ ቢጠሩት የማይሰማ ሀብታም ሆነ፡፡ የአካባቢው ሰዎችም ‹‹ይኼ ሰው ትናንት ምንም አልነበረውም፡፡ የጠፋ ግመል ሊፈልግ ጫካ ገባ፤ ተመልሶ መጣ፤ ከተማ ገባ፤ በአንድ ጊዜ ተመነደገ›› እያሉ ይገረሙ ነበር፡፡ ወተት ብቻ ተሽጦ እንዴት በሁለት ዓመት ሦስት መቶ ግመል ሊገዛ ቻለ፡፡ የሚለው የሕዝቡ ሁሉ ወሬ ሆነ፡፡
ሰውዬው ግን ምንም አልመሰለው፤ በወተቱ ውስጥ ውኃውን እየጨመረ ቀጠለ፤ እንዲያውም እበላ ባይ ቱልቱላዎችን ቀጠረና የእርሱ ወተት ሰው ጠጥቶት የማያውቅ መሆኑን እንዲለፍፉ አደረ፡፡ አንዳንድ ጊዜ እንዲያውም ወተቱን ለመልኩ ብቻ ይጨምርበትና የቀረው ውኃ ያደርገው ነበር፡፡ ‹‹ኧረ ሕዝቡ እያማረረ ነው፤ በአንድ በኩል በድንገት ተነሥህ፤ ከተማ ገብተህ ቢጠሩህ የማትሰማ ሀብታም ሆንክ፤ ይኼንን ስንታገሥህ ደግሞ ወተቱን ቀንሰህ ውኃውን እያበዛህ መሸጥ ጀመርክ፡፡›› ሲሉት ‹‹ተውት ባካችሁ፣ ለመሆኑ የእኔን ወተት ከመግዛት ውጭ ሕዝቡ ምን አማራጭ አለው፤›› ይል ነበር፡፡
በወተቱ ውስጥ የሚጨመረው ውኃም እየበዛ፣ ግመሎቹም እየበዙ ሄዱ፡፡ ግመሎቹም ሀገሩን ሞሉት፡፡ የሚያድሩበትና የሚግጡበት ልዩ የከተማ መሬት ተሰጣቸው፡፡ ወንዝ ዳር የሚገኝ ለም መሬት፡፡
አንድ ቀን ሸበሌ ወንዝ አጠገብ ግመሎቹን አሠማርቶ እርሱ አንድ ዛፍ ጥላ ሥር ሻሂ ከልጁ ጋር ይጠጣ ነበር፡፡ በዚህ መሐል ከደጋ የዘነበ ዝናብ ወንዙን ሞላውና በግራ በቀኝ ሲግጡ የነበሩትን ግመሎች ጠራርጎ ወሰዳቸው፡፡ የጎርፉን ድምጽ ሰምተው አባትና ልጅ ከጥሻው ሲወጡ ግመሎቻቸው ሁሉም ተወስደዋል፡፡ እሪታውን ሰምተው የተሰበሰቡ የሀገሩ ሰዎችም በአግራሞት የሆነውን ነገር ይመለከቱ ነበር፡፡
‹‹አየህ›› አሉት አንድ አዛውንት ‹‹ያ በወተቱ ላይ እየጨመርክ የሸጥከው ውኃ ተጠራቅሞ፣ ተጠራቅሞ ጎርፍ ሆኖ ግመሎቹን ወሰዳቸው፡፡ ግፍ እንደዚህ ነው፡፡ ሲሠራ ቀላል ይመስላል የተጠራቀመ ዕለት ግን ጎርፍ ሆኖ ይወስዳል፡፡ ተው ብንልህ አልሰማ ብለህ ነበር፤ አንተ በግፍ ግመል ስትሰበስብ የግፉ ውኃ ሌላ ቦታ እየተሰበሰበ መሆኑን ረስተህዋል፡፡ ቀን ጠብቆ ግን ይሄው ጎርፍ ሆኖ መጣ›› አሉት፡፡

@aleroe
ኤልሮኢ:
ስውር_ቅኔ


የቤተ_ክርስትያን ደጅ ዕለት ተለት ስሜ
በፆም_በፀሎት በስግደት ደክሜ
አምላኬን ለመንኩት
የሚያስፈልገኝን ዘርዝሬ ነገርኩት
የሚያስፈልገኝ ነገር ቢዘገይ ጊዜ
ነፈከኝ ብዬ በምሬት አንካሴ
ፈጣሪን_ወጋሁት
ልቡን_አደማሁት
በስርዓት_አጥ_ምሬቴ
በአጉል እምነቴ
ልቡ ስለቆሰለ
በደመና_መሀል ጌታዬ እንዲህ አለ
‹‹ ሁሉን የማቀው እኔ ሆኘ ሳለ
ነፈከኝ ለማለት ምነው ልቦናህ ቸኮለ
ዘርዝረህ የላከውን የልመና ፀሎት
ይመለከት ዘንድ ዐይኔ ተተከለ
የምትፈልገው እንጅ የሚያስፈልግህ አንድም እንደሌሌ
የታዘበው እጄ የጠየከኝን ከማድረግ ተከለከለ
ግና ልጄ አዕምሮህ በደንብ ካሰተዋለ
ባለማድረግ ውስጥም ታላቅ ማድረግ አለ>>
_________________
@aleroe
ኤልሮኢ:
"እኔ ነኝ"

ሁለት ዳክዬዎችና አንድ እንቁራሪት ጎደኛሞች ሆነው በአንድ ኩሬ ላይ እየተጫወቱ ክረምቱን በደስታ አሳለፎ:: በጋ ሲመጣ ኩሬው መድረቅ ጀመረ:: በዚህ ምክንያት ቦታ መቀየር እንዳለባቸው ሲረዱ አንድ ነገር አሳሰባቸው:: እነርሱ
መብረር ይችላሉ:: እንቁራሪቷ ግን አትችልምና ምን ማድረግ እንዳለባቸው ተጨነቁ::
በዚህ ጊዜ እንቁራሬት አንድ አሳብ አፈለቀች:: "እናንተ ዳር እና ዳር እንጨት ብትይዙ እኔ መሐሉ ላይ በአፌ ይዤ መኤድ እንችላለን ::"
አለች:: ዳክዬዎችም ሃሳቡን በደስታ ተቀብለው ዳርና ዳር እንጨት ይዘው እንቁራሪቷ መሀሉን ነክሳ በረራ ጀመሩ:: አንድ ገበሬ ድንገት ወደ ላይ ቀና ሲል ያያቸዋል በሁኔታው ተደንቆ"እንዴት ያሎ ዘዴኞች ናቸው ለመሁኑ ሃሳቡን ያፈለቀው ማን ይሁን?
" አለ እንቁራሪቷም ቀድሞውንም ይህን አሳብ በማፍለቋ ልቧ ኮርቶ ነበርና"እኔ ነኝ"ከማለቷ በአፏ የያዘችውን እንጨት ለቃ ተፈጥፍጣ ሞተች::እዚህ ላይ ታዲያ ሐዋርያው ያለውን ቃል ልብ እንበል "ብቃታችን ከእግዚያብሔር ነው እንጂ ከገዛ እጃችን እንደሚሆን አንዳች እንኳ ልናስብ ራሳችን የበቃን አይደለንም"/2ቆሮ 3÷5/

@aleroe