የጊንር ጽጌ ተዋህዶ ሰ/ት ቤት
287 subscribers
885 photos
16 videos
12 files
19 links
ይህ ቻናል ዓላማውን የሰንበት ት/ ቤቱን ጠቃሚ መረጃዎች እና መልእክት ማስተላለፍ አድርጎ ጥር 19/2012ዓም ሌሊት 6:50 ላይ ተከፈተ፡፡
Download Telegram
ዓርብ

የስቅለት ዓርብ ይባላል

ጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ የዋለበት ዕለት ነውና ማቴ ፳፯፥፴፭ የስቅለት ዓርብ ይባላል።

መልካሙ ዓርብ ይባላል

ከጌታ ስቅለት በፊት በተለይም በሮማውያን ህግ የወንጀለኛ መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል ጌታችን በደሙ ቀድሶ የምህረት፣ የሕይወት አርማ፣ የዲያቢሎስ ድል መንሻ ስላደረገው፤ በሞቱ መልካሙን ሕይወት ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ይባላል።

-----------------------------------------

“ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።” 1ኛ ዮሐንስ 4፥10

እንኳን አደረሳችሁ !!
"በላይ በሰማያት በኪሩቤል ክንፍ የምትከለለው በኢየሩሳሌም ግን የእሾህ አክሊል ተቀናጀህ".... ውዳሴ መስቀል....
"በባሕርዩ የማይመረመር እርሱ ጀርባዬን ለግርፋት ፊቴን ለጽፋት ሰጠሁ፤ ከማያሳፍር ምራቅም ፊቴን አልመለስኩም አለ"....ድርሳነ አትናቴዎስ....
አውቀውስ ቢሆን የክብር ባለቤት ጌታን ባልሰቀሉትም ነበር ሰማይ ዙፋኑ ምድር በእግሮቹ የተረገጠች ስትሆን ስለኛ በእንጨት ተሰቀለ
....ድርሳነ ማኅየዊ ዘዐርብ....
"ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ?" እንዳንባል [ሉቃ ፳፬፥፭] በሕያዊት ሥፍራ በቤተ ክርስቲያን እንጂ
ሕይወት ክርስቶስን፣ የሕይወትን እናት ድንግልን፣ ሕያዋን ቅዱሳንን- በሙታን መናፍቃን አዳራሽ፤ ሕይወት መንፈሳዊነትን- በዓለማዊነት ውስጥ፤ ... አንፈልግ!
+ የሚሮጥ ዲያቆን +
© ዲን ሄኖክ ኃይሌ

የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት ገደማ ነው:: አቧራማውን የጋዛ ምድረ በዳ በፈጣን ሩጫ እያቦነነ የሚከንፍ አንድ ወጣት ታየ:: ሩጫው የነፍስ አድን ሠራተኞች ዓይነት ፍጥነት ያለው ነበረ:: አንዲትን ነፍስ ሳታመልጠው ለማትረፍ እየከነፈ ነው:: የሚሮጠው ደግሞ በፍጥነት በሚጋልቡ ፈረሶች የሚጎተት የቤተ መንግሥት ሠረገላ ላይ ነው:: በሰው አቅም ፈረስ ላይ ሮጦ መድረስ ባይቻልም ይህ ወጣት ግን ፈረሶቹ የሚያስነሡትን የጋዛን አቧራ በአፉ እየቃመ በአፍንጫው እየታጠነ እንደምንም ደረሰ::
በሠረገላው ውስጥ አንድ ጸጉረ ልውጥ የሩቅ ሀገር ሰው ተቀምጦ በእርጋታ መጽሐፍ እያነበበ ነው::

እግሩን እንደ ክንፍ ያቀለለው ሯጩ ዲያቆን ፊልጶስ ይባል ነበር:: በዚያ ምድረ በዳ ብቻውን ሲሮጥ የሚያጨበጭብለት ሰው የሚሸልመው ደጋፊ አልነበረም:: እንዲያውም ልብ የሚሰብ ኀዘን ላይ ነበረ:: እስጢፋኖስ የሚባል አብሮት ዲቁና የተሾመ የቅርብ ጓደኛውን በድንጋይ ወግረው በአሰቃቂ ሁኔታ ከገደሉበት ገና አርባ ቀን አልሆነም:: "ቤተክርስቲያን ስደት ላይ ሆና ምን ስብከት ያስፈልጋል?" በሚል ቀቢጸ ተስፋ እጁን አጥፎ ያልተቀመጠው ፊልጶስ ግን የወንድሜን ኀዘን ልወጣ ሳይል የምሥራች ለማብሠር በበረሃ ሮጠ::

ቀርቦ ያናገረው ጃንደረባ ደግሞ "የሚመራኝ ሳይኖር እንዴት ይቻለኛል?" የሚል ኦሪትን ይዞ ትርጓሜ ፍለጋ የሚቃትት ፣ ጥላው ይዞ አካሉን ፍለጋ የሚጨነቅ ትምህርት የተጠማ ኢትዮጵያዊ ነበረ:: ስለዚህ ይህ ዲያቆን መዳን የምትሻውን የጃንደረባውን ነፍስ በመዳን እውቀት አረስርሶ አሁኑኑ ካልተጠመቅሁ አሰኛት:: ብቻውን የሮጠውና አንድ ሰው ያስተማረው ዲያቆን ፊልጶስ ሮጦ ያዳነው አንድ ሰውን ብቻ አልነበረም:: በአፍሪቃ ቀንድ ለምትገኘው ሀገር ኢትዮጵያና ሕዝቦችዋ የመዳን ቀንድ የሆነ ክርስቶስን አሳያቸው:: አንድ ኢትዮጵያዊ አጥምዶ በእርሱ ብዙዎችን ከማጥመድ በላይ ምን ሙያ አለ? ጴጥሮስን በጀልባው ላይ ከዓሣ አጥማጅነት ወደ ሰው አጥማጅነት የቀየረ አምላክ ገንዘብ ያዡን ባኮስ ነፍሳት ያዥ አድርጎ ሸኘው:: "የህንደኬ ሹም ባኮስ ሆይ ከአሁን ወዲህ በህንደኬ ገንዘብ ላይ ብቻ አትሠለጥንም ፤ የእግዚአብሔር ገንዘቦች የነፍሳት ግምጃ ቤት ላይ የሠለጠንህ የመንግሥተ ሰማያት በጅሮንድ አደርግሃለሁ" ብሎ ሾመው::

ይህ ከሆነ ሁለት ሺህ ዓመት አለፈ:: የጃንደረባው የልጅ ልጅ የኢትዮጵያ ሕዝብም ከሠረገላ አልፎ በፍጥነት በሚሔድ ብዙ ዓይነት መጓጓዣ ሊሳፈር ተሰለፈ:: ትዕግሥት አጥቶ በገንዘብ ላይ ከመሠልጠን ይልቅ ገንዘብ ሠልጥኖበት በፍጥነት ከነፈ:: አንዱ ፊልጶስ ብቻ ሮጦ የማይደርስበት እልፍ ሕዝብ ዛሬ ሠረገላውን አጨናንቆታል:: እንደ ጃንደረባው መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ሳይሆን ስልኩ ላይ ያቀረቀረ ፣ ስለ ትንቢት ትርጉም ሳይሆን ስለ ኑሮ ብልሃት የተመራመረ ትውልድ ተነሥቶአል:: የኢሳይያስ ትንቢት ስለማን ቢነግር የማይገደው የሕይወት ውጣ ውረድ ፍቺ የሚሻ ትንቢት የሆነበት ፣ በመንፈስ ጭንቀት የታወከ ምስኪን ትውልድ ተነሥቶአል:: በእርግጥ ይህ ትውልድ ከዚህ ጭንቀት ለመውጣት የሚመራው ሳይኖር እንዴት ይቻለዋል? ለዚህ ሁሉ ሕዝብ የሚሆን ፊልጶስ ከወዴት ይምጣ?

ኸረ የዲያቆን ያለህ? ነፍስ አድን ፊልጶሳዊ ዲያቆን ሆይ ከወዴት ነህ? ነፍሳትን ለማዳን የሚያሳድድ እንጂ የሥጋ ምኞቱን የሚያሳድድ ዴማሳዊ ዲያቆን አልጠፋም:: እንደ እስጢፋኖስ በድንጋይ የሚወገር ዲያቆን እንጂ ድንጋይ አንሥቶ የሚማታ ዲያቆን አልጠፋም:: ሰረገላ ላይ ሆነው ግራ የተጋቡ ባኮሶች ብዙ ናቸው የፊልጶስ ግን እጥረት አለ:: ችግራቸውን ፈትቶ ጥያቄያቸውን መልሶ የሚሰወር ከሠረገላ አልወርድም ብሎ የማያስቸግር ፊልጶስ ግን እጥረት አለ:: ከእናንተ ቀድመን በተሾምን ዲያቆናት አንገትዋን የደፋች ቤተ ክርስቲያን በእናንተ ቀና እንድትል እንመኛለን:: የሚሮጥ ዲያቆን ያድርጋችሁ:: ምእመናን እሱን ፍለጋ የሚሮጡለት ዲያቆን ሳይሆን ነፍሳትን ፈልጎ የሚሮጥ ዲያቆን ያድርጋችሁ:: ከመቅደሱ ጠፍቶ የሚፈለግ ሳይሆን ፈረስ የማያመልጠው ዲያቆን ያድርጋችሁ::
ሃምሳው ቀናት 

ሃምሳው ቀናት እንደ አንድ ቀን ሆነው ይታያሉ። ረቡዕና ዓርብ ሳይቀር አይጾሙም። ጠዋት ይቀደሳል፣ በጠዋት ይበላል። በሃምሳው ቀን ጾም የለም። የጾም ቀኖና አይሰጥም። 

እነዚህ ሃምሳ ቀናት ወጪ ገቢ በሆነው ወይም ሂያጅ linear ሓላፊ በሆነው አሁን ባለንበት ቀን አቆጣጠር Chronos በሆነው ጊዜ ሲታዩ ከሰኞ እስከ እሑድ እንዳሉት ቀናት ይኖራቸዋል  እንጂ በቤተ ክርስቲያን ወይም በትንሣኤ የቀን አረዳድ የማያልፈው ጊዜ (Kairos) ማሳያ ናቸው። 

ይኽ ዘመን አልፎ ከትንሣኤ በኋላ መምሸት መንጋት የጊዜ መፈራረቅ የለም ሰኞ ማክሰኞ የሚባል ቀን የለም። አንድ ሕይወት ነው የሚኖረው። ከትንሣኤ በኋላ ያሉት ሃምሳ ቀናት የዚያ ዘለዓለማዊ ሕይወት ማሳያ ናቸው። 

ሃምሳው ቀን ከትንሣኤ በኋላ ያለውን ሕይወት በጥቂቱ እየቀመስን ነው። “ነገር ግን ለዚሁ የሠራን እግዚአብሔር ነው እርሱም የመንፈሱን መያዣ ሰጠን” 2 ቆሮ.5:5 

መያዥ ማለት ቀብድ ነው። ከዋጋው ያነሠ ሆኖ እቃውን ለመግዛት ማስያዣ ነው። ቀብድ የከፈለ ሰው ሙሉ ዋጋውን ከፍሎ እቃውን ይወስዳል። ቀብድ መክፈል እቃውን ለመግዛት ማረጋገጫ ነው። ዕቃውን ካልገዛ የከፈለው ቀብድ ይቀርበታል። 

ክርስቶስ ከሞት በኋላ ለሚሰጠን ሕይወት ማረጋገጫ ሰጥቶናል። ለዚያ ሕይወት ማሳያ አንዱ ከትንሣው በኋላ ያለው የሃምሳው ቀን ነው። ትንሣኤ የሥጋ ትንሣኤ መያዣ ነው

ትንሣኤ የሁሉም ነገር መሠረት ነው። ያለ ትንሣኤ ክርስትና አይኖርም ነበር። “ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ደግሞ ከንቱ ናት” 1.ቆሮ.15:17

ክርስትናችን የተመሠረተው በክርስቶስ ትንሣኤ ላይ ነው። ወደ ክርስትና የምንገባበት በር ጥምቀት ነው። የምንጠመቀው በሞቱና በትንሣኤ ልንሳተፍ ነው። ወደ ውኃው ስንገባ ሞት ወይም መቀበር ነው። ስንወጣ ትንሣኤ ነው። “እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን። ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን” ሮሜ.6:4

ሞትና ትንሣኤውን እንመሰክራለን የመጠመቂያው ገንዳ (ቦታ) ጎልጎታ ነው። ጌታ ሞቶ ባይነሣ ኖሮ ጥምቀት የለም ነበር። የተጠመቅነው በሞቱና በመነሣቱ ነው። 

የምንቀበለው ሥጋና ደም በሞቱና በትንሣኤው የተመሠረተ ነው። ባይሞትና ባይነሣ ኖሮ ሥጋና ደሙን አይሰጠንም ነበር። ሥጋው መለኮት የተዋሐደው ነፍስ የተለየው ነው። ሥጋውን በመስቀል ላይ የሰጠን ስለ ሞተ ነው። ሞትን ድል አድርጎ የተነሣ ስለሆነ እንቀበለዋለን። ሞቶ ባይነሣ ግን አንቀበለውም ነበርም። 

ሞት ይዞት ያላስቀረው ሕያው ስለሆነ ሞት ሊይዘው ያልቻለ ሕያወ ባሕርይ ስለሆነ ሕይወትን የሰጠን ስለሆነ የእርሱን ሥጋ እንደበላለን ደሙን እንጠጣለን። ሞትን ድልን አድርጎ ስለተነሣ ሕይወት ነው። ሞቶ ቢቀር ኖሮ ሥጋውን ማን ይበላል ቢበላስ ምን ይጠቀማል?። 

ሞትን ድል የሚያደርግ ሕይወት ስለሆነ የሞት መድኃኒት ስለሆነ The medicine of immortal “ኢመዋቲነትን የሚሰጥ ዘር” አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ። 

ክህነት መሠረቱ ትንሣኤ ነው። በይሁዳ ምትክ ሰው ሲመርጡ መለኪያው የትንሣኤ ምስክር መሆንን ነው። “ስለዚህ ከዮሐንስ ጥምቀት ጀምሮ ከእኛ ዘንድ እስካረገበት ቀን ድረስ፥ ጌታ ኢየሱስ በእኛ መካከል በገባበትና በወጣበት ዘመን ሁሉ ከእኛ ጋር አብረው ከነበሩት ሰዎች፥ ከእነዚህ አንዱ ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር ይሆን ዘንድ ይገባል” ሐዋ.1:21 

ክህነት ያስፈለገው ሞትና ትንሣኤውን መመስከር ነው። መምህራን ያስፈለጉትም ለዚሁ ነው። 

ተክሊል መሠረቱ የክርስቶስ  ሞትና ትንሣኤ ላይ ነው። ጋብቻ ሊፈጽሙ የወሰኑ በአንድነት የክርስቶስን መስቀል ለመሸከም በሚወስኑ አንድ ወንድና አንዲት ሴት ጥንዶች በጸሎት ከብረው ሥጋወደሙን ተቀብለው አክሊል ደፍተው ጋብቻ የሚፈጽሙት በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ላይ ነው። የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ በተግባር ለመኖር ነው። 

ክርስቶስ ሞትን ድል እንዳደረገ እናንተም በዚኽ ዓለም ያለ ውጣ ውረድን ክርስቶስ የእሾኽ አክሊል ደፍቶ ድል እንዳደረገ እነርሱም ድል ያደርጉ ዘንድ አክሊል ይደፋሉ። ይኽ አክሊል ክርስቶስ የደፋው የአሸናፊነት  አክሊል ነው። 

የክርስቶስ አክሊለ ሶክ ከብረት የጠነከረ ከጠንካራ የእንጨት እሾኽ የተሠራ ነው። የቤተ ክርስቲያን አክሊል የሚዋጋ ነው። ትዳር የደስታ ሕይወት አይደለም። ለብቻ ሆኖ የሚከብድን መስቀል ሁለት ሆኖ መስቀሉን ተሸክሞ መክበር ሕይወት ነው። የሚደፋው አክሊል የካሜራ ጌጥ አይደለም። አክሊለ ሶክ ነው። 

መ/ር ንዋይ ካሳሁን
“እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለው እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፡፡ እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፡፡ ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ፡፡” ሉቃ 24 ፥51

እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ዕርገት አደረሳችሁ አደረሰን፡፡ እኛንም ኢየሩሳሌም በተባለች ቤተክርስቲያን አኑሮን ከዓለም ወደ እግዚአብሔር ከክፋት ወደ ጽድቅ ከመለያየት ወደ አንድነት ከጥላቻ ወደ ፍቅር ወደ መተሳሰብ ከፍ ከፍ ያርገን፡፡
➠መልካም በዓል!

© ዲን አበበ ግርማ
“ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ፥ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው።” መዝ 133፥1

የጊንር ፅጌ ተዋህዶ  ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ትላንት ሰኔ 9  በአዲሳ አበበ  በአዳማ እና በጊንር ሁላችንም በያለንበት በመገናኘት ጥሩ ጊዜ አሳልፈናል ።

ይህ እንዲሆን የፈቀደ አአባቶቻችን አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን 

👇👇👇👇👇👇
የጊንር ፅጌ ተዋህዶ ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በ አዲስ አበባ