TechIn2
1.22K subscribers
1.47K photos
1 video
120 files
500 links
Technology & Innovation Institute (TechIn2), Ethiopia

የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኢኒስቲትዩት

ጠቃሚና ወቅታዊ የሆኑ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ፈጠራ፣ ጤና እና ሰብአዊ-ኣቅም ግንባታ(Human Development)መረጃዎችንና ምክሮችን በየእለቱ እናደርሶታለን።
Download Telegram
የኤሌክትሪክ መንገድ በቴላቪቭ
*************************
የቴላቪቭ ከተማ በአለም የመጀመሪያ የሚያደርጋትን ለህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚውል የኤልክትሪክ መንገድ በተሳካ ሁኔታ መገንባቷን CNN በቢዝነስ ዘገባው አመልክቷል፡፡ መንገዱ የኤሌክትሪክ መኪናወችን ባትሪ መሙላት እንዲችል ተደርጎ የተሰራ ነው፡፡ ዘገባው እንዳመለከተው Tel Aviv-Yafo እና ElectReon በተባሉ ድርጅቶች የሚመራ ሲሆን የቴላቪቭ ከተማ አስተዳደርና የግሉ ዘርፍ ፋይናንስ አድርገውታል፡፡
ከዚህ በፊት የኤሌክትሪክ መኪኖች ቻርጅ ለማድረግ ወደ ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎች ማምራት ይጠበቅባቸው የነበረ ሲሆን ይህ ፕሮጀክት ግን ይህን ሁሉ አስቀርቷል፡፡
ይህ በፓይለት ወይም በሙከራ ደረጃ ያለው ስራ ከተሳካ አለማችን በከባቢ አየር ብክለት ምክንያት እየገጠማት ያለውን ቀውስ ለመቀነስ ያስችላታል፡፡ በተለይም ወደፊት ሀገራችን ኢትዮጵያ የሐይል ማመንጫ ግንባታዎችን አጠናክራ ከገነባችና እነዚህን መኪኖች የማምረትና የመገጣጠም ስራው እንደ ኒያላ ሞተርስ ባሉ ድርጅቶች ከተከናወነ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን መቅረፍ ትችላለች፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በአለማችን ትልቁ የመኪና አምራች ድርጅት ቴስላ በቅርቡ የኤሌክትሪክ መኪና ባትሪን አሁን ካለበት ዋጋ በጣም ይቀንሳል ያለውን የባትሪ ማሻሻያ ሰርቷል፡፡ ይህም የዚህን የኤሌክትሪክ መኪና ተመራጭነት ከፍተኛ እንዲሆን በማድረግ የካምፓኒውን መኪናዎች ተፈላጊነት በ20% ከፍ ያደርገዋል፡፡ እንደ tuchcrunch ዘገባ ከሆነ ካምፓኒው የባትሪ መሙያውን ዋጋ ወደ $1.20 ዝቅ ያደርገዋል፡፡
የእነዚህ ከላይ የተገለጹት ግኝቶች ጥምረት ሊኖረው የሚችለውን ጥቅም ማሰብ በጣም ቀላል ነው፡፡ ከተማችን አዲስ አበባ ፈጣን የአውቶብስ መንገድ የመስራት እቅድ እንዳላት ይታወቃል፡፡ ታዲያ እንደነዚህ አይነት ግኝቶችን አብሮ ማሰብ ጠቃሚ አይደለም ትላላችሁ፡፡ ሀሳባችሁን አካፍሉን፡፡
ዘገባው የCNN international እና Techcrunch ነው፡፡
170 የሚጠጉት የኮቪድ 19 ክትባቶች በምን ደረጃ ላይ ይገኛሉ?
--------------------------------------------------------------
አሁን ላይ የአለም ጤና ድርጅት ክትትል የሚያደርግባቸው ከ170 በላይ የኮሮናቫይረስ ክትባቶች ውጤታማነታቸውና ደህንነታቸው በተረጋገጠ መልኩ ለማከናወን አራት መሰረታዊ የክሊኒካል የሙከራ ደረጃዎችን የሚያልፉ ሲሆን አራቱም ሂደቶች የየራሳቸው መስፈርቶች እና መገለጫዎች ያሏቸው ናቸው፡፡ በዚህ መሰረት አራቱን መሰረታዊ የሙከራ ደረጃዎች ክትባቶቹ ከሚገኙባቸው ሂደቶች አንፃር ብናስቀምጣቸው የሚከተለውን ይመስላሉ፡፡
ሙሉን ለማንበብ ሊንኩን ይጫኑ http://www.techin.gov.et/post/282/
የማስታወስ ችሎታን የሚያዳብሩ መንገዶች
***********************************
ምንም እንኳን ሰዎች ከዕድሜ ብዛት የተነሳ አንዳንድ ነገሮችን ብንረሳም የማስታወስ አቅማችንን ማሳደግ የምንችልባቸው መንገዶች እንዳሉ መገንዘብ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ እንደ አጠቃላይ የጤና ህግ ለሰውነታችን ተስማሚ የሆነ ነገር ሁሉ ለአእምሯችንና ለማስታወስ ብቃታችን ተስማሚ ነው፡፡ በዚህ ጽሁፍ አምስት የማስታወስ ብቃትን ማሳደግ የሚያስችሉ መንገዶችን ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡

1ኛ. ተስማሚ ምግቦችን መመገብ
በቫይታሚን ቢ፣ በኦሜጋ 3 እንዲሁም በፋቲ አሲድ የበለጸጉ ምግቦች አእምሯችን ጤናማ እንዲሆን በመርዳት ረጅም ትውስታ እንዲኖረን ያደርጋሉ፡፡ ለአእምሯችን ተስማሚ ከሆኑ ምግቦች እንደ ፍራፍሬ፣ አሳ፣ ቅጠላ ቅጠል የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
2ኛ. የልብን ጤንነት መጠበቅ
ብዙዎቹ የአእምሮ ሀኪሞች ለልብ ጥሩ የሆነ ለአእምሮም ጥሩ ነው በሚል አባባላቸው ይታወቃሉ፡፡ በአብዛኛው የልብ ችግር የሚያጋጥማቸው ሰዎች የማስታወስ ችግርም ተጠቂዎች ይሆናሉ፡፡ ስለዚህ የደም ግፊትን መቆጣጠር፣ በሰውነታችን ያለውን የስብ መጠን መቆጣጠር፣ የስኳር መጠናችንን መቆጣጠር፣ አልኮል መቀነስና ሲጋራን መተው ልባችንን የምንንከባከብባቸው መንገዶች ናቸው፡፡
3ኛ. የጸሐይ ብርሐን በበቂ ሁኔታ ማግኘት
ሰዎች የሚያገኙትን የጸሐይ ብርሐን መጠን ባሻሻሉ ቁጥር የማስታወስና የማሰብ ችሎታቸውን ማዳበር ይችላሉ፡፡ በተለይ የብርሐን መጠን በሚያንስበት በክረምት ወቅት የመጨነቅ ባህሪ ለሚያሳዩ ሰዎች ሁነኛ መፍትሔ ነው፡፡
4ኛ. ጥሩ እንቅልፍ መተኛትና በጥዋት መንቃት
ጥናቶች እንደሚያሳዩት አርፍደው የሚነሱ ሰዎች በጥዋት ከሚነሱ ሰዎች ያነሰ የማስታወስ ችሎታ አላቸው፡፡ በንጽጽር ጥሩ እንቅልፍ ማግኘት በጥዋት ከመነሳት የተሻለ ጠቀሜታ አለው፡፡ በተቻለ መጠን በሳምንቱ ቀናት ውስጥ የምንተኛባቸውና የምንነቃባቸው ሰዓቶች ተመሳሳይ ቢሆኑ ይመረጣል፡፡
5ኛ. የማስታዎስ ችሎታ ልምምዶችን ማድረግ
የማስታዎስ ችሎታችሁ ከሚጠበቀው በታች ከሆነ በባለሙዎች የሚዘወተሩ እንደ በምስል መከሰት (Visualization) እና ማመሳሰል ወይም ማዛመድ (association) የመሰሉ ተግባራትን መከወን ስሞችንና ዝርዝር ነገሮችን ለማስታወስ በጣም ጠቃሚዎች ናቸው፡፡
ምንጭ፡ howstuffworks
የሰው-ሰራሽ አስተውሎት ተአማኒነት እስከ ምን?
==========================
የሰው ሰራሽ አስተውሎት ትልቁ ሀሳብ ማሽኖችን እራስ ገዝ ማድረግ ነው፡፡ በዚህ ሰዓት እራሳቸውን በራሳቸው የሚያሽከረክሩ መኪኖች፣ ውሳኔ የሚወስኑ ሮቦቶችን እና ሌሎችንም እንደዛ የሆኑ ማሽኖች እየተመረቱ እና እየተሰሩ ነው፡፡ይሁንና እነዚህን ማሽኖች ምን ያህል ማመን ይቻላል የሚለው ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ ነው፡፡

የሰው ልጆች አዕምሮ እንዳላቸው ሁሉ ኒውራል ኔትዎርክ የሰውሰራሽ አስተውሎቶች አዕምሮ ነው፡፡ ይህ መረብ አዕምሮ ለሰው ልጆች የሚሰራውን ሁሉ ለማሽኖች እንዲሰራ የታሰበ ሲሆን በዋናነት ትንበያን ማመንጨት ላይ ትኩረት ያደርጋል፡፡ ይሁንና ይህ ምንጭ ተአማኒነቱ ምን ያህል ነው የሚለው ነገር አሳሳቢ ነው፡፡
ለምሳሌ ያህል ብናይ የእራስ ገዝ መኪናዎች ፈተና በመንገድ ላይ የሚገጥሟቸውን ነገራት ምንነት ጠንቅቆ ማወቅ አለማወቅ ላይ ነው፤ ማለትም መንገድ እያቋረጠ ያለው ነገር እንስሳ ነው ወይስ ህጻን ልጅ ፣ ይህ አካል ፈጣን እርምጃ ነው ያለው ወይስ ቀርፋፋ ፣ ሌላ መኪና በተሳሳተ አቅጣጫ ቢመጣበትስ ወደየትኛው ለመንዳት ይወስናል እና የትኛው ያነሰ ጉዳት ያመጣል የሚሉትን በሰው ልጆች አዕምሮ ውስጥ የሚወሰኑ ውስበስብ ውሳኔዎችን ለመወሰን ለማሽኖች ቀላል አይሆንም፡፡

ለመኪናው መረጃ አቀባይ ምንጮች ብዙ ናቸው፡፡ የፊት ለፊት ካሜራ፣ የኮምፒውተር እይታ እና ሌሎችም ይህ መኪናው የትኛውን ሴንሰር ማመን እና መቀበል እንዳለበት ግራ እንያጋባው ያደርጋል፡፡ በተለይም የመረጃ መጣረሶች በሚከሰቱበት ሰዓት መኪናው የሚወስነውን ነገር ጠንቆ ማወቅ ይቸገራል፡፡
ይህንን ጉዳይ በተመለከተ እስከዛሬ ድረስ የሰው ሰራሽ አስተውሎቶችን ተአማኒነት የሚለካ ምንም ዓይነት አሰራር እና መሳሪያ የለም የሚሉት የካሊፎርኒያ ዩኒቨርስቲ ተመራማረዎች ምንም እንኳን ስህተት የማሽኖች ብቻ ሳይሆን የሰው ልጆችም መገለጫ ነው ያሉ ሲሆን የሰው ልጆችም የመወሰን ችግር፣ የመዘግየት በሃሪ እና ሌሎችንም የትንበያ እክሎች እንደሚያተናግዱ እናውቃለን ብለዋል፡፡
ይሁንና አሁንም ቢሆን ኒውራል መረብ ላይ እጅግ መልፋት እና የትክክለኝነቱን መጠን ማሰፋት ላይ በትጋት ሊሰራ ይገባል ያሉ ሲሆን በፈረንጆቹ አቆጣጠር በኦገስት31 /2020 ማሽኖች በማያውቁበት እና ግራ በሚጋቡበት ጊዜ አናውቅም ማለት የሚችሉበትን አዲስ አሰራር የፈጠሩ ሲሆን ይህ ሁኔታ በተሳሳቱ ውሳዎች የሚከሰቱ ውድመቶችን ለመከላከል ዓይነተኛ አማራጭ ነው ብለዋል፡፡
ምንጭ፡- ScienceDaily
አነፍናፊ ውሾች የኮሮና ቫይረስን ለመለየት
**********************************
አለማችን በኮሮና ቫይረስ መጠቃት ከጀመረች ወዲህ የቫረሱን ስርጭት ለመግታትም ሆነ ክትባቱን ለማግኘት ብዙ ሙከራዎችን እያደረገች ትገኛለች፡፡ ቢቢሲ ሮይተርስን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ በፊንላንዷ ሔልሲንኪ- ቫንታ አየር መንገድ አነፍናፊ ውሾች የኮሮና ቫይረስ ያለባቸውን መንገደኞች ለመለየት ተሰማርተዋል፡፡ ለወትሮው እንዲህ አይነት ውሾች ህገ-ወጥ ዝውውሮችን ለመከታተል በየአየር መንገዱ መመልከት አዲስ አልነበረም፡፡ ዛሬ ግን በሔልሲንኪ- ቫንታ አየር መንገድ አነፍናፊ ውሾችን ከተመለከታችሁ ከወትሮው ግብራቸው በተለየ መልኩ የኮሮና ቫይረስ ተጠቂዎችን ለመለየት የተሰማሩ ናችው፡፡

የዚህ ጥናት አስተባባሪ የሆኑት የሔልሲንኪ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር አና ሔሊምጆርክማን ለሮይተርስ የዜና ማሰራጫ እንደተናገሩት ከሆነ አነፍናፊ ውሾቹ ተጓዦች የቫይረሱን ምልክት ከማሳየታቸው አምስት ቀን በፊት ቫይረሱ እንዳለባቸውና እንደሌለባቸው መለየት ይችላሉ፡፡ ፕሮፌሰሯ አክለውም ውሾቹ ወደ 100% የተቃረበ ውጤታማነት አሳይተዋል ብለዋል፡፡

ተጓዦች በተዘጋጀላቸው የናሙና መውሰጃ ጨርቅ አማካኝነት አንገታቸውን ጠርገው ወደ ውሾቹ ፊት ያቀርቡታል፡፡ ከዚያም ውሾቹ ያሸቱትና በcanine test አማካኝነት ውጤቱ በደቂቃዎች ውስጥ ይደርሳል፡፡ ዘገባው አክሎም ጥናቱ ከፍተኛ ተስፋ የሰጠ ቢሆንም አሁንም ተጨማሪ ጥናቶች መሰራት ተገቢ መሆኑን ገልጧል፡፡
ምንጭ BBC news
ወደምድር በጣም ቀርቦ የነበረው 2020 SW አስትሮይድ
===============================
ይህ የአስትሮይድ ቅርበት ጨረቃ ከእኛ ከምትርቅበት የ384,000 ኪ.ሜ ርቀት በእጅጉ ከማነሱም በላይ የቲቪ እና የአየር ሁኔታ መከታተያ ሳተላይቶች ከሚሽከረከሩበት (35,888 ኪ.ሜ ርቀት ካለው) ምህዋርም በእጅጉ ቀርቦ መገኘቱ መጠነኛ ስጋት ፈጥሮ እንደነበር ተመራማሪዎች አስረድተዋል፡፡ አስትሮይዱ ትክከለኛ መጠኑ አስካሁን በውል ባይታወቅም በተቀራራቢነት ግን ከ14 እስከ 32 የጫማ ስፋት ሊኖረው እንደሚችል የCNEOS ተማራመሪዎች ይናገራሉ፡፡
ሙሉን ለማንበብ ሊንኩን ይጫኑ
http://www.techin.gov.et/post/293/
ጉንፋን ወይስ ኮቪድ-19? የምልክት ልዩነቶቹ
==============
በአሁኑ ሰዓት ምድራችንን አስጨንቆ የያዘው የኮቪድ-19 በሽታ ለብዙዎች ህይወት ማለፍ ምክንያት መሆን ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ታድያ ይህ ወረርሺኝ ያሳያቸዋል የሚባሉትን ምልክቶች የጤና ባለሙያዎች በተደጋጋሚ ሲያሳዩን ቆይተዋል፡፡ ሆኖም ወረርሺኙ ብዙውን ጊዜ ከሚከሰትብን ጉንፋን ጋራ ተቀራራቢ ሊባል የሚችል የህመም ምልክት በማሳየቱ ሳብያ የምልክቶቹ መታየት ብዙ ጭንቀትን ሲያስከትልብን ይታያል፡፡ ስለዚህም በሁለቱ መካከል ያሉ የምልክት ልዩነት እና መመሳሰሎችን በተከታዩ ምስል አማካኝነት ልናሳያችሁ ወደድን፡፡
ሳምንታዊውን የቴክ ሳይንስ የቴሌቭዥን ፕሮግራም ምዕራፍ ፪ ክፍል ፩ ሙሉ ዝግጅቱን በዩትዩብ ቻናላችን አማካኝነት ይከታተሉ፡፡>>>>https://www.youtube.com/watch?v=q1LPaFM0rFY
ዘውትር ቅዳሜ በ10 ሰዓት በድጋሚ ደግሞ ማክሰኞ በ10 ሰዓት በ MOE TV ይከታተሉን
(Nilesat 12520/v/27500)
(በተጨማሪም Ethiosat ላይ እንገኛለን)
የዘመናዊ ኮምፒውተር አፈጣጠርና እድገት አጭር ታሪክ
ከ60 ዓመታት በፊት ከነበረው አንድ ቤት ከሚያክል ግዙፍና ቀርፋፋ ነገር ግን በሚሊዮን ዶላር ከሚያስወጣ የመጀመሪያው ‘ENIAC’የተሰኘ ኮምፒውተር ተነስተን ከመቶወች ዶላር ባልበለጠ ዋጋ ተገዝቶ መዳፍ ላይ ሊቀመጥ የሚችል አነስተኛ መጠንና ፈጣን ብቃት ወዳለው የኮምፒውተር ዘመን ደርሰናል፡፡ ኮምፒውተሮች ዛሬ ላሉበት የተራቀቀ እድገት ለመድረስ ብዙ ሂደቶችን አልፈዋል፡፡ ይህ ጽሁፍ የዘመናዊ ኮምፒውተር አፈጣጠርንና እድገት አጭር ታሪክ ለማስታወስ ታስቦ ከሰሎሞን ሙሉጌታ ካሳ ግርምተ ሳይ-ቴክ መጽሀፍ ላይ ተቀንጭቦ የተወሰደ ነው፡፡

1950ዎቹ፡-

Ø በ “ቫኪዩም ቲዩብ“ ብቻ ይሰሩ የነበሩ ኮምፒውተሮች መጠናቸው የአንድ ቤት መጠን እስኪክል ድረስ እጅግ ግዙፍ የነበሩ ሲሆን በአንጻሩ ደግሞ እጅግ ቀርፋፋ ነበሩ በወቅቱ እነዚህን ኮምፒውተሮች በብቸኝነት ይጠቀምባቸው የነበረው የአሜሪካ ሚሊቴሪ ተቋም ሲሆን ዋጋቸውም ከፍተና ነበር፡፡

1960ዎቹ፡-

Ø ከትራነዚሰተሮች መፈጠር የተነሳ ቀርፋፋውን የ “ቫኪዩም ቲዩብ“ አሰራርን በመቀየር የኮምፒውተሮቹን የአካል መጠን መቀነስ ሲቻል ብቃታቸውንም ማሻሻል ተቻለ፡፡ በዚህ ወቅት ነበር ሜይንፍሬም (mainframe) የተባሉ ፈጣን ውድ ኮምፒውተሮች ተፈጥረው ከሚሊቴሪናየመንግስት ተቋም አልፎ ለግል ድርጅቶች ጥቅም ላይ መዋል የጀመሩት፡፡

1970ዎቹ፡-

Ø በመቶዎች የሚቆጠሩ ትራንዚሰተሮችን ያካተተ ኢንተግሬትድ ሰርኪዩት (integrated circuit) አንድ ክፍል ሊሞላ የሚችል መጠን ያለውን የሜይ ፍሬም ኮመፒውተር አሳንሶ በጠረዛ ላይ የሚቀመጥ ኮምፒውተር (desktop) እንዲፈጠር አስቻለ::

1980ዎቹ፡-

Ø በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተራንዚስተሮች እጅግ በታም ትንሽ በጠን ባለው የኮምፒውተር ቺፕ ውስጥ ህያው መሆን የኮምፒውተር መጠን በታም አንሶ በአንዲት ቦርሳ ውስጥ የሚገባና ከድርጅት አልፎ ለግል ጥቀም መዋል የሚችልበት “personal computer” (PC) ዘመን ተወለደ፡፡ ኮምፒውተሮች ጠረጴዛ ላይ ከመቀመጥ አልፈው ጭን ላይ የሚቀመጡበትን መጠን ይዘው “laptop” በሚል ስያሜ ብቅ አሉ፡፡





1990ዎቹ፡-

Ø የኢንተርኔት መወለድ ኮምፒውተሮች እርስበርሳቸውና በሌላ ቦታ ከሚገኝ ከፍተኛ አቅምና መረጃ ብዛት ለው የኮምፒውተር ስብስብ ‘datacenter’ ጋር ተገናኝተው ከዚህ ቀደም በራሳቸው አቅም ብቻ ከሚሰጡት አገልግሎት እጅግ የላቀ ጥቅምን በፍጥነት መስጠት እንዲችሉ አደረገ፡፡

2000ዎቹ፡-

Ø በእጃችን መዳፍ እንኳን የማይሞሉ ነገር ግን በብቃታቸው ከአንድ መጠኑ ከፍ ካለና ምርጥ ከሚባል ኮምፒውተር ያልተናነሰ ተግባር ማከናወን የሚችሉ እንደ ረቀቀ ስልክ (smart phone) ያሉ ተንቀሳቃሽ ቁሶች በስራ ላይ ዋሉ፡፡ ከስልኮችም አልፎ ታብሌቶቻችን፣ ሰዓቶቻችን፣ የቤት ቁሶቻችን፣ መኪናወቻችንና ልብሶቻችን ሳይቀር የኮምፒውቲንግ ብቃት እተካተተባቸው ይገኛል፡፡

Ø ከዚህም በተጨማሪ ይህ ዘመን አብሮን ባለ በአንድ ኮምፒውተር ብቻ ከመደገፍ ይልቅ እንደ ክላውድ ኮምፒውቲንግ (cloud computing) እና የመሳሰሉ የተራራቁ በኢንተርኔት ተገናንተው መስራት የሚችሉና ከእና ርቀው በተለያየ የኣለም ክፍሎች ተበታትነው በሚገኙ እጅግ ፈታን ኮምፒውተሮች አማካኝነት እጅግ በርካታ ተግባር ማከናወን ተቻለ፡፡

(ሰለሞን ሙሉጌታ ካሳ፣ ግርምተ ሳይ-ቴክ፣ገጽ299-301)
ስልጠና፤ለዲዛይነሮች
============
ውድ ተከታታዮቻችን “BASIC PRODUCT SKETCHING TECHNIQUE” በሚል ርዕስ በበይነ መረብ ሲሰጥ የቆየውን ስልጠና ዳግም በአዲስ መልክ በኢንስቲትዩቱ ዩቲዩብ ቻናል ላይ ( https://www.youtube.com/channel/UC6jvUOLRSkVEQtc5Annfwvg ) እንድትከታተሉ ባሳለፍነው ሳምንት መጋበዛችን ይታወሳል፡፡
በመሆኑም ስልጠናውን ከሰኞ ጀምሮ በዩትዩብ ቻናላችን መከታተል የምትችሉ ሲሆን ስልጠናውን አስመልክቶ የሚቀርቡላችሁን የመለማመጃ ጥያቄዎች ሞልታችሁ በኢሜይል አድራሻችን (stic.ethiopia@gmail.com) የምታደርሱን ይሆናል፡፡
ማሳሰቢያ፡ ስልጠናውን ለመከታተል ምንም አይነት ምዝገባ የማያስፈልገው መሆኑን መግለፅ እንወዳለን፡፡
ቀለም እና ብሔራዊ ማንነት
==============
ቀለሞችን አይተን በውስጣችን የሚከሰቱት የደስታ፣ ሀዘን፣ ፍቅር፣ ኩራት እና ሌሎች ስሜቶች በሀገራዊ ማንነታችን ላይ የተመሰረቱ እንደሆነ የሚያሳይ ጥናት በቅርብ ይፋ ሆኖ ነበር፡፡ በዚህም አጥኚዎች አንድ ሰው ከየትኞቹ ቀለሞች ጋራ የስሜት ትስስር እንዳለው በመመልከት ብቻ ሰውየው የየት ሀገር ሰው እንደሆነ መገመት ችለዋል፤ ከግምቶቻቸው ውስጥም 80 በመቶ ያህሉ ትክክል ሆነው ተገኝተዋል፡፡
ተመራማሪዎቹ ከቻይና፣ ጀርመን፣ ግሪክ እና ብሪታንያ የተውጣጡ 711 ሰወዎችን በናሙናነት አካተው ነበር ጥናታቸውን ያከናወኑት፡፡ በጥናቱ ላይ በጎ ፍቃደኝነታቸውን አሳይተው የተገኙት የጥናቱ ተሳታፊዎች እንደ አረንጓዴ፣ ሰማያዊ-አረንጓዴ የመሳሰሉ የቀለማት ስያሜዎችን እንዲያነቡ ተደርገዋል፡፡ በዚህም አማካኝነት ከተቀመጡት 20 የስሜት አይነቶች ውስጥ አዕምሮአቸው ለየትኛው ቀለም ምን አይነት ስሜት እንደሚያሳይ እና ቀለሞቹ ከስሜቶቹ ጋራ ያላቸው የስሜት ትስስር ጥንካሬ ተለክቶበታል፡፡
ከተሳታፊዎቹ መካከል የብዙዎቹን ስሜት በመቀስቀስ ረገድ ቀይ፣ ጥቁር እና ሮዝ ቀለሞች ቀዳሚዎች ነበሩ፡፡ በተቃራኒው ቡናማ እና ሀምራዊ አነስተኛ የስሜት መነሳሳትን ሲከስቱ ታይተዋል፡፡ በሌላ መልኩ ጥቁር ቀለም ከሁሉም ሀገራት በመጡት ተሳታፊዎች ዘንድ የሀዘን ስሜትን ገላጭ ሆኖ ሲገኝ ቀይ በበኩሉ እንደ ፍቅር እና ደስታ ያሉ አውንታዊ ስሜቶችን ንዴት እና ጥላቻን ከመሳሰሉት አሉታዊ ስሜቶች አጣምሮ መያዙን በሮያል ሶሳይቲ ኦፕን ሳይንስ ጆርናል ላይ ታትሞ የወጣው ይህ ጥናት አመላክቷል፡፡
ሆኖም እንደየ ዜግነታቸው የተወሰኑ ልዩነቶች ተስተውለዋል፡፡ ለምሳሉ ከጀርመን የመጡት ተሳታፊዎች ከየትኛውም ሀገር በላቀ ቡናማ ቀለም ከአስጸያፊነት ጋራ ሲያስተሳስሩት፤ ከግሪክ የመጡቱ በበኩላቸው ሀምራዊን በዋናነት ከሀዘን ጋራ በማስተሳሰር ብቸኞቹ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ በከቻይና የመጡት ተሳታፊዎች ደግሞ ነጭ ቀለም በበለጠ አሉታዊ ስሜትን ሲጭርባቸው (በቻይናዊያን ባህል ቀብር ላይ ነጭ መለበሱን ልብ ይሏል)፤ ቢጫ ቀለም ደግሞ ከግሪኮች በተቀረ በሁሉም ሀገራት ላይ አውንታዊ ስሜትን አጭሯል፡፡
የተሰበሰበን ጥሬ ሀቅ (Data) ወስዶ አንድ ፕሮግራም የሰው ልጆች ወዲያው ሊያስተውሏቸው የማይችሉ ግምት እና ትስስሮችን እንዲያሳይ አድርጎ የሚያሰለጥነውን ማሽን ለርኒንግ የተባለ የሰው ሰራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) አይነት በመጠቀም ነው ተመራማሪዎቹ የትኛው የጥናቱ ተሳታፊ ከየት ሀገር እንደሆነ ለመለየት የቻሉት፡፡ እንደ ቡድኑ ከሆነ ጥናቱ መሰል ቴክኖሎጂ ለወትሮው ጥሬ ሀቆች ውስብስብ፣ ብዙም ግልፅ ያልሆኑና ለመለየት የሚዳግቱ የሚሆኑበትን የስሜት ጥናት (Emotion Research) ዘርፍን ለመረዳት እንደሚያስችል ጥቁምታን የሰጠ ነው፡፡
ምንጭ፡ Science
ኮቪድ-19ኝን ተከትሎ የበዛው ፅንስ ውስጥ ሞተው የሚወለዱ ህፃናት ምጣኔ
==============
የተለያዩ ጥናቶች እያመላከቱ እንዳሉት በዓለም ዙርያ በማህፀን ውስጥ ሞተው የሚወለዱ ህፃናት ምጣኔ በአሳሳቢ ፍጥነት እያደገ ነው፡፡ እንደ አጥኚዎች ከሆነ በአንዳንድ ሀገራት ነፍሰ ጡር ሴቶች ኮቪድ 19ኝን ተከትለው በመጡ ገደቦች ምክንያት ለወትሮው ሊያገኙት ይገባ የነበረው የጤና ባለሙያ ክትትል ተነፍጓቸዋል፡፡ በዚህ መንስኤነትም ህፃናት ሞተው እንዲወለዱ የሚያደርጉ የጤና እክሎች ተገቢውን ክትትል አላገኙም፡፡ በደቡብ አውስትራሊያ ዩኒቨርሲቲ በስነ ወሊድ ስፔሻሊስት እንደሆኑት ጄን ዋርላንድ አነጋገር “ነፍሰ ጡር ሴቶችን ከኮቪድ 19 ለመከላከል በምናደርገው ጥረት ባልታሰበ ሁኔታ በማህፀን ሞተው የሚወለዱ ህጻናትን ቁጥር አሳድገናል”፡፡
በጉዳዩ ላይ ከተሰሩት ጥናቶች በስፋት የሚልቀውና በኔፓል ውስጥ በሚገኙ ዘጠኝ ሆስፒታሎች ልጅ የወለዱ 20 ሺህ ሴቶችን አካሎ የወጣው ጥናት ከሁለት ሳምንት በፊት በላንሴት ግሎባል ኸልዝ ላይ ታትሞ ወጥቶ ነበር፡፡ ጥናቱ ይፋ ባደረገው ውጤት መሰረት በማህጸን ሞተው የሚወለዱ ህጻናት ቀድሞ ከነበረበት ከ1000 ውልጃዎች 14ቱ በማህጸን ሞቶ መወለድ ምጣኔ የወረርሺኙን ስርጭት ለመገደብ የተጫኑ የእንቅስቃሴ እገዳዎችን ተከትሎ ቁጥሩ በግማሽ በመጨመር ከሚወለዱ 1000 ህፃናት ውስጥ 21ዱ በማህጸን ሞተው እንደሚወለዱ ለማረጋገጥ ችሏል፡፡ ከዚህ የህፃናት በማህፀን ውስጥ ሞቶ የመገኘት ምጣኔ ዕድገት በስፋት የተስተዋለው የእንቅስቃሴ ዕገዳው በተጣለባቸው የመጀመሪያዎቹ አራት ሳምንታት ውስጥ ነበረ፡፡ በዚህ ወቅት ሰዎች ምግብ ለመግዛት ካልሆነና ጥብቅ የጤና ጉዳይ ካላጋጠማቸው በቀር ከቤት ለመውጣት አይፈቀድላቸውም ነበር፡፡
በስዊድን ባለሙያዎች የሚመራው ጥናት እንዳመለከተው ምንም እንኳን በማህጸን ውስጥ ሞተው የሚወለዱ ህፃናት ምጣኔ በከፍተኛ ሁኔታ ቢያሻቅብም አጠቃላይ ቁጥሩ ላይ ግን ለውጦች አልታዩም፡፡ ይህ ግን በተለይ በሆስታል የሚከናወኑ ውልጃዎች ቀድሞ በሳምንት ከነበሩበት የአማካኝ 1261 ውልጃ በግማሽ በማሽቆልቆል ወደ 651 ዝቅ ከማለቱ ጋራ የተያያዘ ነው፡፡ በወቅቱ ሆስፒታል ውስጥ ሲደረጉ ከነበሩት ውልጃዎች መካከልም ሰፊውን እጅ የያዙት ውስብስብ የሆኑ ውልጃዎች ነበሩ፡፡ በዚህም ምክንያት ከሆስፒታል ውጭ የወለዱ እናቶችም ሆነ ልጆቻቸው ምን እንዳጋጠማቸው መረዳት ባለመቻላቸው ሳብያ ከአጠቃላዩ የነፍሰጡሮች ቁጥር ውስጥ ምን በማህፀን ውስጥ የሞቱ ህፃናትን እንደወለዱም ሆነ አጠቃላይ ምጣኔው ስለመጨመሩ በእርግጠኝነት እንዳይናገሩ አድርጓቸዋል፡፡
በሆስፒታል ውስጥ ከተደረጉ ውልጃዎች መካከል በማህፀን ውስጥ የሞቱ ህፃናት ውልጃዎች የተከሰቱት ወረርሺኙ እናቶች ላይ በቀጥታ ባመጣባቸው የጤና ጉዳቶች ሳይሆን የጤና ስርአቱን ከማቃወሱ ጋራ በተገናኘ ሊሆን መቻሉን ባለሙያዎቹ ያስረዳሉ፡፡ ምናልባትም የመጓጓዣ ስርኣቱ መስተጓሉን ተከትሎ ነፍሰ ጡር እናቶች የፅንሱን ሁኔታ ለመከታተል ወደ ሆስፒታል መሄድ አለመቻላቸውን አልያም ቀጠሮአቸው መሰረዙን፤ ሌሎች ደግሞ ወረርሺኙን ሽሽት ወደ ሆስፒታሎች ከማቅናት መቆጠባቸውንና ክትትል ካደረጉምነ በይነ መረብ እና የስልክ ግንኙነትን በመጠቀም ብቻ መሆኑን ግምታቸውን ያስቀምጣሉ፡፡
ከኔፓል ባለፈ ሌሎች የአለም ሀገራትም ተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ እራሳቸውን አግኝተዋል፡፡ በሀገረ እንግሊዝ ለንደን ወስጥ ባለው የቅዱስ ጊዮርጊስ ሆስፒታል የተደረገ ሌላ ጥናት እንዳመላከተው በሆስፒታሉ በሚደረጉ ውልጃዎች ላይ በወርሀ ጥር የነበረው ከ1000 ውልጃዎች 2.38ቱ ሞቶ የመወለድ ምጣኔ ከየካቲት እስከ ሰኔ ባሉት ወራት ውስጥ ወደ 9.31 ማደጉን አመላክቷል፡፡ ይህም እንደ ባለሙያዎቹ ከሆነ እናቶች በወረርሺኙ አመጣሽ ምክንያቶች አማካኝነት ወደ በሆስፒታል መጥተው የህክምና ክትትል ባለማድረጋቸው ወይም የጤና እክሎች ሲባባሱ ብቻ ወደ ሆስፒታል በማቅናታቸው መነሻነት ይሆናል፡፡ በተመሳሳይ በህንድ እና ስኮትላንድም ይህ ሁኔታ ታይቷል፡፡
የአለም ጤና ድርጅት እናት እና ልጁን ከጉዳት ይጠብቅ ዘንድ ነፍሰ ጡር ሴቶች በእርግዝና ወራቶቻቸው ውስጥ ቢያንስ ለስምንት ጊዜ ክትትል እንዲያደርጉ ይመክራል፡፡ አብዛኛዎቹ በፅንስ ውስጥ ሞተው የመወለድ ችግሮችንም በእርግዝና ወቅት በጎን በመተኛት፣ ማጨስ በማቆም እንዲሁም ለጤና ባለሙያዎች ፅንሱ እንቅስቃሴውን እንደቀነሰ በማሳወቅ መከላከል ይቻላል፡፡ በተለይ በመጨረሻዎቹ ሶስት ወራት ውስጥ በአግባቡ ክትትል ማድረግ እጅግ ጠቃሚ ሲሆን በሌሎቹ ወራት ቢሆንም ግን ሰፍሰ ጡር እናቶቹ እንደ ደም ግፊት እና የልጁን ዕድገት በጤና ባለሙያዎች ይመረመራሉ፡፡
ምንጭ፡ Nature